Administrator

Administrator

የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ምክትል ሊቀመንበር አቶ መልካሙ ሹምዬ፣ ከድርጅቱ የምክትል ሊቀመንበርነትና ከስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባልነት ሰሞኑን በገዛ ፈቃዳቸው መልቀቃቸው ታውቋል፡፡
በሳለፈው ረቡዕ ነሐሴ 3 ቀን 2015 ዓ.ም ለፓርቲው ማዕከላዊ ኮሚቴ በተፃፈ ደብዳቤ፣ ከድርጅቱ ምክትል ሊቀመንበርነትና ከስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባልነት በፈቃዳቸው መልቀቃቸውን ያሳወቁት የፓርቲው ም/ሊቀመንበር አቶ መልካሙ ሹምዬ ሃላፊነታቸው ለመልቀቃቸው ምክንያት የሆነው ጉዳይ ከአብላጫ የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ጋር ያላቸው የአቋም ልዩነት እየሰፋ በመሄዱ መሆኑን አመልክተዋል፡፡
“በክልሉ ካለው ተጨባጭ ሁኔታ አንፃር የድርጅቱ ምክትል ሊቀመንበርና የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባል ሆኖ መቀጠሉ የድርጅቱንና የህዝቡን ጥቅም የሚያስከብር ሆኖ ባለማግኘቴ ሃላፊነቴን ለመልቀቅ ወስኛለሁ” ያሉት ም/ሊቀመንበሩ በፓርቲው ማእከላዊ ኮሚቴ አባልነታቸው ግን እንደሚቀጥሉ ጠቁመዋል፡፡
በሌላ በኩል በጠ/ሚኒስትር ዐቢይ ላይና በገዢው መንግስት ላይ የሰላ ትችት በመሰንዘር የሚታወቁት  የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት አባልና የአብን ፓርቲ አባል የሆኑት አቶ ክርስቲያን ታደለ ባለፈው ሳምንት መጨረሻ ላይ የፀጥታ ሃይሎች ከቤታቸው ወስደው እንዳሰሯቸው ይታወሳል፡፡

የተመድ የሰብአዊ መብት ኮሚሽንም፣ በአማራ ክልል እየተባባሰ የመጣው ግጭት በጽኑ አሳስቦናል ብሏል
- የአውሮፓ ህብረት ልዑክ 19 አገራት ኤምባሲዎችም በጋራ መግለጫቸው በአማራ ክልል በተቀሰቀሰው ሁከት የዜጎች ሞትና አለመረጋጋት እንዳሳሰባቸው ገልጸዋል


በኢትዮጵያ በተለይም በአማራና በኦሮሚያ ክልሎች ውስጥ የተከሰቱት ግጭቶች እንዳሳሰባቸው እንግሊዝና አሜሪካን ጨምሮ 5 አገራት በጋራ ባወጡት መግለጫ አስታወቁ። አገራቱ በዚሁ መግለጫቸው፤ አለም አቀፉ ማህበረሰብ ኢትዮጵያውያን ሁሉ ዘላቂ ሰላም የሚደረገውን ጥረት መደገፉን እንደሚቀጥልም አስታውቀዋል።
አሜሪካ፣ ዩናይትድኪንግደም፣ አውስትራሊያ፣ ጃፓንና ኒውዚላንድ ትናንት በጋራ ባወጡት መግለጫቸው፤ በአማራና በኦሮሚያ ክልሎች የተቀሰቀሰው ግጭት ለሰላማዊ ሰዎች ሞትና ለአካባቢው አለመረጋጋት ምክንያት ሆኗል ብለዋል።
የኢትዮጵያውያንን ዘላቂ የተረጋ አገር የመፍጠር ግብን እንደሚደግፉ የገለጹት አምስቱ አገራት፤ ሁሉም ወገኖች ንፁሃን ዜጎችን እንዲጠብቁና ሰብአዊ መብትን እንዲያከብሩ ጠይቀዋል። አገራቱ ሁሉም ወገኖች ግጭቶችን  በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት በጋራ እንዲሰሩ ጥሪ ባቀረቡበት በዚሁ የጋራ መግለጫቸው፤ እንዳመለከቱት አለም አቀፉ ማህበረሰብ ለኢትዮጵያውያን ዘላቂ ሰላም እንዲሰፍን የሚደረገውን ጥረት መደገፉን እንደሚቀጥል ጠቁመዋል።
መቀመጫቸውን በአዲስ አበባ ከተማ ያደረጉ የአስራ ዘጠኝ አገራት ኤምባሲዎችና በኢትዮጵያ የአውሮፓ ህብረት ልዑክ በበኩላቸው፤ ሁሉም ተፋላሚ ወገኖች ንፁሃን ዜጎችን ከጥቃትና ከጉት እንዲጠብቁ አሳስበዋል።
በአማራ ክልል የተቀሰቀሰው ሁከትና የንፁሃን ዜጎች ሞት እጅጉን አሳስቦኛል ያለው በኢትዮጵያ የህብረቱ ልዑክና መቀመጫቸውን በአዲስ አበባ ያደረጉ የአስራ ዘጠኝ አገራት ኤምባሲዎች የጋራ መግለጫ፤ የውጪ አገር ዜጎች ከግጭቱ አካባቢ ለቀው እንዲወጡና ደህንነቱ ወደተጠበቀበት ስፍራ እንዲሄዱ እንዲፈቀድም ጠይቀዋል።
ከአውሮፓ ህብረት ልዑክ ጋር በጋራ መግለጫቸውን ያወጡት የፈረንሳይ፣ የጀርመን፣ ሲውድን፣ አውስትሪያ፣ ቤልጂየም፣ ፊንላንድ፣ ዴንማርክ፣ ቼክ ሪፐብክ፣ ጣሊያን፣ አየርላንድ፣ ስፔን፣ ሮማኒያ፣ ፖላንድ፣ ስሎቬኒያ፣ ማልታ፣ ኔዘርላንድስ፣ ሉክሰምበርግና ሃጋሪ ኤምባሲዎች ናቸው።
በተያያዘ ዜና የተባበሩት መንግስታት ድርጅት አለም አቀፉ የሰብአዊ መብት ኮሚሽን ከትናንት በስቲያ ባወጣው መግለጫ በአማራ ክልል እየተባባሰ የመጣው ሁኔታ ግጭት በእጅጉ  አሳስቦኛል ብሏል።

 
በአስቸኳይ ጊዜ ዐዋጁ መሰረት 23 ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ሥር ውለው ምርመራ እየተጣራባቸው እንደሚገኝ፣ የጠቅላይ መምሪያ ዕዝ አስታወቀ።
የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትሩ ለገሰ ቱሉ (ዶ/ር)  በወቅታዊ ሁኔታ ዙሪያ በሰጡት መግለጫ፣ የአስቸኳይ ጊዜ ጠቅላይ መምሪያ ዕዝ ከተቋቋመ ጊዜ ጀምሮ ያከናወናቸውን የመጀመሪያ ምዕራፍ ተግባራት መገምገሙን አስታውሰዋል፡፡
የፀጥታ ችግር በተከሰተባቸው የአማራ ከልል አካባቢዎች፣ የተቋማት እንቅስቃሴ ወደ ነበረበት እየተመለሰ መሆኑንም ተናግረዋል።

እንግዲህ ከሰሞኑ   ያደረግነውን  የአርባምንጭ  ጉዞ በተመለከተ በራሴ ተነሳሽነት (በህዝብ ሳልጠየቅ ማለቴ ነው) አስተያየት የጻፍኩኝ የመጀመሪያው ጋዜጠኛ እኔ ሳልሆን አልቀርም፡፡ በእርግጥ እኔም ቀልቤ ጻፍ ጻፍ ብሎ ቢወተውተኝ ነው፣ ከመሸ  ወዲህ የከተብኩት፡፡

አስተያየቱ ምን ላይ ያተኩራል ለሚለው ጥያቄ፣ ምላሼ፣ አንብባችሁ ድረሱበት የሚል ነው፡፡ በጣም አጭር ስለሆነ  ትንሽ ብቻ  ታገሱ፡፡

እስካሁን ድረስ እንደ ብዙዎቹ ሪፖርተሮቹ ባይሆንም፣ ብዙ ቦታ ተጉዣለሁ ብዬ አምናለሁ፡፡ ሁለቴ ናይሮቢ ለሥልጠና የተጓዝኩትን ጨምሮ፣ በርካታ የአገር ውስጥ ጉዞም አድርጌያለሁ፡፡ ነገር ግን የትኞቹም ጉዞዎች የአርባምንጭን አያክሉም፡፡ አርባምንጭ እንዴት ከናይሮቢ ጋር ይወዳደራል ከተባለ ምክንያቶቼን በቅጡ አቀርባለሁ፡፡ ለእኔ የአርባምንጩ ድንገተኛ የ4 ቀን ጉዞ፣ የሥራ ብቻ አይደለም፤ የመዝናናት፣ አገር የማየት፣ አየር የመለወጥ፣ የማላውቃቸውን አዳዲስ ጋዜጠኞች የመተዋወቅ (ኔትዎርክ የማስፋት) ጭምር ነው፡፡ አዲስ የህይወት ተሞክሮ እንደማለት ነው፡፡ ድንገተኛም መሆኑ  ልዩ ያደርገዋል፡፡ በአንድ ቀን ተነግሮኝ ነው ለጉዞ የተነሳሁት፡፡ በዚህ ወቅት ከአዲስ አበባ መውጣት ለራስም ለቤተሰብም ስጋት ስለሚፈጥር በቅርቡ ከፊንፊኔ ወጥቼ አላውቅም፡፡

ከመጀመሪያውም የአርባምንጩ  ጉዞ ሲነገረኝ፣ (ያውም በአንድ ቀን ብቻ Notice)፣ለምን እንደምንሄድ እንኳን ሳልጠይቅ ነው የተስማማሁት፡፡ ቀልቤን (ፈረንጅ instinct እንዲል) አድምጬ ነው እንጂ፣ በቅጡ አስቤበት አይደለም፡፡ ለቤተሰብ  እንኳን ሳላሳውቅ ነው በራሴ የወሰንኩት፡፡ ደግነቱ እነሱም  ብዙ አልተቃወሙም፡፡

ቀልቤን በማዳመጤም ሳይሆን አይቀርም፣ ጉዞው የተቀዋጣለትና የሰመረለት የሆነው፡፡ ከሁሉም በላይ ጉዞውን አስደሳች ያደረገው ግን ተጀምሮ እስኪጠናቀቀቅ ድረስ በፍቅር፣ በጨዋታ፣ በመተሳሰብና በመከባበር የታጀበ በመሆኑ ይመስለኛል፡፡ ( ከተሳሳትኩ እታረማለሁ)  ጉዞው በተጨማሪም  ነጻነትና እኩልነት፣ ፍትህና ዲሞክራሲያዊነት የሰፈነበት (ያውም ከአገራችን የፖለቲካ ፓርቲዎች በእጅጉ የተሻለ) ነበር ማለት ይቻላል፤ያለ ምንም ማጋነነን፡፡  

በዚያ ላይ የጉዞውን አስተባባሪ ተሼን ጨምሮ፣ ሁሉም ጋዜጠኞች፣ ነጻና ተጫዋች (የማያካብዱ)፣ ቀልድና ተረብ የሚወዱ፤ (የገባቸው የሚባሉ)  ናቸው፤ በጉዞው  ብቸኛዋ የሄዋን ዘር የነበረችውን ጋዜጠኛ ጨምሮ ማለት ነው፡፡

ሌላው ቀርቶ ከዚህ በፊት የማናውቀው ቴዲ የተባለው ሹፌራችን ሳይቀር፣ የጋዜጠኞች ቡድኑን መንፈስና ስሜት በቅጡ ተገንዝቦ፣ በተመሳሳይ ቫይብና ሥልተ-ምት ለመንቀሳቀስ ሲሞክር ነው የተስተዋለው፤ስንሄድም ስንመጣም፡፡ ለዚህ ደግሞ የጉዞው አስተባባሪ፣ ሰብአዊና ወዳጃዊ አቀራረብ ጉልህ አስተዋጽኦ አድርጓል ባይ ነኝ፡፡ የተሼ ጠንካራ ጎን የሚጀምረው እንግዲህ ከዚህ ነው፡፡ (የአራዳ ልጅ ይሏል ይሄ ነው!)

የጉዟችን አስተባባሪና መሪ (ተሼ)፤ ከሳቅና ጨዋታ በቀር ጭቅጭና ንትርክ አይመቸውም፡፡ የሥራ ባልደረቦቹ፣ የሥራ ባልደረቦች ብቻ ሳይሆኑ ጓደኞቹም ጭምር ናቸው፡፡ እንደ ጓደኛ ያከብራቸዋል፤ ያስብላቸዋል፤ምቾታቸው እንዳይጓደል የቻለውን ሁሉ ያደርጋል፡፡ ይህንን ነው በ4 ቀናት የአርባምንጭ ጉዟችን የታዘብኩት፡፡

ከዚህ በተጨማሪ ተሼ የዋህ፣ ቀና አመለካከት ያለው፣ ከጥቃቅን ተራ ጉዳዮች ይልቅ ትላልቅ ረብ ያላቸው ጉዳዮች ላይ የሚያተኩር መሆኑንም  በግሌ ተገንዝቤአለሁ፡፡  ነገ ሊደርስበት ያለመው ትልቅ ህልምና ግብ በትክክል አስቀምጦ፣ በትጋት እየሰራ ያለ መሆኑን ለማወቅ ነቢይ መሆን አይጠይቅም፡፡  

በሌላ በኩል፤ይሄን ጉዞ አስደሳችና አይረሴ የሚያደርገው ሌላው ጉዳይ ደግሞ ወደ አርባምንጭ የተጓዝንበትን  ዋና ዓላማ፣ ሙሉ በሙሉ ማሳካት መቻላችን ነው፡፡ የምንፈልጋቸውን መረጃዎች በቀጥታ ከጉዳዩ ባለቤቶች (from the horse’s mouth እንዲሉ) አግኝተናል፤ በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ ይሏል ይኼ ነው፡፡  

አርባምንጭ የቆየነው ለሦስት ቀናት ብቻ ቢሆንም፣ በተለያዩ ምክንያቶች፣ በሦስት የተለያዩ ሆቴሎች ውስጥ ማደራችንን ወድጄዋለሁ፡፡ አገር ካዩ አይቀር እንዲህ ነው፡፡ የአርባምንጭን ጥሬ ሥጋ በቆጭቆጫ እንዲሁም አገሩ የሚታወቅበትን ምርጥ ዓሳ በጥብሱም በዱለቱም በደንብ አጣጥመናል፡፡ የአካባቢው  ተስማሚ የአየር ንብረትና  ማራኪው መልክአምድርም የሚረሳ አይደለም፡፡ እዚህ  ጋ  የአርባምንጮችን  እንግዳ ተቀባይነትና ልዩ መስተንግዶ  ሳይጠቅሱ ማለፍ ንፉግነት ነው የሚሆነው፡፡ ከልብ እናመሰግናለን፡፡

በመጨረሻም የጉዞውን አስተባባሪና የጋዜጠኞች ቡድን አባላት፣ ላሳለፍነው አስደሳችና አይረሴ ጊዜ ሁሉ ላመሰግናቸው  እወዳለሁ፡፡ ወደፊት ስለ አርባምንጭ ያየሁትንና የማረከኝን በስፋት ለማቅረብ እሞክራለሁ፡፡ የነገ ሰው ይበለን፡፡
ፈጣሪ ሰላሙን ያውርድልን !

• ካፒታሉን ከ1 ሚሊዮን ብር ወደ 2 ቢሊዮን . ብር አሳድጓል
• የኩባንያው ቴሌቪዥን ጣቢያ በይፋ ሥርጭት ጀምሯል
ፐርፐዝ ብላክ ኢትዮጵያ፣ የተመሰረተበትን የ2ኛ ዓመት ክብረ በዓሉን፣ "ከሚሊዮኖች ወደ ቢሊዮኖች - ቃል በተግባር" በሚል ዛሬ ተሲያት ከ8 ሰዓት ተኩል ጀምሮ፣ በተለያዩ ዝግጅቶች በሚሊኒየም አዳራሽ አክብሯል፡፡
በ1 ሚሊዮን ብር ካፒታል የተመሰረተው ኩባንያው፤ በ2 ዓመታት ጊዜ ውስጥ ካፒታሉን ወደ 2 ቢሊዮን ብር ማሳደግ መቻሉን የፐርፐዝ ብላክ መሥራችና ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዶ/ር ፍስሃ እሸቱ በክብረ በዓሉ ላይ ባደረጉት ንግግር አስታውቀዋል፡፡
“ከገበሬው ቲቪ” (ኬቲቪ) የተሰኘው የኩባንያው ቴሌቪዥን ጣቢያ፣ በዛሬው ዕለት የሙከራ ሥርጭቱን በይፋ እንደጀመረ ያበሰሩት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፤ ጣቢያው ትኩረቱን በግብርናና ኢኮኖሚ ላይ አድርጎ ለ24 ሰዓት እንደሚሰራጭም ጠቁመዋል፡፡
እስካሁን በ10ሺ የሚሰሉ አርሶአደሮችና ሌሎች ኢትዮጵያውያን፣ የፐርፐዝብላክ ባለአክሲዮኖች መሆናቸው የሚታወቅ ሲሆን፤ ኩባንያው ባለፉት ሁለት ዓመታት፣ የኑሮ ውድነትን ለማቃለል ምርቶችን በቀጥታ ከገበሬው በማምጣት፣ለተጠቃሚው ማህበረሰብ በተመጣጣኝ ዋጋ ሲያከፋፍል ቆይቷል፡፡
ፐርፐዝብላክ፣ በከተማዋ የሚስተዋለውን ከፍተኛ የመኖርያ ቤት ችግር ለማቅለል በማለምም፣ በቅርቡ ፊቱን ወደ ሪልእስቴት ግንባታ ያዞረ ሲሆን፤ ዜጎች በተመጣጣኝ ዋጋ መኖሪያ ቤት የሚያገኙበት ፕሮጀክት እንደሆነም ተነግሯል፡፡
የዛሬ ሁለት ዓመት ግድም፣ የዩኒቲ ኮሌጅ መሥራችና ባለቤት በነበሩት ዶ/ር ፍስሃ እሸቱ፣ጠንሳሽነት የተቋቋመው ብላክፐርፐዝ ኢትዮጵያ፤ የጥቁርን ህዝብ የኢኮኖሚ የበላይነትና ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ፕሮጀክቶችን ቀርጾ በሥራ ለማዋል እየተጋ የሚገኝ ኩባንያ ሲሆን፤ በቅርቡ አዲስ ሁለገብ የበይነመረብ መገበያያ መድረክ ይፋ ማድረጉ ይታወሳል፡፡

በአዲስ ዓመት ዋዜማ ታዋቂ ዓለም አቀፍ አርቲስቶችን ወደ ኢትዮጵያ በማምጣት የሙዚቃ አፍቃሪያንን በማዝናናት የሚታወቀው ሸራተን አዲስ ሆቴልና የኢትዮጵያን ባህልና ሙዚቃ ለዓለም ለማስተዋወቅ የሚተጋው “ይሳቃል ኢንተርቴይመንት” በመተባበር በአዲስ ዓመት ዋዜማ ታላቅ የሙዚቃ ኮንሰርት እንደሚያዘጋጁ ገለፁ።
አዘጋጆቹ ይህን የገለጹት ትላንት ሀምሌ 28 ቀን 2015 ዓ.ም ረፋድ ላይ በሸራተን አዲስ ሆቴል በጋራ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ነው። በዚህ ኮንሰርት ላይ በተለያዩ ዓለም አቀፍ መድረኮች አድናቆትና ተቀባይነት ያገኘውና በመድረክ ስሙ “ሬማ” በሚል መጠሪያ የሚታወቀው ናይጄሪያዊው የአፍሮቢት ስልት አቀንቃኝ ሥራውን የሚያቀርብ ሲሆን፤ በአዲስ የሂፕ ሆፕ ስልት ሙዚቃው ተወዳጅነትን ያተረፈው ልጅ ሚካኤል (ፋፍ)፣ ተወዳጇ ድምፃዊት ብሩክታዊት ጌታሁን (ቤቲጂ)፣ እንዲሁም ተቀባይትን እያገኙ ከመጡት አዳዲስ ድምፃዊያን አንዱ የሆነው ድምፃዊያን አዲስ ለገሰ ሥራዎቻቸውን እንደሚያቀርቡ አዘጋጆቹ ገልጸዋል።
የመግቢያ ዋጋንና ሌሎች ጉዳዮችን በተመለከተ ጊዜው ቀረብ ሲል እንደሚያሳውቁም ተጠቁሟል።


”ባለሃብቱ የአካባቢውን ገጽታ ማጠልሸቱ ተገቢነት የለውም”

በቅድሚያ ስምዎትንና የሥራ ሃላፊነትዎን ይንገሩን?
አቶ ታምራት ጎአ እባላለሁ፡፡ አሁን ላይ የገረሴ  ዙሪያ ወረዳ ገቢዎች ፅ/ቤት ሃላፊ ነኝ፤ የቀድሞው የንግድ ፅ/ቤት ሃላፊ ማለት ነው፡፡
በሥራ ሃላፊነትዎ ስለ ኦልግሪን አግሮ ኢንዱስትሪ የሚያውቁትን ያካፍሉን?
ኦልግሪን በኮሻሌ አካባቢ በጊዜው በተወሰነ ደረጃ እያለማ ነበር፡፡ እኔ በዚያን ጊዜ የማውቀው ከሰራተኞች የተቆረጠ የስራ ግብርና የእርሻና መሬት መጠቀሚያ ግብር እንዳልተከፈለና በየጊዜው ከወረዳው ጋር  ጭቅጭቅ እንደነበረ ነው፡፡
ምን ያህል ነው በወቅቱ ያልተከፈለው የግብር መጠን?
በጊዜው  ብዙ ነበር፤ ከ2013 በፊት የሰራተኛ የስራ ግብር ወደ 593 ሚሊዮን ብር ገደማ አለመከፈሉን አውቃለሁ። በወቅቱ  በዚህ ጉዳይ ከፍተኛ ፍ/ቤት ድረስ ከስሰናል፡፡ ባለሃብቱ ሲገኝ ንብረትም ካለው ንብረቱ ተይዞ እንዲከፍል ተብሎ ነበር የተወሰነው፡፡ እስካሁን የክስ ንብረት አጥተን ነው የተውነው፡፡ ግን  ባለሃብቱ ለወረዳው መገበር ወይም መክፈል ያለበት እዳ እንዳለ አውቃለሁ።
ይሄን ሁሉ ገንዘብ እናንተ ለምንድነው በጊዜው ያልጠየቃችሁት?
በየጊዜው  ይጠየቃል፤ ይከፈላል ይባላል፤ ቀጠሮ ይሰጣል፡፡ ይሄ እኮ ሌላ የሥራ ትርፍ ግብር አይደለም፤ በባለሃብቱ  ሥር  ያሉ ሰራተኞች መክፈል ያለባቸው የሥራ ግብር ነው። ከኢንቨስተሩ ጋር የሚያገናኘው ነገር የለም። ባለሃብቱ በታማኝነትና በአደራ ያንን ቆርጦ ለመንግሥት ማስገባት ሲገባው ለግል ጥቅሙ እያዋለው በወቅቱ ማስገባት አልቻለም። በጊዜው ሲጠየቅም መልካም ምላሽ የማግኘት እድሉ በጣም ጠባብ ነው የነበረው።
ይሄ የአንድ ዓመት ወይም የሁለት ዓመት ብቻ ዕዳ አይደለም። አንድ ባለሃብት ይሄን ያህል ዕዳ እስኪጠራቀምበት ድረስ እንዴት ዝም ተባለ? ወይስ ማስጠንቀቂያ ሰጥታችኋል?
በየጊዜው ማስጠንቀቂያ ይሰጣል፤ ተወካይ አለው፤ በተወካዩ በኩል እንዲደርሰው ብዙ ጥረት ተደርጓል፡፡ በእርግጥ ኢንቨስተሩ ብዙ ጊዜ በአካባቢው አይገኝም፡፡ “እሩቅ ነው፣ ሌላ ቦታ ነው፣ ውጭ ነው፣ አዲስ አበባ ነው“ ሲባል ነው የከረመው። ከ2013 በፊት ያለው ከ2.2 ሚሊዮን ብር በላይ የሚሆን እዳ ነው፡፡ እኛ እንደ ገቢዎች ንብረት ለመያዝ ሞክረናል፤ አንድ መኪና ተይዞ እዚህ ታስሮ መጨረሻ ላይ ፍ/ቤት ከስሰን ነበር፡፡ ነገር ግን ከልማት ባንክና ከሌሎች ግለሰቦች ከንብረቱ ያላነሰ ብድር ስላለበት ይሄንን ሸጣችሁ መውሰድ አትችሉም ሲባል፣ ከንብረቱም ከገንዘቡም ሳንሆን ቀረን፡፡
አሁን ለመንግሥት መግባት የነበረበትን ገቢ ማነው የሚሸፍነው?
ባለሃብቱ እንግዲህ መጀመሪያ ላይ 2ሺ ሄክታር መሬት ነው የወሰደው፡፡ ከዚያ ቀጥሎ ወደ 2013 ላይ 1ሺ 500 ሄክታር ነው የሆነው። ይሄን እስከሚያለማ ወይም ልማት ባንኩ መሬቱን ለሌላ ሰው አሳልፎ ሲሰጥ የኛንም እዳ ታሳቢ አድርጎ ለኛም የሚከፍልበት ህግ ስለሚያዝ እሱን እየጠበቅን ነው።
ባለሃብቱ  ስንት ሄክታር ላይ ነበር ያለሙት?
ወደ 300 ሄክታር ነበር ለጊዜው ያለማው፤ የወሰደው ወደ 2ሺ ሄክታር መሬት ነው፡፡
ምን ምን ነበር የለማበት?
 ሙዝና ሌሎች ሰብሎችም ነበሩ፡፡
ሌሎች ሰብሎች ምንድን ናቸው?
ሰሊጥም አምርቷል፤ በቆሎና የተለያዩ ነገሮች ነበሩ በጊዜው።
ባለሃብቱ ከወረዳ እስከ ዞን ድረስ ያሉ አመራሮች ተጽዕኖ አድርገውብኛል የሚል ክስ አቅርበዋል---
እኔ  በእርግጥ ወደ ገቢዎች የመጣሁት ከ2014 ዓ.ም ወዲህ ነው፡፡ ነገር ግን የተለየ ተፅዕኖ በባለሃብቱ ላይ አልተደረገም፡፡ እንግዲህ ከ1996 ጀምሮ  ይሄን መሬት ተረክቦ እያለማ ነው ያለውና ተፅዕኖ ቢኖር እስከ ዛሬ እንዴት ይኖራል?! አንዳንዴ ሰው ሲሸነፍ መሸነፉን ላለመቀበል አካባቢው ላይ የሚፈጥረው ያልተገባ ገፅታ ጥሩ አይደለም። ባለሃብቱ ከፈለገ ነገም ተመልሶ መጥቶ ሊያለማ ይችላል፡፡ ግን ትክክል ያልሆነ ነገር ማውራቱና የአካባቢውን ገጽታ ማጠልሸቱ ተገቢነት የለውም። ስለዚህ ባለሃብቱ ላይ የተለየ ተፅዕኖም ሆነ ጫና አላደርግንም፡፡ ቁጭ ብለን እንነጋገር፤ እዳውንም ጊዜ ሰጥተን መውሰድ እንችላለን ለማለትም እኮ ሰውየውን በአካል እንኳን ማግኘት አልቻልንም። የእሱ ተወካይም ነበር፤ በኋላ ተወካዩንም ማግኘት አልቻልንም። በበቃኝ እኮ ነው ወጥቶ የሄደው፡፡ ሜዳውም ሜዳ የሆነው፣ ሙዙም ሌላውም ውሀ የሚያጠጣው አጥቶ ነው በራሱ ጊዜ የጠፋው እንጂ ወረዳው  በጣም ብዙ ታግሶታል፡፡  ይሄን ያህል እዳ ማንም ግለሰብ ላይ ቢኖርበት፣ ግለሰብ ያሳድራል እንዴ!? ወረዳው መልማት የሚችል በጣም ሰፊ መሬት አለን፣ በቂ ውሃም አለን፤ ተጨማሪ ኢንቨስተሮች ያስፈልጉናል ብሎ በጣም ተሸክሞታል፡፡ ነገር ግን  ዛሬ ላይ ባለሃብቱ የአካባቢውን ገጽታ በሚያጠፋ መልኩ መምጣቱ ብዙም ተቀባይነት የለውም።
ባለሃብቱ ያቀረቡት ክስ ሁሉ ትክክል አይደለም ነው የሚሉት?
ትክክል አይደለም፡፡ ይሄን ያህል ያልተከፈለ ዕዳ እኮ ችለን ባለሃብቱ እስኪመጣ እየጠበቅን ነው። የተለያዩ መኪናዎች፣ ጋሪዎች፣ የተለያዩ ንብረቶች እያሉ፤ ይሄ ቋሚ ንብረት ስለሆነ ቢመጣ ሊያለማው ስለሚችል፣ ሲመጣ እንነጋገራለን ብለን እየጠበቅን ነው ያለነው። እስካሁን መሬቱ ባዶ ሜዳ ጨፈቃ ለብሶ ነው ያለው፤ እና ልዩ ተፅዕኖ አሳድረን የፈጠርነው ነገር የለም፡፡ አሁንም ቢሆን በወረዳችን ሰፊ መሬት አለን፤ ውሃም አለን፤ አየር ንብረቱም በጣም የተሻለ ነው። እርሻ ብቻ ሳይሆን የተለያዩ ማዕድናትም አሉ። የድንጋይ ከሰል ጭምር ያለበት ወረዳ ነው፤ ገና እየተጠና ነው፤ ይረጋገጣል ብለን ተስፋ እናደርጋለን። ወርቅና ቢያንስ ከ15 በላይ ማዕድናት ያሉበት ወረዳ ነው፤ ምንም ያልተነካ ጥሬ የተፈጥሮ ሃብት ያለበት አካባቢ  ነው፡፡ ከዚህ አንጻር  የትኛውንም ጉዳይ በሰላማዊ መንገድ  መነጋገር እንችላለን።
በመጨረሻ የሚያክሉት ነገር ካለ--?
እንግዲህ ባለሃብቱ እስከ 2015 አጋማሽ ድረስ ወደ 2.2 ሚሊዮን ብር እዳ አለበት፡፡ በዚህ የተነሳ ወረዳችን ዛሬ ላይ ደሞዝ መክፈል አልቻለም፤ በጣም ከፍተኛ ችግር ውስጥ ነው ያለነው፡፡
ግለሰቡ እዚህ አገር ላይ እዚህ ወረዳ ላይ የቆየ ሰው ነው፤ ያለማ ሰው ነው፤ ብዙ ሃብት ያገኘ ሰው ነው፤ ይሄንን ታሳቢ አድርጎ እዳውን  የሚከፍልበት መንገድ ቢፈጥር ጥሩ ነው፡፡ ከአሰራር ጋር ተያይዞ የተለየ ነገር ካለ ከእኛ ጋር መነጋገር ይቻላል። ነገር ግን 2.2 ሚሊዮን ብር እዳ ያለበት ግለሰብ መሆኑን፣ ለህዝባችን ልማት እንድንሰራ እኛንም እንዲረዳን ጥሪ ማስተላለፍ እፈልጋለሁ።

,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,---------------------------------------------------------

”ባለሃብቱ ተጽዕኖ ቢደረግበት ኖሮ ይሄን  ያህል ጊዜ አይቆይም ነበር”

በመጀመሪያ ስምዎትንና የሥራ ሃላፊነትዎን ይንገሩን?
ካሣሁን ዋሲሁን እባላለሁ፤ በገረሴ ወረዳ ምክትል ከንቲባና የኢኮኖሚ ክላስተር አስተባባሪ ነኝ።
እስቲ ስለ ወረዳው በጥቂቱ ያስተዋውቁን?
ወረዳው ከአዲስ አበባ 560 ኪ.ሜ ርቀት ላይ የሚገኝ ሲሆን፤ሦስቱንም የአየር ንብረቶች ያካተተ አካባቢ ነው። ቆላማ፣ ወይን አደጋና ደጋ የአየር ንብረት ማለት ነው፡፡ በቆላው አካባቢ ጤፍ፣ ሰሊጥ፣ ሙዝ፣ በቆሎ፣ ማሽላ ሲበቅልበት፤ በደጋውና ወይን አደጋው ደግሞ ባቄላ፣ አተር፣ ስንዴ፣ ገብስና ማሾ  የመሳሰሉት ይበቅሉበታል፡፡
እርስዎ በቀደመው ጊዜ ያለዎት ሃላፊነት  ምን ነበር?
ከ2010 ዓ.ም በፊት ቦንካ ወረዳ ተብሎ ነው የሚታወቀው፡፡ ከዛ በኋላ ነው እንግዲህ ገረሴ ዙሪያ ወረዳ ተብሎ የተዋቀረው።  ከ2010 -2013 ዓ.ም ድረስ በአመራርነት ሰርቻለሁ፡፡
በወቅቱ በአካባቢው ላይ  ምን ያህል ኢንቨስተሮች  ነበሩ?
በወቅቱ በአካባቢው ላይ አንድ በግብርና ዘርፍ ላይ የተሰማራ ባለሀብት ብቻ ነው የነበረው፡፡ ኦልግሪን አግሮ ኢንዱስትሪ ኃ.የተ.የግል ማህበር ይባላል፡፡
ኦልግሪን ብቻ  ነው  የነበረው?
አዎ፤ እሱ ብቻ ነበር።
መቼ ነው እዚህ አካባቢ ኢንቨስት ማድረግ የጀመረው?
ወቅቱን በትክክል ባላውቀውም፣ እኔ ወደ አመራርነት ከመጣሁበት ከ2010-2013 ዓ.ም ባለው ጊዜ  ነበር።
እሱ ብቻ ለምንድን ነው የነበረው? በቂ መሬት የለም ወይስ ፍላጎቱ ያላቸው ሌሎች ባለሃብቶች አልነበሩም ወይስ የእናንተ የማስተዋወቅ (ፕሮሞሽን) ችግር ነው?
የኛ ችግር አልነበረም፤ ሌሎች ባለሃብቶች በመጥፋታቸውም አይደለም፤ በወቅቱ ባለው  ሁኔታ መሬቱን ተቀብሎ የነበረው ኦልግሪን በመሆኑ ነው፡፡
ተጨማሪ መሬቶችን ለሌሎች ባለሃብቶች ለምን ምቹ አላደረጋችሁም?
ይሄ ባለሃብት በሰዓቱ የነበረውን መሬት ተቆጣጥሮት ነበር፡፡ ሰፊ መሬት የነበረን እዚያ አካባቢ ነው፡፡ ከነበረን መሬት ወደ 2ሺ ካሬ የሚሆነው በባለሃብቱ ስም ነው  የነበረው። ለኢንቨስትመንት አመቺና ውሃም በአቅራቢያው የሚገኝ፣ የመሬቱ አቀማመጥ (አግሮኮሎጂው)ለእርሻ የሚያመች  እሱ የያዘው መሬት አካባቢ ነው፡፡
ከባለሃብቱ ጋር ያላችሁ ግንኙነትና  ቀረቤታ እንዴት ነበር?
ከእኛ ጋር በግል ችግር አልነበረብንም።  እንደ መንግስት ደግሞ  ባለሃብቱ ከእርሱ የሚጠበቅበትን ግዴታ ባለመወጣት የተነሳ ብዙ ግጭቶች ነበሩ። የእርሻና የመሬት መጠቀሚያ ግብር በወቅቱ ያለመክፈል ሁኔታ በእጅጉ ይስተዋል  ነበር። ለምሳሌ ከ2007-2009 ዓ.ም ድረስ የገቢዎች ጽ/ቤት ሃላፊ ነበርኩ። በዚያን ጊዜ የንብረት መያዝ፣ ማስጠንቀቂያ የመስጠት---እስከ መደባደብ የደረስንበት ሂደቶች ነበሩ። በተደጋጋሚ ለግብር የንብረት መያዣ ሰጥተን ነበር። በአጋጣሚ እርሱን ስላላገኘነው የክልልና የዞን አመራሮችን ይዞ በዚህ ሲያልፍ የንብረት መያዣ ስንሰጠው አልቀበልም የሚል እሰጣ ገባ ውስጥ የገባንበት ሂደት ተፈጠረ፡፡
እርምጃ አልወሰዳችሁም?
አልወሰድንም። በደራሼ ሲመለስ በዞን ተይዞ ታስሮ ነበር፡፡ ሆኖም ግን ዕዳውን አልከፈለም፡፡ ከዚያም ለውጡ መጣ፡፡ ግን ችግሩ በዚያው ነው የቀጠለው፡፡
ባለሃብቱ፤ በወቅቱ የነበሩት አመራሮች እርስዎን ጨምሮ ከፍተኛ ጫና አድርገውብኛል፤ ከፍተኛ በደል ተፈጽሞብኛል፤ ጥቂት ባለሃብቶች ለጥቂት የወረዳው ባለሥልጣናት ሙስና በመስጠት በጣም ከፍተኛ ጫና አድርሰውብኛል፡፡ በዚህ የተነሳ ለ500 ሚሊዮን ብር ኪሳራ ተዳርጌአለሁ ብለዋል፡፡ እርስዎ በዚህ ጉዳይ ላይ ምን ይላሉ?
እንግዲህ በሰዓቱ ሌላ ባለሀብት አልነበረም፤ እሱ ብቻ ነው የነበረው። እሱ ብቻ ሆኖ ከሌላ ባለሃብት ጋር ተሞዳሙደን በእሱ ላይ ጫና የምናደርስበት ሁኔታ እንደሌለ ማወቅ አለባችሁ። ባለሃብቱ ከ1997 ዓ.ም ጀምሮ ነው መሬቱን የያዘው፤ከዚያ ጊዜ ጀምሮ እስካሁን ድረስ ምንም ሳያመርት፣ ለህብረተሰቡ ለአርሶ አደሩ ምንም መሰረተ ልማት ሳይገነባ ነው የቆየው። ይህን ንብረት መያዣ እያደረገ ከየባንኩ እየተበደረ  ነው የቆየው። ተጽእኖ ቢደረግበት ኖሮ ይሄን ያህል ጊዜ አይቆይም ነበር።
በተጨማሪም ባለሃብቱ በብሔሬ፣ በማንነቴ የተነሳ ከፍተኛ ተፅዕኖ ተደርጎብኛል ብለዋል፡፡ በዚህ ቅሬታስ ላይ ምላሽዎ ምንድን ነው?
በብሄር ላይ ተንተርሰን ተጽዕኖ ያደረግነው ነገር የለም፤ ሊኖርም አይችልም፤ ህገ-መንግስታችንም ይሄን አይፈቅድም። ይሄ ደግሞ ቢኖርም በሰዓቱ በህግ መብቱን ሊያስከብር ይችላል። እኔ በነበርኩበት ወቅት  ያለብህን እዳ ክፈል ተብሎ ከመጠየቅ ያለፈ ብሄር ተኮር ጥቃት አልተደረገበትም።
ከዚህ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ስጋት ለገባቸው ሌሎች ባለሃብቶች ምን መልዕክት ያስተላልፋሉ?
ብዙ ከሌላ ቦታ የመጡ ሰዎች አሉ፤ ኑና አካባቢያችንን አልሙ ነው የምለው። ለዚህ ደግሞ ዋስትናችሁ ህገ-መንግስቱ ነው እንጂ ግለሰብ አይደለም፤ ስለዚህ አትፍሩ የሚል መልዕክት ነው የማስተላልፈው።


-  የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር  የፌደራል መንግስት ጣልቃ እንዲገባ በይፋ ጠይቀዋል
- የሚኒስትሮች ም/ቤት በክልሎ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እንዲታወጅ ወስኗል
-  የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ጎንደርና ላሊበላ የሚያደርገዉን በረራ አቋርጧል
-  እንግሊዝና  ስፔን  ዜጎቻቸው  ወደ አማራ ክልል እንዳይጓዙ አስጠንቅቀዋል

ለወራት በተለያዩ የአማራ ክልል አካባቢዎች ሲካሄድ የነበረው ተቃውሞና የታጣቂዎች ግጭት አሳሳቢ ደረጃ  ላይ  መድረሱ ተነግሯል። የቀውሱ አካባቢም እየሰፋ  በመሄድ በርካታ ቦታዎችን አዳርሷል።
ለሁለት አመታት  በትግራይ ታጣቂ ሃይሎች የተከፈተውን  ጦርነት  ሲያስተናግድ የከረመው ክልሉ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ   በታጣቂዎችና በፀጥታ ኃይሎች መካከል በተቀሰቀሰው ግጭት ሳቢያ የክልሉ ነዋሪዎች ለከፍተኛ ስጋት የተጋለጡ ሲሆን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ዶ/ር ይልቃል ከፋለ፣  የፌደራል መንግሥቱ ጣልቃ እንዲገባ በይፋ ጠይቀዋል።
በክልሉ ርዕሰ መስተዳደር  ዶ/ር ይልቃል ከፋለ ተፈርሞ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ በተጻፈው  ደብዳቤ፣  በክልሉ ያለውን  የፀጥታ መደፍረስ በመደበኛ የሕግ ማስከበር ሥርዓት ለመቆጣጠር አዳጋች በመሆኑ የፌደራል መንግሥቱ ጣልቃ እንዲገባ ተጠይቋል።
“በመደበኛው የሕግ ማስከበር ሥርዓት ለመቋቋም የማይቻል ሁኔታን ስለማሳወቅ” በሚል ከአማራ ክልል መንግሥት፣ ለፌደራሉ መንግሥት ሐምሌ 27 ቀን 2015 ዓ.ም በተጻፈው ደብዳቤ ላይ ክልሉ ከባድ ችግር እንደገጠመው ተጠቅሷል።
በዚህም ምክንያት “የፌደራል መንግሥት አስፈላጊውን የሕግ ማዕቀፍ እንዲተገብር”፣ የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ጥያቄ ማቅረቡ በደብዳቤው ተገልጿል። በክልሉ ያለው የፀጥታ መደፍረስ በክልሉ ከፍተኛ ሰብአዊ፣ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳት እያስከተለ መሆኑን የጠቀሰው የክልሉ መንግሥት፣ የፌደራል መንግሥቱ በአገሪቱ ሕገ መንግሥት መሠረት አስፈላጊውን እርምጃ እንዲወስድ ጠይቋል።
በሌላ በኩል፤ የሚንስትሮች ም/ቤት በአማራ ክልል የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እንዲታወጅ ውሳ አሳልፏል።
በክልሉ  ባለው የጸጥታ ችግር መባባስ ምክንያት የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ክልሉ የሚያደርጋቸውን በረራዎች ለመሰረዝ ተገዷል። አየር መንገዱ ከትናንት ጀምሮ ወደ ጎንደር፣ ላሊበላና ኮምቦልቻ የሚያደርጋቸውን በረራዎች መሰረዙን ለማወቅ ተችሏል።
የፈረንሳዩ የዜና ወኪል አዣንስ ፍራንስ ፕሬስ፣ ታጣቂዎች የላሊበላ አውሮፕላን ማረፊያን በቁጥጥራቸው ስር ማድረጋቸውን ዘግቧል። የኢትዮጵያ አየር መንገድም ወደ ጎንደርና ላሊበላ በረራ አቋርጫለሁ ማለቱን ዘገባው ጨምሮ  ጠቅሷል።
በተጨማሪም በጎንደር ከተማ ካለፈው ረቡዕ ጀምሮ በመንግሥት የጸጥታ አካላትና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል እየተደረገ ባለው ውጊያ ምክንያት ከሐሙስ ጀምሮ ወደ ጎንደር የሚደረግ የአየር በረራ ተቋርጧል። ወደ ላሊበላ በቀን ሁለት ጊዜ ከሚደረጉ  በረራዎች የመጀመሪያው ማክሰኞ ሐምሌ 25 ቀን 2015 ዓ.ም ጠዋት ላይ የተደረገ ሲሆን፤  “ተጨማሪ የመከላከያ ሠራዊት አባላት ላሊበላ አየር ማረፊያ ሊገቡ ነው” የሚል ወሬ የሰሙ የፋኖ ታጣቂዎች ወደ ሥፍራው አቅንተው ጥበቃ ላይ ከነበሩ የፌዴራል ፖሊስ አባላት ጋር የተኩስ ልውውጥ ማድረጋቸውን እማኞች ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል።  ይህን ተከትሎም ከቀኑ 6 ሰዓት ከ50 ላይ ላሊበላ ኤርፖርት ማረፍ የነበረበት ተሣፋሪዎችን የጫነው  ሁለተኛው የመንገደኞች አውሮፕላን ካለው የጸጥታ ስጋት አንጻር ሳያርፍ  ተመልሷል።
በክልሉ እየተካሔደ በሚገኘው ግጭት ምክንያት፣ እንግሊዝና ስፔን፣ ለዜጎቻቸው የጉዞ ማስጠንቀቂያ ሲወጡ ሲሆን፣ የእንግሊዙ የውጭ ጉዳይ ቢሮ፣ “የዐማራ ሚሊሻ ፋኖ፣ የላሊበላን አየር ማረፊያ ተቆጣጥሯል፤” ሲል አስታውቋል።
ከእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ ቢሮ ጋራ ተመሳሳይ የጉዞ ማስጠንቀቂያ ያወጣው፣ በአዲስ አበባ የሚገኘው የስፔን ኤምባሲ፣ በላሊበላ የሚገኙ የስፔን ዜጎች፣ ኤምባሲውን እንዲያነጋግሩ  አሣስቧል።
የኢፌዲሪ መከላከያ ሰራዊት ሰሞኑን  በሰጠው መግለጫ፤ በፋኖ ስም እየተንቀሳቀሱ የሃገር ሰላም ለማወክ በሚሰሩ አካላት ላይ እርምጃ እወስዳለሁ ብሏል።
የሰራዊቱ የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተሩ ኮሎኔል ጌትነት አዳነ በሰጡት መግለጫ  ላይ እንዳመለከቱ፤  ከሰሞኑ በጎንደር የሰሜን ምዕራብ ዕዝን ዓመታዊ አፈጻጸም ለመገምገም ወደ ስፍራው እያቀኑ በነበሩ የሰራዊቱ አባላት ላይ ከጩሂት 2 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ሲደርሱ ተኩስ ተከፍቶባቸዋል ብለዋል ።
የሰራዊቱ አባላት በመመለስ ላይ ሳሉም በቆላድባ አካባቢ በተመሳሳይ ተኩስ እንደተከፈተባቸው ገልጸው፤ “ሃሳብ ሲነጥፍ ነፍጥ አንግቤ እዋጋለሁ” የሚል አካል ላይ ሰራዊቱ የሚወስደውን እርምጃ አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።
ኮሎኔል ጌትነት በዚሁ መግለጫቸው፤ ጉልበተኛና መሳሪያ ታጥቆ እንቅፋት እሆናለሁ ያለው አካል ላይ የሃይል እርምጃ ይወስዳል  ብለዋል።  ከዚሁ ጋር አያይዘውም  መከላከያ ላይ ነፍጥ ከሚያነሱ በተጨማሪ ሚዲያን ጨምሮ ሌሎች ግንባሮችን ይመራሉ ያሏቸው ወገኖች  ላይም እርምጃ በመውሰድ ተቋማቸው አገራዊ ጸጥታን የማስከበር  ኃላፊነቱን  እንደሚወጣ  አስገንዝበዋል፡፡

በደቡብ ክልል ጋሞ ዞን  2ሺ ካ.ሜ መሬት ወስዶ በሙዝ እርሻ፣ በግመል እንዲሁም በበግና ከብት እርባታ ላይ መሰማራቱን የሚገልጸው ኦልግሪን አግሮ ኢንዱስትሪ ኃላ. የተ. የግል ማህበር፣ በዞኑ ባለው የአስተዳደር በደል ሳቢያ ሃብት ንብረቱ እየተዘረፈበት መሆኑን አስታውቋል፡፡
የጋሞ ዞን አስተዳደር በበኩሉ፣ በኦልግሪን አግሮ ኢንዱስትሪ የቀረበው ክስና አቤቱታ፣ ከእውነት የራቀና የዞኑን  መልካም ገፅታ ለማጉደፍ ያለመ ነው ሲል ኮንኖታል።
የኦልግሪን አግሮ ኢንዱስትሪ ባለቤት አቶ ልኡል ስብሃቱና ወ/ሮ ቀለሟ አለሙ በቅርቡ  በዲሊኦፖል ሆቴል በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ በጋሞ ዞን አስተዳደር ተፈፅሞብናል ያሉትን በደል በዝርዝር አስረድተዋል፡፡
“የወረዳው አመራሮች የቴክኖሎጂ ሽግግር አላደረጋችሁም፤ የተማረ የሰው ሃይል አላስገባችሁም፤ ግብር አልከፈላችሁም የሚል ሰበብ በመፍጠር 200 ሄክታር የደረሰ ሙዝ አውጥተው በመሸጥ የቀረውን 38 ሄክታር በጨረታ በአደባባይ ሸጠውታል፤ ከ200 በላይ ከብቶች በአደባባይ ሸጠውብናል፤ ማሽነሪዎች ተፈታተው ተወስደውብናል፤ ያለማነው መሬትም ተሸንሽኖ ለባለሃብት ተሰጥቶብናል…” ሲሉ ባለሃብቱ የደረሰባቸውን በደል ጠቅሰዋል፡፡
ከኢትዮጵያ ልማት ባንክ የተበደርነው 46 ሚሊዮን ብር በቀን 40ሺ ብር እየወለደ 102 ሚሊዮን ብር ደርሷል ያሉት ባለሃብቱ አቶ ልኡል፤ በዚህ መሃል ጥቂት ባለሃብቶች ከአንዳንድ የመንግሥት ባለሥልጣናት ጋር በመመሳጠር ሃብትና ንብረታችንን እየዘረፉን ነው ሲሉም ከስሰዋል፡፡
 ኦልግሪን አግሮ ኢንዱስትሪ ባሰራጨው መግለጫም፤ በክልሉ ተከስቶ በነበረው አለመረጋጋት፣ የሰራተኞች መገደል፣ የንብረት መውደምና የኮቪድ ወረርሽኝ ሳቢያ ድርጅቱ ኪሳራ እንደደረሰበት አስታውሶ፤ በዚህም ከልማት ባንክ የወሰደው ብድር የመክፈያ ጊዜ እንዲራዘምለት ጠይቆ ምላሽ አግኝቶ እንደነበር አመልክቷል፡፡
“በደቡብ ክልል ጋሞ ዞን፣ ቦንኬ ወረዳ፣ ኮሸሌ ቀበሌ ያለው 1500 ሄክታር እርሻችንና ሃብታችን ልማት ባንክ ሃምሌ 11 ቀን 2015 ዓ.ም በፃፈልን ደብዳቤ፣ የተጠራቀመባችሁን 53 ሚ 250 ሺ ብር እስከ ሃምሌ 21 ቀን 2015 ዓ.ም ድረስ ከከፈላችሁ፣ ዋናው ብድር የሚከፈልበትን ጊዜ እናራዝመዋለን ቢልም፤ በአስተዳደር በደል ሃብታችንን ለመቀማት መንግስት ለነሐሴ 1 ቀን 2015 ዓ.ም ጨረታ አውጥቶብናል፡፡” ሲል ኦልግሪን አግሮ ኢንዱስትሪ አቤቱታውን አቅርቧል፡፡
የጋሞ ዞን አስተዳደር የወረዳ አመራሮች በበኩላቸው፤ የኦልግሪን አግሮ ኢንዱስትሪ ክስና አቤቱታ ከእውነት የራቀና የዞኑን መልካም ገፅታ ለማጉደፍ ያለመ ነው ሲሉ ኮንነውታል። ባለሃብቱ ከወሰደው 2ሺ ካ.ሜ መሬት ውስጥ ጥቂቱን ብቻ ነው ያለማው ያሉት አመራሮቹ፤ ንብረቱም የወደመውና የጠፋው በራሱ የአመራር ችግር ነው ብለዋል፡፡  
ኦልግሪን አግሮ ኢንዱስትሪ ወደ አካባቢው ገብቶ ለ14 እና 15 ዓመታት 2ሺ ሄክታር መሬት ይዞ የቆየ ቢሆንም ያለማው ግን ከ300 ሄክታር እንደማይበልጥ የገለፁት የገረሴ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አዝጌ ካሳዬ፤ በእነዚህ ሁሉ ዓመታት ወረዳውም ሆነ ማህበረሰቡ ከኢንቨስትመንቱ ተጠቃሚ እንዳልሆኑ ይናገራሉ፡፡
“ባለሃብቱ ወደ ኢንቨስትመንት ከገባ በኋላ ለሰራተኞች በአግባቡ ደሞዝ መክፈል አልቻለም፤ ሰራተኞቹንም በትኗል፣ ከሰራተኞች የሚሰበሰብ ግብር ለወረዳው እየከፈለ አልነበረም፤ በርካታ የተወዘፈ የግብር እዳ አለበት፤ የመሬት መጠቀሚያ ኪራይ ግብር እንዲሁ ተወዝፎ መክፈል አልቻለም፤ በተደጋጋሚ ማስጠንቀቂያዎች ቢጻፍም እስካሁን አልተከፈለም” ብለዋል፤ ዋና አስተዳዳሪው፡፡
የገረሴ ወረዳ ገቢዎች ፅ/ቤት ሃላፊ አቶ ታምራት ጎአ በበኩላቸው፤ በወቅቱ ከሰራተኞች የተቆረጠ የስራ ግብርና የእርሻ መሬት መጠቀሚያ ግብር እንዳልተከፈለና በዚሁ ሳቢያ በየጊዜው ከወረዳው ጋር ጭቅጭቅ እንደነበር አስታውሰዋል፡፡ የገቢዎች ጽ/ቤት ሃላፊው አክለውም፤ “ኦልግሪን እስከ 2015 ዓ.ም ድረስ ወደ 2.2 ሚሊዮን ብር ዕዳ አለበት፡፡ በዚህ የተነሳ ወረዳችን ዛሬ ላይ ደሞዝ መክፈል አልቻለም፤ በጣም ከፍተኛ ችግር ውስጥ ነው ያለነው፡፡ ግለሰቡ እዚህ ወረዳ ላይ የቆየ ነው፤ ያለማ ሰው ነው፤ ብዙ ሃብት ያገኘ ሰው ነው፤ ይሄን ታሳቢ አድርጎ እዳውን የሚከፍልበትን ሁኔታ ቢፈጥር ጥሩ ነው፡፡” ብለዋል፡፡
ባለሃብቱ አቶ ልኡል ስብሃቱ፤ “በወቅቱ የነበሩት አመራሮች ከፍተኛ ጫና አድርገውብኛል፤ ከፍተኛ በደል ተፈፅሞብኛል፤ ጥቂት ባለሃብቶች ለአንዳንድ የወረዳው ባለስልጣናት ሙስና በመስጠት ከፍተኛ ጫና አድርሰውብኛል” በሚል ላቀረቡት አቤቱታ የገረሴ ወረዳ ምክትል ከንቲባና የኢኮኖሚ ክላስተር አስተባባሪ አቶ ካሳሁን ዋሲሁን በሰጡት ምላሽ፤ “በወቅቱ ሌላ ባለሃብት አልነበረም፤ እሱ ብቻ ነው የነበረው፡፡ ከሌላ ባለሃብት ጋር ተሞዳሙደን በእሱ ላይ ጫና የምናደርስበት ሁኔታ አይኖርም፡፡ ባለሃብቱ ከ1997 ጀምሮ ነው መሬቱን የያዘው፤ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ እስካሁን ድረስ ምንም ሳያመርት፣ ለህብረተሰቡና ለአርሶ አደሩ ምንም መሰረተ ልማት ሳይገነባ ነው የቆየው፡፡ ተፅዕኖ ቢደረግበት ኖሮ ይሄን ያህል ጊዜ አይቆይም ነበር፡፡” ብለዋል፡፡
ባለሃብቱ በትህነግ ጦርነት ወቅት “ትህነግ አፍቃሪ” በሚል በብሄር የተነሳ ከፍተኛ ተፅእኖ ተደርጎብኛል ሲሉ ላቀረቡት ስሞታም ምክትል ከንቲባው ምላሽ ሰጥተዋል፤ “በብሄር ላይ ተንተርሰን ተፅዕኖ ያደረግነው ነገር የለም፣ ሊኖርም አይችልም፣ ህገመንግስታችንም ይሄን አይፈቅድም፤ ይሄ ደግሞ ቢኖርም በሰዓቱ በህግ መብቱን ሊያስከብር ይችላል፡፡ እኔ በነበርኩበት ወቅት ያለብህን እዳ ክፈል ተብሎ ከመጠየቅ ባለፈ ብሄር ተኮር ጥቃት አልተደረገበትም፡፡” በማለት፡፡
ባለሃብቱ ዘመናዊ የመስኖ ቴክኖሎጂን ተጠቅሞ እርሻውን በስፋት በማምረት በአገር ደረጃ ተወዳዳሪ መሆን ሲጠበቅበት ዝናብ ጠብቆ ነበር የሚያመርተው ሲሉ የወቀሱት የወረዳው ዋና አስተዳዳሪ አቶ አዝጌ ካሳዬ፤ ከዚህም ሌላ ባለሃብቱ ፈቃድ ባልወሰደበት ከሰል የማክሰል ስራ ላይ ተሰማርቶ ችግሮችን ሲፈጥር ቆይቷል ብለዋል፡፡

       የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ትላንት ምሽት በአማራ ክልል ያለውን አሳሳቢ የጸጥታ  ሁኔታ በተመለከተ ባወጣው መግለጫ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ወቅትም ሰብአዊ መብቶች ሊከበሩና ለሰላማዊ ውይይት ቅድሚያ ሊሰጥ እንደሚገባ አሳስቧል፤ ኮሚሽኑ ከሚያዝያወር 2015 ዓ.ም ጀምሮ እየተባባሰ የመጣውን የአማራ ክልል የትጥቅ ግጭትና የጸጥታ ችግር እንዲሁም በሰብአዊ መብቶች ላይ ያስከተለውን ተጽዕኖ ሲከታተል መቆየቱንና ይህንኑም አስመልክቶ በነዋሪዎችና በአካባቢው ላይ ያደረሰውንና የሚያደርሰውን ጉዳት ከግምት ውስጥ በማስገባት፤ ለሰላም አማራጮች ቅድሚያ እንዲሰጥ፣ ሲቪልሰዎች ለተጨማሪ ጉዳት እንዳይዳረጉ ጥንቃቄ እንዲደረግ ማሳሰቡ የሚታወስ ነው። ሆኖም የጸጥታ ሁኔታው ከመሻሻል ይልቅ ከሐምሌ ወር 2015 ዓ.ም አጋማሽ ጀምሮ እየተባባሰ በመምጣቱ ብዙ የክልሉ አካባቢዎች በግጭት ውስጥ መሆናቸውን፣ በአንዳንድ አካባቢዎች ሲቪል ሰዎች ላይ ጥቃት መፈጸሙንና ሲቪል ሰዎችና ንብረት ላይ ጉዳት መድረሱን፣ የትራንስፖርትና ሌሎች ማኅበራዊ አገልግሎቶች መቋረጣቸውን፣ በቅርቡም የኢንተርኔት አገልግሎት በብዙ የክልሉ አካባቢዎች መቋረጡን፣ ነዋሪዎች በነጻነት ለመንቀሳቀስና ሥራቸውን ለመከወን መቸገራቸውን እንዲሁም የእንቅስቃሴ ገደቦች በአንዳንድ አካባቢዎች መጣላቸውን ለመገንዘብ መቻሉን ኮሚሽኑ ጠቁሟል።
ግጭቱ ከሌሎች የሀገሪቱ አካባቢዎች በግጭትና በተለያዩም ክንያቶች የተፈናቀሉ፣ እንዲሁም ከጎረቤት ሀገራት ግጭት በመሸሽ የተሰደዱ በክልሉ የሚገኙ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ሰዎችንም (ስደተኞች፣ ጥገኝነት ጠያቂዎች እንዲሁም ፍልሰተኞች) ለከፍተኛ ችግር የሚዳርግ ነው ብሏል- ኢሰመኮ።
ኮሚሽኑ ከሚመለከታቸው የክልሉና የፌዴራል መንግሥት አካላት ጋር መነጋገርን ጨምሮ፣ በክልሉ እያከናወነ ያለውን የሰብአዊ መብቶች ሁኔታ ክትትል፣ እንዲሁም በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ወቅትም በአዋጅ ቁጥር 210/1992 (በአዋጅ ቁጥር 1224/2012 እንደተሻሻለው) አንቀጽ 6(12) መሠረት፣ በተሰጠው ተግባርና ኃላፊነት እንደሚቀጥል አስታውሷል።
ሁሉም ወገኖች ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት ለሰላም አማራጮች ቅድሚያ እንዲሰጡ፣ ግጭቱን ከሚያባብሱ ድርጊቶች እንዲቆጠቡ፣ የክልሉን ሰላምና ደኅንነት ለማረጋገጥ በመንግሥት የሚወሰዱ እርምጃዎች በማናቸውም ሁኔታ ቢሆን ነዋሪዎችን ለበለጠ ጉዳትና ለሰብአዊ መብቶች ጥሰት እንዳይዳርጉ ተገቢው ጥንቃቄ እንዲደረግ ኮሚሽኑ አሳስቧል። በተጨማሪም የሚኒስትሮች ምክር ቤት ሐምሌ 28 ቀን 2015 ዓ.ም ያወጀው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ቁጥር 6/2015 በሕገ-መንግሥቱና ኢትዮጵያ ተቀብላ ባጸደቀቻቸው ዓለም አቀፍ ስምምነቶች ዕውቅና ያገኙሰብአዊ መብቶችንና የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መርሖችን በተለይም የጥብቅ አስፈላጊነት፣ በማናቸውም ሁኔታ የማይገደቡ መብቶችን የመጠበቅ፣ የተመጣጣኝነትና ከመድልዎ ነጻ መሆን መርሖችን ባከበረ መልኩ እንዲተገበር ኢሰመኮ ትላንት ምሽት ባወጣው መግለጫ አሳስቧል።

Page 8 of 665