Administrator

Administrator

“አፍሪካ ታከብራለች” ከጥቅምት 27 እስከ ሕዳር 1 ቀን 2017 ዓ.ም.  በአዲስ አበባ ከተማ ሊካሄድ መሆኑን ተገልጿል። በዚህ መርሐ ግብር ላይ በርካታ ሁነቶች እንደሚከናወኑ አዘጋጆቹ ሐሙስ መስከረም 9 ቀን 2017 ዓ.ም. በተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን (ኢሲኤ) ለጋዜጠኞች በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አመልክተዋል።

ሌጄንደሪ ጎልድ ሊሚትድ እና ማያልዝ ኤቨንትስ ከአፍሪካ ሕብረት እና ከኢሲኤ ጋር በመቀናጀት የሚያዘጋጁት ይህ መርሐ ግብር፣ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ድጋፍ እንደተደረገለት በመግለጫው ተጠቅሷል። በአፍሪካ ሕብረት እና ኢሲኤ አዳራሾች ውስጥ የሚከናወን መርሐ ግብር ሲሆን፣ “በአፍሪካ አሕጉር ያለው ብዝሃነት ውስጥ የሚገኘውን አንድነት ለማሳየት እና የኢኮኖሚ ብልጽግናን በኪነ ጥበብ ስራዎች፣ በባሕል፣ በቅርስ፣ በቴክኖሎጂ እና በንግድ እንቅስቃሴዎች ለማጉላት ታልሞ የተዘጋጀ ነው” ተብሏል።

የዘንድሮው መርሐ ግብር መሪ ቃል “ለ21ኛው ክፍለ ዘመን የሚመጥን አፍሪካዊ አስተምህሮ” እንደሆነ በጋዜጣዊ መግለጫው ተነግሯል። የመክፈቻ ስነ ስርዓቱ ጥቅምት 27 ቀን 2017 ዓ.ም. በአፍሪካ ሕብረት ዋና ጽሕፈት ቤት የሚካሄድ መሆኑን ተገልጿል።

በተከታታይ አራት ቀናት የተለያዩ የውይይት መድረኮች፣ የሙዚቃ ኮንሰርት፣ ኤክስፖ፣ የባሕል እና የሽልማት ምሽቶች እንደሚካሄዱ በዚሁ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ተብራርቷል።

Thursday, 19 September 2024 00:00

ጉርሻና ቅምሻ

በደራሲና ገጣሚ ማትያስ ከተማ የተፃፈዉ "ጉርሻና ቅምሻ" የተሰኘ አዲስ መፅሃፍ የሀገራችን ደራሲዎችና የኪነጥበብ ባለሙያዎች በተገኙበት እሁድ መስከረም 12 ቀን 2017 ዓ.ም ከጠዋቱ 3:00 ጀምሮ በኢትዮጵያ ቤተመዛግብት እና ቤተመጻሕፍት አገልግሎት (ወመዝክር) አዳራሽ ውስጥ ይመረቃል።

ኢትዮ ቴሌኮም ከሼንዜን ግሪንቴክ አርኤፍ ኮሚዩኒኬሽን ሊሚትድ ጋር የውጭ ምንዛሪ አቅርቦትን ያካተተ ስትራቴጂያዊ የአጋርነት መፈጸሙ ተገልጿል። ዛሬ የተፈረመው ይህ ስምምነት በኢትዮጵያ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን እውን ለማድረግ "ያግዛሉ" የተባሉ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን ወደ አገር ውስጥ የሚያስችል መሆኑም ታውቋል።
ዛሬ መስከረም 11 ቀን 2017 ዓ.ም. በኢትዮ ቴሌኮም ዋና ስራ አስፈጻሚ ፍሬሕይወት ታምሩ እና በሼንዜን ግሪን ቴክ አር ኤፍ ኮሙዩኒኬሽን ሊሚትድ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ሊዮ ካይ መካከል ስምምነቱ የተፈጸመ ሲሆን፣ ሊዮ ካይ አፍሪካን ሲጎበኙ የመጀመሪያ ጊዜያቸው መሆኑን ገልጸዋል።
ግሪንቴክ በቻይና አስር ግዙፍ ከሆኑ የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች ውስጥ አንዱ ሲሆን የኮሙኒኬሽን እና ዲጂታል ሶሉሽኖችን በማቅረብ አንጋፋ የሆነ ኩባንያ ነው፡፡
ኢትዮ ቴሌኮም የ2017 በጀት አመት ዕቅዱን ይፋ ባደረገበት ዕለት ዋና ስራ አስፈጻሚዋ በዘርፉ የተሰማሩ ከአገር ውስጥ እና ከሀገር ውጪ የሚገኙ አጋሮች አብረው እንደሚሰሩ መግለጻቸው ይታወሳል፡፡

• የእነ ደብረጽዮን ህወሓት ጊዜያዊ አስተዳደሩን እያደናቀፉት ነው
                    • ህወሓት የራሱን ህገ ደንብና የአገሪቱን ህግ ጥሷል
                    • ትግራይ አሁን በሁሉም ዓይነት ቀውስ ውስጥ ናት
                    • ስብሰባዎቹ ድጋፍ ማጠናከሪያ እንጂ ሌላ ፋይዳ የላቸው

        ከህወሓት አንጋፋ ታጋዮች አንዱ ናቸው፤ አቶ ገብሩ አስራት። የትግራይ ክልል ፕሬዚዳንት በመሆን ያገለገሉት አቶ ገብሩ፤ከ1993 ዓ.ም. የህወሓት ክፍፍል ወዲህ ደግሞ ወደ ተቃውሞ ጎራ በመቀላቀል አረና ትግራይ የተባለ ፓርቲ መስርተው 15 ዓመታት ያህል በአመራርነት ተሳትፈዋል፡፡ ህወሓት በ93 ዓ.ም ክፍፍል ወቅት እሳቸውን ጨምሮ በርካታ አመራሮችን ከህግ ውጭ ማባረሩን የሚያስታውሱት አቶ ገብሩ፤ አሁንም የዚያኑ ግልባጭ ነው ያደረገው ይላሉ፤ ከሰሞኑ የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዚዳንት አቶ ጌታቸው ረዳን ጨምሮ በ16 የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት ላይ የወሰደው እርምጃ ህገወጥ መሆኑን በመግለጽ፡፡
የትግራይ  ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር የአመሰራረት ችግር እንደነበረበት የሚገልጹት ፖለቲከኛው፤ ሥራ አስፈጻሚውን የሚቆጣጠር ም/ቤት ወይም አካል እንደሌለ ይናገራሉ፡፡ የጊዜያዊ አስተዳደር አወቃቀር አካታችነት እንደሚጎድለውም ይገልጻሉ፡፡ በተፋጠጡት የህወሓት ቡድኖች መካከል አንዳችም የርዕዮተ ዓለም ልዩነት እንደሌለ በመጠቆምም፣ የሚያሻኩታቸው የሥልጣን ጉዳይ  ብቻ ነው ይላሉ፡፡
 አቶ ገብሩ አሥራት ከአዲስ አድማስ ጋር ባደረጉት ሰፊ ቃለ መጠይቅ የጊዜያዊ አስተዳደሩን ድክመቶችና ተግዳሮቶች ያብራራሉ፡፡ ከመንግሥት ውጭ ያለው በዶ/ር ደብረጽዮን የሚመራው የህይወት ቡድን እንዴት ጊዜያዊ አስተዳደሩን አላሰራ ብሎ እንቅፋት እንደሆነበትም ይገልጻሉ፡፡ ህወሓት የራሱን ህገ ደንብና የአገሪቱን ህጎች በመጣስ ህገወጥ ጉባኤ ማካሄዱን፣ 16 የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላትንም በህገወጥ መንገድ  ከፓርቲው ማገዱን ይናገራሉ፡፡ ህወሓቶች ከሻዕቢያ ጋር መሞዳሞድ መጀመራቸው ለትግራይም ለአገርም አደጋ መሆኑን ሳይጠቅሱ አላለፉም፡፡ በትግራይም ብቻ ሳይወሰኑ በሌሎች የአገሪቱ አካባቢዎች የሚካሄደው ጦርነት በፖለቲካዊ መፍትሄ መቋጨት ካልተቻለ፣ እንደ አገር እየተዳከምን በመሄድ፣ እንደ ግብጽ ላሉ ውድቀታችንን ለሚመኙ አገራት እንጋለጣለን ሲሉ ስጋታቸውን ይገልጻሉ፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ  ሚኪያስ ጥላሁን ከአንጋፋው ፖለቲከኛ አቶ ገብሩ አሥራት ጋር ያደረገው ቃለ ምልልስ እንዲህ ተጠናቅሮ ቀርቧል፡፡


          የትግራይ ወቅታዊ የፖለቲካ ሁኔታን በቅርበት እንደሚከታተል አንጋፋ ፖለቲከኛ፣ የክልሉ  ጊዜያዊ አስተዳደር ከተቋቋመበት ጊዜ አንስቶ ያለውን የስራ እንቅስቃሴ እንዴት ይገመግሙታል?
 እኛ እንግዲህ የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር፣ ከአመሰራረቱ ጀምሮ ችግር አለበት ብለን ነው የምናምነው። መጀመሪያ ሲቋቋም ከመርሁና ከአመሰራረቱ ጀምሮ፣ ችግር ያለበት ሆኖ ነው የሚታየኝ። ይኸውም ምንድን ነው? በማዕከላዊ መንግሥትና በህወሓት ስምምነት የተፈጠረ አስተዳደር ነው። ነገር  ግን በፕሪቶሪያው ስምምነት፣ ሁሉን-አካታች ጊዜያዊ አስተዳደር ይቋቋማል ነበር የተባለው፡፡ በመጨረሻ የተመሰረተው ግን የህወሓት አስተዳደር ነው። ፓርቲዎችንና ሌሎች የማሕበረሰብ ክፍሎችን አላሳተፈም። አካታች አልነበረም። ስለዚህ ችግር አለበት። ሌላ ደግሞ፣ በአስተዳደሩ ውስጥ ሥራ አስፈጻሚ እንጂ፣ ሥራ አስፈጻሚውን የሚቆጣጠር ሌላ አካል የለም። እንደ ምክር ቤትም ሆኖ፣ ይህን የሚቆጣጠር የለም። ስለዚህ ሥራ አስፈጻሚው ብቻውን ነው እያስተዳደረ ያለው፤ እርሱን የሚቆጣጠር ምክር ቤትም ሆነ ሌላ አካል የለም። እና፣ ከጅምሩ ችግር ያለበት ሆኖ ይታየኛል። ይህም ሆኖ ሌላው ትልቁ ችግር ደግሞ በመንግሥት በኩል ባሉ የህወሓት አባላትና ከመንግስት ውጭ ባሉት የህወሓት አባላት ወይም አመራሮች መካከል የተፈጠረው ግጭት ነው፡፡ ይሄ ሽኩቻ ጊዜያዊ አስተዳደሩን  ምንም እንዳይሰራና እንዳይላወስ አድርጎታል። በወረዳና በቀበሌ ያሉ ምክር ቤቶችንና ካድሬዎችን ከመንግሥት ውጪ ያለው አካል ነው የተቆጣጠረው፤እነ ደብረጽዮን ማለት ነው፡፡ መንግሥቱን ደግሞ እነ ጌታቸው ተቆጣጥረውታል። ስለዚህ ጭራሽ ሊያሰሯቸው አልቻሉም። እንግዲህ ጊዜያዊ አስተዳደሩ ከተቋቋመ ሁለት ዓመት ይሆነዋል። ግን ይህ ነው የሚባል አመርቂ ስራ እስካሁን አልሰራም፡፡ እንዲያውም አሁን የስልጣን ሽኩቻው ከፍተኛ ደረጃ ላይ ስለደረሰ፣ ህዝቡ ተፈላጊውን የመንግሥት አገልግሎት እያገኘ አይደለም፡፡ እንዲያውም የጨነገፈ ዓይነት መንግስት ሆኖ ወሮበሎች፣ የጦር አበጋዞችና ካድሬዎች እንደ ልባቸው የሚቆጣጠሩት የወንጀል ማዕከል ሆኗል፤ ትግራይ። የወንጀለኞች መናኸርያ  ነው የሆነው።
ሥራ አስፈጻሚውን የሚቆጣጠር ምክር ቤትም ሆነ ሌላ  አካል የሌለው ለምን ይመስልዎታል?
እኔ የሚመስለኝ ከአቋቋሙ ጀምሮ ያለው ችግር ነው። ሲቋቋም፣ ሥራ አስፈጻሚ ብቻ እንጂ እርሱን የሚቆጣጠር ሌላ አካል እንዲቋቋም አልፈለጉም። ኋላ ቆይቶ ግን ጊዜያዊ አስተዳደሩ ይህ ነገር እንደሚያስፈልግ ተገንዝቦ ሊያቋቁም ሞክሮ ነበር። “የአማካሪ ካውንስል” የሚባል ሊያቋቁም ሞከረና ህወሓት ሳይቀበለው ቀረ፡፡ ህወሓት፤ “ይሄ ነገር እኔን ከጨዋታ ውጪ የሚያደርግ ነው” ብሎ ስላሰበ፣ ካውንስሉ እንዳይቋቋም አጥብቆ  ነው የተቃወመው፡፡ ስለዚህ ይህ የአማካሪ ካውንስል ወይም ተቆጣጣሪ አካል እንዳይኖር አሁን ዋናው ደንቃራ፣ የእነ ደብረጽዮን ህወሓት ነው። እንግዲህ በደንብ ደረጃ  እንዲቋቋም እነ ጌታቸው ደንብ ካወጡ ወራትን አስቆጥሯል። ሆኖም ሌላው ቡድን ስለተቃወመው እስካሁን ድረስ ሳይቋቋም ቀርቷል። ሥራ አስፈጻሚው የሚሰራው ሥራ በማን ነው የሚጠየቀው? የሚያወጣው ገንዘብ፣ የሚመድበው በጀት በትክክል ስራ ላይ ውሏል ወይ? የሚለውን ማን ይቆጣጠረዋል? የሚሰራቸውን ሥራዎች፣ ዕቅዶች--ተግባራዊ መሆናቸውን ማነው የሚቆጣጠረው? ተቆጣጣሪ በሌለበት እንዳሻው ነው የሚሄደው ማለት ነው። እናም፣ ጊዜያዊ አስተዳደሩ ከአቋቋሙ ጀምሮ ችግር ያለበት ሆኖ ይታየኛል።
የአካታችነት ጉዳይን በተመለከተ አንዳንድ “ጊዜያዊ አስተዳደሩ አካታች ነው” ብለው የሚያምኑ ወገኖች፣ “በሚመሰረትበት ወቅት ከምሁራን፣ ከተዋጊዎችና ከተቃዋሚ ፓርቲዎች የተወሰኑ አካላት ወደ ጊዜያዊ አስተዳደሩ እንዲገቡ ተደርገዋል።” ብለው ይሞግታሉ፡፡ እርስዎ በዚህ ላይ ምን ይላሉ?
እንግዲህ  ተቃዋሚ ፓርቲዎች...የራሳቸው የሆነ ደጋፊ ማሕበረሰብ አላቸው። ፓርቲው ሲወከል እርሱ የሚወክለው ማሕበረሰብ ይወከላል ማለት ነው፡፡ ነገር ግን እነዚህ ፓርቲዎች ከአንድ ፓርቲ በስተቀር አልተሳተፉም፤ ባይቶና ከሚባለው ፓርቲ ውጪ። እርሱም እንደገና ተቃውሞ ተቆርጦ የቀረ እንጂ ፓርቲዎችን አላካተተም። ከጅምሩ ህወሓት ከፓርቲዎችም ጋር አልተስማማም። እርሱ እንደሚፈልገው ነው የቀየሰው እንጂ ፓርቲዎች እንዲሳተፉበትና እንዲነጋገሩበት አላደረገም። እናም፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች እዚህ ላይ አልተሳተፉም። ሁለተኛ፣ የማሕበረሰብ አካላት የሚባሉትም ቢሆኑ፣ የተሳተፉ እኮ የሉም። GSTS የሚባል የትግራይ ምሁራን ስብስብን ወክያለሁ ብሏል። ከዚህ ውጭ ሌላ የተሳተፈም የለም። እንግዲህ ዋናዎቹ ተሳታፊዎች TDF ወይም ሰራዊቱ እና ህወሓት ናቸው ማለት ነው። ሰራዊቱም እንደምናየው የህወሓት ደጋፊ ነው። ስለዚህ ጠቅላላውን ስታየው፣ የህወሓት ነው እንጂ ሌሎቹን ያላካተተ ነው። በማሕበረሰብ ደረጃም አላካተተም። በፓርቲዎች ደረጃም አላካተተም።
ወደ ሁለት ዓመት ገደማ ያስቆጠረው ጊዜያዊ አስተዳደሩ፣ የራሱን የቤት ስራዎች አልሰራም በሚል የሚወቅሱት ወገኖች አሉ። ለምሳሌ፦ ተፈናቃዮችን ወደ ቀድሞ ቀያቸው ከመመለስ፣ ሰብዓዊ ዕርዳታ እንዲዳረስ ከማድረግ እንዲሁም ጸጥታ ከማስፈንና ወንጀልን ከመቀነስ አንጻር በቂ ሥራ አላከናወነም ይላሉ፡፡ እርስዎ ከመንግሥት ውጭ ያሉት የህወሓት ቡድን፣ ጊዜያዊ አስተዳደሩ እኒህን ሃላፊነቶቹን እንዳይወጣ እንቅፋት ሆኗል ብለው ያምናሉ?
 ጊዜያዊ አስተዳደሩ ወደፊት እንዳይራመድ የሚያደርጉ ሁለት ሃይሎች አሉ። አንዱ ማዕከላዊ መንግሥት ነው። ተፈናቃዮችን የመመለስ ጉዳይ፣ የነበረውን አስተዳደር ወደ ቀድሞው ሁኔታ የመመለስና የመሳሰሉ ሥራዎች በዋነኛነት ማዕከላዊ መንግስት መፈጸም ያለበት ነው። ተፈናቃዮች ቶሎ ወደ ቦታቸው እንዲመለሱ፣ ሰራዊቱም ቶሎ ትጥቅ እንዲፈታና እንዲቋቋም፣ አስተዳደሩም ቶሎ ወደነበረበት እንዲመለስ የሚል ስምምነት አለ። እኔ እንደሚመስለኝ፣ በዚህ በኩል ተጠያቂው ማዕከላዊ መንግሥት ነው። ማዕከላዊ መንግሥት ፈቃደኛ አይደለም። ይህ ነገር እንግዲህ በጊዜያዊ አስተዳደሩ አቅም የሚሰራ አይደለም። ማዕከላዊ መንግሥቱ በጣም ብዙ ገንዘብ ከዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ ማሰባሰብ አለበት። ምክንያቱም ውድመቱ በጣም ከፍተኛ ነው። የተፈናቀለው በሚሊዮኖች የሚቆጠር ነው። ሰራዊቱም ብዛት አለው። እነዚህን ለማቋቋም ብዙ ገንዘብ ያስፈልጋል። ከዚህ አንጻር ብዙ እንቅስቃሴ አይታይም፡፡ በዚህ በኩል ጊዜያዊ አስተዳደሩን አንወቅስም። ለዚህ ተጠያቂው ማዕከላዊ መንግስት ይመስለኛል።
 በሁለተኛ ደረጃ የሚከሰሰው ህወሓት ነው። “ስልጣን እኔ ካልያዝኩ በስተቀር እነ ጌታቸውን ማደናቀፍ አለብኝ” ብሎ ከጅምሩ፣ “እነዚህ የብልጽግና ሰዎች ናቸው፣ እነዚህ የሲአይኤ ሰዎች ናቸው፣ እኛን አይወክሉም” እያለ ምንም ዓይነት ሥራ እንዳይሰራ ያደረገው የደብረጽዮን የሕወሓት ቡድን ነው። ይህም ሆኖ ግን ጊዜያዊ አስተዳደሩም ቢሆን፣ ሊሰራቸው የሚችላቸው ለሕዝብ ግልጽ የሆኑ ሥራዎች እኔ አላየሁም። በዕቅድ የሚታወቁ “ይህን እፈጽማለሁ” ብሎ ሕዝብ የሚያውቃቸው፣ ሕዝቡን አሳትፎ የሚሄድበት መንገድ ስለሌለ፣ እርሱም ተጠያቂ ነው። ሦስቱም በየራሳቸው መንገድ ተጠያቂዎች ናቸው።
የጊዜያዊ አስተዳደሩ ከፍተኛ አመራሮች በተለያዩ የትግራይ አካባቢዎች ሕዝባዊ ስብሰባ እያደረጉ ነው፡፡ በእርስዎ ዕይታ እነዚህ ሕዝባዊ ስብሰባዎች መፍትሄ ያመጣሉ?
እኔ ሳየው፣ ስብሰባዎች ምንም ማለት አይደሉም። ነገሮች መፍትሔ የሚያገኙት በስብሰባ አይደለም። የተቀናጀ ዕቅድ ይዞ፣ የተቀናጀ ስትራቴጂ ወይም ደግሞ የተቀናጀ ፍኖተ ካርታ ይዞ መሥራት ነው እንጂ በስብሰባ የሚፈታ ነገር ብዙም አይደለም። ስብሰባ ወይ የፕሮፓጋንዳ ነው፣ ወይም ደግሞ ዕቅዶችን የማሳወቅ ጉዳይ ነው። አሁን ህወሓት ለሁለት ተሰንጥቆ በተካረረበት ጊዜ ስብሰባዎቹ ድጋፍ የማግኘት ጉዳይ ወይም ድጋፍን የማጠናከር ነገር ካልሆነ በስተቀር ሌላ ፋይዳ የላቸውም። ዋናው ነገር ግን ሕዝቡ ፍላጎቱን አሳይቷል። ከእንግዲህ ወዲህ ህወሓት እንደማይጠቅመው፣ ላለፉት ዓመታት እንደጨቆነው በድፍረት የገለጸበት አጋጣሚ ነው፡፡ ህወሓት ሁሉንም ዓይነት ኋላቀር አስተሳሰቦችን የያዘና ለሕዝቡ ጭራሽ የማይፈይድ ድርጅት እንደሆነ ወጣቱ ያሳየበት ሁኔታ ነው የተስተዋለው። እኔ በሦስቱም ስብሰባዎች እንደተመለከትኩት ማለት ነው።  ከዚያ የበለጠ ፋይዳ ግን  ያለው አይመስለኝም።
ባለፈው እሁድ ጊዜያዊ አስተዳደሩ በሽረ ከተማ የጠራው ሕዝባዊ ስብሰባ በተቃውሞ እንዲቋረጥ ተደርጓል፡፡ መንግሥት የጠራውን ስብሰባ የማቋረጥ አቅም ያለው ቡድን አለ ማለት ነው?
የስብሰባው መቋረጥ እንግዲህ የህወሓት ሥራ ነው። የሕዝብ ሥራ አይደለም። ህወሓት የትግራይን ሕዝብ በልማት ቡድኖች እና “አንድ ለአምስት” በሚል ጠፍሮ የያዘበት ሁኔታ ነው ያለው። እነዚህ ባልፈረሱበት ወይም ባልተዳከሙበት ሁኔታ፣ መንግሥትን ይቃወምበታል፤ ተቃዋሚዎችን ይቃወምበታል። ይቃወሙኛል የሚላቸውን ሃይሎች በእነዚህ በኩል ነው የሚደፍቀው። እነዚህ የልማት ቡድኖችና “አንድ ለአምስት” የሚባሉት እስካልፈረሱ ድረስ፣ የትግራይ ሕዝብ ምንጊዜም ቢሆን ነጻነት ይኖረዋል ብዬ አላስብም። ወጣቱም፣ ሕዝቡም መገንዘብ ያለበት፣ ይህ ጊዜያዊ መንግሥት ቢቀበሉትም፣ ባይቀበሉትም መንግሥት ነው። መስማት ማዳመጥ ነበረባቸው። ህወሓት በስብሰባው ውስጥ የራሱን ቡድን አደራጅቶና አስገብቶ ማፍረሱ ለእኔ አዲስ ነገር አይደለም። እኔ የአረና ፓርቲ አባል ነበርኩ። ባለፉት 15 ዓመታት ባካሄድናቸው ስብሰባዎች ካድሬዎችን፣ ወሮበሎችንና የተለያዩ የልማት ቡድኖችን በማሰለፍ፣ በእኛ ላይ የስድብ ውርጅብኝ፣ ለድብድብ መቃጣት፣ ስብሰባን ማፍረስና ሕዝቡ ወደ ስብሰባ አዳራሽ እንዳይገባ ማስፈራራት የህወሓት ባሕርይ ነው።  እርሱን የሚቃወም ወይም የማይደግፍ ካለ፣ ወይ ያፈርሰዋል፤ ወይ ይቃወመዋል፤ ወይም እስከ መግደል ድረስ ይሄዳል። በሽረ የተፈጸመው ድርጊት የህወሓትን ባሕርይ ፍንትው አድርጎ ያሳየ እንጂ ሌላ አዲስ ነገር የለውም።
ህወሓት ባለፈው ባካሄደውና በምርጫ ቦርድ ዕውቅና ባልተሰጠው ጉባኤ ላይ ያልተሳተፉ አመራሮቹን ከድርጅቱ ማባረሩን አስታውቋል። እነዚህ አመራሮች የተባረሩበት ሁኔታ እርስዎና ሌሎች ከፍተኛ አመራሮች ከተባረሩበት ከ1993ቱ ክፍፍል ጋር  የሚመሳሰል እርምጃ ነው ማለት ይቻላል?
በትክክል ይመሳሰላል። ህወሓት በሕጋዊ መንገድ አይደለም የሚሰራው። በራሱና በአገሪቱ ሕግ የማይገዛ መሆኑን ያመላከተበት ተግባር ነው። አሁን ስታየው ጉባኤው ራሱ ምርጫ ቦርድ ያልተቀበለው ነው። በኢትዮጵያ ሕግ መሰረት፣ ማንኛውም ጉባኤ ምርጫ ቦርድ የታዘበውና ዲሞክራሲያዊና ሕጋዊ ነው ብሎ የመሰከረለት ካልሆነ በስተቀር፣ በሕግ ደረጃ  ተቀባይነት የለውም። ህወሓት ደግሞ የአገሪቱን ሕጎች፣ ተቋማትና ሕገ መንግስቱን ተቀብያለሁ በማለት በፕሪቶሪያ የፈረመውን ስምምነት እያፈረሰው ነው፤ አፍርሶታልም። የራሱን ሕገ ደንብ አላከበረም። ቁጥጥር ኮሚሽኑ ተቃውሞታል። 16 ያህል የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት ተቃውመውታል። ስለዚህ ይህ ጉባኤ ምንም ተቀባይነት የለውም። በእኛም ጊዜ የሆነው ይህ ነው። በርግጥ፣ ጉባኤ ላይ አልደረስንም። ማዕከላዊ ኮሚቴው ግን ሕገ ደንቡ በማይፈቅደው መንገድ ነው እኛንም ያባረረው። አሰራሩ በኔትዎርክ የታጠረ ነው። ውስጥ ውስጡን ነው የሚሄደው። እኔ ደጋግሜ እንደምለው ይህ ስብሰባ እንጂ ጉባዔ አይደለም። በዚህ መንገድ ሌሎች የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላትን ማባረር፣ ሕጋዊ ዕውቅና የሌለው ነው።
የአሁኑ የህወሓት ክፍፍል ዋነኛ መንስዔ ምን ይመስልዎታል?
እዚህ ላይ ማየት ያለብን ዋናው ነገር፣ በሁለቱም ቡድኖች መካከል ያለው ግልጽ የሆነ የስልጣን ሽኩቻ ነው። በአብዛኛው በመንግስት በኩል ያለው የህወሓት አመራርና ከመንግስት ውጭ የሆነውና ስልጣን የቋመጠው የህወሓት ቡድን መካከል ያለው ፍጥጫና ቅራኔ ነው እንጂ ሌላ የሃሳብ ልዩነት አላየሁም። ምክንያቱም በእነ ጌታቸው ወይም በአስራ ስድስቱ የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት በኩል ከእነዚህ የተለየ የርዕዮተ ዓለም ልዩነት ሲፈነጥቁ አላስተዋልኩም። እነ ደብረጽዮን በግልጽ አብዮታዊ ዴሞክራሲ ወይም ልማታዊ መንግሥት የሚሉትን ለውድቀት የዳረጋቸውን ርዕዮተ ዓለም ተከትለው ለመሄድ ነው የተስማሙት። ስለዚህ በጉባኤ የመጣ አዲስ ነገር የለም። ከጉባኤ በፊት የታዩ የርዕዮተ ዓለም ለውጦችም የሉም። እንዲያውም ምንም ዓይነት ለውጥ እንደማይኖር ነው በግልጽ ያወጁት። በዚህም በኩል ያየሁት የርዕዮተ ዓለም ልዩነት የለም። ያም ሆኖ ግን በአንዳንድ ጉዳዮች ያነሷቸው ነጥቦች አሉ። የአጀንዳ ጉዳዮች ናቸው፡፡ ለምሳሌ፦ “ጦርነቱን እንገምግም” ብለዋል። ትክክለኛ ሃሳብ ነው። አንዳንዶቹ “ይህ ታሪክ ነው፣ የወደፊቱን እንመልከት” ይላሉ፡፡ ግን ትክክል አይደለም። በትግራይ ሕዝብ ከደረሰው እልቂትና ውድመት አንጻር ስንመለከተው፣ ጦርነቱ የታሪክ ጉዳይ አይደለም። አሁንም ያለ ጉዳይ ነው። በዚያ በኩል የተፈጠረው ችግር ሳይታይ፣ መቀጠል ስሕተት ይመስለኛል። በሌላ አገር ቢሆን፣ እነዚህ መሪዎች ይቅርታ መጠየቅ ብቻ ሳይሆን፣ በሕግም ጭምር መጠየቅ ያለባቸው ናቸው። እንጂ በመደበኛ ሁኔታ ውስጥ ለመቀጠል ሞራል ያላቸው አይመስለኝም። “ምንም እንዳልተፈጠረ እንቀጥላለን” የሚሉት ነገር ትክክል ሆኖ አይሰማኝም። ስለዚህ ይህ የወጣው አንደኛው ቡድን፣ “ይህ ነገር እንደገና እንዳይደገም እንደ አጀንዳ እንየው” ብለዋል። ሌሎቹ ደግሞ፣ ይህንን ማየት አይፈልጉም። ምክንያቱም ያስጠይቀናል ብለው ስለሚሰጉ፣ አለባብሰው መሄድ ይፈልጋሉ። ቅድም ካነሳኸው የ93ቱ ክፍፍል ጋር የሚመሳሰል ትይዩ አጋጣሚ ነው። 93 ላይ “የኢትዮ-ኤርትራን ጦርነት እንገምግም” ስንል፣ “ችግራችን ይህ አይደለም፣ ቦናፓርቲዝም እና መበስበስ ነው ችግራችን” ብሎ፣ ያኔ መለስ የሌለ አጀንዳ ነበር የፈጠረው። እነዚህም ዋናውና ሕዝቡን የሚመለከተው፣ ለዚህ ሁሉ ዕልቂት የዳረገውን ጉዳይ ትተው ሌላ አጀንዳ አስቀምጠዋል። ምንም ሳይለወጥ፣ እንደ ድሮው አቋም ወስደዋል። ስለዚህ የእነ ጌታቸው ቡድን በአንድ በኩል፣ “ይህንን ጉዳይ እናንሳ” ብሏል። ሌላው ደግሞ ትንሽ ፍንጭ የሚሰጠው “መንግሥት እና ፓርቲ መለያየት አለባቸው” የሚለው ነጥብ ነው። በእነዚህ ሁለት አጀንዳዎች ሁለቱ ቡድኖች ይለያያሉ። አጠቃላይ ለውጥን በተመለከተ ግን በፖለቲካ አቅጣጫቸው በኩል ያየሁት ልዩነት የለም።
በህወሓት ውስጥ ከኤርትራ መንግስት ባለስልጣናት ጋር ግንኙነት የፈጠረ ወይም ለመፍጠር ዝግጁ የሆነ ቡድን አለ የሚሉ ወገኖች አሉ። በእርግጥም ከኤርትራ መንግስት ባለስልጣናት ጋር ግንኙነት ስለመፍጠሩ የሚያሳይ ማስረጃ አለ?
 እኔ ከሦስት ሳምንታት በፊት ከተለያዩ ሚዲያዎች ጋር ባደረግኋቸው ቃለ መጠይቆች ከሻዕቢያ ጋር እንደሚገናኙ በግልጽ አስቀምጫለሁ። ምክንያቱም መረጃው አለኝ። የታወቀ ነው። “ህወሓቶች ከሻዕቢያ ጋር እየተገናኙ ነው” ብዬ ስናገር፣ የእነርሱ ደጋፊ የሆኑ ሚዲያዎችና ካድሬዎች በጣም ነው የጮኹብኝ። “ምን ማስረጃ አለህ? ከየት አመጣኸው?” ብለው ተችተውኛል። በቅርቡ እንደተሰማው፣ ደብረጽዮን “ከሻዕቢያ ጋር ግንኙነት እንፍጠር ብለን ወስነናል” ብሎ ወጥቶ ተናግሯል። በሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ደረጃ ነው የወሰኑት። የመጀመሪያው ግንኙነት ዱባይ ላይ በጌታቸው ረዳ አማካይነት “ከሻዕቢያ ጋር ተገናኝተናል” ብለዋል። ይህ ከሚዲያ የሚደበቅ ነገር አይደለም። አሁንም እየቀጠሉ ነው። ግብጾችም ይህን ይፈልጉታል። ሻዕቢያም ይፈልገዋል። ህወሓትም ይህን ይፈልጉታል። እንግዲህ ለዚህ ግንኙነት ምክንያት ሲያስቀምጡ፣ “ሰላም ስለፈለግን ነው” ይላሉ። ሻዕቢያ በትግራይ ውስጥ እስከ ጄኖሳይድ የሚደርስ ከፍተኛ ወንጀል የፈጸመና አሁንም የትግራይን ብሎም የኢትዮጵያን መሬት ተቆጣጥሮ ያለ ሲሆን፤በትግራይ ላይ ከፍተኛ ውድመት ከፈጸመ ድርጅት ጋር ተጠያቂነት ሳይኖር “ግንኙነት እንፍጠር” ማለት የራሳቸውን ስልጣን ለማስጠበቅ እንጂ ለሕዝቡ ደንታ እንደሌላቸው ያሳዩበት ነው። ጌታቸው ከባለስልጣናቱ ጋር የተገናኘው በእነርሱ ውሳኔ ነው። ግን ዋናው ቁም ነገር ጌታቸው “ይህ ነገር ወደ ጦርነት ስለሚወስደን ማድረግ የለብንም” እንዳለና እነርሱ ደግሞ በያዙት አቋም ለመቀጠል፣ ብሎም ከእነርሱ ጋር ሆነው በማዕከላዊ መንግሥት ላይ ጫና ለመፍጠርና ራሳቸውን ከተጠያቂነት ለማዳን ከሻዕቢያ ጋር እንደተሞዳሞዱ፣ ከእርሱም ጋር ዝምድና እንደመሰረቱ ራሳቸው ተናግረውታል። ያለሃፍረት ነው የተናገሩት።
ከሰሞኑ ደግሞ ግብጽ፣ ኤርትራና ህወሓትን ለማሸማገል ስላላት ፍላጎት በተለያዩ መገናኛ ብዙኃን ተዘግቧል። ይህን ፍላጎት ሰፋ አድርገን ካየነው፣ ጉዳዩ ቀጣናዊ መልክ እየያዘ እየመጣ ነው ብንል አያስኬደንም?
አዎ፣ ነው። እንግዲህ በአካባቢው የግብጾች ፍላጎት የታወቀ ነው። ኢትዮጵያን አዳክመው በዓባይ ወንዝ ላይ ያላት ተጽዕኖ እንዲቀንስ፣ የዓባይን ውሃ እንዳትጠቀምና እንዳትቆጣጠር የማድረግ በርካታ ዓመታትን ያስቆጠረ ፖሊሲ አላቸው። በ19ኛው ክፍለዘመን ጦርነት አድርገዋል። ኤርትራ የኢትዮጵያ አካል እያለች በጉራዕ እና በጉንደት ከአጼ ዮሐንስ ጋር ያደረጉት ጦርነት አለ። እስከ 1885 ዓ.ም. ድረስ ሐረርን ተቆጣጥረው ነበር። ኢትዮጵያን በቀጥታ የመቆጣጠር ፍላጎታቸው መክኗል፤ አልቻሉም። በሁሉም በኩል ተሸንፈው ነው የወጡት። ከዚያ በኋላ ግን የውክልና ጦርነት በማድረግ ነው የቀጠሉት። በሶማሊያ በኩል፣ እንዲሁም የኤርትራ ድርጅቶችን በመደገፍ ኢትዮጵያን የማዳከም፣ ጦርነትና ብጥብጥ ውስጥ ቆይታ ስለ ልማት እንዳታስብ፣ ወንዞቿን እንዳትጠቀም የሚያደርገው ሂደት የቆዩበትና የሚቀጥሉበት ነው። አሁን ደግሞ እንደ 1969 ዓ.ም. ሁሉ፣ ኢትዮጵያን ያዩበት አተያይ አለ። ኢትዮጵያ አሁን “እየፈራረሰች ነው” የሚል ግምገማ አላቸው። በተወሰነ መጠን ትክክል ነው። የዚያን ወቅት ዓይነት ተመሳሳይ ሁኔታ ተፈጥሯል። ከትግራይ ጋር የተደረገው ጦርነት በውል አልተቋጨም። በአማራ ክልል ያለውን ጦርነት እናውቀዋለን። በኦሮሚያ ውስጥ ያለውንም እናውቀዋለን። ስለዚህ እነዚህን ነገሮች አገጣጥመው ከ’69 ዓ.ም. ሁኔታ ጋር አመሳስለውታል። አሁን ከሱዳንም ይሁን ከሶማሊያ ጋር ተባብረው፣ ግብጾች በአካል ወደ ድንበሮቻችን እየተጠጉ ያሉበት ሁኔታ ነው ያለው። በሰሜን በኩል ደግሞ መሳሪያቸው የሆነው ሻዕቢያ -- የዓረብ ሊግ ታዛቢ አባል ነው -- ኢትዮጵያ ወደ ቀይ ባሕር እንዳትጠጋና ዓባይን እንዳትጠቀም እያደረገ ነው። እዚህ ላይ የሚገርመኝ የህወሓቶች ነገር ነው። እንግዲህ ይህ የህወሓቶች አካሄድ የዓባይን ተፋሰስ ማለትም ተከዜንም፣ ባሮንም እንዲሁም ሌሎቹን ወንዞች እንዳናለማ የሚያደርግ ነው። አጼ ዮሐንስ ይህን ተገንዝበው ነው የተዋጉት። የአሁኖቹ ህወሓቶች ግን ከግብጽና ከኤርትራ ጋር ለመስራት እየቋመጡ ያሉት ለራሳቸው ስልጣን ሳይሆን፣ እንዲያው ከስትራቴጂ ጥቅም አንጻር ነገሩን አልተመለከቱትም። ግብጾች ወደዚህ ከተጠጉ፣ እኛ ተከዜን፣ በአጠቃላይ ተፋሰሱን መጠቀም አንችልም። ስለዚህ ለሌላ አገር አሳልፎ የመስጠትና ተወካይ ሆኖ በውክልና ጦርነት ለመሳተፍ ወደ ኋላ አይሉም፤ እኔ እንደተመለክትኩት። ከሻዕቢያ ጋር ለመተባበር ከፈቀዱ እዚያው ላይ ከግብጽ ጋር የማይተባበሩበት ምክንያት የለም፤ ለስልጣናቸው ሲሉ፣ ከስትራቴጂ አንጻር ጥቅማቸውን የሚጎዳ ነገር ሁሉ ሊያደርጉ ስለሚችሉ። የሰሜኑ ሻዕቢያ የታወቀ ነው። በግልጽ ኢትዮጵያን ለማዳከም ከግብጾች ጋር እየተሰለፈ ነው። ህወሓት ከሻዕቢያ ጋር ዝምድና እንደፈጠረ ራሱ ነግሮናል። በተዘዋዋሪ ከግብጽ ጋር ሊገናኝ ነው ማለት ነው። ይህ ነገር ኢትዮጵያን በምስራቅም፣ በሰሜንም ለማፈን እየተሰራ ያለ ስራ ነው። በትግራይ አንጻር ስመለከተው፣ የግብጾች ጉዳይ ተከዜንም ሆነ ሌሎች ወንዞችን እንዳንጠቀም ወይም ለመቆጣጠር ካልሆነ በስተቀር፣ ወደዚህ የሚመጡበት ሌላ ምክንያት የላቸውም። አጼ ዮሐንስ መክተው ከመለሷት ግብጽ ጋር  መሞዳሞድና መሥራት ታላቅ ክህደት ነው ብዬ አስባለሁ።
የጊዜያዊ አስተዳደሩና የህወሓት ፍጥጫ በዚሁ ከቀጠለ የትግራይ ፖለቲካዊ ሁኔታ ወዴት ሊያመራ ይችላል ብለው ይገምታሉ?
በጣም አስቸጋሪ ነው። የትግራይም ይሁን የኢትዮጵያ ፖለቲካ ከተበላሸና ከተመሰቃቀለ ከራርሟል፡፡ በእኔ ዕይታ፣ ቀውስ ውስጥ ከገባ ቆይቷል። ዓመታትን አስቆጥሯል። የፖለቲካ ቀውስ አለ፣ የማሕበራዊ ቀውስ አለ፣ የአለመረጋጋት አለ፣ የኢኮኖሚው ቀውስ አለ። በአጠቃላይ ሁሉም ዓይነት ቀውስ ያለበት አገር ነው የሆነው። የትግራይን ሁኔታ ስንመለከት፣ ችግሩ በትግራይ ብቻ ተወስኖ የሚቀር አይደለም። ወደ ሌላም አካባቢ የሚዛመት ነው። በዚያ ታጥሮ አይገደብም። የትግራይን ሕዝብ አስቦ ተፈናቃዮችን እንዳይመልስ፣ አስተዳደሩን መልሶ እንዳያዋቅር፣ የወደመው መሰረተ ልማት እንዳያገግም የሚያደርግ የስልጣን ሽኩቻ ነው። ይህ ነገር በትግራይ ሕዝብ ላይ ከፍተኛ ጫና ይኖረዋል። በህወሓት በኩል ያለው ሽኩቻ እነዚህ ትልልቅ ስራዎች እንዳይሰሩ እንቅፋት የሚፈጥር ነው። በትግራይ ፖለቲካ፣ ኢኮኖሚ፣ ጸጥታ ላይ ተጽዕኖ ይኖረዋል። በግልጽ የምናየው ነገር ነው። ትግራይ አሁን የሁሉም ዓይነት ችግሮች መገለጫ  ሆናለች። የማዕድን ስርቆት፣ የሐብት፣ የመሰረት ልማትና የመሬት ዝርፊያዎች፤ ሕገ ወጥ የሰዎች ዝውውር የሚታዩባት አካባቢ ሆናለች፤ መንግሥት ስለሌለ። ሁሉም መስተካከል የሚችለው መጥፎም ቢሆን መንግሥት ሲኖር ነው። መንግሥትን በሚጎዳ ጭቅጭቅና ቀውስ ላይ ጊዜ ከተወሰደ፣ በትግራይ ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ ይኖረዋል፡፡ በትግራይ ላይ ብቻ ሳይሆን፣ ለኢትዮጵያም የሚተርፍ ቀውስ ነው የሚሆነው።
ሌላው በኢትዮጵያ ያለውን አጠቃላይ ሁኔታ ማየት አለብን። በአማራና ኦሮሚያ ክልሎች ያለው ጦርነት ካልቆመ፣ ኢትዮጵያ ችግር ላይ ነች።  በእኔ ዕይታ፣ የዚህ ሁሉ ምንጭ የፖለቲካ ችግር ነው። ቁጭ ተብሎ በንግግር ፖለቲካዊ መፍትሔ ማግኘት ካልተቻለ በቀር፣ ሌላ መላ  የለውም። ኢትዮጵያ መጠንከር አይደለም ባለችበት ለመቀጠል የሚያስቸግራት ይሆናል። ይህን ያዩት ናቸው ጊዜው አሁን ነው ብለው በተለያዩ አቅጣጫዎች  የሚያሰፈስፉት። በትግራይም ይሁን በአገር አቀፍ ደረጃ የውስጡ ፖለቲካው  መፍትሔ ካላገኘ በቀር -- (መፍትሔ ሲባል የብልጽግና ፓርቲ መፍትሔ ሊያመጣ አይችልም።) በትግራይም ህወሓት ብቻውን መፍትሔ ሊያመጣ አይችልም። ሁሉን ያካተተ እውነተኛ ድርድርና ውይይት ተደርጎ የውስጣችንን ፖለቲካዊ ችግር እስካልፈታን ድረስ፣ ኢትዮጵያ ባለችበት ሁኔታ መቆየት የምትችል አይመስለኝም። የውስጡ እንዳለ ሆኖ፣ የውጭም ተጽዕኖ ተጨምሮበት ከፍተኛ ችግር ላይ ልንወድቅ እንችላለን።


 አንድ የአይሁዶች አፈ-ታሪክ አለ፡፡
አንድ ጊዜ አንድ ትንሽ ልጅ፣ አባቱና አያቱ አብረው ይኖሩ ነበር፡፡ አያትዬው በጣም ከማርጀት-ከመጃጀታቸው የተነሳ ዐይኖቻቸው ወደ አለማየት፣ ጆሮዎቻቸው ወደ አለመስማት፣ እጆቻቸው ወደ አለመጨበጥ በመሸጋገር ላይ ነበሩ፡፡ እያደርም ራሳቸውን ችለው በእግራቸው መቆም ስለማይችሉ የሰው ድጋፍ ይፈልጉ ጀመር፡፡ በተለይም ገበታ ላይ ሲቀመጡ አንዳንዴ፣ የሾርባ ማንኪያ እንኳ በጣታቸው መያዝ ያቅታቸዋል፡፡ ትንሹ ልጅ፣ የአባቱን አባት - አያቱን፣  ለመርዳት ያስባል ግን አቅም አልነበረውም፡፡
የልጁ አባትና እናት ክፉዎች ነበሩ፡፡
ሲያረጁ አይበጁ ነውና አያትዬው መንገድ የሚመራቸው ሰው ሲያጡ አይረዷቸውም፡፡ ጆሮዋቸው ስለማይሰማ አንዴ የተናገሩትን ድገሙልኝ ሲሉ የሚደግምላቸው የለም፡፡ መነሳት ሲያቅታቸው የሚደግፋቸው፣ መራመድ ሲያቅታቸው መንገድ የሚያሻግራቸው አንድም ሰው አጡ፡፡
ታዲያ አንድ የፋሲካ ጊዜ ቤተ-ዘመድ ሁሉ ተጠርቶ ምግቡ ሁሉ ቀርቦ፣ መጠጡ ተሰናድቶ ባለበት ሰዓት አያትዬውም ተጠርተው እንደምንም እየተንገዳገዱ ገበታ ቀረቡ፡፡ ሆኖም እርጅናው በጣም ስለባሰባቸው የተሰጣቸውን የሾርባ ማንኪያ አንስተው፣ ሾርባ ቀድተው ወደ አፋቸው ሲሰድዱት፣ እጃቸው ተንቀጠቀጠና ሾርባውን ካማረው ነጭ የጠረጴዛ ልብስ ላይ አፈሰሱት፡፡ አፋቸውም ሾርባውን በቅጡ ለመሰብሰብ ስላልቻለ ሲዝረከረክባቸው ነጭ ሸሚዛቸው ተበከለ፡፡
ባልና ሚስቱ ቤተ - ዘመድ ፊት እንደተዋረዱ ቆጠሩት፡፡ ስለዚህም ያ ሁሉ ሰው ባለበት ሚስትዬው ባሏን፤
“እኚህን አባትህን አንድ ትላቸው እንደሆነ አንድ በላቸው፡፡ በበኩሌ ከዛሬ ጀምሮ አብረውን ገበታ እንዲቀርቡ ፈቃደኛ አይደለሁም!” አለችና ተመናቅራ ወደ ጓዳ ገባች፡፡
ባልየው ተከትሏት ወደ ጓዳ ይገባና በጣም ያባብላታል፡፡ ከብዙ ልመና በኋላም፣ አባቱ ሁለተኛ ወደ ገበታው እንደማይቀርቡና፣ ይሄንንም አሁኑኑ ቤተ-ዘመድ ባለበት በይፋ እንደሚናገር ቃል ይገባላትና፣ ተመልሳ ወደ ገበታው ለመምጣት ፈቃደኛ ትሆናለች፡፡
’ሴት የላከው ሞት አይፈራም‘ ሆነና አባ-ወራው ተነስቶ አባቱን፣
“ከዛሬ ጀምሮ ከእኛ ጋር ገበታ አትቀርብም፡፡ ለብቻህ ማድቤት ሆነህ እንድትበላ” ሲል አዘዘ፡፡
ከዚህ ጊዜ ወዲህ አያትዬው ማድቤት አንድ ጥግ ላይ ቁጭ ብለው እንዲመገቡ ይፈረድባቸዋል፡፡ ምግቡም የሚቀርብላቸው በአንድ በሸክላ በተሰራ ገበቴ ላይ እንዲሆን ይደረጋል፡፡ ከዚያ የክፋው ደግሞ የምትቀርብላቸው ምግብ ራሱዋ በጣም ጥቂት ትርፍራፊ፣ ሆድ እንኳ በአግባቡ የማትሞላ ሆነች፡፡
አያትዬው ምግብ በቀረበላቸው ቁጥር እንባቸው በአይናቸው ይሞላል፡፡ ምርር ብለው ያዝናሉ፡፡ “ሆድ ይፍጀዋ፣ እስቲ ይሁን!” ይላሉ በረዥሙ ተንፍሰው፡፡
አንድ ቀን በሸክላው ገበቴ ምግብ ተሰጥቷቸው፣ እሱን ይዘው ወደ ማድቤት ሲሄዱ እጃቸው ክብደቱን አልችል አለና መሬት ላይ ወድቆ እንክትክቱ ወጣ፡፡ ምግቡም ወለሉን ሞላው፡፡ ጦማቸውን ዋሉ፡፡ ተለዋጭ ምግብ የሰጣቸው ሰው የለም፡፡
ሚስትዬው ተቆጣች
“አለመብላት መብትዎ ነው፡፡ ያንገበገበኝ የሸክላ ገበቴዬ ነው! ለሁለተኛው ግን አንድ የእንጨት ገበቴ ይሰራልዎትና በዚያ ይበላሉ!” ብላ እንደ ልማዷ እየተመናቀረች፣ ለሳቸው የማይሰማቸውን ስድብ እየተሳደበች ወጣች፡፡ እሳቸው ምንም አልመለሱላትም፡፡
ከዚያን ቀን ወዲህ ሽማግሌው ምግባቸውን የሚበሉት በእንጨት ገበቴ ሆነ፡፡
ይሄ ሁሉ ሲሆን ትንሹ ልጅ አንድ በአንድ ያስተውል ኖሯል፡፡
አንድ ቀን ጠዋት ያ ትንሽ ልጅ፣ ደጅ ሜዳው ላይ ተቀምጦ፣ አንድ ትልቅ የእንጨት ጉማጅ መሬት ላይ አጋድሞ በመዶሻና በመሮ ለመፈልፈል ሲፍጨረጨር ይታያል፡፡ እናትና አባት የሚሰራው ነገር ግራ ገብቷቸው ወደ ልጁ ይመጣሉ፡፡
አባት - “ልጄ ምን እየሰራህ ነው?” ይሉና ይጠይቁታል፡፡
ልጁም- “እኔ ትልቅ ሰው በምሆንበት ጊዜ አባትና እናቴ ማድቤት ቁጭ ብለው ምሳ የሚበሉበትን የእንጨት ገበቴ ካሁኑ ላዘጋጅላቸው እየሞከርኩ ነው!”
አባትና እናት እርስ በርስ ተያዩ፡፡ በድንጋጤ ዐይናቸው እንደፈጠጠ ለደቂቃዎች ቆዩ፡፡ ከጥቂት ጊዜ በኋላ በዐይናቸው የፀፀት እንባ ሞላ፡፡
ከዚህች ቅፅበት በኋላ አያትዬውን እንደ ዱሮው ወደ ገበታው ደግፈው እያመጡ እያስቀመጡ፣ ምግብ ቢንጠባጠብባቸው እንኳ አፋቸውን በደንብ እየጠረጉ፣ በሚገባ መንከባከብ ጀመሩ፡፡
*           *           *
“አጓጉል ትውልድ
ያባቱን መቃብር ይንድ”
ይላሉ አበው ከላይ ያየነውን አይነት አባትና አያት ታሪክ ሲያጋጥማቸው፡፡ ከቶውንም ዛሬ በአባቶቻችን በአንጋፋዎቻችን ላይ የምናደርሰው በደል፣ ነገ በእኛ ላይ ሊደርስብን የሚችለውን መከራ ጠቋሚና አመላካች ነው፡፡ የሀገራችንን የእለት እለት የፖለቲካና ማህበራዊ አካሄድ ስናስተውል፣ ነገ ለሚደርስብኝ መከራ ነገ ራሱ ይጨነቅ የሚል አይነት የምን-ግዴ እምነት ያለ ይመስላል፡፡ የአንዳንድ ግለሰቦች፣ የመሪዎች፣ የፖለቲካ ድርጅቶችም ነገረ-ሥራ “እድሜው ያጠረ በግ፣ ተኩላ ቤት ሄዶ ያወጋል” የሚባለውን አይነት ሆኗል፡፡ በትንሽ በትልቁ መጋጨት፣ ግንዱን ትቶ በቅርንጫፉ መጠላለፍ፣ የቅርፅ አቤቱታ ማብዛት ያበዛሉ፡፡ ያንኑም በወጉና በትክክለኛው ጊዜና ቦታ አለማዋል ሁለተዜ ጥፋት ነው፡፡
ሌሎች ደግሞ ዋና ህፀፃቸው “የጓደኛህን እግር አይተህ ዝለል” የሚለውን ተረት አለመገንዘብ ነው፡፡ ሌላው በገባበት አረንቋ ያላንዳች ማወላወል ዘልሎ መስመጥን፣ እስከዛሬ የሚታገሉት ቦታውን ፍለጋ እንጂ ሀገር-አቀፉን አላማ በስራ ላይ ለማዋል አይመስልም፡፡ በዶሮው ቀርቶ በላባው የሚጣሉ ትልቁን ሀገር የመምራት ኃላፊነት በአግባቡ ተሸክመው ለመምራት፣ ምረጡኝ ይሉ ዘንድ ይቻላቸዋልን? ብሎ መጠየቅ ያባት ነው፡፡
አንዳንዶቹ፤ ትራፊክ እንዳይዘው ለማምለጥ በከፍተኛ ፍጥነት እየነዳ ተገልብጦ እንደሚያዝ ሾፌር፣ መኪናውን ከጥቅም ውጪ ከማድረግም፣ ህይወትን አደጋ ላይ ከመጣልም፣ ከመያዝም የማያድን እርምጃ ሲወስዱ ይታያሉ፡፡ በጥንቃቄ መንዳት፣ አስቀድሞ መድረሻን ማወቅ፣ የትራፊክ ህግጋቱን በቅጡ ማጤን፣ የትላንትናውን ስህተት ጠንቅቆ አውቆ መጓዝ ዛሬም አንገብጋቢ ጥያቄ ይመስላል፡፡ “ጠላቴ ጧት ሞቶ እኔ ልሙት ማታ” በሚል የጥድፊያ ፉከራና መንደርደር ያልታየ ኩርባ፣ የፈረሰ ድልድይ፣ የተዘጋ መንገድ ላይ ሊጥል ይችላል፡፡
የነቃና የተባ ትውልድ መፍጠር የቀዳሚው ትውልድ አደራ ነው፡፡ ሞገደኛና ጠበኛ ልጅ ወልዶ እንቅልፍ ማጣት ብቻ ሳይሆን ሰንብቶ አጉል ጦርነት ውስጥ መግባት ሊከተል ይችላል፡፡ ኋላ ውሎ አድሮ ደግሞ የልጅን አጥቂና አጥፊ፣ አጠፋ ብሎ ሌት - ተቀን በሽምቅና በህቡዕ አድፍጦ ጥይት እንዳጎረሱ፣ ማደርም ይመጣል፡፡ ልጅ፤ ከአብራክ የወለዱት ልጅ ብቻ አይደለም፡፡ ይልቁንም በዘመኑ ተዘርቶ የበቀለው ሁሉ ነው፡፡ አስተማሪ ለሆነ ተማሪው ልጁ ነው፡፡፡ ቀጥሮ ለሚያሰራ ተቀጣሪው ልጁ ነው፡፡ ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ ላይ ለተሰማራ ምልምሉ አባሉ ልጁ ነው፡፡ መሪ ሆኖ ለተመረጠ ተመሪው ልጁ ነው፡፡ በየመሥመሩ፣ በየክልሉ፣ በየቢሮው፣ በየፓርቲው አባትና ልጅ አለ፡፡ ደህና ልጅ የመፍጠር ተግባር አገር የማዳን ተግባር ነው፡፡ ሞገደኛ ልጅ፣ ጋጠ-ወጥ ልጅ፣ አፈንጋጭ ልጅ፣ ነገር-ፈታይ ልጅ፣ ያለኔ ልጅ አይኑር የሚል ልጅ ወዘተ… የልጅ አይነቱና መልኩ እልቆ-መሳፍርት የለውም፡፡ መልካም ልጅ ለመፍጠር ያልተጋ አባት፣ “በልጄ አልተኛሁ፣ በልጄ ገዳይ አልተኛሁ” እንዳለው አባት ከመሆን አይድንም፡፡

  ህወሓት ባካሄደውና ከብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ዕውቅና ባልተሰጠው ጉባኤ ላይ ያልተሳተፉ 16 የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት ሰሞኑን ባወጡት መግለጫ፤ “ሕገ መንግስትና ሕገ ደንብ በመጣስ፣ ሕገወጥ ጉባኤ ያካሄደ ቡድን ሌላውን የማባረር ሞራልና ስልጣን የለውም” ሲሉ  በዶ/ር ደብረፅዮን ገ/ሚካኤል በሚመራው የህወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ የተላለፈባቸውን የእግድ ውሳኔ አጣጥለውታል፡፡
ከሁለት ዓመቱ ደም አፋሳሽ የሰሜኑ ጦርነት ጋር ተያይዞ የሞቱትን የትግራይ ተወላጆች በተመለከተ የድርጅቱ ሊቀ መንበር ዶ/ር ደብረጽዮን ገብረሚካኤል ከሰሞኑ የሰጡት አስተያየት፣ “በትግራይ ሕዝብ ላይ የደረሰውን ጉዳት ወደ ቁጥር ጨዋታ በማውረድ፣ የሕዝቡን መስዋዕትነትና የወጣቶችን ጉዳት ዋጋ ያሳጣ ነው” ሲሉ ተችተዋል- በመግለጫቸው።
በህወሓት ጠቅላላ ድርጅታዊ ጉባዔ ያልተሳተፉ 16 የህወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት፣ ባለፈው ረቡዕ መስከረም 8 ቀን 2017 ዓ.ም. ባወጡት በዚህ መግለጫ፤ “ህገ-መንግስትና ህገ-ድርጅት በመጣስ ህገወጥ ጉባኤ ያካሄደ ቡድን ሌላውን የማባረር ሞራልና ስልጣን የለውም “ ብለዋል። አያይዘውም፤ በድርጅቱ ውስጥ “አጋጥሟል” ያሉት የአመራር ውድቀት፤ ህወሓትን “ለመፍረስ አደጋ”፣ የትግራይን ሕዝብ “ተስፋ ቆርጦ በስጋት እንዲኖር” አድርጎት  ይገኛል ብለዋል።
የ“ሕገ ወጡ ቡድን መሪ” ሲሉ የጠሯቸው የህወሓት ሊቀ መንበር ደብረጽዮን ገብረሚካኤል፣ “ኒው ሆራይዘን” ከተሰኘ የዩቲዩብ ሚዲያ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ የሰጡት አስተያየት፤ “በትግራይ ሕዝብ ላይ የተፈፀመ የዘር ማጥፋት ወንጀል ፍትሕ እንዲያገኝና ተጠያቂነት እንዲረጋገጥ መታገል ሲገባቸው፣ ጉዳቱን ወደ ቁጥር ጨዋታ በማውረድ፣ የሕዝብ መስዋዕትነትንና የወጣቶችን ጉዳት ዋጋ እያሳጡት ይገኛሉ” ሲሉ ተችተዋል፡፡  
ደብረጽዮን ገብረሚካኤል በዚህ ቃለ ምልልስ ላይ ሲናገሩ፤ “በነገራችን ላይ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ‘አለቀ’ የሚለው ነገር ማስረጃ የለው፣ ጥናት የለው፣ ለማስፈራርያነት ነው የሚውለው። ‘ተጨፍጭፈናል’ ለማለትም አይደለም። ‘የዘር ማጥፋት ወንጀል ‘ተፈፀመብን’ ለማለትም አይደለም። አመራሩ ‘አስጨረሰን’ ይላሉ። አመራር ለመምታት፣ ስልጣን ለመያዝ የማይሰራ ነገር የለም።” ብለዋል፡፡
ይህን አስተያየታቸውን ተከትሎ፣ በርካታ ትችቶች በመሰንዘራቸው ሳቢያ፣ ምላሽ ለመስጠት የተገደዱት የህወሓት ሊቀ መንበር፤ “በሕዝባችን ላይ የተፈፀመው የዘር ማጥፋት ወንጀል አሁንም በርካታ በወራሪዎች ስር ያሉ የትግራይ አካባቢዎችን ነፃ ባለመውጣታቸው ምክንያት የተሟላ መረጃ መስጠት ባይቻልም፣ የደረሰው ዕልቂት ግን ከተጠቀሰው ቁጥር በላይ መሆን እንደሚችል ለመግለፅ እፈልጋለሁ” የሚል ማስተባበያ በይፋዊ የፌስቡክ ገጻቸው ላይ አስፍረዋል።
“እንደዚህ ዓይነት ክሕደትና ፖለቲካዊ ውድቀት ስንሰማ፣ እንደህወሓት ከፍተኛ አመራሮች፤ በተለይም እንደድርጅቱ ማዕከላዊ ኮሚቴ በጣም አፍረናል” ያሉት እነዚሁ 16 የህወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት፤ “እኛ የህወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት የቡድኑ መሪ በሰጡት ማብራሪያ በትግራይና ሕዝቧ ላይ የደረሰውን ውድመት ለተራ የስልጣን ፍላጎት ሲባል አዛብተው በመናገራቸው፣ በጥብቅ እንቃወማለን። ይህ ጉዳይ እንደተራ ስሕተት በይቅርታ ተድበስብሶ የሚያልፍ አይደለም።” ብለዋል።
 በትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዚዳንት አቶ ጌታቸው ረዳ የሚመራው የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት ቡድን “ሕገ ወጥ” ሲል የሚጠራውን በደብረጽዮን ገብረሚካዔል የሚመራውን ህወሓት፤ “የተፈጸመውን ዓለም አቀፋዊ ወንጀል ሸምጥጦ በመካድ፣ የዓለም ማሕበረሰብ የተከራከረለትና የመሰከረውን የሕዝብ እልቂት ወደ ጎን በመተው ዋጋ የሌለው እንዲሆን ወስኖ ጥላሸት በመቀባት ላይ ይገኛል፡፡” ሲል ከስሷል።
“ሕገ ወጥ ቡድኑ ቡድናዊ የስልጣን ፍላጎቱን በጸረ ዴሞክራሲያዊ አካሄድ፣ በማስፈራራትና ሃሳቦችን በማፈን ለመጫንና ለማሳካት ላይ ታች እያለ ይገኛል” ያሉት 16ቱ የህወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት፤ “ይባስ ብሎ የመንግሥት መዋቅር አንዲፈርስና ትግራይ መንግሥት አልባ ሆና የረብሻና ግርግር ማዕከል እንድትሆን እየሰራ ነው፡፡” ሲል ከስሷል።
የ50 ዓመታት ዕድሜ  ያስቆጠረውን የህወሓት ሕጋዊ ሰውነት ለማስመለስ ፖለቲካዊ ውይይት መጀመሩንም ጠቁመዋል። “የትግራይ ሕዝብን ትግል የካደውን ቡድን”፣ ሕዝቡና የዳያስፖራ አባላት እንዲታገሉትም ጥሪ አቅርበዋል፤ የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላቱ፡፡ በህወሓት ፍጥጫ ዙሪያ አስተያየት የሰጡት አንጋፋው የህወሓት ታጋይ አቶ ገብሩ አስራት፤ የሁለቱ ቡድኖች ሽኩቻ የሥልጣን እንጂ የሌላ አይደለም- ብለዋል።  በደብረፅዮን የሚመራው ህወሓት ያደረገው ጉባኤ የራሱን ህገ-ደንብና የአገሪቱን ህጎች የጣሰ ነው ሲሉ ክፉኛ የተቹት አቶ ገብሩ፤ ጊዜያዊ አስተዳደሩን እያደናቀፈ ያለው ይኸው ቡድን ነው ሲሉ ወቅሰዋል።
በደብረፅዮን ገብረሚካኤል የሚመራው ህወሓት፣ ከብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ዕውቅና ውጪ ባካሄደው 14ኛው ጠቅላላ ድርጅታዊ ጉባኤ ላይ ያልተሳተፉና የጉባኤ ሂደቱን የተቃወሙትን የህወሓት ምክትል ሊቀመንበር አቶ ጌታቸው ረዳን ጨምሮ 16 የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላትን ከአባልነትና ከድርጅት ሃላፊነታቸው ማባረሩን ያስታወቀው፣ ባለፈው ሰኞ መስከረም 5 ቀን 2017 ዓ.ም. መሆኑ ይታወቃል፡፡


 ባለፈው አንድ ዓመት በአማራ ክልል በመንግስትና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል የቀጠለው ግጭት፤ የቱሪዝምና ሆቴል ዘርፉን እንደጎዳው ተገለፀ። የኢትዮጵያ ቱሪዝምና ሆቴሎች ማርኬት ማሕበር ፕሬዚዳንት አቶ ጌታሁን ዓለሙ፤ ሆቴሎች ገቢያቸው ክፉኛ እንደተጎዳ ተናግረዋል።
አቶ ጌታሁን ለአዲስ አድማስ እንደገለፁት፤ በአማራ ክልል ከዚህ ቀደም በኮሮና ቫይረስ የተጎዳው የቱሪዝምና ሆቴል ዘርፍ በቅጡ ሳያገግም፣ አሁንም በመንግስትና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል በቀጠለው ግጭት ሳቢያ በተጽዕኖ ውስጥ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። “ግጭቶች ሲኖሩ አዲስ አበባ የሚገኙ የተለያዩ አገራት ኤምባሲዎች የጉዞ ማስጠንቀቂያ ያወጣሉ። ይህም የአገርን ገጽታ የሚጎዳ ነው” ብለዋል-ፕሬዚዳንቱ።
የእንቅስቃሴዎች መገደብና ሆቴልን ጨምሮ በተለያዩ ዘርፎች ላይ የሚሰሩ ባለሞያዎች መፍለስ አጠቃላይ ተግዳሮት መፍጠሩንም አልሸሸጉም።
በዚህም ሳቢያ ሆቴሎች ገቢያቸው እንደተጎዳና ዳግም ራሳቸውን አጠናክረው ለመስራት መቸገራቸውን ያመለከቱት አቶ ጌታሁን፤ የዘርፉ ባለድርሻዎች ለቱሪስቶች የጥቅል አገልግሎቶችን ለማቅረብ መዘጋጀት እንዳለባቸውና የአገር ቤት ቱሪዝም ላይ ትኩረት ተሰጥቶ መስራት እንደሚያስፈልግ ጠቁመዋል።
በሆቴልና ቱሪዝም ዘርፍ በኩል ፖሊሲው መሻሻል እንዳለበት ያሳሰቡት የማሕበሩ ፕሬዝዳንት፣ በአሁኑ ወቅት የዘርፉ ተዋናዮችን “የማያሰሩ” ፖሊሲዎች እንዳሉ ጠቁመዋል። “ከ20 ዓመታት በላይ የሚሆነው ለቱሪዝም ዘርፍ የሚያገለግል ከቀረጥ ነጻ ማበረታቻ ፖሊሲ ወጥቷል።  የዛሬ 7 ዓመት ደግሞ፣ ፖሊሲውን ለማሻሻል ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር ዓውደ ጥናት አድርገን ነበር። ከዚህም በመነሳት የማሻሻያ ሃሳቦች ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቢቀርብም፣ እስካሁን አላጸደቀውም። መንግስት የቤት ስራውን ትኩረት ሰጥቶ መስራት አለበት።” ብለዋል።
ከሰሞኑ መንግስት የቱሪዝም መረጃ መሰብሰቢያ ጣቢያ (ሳተላይት) መክፈቱን የጠቆሙት ፕሬዚዳንቱ፤ ከዚህ ቀደም የቱሪስት ብዛት በግምት ይሰላ እንደነበር አስታውሰው፣ ይህም አሰራር የቱሪስት ፍሰት ለአገራዊ ጥቅል ምርት ያለውን ድርሻ በቅጡ ለማወቅ ሳያስችል መቆየቱን አስታውቀዋል።
በሌላ በኩል፣ በሆቴሎች ጥራት ላይ መስራት እንደሚገባ በአጽንዖት የሚናገሩት አቶ ጌታሁን፣ በተለይም የኮከብ ደረጃ አሰጣጥ ላይ ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚገባ አሳስበዋል። የኮከብ ደረጃ የተሰጣቸው ሆቴሎች ከአስር ዓመት በኋላ በተመሳሳይ ደረጃ ላይ ስለመሆናቸው ግምገማ ማድረግ እንደሚያስፈልግና የደረጃ አሰጣጡ መሻሻል ግድ እንደሚል፣ ከዚህም ባሻገር በሆቴሎች አስፈላጊ መሰረተ ልማቶችን በማሟላት የቱሪስቶችን ቅሬታ መቀነስ እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል።
መስከረም 17 ቀን 2017 ዓ.ም. ለሚከበረው የዓለም ቱሪዝም ቀን  “የምንሰራቸው ስራዎች ይኖራሉ” ያሉት አቶ ጌታሁን፣ የተለያዩ ዝግጅቶች ከወዲሁ እንደተሰናዱ አመልክተዋል። የተለያዩ ዓውደ ርዕዮች ተከፍተው ለጎብኚዎች ክፍት እንደሚደረጉና ቀኑን በማስመልከት ዓውደ ጥናቶችን ለማድረግ ዝግጅቱ መጠናቀቁንም ተናግረዋል።
በዓውደ ጥናቶቹ የተለያዩ ምሁራን ጥናታዊ ፅሁፎችን እንደሚያቀርቡ የተገለፀ ሲሆን፤ እነዚህ ጥናታዊ ወረቀቶች ቀኑን ለማክበር ብቻ የሚቀርቡ ሳይሆኑ፣ ለወደፊት ለዘርፉ መሻሻል የራሳቸውን አስተዋፅኦ የሚያደርጉ፣ መሆን እንዳለባቸውም ተጠቁሟል።

አጠቃላይ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያውን ተከትሎ፣ የታሪፍ ለውጥ አለማድረጉን ኢትዮ ቴሌኮም ገልጿል። ኩባንያው ባለፈው ሐሙስ መስከረም 9 ቀን 2017 ዓ.ም. በአዲስ አበባ፣ ስካይላይት ሆቴል ባካሄደው የ2017 ዓመት የበጀት ዓመት ዕቅድ ማሳወቂያ መርሃግብር ላይ ለሰራተኞቹ የደመወዝ ማሻሻያ ማድረጉ ተጠቁሟል።
የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ስራ አስፈጻሚ ፍሬሕይወት ታምሩ በመርሃግብሩ ላይ እንደተናገሩት፣ የዚህ ዓመት ዕቅድ ለየት የሚያደርገው የሦስት ዓመት መሪ የዕድገት ስትራቴጂ የሚጠናቀቅበትና አጠቃላይ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ የተደረገበት መሆኑ ነው። 500 ተጨማሪ ከተሞችን የ4ጂ አገልግሎት፣ 15 ተጨማሪ ከተሞችን ደግሞ የ5ጂ አገልግሎት ተጠቃሚ ለማድረግ በዕቅድ መያዙን ዋና ስራ አስፈጻሚዋ የተናገሩ ሲሆን፣ ከ1 ነጥብ 1 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ የቴሌኮም መሳሪያዎች ለግለሰብና ድርጅት ደንበኞች ለማቅረብ እንደታቀደ አመልክተዋል።
በዚህ አመት የደንበኞችን ቁጥር ወደ 83 ሚሊዮን ለማሳደግ መታቀዱን፣ ባለፈው 2016 ዓ.ም ከ93 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መገኘቱን የጠቆመው ኩባንያው፤ በ2017 መጨረሻ 163 ቢሊዮን ብር ገቢ ለማድረስ ማቀዱን ገልጿል። በተጨማሪም፣ 282 ነጥብ 85 ሚሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሬን ለማስገኘት መታቀዱም ተጠቅሷል።
በቴሌ ብር አገልግሎት አማካይነት ላለፋት 3 ዓመታት 3 ነጥብ 7 ትሪሊዮን ብር መዘዋወሩን የተናገሩት ሥራ አስፈፃሚዋ፤ በአሁኑ ዓመትም አገልግሎቱን በተሻለ መንገድ ለማዘመንና የተጠቃሚዎችን ብዛት ወደ 15 ሚሊዮን ለማስፋት መታቀዱን ጠቁመዋል።
የተደረገውን የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ታሳቢ ያደረገ እቅድ የወጣ መሆኑንና ለውጭ ኢንቨስተሮች በጋራ የመስራት እድል እንደሚከፈትም በዋና ስራ አስፈጻሚዋ ማብራሪያ ላይ ተመላክቷል።  በተለያዩ የገጠር ከተሞች ተደራሽነትን በማስፋት ለ1 ሺሕ ቀበሌ ነዋሪዎች ተጠቃሚ ማድረግ የሚያስችል አገልግሎት እንደሚዘረጋም ተገልጿል።
ከአጠቃላይ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ጋር በተገናኘ ከጋዜጠኞች ጥያቄ የቀረበላቸው ዋና ስራ አስፈጻሚዋ፣ በአፈጻጸም ላይ ሊያጋጥሙ የሚችሉ ውስንነቶች ሊኖሩ እንደሚችሉ ተናግረዋል። አክለውም፣ ከአሁን በፊት የተለያዩ የማስፋፊያ ስራዎችን ለመስራት የሚያስፈልግ የውጭ ምንዛሪ ለማግኘት አዳጋች እንደነበር በመጥቀስ፣ ማሻሻያው የውጭ ምንዛሪ ዕጥረት ይቀርፋል የሚል ዕምነት እንዳላቸው አስረድተዋል።
ማሻሻያውን ተከትሎ የደንበኞች የመክፈል አቅም ተጽዕኖ ሊገጥመው እንደሚችል የሚናገሩት ፍሬሕይወት ታምሩ፣ ተቋማቸው እስካሁን ድረስ የታሪፍ ለውጥ አለማድረጉን አመልክተዋል። ከዚህ በፊት የታሪፍ ማሻሻያ የተደረገው በፈረንጆቹ መስከረም ወር 2018 ላይ መሆኑንና ይህም ማሻሻያ የተጠቃሚዎችን የመክፈል አቅም ባገናዘብ መልኩ መከናወኑን ተናግረዋል።
ዋና ስራ አስፈጻሚዋ አሁን ለምን የታሪፍ ማሻሻያ እንዳልተደረገ ሲናገሩ፣ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው እንዲረጋጋ በማሰብና የተጠቃሚዎችን የመግዛት አቅም በማገናዘብ ነው ብለዋል። ይሁንና በአንዳንድ ምርትና አገልግሎቶች ላይ የዋጋ ጭማሪ ሊኖር እንደሚችል አልሸሸጉም።
ከማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ጋር በተያያዘ የኢትዮ ቴሌኮም ሰራተኞች ደመወዝ ላይ ማሻሻያ መደረጉን የጠቆሙት ፍሬህይወት ታምሩ፤ ደመወዝን በተመለከተ ከሌሎች ተቋማት ጋር ሲነጻጸር፣ ኢትዮ ቴሌኮም የተሻለ አሰራር አለው ብለዋል።




Saturday, 21 September 2024 12:45

የወቅቱ ጥቅስ

“የነቃና የተባ ትውልድ መፍጠር የቀዳሚው ትውልድ አደራ ነው፡፡ ደህና ልጅ የመፍጠር ተግባር አገር የማዳን ተግባር ነው፡፡”



•  ሊባኖሳዊያን በእጃቸውና በቤታቸው ያሉ የቴክኖሎጂ
መሳሪያዎችን እየጣሉ ነው ተባለ


7 ሚሊዮን ዶላር ዋጋ ወጥቶበት የነበረው የሂዝቦላህ አመራር በእስራኤል ጦር መገደሉ ተዘግቧል፡፡ ከአንድ ዓመት በፊት የሐማስ ታጣቂዎች በእስራኤል ላይ ድንገተኛ ጥቃት መሰንዘራቸውን ተከትሎ የተጀመረው ጦርነት መልኩን ቀይሮ አሁን ወደ ሊባኖስ ፊቱን አዙሯል፡፡

የእስራኤል ጦር ከትናንት ጀምሮ በደቡባዊ ሊባኖስ በኩል ከፍተኛ ጥቃት በማድረስ ላይ ሲሆን፤እስራኤል ከደቂቃዎች በፊት በሀገሪቱ መዲና ቤሩት የአየር ላይ ጥቃት መሰንዘሯ ተሰምቷል፡፡  በዚህ ጥቃት ከዚህ በፊት በአሜሪካ ይፈለግ የነበረው የሂዝቦላህ ሬድዋን ሀይል ኮማንደር የሆነው ኢብራሂም አኪል መገደሉን የፈረንሳዩ የዜና ወኪል  ኤኤፍፒ ዘግቧል፡፡

ከኢብራሂም አኪል በተጨማሪ ስምንት ሰዎች ሲገደሉ፣ 60 ሰዎች ገደማ ደግሞ ቆስለዋል፡፡  እስራኤል ከሂዝቦላህ ከፍተኛ አመራር መካከል ባለፈው ሀምሌ ወር ላይ ፉአድ ሽኩርን በደቡባዊ ሊባኖስ መግደሏ ይታወሳል፡፡ ኢብራሂም በፈረንጆቹ 1983 ዓ.ም  ላይ በቤሩት በሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ በደረሰው የቦምብ ጥቃት እንዲሁም በዚሁ ተመሳሳይ ዓመት በሊባኖስ በነበሩ የአሜሪካ ባህር ሃይል  አባላት ላይ የተፈጸመውን ጥቃት አቀነባብሯል ተብሎ ሲፈለግ እንደነበር ይታወቃል፡፡  
በመላው ሊባኖስ የኮሙኒኬሽን መሳሪያዎች መፈንዳታቸውን ተከትሎ፣ ከ37 በላይ ሰዎች ሲገደሉ ከዚህ ሴራ ጀርባ እስራኤል እጇ እንዳለበት ሂዝቦላህ ገልጿል፡፡ ፍንዳታዎቹን ተከትሎ ሊባኖሳዊያን በእጃቸውና በቤታቸው ውስጥ ያሉ የቴክኖሎጂ መሳሪያዎችን እየጣሉ ነው ተብሏል፡፡

Page 9 of 732