Administrator

Administrator

ከዕለታት አንድ ቀን፤ አንድ ሰው፣ ለወዳጆቹ የሚከተለውን ደብዳቤ ፃፈ፡፡ ኑ አቃብሩኝ ዛሬ የጥንቱ የጠዋቱ ወዳጃችን አቶ “ማኅበራዊ-ብስለት” (Common Sense) የቀብሩ ሥነ ስርዓት ስለሚካሄድ ቀብር ላይ ተገኝታችሁ አብረን እንቀብረው ዘንድ ጥሪዬን አቀርባለሁ፡፡ እንደምታውቁት አቶ “ማህበራዊ-ብስለት” የሁላችንም የረዥም ጊዜ ወዳጅ ነው፡፡ ዕድሜውን ማንም አያውቅም፡፡ ምክንያቱም ከልጅነቱ ጀምሮ በቢሮክራሲው ቀይ-ጋዲ (bureaucratic red tape) በየጊዜው እየተተበተበና እየታሠረ በመኖሩ ነው፡፡ ትቶልን የሄደው ቅርስ ግን አይረሴ ትምህርት ነው፡፡ ይኸውም፡- ከዝናብ መቼ መውጣትና መጠለል እንዳለብን በጠዋት የተነሳች ወፍ በጊዜ ቀድማ ትል መያዝና መብላት እንደምትችል ህይወት ሁሌ አልጋ በአልጋ እንዳልሆነችና ሁሌም ሚዛናዊ ሆኖ እንደማናገኛት ምናልባት ጥፋቱ ከኔ ነው ብሎ ማሰብ እንደሚገባ፡፡ “ማኅበራዊ-ብስለት” በህይወት ሳለ፣ ህይወትን ቀለል አድርጎ የሚያይ ከመሆኑም በላይ፤ “ከምታገኘው በላይ አታውጣ! አታጥፋ” የሚል የፋይናንስ ስትራቴጂ እየተከተለ ነበር የሚኖረው፡፡

በተጨማሪም አዋቂዎች እንጂ ልጆች ኃላፊነት እንደሌለባቸው እንድንገነዘብ አስተምሮናል፡ “ማኅበራዊ - ብስለት” ጤንነቱ ድንገትና በፍጥነት መታወክ የጀመረው ለመልካም ታስበው የተፀነሱት ህግጋትና ደምቦች ከታወጁ ቀን ጀምሮ ነው፡፡ ይኸውም፤ አንድ የ6 ዓመት ህፃን የክፍል ጓደኛውን ፆታዊ ጥቃት አድርሶባታል ተብሎ ሲከሰስ፣ አስተማሪ ተማሪ አባረረ ተብሎ ሲከሰስ፣ ወላጆች ልጆቻቸውን በግብረ-ገብነት ገርተው መያዝ ሲገባቸው፤ አስተማሪዎችን ሲወቅሱ፤ ወላጆች የተማሪዎችን የፀጉርና የፊት-ቅባት አጠቃቀምን፤ እንዲሁም የአስፕሪን አዋዋጥን በተመለከተ የምክር አገልግሎት ያገኙ ዘንድ ት/ቤት ድረስ ሲጠሩ፤ ያም ሆኖ ሴት ልጃቸው ማርገዝዋንና ማስወረድ እንደሚያስፈልጋት ሳይነገራቸው ሲቀሩ፤ “ማኅበራዊ-ብስለት” ታሞ አልጋ ላይ ዋለ! እጅግ በሽታው የባሰበትና መኖር ያስጠላው ደግሞ፤ ቤተክርስቲያኖች የንግድ ቦታ ሲሆኑና ወንጀለኞች ወንጀል ከተፈፀማባቸው፤ ከተበዳይ ወገኖች ይልቅ፤ ምቾትና እንክብካቤ ሲደረግላቸው ሲያይ ነው፡፡ ህይወት እጅግ በጣም ከፍታ ውጪ-ነብስ፣ ግቢ-ነፍስ የሆነበት ደግሞ፤ ዘራፊ ወሮ-በላ፤ ሰው ቤት ገብቶ ባለቤቱ መከላከል ሲያቅተውና ዘራፊው ራሱ ዘርፎ ሲያበቃ፣ ራሱ ከሳሽ ሆኖ ሲገኝ ነው! በመጨረሻ ፍፁም ተስፋ የቆረጠውና ለጣር የበቃው ግን፤ በአሁኑ ዘመን፣ እንፋሎቱ እየተነነ ያለ ቡና ትኩስ መሆኑን መገመት ያቃታት ሴት ሲያይ ነው፡፡

ትንሽ እጭኗ ላይ ጠብ ስታደርግ ዋጋውን አገኘች!! “ማኅበራዊ ብስለት” ሲሞት፤ አምስት ልጆቹን እዚህ አገር ትቶ ነው የሄደው፡፡ ሦስቱ የእንጀራ ልጆቹ ናቸው፡፡ ስማቸውም - (የመጀመሪያው) መብቴን አውቃለሁ (ሁለተኛው) አሁኑኑ እፈልገዋለሁ (ሦስተኛው) ጥፋተኛው ሌላ ሰው ነው (አራተኛው) እኔ ተበዳይ ነኝ (አምስተኛው) ምንም ሳልሠራ ክፈለኝ፤ ይባላል፡፡ ብዙ ሰዎች ቀብሩ ላይ አልተገኙም፡፡ ምክንያቱም “ማኅበራዊ-ብስለት” መሞቱን አላወቁም፡፡ አሁንም “ማኅበራዊ-ብስለትን የምታስታውሱት ካላችሁ ይህንን ልቅሶ ላልሰሙ አሰሙ፡፡ ካልሆነ፤ ከብዙሃኑ ጋር ምንም ሳትሠሩ፣ እጃችሁን አጣጥፋችሁ ተቀመጡ፡፡ የጥንት ወዳጃችሁ በማናቸውም ህይወታችን ረገድ፣ በየእርከኑ ከሚያጋጥመን ውሽንፍር-አዘል ዝናብ የምናመልጥበትና የምንጠለልበት ልዩ ብስለት ያሻናል፡፡ ጊዜን ለይተን፣ በጠዋት ነቅተን፣ ግባችንን ለመምታት የጧት - ተነሽ (ማላጅ - Early – riser እንዲሉ) መሆን ይገባናል፡፡ ዘርቶ፣ አጭዶ፣ ወቅቶና ጐተራ ከቶ፣ ከዚያም አብስሎና ቆርሶ፣ የሚያበላንና የሚያኖረን ከራሳችን በቀር ማንም የለም፡፡ የባዕድ አንጐል እንጂ የባዕድ እጅ ማየት የለብንም፡፡ የመተሳሰብ፣ የመቻቻል፣ የመማማር ክህሎት መጀመሪያ አንቀጽ፤ እኔ ተሳስቼስ ቢሆን? የማለት ትሁት ብስለት ነው፡፡

“ተጣልቶ ለመታረቅ የማይችል ወይም የማይሻ፤ ካብ - አይገባ - ድንጋይ ነው፡፡ ሳይጣላ የሚታረቅም ያለዕዳው ዘማች ነው” ይላሉ አበው፡፡ አንድ ብስለት ይሄን ማወቅ ነው፡፡ የብስለት ሌላኛው እጁ ሰው ከሰው መቻቻሉ ነው፡፡ ሎሬት ፀጋዬ በ”ነይ መርካቶ” ግጥሙ እኒህን መስመሮች ለግሶናል-እንድንቻቻል፡- “በአራዳው ጊዮርጊስ ፈረስሽ፣ ተንጠራርተሽ እስከአንዋር “ኪራራ ይሶን” ጥሪሽን፣ አሸጋግረሽ “በአላህ አክበር” በአባ መቻል ላይ ድልድይሽ፣ ታጅበሽ እስካማኑኤል ዳር በአባ መቻል ላይ ድልድይሽ፣ ታጅበሽ እስካማኑኤል ዳር መርካቶ ነይ እንደገና፤ ፀሎታችን ይታደግሽ ምርቃታችን ያካብትሽ፣ የከርታቶች መጠለያ መርካቶ ያዲሳባ አድባር ከሰባት ቤት ጉራጌሽ ቤት፣ ከኦሮሞሽ አውድማ ዳር ከወሎሽ ጀበና መጀን፣ ከጊሚራው በርሽ አፋር ከአማራሽ የሰብል አውጋር፣ ከጎጃም በረንዳሽ ግንባር እንደገና ነይ መርካቶ፡፡ ሌላው ብስለት የወራሽና አውራሽ መንገዳችን ነው፡፡ አዲሱ አሮጌውን መተካቱ፣ ገፍቶ መጣሉ ወይም ከናካቴው ማጥፋቱ፤ ያለና የነበረ ዲያሌክቲካዊ ሀቅ ነው፡፡ “በሕግ አምላክ”፣ “በንጉሥ አምላክ!” ብሎም ቢሆን፤ መግፋት የተለመደ ነው፡፡

“ወድቆ በተነሳው ነው ተነስቶ በወደቀው ባንዲራ የሚባለው?” ትላለች አንድ የሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን ዕብድ ገፀ-ባህሪ! ስለመተካካት ስናስብ አንድ አንድ መሠረታዊ ነቁጦችን ልብ እንበል፡፡ “ከአንተ ቀድሞ በነበረው ባለሥልጣን ወይም አባት ሰው፤ የተለየሁ ነኝ ብለህ ታምን ይሆናል፡፡ ሆኖም እያደግህ ስትሄድ እስከወዲያኛው ቆራጥ ካልሆንክ ተፃርረኸውና አምፀኽበት የነበረውን አባትህን ትሆናለህ” ይላል አንድ የፖለቲካ ፀሀፊ፡፡ አባትህን መተካት በአያሌው ያንተን ፅንዓት ይጠይቃል፡፡ የሚያስከፍለው ዋጋ አለ፤ ሲል ነው፡፡ “ውሎ አድሮ አንተ የራስህን አባት መሆንህን አትርሳ! ስለዚህም ዞረህ ዞረህ መከላከያህን መክነህ፣ ጭምብልህን አውልቀህ ያው የትላንቱ ጣረ-መንፈስ ማለትም፤ አባትህ፣ ልማድህና ታሪክህ-መልሶ መምጣቱ ላይቀር፤ ሌላ አንተነትህን ለመፍጠር ስትፍጨረጨር ዕድሜህን አትፍጅ” የሚለውን አፅንዖት ይሰጠዋል ያው ፀሀፊ፡፡ ሆኖም አንድን ዕውነት ዋና መልሕቅ አድርጐ ጠንካራ አደራ ያሰፍራል፡፡

በግጥም ስናስቀምጠው የቁም ነገሩ ቡጥ የሚከተለው ነው፡፡ “አየህ፤ ከትላንትህ ተጋጭተህ፣ ትላንትናህ ላይ አምፀህ ጉልላት አናት የወጣህ፤ ግርጌህ ያሉትን አትርሳ፤ ከቶም ዐይንህን አትንቀል አመፃ ያንተው ቅጂ ነው፣ በተከሉት የሚተከል! ይነሳሉ፤ ያው እንዳንተው አንድም ዕድል አትስጣቸው፤ ካይንህም አታርቃቸው ወንድሜ ዕንቅልፍ አይጣልህ፣ መንገዱ ያንተው መንገድ ነው!!” በሀገራችን ረጅም የፖለቲካ ሂደት ውስጥ አንዳንድ ከመሠረቱ የተበላሹ ስህተቶች እንደጥቁር ጥላ ይከተሉናል፡፡ እንደ ዲሞክራሲ፤ እንደ ኤትኒክ-ፌዴራሊዝም፣ ስለ ጠረጴዛ ውይይት፤ ማለትም ስንታረቅና ስንጣላ፣ ስንደራደርና ስንግደረደር ብስለት ለማጣታችን፣ እንደምርጫ፣ እንደ ዕርቅና ሽምግልና ያሉ፤ አንጓ አንጓ ጉዳዮች ከነእንከናቸው ያሳድዱናል፡፡ መሻሻል፣ መቃናት፣ ፈር-መያዝ አለባቸው፡፡ “አሳማ ነው እንጂ ጨዋ ወደ ትፋቱ አይመለስ” ይላል ገጣሚው፡፡ ከውሉ፣ ከመሠረቱ ያለውን መርምሮ፣ “ካፈርኩ አይመልሰኝ” ሳይሉ፤ ማቃናት ደግ ነው፡፡ ለዚህም፤ “ስልቻ ተበላሸ፡፡ ምኑጋ? ሲነፋ፡፡ ሲነፋ አይደለም፡፡ መጀመሪያ ሲገፈፍ ነው”፤ የሚለውን ተረትና ምሳሌ ልብ ማለት መልካም ነው፡፡

ዛሬ ማንም ጋዜጣ ላይ የጻፈ ሰው፤ ነገ መጽሃፍ ይዞ እንደሚመጣ እርግጠኛ እስከመሆን ደርሰናል፡፡ ይሄ ደግሞ “ደራሲ” የሚለውን ብርቅ ስም ያለአቅም ለመሸከም ምክንያት እየሆነ መጥቷል፡፡ ፖለቲካ የጻፈው፣ ስለሳይንስ ያወራው፣ ሁሉም ከጋዜጣ ወደ መጽሃፍ መሸጋገሩ ተለምዷል፡፡ ይህ ልምድ ደግሞ የኛ ብቻ አይደለም፡፡ በተለይ ያደጉት ሃገራት ደራሲያን ይህንን ሲያደርጉት ለመኖራቸው በጄ ላይ ያሉ መጽሃፍት እማኝ ናቸው፡፡ በጋዜጣ ላይ የወጡ ብቻ ሳይሆኑ በሬዲዮ የተተረኩና በቴሌቪዥን የታዩ ፕሮግራሞች ሳይቀሩ ታትመው ለህዝብ ቀርበዋል፤ይሁንና ውስጣቸው ሲታይ ግን እንቶ ፈንቶ አይደሉም፡፡ ለምሳሌ ዴቪድ ፍሮስት የተባሉ የቴሌቪዥን ጋዜጠኛ የጻፉት መጽሃፍ ቀላልና ተራ ነገር የያዘ ሳይሆን ታላላቅ የአሜሪካ የኪነጥበብና የፖለቲካ እንዲሁም የህግና የሌላም ሞያ ባለቤቶችን ያካተተ በመሆኑ የሚሰጠው ዕውቀት ቀላል አይደለም፤ለምሳሌ የማርቲን ሉተር ኪንግ ያልተነገሩ ነገሮች በጓደኛው አማካይነት ተጽፈው ቀርበዋል፡፡ በተመሳሳይ ሁኔታ የተለያዩ ደራሲያን የጻፏቸው መጣጥፎች ተሰባስበው ታትመዋል፡፡

ለዚህ ምሳሌ የሚሆኑን የፐርልስ በክና የሌሎች የስነጽሁፍ ምሁራን ስራዎች ናቸው፡፡ የተለያዩ ደራሲያንን ቃለምልልስ የያዘው የቻርልስ ሩአስ “conversations with American writers” የተሰኘ መፅሐፍ ተጠቃሽ ነው፡፡ ወደ እኛ ሃገር ስንመጣ ግን እውነታው ሌላ ነው፡፡ በእርግጥ ጊዜ የማይሽራቸው ፣የታላላቅ ሰዎችን ታሪክ የያዙ ወይም ደግሞ እንደ ጲላጦስ “ፍልስፍና” ዓይነቶቹ በመፅሐፍ መልክ መታተማቸው ጥሩ ነው፡፡ ምክንያቱም እነዚያ ጸሃፊው ደክሞ የሰራቸው ሃሳቦች በቀላሉ ዳግም ስለማይገኙ፣ የዚህ ዓይነት ስራዎችን ማሳተም ለትውልድ እንደማስተላለፍም ይቆጠራል፡፡ዕውቀት ሆነው ለትውልድ የሚተላለፉ ከሆነ ደግ ነው፡፡ ከዚያ ውጪ ከሃሜት ያልተለዩ ፅሁፎችን፣ በጥላቻና በቂምበቀል የተሞሉ ፖለቲካዊ የጋዜጣ ፅሁፎችን በመፅሐፍ ማሳተም ግን ጥጃዋ ለሞተባት ላም ፣ ጭድ የተወተፈበት ቆዳ በማቅረብ ወተት እንድትሰጥ እንደማታለል ነው፡፡

ላም እንስሳ ስለሆነች የሟች ጥጃዋን ቆዳ ገፍፈው ጭድ በመክተት ሲያቀርቡላት ጡትዋን ትሰጣለች ፤ እኛ ግን ሰዎች ነን - ለዚያውም አንባቢ! አንባቢ ደግሞ የተሻለ መመዘኛ አለው ብዬ አምናለሁ፡፡ አሁን አሁን ግን እኛ ጋ የአንድ ሰሞን የፖለቲካ ትኩሳት፣የሚያልፍ ገጠመኝ ወዘተ ይዘን “አረ ጎራው” እንላለን፡፡ ወይም ለሽቀላ እንነሳለን፡፡ እንደኔ እንደኔ በተለይ እንደበዕውቀቱ አይነት አዳዲስ ሃሳብ ብቅ የሚልባቸው ወጎችና ጽሁፎች እንዲታተሙ መፈቀድ ብቻ ሳይሆን ገንዘብ ያለው ጥበብ ወዳድ ቢኖርና ቢያሳትመው ደስ ባለኝ ፤ክፋቱ የኛ ሃገር ድርጅቶች ስፖንሰር የሚያደርጉት ምናልባት እግር ኳስን እንጂ ጥበብ ብዙም አይማርካቸውም፡፡ ለነገሩ ጥበቡም አላማረበትም፡፡ ውበት እየተረሳ ፣ ሽቀላ ብቻ እየነገሰ መጥቷል፡፡ ብር ከሰውም ከጥበብም ይልቅ ሃገር እየገዛና እየሸጠ ያለበት ዘመን ቢኖር ዛሬ ነው፡፡ አውጣን እያሉ ከመታገል ውጪ ምንም ማድረግ አይቻልም፡፡

ጋዜጠኞቻችን እጅግ በሚያሳፍር ሁኔታ ለብ ለብ ናቸው፡፡ ሌላው ቀርቶ ሳምንታዊ ጋዜጣዎችን የሚያነቡ ስንት ናቸው ብትሉ እፍኝ አይሞሉም፡፡ ስለዚህ ስለንባብና ስለጥበብ ያላወቀ “ነጋዴ ጋዜጠኛ” ስነጽሁፍ ሲወድቅና ሲነሳ ምን ስሜት ሊሰጠው ይችላል? ቀድሞ ራሱ ወድቋልና፡፡ምናልባት እንደጋንዲ ያለ ሰው ያስፈልገን ይሆናል፡፡ ግን ከየት ሊወለድ ይችላል? ጋንዲ ያልኩት ጥበብ እንዲያሳድጉ የተሰጣቸውን ስልጣን፤ አዙረው ለሌላ ፖለቲካዊ ጥቅም ለመመንዘር የሚተጉ ሰዎችን ስላየሁ ነው፡፡ ጥበቡን ሸጠው እንጀራና ስልጣን የሚያሳድዱ ሰዎችን ማየታችን እንግዳ አይደለም፡፡ ለዚህ ነው የጥበቡ ሰፈር ጭርታ የበዛበት! አሜሪካዊቷ የወግና መጣጥፍ ጸሃፊና ደራሲ ማርጋሬት ሲ ባኒንግ እንደሚሉት፤ በጋዜጣ ላይ የሚወጡ ተከታታይ ጽሁፎች ለፈጠራ ደንቃራ ናቸው፡፡ እንዲያውም በጋዜጣ ላይ በተከታታይ የሚታተሙ ልቦለዶች እንኳ የረዥም ልብወለድ (ኖቭል) እንጀራ ልጆች ናቸው፡፡

ጥበብ በሚገባ እንዳያድግ መንገድ የሚይዙ፡፡ እናም በስነጽሁፍ አለም ውስጥ ምንም አክብሮት አይሰጣችውም፤ወይም ግርማ የላቸውም ይላሉ - ደራሲዋ፡፡ እርሳቸው በሚጽፉበት የሴቶች ጉዳይ ላይ ያተኮረ መጽሄት፤ የዚህ ኣይነቱን ጽሁፍ ክፉኛ በመተቸቱ፣ አሁን አሁን አቅም እያጣ እንደመጣ ይናገራሉ፡፡ እኛ አገር ግን ትችትና ሂስ እየተዳከመ በመምጣቱ ሁሉም የፈለገውን እየፃፈ የሚያሳትምበት ጊዜ ላይ ደርሰናል፡፡ የጋዜጣ ላይ ጽሁፎች መጽሃፍ ላይ መታተማቸውን አስመልክቶ አንድ ጸሃፊ ከጥቂት ወራት በፊት የጻፉትን ጽሁፍ አንብቤ ነበር፡፡ ይሁንና ሙሉ ለሙሉ ተቃውሞ ብቻ ስለነበር ፣ ግለሰቦች ላይ ያነጣጠረና አሁንም “ሸቀጣዊ” አስተሳሰብ ያለው ስለመሰለኝ በአክብሮት ልቀበለው አልቻልኩም፡፡ በርግጥ ጽሁፉ የሚያሳያቸው እውነታዎች አሉ፡፡ ጥቅል ሃሳቡ የጋዜጣ ላይ ጽሁፎች ህትመት ሲበዛ፤ አንባቢው አዳዲስ ስራዎች አያገኝም የሚል ነው፡፡ የበዕውቀቱንና መሰል ፀሃፍትን ጽሁፎችም ጠቅሶ ነበር፡፡ ግና መስመር ያለማበጀቱ አናደደኝ፡፡ እንዴት ነው የበዕውቀቱ ወጎች ከሌሎች የጋዜጣ ጽሁፎች ጋር በጅምላ የሚተቸው?የእሱ ቀልዶች እኮ ሰማይ ቀድደው ያያሉ፡፡ “የአስተናጋጁ ማስታወሻ” ላይ ያነበብኩት አንድ ታሪክ ሁሌ ይገርመኛል፡፡

ሲቀልዱ ሰውን ማሳቅ ብቻ ሳይሆን በጥልቀት እንዲያስቡ ማድረግ እንደሚቻል በዕውቀቱ አሳይቷል፡፡ አንድ የቆሰለ ሰውዬ ቀይ ቀበሮ ቁስሉን ስትበላው አይቶ፣ ባለጠመንጃው ሊተኩስ ይሞክርና ቀይ ቀበሮ መሆንዋን ያያል፣ያኔ ጠመንጃውን መለስ ያደርጋል፡፡ ለካ እኛ ሃገር ቀይ ቀበሮ ከሰው ይልቅ ውድ ነው!... ደሃ ስለሆንን ከሰው ይልቅ ለሰው የሚያስፈልጉት ነገሮች ናቸው! እንዲህ መሰል ነገሮችን የጻፈው በዕውቀቱ፣ ደጋግሞ ቢጽፍና ቢያሳትም ከዳቦዬ ቆርሼ ከመግዛት ወደ ኋላ አልልም፤ አልቆጭም፡፡ ለአለማየሁ ገላጋይ ፅሁፎችም ያለኝ አመለካከት ከዚሁ ጋር የተመሳሰለ ነው፡፡ ውብ የቋንቋ አጠቃቀምና ጥሩ ሃሳብ የመምረጥ አቅም አለው፡፡ ስሜትና ወሬ ብቻ ይዞ አይጋልብም፡፡ አንዳንዴ ሊያነቅፈው ቢችልም ጎበዝን ሲሳሳት መታገስ ያስፈልጋል፡፡ ከሺህ “ኮተታሞች” አንድ ጥርት ያለ ይሻላል፡፡ የግጥሙ ሰፈር የተበለሻሸው በዚህ የተነሳ ይመስለኛል - ሺ “ኮተታሞች” አደባባይ ላይ ብዙ ሳይደክሙ መታየት ስለሚፈልጉና “መጽሃፍ አሳተመ” መባልን እንደ ገድል ስለሚቆጥሩት፡፡ አሁንም የጋዜጣ ጽሁፎች አንዱ ሩጫ ያልተወለዱበትን ተልዕኮ ለማሳካት የሚደረግ መታተር ነው፡፡ ያለመክሊት ስም መፈለግ!... አንዳንዶቹ ለንጹህ ሽቀላ ሲሆን፣ ሌሎቹ ለስም ነው - ”ደራሲ” ለመባል ያላቸውን ናፍቆት ለመወጣት፡፡ ተፈጥሮና ፈጣሪ ካልሰጡኝ ቢቀርስ!... በቃ መጣጥፍ ጸሃፊ ብሆን! ህሊና ሲኖር ይህ ይቻላል፡፡ አንዳንዶቹማ የሰዎችን ስም መጥራት ሲቀራቸው ስድባቸውን በመጽሃፍ ማሳተም ጀምረዋል፡፡

ምነው ጎበዝ! የሃገራችንን ስነጽሁፍ ክብር ይህንን ያህል ማዋረድ ይገባናል እንዴ? . ለሽሙጥና ግለሰቦችን ለመስደብ መፅሐፍ ከማሳተም ይልቅ አዝማሪ ቤት መክፈት አይሻልም ? እዚያም ቢሆን ግን ልክና ጨዋነትን ይጠይቃል፡፡እንደ እኔ እንደ እኔ የዚህ ዘመን አብዛኞቹ ጽሁፎች ቁም ነገር አዘል የማይሆኑት ካለማንበብ የተነሳ ነው፡፡ ምንም ሲጠፋ ከስድብ ውጪ በአፋችንም ሆነ በብዕራችን አይመጣም፡፡ ያልዘሩት አይታጨድምና! ብናነብ ግን የስነ ጽሁፍም ክብር ይገባን ነበር፡፡ ሚዛናዊነትን እንለምዳለን፤ ከመሳደብ ይልቅ ወደ መወያየት እንመጣለን፡፡ ትውልድን ላለማበላሸት ሃላፊነት ይሰማናል፡፡ ትውልድ ከሳንቲም ሽቀላ እንደሚበልጥ እንረዳለን፡፡ ሃገር መውደድና ለሃገር መታገል ትውልድን በጥላቻና በቂም ውስጥ እየዘፈቁ አይደለም፡፡ ለሆድ ሳይሆን በእውነት ለወገን በመቆርቆር ነው፡፡ አርቆ አሳቢ በመሆን! ብርን ብቻ መውደድ የቅርብ ቅዠት እንጂ የሃገር ህልም ሊሆን አይገባም፡፡ ቂምና ጥላቻን መዝራትም በሽታ ነው፡፡ ፈውስ የሚመጣው በቂም አይደለም፤ እውነትን በፍቅር በማስተላለፍ ነው፡፡

ሃገራችን በብዙ መልኩ ጥንካሬዎችዋን እያጣች የመጣች ይመስላል፡፡ ምናልባት ዓለማችንም ማለት ይቻላል፡፡ ሙዚቃው ለብለብ፣ ጽሁፉ ለብለብ፣ ምግቡ ለብለብ፣ ፖለቲካው ለብለብ እየሆነ ነው፡፡ የሃገራችንን ሁለንተና መለወጥ ያለብን እኛ ነን ብዬ አምናለሁ፡፡ እንግዲህ ያያችኋት ናት ሃገራችን - በጥበቡ ሰፈር፡፡ የገጣሚ ነቢይ መኮንንን “ሃገርህ ናት በቃ!” የምትል ግጥም አንብቡና ራሳችሁን ፈትሹ፡፡ ይቺው ናት ኢትዮጵያ ሃገርህ ናት በቃ! በዚች ንፍቀ-ክበብ፣ አይምሽ እንጂ መሽቶ፣ማታው ከጠረቃ የነቃም አይተኛ የተኛም አይነቃ፡፡ ይቺው ናት ዓለምህ፣ ብቻዋን የተኛች ከዓለም ተደብቃ!! አኪሯ ቀዝቅዞ፡- “ያንቀላፋች ውቢት” ያንተው የክት ዕቃ! ምን ትሆን እንግዲህ ሀገርህ ናት እሷ! ልቧን አታውልቃት አትጨቅጭቃት በቃ፣ አብረህ አንቀላፋ ወይ አብረሃት ንቃ!! ሁሉንም አወራን ባንል ትንሽ ነካካን፤ገናም ወደ ፊት እናወራለን፤ግን ሃገራችንን የምንሰራት እኛ ነን፤ማንም አይመጣልንም፡፡ ሽቀላ ብቻ አይደለም፤ ሃላፊነትም ሊሰማን ይገባል፡፡ በተለይ ጋዜጠኞቻችን እባካችሁ ክፉና ደግ ለመለየት እንኳ አንብቡ፡፡ ማንበብ ሙሉ ሰው ያደርጋል፡፡

Saturday, 06 April 2013 14:27

ቢራቢሮ

ቢራቢሮ እንደ ደብተር ተከፍታ ደረቷን ለጧት ፀሀይ ሰጥታለች፡፡ ደስ ማለቱ! የጧት ፀሀይ ሙቀቱ! ሽው ብሎ በላይዋ ላይ አለፈ - አስደንጋጭ የድምቢጥ ጥላ ክንፏ ዝግት! ጸጥ! ከነድንቢጥ ሆነ ከሌሎቹ የሞት መላእክት ራሷን የምትከላከልበት አንድም መሳሪያ የላት፡፡ ወላ ጥርስ - ወላ ቀንድ - ወላ መርዝ - ምንም! ምክር ፍለጋ ዶክተር አሊ ዘንድ ሄደች፡፡ ዶክተር ኤሊ ጥንት ከነቢዩ ኤልያስ ጋር ነበሩ፡፡ የመፃህፍትና የአበው ጥበብ በድንጋይ ልብሳቸው ሙሉ ተጽፏል እየተባለ ይነገርላቸዋል፡፡ “አበባን የፈጠርክ ፈጣሪ! አቤት አፈጣጠሩን ስታውቅበት! ኧረ ተመስገን!” እያለች ቢራቢሮ አበባዋ ላይ አረፈች፡፡ ወለላውን ልትጠጣ ብትሞክር ታድያ፣ በየት በኩል? ጥርሶቿ - እንዲያ በጥንቃቄ የመረጠቻቸውና እንዲያ ስትመካባቸው የቆየች ጥርሶቿ፣ አላስጠጣ አሏት፡፡

ይባስ ብለው ደሞ ያችን የጠራቻትን አበባ ቦጫጨቋት እነዚያ ባይተዋር ጥርሶች! ቅፅበታዊ ውስጣዊ ፀጥታ … ክንፏ ፀጥ እርጥ እስኪል ድረስ … “እንግዲያውስ ጥርስ ምን ሊያደርግልኝ ኖሯል? የኔ ምግብ እንደሆነ አይታኘክ፡፡ ለሳቅ ለፈገግታ እንደሆነ፣ የኔ ሳቅ ፈገግታዬ ክንፌና በረራዬ ውስጥ ያበራሉ፡፡ ሌላው ትርፍ ሸክም!” አለችና፣ እነዚያን የሾሉ ሹላሹል ጥርሶች ወድያ አሽቀንጥራ ጣለቻቸው (እዝጌርን ስትጐበኝ በስውር ሲሰልላት የነበረው ዲያብሎስ እንኳ ወደ ገሀነብ መቀመቅ ያን ያህል አልተወረወረም!) ከአበባዋ ወለላዋን ጠጣችና ጉዞዋን ስትቀጥል “ሆ! ኧረ‘ንኳንም ጥርስ አልፈጠረልኝ!” አለች፡፡

በሚቀጥለው ምእራፍ (ማለቴ በረራ) ቢራቢሮ ሲሾል የኖረ ሹል ጦሯን ወደ ሰማይ አሾለች አመቻቸችና፣ ክንፎቿን እስከ ጫፍ ዘርግታ ደረቷን ለፀሀይ ሰጥታ ስታበቃ “እነሆ በረከት! እነሆ ቢራቢሮ ለምሳ!” አለች፣ በክንፎቿ ክፍት ክድን የቢራቢሮ ሳቅ እየሳቀች፡፡ ሽው! ብሎ ወረደ - ለቢራቢሮ ሞትን የጫነ ድምቢጥ! ከሰማይ ያመጣችው ጦር ጥልቅ ሲልበት፣ ከህመሙ ይልቅ መገረሙ፣ መደንገጡ ብሶበት እዚያው ክንችር አለ፡፡ “አይ አቶ ድምቢጥ! ለካ የተጫንከው የኔን ሳይሆን የራስክን ሞት ኖሯል! ተመስገን!” እያለች ቢራቢሮ ሆዬ፣ ጦሩን ከድምቢጥየው ሬሳ ላይ ለመንቀል ብትሞክር ብትፍጨረጨር፣ እሷ ትቦጨቅ እንደሆነ እንጂ ጦሩ የማይነቃነቅ ሆነ፡፡ ደሞስ የደሙ ክርፋት! “እንግዲያውስ ጦር ምን ሊያደርግልኝ ኖሯል? ገድያቸው እንዲህ ከሚገሙኝ፣ እንዲህ እንደ ሰይጣን ፈስ ከሚከረፉኝ፣ ብቅ ሲሉ ክንፌን እጥፍ አድርጌ አልሰወርባቸውም? ይሻለኛልም ይቀለኛልም አለችና ጦሩን እዚያው ለድምቢጡ “ማስታወሻ ይሁንህ፣ ትቼልሀለሁ” እያለች ወደ ሰፈሯ ሄደች (ማለቴ በረረች)

 ሌላ የቢራቢሮ ምእራፍ (ማለቴ በረራ) እነሆ፡- ውድቅት ነው፡፡ ፍጡራን እንደየ ፍጥርጥራቸው በየፊናቸው ሲመገቡ አርፍደው፣ እንደአይነታቸው ውሀ ቸውን ጠጥተው፣ በየስፍራቸው እፎይ ብለው በማረፍም በማንቀላፋትም ላይ ናቸው፡፡ ይህን ጊዜ ቢራቢሮ አበባ ላይ ተመቻቸችና እዝጌር የሰጣትን፣ ከአንበሳ ጩኸት ሰባት ጊዜ ጐልቶ የሚጮኸውን አዲስየውን ጩኸቷን ለቀቀችው! ፍጡራን ከመበርገግ የባሰ በረገጉ፣ ብዙ ሯጮች ወለም አላቸው፣ በርካታ በራሪዎች ክንፋቸውን ቅርንጫፍ አቆሰላቸው፡፡ ፍጡር ሁሉ በየበረገገበት እንደየፍጥርጥሩ አደፈጠ፡፡ ብዙ ብዙ ቆይቶ በየፊናው አደጋውን ለማየት እዚህም እዚያም ተገላመጠ፡፡ ማንም የለም፡፡ ቀስ በቀስ ወደየስፍራቸው ተመለሱ፡፡ “እኔ ብቻ ሳልበረግግ” አለች ቢራቢሮ “እሱን ተይው! ያልበረገገ የለም” አሉዋት “ከኔ በስተቀር” “ኧረ ባክሽ? አሁንስ አንጎልሽም እንደ በረራሽ አበደ'ንዴ? አንበሳ ራሱ በርግጓል እንኳን አንቺ” “ሸረሪት ትጠየቅ” አለችና ቢራቢሮ የውልብልብ እየበረረች ሄደች … … እንግዲህ ሸረሪት ስትበረግግ መብረር ወይ መሮጥ ሳይሆን፣ ጥልቅ! ድብቅ! ሽፍን! ነው በዚያ በድርዋ - የምግብ ማግኛ መሳሪያዋ - ልብሷ - ቤትዋ - እንቁላል መጣያዋ - በጥበቧ ከገዛ ውስጧ የፈጠረችው ድርዋ፡፡ የምን ከንቱ ልፋት? ጥበቡን ሰጥቷታል፡፡

እና ከተሸሸገችበት ቀስ ብላ ብቅ ብትል፣ ቢራቢሮ ሆዬ አበባዋ ዙሪያ እየበረረች፣ ራሷን በራሷ እያባረረች በሳቅ ትንከተከታለች - የክንፍ ሳቅ “በረራሽ የእብድ መሆኑን አይቻለሁ” አለቻት ሸረሪት፡፡ ግን ፍጥረትን በሙሉ የሚያስበረግግ ጩኸት ሲያስቅሽ ሰባቴ ነው ያበድሽው፣ አንዴም አይደለ” “ያላስበረገገኝ ምክንያቱ የጮህኩት እኔ ራሴ ስለሆንኩ ነው’ኮ!” አለቻት - ቀለማት ክንፎቿን እያክነፈነፈች፡፡ “እየባሰብሽ ሄደ፡፡ አሁንማ ሰባ ጊዜ ሰባት አበድሽ!” ቢራቢሮ በረራዋን ትታ አበባዋ ላይ ቆመች - ተቀመጠች - ተሰየመችና፡- “አንቺ ተአምራዊ ድር ሊኖርሽ ከቻለ፣ እኔ ሃያል - መርእድ - መደንግጽ ጩኸት ሊኖረኝ ለምን አይችልም? ወይስ የተፈጥሮን ምስጢር ሁሉ ታውቂዋለሽ?” ሸረሪት ብዙ ስለማትንቀሳቀስ በጥሞና ለማሰብ ጊዜ አላት፡፡ ያውም ከድርዋ እኩል ተአምር የሆኑ ሀሳቦች፡፡

እርጋታ አለ ሸረሪት ቤት (ማለቴ ድር) ተረታችን ውስጥ፣ የመነኑት ባህታውያን እርጋታን ለመማር ወደ ሸረሪት ያተኩራሉ፣ ለሰባት ሙሉ ሰአት! (ያሬድ ማህሌታይን ሰባት አመት እናስታውሳለን) ስለዚህ ሸረሪት በእርጋታ “አሳምኚኝ” አለቻት ቢራቢሮን፤ “አዳሜ ፍጡሬ ከብርገጋዋ ተመልሳ በየስርፋዋ ታርፋለች፣ እማደል? ያን ጊዜ ትኩር ብለሽ እዪኝ፡፡ እጮሀለሁ፣ ይበረግጋሉ፡፡ አንቺ ግን ስጮህ እያየሽኝ ስለሚሆን አትደነግጪም” እንደተባባሉት ፍጡር ሁሉ እንደየድፍረትዋ፣ በየተራዋ በየስርፋዋ ተመልሳ አረፈች፡፡ ቢራቢሮ ለምናልባቱ ሸረሪትን ለማስጠንቀቅ ጥቂት በራረረች … አበባዋ ላይ አረፈች … እና ድምፁን … ጩኸቱን … ከፈጣሪ ቤት ያመጣችውን (እና፣ እብድም ይጠነቀቃልና፣ በጥንቃቄ የክንፏን ቀለም አስመስላ ክንፉ ላይ ለጥፋ ደብቃው የነበረውን ጩኸት) አነሳችና፡- አንድ ጊዜ ስትጮኸው ጊዜ፣ ፍጡሬ አዳሜ እንደ ቅድሙ አልበረገገላችሁም!? ቢራቢሮ እየበረረች ባበባዋ ዙሪያ በክንፏ ስትስቅ … ስትስቅ … ስትስቅ … “እሽ! እስቲ ዝም በይ አንዴ” አለቻት ሸረሪት “ሳይመለሱ ስሚኝ፣ ሲመለሱ ምንም እንደማናውቅ እናስመስል፡፡

በኋላ በየስርፋቸው ጩኸትሽን ስጪኝና አንዴ ልጩኸው” “እኔ ገና አልጠገብኩትማ!” “ተይ ተይ ተይ! አንዴ ብቻ? እሺ እንለዋወጥ፡፡ ያንቺን ጩኸት ላንዴ ብቻ ስጪኝ፣ የኔን ድር ጥበብ አስተምርሻለሁ፡፡ አቤት አንዴ ብትወዘውዢ! በኔ ድር! ሸሪሪት በሆንኩ! ትያለሽ፡፡” “እሺ” አለቻትና ተለዋወጡ፡፡ ቢራቢሮ በሀር ክር ጥቂት ከተወዛወዘች በኋላ ሰለቻትና “እንቺ ድርሽን፡፡ እኔ መሄዴ ነው” አለቻት “አንዴ’ንኳ ሳልጮህባቸው? ያውም እሺ ብለሽኝ?” “ኧረ አስር ጊዜ ጩሂ ተፈለግሽ! ጩኸቱን መርቄልሻለሁ” “ገና አልጠገብኩትም አላልሽም?” “አሁን ጠገብኩታ” አለችና ቢራቢሮ፣ የውልብልብ እየበረረች ሄደች “ደሞ ጩኸት ምን ያደርግልኛል?” እያለች ለራሷ “ትርፉ ሸክም!” ሸረሪትም “ቢራቢሮን ያሳበድክ ተመስገን!” እያለች ጩኸቱን ለእንስሳቱ እያከራየች እጅጉን ከበረች፡፡ ምን መክበር ብቻ? ሚሊዬነር ሆነች፡፡ ለፈጣሪ ምን ይሳነዋል? እያለች

“ለልጆቻችን ደህንነት ለማይጨነቁ ልበቢሶች ነው የሰራሁት” ካናዳዊው ኮሜዲያን ጂም ኬሪ የጦር መሳርያ የመታጠቅ መብትን ለመቃወም “ኮልድ ዴድ ሃንድ” የተሰኘ የሙዚቃ ቪድዮ በመስራት እንዳሰራጨ ተገለፀ፡፡ “ፈኒ ኦር ዳይ” በተባለ ድረገፅ የተለቀቀውን ይሄን ክሊፕ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ሰው እንደተመለከተው የዘገበው ፎክስ ኒውስ፤ በኮሜዲያኑ ላይም ከፍተኛ ትችት እንደቀረበበት ጠቁሟል፡፡ ጂም ኬሪ ከአራት ዓመት በፊት ህይወቱ ያለፈውን የቀድሞ ተዋናይ እና የ“ናሽናል ራይፍልስ አሶሴሽን” ፕሬዝዳንት የነበረውን ቻርልስ ሄስተን ገፀባህርይ በመላበስ በካንትሪ ስልት ሙዚቃውን ተጫውቷል፡፡ በክሊፑ ላይ ጆን ሌነን፤ ማህተመ ጋንዲ እና አብርሃም ሊንከልንም ተተውነዋል፡፡

እስከ 10 ሚሊዮን የሚደርሱ አድናቂዎቹ በሚከታተሉት የትዊተር ማስታወሻው ላይ ጂም ኬሪ በፃፈው መልእክት፤ የሙዚቃ ቪድዮውን ለልጆቻችን ደህንነት ለማይጨነቁ ልበቢሶች ነው የሰራሁት ብሏል፡፡ በአሜሪካ ጦር መሳርያ የመታጠቅ መብት እንዲታገድ መጠነ ሰፊ ቅስቀሳ ሲካሄድ ቢሰነብትም ጦር መሳርያ የመታጠቅ መብትን የሚከለክል ህግ እንዲወጣ የሚደረገው ጥረት ስኬታማ መሆኑ ያጠራጥራል እየተባለ ነው፡፡ የኒውዮርክ ከንቲባ ማይክል ብሉምበርግ እስከ 12 ሚሊዮን ዶላር በጀት ይዘው የፀረ ጦር መሳርያ እንቅስቃሴ እያካሄዱ መሆኑን የዘገበው ብሉምበርግ ኒውስ ፤ በተቃራኒው በአሜሪካ መንግስት ከፍተኛ ተፅእኖ ያላቸው 15 ዴሞክራት እና ሪፐብሊካን ሴናተሮች የጦር መሳርያ የመታጠቅ መብትን ለመከልከል የተያዘውን ዘመቻ በይፋ እየተቃወሙ እንደሆነ አመልክቷል፡፡ ከ32 በላይ ፊልሞችን የሰራውና በመላው አለም እስከ 2.4 ቢሊዮን ዶላር የሚደርስ ገቢ ያስገባው ኮሜዲያን ጂም ኬሪ ፤ ቢያንስ 12 ያህል ፊልሞቹ ከ100 ሚሊዮን ዶላር በላይ ገቢ እንዳስገኙለት ይታወቃል፡፡

የብሪታኒያ ተዋናዮች በሆሊውድ ፊልም ሰሪዎች ተመራጭ እና ተፈላጊ እየሆኑ መምጣታቸውን ዘ ሆሊውድ ሪፖርተር አስታወቀ፡፡ በማራኪ የእንግሊዘኛ ቋንቋ አነጋገር፤ በምርጥ የትወና ብቃታቸው፤እንዲሁም በሚጠይቁት ተመጣጣኝ ክፍያ የእንግሊዝ ተዋናዮች ተመራጭ ሆነዋል ተብሏል፡፡ በበርካታ የሆሊውድ ፊልሞች መሪ ተዋናይነት በመስራት እና በመልመል አሜሪካውያኑን ከገበያ እያስወጡ እንደሆነም ዘ ሆሊውድ ሪፖርተር ዘግቧል፡፡

የእንግሊዝ ምርጥ የትወና ብቃት በሲኒማ ብቻ ሳይሆን በቲቪ ተከታታይ ፊልሞችም እየታየ ሲሆን በአሜሪካ የቴሌቭዥን ጣቢያዎች በአሜሪካውያን ህይወት ላይ የሚያጠነጥኑ ፊልሞች ላይ ሳይቀሩ እንግሊዛውያኑ በብዛት እየተወኑ ነው፡፡ የታላቋ ብሪታኒያ የፊልም ኢንዱስትሪ 100ኛ ዓመት ክብረ በዓል ከወር በኋላ ንግስት ኤልዛቤት በሚገኙበት እንደሚከበር የገለፀው ዘጋርድያን፤ በዚሁ ስነስርዓት ላይ በሆሊውድ ከፍተኛ ተቀባይነት ያገኙ የብሪታኒያ ምርጥ ተዋናዮች ይመሰገናሉ ብሏል፡፡

ድሮ ድሮ በሆሊውድ ፊልሞች የመጥፎ ገፀባህርያት ሚና ይሰጣቸው የነበሩ የብሪታኒያ ተዋናዮች፤ ከቅርብ አመታት ወዲህ ግን በከፍተኛ በጀት በተሰሩ፤ ታሪካዊ ይዘት ባላቸው እና በሱፐር ሂሮ ፊልሞች ላይ መተወን ይዘዋል፡፡ በሆሊውድ የእንግሊዞቹ ዋና ተፎካካሪዎቻቸው አውስትራሊያውያን ብቻ እንደሆኑም ታውቋል፡፡ አንቶኒ ሆፕኪንስ፤ ማይክል ኬን፤ ጋሪ ኦልድማን፤ ሲን ኮነሪ፤ሁውጅ ግራንት፤ራልፍ ፊነስ በሆሊውድ በግንባር ቀደምነት የሚጠቀሱ የእንግሊዝ ተዋናዮች ናቸው፡፡

በ“ሊንከለን” ፊልም ላይ የተወነው እንግሊዛዊው የፊልም ባለሙያ ዳንኤል ዴይ ሊውስ ለሶስተኛ ጊዜ በምርጥ ተዋናይነት የዘንድሮን ኦስካር በመውሰድ ሪከርድ ያስመዘገበ ሲሆን ባለፉት አምስት ዓመታት ከአምስት በላይ የብሪታኒያ ተዋናዮች የኦስካር ሽልማቶችን እንደወሰዱ ይታወቃል፡፡ 2013 ከገባ ወዲህ ክርስትያን ቤል፤ጃሬድ ሃሪስ፤ ዳንኤል ዴይ ሊውስ፤ ኢድሪስ ኤባ እና ሌሎች እንግሊዛውያን ተዋናዮች በምርጥ የሆሊውድ ፊልሞች ላይ በመሪ ተዋናይነት በመተወን ተወዳዳሪ አልተገኘላቸውም፡፡

የሊል ዋይኔ አዲስ አልበም ‹‹አይ አም ኖት ኤ ሂውማን ቢንግ 2›› በሳምንቱ አጋማሽ ላይ ለገበያ የቀረበ ሲሆን ሽያጩ እንደሚደራለት ከወዲሁ ተገምቷል፡፡ ከሳምንት በፊት ሊል ዋይኔ ከድንገተኛ የልብ ህመም ጋር በተገናኘ በገጠመው የጤና እክል ከሞት አፋፍ እንደተረፈ ተዘግቧል፡፡ በማህበረሰብ ድረገፆች አነጋጋሪ በመሆን በአንድ ሳምንት ውስጥ ከቀድሞው የ19ኛ ደረጃ ወደ ሁለተኛ ደረጃ የተመነደገው ራፐሩ፤ አጋጣሚው ለአዲሱ አልበሙ ጥሩ ማሻሻጫ ይሆንለታል ተብሏል፡፡ ራፐሩ ከሚወስደው ሃይል ሰጭ መጠጥ ጋር በተያያዘ ለህይወቱ የሚያሳስብ አደገኛ ደረጃ ላይ ደርሶ እንደነበረ ያወሱት ዘገባዎች ፤ ሆስፒታል ገብቶ በተደረገለት ከፍተኛ የህክምና ክትትል ህይወቱ እንደተረፈ ጠቁመዋል፡፡ ሊል ዋይኔ የገጠመው የጤና እክል ከጭንቀት ጋር በተያያዘ የተፈጠረ እንጅ በአደገኛ እፅ ተጠቃሚነት አለመሆኑን ያስተባበለው የአሳታሚው “ካሽ መኒ” ስራ አስኪያጅ ፤ በቂ እረፍት በመውሰድና ራሱን በማዝናናት ጤንነቱ እንደሚመለስለት ተናግሯል፡፡

ከ2013 ምርጥ አልበሞች አንዱ እንደሚሆን ተስፋ የተጣለበት የሊል ዋይኔ አዲስ አልበም በከፍተኛ ጉጉት ሲጠበቅ እንደቆየ የዘገበው ሮሊንግ ስቶን መፅሄት፤ በአልበሙ ላይ ኒኪ ማንጅ፤ ድሬክ፤ ቢግ ሲን፤ ገን ፕሌይ እና ሌሎች ራፐሮች በአጃቢነት እንደሰሩ አመልክቷል፡፡ የአልበሙን ሽፋን ምስል የሰራለት የሂፖፕ ሙዚቀኛው ካናዬ ዌስት እንደሆነ የገለፀው መፅሄቱ ፤ ሊል ዋይኔ የዓለም ምርጥ ራፐር መሆኑን ካናዬ መመስከሩንም ጨምሮ አስታውቋል፡፡ ራፐሩ ከሁለት ዓመት በፊት ‹‹አይ አም ኖት ኤ ሂውማን ቢንግ›› በሚል ስያሜ የመጀመርያውን የአልበሙን ክፍል ለገበያ እንዳበቃ የሚታወስ ነው፡፡ ሊል ዋይኔ ከአዲሱ አልበሙ ‹‹አይ አም ኖት ኤ ሂውማን ቢንግ 2›› በኋላ አጠቃላይ የስራዎቹን ብዛት 11 ያደረሰ ሲሆን በሙዚቃ ህይወቱ 95 ሚሊዮን ዶላር የሚደርስ ሃብት ማፍራቱን ለማወቅ ተችሏል፡፡

Saturday, 30 March 2013 16:03

አዳዲስ ፊልሞች

አዲስ አበባ የሚገኘው የብራዚል ኤምባሲ ዘንድሮ ለሁለተኛ ጊዜ ያዘጋጀውና ከየካቲት 22 ጀምሮ ሲካሄድ የሰነበተው የብራዚል የባህል ፌስቲቫል ነገ በኤምባሲው በሚቀርብ የሙዚቃ ዝግጅት ይጠናቀቃል፡፡ የካቲት 22 ቀን 2005 ዓ.ም ሸራተን አዲስ በሼፍ ክርስቲያኖ ላና፤ በሸራተን አዲስ በቀረበና ለስምንት ቀናት በዘለቀ የምግብ ፌስቲቫል የተጀመረው ዝግጅት፤ ከመጋቢት 2 እስከ መጋቢት 7 በቆየ የፊልም ፌስቲቫለ የቀጠለ ሲሆን “The Passion of Brazilian Football” በሚል ርእስ መጋቢት 11 የጀመረው የፎቶግራፍ አውደርእይም ዛሬ ይዘጋል፡፡ የኤምባሲው አንደኛ ፀሐፊ እና የባህል አታሼ ሚስተር ማርሴሎ ቦርሄስ ለአዲስ አድማስ እንደገለፁት፤ ዛሬ ማታ በኤምባሲው የሚደረገውን መዝጊያ ፊደል የሙዚቃ ባንድ ያቀርባል፡፡

ታላቁን የኢትዮጵያ የዜማ አባት ቅዱስ ያሬድ 1500ኛ ልደት ምክንያት በማድረግ የተዘጋጀ የህይወት ታሪኩን እና ሥራዎቹን የተመለከተ መፅሐፍ ታተመ። በአቶ ታደሰ አለማየሁ የተዘጋጀው ባለ 202 ገፆች መፅሐፍ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስትያን ሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምርያ ማህበረ ቅዱሳን አሳትሞ እያከፋፈለው ነው፡፡ ይኸው መፅሐፍ ዛሬ ከቀኑ 8 ሰዓት በብሔራዊ ቤተመዘክር ትልቁ አዳራሽ እንደሚመረቅ ከማህበሩ የተገኘው መግለጫ ያስረዳል። በመፅሐፉ ውስጥ ከተካተቱ ርእሰ ጉዳዮች መካከል የዘፈን እና የመዝሙር ልዩነትን ይመለከታል፡፡ የመፅሐፉ ዋጋ 50 ብር ነው፡፡

Saturday, 30 March 2013 15:30

ኃይሌ በ40 ዓመቱ ይሮጣል

በሃዋሳ በስሙ የሚያዘጋጀው ማራቶን ትኩረት እያገኘ ነው በቅርቡ 40ኛ ዓመቱን የሚይዘው ኃይሌ ገብረስላሴ በ “ግሬት ማንችስተር ራን” እንደሚሳተፍ የውድድሩ አዘጋጆች አስታወቁ፡፡ ስለተሳትፎው የተጠየቀው ኃይሌ ‹‹ሩጫ ስለሚያስደስትኝ መሮጤን እቀጥላለሁ፤ መቼ እንደሚያበቃልኝ አላውቀውም፤ ወደ ማንችስተር ተመልሼ ለመወዳደር የምችልበትን እድል መተው አልችልም›› ብሏል፡፡ ኃይሌ በ “ግሬት ማንችስተር ራን” የ10 ኪሎሜትር ሩጫ ለ6 ጊዜያት ሲያንፍ፤ ላለፉት አምስት ተከታታይ ዓመታት የውድድሩ አሸናፊ ነበር፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ዘንድሮ “ኃይሌ ገብረስላሴ ማራቶን” በሃዋሳ ከተማ መካሄዱ ትኩረት እየሳበ ነው፡፡ የውድድሩ አምባሳደር አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ ለተሳታፊዎች ባቀረበው በጥሪ ለ20 ዓመታት ካሳለፈው የሩጫ ዘመን በኋላ ዓለምን ወደ አገሩ ኢትዮጵያ ሲጋብዝ በታላቅ ጉጉት እንደሆነ ገልጿል፡፡

የኃይሌ ገብረስላሴ ማራቶን በኢትዮጵያ በአውሮፓ እና በአሜሪካ ከፍተኛ ልምድ ያላቸው የውድድር አዘጋጆች በተሰባሰቡበት ቡድን የሚመራ ሲሆን ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀና ቀለሙ ኢትዮጵያዊ ማራቶን ነው ተብሏል፡፡ ከ1200 በላይ ተሳታፊዎች እንደሚኖሩት ከሚጠበቀው ኃይሌ ገብረስላሴ ማራቶን ጋር በመያያዝ የግማሽ ማራቶን፤ የ5 ኪሎሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ እና የህፃናት ውድድሮችም ይደረጋሉ፡፡በውድድሩ ኦፊሴላዊ ድረገፅ በቀረበው መረጃ መሰረት በኃይሌ ገብረስላሴ ማራቶን ተሳታፊ ለሚሆኑ ራጮች የጉብኝት ፕሮግራም የተዘጋጀ ሲሆን የኢትዮጵያን ባህልና ታሪክ ለማስተዋወቅ ታስቧል፡፡ የኃይሌ ገብረስላሴ ማራቶን ጋር ተያይዞ በሚደረገው የገቢ ማሰባሰብ 200ሺ ዶላር ለእንጦጦ ፋውንዴሽን እንደሚበረከትም ታውቋል፡፡ በኃይሌ ገብረስላሴ ማራቶን በሁለቱም ፆታዎች ለሚያሸንፉ አትሌቶች ለእያንዳንዳቸው 12 ወቄት ወርቅ ይሸለማል፡፡

ለውድድሩ መሮጫ የተመረጠችው የሃዋሳ ከተማ ከዓለም አቀፉ የአማተር አትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር ጋር በሚደረግ ትብብር በቀጣይ ወራት የእውቅና ሰርተፍኬት ለውድድሩ አዘጋጅነት ይሰጣታል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ በተያያዘ ዜና ባለፈው ሳምንት በፖላንዷ ከተማ ባይድጎስዝ በተደረገው 40ኛው የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ኬንያ 5 ወርቅ በማግኘት ስኬታማ ስትሆን ኢትዮጵያ በግልና በቡድን 10 ሜዳልያዎች በመሰብሰብ ከፍተኛ ውጤት አስመዘገበች፡፡ በሻምፒዮናው አጠቃላይ የውጤት ሰንጠረዥ ኬንያ 5 ወርቅ፤ 3 ብርና 1 ነሐስ በመውሰድ አንደኛ ሆና ጨርሳለች፡፡ ኢትዮጵያ በ3 የወርቅ፤ 4 የብርና 3 የነሐስ ሜዳልያዎች በማግኘት ሁለተኛ ሆና በሻምፒዮናው በአዋቂ ወንዶች 12 ኪሎ ሜትር፤ በአዋቂ ሴቶች ስምንት ኪሎ ሜትር እንዲሀም በወጣት ሴቶች የ4 ኪሎ ሜትር ውድድሮች ኬንያውያን የወርቅ ሜዳልያዎችን በመሰብሰብ ውጤታማ ሆነዋል፡፡

የኢትዮጵያው አትሌት ሃጎስ ገብረ ህይወት በወጣት ወንዶች 6 ኪሎ ሜትር ብቸኛውን የወርቅ ሜዳልያ ድል አስመዝግቧል፡፡ ከ32 አገራት የተወከሉ 102 አትሌቶች በተሳተፉበት የአዋቂ ወንዶች 12 ኪሎ ሜትር ውድድር በቡድን ውጤት ኢትዮጵያ 1ኛ ደረጃ ስትወስድ አሜሪካና ኢትዮጵያ ተከታታዩን ደረጃ ወስደዋል፡፡ ከ29 አገራት የተወከሉ 97 አትሌቶች በተሳተፉበት የአዋቂ ሴቶች 8 ኪሎ ሜትር ውድድር ደግሞ በቡድን ውጤት ኬንያ 1ኛ ደረጃ ስትወስድ ኢትዮጵያና ባህሬን ተከታታዩን ደረጃ ወስደዋል፡፡