- ዶ/ር አረጋ ይርዳው (የሚድሮክ ዋና ሥራ አስፈፃሚ)

       በኩባንያችን በኩል ባለፈው አመት የተከናወኑት ተግባራት በሙሉ አመርቂ ነበሩ፡፡ በተለይ በቴክኖሎጂ ግሩፑ አካባቢ ጥሩ ስራ ነው የተሠራው፡፡ በቀጣይ ደግሞ በተለይ የመብራት አገልግሎቱ መሻሻልና የባቡር ዝርጋታው መጠናቀቅ፣ በሀገራችን ያለውን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ መልካም ያደርጉታል የሚል እምነት አለኝ፡፡ በአጠቃላይ 2007 እና ከዚያ በኋላ ያለው ዘመን ለኢንቨስትመንቱ አመቺ ይሆናል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ቴክኖሎጂ ግሩፑን በተመለከተ የወርቅ ምርት የመሳሰሉትን ሥራዎች እያስፋፋን ነው፡፡ የምናስፋፋበትም ምክንያት እስከዚያ መብራቱም ይደርሳል ብለን ስለምናስብ ነው፡፡ በአጠቃላይ በአገራችን የሚታየው ነገር ተስፋ ሰጪ ነው፡፡ በተረፈ ለኢትዮጵያ ህዝብ ዘመኑ የሰላም፣ የጤናና የብልጽግና እንዲሆን እመኛለሁ፡፡

Published in ህብረተሰብ
Saturday, 20 September 2014 10:43

የሚዲያ ጥቅም ያልገባት ሀገር!

የማስተካከያ መልዕክት ለተወዛገበውና ላወዛገበው ኢቴቪ

       ውድ አንባብያን፤ ባለፈው ዓመት መጨረሻ ላይ ተገናኝተን ነበር፡፡ ከሁለት ሳምንት በኋላ እነሆ በዚሁ ነጻ አስተያየት ዓምድ ዛሬ ተገናኘን፡፡ እንኳን አደረሰን! ሰሞኑን የመነጋገርያ አጀንዳ በሆነውና በኢቴቪ በተላለፈው “ያልተገሩ ብዕሮች” የተሰኘ ዘጋቢ ፊልም ዙርያ አንዳንድ ጉዳዮች በመመዘዝ ላይ ይገኛሉ፡፡ በዚህ በርካታ የሙያ ክፍተት ባስተናገደው ዘጋቢ ፊልም ላይ በእንግድነት ተጋብዤ ቃለ መጠይቅ መስጠቴን ባለፈው ጊዜ መግለጼ ይታወሳል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ኢቴቪ (ኢብኮ) የጋዜጠኝነት ሙያ ከሚጠይቀው አግባብ ውጪ በሆነ መልኩ በርካታ ነገሮች ተቆራርጠው ጣቢያው የሚፈልገውን መልዕክት ማስተላለፍ እንደቻለ ማስረጃዎችን በማካተት በዝርዝር አቅርቤ ነበር፡፡ ይህን ተከትሎ አቶ ታምራት ደጀኔ የተባሉ ወዳጄ፣ በዚሁ ዓምድ “አድርባይነት የተጠናወተው የምሁሩ አስተያየት” በሚል ርዕስ፣ ከዕውቀት የጸዳ ምላሻቸውን አስፍረዋል፡፡ ምንም እንኳን ላቀረቡት ያልሰለጠነ ሂሳቸው ሙሉ አክብሮት ቢኖረኝም፤ አስተያየታቸው ከዘጋቢው ፊልም ያልተናነሰ በርካታ ክፍተቶች እንዳሉበት ግን ለመገንዘብ ችያለሁ፡፡

በመሆኑም ኢቴቪን “ገለልተኛ” ነው ለማለት የደፈሩት እኝህ አስተያየት ሰጪ፤ የማስተካከያ ምላሽ ካልተሰጣቸው በተሳሳተ መንገድ ህዝቡን ማሳሳታቸው እንደማይቀር ግልጽ ነው፡፡ በመጀመሪያ ስህተታቸውን ለማረም ዝግጁ ከሆኑ አንዳንድ ማስተካከያ ባጭሩ ልስጥ፡፡ አቶ ታምራት፤ ለመሆኑ ኢቴቪ ገለልተኛ ነው ለማለት ያስደፈራቸው ምን ይሆን? ለነገሩ የኢቴቪን ገለልተኛነት ደግፎ ለመከራከር በዕውቀት የተመሰረተ ምክንያት ማጣታቸውን ምክንያት አልባው ምላሻቸው ይናገራል፡፡ ወዳጄ፤ ገለልተኝነት በጋዜጠኝነት መነጽር ሲታይ፣ ከሌሎች ዘርፎች ለየት የሚያደርጉት አንዳንድ ነጥቦች አሉ፡፡ እርስዎ እንዳሉት፤ የፖለቲካው ብቻ ሳይሆን፤ ከማንኛውም ዓይነት ተፅዕኖ ነጻ መሆን (distance from faction) ነው፡፡ ስለዚህ አንድ ጋዜጠኛ መረጃውን አሰባስቦ ካበቃ በኋላ ሙያዊ ስነምግባሩን ተከትሎ ህዝቡ ዘንድ መድረስ ያለበትን በነጻነት ማቅረብ ይጠበቅበታል፡፡ ከዚሁ ጋር ተያይዞ የሚነሳው የጋዜጠኝነት መርህ ደግሞ የተገኘውን መረጃ ትክክለኛነት ማረጋገጥ (verification) ነው፡፡ ይህ መርህ ጋዜጠኝነት ከልቦለድ፣ ፕሮፓጋንዳና ማስታወቂያ የመሳሰሉት የጥበብ ስራዎች የተለየ ያደርገዋል፡፡ ይህን መርህ አንዳንድ ምሁራን ሲያብራሩ፤ ማንኛውም ጋዜጠኛ እናቱ እንኳን እወድሃለው ብትለው ማረጋገጥ እንዳለበት ይመክራሉ፡፡

የእናት ፍቅር በመጠራጠራቸው ሳይሆን ደጋግሞ ማጣራትና ማረጋገጥ ትልቁ የጋዜጠኝነት መርህ መሆኑን ለማስታወስ ነው፡፡ ስለ ሁለቱም ተያያዥ መርሆች ይህን ያህል ካነሳሁ፣ አሁን ወደ ኢቴቪ ልመለስ፡፡ ኢቴቪ በብቸኛ የዜና ምንጭነት ጋዜጣዊ መግለጫ (press release) ወይም የህዝብ ግንኙነት ባለሙያዎች የሚያዘጋጁትን ዜና በስፋት እንደሚጠቀም የተለያዩ ጥናቶች ይጠቁማሉ፡፡ በየትኛውም ሚዲያ እነዚህን የዜና ምንጮች እንደብቸኛ የዜና ምንጭ አድርጐ መጠቀም አይመከርም፡፡ ምክንያቱም ህዝብ ግንኙነት ለሚሰራበት ድርጅት በጐ ገጽታ ግንባታ የሚተጋ ሲሆን ጋዜጠኝነት ግን ከዚህ በተለየ መልኩ እውነታውን ለህዝቡ ለማሳወቅ የሚታትር በመሆኑ ነው፡፡ እና ታዲያ የቱ ጋ ነው ገልተኝነቱ? በተዘዋዋሪ ኢቴቪ የተለያዩ ድርጅቶችን (ገዢውን ፓርቲ ይጨምራል) በጐ ገጽታ በመገንባት የራሱ ሚና ይጫወታል ማለት ነው፡፡ ሌላው አቶ ታምራት አንስተውት በተሳሳተ መንገድ ካቀረቡት መርህ አንዱ ሚዛናዊነት ነው፡፡ ሚዛናዊነት የሚባለው አንድ ፕሮግራም የተለያዩ አመለካከቶችን ተገቢ (fair) በሆነ መልኩ ሲያቀርብ ነው፡፡ ይህም ማለት በኢቴቪ ዶክመንታሪ ላይ የግል ሚዲያውን በመደገፍ፣አሳማኝ ምክንያቶችን ማቅረብ የሚችል ማንኛውም ሰው በዚሁ ሚዛናዊ ያልሆነው ዘጋቢ ፊልም ላይ መቅረብ ነበረበት፡፡ እነዚህ የተለያዩ አመለካከቶች ተመጣጣኝ የሆነ የአየር ሰዓት ሊሰጣቸው እንደሚገባ የዘርፉ ምሁራን ይገልጻሉ፡፡

ይህም ተመልካቹ በጉዳዩ ዙርያ የተሟላ ምስል እንዲኖረው ያስችላል፡፡ የሚያሳዝን የሙያ ግድፈቶችን ያስተናገደው ዘጋቢ ፊልሙ፤ተመሳሳይ መልዕክት ከማስተላለፉ በተጨማሪ ሚዛናዊ አለመሆኑ ለመረዳት እኔ ያቀረብኩት ሐሳብ መቆረጡ ማሳያ ነው፡፡ አስተያየት ሰጪው፣ ይህን ዘጋቢ ፊልም ለማድነቅ ምን ይሆን የገፋፋዎት? አንድ ዘጋቢ ፊልም ሲሰራ ታሳቢ መሆን ካለባቸው ነገሮች አንዱና ትልቁ ነገር ጥናት (research) ነው፡፡ ይህንን እንዳለመታደል ሆኖ በኢቴቪ በሚሰሩት ዘጋቢ ፊልሞች ላይ አንመለከተውም፡፡ እንደ ምሳሌ ቢቢሲና ሲኤንኤንን በመሳሰሉት ትልልቅ የመገናኛ ብዙሃን፣ በበቂ ጥናት ላይ ታግዘው የሚሰሩ ሚዛናዊ የሆኑ ዶክመንተሪዎቻቸውን ማየት በቂ ነው፡፡ ምንም እንኳን የቴክኖሎጂና ሌሎች ልዩነቶች ቢኖሩም ሙያው የሚጠይቀውን ዘጋቢ ፊልም ለመስራት ግን ህዝብን በቅንነት የማገልገል ፍላጎት በቂ ይመስለኛል፡፡ አስተያየት ሰጪው እኔ ባቀረብኩት ሐሳብ ላይ ትኩረት በማድረግ፣አስተያየታቸውን በምክንያት በማስደገፍ ማቅረብ ሲገባዎ፣ “አድርባይነት፣ ያዙኝ ልቀቁኝ…” በመሳሰሉት ቃላት እኔን ለመግለፅ ሞክረዋል፡፡ ቁምነገሩ እኔ የሰጠሁት አስተያየት መቆረጡ ብቻ ሳይሆን ኢቴቪ ሚዛናዊ ባልሆነው ዘገባው ህዝቡን የማሳሳት ዘመቻውን መቀጠሉ ነው፡፡ እንዳለመታደል ሆኖ ባለ አንድ ብሄራዊ የቴሌቪዥን ጣቢያ ባለቤት መሆናችን ነው እንጂ ይህ ጣቢያ እንደዚህ ሰፋ ያለ ትኩረት ስለማግኘቱ እጠራጠራለሁ፡፡ ቢሆንም ግን በዚህ ቴሌቪዥን ጣቢያ ቃለመጠይቅ መስጠት ነውር ነው የሚለውን መልዕክት ለማስተላለፍ ግን አልፈልግም፡፡ ምናልባት በመለፍለፍ ላይ ብቻ የተጠመደው ይህ ድርጅት፤ መስማት ከጀመረ የማስተካከያ እርምጃ በመውሰድ እንዲለወጥ የሁላችንም ምኞት ነው፡፡

ከዚህ በተጨማሪ አቶ ታምራት፤ “ፅንፈኛ” ያሉትን የግሉን ሚዲያ መተቸትን እንደ ጦር መፍራቴን በአስተያየታቸው አንስተው ነበር፡፡ የግል ሚዲያው በተለይ ጋዜጦች የግል አስተያየቶች መጠራቀምያ እየሆኑ መምጣታቸው በጣም ያሳዝነኛል፡፡ ሐሳብን የመግልፅ መብት መበረታታት ቢኖርበትም እነዚህ የግል ሚዲያዎች ሙያው የሚጠይቀውን አንዳንድ ቁልፍ ነጥቦች መዘንጋታቸው ግልፅ ነው፡፡ ለምሳሌ በአንድ የግል ጋዜጣ መካተት ያለበትና ትልቁ የጋዜጠኝነት ስራ የሆነውን የዜና እጥረት ይታይባቸዋል፡፡ ስለዚህ የግሉንና የመንግስት ሚዲያን ለመተቸት የሚያስችል ገለልተኛ የመገናኛ ብዙሃን ስፈልገናል፡፡ የህዝቡ የማወቅ መብቱ መገደቡና አማራጭ የመረጃ ምንጭ (alternative source of information) እየጠበበ መምጣቱ በጣም አሳሳቢ ሆኗል፡፡ ለዚህም ነው የግል ሚዲያውን ህልውና አደጋ ውስጥ ሊጥል የሚችል ማንኛውም ዘመቻ መገደብ የሚኖርበት፡፡ ከሌላው በተለየ መልኩ በሚዲያ ላይ የሚደረገው ማንኛውም አስተያየት በዕውቀት ላይ የተመሰረተ ሊሆን ይገባል፡፡ ይህ ካልሆነ በጨቅላነት እድሜው ላይ የሚገኘው የሚዲያ ኢንዱስትሪ እንዳይጠፋ እሰጋለሁ፡፡ የጥርስ ሀኪም ዓይን እንደማያክም እየታወቀ፣ ለምን ሙያውን ለባለሙያ እንደማንሰጥ ግልጽ አይደለም፡፡ በ1930ዎቹ የአሜሪካ ቀዳሚ እመቤት የነበሩት ኤልኖር ሩስቬልት፤ ሰዎችን በሚወያዩበት ርዕስ ዙሪያ ለሶስት ይከፍሏቸዋል፡፡ የመጀመሪዎቹ ያልሰለጠነ አስተሳሰብ (small minds) ያላቸው ሲሆኑ እነዚህ ሰዎች በግለሰቦች ዙርያ መወያየት ይቀናቸዋል፡፡ ሌሎቹ መካከለኛ አስተሳሰብ (Average minds) ያላቸውና በክስተቶች (events) ዙሪያ የሚነጋገሩ ናቸው፡፡ ከነዚህ በተለየ መልኩ የሰለጠነ አስተሳሰብ (great minds) ያላቸው ሰዎች በበኩላቸው፤ በሀሳብ (idea) ላይ ትኩረት ያደርጋሉ፡፡

ወዳጄ! የቱ ላይ ራስዎትን አገኙት? የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ዕውን ለማድረግ ከተፈለገ፣ መንግስት በቂ የመጫወቻ ሜዳ መፍቀድ አለበት፡፡ ይህ ሜዳ ከማንኛውም ጣልቃ ገብነት የጸዳና ጋዜጠኞች በነጻነት የሚሯሯጡበት መሆን ይኖርበታል፡፡ ጋዜጠኞችም ፕሮፌሽናል መሆን ይኖርባቸዋል፡፡ ጋዜጠኝነት ሀብትን ለመሰብሰብ አልያም ዝናን ፍለጋ የሚገቡበት ሳይሆን ትልቅ ኃላፊነት መሆኑን ተረድተው፣ ህዝብን ለማገልገል ቁርጠኝነት ሊኖራቸው ይገባል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ገለልተኛ የሆነ ዳኛ ያሻዋል፡፡ እነዚህ ተጫዋቾች የሙያ ክፍተት ሲኖርባቸው፣ መንግስት ሳይሆን ይህ ገለልተኛ ዳኛ ሙያዊ አስተያየት የሚሰጥበት ሊሆን ይገባል፡፡ የመገናኛ ብዙሃን ባለቤቶች በበኩላቸው፤ ሚዲያ የግል ስሜታቸውንና ፍላጎታቸውን የሚገልጹበት ሳይሆን ትልቅ የልማትና የዴሞክራሲ መሳርያ መሆኑን አውቀው፣ ሚዲያውና ህዝቡ እንዲቀራረቡ የድርሻቸውን ማበርከት አለባቸው፡፡ በህመም ላይ የሚገኘው የኢትዮጵያ የመገናኛ ብዙሃን መታከም ይኖርበታል፡፡ በርቀት ከመሰዳደብ ተቀራርቦ መወያየት ይበጃል፡፡ መፈቃቀር ባይጠበቅብንም በሰለጠነ መልኩ መነጋገር የግድ ነው፡፡

              ስለ አገራዊነት፣ ጎሰኝነትና አክራሪነት ለመፃፍ፣ ለምን ህንድ ድረስ ትሄዳለህ ልትሉኝ ትችላላችሁ። ይገባኛል። ቢሆንም ግን፣ በህንድ የገጠር መንደር ውስጥ በአንዲት ጦጣ ሳቢያ የተፈጠረው ሰሞነኛ ታሪክ ያስገርማል - የመንደሯ አዋቂ ወንዶች በአንድ ቀን ፀጉራቸውን ወይም ፂማቸውን የተላጩበት ታሪክ። ከ700 በላይ ፂማቸውን ብቻ፣ ከ200 መቶ በላይ የሚሆኑት ደግሞ ፂምና ፀጉራቸውን የተላጩት፣ ለለቅሶ ነው (በሃዘን ምክንያት)። በነገራችን ላይ፣ በአገራችን ነጠላ ማዘቅዘቅ የተጀመረው በአፄ ሃይለስላሴ ዘመን እንደሆነ ያወቅኩት በቅርቡ ነው። ከዚያ በፊትማ፣ ወር ሙሉ በሃዘን መቀመጥና ለተዝካር ጥሪትን ማሟጠጥ፣ ደረትን በድንጋይ ወይም በቡጢ መደለቅ፣ ፊትን መቧጨርና ፀጉር መንጨት፣ መሬት ላይ መንከባለል የተለመደ ነበር። ቅጥ የለሹን የሃዘን ወግ ለመቀየር ዘመቻ ያካሄዱት ራሳቸው አፄ ሃይለሥላሴ ናቸው። ለዚያውም በአዋጅ። የህግ አዋጅ አይደለም - የምክር አዋጅ እንጂ። ሃዘናችሁን ለመግለፅ ነጠላ ማዘቅዘቅ ይበቃል፤ ከሶስት ቀን በላይ አትጥቀመጡ፤ ለተዝካር ጥሪታችሁን አሟጥጣችሁ ቀሪውን ቤተሰብ አታጎሳቁሉ የሚል ሃሳብ የያዘ ነው አዋጁ። ጥሩ የስልጣኔ ምክር ነው። አዋጁ ከምክር አልፎ ህግ እንዲሆን ቢደረግ ኖሮ ግን፣ በነባር ኋላቀርነት ላይ ተጨማሪ አፈናና የነፃነት ጥሰት በሆነ ነበር። ደግነቱ ምክር ነው። እንደአጋጣሚም አርአያነት ታክሎበታል።

ራሳቸው ንጉሡ ልጅ ሞታባቸው ሃዘን የገጠማቸው ጊዜ፣ የራሳቸውን ምክር ተግባራዊ አድርገዋል - ሃዘናቸውን ተቋቁመው። የኋላ ኋላም፣ ፀጉር መላጨት እየቀረና እየተረሳ መጥቷል። ህንዶቹ፣ የሃይለስላሴን ምክር አልሰሙም ማለት ነው። አስገራሚው ነገር፣ ወደ አንድ ሺ የሚጠጉት የትንሿ መንደር ወንዶች ፂምና ፀጉራቸውን የተላጩት የቅርብ ሰው ስለሞተ አይደለም። ቢቢሲ ረቡዕ እለት እንደዘገበው፤ የአካባቢው ነዋሪዎች በድንጋጤ የተሸበሩት፣ በሂንዱ ቤተመቅደሳቸው ውስጥ ከነበሩት ሁለት ጦጣዎች መካከል አንዷ ስለሞተች ነው። የጦጣዋ ሕልፈት፣ በብሔረሰቡ ጥንታዊ ልማድና በሃይማኖታዊ እምነት ተርጓሚዎች ተተንትኖ፤ የሟርት ምልክት እንደሆነ ተነግሯቸዋል። እናማ የጦጣዋን ነፍስ ለመለማመንና ለመሸኘት፣ አንዳች ነገር ማድረግ አለብን ብለው አሰቡ። ቀላል እንዳይመስላችሁ። የመንደሪቷና የአጎራባች ቀበሌዎች ነዋሪዎች ተሰባስበው፣ ትምህርት ቤትና መሥሪያ ቤት ተዘግቶ ነው ሥነሥርዓቱ የተካሄደው።

በሂንዱ እምነት አስከሬኗ ተቃጠሎ አመዱ ባማረ ሸክላ ከተሞላ በኋላ፣ የሃይማኖት መሪዎች ብዙ መቶ ኪሎሜትሮች ተጉዘው፣ እጅግ ቅዱስ እንደሆነ በሚያምኑበት ወንዝ ውስጥ እንዲበትኑት ተደርጓል። ተዝካሯ ደግሞ ባለፈው እሁድ ተከናውኗል።የመንደሪቷ ነዋሪዎች የአቅማቸውን ያህል (ቢመነዘር ወደ 50ሺ ብር ገደማ የሚሆን ገንዘብ) አዋጥተው፤ ተዝካር ደግሰውላታል። ሌላው አስገራሚ ነገር፣ ቢቢሲ ዜናውን ሲዘግብ፣ “ወይ ኋላቀርነት!” የሚል ስሜት ላለማስተላፍ በጣም ተጠንቅቋል። እንዲሁ “ወይ ጉድ!” በሚል መንፈስ ነው የዘገበው። የኔ ጥያቄ፣ “ነገሩ ኋላቀርነት መሆኑን እንዴት በዘገባው አልተካተተም?” የሚል ነው። የሰዎቹን እምነትና ድርጊት የሚከለክል ሃይል ይኑር ማለቴ አይደለም። በሌላ ሰው ላይ ግዴታ እስካልጫኑ ድረስ በጦጣ ህልፈት ሳቢያ መፍራት፣ መላጨትም ሆነ መደገስ መብታቸው ነው። ነገር ግን፤ “ይሄ ነገር ትክክለኛ እምነትና ተገቢ ድርጊት ነው?”፣ ወይስ “ሳይንሳዊ ያልሆነ እምነትና ጎጂ ድርጊት ነው?” የሚል ጥያቄ በቢቢሲ ዘገባ አለመነሳቱ ነው ችግሩ። ጥያቄ ሳያነሳ በዝምታ የታለፈው ለምን ይሆን? ጉዳዩ፣ ከሃይማኖት ስብከትና ከጥንታዊ “የአገር ወይም የብሄረሰብ ባህል” ጋር የተያያዘ ስለሆነ ነዋ። ግን አስተውሉ።

እንዲህ አይነት ታሪክ በእንግሊዝ ወይም በአሜሪካ ቢፈጠር፣ የሚዲያ ተቋማትና ጋዜጠኞች እንደዘበት አያልፉትም። ከላይ እስከ ታች ፈልፍለው፣ ከጓዳ እስከ አደባባይ አፍረጥርጠው ያበጥሩታል። ከሃይማኖት ወይም ከባህል ጋር የተያያዘ ነው ብለው ላይ ላዩን ብቻ በመዘገብ አያልፉትም። ሰሞኑን በአሜሪካ የተከሰተችውን አንዲ ትንሽ አጋጣሚ ተመልከቱ። ታዋቂው የአሜሪካ ስፖርተኛ በቲቪ የሚተላለፍ ቃለምልልስ ላይ እንዲገኝ ተጋብዞ ነው የመጣው። አለባበሱ ግን እንደወትሮው የስፖርት ልብስ አይደለም። “ኢየሱስ ከሌለ፣ ሰላም የለም” (no Jesus, no Peace) የሚል ፅሁፍ በጉልህ የተፃፈበት ቲሸርት ነው የለበሰው። ምን ተፈጠረ መሰላችሁ? መጀመሪያ ልብስህን ቀይር ተባለ። ከዚያ ደግሞ፣ የመነጋገሪያ ርዕሰ ጉዳይ ሆኖ ሰነበተ። በእርግጥ፣ የሂንዱ እምነት ተከታዮች በህንድ የገጠር ከተማ እንዳደረጉት ሁሉ፣ ይሄም ስፖርተኛ ሌሎች ሰዎች ላይ ግዴታ ለመጫን እስካልሞከረ ድረስ፣ ቲሸርቱን መልበስ መብቱ ነው። ነገር ግን፣ የአሜሪካ የሚዲያ ተቋማት፣ “ይሄ ነገር ከሃይማኖት ጋር የተያያዘ ነው” በሚል ስሜት ታሪኩን ብቻ በመተረክ በቸልታ አላለፉትም።

በቲሸርቱ ላይ ያስተጋባው እምነት ትክክለኛና ተገቢ ነው ወይ? የሚሉ ጥያቄዎችን በማንሳት ሲያበጥሩት ሰንብተዋል። እውነትም፣ ቲሸርቱ ተገቢ አልነበረም። አንደኛ ነገር፣ የስፖርት አፍቃሪዎች፣ ስፖርተኞችን የሚመለከቱት የሃይማኖት ስብከት ለመቃመስ አይደለም - አንዳች ልዩ የአካል ብቃት ለማየትና የመንፈስ መነቃቃትን ለማግኘት ነው። ሁለተኛ ነገር፣ ቃለምልልሱን ያዘጋጀው የስፖርት ተቋም (ማህበር)፣ ሃይማኖታዊ ስብከቶችን እንደማያስተናግድ በተደጋጋሚ ገልጿል። ስፖርተኛው፣ በራሱ ጊዜና ቦታ መስበክ መብቱ ነው። ሌሎች ሰዎች ገንዘባቸውንና ጥረታቸውን ባፈሰሱበት መድረክ ላይ በግድ ለመስበክ መሞከር ግን ስህተት ነው። ሦስተኛ ነገር፣ “ኢየሱስ ከሌለ፣ ሰላም የለም” ሲባል፣ ከዛሬ ሁለት ሺ አመት በፊት በአለማችን ሰላም አልነበረም ማለት ነው? ክርስትና ባልተስፋፋባቸው ቦታዎችና ዘመናት፣ ጨርሶ ሰላም ተፈጥሮ አያውቅም? ይሄ ከታሪካዊ መረጃዎች (ማለትም ከሳይንሳዊነት) ጋር ይቃረናል። ደግሞስ፣ እንደ አብዛኞቹ ሃይማኖቶች፣ እንደ ሂንዱ እና እንደ እስልምና፣ ክርስትና የተስፋፋባቸው የመጀመሪያዎቹ ሺ አመታትኮ፣ በአብዛኛው በጦርነት የተሞሉ ናቸው። ሃይማኖትን በማንገብ የተደረጉ ጦርነቶችኮ ስፍር ቁጥር የላቸውም። አራተኛ ነገር፤ ፅሁፉ የአክራሪዎች ዛቻ ይመስላል። ለምሳሌ፣ “ኢየሱስ ካለ፣ ሰላም አለ” የሚል ቲሸርት ቢለብስ ኖሮ፣ ስብከቱ፣ የዛቻ ሳይሆን የማግባባት ሙከራ እንደሆነ ለመረዳት አይከብድም ነበር።

“ኢየሱስ ከሌለ፣ ሰላም የለም” ብሎ ማወጅ ግን፣ “በኢየሱስ ካላመናችሁ፣ ጦርነት ይሆናል” ... ማለትም “በሰላም አላስኖራችሁም” በሚል ሊተጎም ይችላል። እናም፣ እምነቱን በግዴታ የመጫን የአክራሪነት ባህርይ፣ ከዚያም አልፎ አመፅኛ የአፈናና የሽብር ዝንባሌ የተላበሰ ይመስላል። አክራሪነት ደግሞ በሁሉም ሃይማኖቶች የሚከሰት የጋራ ባህርይ በዝምታ ሊታለፍ አይገባም። በክርስትና፣ በእስልምና፣ በሂንዱዝም፣ በቅርቡ በማይነማር እንደታየው በቡድሂዝም፣ እንዲሁም በሌሎች ሃይማኖቶች ውስጥ አክራሪነት በተደጋጋሚ ጥፋትን ሲያስከትል እንደኖረ ይታወቃላ። የአክራሪነት ባህርይ እና የአመፅ ዝንባሌ በዝምታ ከታለፈ፣ ቀስ በቀስ እየገነነ ይሄዳል። ወይ ስልጣን በመያዝ አፋኝ አምባገነንነትን ያሰፍናል። አልያም፣ ስልጣን ለመያዝ ጨካኝ አሸባሪነትን ያስፋፋል። በእርግጥ፣ ስፖርተኛው፣ በሌላ ሰው ላይ አመፅ (ወንጀል) ወደ መፈፀም ካልተሸጋገረና ካልሞከረ በቀር፣ የአክራሪነት ሃሳቦችንም ጭምር በራሱ ጊዜና ቦታ መስበክ መብቱ ነው። ነፃነቱን ማክበርና በዝምታ ማለፍ ግን ይለያያሉ። ነፃነቱን አክብረው፣ ግን ደግሞ “ያስተጋባኸው ሃሳብ የተሳሳተና ጎጂ ነው” ብለው የሚተቹና የሚሞግቱ ሌሎች ሰዎች መኖራቸውም መልካሙ ነገር - እነሱም ሃሳባቸውን የመግለፅ ነፃነት አላቸውና። በነፃነት ትክክለኛ ሃሳብ በማቅረብ፣ አክራሪነትን ይከላከላሉ። የተለያዩ የአሜሪካ ሚዲያዎች በተለያየ መልኩ ከእነዚህ ጥቄዎችና ሃሳቦች መካከል ብዙዎቹን በማስተናገድ ዘግበዋል።

ምን ለማለት ፈልጌ ነው? እንደ ቢቢሲ የመሳሰሉ በአውሮፓና በአሜሪካ የሚገኙ የሚዲያ ተቋማት፣ (ሁሉም ባይሆኑም፤ በአብዛኛውና በአመዛኙ) እንዲህ አይነት ከሃይማኖትና ከባህል ጋር የተያያዘ ታሪክ በምዕራብ አገራት ሲከሰት በቸልታ አያልፉትም - ሳይንስንና ነፃነትን የሚያከብር ባህላቸው ቢዳከምም ገና ተሸርሽሮ አላለቀማ። ቢዳከምም ችግር የለውም ማለት አይደለም። የኤስያ ወይም የአፍሪካ ጉዳይ ሲሆን፣ እነ ቢቢሲ ላይ ላዩን በመዘገብ ጥያቄዎችን ሳያነሱ እንደዘበት የሚያልፉት ለምን ሆነና! “ትምክህተኛ” ተብለው እንዳይሰደቡ ስለሚሰጉ ነው። ምዕራባዊያን ለሳይንስና ለነፃነት የነበራቸው ክብር ባይዳከም ኖሮ፣ በአሜሪካና በእንግሊዝ የሚፈፀሙ ነገሮችን ብቻ ሳይሆን፣ በአፍሪካና በኤስያ የሚከሰቱ ነገሮችንም አብጠርጥረው የመዘገብ ድፍረትና ፍላጎት ባልጎደላቸው ነበር። ምን ያደርጋል? ምዕራባዊያን አገራት፣ በብዙ ነገራቸው አሁንም ድረስ ከአፍሪካና ከኤሲያ በሻለ ሁኔታ በርከት ያሉ የሳይንስና የነፃነት አፍቃሪዎች የያዙ ቢሆኑም፣ እንደ አጀማመራቸው አልዘለቁበትም። ቀስ በቀስ የሳይንስና የነፃነት ባህላቸው እየተዳከመ፣ ወደ ወገኛነት መንሸራተት ከጀመሩ በርካታ አመታት ተቆጥረዋል።

በዚህ በዚህ፣ የተባበሩት መንግስታት ድርጅትን (ዩኤንን) የሚስተካከል አይገኝም ባይ ነኝ። አንድ ምሳሌ ብቻ ላቅርብ። ከ5 ዓመት በፊት በናይጄሪያ የተከሰተ ነው። ያለ ጋብቻ ወሲብ ፈፅማለች በሚል የአክራሪዎች “ክስ” የቀረበባት ናይጄሪያዊት ወጣት ምን እንደተፈረደባት ታስታውሳላችሁ? አደባባይ ላይ ህዝብ ተሰብስቦ በድንጋይ ደብድቦ እንዲገድላት ነበር የተፈረደባት። ብዙም ሳይቆይ፣ በተባበሩት መንግስታት የልማት ፕሮግራም (ዩኤንዲፒ) የተሰራጨ ሪፖርት ስለ ፍርዱ ምን ይላል መሰላችሁ? ያለጋብቻ ወሲብ ፈፅማለች የተባለችን ወጣት በድንጋይ ውርጅብኝ መግደል፣ በደፈናው “መጥፎ ባህል ነው” ብሎ ለመፈረጅ አስቸጋሪ መሆኑን ይገልፃል - የዩኤን ሪፖርት። “መጥፎ ባህል ነው” ብሎ መናገር ተገቢ አለመሆኑን ዩኤን ሲያስረዳ፣ የምዕራባዊያን (ለምሳሌ የእንግሊዝ) ባህል እና የአፍሪካ (ለምሳሌ የናይጄሪያ) ባህል እንደሚለያይ በመጥቀስ፣ ጥሩ እና መጥፎ ብሎ አንዱን ከሌላው ማስበለጥ ስህተት እንደሆነ ገልጿል። ከሳይንስ ትምህርት ጋር የፖለቲካ ነፃነት የጎላበትን የምዕራባዊያን ባህል እና ከሃይማኖት ስብከት ጋር የልማድ አጥባቂነት የበዛበትን የአፍሪካ ባህል ማበላለጥ ተገቢ አይደለም? እናም፣ ዩኤን በእኩል አይን ሊስተናገዱ ይገባል ይላል። ለዚህ ለዚህማ፤ “ቦኮ ሐራም” የተሰኘው አክራሪ ቡድን፣ ባለፉት አምስት አመታት፣ በናይጄሪያ እየገነነ መምጣቱ እንዴት ይገርማል? ራሱን “ቦኮ ሐራም” ብሎ የሰየመውኮ በሌላ ምክንያት አይደለም - “በምዕራባዊያን የተስፋፋው የሳይንስ ትምህርት ለኛ ሐራም ነው” በሚል ስሜት ስያሜውን እንደመረጠው ተገልጿላ። ይህም ብቻ አይደለም። “እያንዳንዱ ሰው የሌላው ሰው ሕይወት ውስጥ ሳይገባ የራሱን አእምሮ ተጠቅሞ የሚያስብበትና ሃሳቡን የሚገልፅበት፣ በራሱ ጥረት ኑሮውን የሚያሻሽልበትና ንብረት የሚያፈራበት፣ በግል ሰብእናው የእኔነት ክብር የሚቀዳጅበትና ሕይወትን የሚያጣጥምበት የምዕራባዊያን የነፃነት ፖለቲካም፣ ለአፍሪካ አያስፈልግም” ማለት ነው። የነቦኮሐራም ፀብ፣ ከምዕራባዊያን ጋር ሊመስለን ይችላል። ግን በጭራሽ አይደለም። ዋና አላማቸው፣ ከምዕራባዊያን ጋር መተናነቅ አይደለም፤ እዚያው አጠገባቸው ያለውን ማነቅ ነው የሚፈልጉት። ለመቃወም የሚደፍር ይኖራል? “ሳይንስን አትማሩም፣ እኛ የምነግራችሁንና የምንሰብካችሁን ብቻ በግድ ትጋታላችሁ፤ እኛ ያዘዝናችሁን ትፈፅማላችሁ፤ የሕይወታችሁ ባለቤት እኛ ነን... ይህን የተቃወመ ሃይማኖትንና አገሩን፣ ህዝቡንና ባህሉን የካደ የምዕራባዊያን ተላላኪ ነው” ብለው አፉን ያስይዙታል። በሌላ አነጋገር፣ ለነቦኮሐራም፣ የሃይማኖት አክራሪነት ብቻውን በቂ አይደለም። በእርግጥ የሃይማኖት አክራሪዎች ዋነኛ መሳሪያ፣ የሌላ ሃይማኖት ተከታዮችን በጠላትነት መፈረጅ ነው። ይህን የሚያደርጉት ታዲያ፣ ዋና ፀባቸው ግን ከሌላ ሃይማኖት ተከታዮች ጋር ስለሆነ አይደለም፤ የራሳቸውን ሃይማኖት የሚከተሉ ሰዎችን ፀጥ ለጥ አድርገው ለመግዛት ምቹ መንገድ ስለሚፈጥርላቸው ነው። እንዴት በሉ። “እያንዳንዱ ሰው ለሃይማኖቱ መስዋዕት መሆን አለበት፤ ከመስዋዕትነት የሚሸሽና ለመቃወም የሚሞክር ሁሉ፣ ከሃዲ፣ መናፍቅና የሌላ ሃይማኖት ተላላኪ ነው” በሚል ማስፈራሪያ ሁሉንም ዝም አሰኝተውና አለቃ ለመሆን ይጠቀሙበታል። ግን ይሄ በቂ አይደለም። አገራዊነትን (ብሔረተኝነትን) ያክሉበታል - የውጭ አገራትን በጠላትነት በመፈረጅ። “ብሔረተኝነት”ን የሚያስተጋቡት ግን፣ ከውጭ አገራት ጋር ለመጣላት በመፈለግ ሳይሆን፤ “ብሔረተኝነት” የዚያው አገር ሰዎችን ለማንበርከክ የሚያገለግል ትልቅ መሳሪያ እንደሆነ ስለሚያውቁ ነው። “እያንዳንዱ ሰው ለአገሩ፣ ለባህሉና ለህዝቡ መስዋዕት መሆን አለበት፤ ከመስዋዕት የሚሸሽና የሚቃወም ሰው፣ ከሃዲ፣ ፀረሕዝብና የውጭ ሃይሎች ተላላኪ ነው” በማለት ያስፈራራሉ። በእርግጥም፣ ትልቅ የአፈና ዘዴ ነው። ከሃዲና ፀረሕዝብ ከመባል፣ ወይም ደግሞ የውጭ ሃይሎች ተላላኪ ተብሎ ከመታሰርና ከመገደል፤ በዝምታ አንገትን ደፍቶ መገዛት ይሻላል ይላላ። ግን እነ ቦኮሐራም በዚህ አያቆሙም። ሌላ የብሔረተኝነት ቅርንጫፍ ይጨምሩበታል - “ጎሰኝነትን”። ቦኮሐራም የገነነበት የሰሜን ናይጄሪያ አካባቢ፣ ከደቡቡ የአገሪቱ ክፍል የሚለየው፣ ሙስሊሞች በብዛት የሚኖሩበት ስለሆነ ብቻ አይደለም። ሰሜኑ እና ደበቡ፣ በብሔረሰብ ወይም በጎሳ ተወላጅነት ቁጥርም ጭምር ይለያያል።

እናም ቦኮ ሐራም የደቡብ ነዋሪዎችን በጠላትነት ይፈርጃል። ለምን? የሰሜን ነዋሪዎችን ሰጥ ለጥ አድርጎ ለመግዛት ነዋ። “እያንዳንዱ ሰው ለብሔረሰቡ መስዋእት መሆን አለበት። መስዋእትነትን በመሸሽ እኛን የሚቃወም ማንኛውም ሰው፣ ወንድማችንም ይሁን ጎረቤታችን፣ ብሔረሰባችንን የካደ የጠላቶቻችን ተላላኪ ነው” በማለት አፉን ያስይዙታል። ለመናገርና ለመቃወም የሚሞክር ሰው ከተገኘም፤ ያስሩታል ወይም ይገድሉታል። “ጎሰኝነትም” ትልቅ የአፈና መሳሪያ ነው። በአጭሩ፣ ከቅር እስከ ሩቅ ብንመለከት፣ የሃይማኖት አክራሪነት እና ብሔረተኝነት (አገራዊነትና ጎሰኝነት) ሲንሰራፋ የምንመለከተው አለምክንያት አይደለም - የሳይንስና የነፃነት ክብር የተሸረሸረበት ዘመን ላይ ስለሆንን ነው። ባለፈው አመት በአገራችን ከተከሰቱት አስደንጋጭና አሳሳቢ ውዝግቦች መካከል አምስቱን ጥቀሱ ቢባል፤ ያለ ጥርጥር የሃይማኖት አክራሪነት እና የብሔረተኝነት ጉዳይ ሳይጠቀሱ ሊታለፉ አይችሉም። ለምሳሌ ብሔረተኝነትን ተመልከቱ። በአንድ በኩል፣ ከግል ነፃነት በፊት “አገር ትቅደም” ብለው የሚያስተጋቡ ብሔረተኞች አሉ። በሌላ በኩል ደግሞ፣ ከግል ነፃነት በፊት “ብሔረሰብ ይቅደም” የሚሉ ብሔረተኞች። በነገራችን ላይ የኢህአዴግ አባላትና ደጋፊዎች፣ ከየትኛው ጋር እንደሚሆኑ ግራ ሲጋቡ ነው የከረሙት። ጠ/ሚ ሃይለ ማሪያም ደሳለኝ፣ ለፓርቲያቸው ወጣት አባላት ሰሞኑን ሲናገሩ፣ አንደኛውን ቡድን “ትምክተኞች”፣ ሌላኛውን ቡድን “ጠባቦች” በማለት ፈርጀዋቸዋል።

የቀድሞው ጠ/ሚ መለስ ዜናዊም፣ ሁለቱ ጎራዎች እርስ በርስ ተመጋጋቢ ናቸው በማለት ያጣጥሏቸው ነበር። መልስ ያልተሰጠው ጥያቄ፣ “የኢህአዴግ ቦታ የትነው?” የሚለው ጥያቄ ነው። ወይስ እያጣቀሰ ለመቀጠል ይፈልጋል? ብዙ አባላትና ደጋፊዎች በአመዛኙ፣ “ብሔር ብሔረሰብ ይቅደም” የሚለውን መፈክር ያዘወትራሉ - ለዚህም ነው በቴዲ አፍሮ ላይ ተጀምሮ የነበረውን የፌስቡክ ዘፈቻ የሚደግፉ በርካታ ኢህአዴጎች የታዩት። በሌላ በኩል ደግሞ፣ “አገራዊ መግባባትን መፍጠር፤ አንድ የኢኮኖሚና የፓለቲካ ማህበረሰብ መገንባት፣ የአገር ፍቅር ማስረፅ” የሚሉ መፈክሮችን የሚያዘወትሩ ኢህአዴጎችም አሉ። እንዲያም፣ “ከራሴ በፊት ለአገሬ” የሚል የደርግ ዘመን መፈክርም አይቀራቸውም። እንግዲህ ተመልከቱ። ኢህአዴግ፣ ሁለቱም የብሔረተኝነት ቅርንጫፎችን ያወግዛል - “አገራዊነት ትምክተኛነት ነው፤ ጎሰኝነት ጠባብነት ነው” በሚል ስሜት። ግን ደግሞ፣ በዚያው መጠን ኢህአዴግ፣ የሁለቱንም ጎራ መፈክሮች ይጠቀማል። ለዚህ ሳይሆን ይቀራል፣ አሁን በፌስቡክ ንትርክ ውስጥ የኢህአዴጎች ቦታ ብዥታ የተፈጠረው? ለነገሩ፣ በብሔረተኝነትና በአክራሪነት ለአደጋ የምትዳረገው አገር ኢትዮጵያ ብቻ አይደለችም።

አለም ሁሉ ያሰጋዋል። በእስልምናም ሆነ ክርስትና፣ በሂንዲዝም ሆነ በቡድሂዝም፣ በነጮችም ሆነ በጥቁሮች፣ በአረቦችም ሆነ በሞንጎሎች.... በሶሪያም ሆነ በዩክሬን፣ በኢራቅም በደቡብ ሱዳን፣ በማይነማርም ሆነ በሶማሊያና በየመንም ሆነ በዩክሬንና በራሺያ፣ አፍጋኒስታንን ጨምሮ በፓኪስታንና በህንድ... ከዚያም አልፎ በእንግሊዝ ስኮትላንድና በስፔን ካታሎኒያም ጭምር... የሃይማኖት አክራሪነት እና ብሔረተኝነት አለምን እያተራመሱ ናቸው። ደግነቱ ፍቱን መድሃኒት አለው። ለብሔረተኝነትም ሆነ ለአክራሪነት ፍቱን መድሃኒቱ፣ የሳይንስና የነፃነት አስተሳሰብ ነው። “እያንዳንዱ ሰው፣ ለሃይማኖትም ሆነ ለባህል፣ ለአገርም ሆነ ለብሔረሰብ መስዋዕት መሆን አይገባውም። መስዋዕት ሁን ብሎ የሚያስገድደው፣ የሚያስረውና የሚገድለው ቡድን፣ ፓርቲ ወይም የመንግስት አካል መኖር የለበትም። እያንዳንዱ ሰው የራሱ ሕይወት ባለቤት ነው” በሚል አስተሳሰብ ብቻ ነው ብሔረተኝነትንና አክራሪነትን መከላከል የሚቻለው። አለበለዚያ፣ የብሔረተኝነትና የአክራሪነት ሰለባ እንሆናለን።

Saturday, 20 September 2014 10:40

‹‹ከአንድ ብርቱ....››

           ከእለታት አንድ ቀን አንድ ብልህ አባት የመሞቻው ቀን እንደተቃረበ አዉቆ፣ አለመተባበራቸው የሚያስጨንቀው ሦስት ልጆቹን ይጠራቸዉና በአንድ ላይ የታሰሩ አስር በትሮችን ሰጥቶ እንደሰበሩዋቸው ይጠይቃቸዋል፡፡ የመጀመሪያው ልጁ ለመስበር ሞክሮ ያቅተዋል፡፡ ሁለተኛውም ልጅ ታግሎ አልሰበር ይሉታል፡፡ የመጨረሻው ትንሹ ልጅ በወንድሞቹ አላዋቂነት እየሳቀ በትሮቹን ተቀብሎ በአንድ ላይ የታሰሩበትን ገመድ በመፍታት ከለያያቸዉ በኋላ፣ እያንዳንዳቸዉን ለብቻ በየተራ ሰባብሮ ይጨርሳቸዋል፡፡ ህመምተኛው አባት ፈገግ ብሎ “አያችሁ ልጆቼ በትሮቹ አንድ ላይ በሆኑ ጊዜ ልትሰብሩዋቸው አልቻላችሁም፡፡ እናንተም አንድ ላይ ብትሆኑ ስለምትጠነከሩ ማንም አይጎዳችሁም” አላቸው ይባላል፡፡“ከአንድ ብርቱ ሁለት መድሃኒቱ”፣ “ድር ቢያብር አንበሳ ያስር”፣ “በአንድ እጅ አይጨበጨብም ” ወዘተ የሚሉትን የሀገራችንን አባባሎች እና ከላይ ያስነበብኩዎትን አይነት የመተባበርን ወይም የህብረትን ጠቀሜታ የሚያወድሱ ተረቶችና ታሪኮችን ብዙ ግዜ ሰምተው እንደሚሆን አልጠራጠርም፡፡

የአባባሎቹንና የታሪኩን እውነተኝነት ምናልባትም በራስዎ ማህበር ውስጥ አረጋግጠው ይሆናል፡፡ ማኅበር ካለዎት ማለቴ ነው፡፡ ለመሆኑ ግን ማኅበር የሌለው ሰው አለ እንዴ? የማኅበራዊ ሳይንስ ጠበብቶች “ሁላችንም የማኅበር ውጤቶች ነን” ይላሉ፡፡ በእርግጥም ማኅበር የብዙዎቹ ችግሮቻችን ቁልፍ ወይም የህልውና ጥያቄ እየሆነ ከመጣ ዘመናት ተቆጥረዋል፡፡ በሀገራችን ከትውልድ ወደ ትዉልድ ሲሸጋገሩ የኖሩትን እንደ እድር እና ዕቁብ ያሉትን ማኅበራት ለአብነት መጥቀሰ ይቻላል፡፡ በተለይ ፍላጎትና አቅማቸውን ተጠቅመዉ ካሉባቸው ችግሮች እንዳይወጡና ለሌላውም እንዳይተርፉ የተለያዩ መሰናክሎች ለሚጋረጥባቸው የህብረተሰብ ክፍሎች፤ ህብረት መፍጠሩ እና መደራጅቱ መሰናክሎቹን በጥበብ ለማለፍ የሚመከር የብልሆች መፍትሄ ነው፡፡

ለአብነት “ከአንድ ብርቱ ሁለት መዳኒቱ” በማለት ማህበር በመመስረት ያሉባቸውን ችግሮች ሁሉ ቀስ በቀስ እየፈቱ፤ ከስልሳ ተነስተዉ ዛሬ ሶስት ሺ አባላት ማፍራት የቻሉትን የአማራ ክልል ነጋዴ ሴቶች ማህበር አባላት ማንሳት ይቻላል፡፡እነዚህ ሴት ነጋዴዎች ያሉባቸውን ችግሮች በማህበራቸው አማካኝነት በመታገላቸውና ለሚመለከታቸው ክፍሎች ድምፃቸውን ማሰማት በመቻላቸው ተሰሚነትና ምላሽ እያገኙ መሄድ ችለዋል፡፡ በመሆኑም አባላቱ የተለያዩ የንግድ ስልጠናዎችን፤ የብድር አቅርቦቶችን፤ ለመስሪያ የሚሆኑ ቦታዎችን፤ በባዛሮችና በንግድ ትርኢቶች ላይ የመሳተፍ ዕድሎችን በማኅበራቸው አማካኝነት ማግኘት ችለዋል፡፡ የማኅበሩ ፕሬዝዳንት የሆኑት ወ/ሮ ንግስት፤ በማኅበር መደራጀታቸው ካስገኛላቸው ጠቀሜታ አንዱ የስራ ዕድሎችን እንደሆነ ሲገልጹ፤ “በ1997 ዓ.ም የባህር ዳር ፔዳጎጂካል ሳይንስ ዩኒቨርስቲ ‘ለአንድ አመት በኮንትራት ምግብ ለማዘጋጀትና ለማቅረብ የሚችል እፈልጋለሁ’ ብሎ ነበር፡፡ ማህበራችን በወቅቱ ፕሬዝዳንት በነበሩት በወ/ሮ ፍሬአለም ሺባባዉ አማካኝነት የማህበሩ አባላት የሆኑ 37 ነጋዴዎች ኮንትራት እንዲወሰዱና እንዲሰሩ አድርጓል፡፡ በዚያን ወቅት አብረውን ይሠሩ ከነበሩት ሴቶች ጂ ፕላስ 3 እስከ መስራት የደረሱ፤ብዙ የተለወጡ አሉ፡፡

” የአማራ ነጋዴ ሴቶች ማህበር የደሴ ቅርንጫፍ አስተባባሪ የሆነችው ወይዘሪት ህለተ ወርቅ ነጋዴ ሴቶች ከማህበሩ ስላገኙት ጥቅም እንዲህ ትገለፀዋለች፡- “አብዛኞቹ ሴት ነጋዴዎች የንግድ እንቀስቃሴያቸው ባሉበት ቦታ ብቻ የተወሰነ ነበር፡፡ ከቤትዋ ወጥታ ምርትዋን ማስተዋወቅ፤ ሰው ፊት ቆሞ መናገር፤ የንግድ ትስስርና ከሰው ጋር ግንኙነት መፍጠር አልተለመደም፡፡ ማህበሩ ባዛር እና የንግድ ትርኢቶችን ሲያዘጋጅ አንዱና ትልቁ ምክንያት የተጋነነ ትርፍ ይዛ ወደ ቤትዋ እንድትገባ ሳይሆን፤ አንደኛ እርስዋ ነጋዴ ናትና ነጋዴነትዋ ይታወቃል፡፡ ሁለተኛ ምርትዋን ታስተዋዉቃለች፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ለቀጣይ የንግድ እንቅስቃሴዋ የሚረዳትን ግንኙነት ከማህበረሰቡ ጋር ትፈጥራለች፡፡” የአማራ ክልል ነጋዴ ሴቶች ማህበር (አክነሴማ) በርካታ ነጋዴ ሴቶች የማህበሩ አባል በመሆን ተጠቃሚ እንዲሆኑ አድርጓል፡፡ በችግር ምክንያት ልጆችዋን ይዛ ጎዳና እስከመዉጣት ደርሳ የነበረችውና በ አሁኑ ወቅት በ 500 ሺ ብር ወጪ የራስዋን ቤት እስከ መስራትና የባልትና ምርቶችን እያዘጋጀች በመሸጥ የምትተዳደርበትን የራስዋን ሱቅ እስከ መክፈት የደረሰችዉ የባህር ዳር ከተማ ነዋሪ ወ/ሮ አገሬ አሰፋ፤ ወደማህበሩ የገባችበትን ሁኔታና ያገኘችዉን ጥቅም እንዲህ ትገልፀዋለች:- “በሶ፣ ሽሮ፣ በርበሬ፣ምስርና የመሳሰሉትን የባልትና ዉጤቶች በቤቴ ሆኜ ካዘጋጀሁ በኋላ በየሱቁ እየዞርኩ ነበር የማስረክበው፡፡ በዚህም የድካሜን ያህል አላገኝበትም ነበር፡፡ የራሴን ሱቅ ከፍቼ ብሰራ የበለጠ ዉጤት እንደማገኝ የመከሩኝና ያበረታቱኝ የአማራ ነጋዴ ሴቶች ማህበር ናቸው፡፡ ከአማራ ብድርና ቁጠባ ብድር እንድወስድ፣ የራሴን ንግድ ፍቃድ እንድይዝና የማህበሩ አባል እንድሆን ሁኔታዎችን አመላክተዉኛል፡፡ በተለያዩ ግዜያትም ስለንግድ የተለያዩ ስልጠናዎች እንድወስድ ረድተዉኛል፡፡ በአሁኑ ወቅት ያለብኝን የሱቅ ኪራይ ችግር ለማስወገድ በማህበሩ አማካኝነት ስምንት ሆነን ተደራጅተን የቤት መስሪያ ቦታ የማረጋገጫ ደብዳቤ ተሰጥቶናል፡፡ የአንድ ማህበር አባላት ህልውና የማህበሩ ህልውና ነው፡፡

የአባላቱ ጤናማና ጠንካራ እንቅስቃሴ ለማህበሩ አስተማማኝ የህይወት ጉዞ መሰረት ነው፡፡ ጆን ስቴዋርት የተባሉ የማህበራዊ ሳይንስ ሊቅ፣ “The Evolution Manifesto” በተሰኘ መፅሀፋቸዉ ላይ፤ ለአንድ የተቀደስ የጋራ ዓላማ በተመሰረተ ጠንካራ ማህበርና በአባላቱ መሀከል ያለውን ቁርኝት እጅግ ከረቀቀውና ከተወሳሰበው የሰውነታችን አወቃቀርና ጤናማ አሰራር ጋር አነፃፅረዉ ይገልጹታል፡፡ “እያንዳንዳችን በሚሊዮን፤በቢሊየን የሚቆጠሩ ሴሎች ጥምረት ውጤት ነን፡፡ እንደ ልብ፣ ኩላሊት፣ ሳንባና የመሳሰሉት የሰውነታችን ክፍሎች የተገነቡት በእነዚህ ሴሎች አንድነትና ውህደት ነው፡፡ በእነዚህ ህዋሳቶቻችንና የሰዉነት ክፍሎቻችን መሀከል ያለው ጥልቀትና ስፋት ያለው ህብረት፡- ምግብ ስልቀጣውን፣የደምና የኦክስጅን ዝውውር ስርአቱን፣ ሊያጠቁን የመጡትን የበሽታ ህዋሳት የመከላከሉን፣ ችግሮቻችንን ለመፍታት የምንጠቀምበት ጥበብ የማፍለቁንና ሌሎች ግዳጆችን በሙሉ ያለማስተጓጎልና ያለእንከን እንዲከናወን ያደርጋል፡፡

ከህዋሳቶቻችንና ከሰውነት ክፍሎቻችን የአንዱ ከአገልግሎት ውጪ መሆን በጠቅላላው ሰውነታችን ላይ የሚያስከትለው መናጋት እስከሞት ሊያደርሰን እንደሚችለው ሁሉ፤ የአንድ ማህበር አባላት ውድቀትና ጥፋት ማህበሩን እከመፍረስ ሊያደርሰው ይችላል” ይላሉ:: በዚሁ መሰረት የአማራ ነጋዴ ሴቶች ማህበር የአባላቱን የንግድ እንቅስቃሴ የሚያዉኩ ችግሮች ለማስወገድ የማይዘይደው መላ፣ የማያንኳኳው በር፣የማይጮኸው ጩኸት፣ በአጠቃላይ የማይፈነቅለው ድንጋይ የለም። እንደ ምሳሌ “የአባቶች ቡድን”ን እንቅስቃሴ ማየት ይቻላል። የአባቶች ቡድን የጾታ እኩልነትን ለማረጋገጥ፣ወንዶች ለትዳር አጋሮቻቸውና ለልጆቻቸው በፊት ከነበራቸው በተሻለ መልኩ አሳቢና አጋዦች እንዲሆኑ ታስቦ እ.ኤ.እ በ1980 መጨረሻ በስዊድን የተጀመረ እንቅስቃሴ ነው። በኢትዮጵያ ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ በአክነሴማ አማካኝነት ተግባራዊ እየተደረገ ይገኛል፡፡ እንደሚታወቀዉ በሃገራችን ጾታን መሰረት አድርገው በሴቶች ላይ የሚደርሱት ተጽእኖዎች ብዙ ናቸው። ከእነዚህ ተፅእኖዎች አንዱ ‘የሴትና የወንድ’ በሚል ለዘመናት የኖረው ያልተመጣጠነ የስራ ክፍፍል ነው፡፡

ማህበሩ ይህን ችግር ለማስወገድ በየዞኑ እንዲቋቋሙ ባደረጋቸው የአባቶች ቡድን አማካኝነት ትልቅ ስራ እየሰራ መሆኑን የማህበሩ ዳይሬክተር አቶ ጥላሁን ሲገልፁ፤ “አባቶች በቡድን ሆነው ወደ 5 በሚደርሱ ዋና ዋና ርዕሰ - ጉዳዮች ላይ እርስ በርሳቸው ይማማራሉ፡፡ አንድ የባህሪ ለዉጥ እንዲያመጣ የሚፈለግ አባዎራ፤ በቤቱ ውስጥ ምን ምን እንደሚያደርግ፤ ከቤተሰቡ ጋር ያለው ግንኙነት ምን መልክ እንዳለው ይገለፃል፡፡ በአርአያነቱ የተመረጠውና አስቀድሞም በስልጠና የተደገፈዉ አባዎራ ደግሞ ጠቅላላ ለቤቱ ያለውን አቋም እና በዚያ ያገኘውን ጥቅም በመግለጽ ልምዱን ያካፍላል፡፡ በዚህ አይነት መማማሩ ይቀጥላል፡፡ በዚህም በርካታ አባዎራዎች በመለወጣቸዉ የትዳር አጋሮቻቸዉ የሆኑ ነጋዴ ሴቶች ያለመሳቀቅ፣ በነፃነት ለንግድ ስራቸዉ በቂ ጊዜ በመስጠት ዉጤታማ መሆን እየቻሉ ናቸዉ፡፡” ከዚህ በላይ በጥቂቱ ለመግለጽ እንደተሞከረዉ፣ በማህበር መደራጀት ጠቀሜታው የጎላ በመሆኑ የአማራ ክልል ነጋዴ ሴቶች ማህበር በክልሉ ካሉ ሴት ነጋዴዎች አልፎ በመላ ሀገሪቱ ያሉ ሴት ነጋዴዎች በማህበር እንዲደራጁ የአንበሳውን ድርሻ እየተወጣ ይገኛል፡፡ ማህበሩ በአሁን ወቅት በ 3 የክልል ከተሞች ማለትም በደብረ ብርሃን፤ በወልድያ እና በደብረ ታቦር ቢሮዎች በመክፈት የአባላቱን ቁጥር ወደ 4000 የማሳደግ እቅድ ይዞ በመንቀሳቀስ ላይ ነዉ፡፡ በዚህ አጋጣሚም አክነሴማ በክልሉ የሚኖሩ ነጋዴዎችን ለአባልነት ይጋብዛል፡፡

           የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን በአዲስ አበባ ሲያካሂድ የቆየውን የ10 ቀናት ዓመታዊ ጠቅላላ ጉባዔው ዛሬ ያገባድዳል፡፡ ፕሬዝዳንቱ ኢሳ ሃያቱ ያለፈውን ሳምንት ከጉባኤው ጎን ለጎን የተለያዩ የጉብኝት ፕሮግራሞች ነበራቸው፡፡ ከሳምንት በፊት ከጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ጋር በመገናኘት ውይይት አድርገዋል፡፡ በኢትዮጵያ እግር ኳስ የእድገት እንቅስቃሴዎች እና የአፍሪካ ዋንጫን ለማዘጋጀት ባላት ሁኔታ ያተኮር ነበር፡፡ በውይይቱ የተሳተፉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ኢትዮጵያ የአፍሪካ ዋንጫ ማዘጋጀት እንደምትችል ሲያስረዱ፤ ኢሳ ሃያቱ በበኩላቸው ኢትዮጵያ መስፈርቱን አሟልታ ብታዘጋጅ ደስተኛ ነኝ ብለዋል፡፡

የአህጉሪቱን ታላቅ የስፖርት መድረክ ማዘጋጀት ክብር እንደሆነ የገለፁት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአፍሪካ መዲና የሆነችው አዲስ አበባ ቤታችሁ ነው ሲሉ ለካፍ ፕሬዝዳንት ነግረዋቸዋል፡፡ ካሜሮናዊው ኢሳ ሃያቱ ባለፈው ሃሙስ ደግሞ ከአፍሪካ ህብረት የወቅቱ ፕሬዝዳንት ንኮሳዛና ዳላሚኒ ዙማ ጋር ስብሰባ የነበራቸው ሲሆን በአዲስ አበባ የሚገኘውን የካፍ እግር ኳስ አካዳሚም ጎብኝተዋል፡፡ ኢትዮጵያ በመስተንግዶው፣ በትራንስፖርት አቅርቦት፤ በፀጥታና ደህንነት ብቁ ብትሆንም የጐደሉት ስታድዬሞች ነው፡፡ የአዲስ አበባ እና የባህር ስታድዬሞች ውድድሩን ለማስተናገድ የሚበቁ መሆናቸውን የተናገሩት የእግር ኳስ ፌደሬሽን ፕሬዝዳንት ጁነዲን ባሻ ናቸው፡፡ በተለያዩ የአገሪቱ ክልልሎች እየተገነቡ ያሉ ስታድዬሞች በግንባታቸው የመጨረሻ ምእራፍ ላይ እንደሚገኙ በመግለፅ የኢትዮጵያ መንግስት ውድድሩን ለማዘጋጀት የተቻለውን ሁሉ ያደርጋል ብለዋል፡፡

የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ፕሬዝዳንት አቶ ጁነዲን ባሻ የ2017 31ኛው አፍሪካ ዋንጫን ማዘጋጀት ባይፈቀድልን በ2019 እና በ2021 እኤአ የሚካሄዱት 32ኛው እና 33ኛው የአፍሪካ ዋንጫዎችን ለማስተናገድ እንጠይቃለን ብለዋል፡፡ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን በአዲስ አበባ ዓመታዊ ጉባኤውን ሲያካሂድ በሴቶች እግር ኳስ፤ በአህጉራዊ ተቋም የማህበረሰብ ድጋፍ እንቅስቃሴዎች፤ በማርኬቲንግ እና የቴሌቭዥን ስርጭት ዙርያ፤ በቻን ውድድር ዝግጅቶች፤ በፉትሳል እና የባህ ዳርቻ ላይ የእግር ኳስ ውድድሮች ላይ ተከታታይ ስብሰባዎችን አድርጓል፡፡ በ2019 እና በ2021 እኤአ ለሚደረጉት 32ኛው እና 33ኛው የአፍሪካ ዋንጫዎች ለማዘጋጀት ፍላጎት ያላቸው እያንዳንዳቸው በ30 ደቂቃ ገለፃቸው ተፎካክረዋል፡፡ አምስቱ ተወዳዳሪ አገራት አልጄርያ፤ ካሜሮን፤ ጊኒ ፤አይቬሪኮስት እና ዛምቢያ ናቸው፡፡ የሁለቱ አፍሪካ ዋንጫዎች አዘጋጆች የኮንፌደሬሽኑ አባል አገራት በሚያካሂዱት ምርጫ ዛሬ ይገለፃሉ፡፡ ከዚሁ ጋር ተያይዞ በ2017 እኤአ ላይ ለሚደረገው 31ኛው የአፍሪካ ዋንጫን ሊቢያን በመተካት ስለሚያዘጋጀው አገር ለሚወስነው ውሳኔ ማመልከቻ የሚገባበት ቀን 10 ቀን ቀርቶታል፡፡ ውሳኔው መቼ እንደሚተላለፍ ግን የታወቀ ነገር የለም፡፡

ይህን የአፍሪካ ዋንጫ ለማዘጋጀት 9 አገራት አመልክተዋል፡፡ ኢትዮጵያ፤ ግብፅ፤ ጋና፤ ማሊ፤ ዚምባቡዌ፤ ኬንያ ለብቻዋ እና ከኡጋንዳ ሩዋንዳ እና ከታንዛኒያ ጋር በመጣመር መስተንግዶውን ጠይቀዋል፡፡ ኢትዮጵያና ተፎካካሪዎቿ የአፍሪካ ዋንጫን ከመሰረቱት አገራት አንዷ የሆነችው ኢትዮጵያ በ1962 እኤአ ላይ 3ኛውን፤ በ1968 እኤአ 6ኛውን እንዲሁም በ1976 እኤአ ላይ 10ኛውን የአፍሪካ ዋንጫ ማዘጋጀቷ ይታወቃል፡፡ ለማስተናገድ እየጠየቀች ያለችው ለ4ኛ ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫውን ለማካሄድ ነው፡፡ኢትዮጵያ በ10 የአፍሪካ ዋንጫዎች ተሳትፎ አድርጋ አንድ ጊዜ ሻምፒዮን ሁለት ጊዜ ሶስተኛ ደረጃ እንዲሁም ለአምስት ጊዜ ለግማሽ ፍፃሜ መድረስ ችላለች፡፡የምዕራብ አፍሪካዋ አገር ማሊ የተሟላ መሰረተ ልማቶች ስላሉኝ ውድደሩን ማስተናገድ ይገባኛል ትላለች፡፡ ኬንያ ደግሞ የአፍሪካ ዋንጫውን ለማዘጋጀት ሁለት አማራጮች ይዛ ነው የቀረበችው፡፡ አንደኛው አማራጭ ውድድሩን በተናጠል ማስተናገድ ነው፡፡ ሁለተኛው አማራጭ ደግሞ ከምስራቅ አፍሪካ ማህበረሰብ አባል አገራት ሩዋንዳ፤ ኡጋንዳ እና ታንዛኒያ ጋር ለጣምራ አዘጋጅነት ማመልከቷ ነው፡፡

የኬንያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ፕሬዝዳንት ይህን በጣምራ የማዘጋጀት ፍላጎት ከሳምንታት በፊት ይፋ ሲያደርጉ ከሩዋንዳ እና ከኡጋንዳ ፈጣን ምላሽ አላገኙም ነበር፡፡ ታንዛኒያም በተናጠል የማዘጋጀት ፍላጎት ነበራት፡፡ በ2002 እኤአ ላይ የማዘጋጀት እድል ተሰጥቷት መሰረተልማቶቿን በሚያስፈልገው የጊዜ ገደብ ባለማጠናቀቋ እድሏ በጣምራ ውድደሩን ላዘጋጁት ናይጄርያ እና ጋና ተላልፎባት ነበር፡፡ በ2010 እኤአ ላይ የአፍሪካ ዋንጫውን ለማዘጋጀት ተወዳድራም በድጋሚ አልተሳካላትም፡፡ ዘንድሮ ግን ዚምባቡዌ በ2017 እኤአ ላይ የአፍሪካ ዋንጫን ማስተናገድ ይገባኛል ብላ በከፍተኛ ደረጃ ዘመቻ እያደረገች ነው ከተሳካላት በ2034 እኤአ ላይ የዓለም ዋንጫን በአፍሪካ ምድር ለሁለተኛ ጊዜ እንዲስተናገድ እንቀሳቀሳለሁ የሚል እቅዷን ይፋ አድርጋለች፡፡ ከላይ ከተጠቀሱት የአፍሪካ ዋንጫን ማዘጋጀት የሚፈልጉ አገራት የማሸነፍ ከፍተኛ እድል እንዳላቸው የተወራላቸው የመስተንግዶ ፍላጎታቸውን የገለፁት ጋና እና ግብፅ ናቸው፡፡ በቂ ስታድዬሞች፤ ምቹ ትራንስፖርት እና የእግር ኳስ እድገት ያላት ጋና ቅድሚያ ግምት ተሰጥቷታል፡፡

በአንፃሩ በአፍሪካ ዋንጫ ስኬታ ግንባር ቀደም የሆነችው ግብፅ እንደጋና ሁሉንም መስፈርት በሟሟላት ለፉክክሩ ብትቀርብም በፀጥታ ችግር የመመረጥ እድል እንደማይኖራት ይገለፃል፡፡ እነማን አዘጋጆች ነበሩ የአፍሪካ እግር ኳስ ፌደሬሽን ከላይ ከተዘረዘሩት አገራት አዘጋጁን የማይመርጥ ከሆነ በምትክነት ውድድሮችን የማስተናገድ እድል ያላትን ደቡብ አፍሪካ ሊመርጥ እንደሚችል ይገለፃል፡፡ባለፉት 60 ዓመታት የተካሄዱትን 29 የአፍሪካ ዋንጫውን አንዴና ከዚያም በላይ ለማዘጋጀት የቻሉት 18 አገራት ናቸው፡፡ እኩል አራት ግዜ በማዘጋጀት የመጀመርያውን ስፍራ የሚወስዱት ግብፅ እና ጋና ናቸው፡፡ እያንዳንዳቸው ሶስት ጊዜ ማስተናገድ የቻሉት ሁለት አገራት ደግሞ ኢትዮጵያ እና ቱኒዚያ ናቸው፡፡ እያንዳንቻቸው ሁለት ጊዜ የውድደሩ አዘጋጅ በመሆን ደግሞ 4 አገራት ናይጄርያ፤ ሞሮኮ፤ ደቡብ አፍሪካ እና ሱዳን ተሳክቶላቸዋል፡፡ 10 አገራት ደግሞ የአፍሪካ ዋንጫን አንድ ጊዜ ያዘጋጁ ሲሆን እነሱም አልጄርያ፤ አንጎላ፤ ቡርኪናፋሶ፤ ካሜሮን፤ አይቬሪኮስት፤ ኢኳቶርያል ጊኒ፤ ጋቦን፤ ማሊ፤ ሴኔጋል እና ሊቢያ ናቸው፡፡

የአፍሪካ ዋንጫ እንዴት ይዘጋጃል? የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን ለአፍሪካ ዋንጫ አዘጋጅነት ብቁ የሚላቸው አገራት በሆቴል እና መስተንግዶ፤ ቢየያንስ አራት አለም አቀፍ ደረጃ የጠበቁ ስታድዬሞች ከእነ ልምምድ ስፍራቸው፤ በቂ የአየር እና የየብስ ትራንስፖርት አገልግሎት፤ አስተማማኝ ደህንነት እና ፀጥታን በዋና መስፈርቶቹ ይመለከታል፡፡ በ2013 እኤአ ላይ ደቡብ አፍሪካ ያዘጋጀችው 29ኛው አፍሪካ ዋንጫ ኢትዮጵያ ከ31 ዓመት መራቅ በኋላ ለመጀመርያ ጊዜ የተሳተፈችበት ነበር፡፡ ደቡብ አፍሪካ ይህን አፍሪካዋንጫ ያዘጋጀችው ለዓለም ዋንጫ ያቀረበቻቸው መሰረተ ልማቶችና ልምዶች በቂ በመሆናቸው ነበር፡፡ ሊቢያ በነበራት የፀጥታ ጉድለት ከውድድሩ አዘጋጅነት ተሰርዛ ደቡብ አፍሪካ መተካቷ የተሳካ ነበር፡፡ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ዋንጫን ከ38 ዓመት በኋላ ለመጀመርያ ጊዜ እንዲሁም በታሪክ ለአራተኛ ጊዜ ማስተናገድ ብትችል ከደቡብ አፍሪካ መሰናዶ ብዙ ልትማር ያስፈልጋል፡፡ ደቡብ አፍሪካ ለ2010 ለዓለም ዋንጫ የነበሩ እና ከፍተኛ ልምድ ያላቸው የአዘጋጅ ኮሚቴ የቦርድ አባላት በማሰባሰብ ውድድሩ ከመዘጋጀቱ ቢያንስ ለ2 ዓመት ተንቀሳቅሳለች፡፡ ይሄ ብሄራዊ የአዘጋጅ ኮሚቴ ሚኒስትሮች፤ ዲኤታዎች፤ ባለሃብቶች፤ ታዋቂ ሰዎች፤ ትልልቅ እና ባለታሪክ ስፖርተኞች እና ሌሎችንም ያካተተ እና እስከ 30 አባላት በቦርድ አባልነት የሰሩበት ነው፡፡ ከዚሁ ቦርድ ስር ደግሞ ቢያንስ አምስት የተለያዩ ኮሚቴዎች ይኖራሉ፡፡

የውድድር አካሄድን፤ ፀጥታ እና ደህንነትን፤ የፋይናንስ ጉዳዮችን፤ የማርኬቲንግ እና የንግድ ተግባራትን፤ የሰው ሃይል ምደባን፤ የሆቴል እና የትራንስፖርት አቅርቦትን እንዲሁም የሚዲያ እና የዓለም አቀፍ ግንኙነትን ያንቀሳቅሳሉ፡፡ ደቡብ አፍሪካ 29ኛውን አፍሪካ ዋንጫ ስታስተናግድ ከመንግስት የበጀት ድጋፍ፤ ከካፍ የገንዘብ አስተዋፅኦ፤ ከስፖንሰርሺፕ እና ከተለያዩ የንግድ እንቅስቃሴዎች ገቢ ነበረው፡፡ የውድድር ማካሄጃ፤ የአስተዳደር ስራዎች፤ የጉዞ እና የሆቴል አገልግሎት እና ሌሎች ተግባራትን በማከናወን ወጭዎች ይኖሩታል፡፡ የአፍሪካ እግር ኳስኮንፌደሬሽን ለአፍሪካ ዋንጫ አዘጋጅ አገር 6.2 ሚሊዮን ዶላር ያበረክታል፡፡ በሁሉም አዘጋጅ ከተሞች የውድድሩ ብሄራዊ ኮሚቴ አብሮ የሚሰራበት ምክር ቤት፤ ከአምስት በላይ ከብሄራዊ ኮሚቴው ጋር ተፈራርመው የሚሰሩ የመንግስት ተቋማት፤ ለ16 ብሄራዊ ቡድኖች በአዘጋጅ ከተሞች ሙሉ የስልጠና ሜዳ እና ከስታድዬም ከ5 እስከ ሰላሳ ደቂቃ ጉዞ ያላቸው የማረፊያ ሆቴሎች፤ዓለም አቀፍ ደረጃ ያሟሉ ቢያንስ አምስት ስታድዬሞች፤ ከ200 በላይ ከብሄራዊ ኮሚቴው ጋር የሚሰሩ ሰራተኞች፤ ከ2500 በላይ ውድድሩን የሚያስተናግዱ በጎፍቃደኞች ፤የውድድሩ ኦፊሴላዊ ድረገፅ ፤ ውድድሩን የሚገልፅ መርህ ፤ የውድድሩ መለያ የሆነ ምልክት እና ሎጎ፤ በከፍተኛ ደረጃ ውድድሩን የሚያስተዋውቁ ባነሮች፤ ቢልቦርዶች እና ፖስተሮችም አንድ የአፍሪካ ዋንጫ አዘጋጅ አገር በተሰካ መንገድ ለማስተናገድ የሚያከናውናቸው ስራዎች መሆናቸውን በደቡብአፍሪካ የ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ሪፖርት መረዳት ይቻላል፡፡ አፍሪካ ዋንጫን በማስተናገድ ለሌሎች አህጉራዊ እና ዓለም አቀፍ የስፖርት መድረኮች በቂ ተመክሮ እና አቅም ይገነባል፡፡ የስፖርቱን አስተዳደር ሁለገብ አቅም ያሳድጋል፡፡ አለም አቀፍ ትኩረት ይገኝበታል፡፡ የስፖርት መሰረተ ልማቶች እንዲስፋፉ ምክንያት ይሆናል፡፡ የስፖርት እድገትን ለማቀላጠፍ ያግዛል፡፡

Saturday, 20 September 2014 10:34

ከባህር ወጥታ ጤዛ ላሰች

(በባር ወጣችም አወናሰችም) - የጉራጌ ተረት

          ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት በባልትናባለሙያ ነኝ የሚሉ ወይዘሮ በአንድ ከተማ ይኖሩ ነበረ ይባላል፡፡ አንድ ቀን “ዛሬ የምሠራው ገንፎ ነው፡፡ ጐረቤት ሁሉ ይጠራ” ብለው አዘዙ፡፡ ጐረቤቱ ሁሉ ተጠራና የገንፎው ግብዣ ተጧጧፈ፡፡ የዱሮ ጊዜ የገንፎ አበላል እንደዛሬ በማንኪያ አልነበረም፡፡ ሁሉም እጁን ታጥቦ ክብ ክብ ሠርቶ የሚችለውን ያህል መጉረስ ነው፡፡ ሴትዮዋ ባለሙያነታቸውን ደጋግመው እየተናገሩ እየፎከሩ፤ “ብሉ እንጂ ጐረስ ጐረስ ነው እንጂ!” እያሉ ያበረታታሉ፡፡ በየክቡ እየዞሩ፤ “እህስ እንዴት ነው ገንፎዬ” ይላሉ፡፡

እንደ ዕውነቱ ከሆነ ገንፎው በጣም ቀጥፎ፣ እጅግ ላቁጦ ጣት ላይ የሚጣበቅ ነው፡፡ አንደኛ ጐረቤት “እንዴ ድንቅ ነው፤ የእርሶ ሙያ ምን ይጠረጠራል” አለ ወደ ሁለተኛው ቀርበው “እህስ ገንፎዬ እንዴት ነው?” ሁለተኛ ጐረቤት - “አይ እጅ! እንዲህ ያለ ሙያ ከየትም አይገኝ!” ሴትዮዋ የበለጠ እየተኩራሩ ወደ ሶስተኛው ዞሩ፤ “እህስ ገንፎዬን እንዴት አገኘኸው?” ይሉታል፡፡ እሱም እንደሌሎቹ የድርሻውን ውዳሴ በመስጠት፤ “ገንፎ ከበሉ አይቀር ይሄን ዓይነቱን ነው! እንደው እንዴት አርገው ቢያገነፉት ነው እሜቴ እንዲህ ያማረልዎ?” ይላል፡፡ በመጨረሻ ወደ አንድ ውሸት የማይወድ አንደበተ - ቀና፣ ቁምነገረኛ ሰው ዘንድ መጥተው፤ “እህስ ወዳጄ ገንፎዬ እንዴት ነው?” ሰውዬው ዝም አለ፡፡ “ምነው ዝም አልክ? አልጣፈጠህም እንዴ?” ብለው አጠንክረው ጠየቁት፡፡ ሁሉ ሰው የሰውዬውን መልስ ይጠብቃል፡፡ ሰውዬው ጉሮሮውን አጠራና፤ “ኧረ እሜቴ፤ እንደው መጣፈጡ ቀርቶ እጄን በለቀቀኝ!” አላቸው፡፡

                                            ***

“ዕውነቱን ተናግሮ የመሸበት ማደር” እጅግ ወሳኝ ነው፡፡አገር ያድናል፡፡ ህዝብን ከግርታ ያወጣል፡፡ በአንፃሩ መሸነጋገል ከቶም የአገር ጠር ነው፡፡ በይሉኝታም ይሁን በፍርሀት፣ አውቀን በድፍረትም ይሁን ሳናውቅ በስህተት፤ መሸነጋገልና መወዳደስ፤ “ሆድ ሲያውቅ ዶሮ ማታ” ነው፡፡ በትክክል ያልሰራነውን ሠርተሃል ተብለን አደባባይ ወጥተን መፎከር ኋላ ደብቁኝ ደብቁኝን ያመጣል፡፡ እንደ እሜቴ ገንፎ ነውና! ለረዥም ዘመን በታዋቂ - ተደናቂነት፣ አሊያም በሥልጣን መከታ፤ ሲሸነግሏቸው እየተኩራሩ የኖሩ አያሌ ናቸው፡፡ “እናቷ መራቂ ልጅቷ አሜን ባይ” እንደሚባለው መሆኑ ነው፡፡ (Yes-men of Athens እንዲሉ ፈረንጆች) ዛሬም ዕውነተኛውን ዲሞክራሲ ከሐሳዊው ዲሞክራሲ መለየት አለብን፡፡ ሀቀኛውን ፍትሕ ከአስመሳዩ ፍትሕ አጥርተን መጓዝ አለብን፡፡

መልካም አስተዳደርን ከብልሹው አስተዳደር ነጥለን ዕቅጩን መናገር አለብን፡፡ በአደባባይ ስለ ፀረ ሙስና እየተናገርን ዙሪያ መለስ የሙስና አረንቋ ውስጥ ተዘፍቀን ከሆነ ጉዱ መለየት አለበት፡፡ በምንንቀሳቀስበት የሥራ ሂደት ውስጥ ሁሉ “የነካነው ሁሉ ወርቅ ይሆናል” ብለን ደርሶ ሚዳስ እንሁን ብንል፣ ውሎ አድሮ የምንጋለጥበት ሰዓት ስለሚመጣ እያንዳንዷን እርምጃችንን በጥንቃቄ ብንመዝን ይሻላል፡፡ ዕውነቱን በትክክል ተናግሮ የወደፊት መንገድን አርሞ መጓዝ እንጂ መገበዝ ወንዝ አያሻግርም፡፡ ኢኮኖሚው እጅግ ያዘቀዘቀው ህዝብ “እንኳን እናቴ ሞታ እንደውም አልቅስ አልቅስ ይለኛል” እያለ መሆኑን እንገንዘብ፡፡ አገር ያለህዝብ ድጋፍ ወደፊት አትራመድም፡፡

ህዝብን አክብሮ፣ ያለ አንዳች ሽንገላ መታደጊያውን ሰዓት እንወቅ፡፡ ህዝብ አብሮ ለመጓዝ ዝግጁነቱን ያሳየበትን ወቅት በትክክል ለይቶ መጠቀም ብልህነት ነው፡፡ ቸገረኝ ሲል እህ ብሎ ማዳመጥ ትክክለኛ የአመራር መርህ ነው፡፡ ኢኮኖሚያዊ ብሶትንም ሆነ ፖለቲካዊ እሮሮን ሰምቶ በአመቸው መንገድ ሁሉ መፍትሔ መስጠት ወቅቱ የሚጠይቀው ጉዳይ ነው፡፡ ወቅቱን ያላወቀ ወይም ያልተገነዘበ አካሄድ “ከባህር ወጥታ ጤዛ ላሰች” እንደተባለው ይሆናል፡፡ አሁንም አሁንም እናስተውል፡፡ 2007 ዓ.ም የማስተዋያ ዓመት ይሁንልን!

Published in ርዕሰ አንቀፅ

            ሸፍተው የነበሩ የዞኑ የፖሊስ ልዩ ሃይል አዛዥና የሚሊሽያ አባላት እጃቸውን ሰጡ

        በጋምቤላ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት በጎደሬ ወረዳ፣ በመዠንገር ዞን በተቀሰቀሰውና አሁንም ድረስ በአንዳንድ ቦታዎች በቀጠለው ግጭት እጃቸው እንዳለበት የተጠረጠሩ የክልሉ ባለስልጣናት ያለመከሰስ መብታቸው ተነስቶ በቁጥጥር ስር እየዋሉ ነው፡፡ በአዲስ አመት ዋዜማ የተቀሰቀሰውና ከ40 በላይ ሰዎችን ህይወት የቀጠፈው ግጭት መነሻ ከመሬት ባለቤትነት ጋር የተያያዘ እንደሆነ ለአዲስ አድማስ የገለፁት ምንጮች፤ “ደገኞች መሬታችንን ይልቀቁ” የሚሉ የአካባቢው ተወላጆችና አንዳንድ የክልሉ ባለስልጣናት በመንግስት ተግባራዊ እየተደረገ ያለውን የሰፈራ ፕሮግራም ተገን በማድረግ ነባር ይዞታ ያላቸውን ነዋሪዎች በማፈናቀላቸው ግጭቱ መፈጠሩን ተናግረዋል፡፡

በአካባቢው ተወላጆችና ከሌሎች አካባቢዎች በመጡ ነዋሪዎች መካከል ለረጅም ጊዜ የቆየና በየጊዜው የሚያገረሽ ግጭት እንዳለ የሚታወቅ ሲሆን፣ በቅርቡ የተከሰተው ግጭት ሊቀሰቀስ እንደሚችል የፌደራል መንግስት በደረሰው መረጃ መሰረት፣ በአፈ ጉባኤ ካሳ ተክለብርሀን የተመራ ቡድን ከክልሉ ከፍተኛ ባለስልጣናት ጋር በመተባበር በአካባቢው የማረጋጋት ስራ ቢሰራም፣ በዞኑ ያሉ አንዳንድ የፖሊስና የሚሊሺያ አባላት “መሬታችንን ይልቀቁ” የሚለው ሃሳብ እንዲሰርፅ በማድረጋቸው ግጭቱ እንደተፈጠረ ምንጮቻችን ጠቁመዋል፡፡

ግጭቱ ከተፈጠረ በኋላም የዞኑን የፖሊስ ልዩ ሀይል አዛዥ ጨምሮ የፖሊስና የሚሊሽያ አባላት ሸፍተው ጫካ መግባታቸውን የተናገሩት ምንጮች፤ በአሁኑ ወቅት አዛዡና ሌሎች ጥቂት አባላት እጃቸውን ለመንግስት ሃይሎች እንደሰጡ ገልፀዋል፡፡ በአካባቢው የተከሰተው ግጭት ሁነኛ መፍትሔ ካልተበጀለት፣ በአቅራቢያ ወደሚገኙ ሌሎች አካባቢዎች ሊዛመት ይችላል የሚል ከፍተኛ ስጋት መፈጠሩን ያመለከቱት ምንጮቹ፤ ከወራት በፊት ማንነታቸው ያልታወቀ የታጠቁ ሰዎች ዲማ ተብሎ በሚጠራው የክልሉ አካባቢ አስር ሰላማዊ ዜጎችን ገድለው መሰወራቸውን ገልፀዋል፡፡ በአካባቢው የተከሰተው ግጭት ከክልሉ የፀጥታ ሃይሎች ቁጥጥር በላይ በመሆኑ፣ የፌደራል ፖሊስና የመከላከያ ሃይል ጣልቃ ገብቶ የማረጋጋት ስራ እየሰራ እንደሚገኝ ለማወቅ ተችሏል፡፡

Published in ዜና

                       በፊልም ባለሙያው ቴዎድሮስ ተሾመና በደራሲ አትንኩት ሙሉጌታ መካከል በተመሰረተው የመብት ይገባኛል ፍትሃብሄር ክርክር፣ ፍ/ቤት በአርቲስት ቴዎድሮስ ተሾመ ላይ የ10 ሚሊዮን ብር እግድ ከትናንት በስቲያ አስተላለፈ፡፡ ከሳሽ ደራሲ አትንኩት ሙሉጌታ፤ ነሐሴ 13 ቀን 2006 ዓ.ም ለፍ/ቤት ባቀረቡት ክስ፤ አርቲስት ቴዎድሮስ ተሾመ ለእይታ ያበቃው “ሦስት ማዕዘን” የተሰኘ ፊልም ጻሪክ በ2000 ዓ.ም ካሳተሙት “ፍቅር ሲበቀል” የተሰኘ የረዥም ልቦለድ መፅሃፍ የተወሰደ ነው የሚል አቤቱታ አሰምተዋል፡፡ “ሦስት ማዕዘን” የተሰኘው ፊልም መፅሃፋቸው ታትሞ ከወጣ ከ5 ዓመት በኋላ ለዕይታ እንደበቃ በክሳቸው የጠቆሙት ከሳሽ፤ አርቲስት ቴዎድሮስ ያለደራሲው ፈቃድ የቦታና ገፀ-ባህርያት ስሞችን በመቀያየር ብቻ የመፅሀፉን መሰረታዊ ጭብጥና የታሪክ ፍሰት በፊልሙ ውስጥ መጠቀሙን አመልክተዋል፡፡ አርቲስት ቴዎድሮስ ፊልሙን በተደጋጋሚ ለተመልካች በማሳየት ከ20 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ማግኘቱን በክስ ማመልከቻው ላይ የጠቆሙት ደራሲው፤ ተከሳሽ በፈፀሙት ተግባር ከፍተኛ የሞራል ውድቀት እንደደረሰባቸውና ፊልሙ የመፅሃፉ ቀጣይ ህትመት ላይ ተፅዕኖ እንደፈጠረ በመጠቆም የ10 ሚሊዮን ብር ካሳ ጠይቀዋል፡፡

ከሳሽ የመፅሃፉን ጭብጥ፣ መቼትና የተለያዩ ታሪኮች ከ“ሶስት መአዘን” ፊልም ታሪክ ጋር በማመሳከር ለፍ/ቤቱ በማስረጃነት አቅርበዋል፡፡ ጉዳዩን እየመረመረ የሚገኘው የፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ ባለፈው መስከረም 6 በዋለው ችሎት፤ የክስ ማመልከቻው ለተከሳሽ ደርሶ መልስ እንዲሰጥበትና የከሳሽ ምስክሮች እንዲቀርቡ ለጥቅምት 28 ቀን 2007 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ በተጨማሪም ከሳሽ ጳጉሜ 3 ቀን 2006 ዓ.ም በፃፉት ማመልከቻ የ10 ሚሊዮን ብር ክስ ማቅረባቸውንና ቢፈረድላቸው ፍርዱን የሚያስፈፅሙበት ንብረት እንደማያገኙ በመጥቀስ ተከሳሹ በተለያዩ ባንኮች ካላቸው ገንዘብ ላይ 10 ሚሊዮን ብር እንዲታገድላቸው ማመልከታቸውን ያስታወሰው ፍ/ቤቱ፤ አቶ ቴዎድሮስ ተሾመ በዘመን ባንክ ከሚገኘው የሂሳብ ደብተራቸው 10 ሚሊዮን ብር እስከ ቀጣዩ ቀጠሮ ድረስ ታግዶ እንዲቆይ ትዕዛዝ አስተላልፏል፡ አርቲስት ቴዎድሮስ ፊልሙን በተደጋጋሚ ለተመልካች በማሳየት ከ20 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ማግኘቱን በክስ ማመልከቻው ላይ የጠቆሙት ደራሲው፤ ተከሳሽ በፈፀሙት ተግባር ከፍተኛ የሞራል ውድቀት እንደደረሰባቸውና ፊልሙ የመፅሃፉ ቀጣይ ህትመት ላይ ተፅዕኖ እንደፈጠረ በመጠቆም የ10 ሚሊዮን ብር ካሳ ጠይቀዋል፡፡

ከሳሽ የመፅሃፉን ጭብጥ፣ መቼትና የተለያዩ ታሪኮች ከ“ሶስት መአዘን” ፊልም ታሪክ ጋር በማመሳከር ለፍ/ቤቱ በማስረጃነት አቅርበዋል፡፡ ጉዳዩን እየመረመረ የሚገኘው የፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ ባለፈው መስከረም 6 በዋለው ችሎት፤ የክስ ማመልከቻው ለተከሳሽ ደርሶ መልስ እንዲሰጥበትና የከሳሽ ምስክሮች እንዲቀርቡ ለጥቅምት 28 ቀን 2007 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ በተጨማሪም ከሳሽ ጳጉሜ 3 ቀን 2006 ዓ.ም በፃፉት ማመልከቻ የ10 ሚሊዮን ብር ክስ ማቅረባቸውንና ቢፈረድላቸው ፍርዱን የሚያስፈፅሙበት ንብረት እንደማያገኙ በመጥቀስ ተከሳሹ በተለያዩ ባንኮች ካላቸው ገንዘብ ላይ 10 ሚሊዮን ብር እንዲታገድላቸው ማመልከታቸውን ያስታወሰው ፍ/ቤቱ፤ አቶ ቴዎድሮስ ተሾመ በዘመን ባንክ ከሚገኘው የሂሳብ ደብተራቸው 10 ሚሊዮን ብር እስከ ቀጣዩ ቀጠሮ ድረስ ታግዶ እንዲቆይ ትዕዛዝ አስተላልፏል፡፡

Published in ዜና

         በ“አዲስ ጉዳይ”፣ በ“ሎሚ” እና በ“ፋክት” መፅሄት አሳታሚዎችና ሥራ አስኪጆች ላይ ለተመሰረቱት የወንጀል ክሶች የቀረቡት ማስረጃዎች ከየመፅሄቶቹ ገፆች የተቆራረጡና ኮፒ የተደረጉ መሆናቸውን የጠቆመው ፍ/ቤት፤ አቃቤ ህግ ኦርጂናል መፅሄቶችን በማስረጃነት እንዲያቀርብ ትዕዛዝ በማስተላለፍ ለፍርድ ውሳኔ በድጋሚ ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጠ፡፡ ፍ/ቤቱ ከትላንት በስቲያ በዋለው ችሎት አቃቤ ህግ ከጥቅምት 3 በፊት ኦሪጂናል መፅሄቶችን በማስረጃነት እንዲያቀርብ አዟል፡፡ የ“አዲስ ጉዳይ” መፅሄት አሳታሚ ሮዝ አሳታሚና ስራ አስኪያጁ አቶ እንዳልካቸው ተስፋዬ፣ የ“ሎሚ” መፅሄት አሳታሚ ዳዲሞስ ኢንተርቴይመንትና ፕሬስ ስራዎችና ስራ አስኪያጁ አቶ ግዛው ታዬ እንዲሁም የ“ፋክት” መፅሄት አሳታሚ ኢንተርቴይመንትና የፕሬስ ስራዎች ኃ/የተ/የግ/ማህበርና ስራ አስኪያጅ ፋጡማ ኑርዬ በጋዜጣ ጥሪ ተደርጎላቸው ባለመቅረባቸው ጉዳያቸው በሌሉበት እየታየ ሲሆን በተለያዩ ጊዜያት ታትመው በወጡ መፅሄቶቻቸው ሃሰተኛ ወሬዎች በማውራት፣ ለአመፅ የሚያነሳሱ ፅሁፎችን ለህዝብ በማድረስ፣ በህገ መንግስቱና በህገ መንግስታዊ ስርአቱ ላይ አመፅ ለማስነሳት ሞክረዋል የሚሉ ክሶች እንደቀረበባቸው ይታወሳል፡፡ ከ“ፋክት” መፅሄት አሳታሚ ድርጅት ስራ አስኪያጅ በስተቀር የሁሉም ተከሳሽ መፅሄቶች ሥራ አስኪያጆችና ባለቤቶች አገር ለቀው መውጣታቸው ይታወቃል፡፡

Published in ዜና

   የሪያድ ልዩ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት፤ የሽብር ተግባራትን ለመፈጸም ተንቀሳቅሰዋል በሚል ክስ በተመሰረተባቸው አራት የሳኡዲ አረቢያ ዜጎችና በአንድ ኢትዮጵያዊ ላይ ከአንድ እስከ አምስት አመት የሚደርስ የእስራት ቅጣት መጣሉን አረብ ኒውስ ዘገበ ፡፡ ስሙ ያልተገለጸው ኢትዮጵያዊና አራቱ ግብረ አበሮቹ፣ የቅዱስ ቁርአንን አስተምሮት በሚጥስ መልኩ ከሚንቀሳቀሱ የአገሪቱ ጽንፈኛ ሃይሎች ጋር ግንኙነት በመፍጠር ብጥብጥ ለማስነሳት ሞክረዋል፤ ሌሎችንም ለአመጽ አነሳስተዋል በሚል በቀረበባቸው ክስ፣ ጥፋተኛ ሆነው በመገኘታቸው፣ ኢትዮጵያዊው የአምስት አመት እስራት ተፈርዶበታል፡፡ የእስር ጊዜውን ጨርሶ ከወጣ በኋላ ወደ አገሩ እንዲመለስ የተፈረደበት ኢትዮጵያዊው፣ ለሃጂና ኡምራ ጸሎት ካልሆነ በቀር፣ ከአሁን በኋላ ወደ አገሪቱ እንዳይገባም ተከልክሏል፡፡

ሁለቱ ግብረ አበሮቹ የአንድ አመት ከስድስት ወራት እስራትና ለሶስት አመታት የሚቆይ የጉዞ ገደብ የተጣለባቸው ሲሆን፣ ቀሪዎቹ ሁለቱ የአንድ አመት እስራትና ለሶስት አመታት የሚቆይ የጉዞ ገደብ ተጥሎባቸዋል፡፡ተከሳሾቹ በ30 ቀናት ውስጥ ይግባኝ ማለት እንደሚችሉ ፍርድ ቤቱ አስታውቋል፡፡ በተከሳሾቹ ላይ የተላለፈው ውሳኔ፣ ባለፉት ወራት ከተላለፉት መሰል ውሳኔዎች ጋር ሲነጻጸር ቀላል የሚባል መሆኑን የጠቆመው ዘገባው፤ ፍርድ ቤቱ በቅርቡ ከ10 በላይ በሆኑ ተጠርጣሪዎች ላይ እስከ እድሜ ልክ የሚደርስ ቅጣት መጣሉን አስታውሷል፡፡

Published in ዜና
Page 7 of 14