የአዲስ አበባ አስተዳደር የቤቶች ልማት ኤጀንሲ በቀጣዩ ወር በሚጀመረው የቤቶች ልማት ፕሮግራም ምዝገባ ላይ እስከ 1.3 ሚሊዮን የሚደርስ ቤት ፈላጊ ይመዘገባል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ በአንድ የምዝገባ ጣቢያ ስር እንዲካተት ከተደረገው የአቃቂ ቃሊቲ ክ/ከተማ በስተቀር በሌሎች ክፍለ ከተሞች በሚገኙ 113 ወረዳዎች በሶስት የቤት ፕሮግራሞች ዘርፍ እንደሚከናወን ታውቋል፡፡ ኤጀንሲው ከመረጃና ደህንነት መስሪያ ቤት ጋር በመተባበር 11 ሚሊዮን ብር ወጪ አድርጐ ዘመናዊ የምዝገባ አሠራርን የዘረጋ ሲሆን ይህን እንዲያስፈፅሙ ከ4ሺህ በላይ ሙያተኞች ስልጠና እንደተሰጣቸውም ተገልጿል፡፡

የአዲስ አበባ ቤቶች ልማት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ መስፍን መንግስቱ ለጋዜጠኞች በሠጡት መግለጫ፤ አዲስ የሚጀመረው የቤቶች ልማት በ1996 ዓ.ም የተጀመረው ቀጣይ ፕሮግራም መሆኑን አስታውሠው፣ በአሁኑ ፕሮግራም ዝቅተኛ ገቢ ላለው ህብረተሠብ ታሣቢ ያደረገ የ10/90፣ መካከለኛ ገቢ ላላቸው የ20/80 እንዲሁም የህብረት ስራ ማህበራት በጋራ ለሚያከናውኑት የ40/60 የቤት ልማት ፕሮግራም እንደተቀረፀ አስታውቀዋል፡፡ ዝቅተኛ ገቢ ያላቸውን ታሣቢ ያደረገው የ10/90 ፕሮግራም፤ ተመዝጋቢዎች በወር 187 ብር በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሂሣብ እያስቀመጡ ከ2-3 ዓመት ባለው ጊዜ እስከ 4ሺህ ብር እንዲቆጥቡ ይጠይቃል፡፡ የአገልግሎቱ ፈላጊ የወር ገቢው ከ1200 ብር በታች የሆነ ይህንንም ለማረጋገጥ ተቀጣሪ ሠራተኛ ከሆነ ከመስሪያ ቤቱ ማስረጃ ማቅረብ የሚችል በግል የሚሠራ ከሆነም ከሚኖርበት ወረዳ ዝቅተኛ ገቢ የሚያገኝ መሆኑን የሚያረጋግጥ ማስረጃ ማቅረብ ይጠበቅበታል፡፡

አሁን ባለው የግንባታ ወጪ ስሌት፤ የአንዱ ቤት ዋጋ 38ሺህ ብር እንደሚሆንም ተጠቁሟል፡፡ የ20/80 የቤት ፕሮግራም፤ 20 በመቶ ወጪውን ቤት ፈላጊው 80 በመቶውን ደግሞ መንግስት የሚሸፍን ሲሆን በ1997 ዓ.ም ለኮንዶሚኒየም የተመዘገቡና እስከ ዛሬ እጣ ያልወጣላቸውም በዚሁ መርሃ ግብር ይታቀፋሉ ተብሏል፡፡ ምዝገባው ለነባር እና አዲስ ተመዝጋቢ በሚል የተለየ ሲሆን፤ ነባር ተብለው የተለዩት በ1997 የተመዘገቡት ናቸው፡፡ እኒህ ቤት ፈላጊዎች ለአምስት አመት በየወሩ መቆጠብ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ለነባር ተመዝጋቢዎች አራት አይነት ቤቶች የተዘጋጁ ሲሆን 61ሺህ ብር የተገመተውን ስቱዲዮ ቤት ፈላጊ በወር 151 ብር መቆጠብ ሲገባው፤ 176ሺ721 ብር የተገመተውን ባለ አንድ መኝታ ቤት ፈላጊ ደግሞ በወር 274 ብር መቆጠብ ይጠበቅበታል፡፡

224,000 ብር ይፈጃል ለተባለው ባለ ሁለት መኝታ ቤት በወር 561 ብር እንዲሁም 304,215 ብር ይፈጃል ለተባለው ባለሦስት መኝታ ቤት በወር 685 ብር መቆጠብ እንደሚያስፈልግ ታውቋል፡፡ ነባር ተመዝጋቢዎችም በመረጃ ቋት ውስጥ ስማቸው መኖሩን ለማረጋገጥ እንዲችሉ ኤጀንሲው ከግንቦት 25-30 በተለያዩ ሚዲያዎች ዝርዝራቸውን ይፋ እንደሚያደርግ አቶ መስፍን ተናግረዋል፡፡ የ20/80 የቤት ፕሮግራም አዲስ ተመዝጋቢዎች በየወሩ በሚፈልጉት የቤት አይነት ዋጋ ለሰባት አመታት መቆጠብ የሚጠበቅባቸው ሲሆን የዚህ ፕሮግራም ተጠቃሚዎች በሶስት አይነት ቤቶች ብቻ ተመዝጋቢ ይሆናሉ - ባለ1 መኝታ ቤት፣ ባለ2 እና ባለ3 መኝታ ቤቶች፡፡ ዋጋቸው ከነባሮቹ ጋር ተመሣሣይ ሲሆን፤ ስቱዲዮ ቤት ለአዲስ ተመዝጋቢዎች አይፈቀድም ተብሏል፡፡ የ10/90 እና የ20/80 የቤት ፕሮግራሞች ምዝገባ ከሠኔ 3-21/2005 ዓ.ም የሚከናወን ሲሆን ለምዝገባው የሚያስፈልጉ መስፈርቶችም፤ በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ቁጠባ መጀመሩን የሚገልፅ ማስረጃ፣ የቀበሌ መታወቂያ፣ በአዲስ አበባ ከሁለት አመት በላይ የኖረ መሆኑን የሚገልፅ ማስረጃ ሲሆኑ በምዝገባው ወቅትም ስለተመዝጋቢው ዋና ዋና መረጃዎች እና የጣት አሻራ ይወሠዳል፡፡

አንድ ሠው ከሶስቱ ፕሮግራሞች በአንዱ ብቻ መሣተፍ እንደሚችል ያስገነዘቡት የስራ ሃላፊዎቹ፤ ባልና ሚስቶችም እንደ አንድ አንድ ሠው እንጂ በተናጥል መመዝገብ እንደማይችሉ ተናግረዋል፡፡ አንድ ሠው ወይም ባለ ትዳሮች ከተፈቀደላቸው በላይ ተመዝግበው ቢገኙ ከፕሮግራሙ ሙሉ ለሙሉ ከመሠረዛቸውም በላይ ወንጀሉ ከ5-15 አመት በሚደርስ እስራት ያስቀጣል ተብሏል፡፡ ሌሎች ከምዝገባ ሊያሠርዙ የሚችሉ ጉዳዮችም በመግለጫው ተጠቅሰዋል፡፡ ማንኛውም ተመዝጋቢ በራሱ ጊዜ አቋርጦ ገንዘቡ እንዲመለስለት ሲጠይቅ፣ ለ6 ተከታታይ ወራት የሚጠበቅበትን ቁጠባ ሳይቆጥብ ሲቀር እንደሆነ እንዲሁም በራስም ሆነ በትዳር አጋሩ የመኖሪያ ቤት አሊያም የመስሪያ ቦታ ያለው ሆኖ ከተገኘ ከፕሮግራሙ ይሠረዛል የሚሉት ይገኙበታል፡፡ ተመዝጋቢው በምዝገባው ወቅት ፎርሞቹን ማግኘት የለበት ከሚመዘገብበት ማዕከል ብቻ ሲሆን በፎቶኮፒ የተባዛ ፎርም ተቀባይነት አይኖረውም ተብሏል፡፡

ከተመዘገበ በኋላም መለያ ቁጥር በመውሰድ በየጊዜው በኢንተርኔት አማካይነት በመረጃ ቋት ውስጥ ስሙ መኖሩንና አለመኖሩን መከታተል ይችላል፡፡ መካከለኛ ገቢ ያላቸውን የህብረተሰብ ክፍሎች ታሳቢ ያደረገው የ40/60 የቤቶች ልማት ፕሮግራም ግንባታው አስቀድሞ የተጀመረ መሆኑን ያመለከቱት የስራ ሃላፊው፤ የዚህ እድል ተጠቃሚ ለመሆን የፈለገ ሰው ቅድሚያ 40 በመቶ በባንክ መቆጠብ ይኖርበታል ብለዋል፡፡ ዝርዝር መረጃዎች በቅርቡ እንደሚወጡም አቶ መስፍን ገልፀዋል፡፡ ከሰኔ 15 በኋላ ምዝገባው በይፋ በሚጀመረው የህብረት ስራ ማህበራት የቤት ፕሮግራም ተጠቃሚ ለመሆን የሚፈልጉ አካላት፣ 24 ሆነው መደራጀት የሚጠበቅባቸው ሲሆን የግንባታውን ውጪም ሙሉ ለሙሉ መሸፈን ይጠበቅባቸዋል፡፡ ማህበራቱ ለምዝገባ ሲቀርቡም የግንባታውን ወጪ 50 በመቶ የገንዘብ መጠን በዝግ ሂሳብ ይዘው መቅረብ ይጠበቅባቸዋል ተብሏል፡፡

በዚህ የቤት ፕሮግራም ልዩ ተጠቃሚ የሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎች ያሉ ሲሆን ሴቶች ከዚህ ቀደም እንደነበረው በእጣው ወቅት የ30 በመቶ ቅድሚያ የማግኘት እድል ይሰጣቸዋል፡፡ የመንግስት ሠራተኛውም የ20 በመቶ ቅድምያ እድል ይኖረዋል፡፡ ለመንግስት ሠራተኞች በ33 መስሪያ ቤቶች ውስጥ የምዝገባ ሂደቱ የተመቻቻላቸው ሲሆን የመንግስት ሠራተኛውን በልዩ ሁኔታ ለማስተናገድ የተፈለገውም መረጃው በየመስሪያ ቤቱ በቀላሉ ስለሚታወቅ መሆኑ በመግለጫው ተመልክቷል፡፡ የ20 በመቶ ቅድሚያ እድል የተሰጠውም በኑሮ አቅሙ ተጐጂ በመሆኑ ነው ተብሏል፡፡ ለሁሉም የቤት ፕሮግራሞች በየወሩ እንዲቆጠብ የሚፈለገውን የገንዘብ መጠን ቀድሞ በባንክ አስቀምጦ መጨረስ የሚቻል ሲሆን በየጊዜው እየናረ ያለውን የግንባታ ወጪ መነሻ በማድረግም የመዋጮው መጠን ሊጨምር እንደሚችል ተመልክቷል፡፡

Published in ዜና

ወርዷ ክንፎቿንም ጨምሮ፣ ከአንድ ጣት ውፍረት ብዙም አይበልጥም። “ንብ የምታክል ሮቦት” ለማለትም ይመስላል፤ ስሟን RoboBee ብለው የሰየሟት። በእርግጥ ባለፉት አስር አመታት በተካሄዱ ጥናቶችና ምርምሮች ጥቃቅን በራሪ ማሽኖች (ሮቦቶች) ተፈጥረዋል። ሁለት ሶስት ግራም የሚመዝኑ ብቻ ሳይሆኑ፤ ከአንድ ግራም በታች ክብደት ያላቸው እንደ ነፍሳት ማንዣበብ ወይም መብረር የሚችሉ ሮቦቶች ተሰርተዋል። በሃርቫርድ ዩኒቨርሲቲ አራት የጥናት አመታትን የጠየቀው RoboBee (ሮቦንብ) ግን፣ ከእስካሁኖቹ ጥቃቅን በራሪዎች ሁሉ እጅጉን ያነሰ ነው። 12 በራሪዎች ቢመዘኑ፣ በድምር አንድ ግራም አይሞሉም።

የተመራማሪዎቹ ጥረት ተሳክቶ ሰሞኑን፣ እንደ ንብ ክንፉን የሚያርገበግብ በራሪ ሮቦት በይፋ አስመርቀዋል። ደግሞም፣ እንደ ንብ መንጋ፣ በሚሊዮን የሚቆጠሩ “ንብ የመሰሉ ሮቦቶችን” ማምረት ቀላል እንደሆነ ተመራማሪዎቹ ገልፀዋል። “ድንቅ ፈጠራ” ተብሎ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ተቋማት የተደነቀው “ሮቦንብ”፣ በብዙዎች ዘንድ ስጋት ማሳደሩ አልቀረም። ትናንሽና ጥቃቅን በራሪ አካላት አሁን አሁን ቁጥራቸው እየተበራከተ መጥቷል። መንግስታት ለወታደራዊ ስለላና ለፖሊስ ቅኝት በራሪ “ሮቦቶችን” መጠቀም ጀምረዋል። ዜጎችን ለመሰለልና የአፈና ቁጥጥር የማካሄድ ጥማት ያለባቸው መንግስታት፤ በየከተማው በሚሊዮን የሚቆጠሩ ትናንሽና ጥቃቅን በራሪ ሮቦቶችን ቀን ከሌት እንዳያዘምቱ ምን ያግዳቸዋል? አሳሳቢው ነገር ይሄ ነው።

Published in ዜና
Saturday, 18 May 2013 10:04

የ5 ሚሊዮን ብር መኪና

የዛሬ አርባ አመት ገደማ፣ ይህን ማዕረግ ለማግኘት የመኪናዋ አቅም 300 የፈረስ ጉልበት መሆን ነበረበት። ፍጥነቷም ቢያንስ ከ160 ኪሎሜትር በላይ። ዛሬ ይሄ ተቀይሯል። ሱፐርካር ለመባል ከ600 በላይ የፈረስ ጉልበት፣ እንዲሁም በሰዓት ከ350 ኪሎሜትር በላይ የመብረር አቅም ያስፈልጋል። ይህን መመዘኛ አሟልተው በአመቱ ከተመረቱት ልዩ መኪኖች መካከል፣ በማክማረን ኦቶሞቲቭ የተሰራው ስፓይደር የተሰኘው መኪና የ“ራብ ሪፖርት” ምርጫ ሆኗል።

ከመቼው የመኪናው ሞተር ተነስቶ፣ ከመቼው መብረር እንደሚጀምር ሲታይ ያስደንቃል። በሶስት ሴኮንድ ውስጥ፣ ፍጥነቱ ከ“95” በላይ ይሆናል። በሌላ አነጋገር፣ ቆሞ የነበረው መኪና… ገና 1፣ 2፣ 3 ብለን ቆጥረን ሳንጨርስ፣ ከ400 ሜትር በላይ ርቀት ተጉዟል። ከዚያማ ማርሽ እየቀየሩ ፍጥነት መጨመር ብቻ ነው - በሰባት ማርሽ። በአንድ ሊትር 10 ኪሎሜትር ይጓዛል። ታዲያ ዋጋው ቀላል አይደለም። 266ሺ ዶላር ነው (5 ሚሊዮን ብር ገደማ መሆኑ ነው)።

በመፅሄቱ ሪፖርት ላይ እንደዘረዘረው፣ የማክማረን ስሪት የሆነው “ስፓይደር”፣ እንደፌራሪና ላምቡርገኒ ከመሳሰሉ በጉልበትና በፍጥነት ከሚታወቁ የቅንጦት መኪኖች በምንም አያንስም። ለነገሩ ማክማረን የሚያመርታቸው የስፖርት ውድድር መኪኖችም፣ በአለም የሚታወቁ ናቸው። የተለያዩ ውድድሮችን በማሸነፍ፣ ከፌራሪ ቀጥሎ የሚጠቀሰው ማክማረን ነው ይላል ሪፖርቱ። በእርግጥ የስፖርት መኪኖቹ ዋጋ ከፍ ይላል። በ2013 መጨረሻ አካባቢ ከ“ስፓይደር” ጎን ለገበያ የሚቀርበው “ፒ1” የተሰኘ አዲስ የማክማረን የስፖርት መኪና፣ ዋጋው 1.1 ሚሊዮን ዶላር ነው - ሃያ ሚሊዮን ብር! ጉልበቱና ፍጥነቱ ግን እንደ ዋጋው ነው። በ960 የፈረስ ጉልበት፣ በሰዓት 400 ኪሎሜትሩን ፉት ብሎ መጨረስ ይችላል።

Published in ዜና
Saturday, 11 May 2013 14:32

የዝንጀሮ ቆንጆ

ምዕራፍ አንድ - “በጣም እርቦኛል፤ ባገኝ እበላለሁ” ገና መንጋቱ ነው፡፡ ገና መንቃቴ ነው፡፡ እናት እና አባቴም ነቅተዋል፤ ሲያወሩ ይሰማኛል፡፡ “አንተ ምን ሆነህ ነው?” ትላለች እናቴ፡፡ “ምን ሆንኩ?” አላት አባቴ፡፡ “ሌሊት እራስህን አታውቅም ነበር፡፡” “አይደለምና በሌሊት እና በእንቅልፋቸው፣ በቀኑ እና በእውናቸው፣ እራሳቸውን የሚያውቁ ጥቂት ናቸው፡፡” እንዲህ ነው አባቴ፣ በግጥም ነው የሚያወራው፡፡ “መዘላበዱ ጀመረህ ደግሞ ገና ሳይነጋ፡፡” “ማዘንጊያ ይቅርታ፤ ሳልስምሽ ነጋ፡፡” “ከአለቃ ገብረሃና ጋር እኮ የሚያመሳስላችሁ ድንክነታችሁ ብቻ ነው፡፡” “ሊቃንነታችንስ?” “ድንቄም እቴ!” “እንትናችንስ?” “አፈር ብላ፤ አፈር ያስበላህ፡፡” “በጣም እርቦኛል፤ ባገኝ እበላለሁ፡፡” “ሳታቅፈኝ አድረህ አታውቅም ነበር፡፡” አፈርኩ፡፡ እናቴ ድምጽ ውስጥ የጋለ ስሜት አለ።

ቤታችን አንድ ክፍል ናት፡፡ ወዲያ ጥግ እና ወዲህ ጥግ ሁለት ፍራሾች አሉ፡፡ ወዲያ ጥግ ያለው ፍራሽ የእናትና አባቴ መኝታ ቤት ነው፤ ወዲህ ጥግ ያለው ፍራሽ የኔ መኝታ ቤት ነው፡፡ “አንተ ልጅ ሰዓት አልደረሰብህም?” እናቴ ናት፤ እኔን ነው፡፡ እንድሄድላቸው ፈልጋለች መሰለኝ፡፡ “ልክነሽ፤ ደርሷል፡፡” የትምህርት ቤት ሰዓት መድረሱን ነው የጠቆመችኝ፡፡ ምዕራፍ ሁለት - ምፅዋት አቆለቆልሁ፡፡ ወደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ስድስት ኪሎ ካምፓስ፡፡ ረዥም ነኝ፡፡ በቁመት በማን እንደወጣሁ አላውቅም፡፡ አባቴ ድንክ ነው። ጥርሴ የናቴ፣ ከርዳዳ ፀጉሬ ደግሞ ያባቴ ውርስ ናቸው። አፍንጫዬ እንደ እናቴ ሰልካካ፣ እንደ አባቴም ጥፍጥፍ አይደለም፡፡ ትንንሾቹ አይኖቼ የራሴ ናቸው፡፡ ስሄድ አንገቴን በጣም ከመድፋቴ የተነሣ አገጬ ደረቴን ይነካል፡፡ በዚህም የተነሳ ከሰው ጋር የምጋጭበት ጊዜ ትንሽ አይደለም፡፡ ይቅርታ አልጠይቅም፡፡

ስንጋጭ ይቅርታ የሚጠይቅ ጠይቆኝ፣ የሚሳደብ ሰድቦኝ ያልፋል፡፡ ስንጋጭ ይቅርታ የማልጠይቀው ሲሰድቡኝም መልስ የማልሰጠው፤ ትዕቢተኛ ወይም ትዕግስተኛ ሆኜ አይደለም፤ በሃሣብ ስለምዋጥ ነው፡፡ ዛሬ የማስበው ስለኢኮኖሚክስ መምህሬ ነው፡፡ በቀደም እለት አለቅጥ አናዶኝ ነበር፡፡ የኔ የተግባር መልስ ብድሬን ይመልስ አይመልስ ግን እንጃ፡፡ አስተምሮ ሊወጣ ሲል፣ በቀደም እለት “የትምህርት ሰዓት ሲያበቃ እፈልግሃለሁ፡፡” ብሎ ቢሮ እንደሚጠብቀኝ ተናግሮ ወጣ፡፡ በእርጋታ ነው ቀጣዩን ትምህርት የተከታተልሁት፡፡ እንዲያውም ቀጠሮውን ረስቼ ልወጣ የግቢው በር ጋ ከደረስኩ በኋላ ነበር አስታውሼ ወደ ቢሮው ያመራሁት። አልፎ አልፎ እንደሚያደርገው በቅርቡ ባነበበው መጽሐፍ ላይ እንድንወያይ ይሆናል የፈለገኝ ብዬ ነበር የገመትኩት፡፡ በቋቋቲያም ጣቶቼ ለአመል ያህል የቢሮውን በር ነካክቼ ገባሁ፡፡ ወንበሩ ላይ ወደኋላ ተለጥጦ አይኑን ፊት ለፊት ካለው ግድግዳ ላይ ተክሏል፡፡ ፊት ካለው ጠረጴዛ ላይ ተደራርበው የተቀመጡ ሱሪ፤ ሸሚዝና ጫማ ይታያሉ፤ አዲሶች አይደሉም፤ ስለዚህ ሌላ ምንም ስያሜ ሊሰጣቸው አይችልም፤ ከአሮጌ በቀር። ገብቼ ትንሽ እንደቆምኩ ከሃሳቡ ነቃ፡፡ “እስኪ እነኚህን ልብሶች ለካቸው፤ ጫማውንም እየው፡፡”

አለኝ በረዥሙ ተንፍሶ፡፡ በወቅቱ የጠራ ስሜት አልተሰማኝም፤ ራሴን ነው ያየሁት፡፡ ሱሪዬ ሁለቱም ጉልበቶቼ ላይ ተቀዷል፡፡ ነጠላ ጫማ ነው እግሬ ላይ የሰካሁት፤ እርሱም አንድ እግሩ ተበጥሶ በሽቦ አያይዤዋለሁ፤ ክንዶቹ፣ አንገቱ ላይና ጠርዞቹ ላይ የተበላ የክር ሹራብ ከላይ ለብሼአለሁ፤ እናቴ ናት የሰራችልኝ፡፡ ይኼን ብሎኝ ሳለ ከበስተውጭ ተጠራ፡፡ “ውሰዳቸው ልክህ ከሆኑ ትለብሳቸዋለህ። ካልሆነም…” እየሄደ ስለሆነ የተናገረው የመጨረሻዎቹን ቃላት አልሰማኋቸውም፤ ምን ሊሆኑ እንደሚችሉ አውቃለሁ፡፡ ልክ እርሱ እንደወጣ ጥርት ያለ ስሜት ተሰማኝ። ንዴት፡፡ የተናቅሁ መሰለኝ፡፡ እርዳታ፣ ምጽዋት ለእኔ?! እንዲህ ነኝና ፍቃዱ ይህን ነገር ገብቼ ለእናቴ ብነግራት “ለምን በጥፊ አላልከውም ነበር?!” ነው የምትለኝ፡፡ እውን ለምን በጥፊ አላልኩትም? ነደደኝ፡፡ ጆሮዎቼ ጋሙ፡፡ ቢሆንም ልብሶቹንም ጫማውንም ይዤ ወጣሁ። የትምህርት ተቋሙ ግንብ ስር የሚያድር አንድ ወጣት አለ፡፡ በቀጥታ ወደ እርሱ አመራሁ። ኩርምት ብሎ ተኝቷል፤ እንቅልፍ ወስዶታል፤ ቀሰቀስኩት፤ ነቃ፡፡ “ውሰዳቸው፡፡” አልኩት፤ የያዝኳቸውን ልብሶችና ጫማ ከፊቱ እያደረግሁ፡፡ “ልክህ ከሆኑ ትለብሳቸዋለህ፣ ካልሆነም…ትሸጣቸዋለህ፡፡” “እ…ምን…” ባለማመን ዓይነት ከላይ እስከታች እያየኝ፡፡ “ውሰዳቸው፤ ልክህ ከሆኑ ትለብሳቸዋለህ፣ ካልሆነም…ትሸጣቸዋለህ፡፡” ብዬ የሰፈሬን መንገድ ተያያዝኩት፤ ሽቅብ ወደ ሽሮ ሜዳ፡፡

***

መምህሩ ላይ የጠበቅሁትን ያህል ለውጥ አላየሁበትም፤ ብቻ እኔን ሲያይ የመገረም፣ የንቀትና ሌላ ሊገባኝ ያልቻለ አንድ ስሜት አየሁበት፡፡ ልብሱንና ጫማውን ያ ወጣት ጐዳና አዳሪ አድርጐት እንዳየው እርግጠኛ ነኝ፡፡ ልጁ ከዩኒቨርሲቲው በር አካባቢ አይጠፋም፡፡ መምህሩ አቶ አባ መስጠት አሁን ስለ ተመጽዋቾች ጥሩ የሆነ ሃሳብ እንደሚጨብጥ ሙሉ እምነት አደረብኝ፡፡ ራቁቴን በቡቱቶ፣ ሌጣዬን ያለጫማ እሄዳለሁ እንጂ የምጽዋት ልብስ ልለብስ?! ከተመጽዋችነት ጋር ስለማልተዋወቅ አይደል እንዴ ለዚህ የበቃሁት?! ማለት መኪና እያጠብኩ ያለ ምንም እረዳት ዩኒቨርሲቲ ድረስ ልማር የበቃሁት?! ዋ አለማወቅ፡፡ ምዕራፍ ሶስት፡- ኑሮ እናቴ ሹራብ ትሠራለች፤ ስፌት ትሰፋለች፣ ሰዎች ትነቅሣለች (በነገራችን ላይ ንቅሳት በጣም ያበላል፡፡ ብዙ ሰዎች የሚታይ ቦታ ላይ ብቻ ሰዎች የሚነቀሱ ይመስላቸዋል፤ ነገሩ ግን እንደዚያ አይደለም፡፡ ሴተኛ አዳሪዎች፣ ወጣት ሴቶች፣ አንዳንድ ባለትዳሮችና በጠንቋይ ትዕዛዝ… አዎ በጠንቋይ ትዕዛዝ … ጡታቸው ላይ፣ ጭናቸው ላይ፣ መቀመጫቸው ላይ፣ የተለያየ ነገር ይነቀሳሉ፡፡

የሚነቀሱት ነገር ደግሞ ማስረገሙ፣ የሰው ስም፣ ሸረሪት፣ ቢራቢሮ፣ እንዝርት፣ አበባ፣ ጀበና፣ የኮከብ ቅርፅ፣ የሶስት ማእዘን ቅርፅ … በጠንቋዩ ትእዛዝ እና በራሳቸው ምርጫ ይነቀሳሉ፡፡ አብዛኞቹ ጠንቋዮች እናቴን በሙያዋ አውቀዋታል፤ እና አብዛኞቹን ሴቶች የሚልኳቸው ወደ እኛ ቤት ነው፡፡ የእኔ መኖር ራሱ ለገበያው አስተዋፅኦ አድርጓል፡፡ (ጠንቋዮቹ ሴቶቹ እንዲነቀሱ የሚያዟቸውን ነገሮች በሙሉ ልቅም ባለ ዲዛይን የምሰራው እኔ ነኝ፤ እና እኔ እና እናቴ ስንት ጡቶች፣ ስንት ጭኖች፣ ስንት መቀመጫዎች እንዳየን መገመት ትችላላችሁ፡፡) አባቴ ቀን ቀን ለሀብታም ውሾች ከሆቴል የኮንትራት ምግብ ያመላልሳል፤ ማታ ማታ ቡና ቤት በዘበኝነት ያድራል፡፡ እኔ መኪና አጥባለሁ፤ አቅሜ የፈቀደውን ያህል እሸከማለሁ፤ ሌላ ድንገተኛ ሥራም እሰራለሁ፤ እንዲህ ነው የምንኖረው፡፡ ሶስታችንም ራሳችንን መቻል ብቻ ነው የሚጠበቅብን፡፡ ማንም የማንንም እጅ አያይም። እኔም ምፅዋትን፣ ተረጂነትን፣ እንድጠላ ያደረጉኝ እነርሱ ናቸው፡፡ መክረውኝ አይደለም፣ ያደግሁበት ስለሆነ ብቻ ተዋሃደኝ፡፡ እራሳችንን መቻል እንችልበታለን፡፡ ሽሮ ሜዳ ውስጥ የተከበርን ቤተሰብ ነን፡፡ አባቴ አንድ እለት እርቦት አንጀቱ ታጥፏል፡፡ እሱ ብቻ አይደለም እኔም፣ እናቴም ተርበናል፡፡

ሰውዬው ከሚያመላልሰው የውሾቹ ምግብ ላይ ተደብቆ ትልልቅ ጉርሻዎችን ውጦ ረሃቡን አስታገሰ፡፡ ከሰዓት በፊት ግን ጎረቤት ገበታ ላይ ደርሶ ምግብ ብላ ተብሎ ሲለመንና እምቢ ሲል በአይኔ አይቼዋለሁ፡፡ ለእኔና ለእማዬም ደህና የሚጋጡ አጥንቶችን አምጥቶልን በእነርሱው ውለን አድረናል፡፡ ምዕራፍ አራት፡- ተረት እና ሌብነት የትምህርት ሰዓት አብቅቶ ወደ ቤቴ ስሄድ አንጀቴ አንድ ላይ ጥብቅ አለብኝ፡፡ ከነጋ የአሥር ሣንቲም ቆሎ ብቻ ነው አፌ ያደረግሁት፡፡ ከቤት ከመውጣቴ በፊት አባቴ “በጣም እርቦኛል፤ ባገኝ እበላለሁ።” ሲል ሰምቼ ነበር፡፡ እናቴ ከየትም አምጥታ ልትበላ አትችልም፡፡ እዚህ ጋ አንድ ኢትዮጵያዊ ግጥም ፀሐፊ እንዳለው “ረሀብ ስንት ቀን ይፈጃል” ሊባል ይችላል፡፡ ይህንን የሰማ አንድ ብፁእ ያልሆነ ኢትዮጵያዊ “ለምን ሞክረህ አታየውም” ብሏል። (ሳያዩ የሚያምኑ ብፁዐን ናቸው) አንዱ ጥጋበኛ ኢትዮጵያዊ ደግሞ “ረሀብ ስንት ቀን ይፈጃል” ብሎ ጥያቄ የጥጋበኛ ጥያቄ ነው” ብሏል፡፡ ይህን ብልም በቀጥታ ወደ ቤቴ ነው ያመራሁት። የሠፈራችን መግቢያ ላይ አንዲት ፍራፍሬ መሸጫ መደብር አለች፡፡ ባለ መደብሩ ያቀርበኛል፡፡ እኔ ግን ባልጠላውም ልቀርበው አልፈልግም፡፡ ቀርቤ ሳወራው ቶሎ ብሎ አፉን ይከፍታል፡፡

ለሰው ሳወራ ፊትን ትኩር ብሎ የመመልከት ልማድ ስላለኝ የእርሱን የተከፈተ አፍ ማየት ያስጠላኛል፤ የበሰበሱ ጥርሶች፤ ምናምን የተለጠፈበት ምላስ … ቅፅበታዊ ሃሣብ ብልጭ አለልኝና ከመንገዴ ወጥቼ ወደ እርሱ ሄድኩኝ፡፡ በፈገግታ ተቀበለኝ፡፡ ሰላምታ ተለዋውጠን ለትንሽ ጊዜ የሚስብ ወሬ ፍለጋ ዝም አልኩና ጀመርኩለት፡፡ “በመጀመሪያ አዲስ አበባን የረገጠውን ጉራጌ ታውቀዋለህ?” “ኧረ አላውቀውም” “ይኸውልህ ያኔ የጉራጌ ምድር እንዲህ እንደ አሁኑ ሰው አልበዛበትም ነበር፤ የሚታረስ መሬት፣ የሚያርስ በሬ፣ የምትታለብ ላም በሽ በሽ ነበር። መሬቱ ያለ ብዙ ልፋት ብዙ ይለግስ ነበር፡፡ እንዲያውም አብዛኛው ነገር ከዱር የሚገኝ ነበር፡፡” “ኧረ ባክህ?!” “እውነቴ ነው የምልህ፣ እና አሁን የምልህ ሰውዬ በመጀመሪያ አዲስ አበባን የረገጠው ጉራጌ ሁሌ ጠግቦ ይበላና፣ ሚስቱ የምታወጣውን ጨሌ አረቄ በኮዳ ይይዝና፣ ከቤቱ በላይ ያለችው ጉብታ ላይ ቁጭ ብሎ ያብሰለስል ነበር፡፡ ይፈላሠፍ ነበር፡፡” “ኧረ ባክህ?!” “እውነቴን ነው የምልህ እና አሁን የምልህ ሰውዬ፣ በመጀመሪያ አዲስ አበባን የረገጠው ፈላስፋ ጉራጌ ጉብታው ላይ ቁጭ ብሎ፣ አረቄውን እየተጎነጨ ድንገት ቀና ቢል አድማስ ታየው፡፡ ሁሌም በአድማስ ይገረም ነበር፡፡ “ከዚያ በኋላ ምን ይሆን ያለው” እያለ ያብሰለስል ነበር፡፡ እና የዚያን እለት አረቄውን እየተጎነጨ በጣም በአድማስ ተመሰጠ፡፡

“ከዚያ በኋላ ምን ይሆን ያለው፣ እያልኩ እስከመቼ እኖራለሁ፤ ለምን ሄጄ አላየውም” ብሎ መንገድ ጀመረ፡፡” “ኧረ ባክህ?!” “እውነቴን ነው፤ እና አሁን የምልህ ሰውዬ፣ በመጀመሪያ አዲስ አበባን የረገጠው አብሰልሳይ ጉራጌ ከአድማስ ወዲያ ማዶ ምን እንዳለ ለማየት ጉዞ ጀመረ፡፡ አስብ ለማንም አልተናገረም፡፡ የሚወዳትን ሚስቱን እና ሁለት ልጆቹን ወደ ኋላ ትቶ አድማስን ወደፊት እያየ ገሰገሰ፡፡ አስብ ስንቅ አልያዘም፤ በጁ ያለው የአረቄ ኮዳው ብቻ ነው፡፡” ዝም አልኩ፡፡ “እና ከዛስ?!” “ከዚያማ ሲሄድ፣ ሲሄድ፣ ሲሄድ፣ … ከአንድ ወንዝ ደረሰ፡፡ በጣም ተጠምቶ ነበር፡፡ ውሃ ጠጣ፤ ብዙ ጠጣ፡፡ እና ውሃውን መጠጣት በቅቶት በውሃ እየተጫወተ እያለ አንድ የሚያብለጨልጭ ነገር አየ፤ ከውሃው ውስጥ አውጥቶ አየው፤ የንጉሱ ምስል ያለበት የወርቅ ገንዘብ ነበር፡፡

እንደገና ጎንበስ ብሎ ቢያይ ያንኑ የሚመስሉ ብዙ የወርቅ ሳንቲሞች አየ፡፡ እየለቀመ ኪሶቹን ሞላ፡፡” “እና ከዛስ?!” “ከዚያማ ኪሶቹን በሙሉ በወርቅ ሳንቲም ሞልቶ ሳንቲሞቹን ለንጉሱ ሊያስረክብ መንገድ ቀጠለ … መንገድ ላይም አንዲት መልአክ የምትመስል ሴት አግኝታው ወዴት እንደሚሄድ ጠየቀችው … ነገራት…” “ኧረ ባክህ?!” አየሁት “አአአ” ብሏል፤ አፏን ከፍቷል፡፡ የፍራፍሬ መደርደሪያውን ተደግፌ ነው የቆምሁት፡፡ ረዥሙ የፍራፍሬ መደርደሪያ በርብራብ ተከፋፍሎ ብርቱካኑ በአንድ ወገን፣ አቦካዶ፣ ፓፓያ፣ ሙዝ በሌላ ወገን ተቀምጦበታል፡፡ ከእነዚህ በላይ ደግሞ በስስ ላስቲክ የታሠሩ መጠነኛ ክብ ቢጫ ዳቦዎች ጣል ጣል ተደርጎባቸዋል፡፡ እጄን ሰድጄ አንዱን ቢጫ ዳቦ ያዝኩት፤ ዳቦውን ጀርባዬ ውስጥ ወሸቅሁት፡፡ የጀመርሁለትን አጓጊ ወሬ በውል ሳልቋጭ ጥዬው ወደ ቤቴ፡፡ ፊቱ ላይ ቅሬታ ይነበብ ነበር፡፡ ነገ እንደምቀጥልለት ቃል ገብቼለታለሁ፡፡ ስለየው እንኳ አፉን አልከደነም ነበር፡፡ ዳቦውን ይዤ ስገባ የእናቴ ጠባብ ሰልካካ ፊት በነጫጭ ችምችም ጥርሶቿ ታግዞ ሲፈካ ታየኝ፡፡ አሁን ከየትም ላምጣው አትጠይቀኝም። በጣም የተራብን እለት አባዬ የውሾችን ምግብ ሠርቆ እንደአመጣ እያወቅን ያለ ጥያቄ ተቀብለነው እንበላለን፤ እና እኔም ዛሬ … ግን የቱ ይሻላል? ምፅዋት መቀበል? መስረቅ? ወይስ ምን?

Published in ልብ-ወለድ

“ እኔ ወደጋንዲ ሆስፒታል የመጣሁት ሁለት ሴት ልጆች የመደፈር ጥቃት ስለደረሰባቸው ነው፡፡ ልጆቹ የጎረቤት እና የራሴ ሲሆኑ የጎረቤ ልጅ የዘጠኝ አመት ስትሆን የእራሴ ግን የሰባት አመት ናት፡፡ ልጆቹ ለእኛ እንደነገሩን ከሆነ የመደፈር ጥቃት የተፈጸመባቸው አንድ ጊቢ አብሮን በሚኖር ሰው ነው፡፡ በእርግጥ ገና በህግ እስኪረጋገጥ እንዲህ ነው ማለት ባይቻልም የልጆቹ አንደበት የመሰከረው ይህንኑ ነው፡፡ አሁን በሕክምናው ታይተዋል፡፡ ቀጥሎ ደግሞ በፖሊስ መዝገብ ላይ ሁኔታው ሰፍሮ ወደ ፍትሕ እንሄዳለን፡፡ ጉዳዩ እጅግ በጣም ፈታኝ ነው፡፡ እኛም ተከራዮች ነን...እሱም ተከራይቶ የሚኖር ነው፡፡ ወደፊት እንዴት እንደምናደርግ አላውቅም” አሳካሚ እናት... የሴቶችና ሕጻናት የተቀናጀ የፍትህና የእንክብካቤ ማአከል በጋንዲ መታሰቢያ ሆስፒታል ከተቋቋመ ሚያዝያ 2005 ዓ/ም ልክ አንድ አመት ሆኖታል፡፡

ማእከሉ በዩኒሴፍ የገንዘብ እርዳታ እና በፍትህ ሚኒስር የበላይነት የተቋቋመው የዛሬ አመት ሚያዝያ 22/2004 ዓ/ም ነበር እንደ ዶ/ር ደረጀ አለማየሁ የጋንዲ መታሰቢያ ሆስፒታል ሜዲካል ዳይሬክተር መረጃ ፡፡ይህ ማእከል ከመቋቋሙ በፊት በአገር አቀፍ ደረጃ የሚመለከታቸው መስሪያ ቤቶች ተወካዮች ያሉበት አንድ ኮሚ ተቋቁሞ ልምድ ለመቅሰም ወደ ደቡብ አፍሪካ እንዲሄድ ተደርጎ የነበረ ሲሆን በዚያ መሰረት ማእከሉ ተቋቁሞ አገልግሎት በመስጠት ላይ ነው፡፡ የሴቶችና ሕጻናት የፍትህና የእንክብካቤ ማእከል አገልግሎት የሚሰጠው ከፈቃዳቸው ውጭ በሆነ መንገድ የግዳጅ ወሲብ ለተፈጸመባቸው ሴቶች ሲሆን በዚህ አንድ አመት ውስጥ ወደ 1100/አንድ ሺህ አንድ መቶ የሚሆኑ ባለጉዳዮች ተስተናግደዋል፡፡ በእድሜም ከአንድ አመት ከአራት ወር ሕጻን እስከ 80/ሰማንያ አመት የእድሜ ባለጸጋ የሚሆኑ ሴቶች የአስገዳጅ ወሲብ ተፈጽሞባቸዋል፡፡

የዚህን ማእከል የስራ እንቅስቃሴ ለመመልከት በጋንዲ ሆስፒታል በተገኘንበት ወቅት የሁለት አመት ከስድስት ወር ሴት ሕጻን በዚሁ ጉዳይ በሐኪም እየታየች ነበር፡፡ አስተባባሪ ነርስ የሆነችው ሲስተር ሙሉነሽ ወልደመስቀል በማእከሉ ከአስተባባሪነት በተጨማሪ ከስነአእምሮ ጋር በተገናኘ ችግር ያለባቸውን እንዲሁም ከመደፈር ጋር ተያይዞ ጭንቀት የደረሰባቸውን ማረጋጋት እንዲሁም ሕክምና መስጠት የመሳሰለውን ሁሉ ትሰራለች፡፡ ሲስተር ሙሉነሽ እንደገለጸችው ሴቶች በቤታቸው፣ በስራ ቦታ እንዲሁም በተለያየ አጋጣሚ ሊደፈሩ ስለሚችሉ አገልግሎቱ የሚሰጠው የእድሜ ገደብ ሳይኖረው ለሁሉም ሴቶች ነው፡፡ የመደፈር ጥቃት በሴቶች ብቻ ሳይሆን በወንዶች ላይም እንደሚከሰት የታወቅ ሲሆን ማእከሉም እንደ ተከፈተ ብዙ ወንዶች የሐኪም መረጃ ለማግኘት ወደማእከሉ ቢመጡም ሊሟሉ የሚገባቸው ብዙ የህክምና አሰራሮች ስላሉ በአሁኑ ወቅት ግን የወንዶቹ ተቋርጦአል። ስለዚህ ወንዶቹ የሚሄዱት ወደሌሎች ሆስፒታሎች ሲሆን ጋንዲ መታሰቢያ ሆስፒታል የሴቶች እንደመሆኑ መጠን ሴቶቹ ሙሉ ለሙሉ ሕክምናው ይሰጣቸዋል ብለዋል፡፡

በማእከሉ የሚሰጠውን አገልግሎት ተዘዋውረን እንደተመለከትነው ከሆነ ሕጻናቱ የሚጫወቱባቸው ቁሳቁሶች እንዲሁም ቤተሰብ የሌላቸው ለተወሰኑ ቀናት የሚያርፉበት መኝታ ክፍል እና በተሟላ የምግብ አቅርቦት እንደሚስተናገዱ ለመመልከት ተችሎአል፡፡ ሲ/ር ሙሉነሽ ወልደመስቀል እንደተናገሩት ከሆነ ሕጻናቱን እና የተጎዱትን በማስተናገዱ ረገድ በክፍሉ ውስጥ ያሉት ነርሶች በሙሉ ፈቃደኝነት አገልግሎቱን እንደሚሰጡ ለመረዳት ተችሎአል፡፡ ዶ/ር ስንታየሁ ታከለ የማእከሉ አስተባባሪ ናቸው፡፡ ዶር ስንታየሁ እንደገለጹት ተጠቂዎቹ ሕጻናት ከሆኑ በቤተሰባቸው አማካኝነት አዋቂዎቹ ደግሞ እራሳቸው ወደማእከሉ ይቀርባሉ። ማንኛዋም ሴት ተደፍሬአለሁ ስትል ቃሉዋ ታማኝነት አለው። ስለዚህ ተጠቂዋ ካርድ በማውጣት የህክምናውን አገልግሎት ለላቦራቶሪ ፣ለመድሀኒት፣ ተኝቶ ለመታከም ...ወዘተ ሁሉንም ሙሉ በሙሉ በነጻ ታገኛለች፡፡ በተለይም ሴትዋ ጥቃቱ በተፈጸመ በቅርብ ቀን ድረስ ባለው ጊዜ ...ማለትም ፡- ጥቃቱ ከተፈጸመባት እስከ ሶስት ቀን ድረስ ባለው ጊዜ ወደማእከሉ ከመጣች ከኤችአይቪ ቫይረስ ለመከላከል የሚያስችለውን መድሀኒት እንድታገኝ ይደረጋል፡፡ ጥቃቱ በተፈጸመ እስከ አምስት ቀን ድረስ ወደ ሕክምናው ማአከል ከመጣች ያልተፈለገ እርግዝናን ለመከላከል የሚያስችል መድሀኒት ይሰጣታል፡፡ ጥቃቱ ከተፈጸመባት እስከ ሁለት ሳምንት ድረስ ባለው ጊዜ ከመጣች የአባላዘር በሽታ እንዳይይዛት የሚከላከል መድሀኒት ይሰጣታል፡፡

ዶ/ር ስንታየሁ እንደችግር የገለጹት ተጠቂዎቹ ሁሉም በቅርብ ቀን ውስጥ ወደህክምና ማእከሉ አለመምጣታቸውን ነው፡፡ ማእከሉ ከተከፈተ ጀምሮ እንደታየው ልምድ ከሆነ ሴቶች የሚመጡት ጥቃቱ በተፈጸመ ከሶስት እስከ ስድስት ወር እና ከዚያም ካለፈ በሁዋላ ነው፡፡ አንዳንዶቹ ወደማእከሉ የሚደርሱት ያልተፈለገ እርግዝና ከተከሰተባቸው በሁዋላ ሲሆን በአገሪቱ የውርጃ ሕግ መሰረት ተጠቃሚ እንዲሆኑ የሚደረግ ቢሆንም በከፊል ይህንን እርዳታ ሊያገኙ የማይችሉ ይሆናሉ። ለምሳሌም እርግዝናው ከ28/ሀያ ስምንት ሳምንት በላይ ከሆነው ተንከባክበናት እንድትወልደው ከማድረግ ውጭ ሌላ እርዳታ ማድረግ አይቻልም፡፡ከዚያም ውጭ ሌሎች በሽታዎችን ለመከላከል ሲባል ሊያገኙ የሚገባቸውን እርዳታ እንዳያገኙ ይሆናሉ እንደዶክተር ስንታየሁ ማብራሪያ፡፡ ዶ/ር ስንታየሁ አክለውም ይህ ማእከል ከሚሰራቸው ስራዎች መካከል የህክምና ማስረጃ መስጠት ይገኝበታል፡፡ ይህ የህክምና ማስረጃ እንደቀድሞው በእንግሊዝኛ ሳይሆን በአማርኛ የሚጻፍ ነው፡፡ እንደቀድሞው በእንግሊዝኛ ተዘጋጅቶ ወደትርጉም ቤት የሚያስኬድ እና የሚያስቸግር ሳይሆን በወቅቱ በሴትዋ አካል ላይ የተገኘውን መረጃ መሰረት በማድረግ ወደፖሊስ የሚላበት ነው ፡፡

በእርግጥ ይህ ወንጀል ነው አይደለም የሚለውን የሚወስነው የፍትህ አካሉ እንጂ ሕክምናው አይደለም፡፡ በዚህ አጋጣሚ የምናገረው አሉ ዶ/ር ስንታየሁ ...ማንኛዋም ጥቃቱ የደረሰባት ሴት ችግሩ በደረሰ ውስን ቀናት ውስጥ ወደማእከሉ መቅረብ ብትችል መረጃውን በተሟላ ሁኔታ ማቅረብ ይቻላል፡፡ ነገር ግን ብዙዎቹ የቆሰለው አካላቸው ድኖ ገላቸውን ፣ልብሳቸውን ታጥበው እና ከቀናትም ባለፈ ወራት ፈጅተው ስለሚመጡ ምንም መረጃ የማይገኝበት አጋጣሚ ብዙ ነው ብለዋል ዶ/ር ስንታየሁ ታከለ የማእከሉ አስተባባሪ፡፡ በማእከሉ ያገኘናት የፖሊስ ባልደረባ ም/ሳይጅን ጽጌ ደግፌ ትባላለች፡፡ ም/ሳጅን ጽጌ ቢሮ ውስጥ አንድ ጥሩ አሻንጉሊት ፊት ለፊት ተቀምጦአል፡፡ እሱዋም እንደገለጸችው ይህ አሻንጉ ሊት ሴቶቹ በተለይም ህጻናቱ የደረሰባቸውን ችግር ለማስረዳት እፍረት ቢሰማቸውና ድብቅ ቢሆኑ እንዲናገሩ ለማጫወቻነት የተቀመጠ ነው፡፡

እንደ ምክትል ሳይጅን ጽጌ መግለጫ ቀደም ሲል በፖሊስ ጣቢያ ይህ ስራ በሚሰራበት ጊዜ መረጃው በፍጥነት ስለማይደርስና ባለጉዳ ዮቹም ከቦታ ቦታ በመዘዋወር እንግልት ስለሚደርስባቸው ጉዳዩ ፍትህ ሳያገኝ መዝገብ የሚዘጋበት እና ተከሳሾች ነጻ የሚወጡበት አጋጣሚ ይስተዋል ነበር፡፡ አሁን ግን ከአንድ አመት ወዲህ ይህ የፖሊስ ስራ ከህክምናው ጋር ተጣምሮ በአንድ ማእከል ውስጥ ሐኪም፣ አቃቤ ሕግ እና ፖሊስ በመሆን መስራት በመቻሉ ውጤቱን በፍጥነት በመቀባበል ተጎጂዎቹም ሳይንገላቱ መረጃው ለፍትህ አካላቱ እንዲደርስ አስችሎአል፡፡ ም/ሳይጅን ጽጌ የተጠቂዎችን የእለት ሁኔታ ስትገልጽ ከአስሩም ክፍለ ከተማ አንዳንድ ጊዜ ምንም ተጎጂ ላይመጣ ሲችል አንዳንዴ ደግሞ በቀን እስከ አስር እና ከዚያም በላይ ሴቶች ተጎጅዎች ወደ ማከሉ ሊመጡ ይችላሉ፡፡ በእድሜ ደረጃም በአብዛኛው ሕጻናት በተለይም እስከ አስራ አምስት አመት ድረስ ያሉት ተጎጂዎች ናቸው፡፡ በጋንዲ ሆስፒታል በተቀቋቋመው ማእከል ውስጥ አገልግሎት የሚያገኙ ተጎጂዎች ሕክምናውን ካገኙና የደረሰውን ችግር ካስረዱ በሁዋላ ወደመጡበት ክፍለ ከተማ በመሄድ የፖሊስ ሪፖርቱን እንዲያገኙ ይደረጋል፡፡ ጉዳት ያደረሱት ሰዎች ተገቢውን የፍትህ እርምጃ እንዲያገኙና ተጎጂዎቹም በዚህ ፍትሕ እንዲረኩ ለማድረግ ዋናው የህክምናው ማስረጃ ሲሆን ለዚህም ተጎጂዎች በጊዜ ወደህክምና ማእከሉ በመቅረብ ተገቢውን ክትትል ቢያደርጉ ለአሰራር ይበልጥ አመቺ መሆኑን እንመሰክራለን፡፡

የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ከፍትሕ አካሉና ከህክምና ማእከሉ ጋር በመጣመር ይህንን ስራ ከጀመረ ወዲህ በሴቶችና በቤተሰብ ላይ የነበረው መንገላታት በእጅጉ መቀነሱን መመስከር ይቻላል ብላለች ም/ሳጅን ጽጌ ደግፌ፡፡ የሜዲካል ዳይሬክተሩ ዶ/ር ደረጀ አለማየሁ እንደሚሉት ፖሊስ፣ አቃቤ ህግና የህክምናው ዘርፍ በጋራ የሚሰሩበት ይህ የሴቶችና ሕጻናት የተቀናጀ የፍትህና የእንክብካቤ ማእከል በሀገራችን የመጀመሪያው ሞዴል ማእከል ነው፡፡ የጋንዲ ሆስፒታል የተመረጠበትም ምክንያት የሴቶች ሆስፒታል ስለሆነ እና አገልግሎቱን ከዚያ በፊትም ስለሚሰጥ ነው፡፡ በፌደራል ጤና ጥበቃ ሚኒስርና በጤና ቢሮ አማካኝነት ጥያቄው ሲቀርብ የህብረተሰቡ ትልቅ ችግር እና ሴት ሕጻ ናቱ የሚጎዱበት እንደመሆኑ ጋንዲ ሆስፒታልም የራሱን ግልጋሎት ሊሰጥ ይገባል በሚል ከስም ምነት ተደርሶ እነሆ ስራው ከተጀመረ አንድ አመትን አስቆጥሮአል፡፡

በአሁኑ ወቅት በአገራ ችን ከፍላጎታቸው ውጭ የወሲብ ጥቃት ለደረሰባቸው ሴቶች የህክምና ማስረጃን ለፍትህ አካል የማ ቅረብ ስራን የሚሰራው ይህ በጋንዲ ሆስፒታል የሚገኘው የሴቶችና ሕጻናት የተቀናጀ የፍት ህና የእንክብካቤ ማእከል ብቻ ነው፡፡ ወንዶቹን በሚመለከት ግን የህክምናውን ማስረጃ በትክክል ከሚመለከተው ሐኪም የማግኘትን አሰራር በመከተል ወደ ጥቁር አንበሳ እና ዘውዲቱ ሆስፒታል እንዲሄዱ ይደረጋል ብለዋል ዶ/ር ደረጀ አለማየሁ የጋንዲ ሆስፒታል ሜዲካል ዳይሬክተር፡፡

Published in ላንተና ላንቺ

ማህበሩ የጓደኞች ነው የቤተሰብ?

የት/ቤት ጓደኞቼም የቤተሰብም አለኝ፡፡ ከ40 ዓመት በፊት የተጀመረ ነው፡፡ አንዳንድ ጓደኞቼ፣ እህቶቼ ቢያልፉም እስከዛሬ ይሄው ማህበሩን እንጠጣለን፡፡ ዛሬ አንቺም ወደ ቤቴ የመጣሽው የመድሃኒያለም ማህበር ትናንት አውጥቼ ነው፡፡ በጣም የተለየ ፍቅር አለን፡፡ የትምህርት ቤት ጓደኞችሽ---የት ነው የተማርሽው? የቄስ ትምህርት አባታችን አስተማሪ በቤታችን ቀጥረው ነው ያስተማሩን፡፡ ከ1ኛ- 8ኛ ክፍል ደግሞ አስፋው ወሰን ት/ቤት ነው የተማርኩት፡፡ ከትምህርት ቤት ጓደኞቼ ጋር በ21 እና በ27 ማህበር አለን፤ ማህበር ሲኖር በየቤታችን አዝማሪ ይቆማል፤ ማስንቆ የሚጫወት፡፡ ወንጂና ናዝሬትም እህቶቼ አሉ፤እዛም እየሄድን እንዝናናለን፡፡

እረ እንደው ተይኝ አልኩሽ ---- የተንፈላሰሰ ዘመን ነበር፡፡ በማህበራችሁ ቀን የሚጫወቱት አዝማሪዎቹ የሚታወቁ ነበሩ? አዎ፡፡ እነ ወረታው፣ ባይረሳው---- እንዴት ቆንጆ ድምፅ አላቸው መሠለሽ፡፡ እነሱ ወደ ቤታችን ሲመጡ ታዲያ ሁሉም ግጥም ሰጪ ነው፤ ሁሉም ተቀባይ ነው፡፡ ቤትም ባይመታም፡፡ ማሲንቆዋቸውን ይዘው ይመጣሉ፤ ጨዋታው ሌላ ነው አልኩሽ፡፡ ደሞዝ እኮ የላቸውም ግን በየወሩ ፅዋ የገባበትን ቤት ስለሚያውቁ ማህበሩ በሚወጣበት ቤት ይመጣሉ። መጀመሪያ ፀሎት ይደረግና ምሳ ይበላል፣ ከምሳ በኋላ የንስሃ አባቶቻችን ያሳርጋሉ፡፡ ከዛ በኋላ አሸሸ ገዳሜ ነው የእኔ እናት፡

ግጥም ከመስጠት ወደ ዘፋኝነት ገባሽ ማለት ነው?

ያን ጊዜ ዘፋኝነትን አልሜው አላውቅም ነበር። ድምፃዊ ሰይፉ ዮሐንስ የሚባል ወንድም ነበረኝ፡፡ ወላጅ አባታችን ዘፋኝ ሆነ መባልን ሲሰሙ የሞተ ያህል ነው ያለቀሱት፡፡ አለማወቅ እኮ ነው--- ማን ያውቀዋል ይሄንን፡፡ አባቴ በጣም አዘኑ…የወንድሜን መታመም ሲሰሙ ግን ድንጋጤአቸው ባሰ፡፡ በጣም በጣም ደግ ልጁ ነበረ፡፡ እርሱም ሞተ፤ አባቴ በጣም ተፀፀቱ --- ምን ታደርጊዋለሽ? አለማወቅ ይጎዳል። ወንድሜ በሞተ በዓመቱ ነው አባታችን የሞቱት፤ በእርሱ ሃዘን (እንባ) ወንድሜ ከሞተ ከአስር ዓመት በኋላ ነው ሙዚቃ የጀመርኩት፡፡ አባቴ ዘፈን አይወዱም ነበር፡፡ ግን በገና ነበራቸው፤ የቅዳም ሱር እለት በገናቸውን አውጥተው ሲደረድሩ ፤የገና ዕለት ጌታን እያመሰገኑ ሲጫወቱ የድምፃቸው ማማር ልዩ ነው ---- እናቴም ጥጥ ስትፈትል እያንጎራጎረች ነበር፡፡ ‹‹…ባለድሪ›› የሚለውን ዘፈን ከእርስዋ ነው የወሰድኩት። ‹‹…ገዳማይ ---- ገዳማይ ---ገዳማይ›› እያለች ታንጎራጉራለች፡፡ የእናቴን ድምፅ ወንበር ስር ተደብቀን ወይም ግድግዳ ተከልለን ነው የምንሰማት። እማዬ ድምፅዋ በጣም ነበር የሚያምርው፡፡ አሁን በህይወት የለችም፡፡

እናትሽ የሙዚቃ ስራ ስትጀምሪ በህይወት ነበሩ?

አዎ! ድምፄን የሞረድኩበትን ‹‹አንተ ባለድሪ” የሚል ዘፈን እናቴ ትወደው ነበር፡፡ በአባትዋ ጎንደሬ ስለሆነች ጨዋታው ይስባታል፡፡ የመጀመሪያ የካሴት ስራዬንም እናቴ እንዴት ትወደው ነበር መሰለሽ፡፡

ከዘፈን በፊት ምን ነበር የምትሰሪው?

“ፎር ሽፕ ትራቭል ኤጀንት” የሚባል ድርጅት ውስጥ ትኬት ኤጀንት ሆኜ እሰራ ነበር፡፡ ራስ ሆቴል ዴስክ ነበረችኝ፡፡ እዛ እንግዳ ይመጣል፡፡ እንግዶችን ተቀብሎ የሚፈልጉትን መረጃ መስጠት፣ መኪና ማከራይት፣ ፎርም ማስሞላት፣ ዲፖዚት መቀበል ነበር ሥራዬ፡፡ ድርጅቱ ከተወሰነ ጊዜ በኋላ ተዘጋ። በወቅቱ የልጆች እናት፤ የቤተሰብ ሃላፊ ነበርኩ---‹‹ምን ሆኜ ነው የምኖረው..›› ብዬ ሳስብ፣ ጓደኞቼ “እነ በቀለች ክትፎ ከትፈው እየሸጡ ይኖሩ የለ፡፡ ክትፎ ክተፊ›› አሉኝ፡፡ ክትፎ ግን ሞያ ይጠይቃል አይደል-- ሞያ ለእኔ!! እኔ እናትሽ እኮ አንቱ የተባልኩ ባለሞያ ነኝ፡፡ የወላጆቼ ቤት እዚህ ካዛንቺዝ ነበር። እዛው ጊቢ ውስጥ አንድ ክፍል ተሰጥቶኝ እኖር ነበር፡፡ ክትፎ ቤት ከፈትኩ፡፡ አንድ ቀን ታዲያ ሰዎች ክትፎ ሊበሉ ቀብረር ያለውን ድምፃዊ ከተማ ይፍሩን ይዘውት መጡ፡፡ ያን ቀን አንድ ዕቃ ጠፍቶብኝ ተበሳጭቼ ነበር፡፡

ይሄን ያህል የተበሳጨሽው ምን ቢጠፋብሽ ነው?

አንድ ሙሉ ካርቶን ውስኪ፡፡ አንድ ዘመድ ነበር--- አውጥቶ ሽጦብኝ ብስጭት ብዬ ነበር፡፡ አልቅሼ ፊቴን ስጠራርገው የልጅነት መልክ ጥሩ ነው፣ ወለል ‹‹ፏ›› ነው የምለው፡፡ እነ ከተማ ክትፎውን እየበሉ ይጨዋወታሉ፡፡ ከዚያ ከተማ መዝፈን ማንጎራጎር ጀመረ፡፡ እኔም ከጎኑ ቁጭ ብዬ አንጎራጉራለሁ፡፡ ከዛ ከተማ ድንገት ብድግ ብሎ ‹‹እዚህ ቤት ሁለተኛ ክትፎ እንዳይከተፍ›› አለ፡፡ ‹‹ምነው አመምዎት?›› አልኩኝ ያልተስማማቸው፣ አለርጂ የሆነባቸው መስሎኝ፡፡ ‹‹ይሄን ቆንጆ ድምፅ ይዘሽ በምን ምክንያት ነው የማትዘፍኝው?›› አሉ፡፡ ‹‹ድምፅ አለኝ እንዴ?›› አልኩኝ ለራሴ ‹‹ምንድን ነው የምትጠጭው?›› አሉኝ፡፡ እኔ ግን እንኳን በዛ ጊዜ ዛሬም መጠጥ የሚባል አልቀምስም፡፡ ‹‹እረ እኔ ምንም አልፈልግም… አልጠጣም›› አልኳቸው፡፡ ሲያስጨንቁኝ ‹‹ኮካ ይሻለኛል›› አልኩኝ፡፡ ያን ጊዜ ግሩም ነበር ኮካኮላ---ከኮካኮላው ውስጥ ሳላይ ውስኪ ጨምረውብኝ….እንደ ውሃ ጭልጥ አደረኩት፡፡ ከትንሽ ደቂቃ በኋላ ደስ አለኝ… ‹‹እንዴ ምን ሆኜ ነው ደስ ያለኝ…ምን አገኘሁ›› እያልኩ አስብ ነበር። ለካ ለብታ ማለት ይሄ ነው፡፡ ከዛ በኋላ ሰንጥቄ ሰንጥቄ ለቀቅኩት ዘፈኑን፡፡ የማንን ዘፈን እንደዘፈንሽ ታስታውሺያለሽ?

ከተማ እኔ ቤት የተጫወተውን ባቲ፣ ትዝታን፣ ተይ ማነሽን ተጫወትኩ --- ከአሁን በኋላ ‹‹አምቦ ውሃሽን አቀዝቅዥ፣ ቆንጆ ውስኪ አቅርቢ --- እኛ እንግዳ ይዘን እንመጣለን ---- አበቃ ክትፎ ቤት›› አሉኝ፡፡ ከዛ ምን አለፋሽ --- ከአለም አንደኛ ሆንኩኝ፡፡

በማግስቱ የምሽት ክበብ ተጀመረ?

መጀመሩስ ተጀመረ፡፡ መጥተው “በይ ተጫወቺ” ሲሉኝ ከየት ይምጣ፡፡ ያቺ የለችማ የተለመደችው ብረት ለበስ…. ታዲያ ወሰድ አታደርጊም ነበር--- እኔ ምኑን አውቄው----በፊትም እኮ ወኔዬን ያመጣው ምን እንደሆነ አላውቅም፡፡ በኋላ እኮ ነው የነገሩኝ፡፡ ግን እየለመድኩ መጣሁ ---- ሌላ ሆነ እንግዳው፣ ደንበኞቼ በዙ---የብር አቆጣጠሬን ብታይ አስቅሻለሁ፡፡ እንግዶቼን ሸኝቼ ስጨራርስ----.ብር እቆጥራለሁ፡፡ ‹‹..አንድ..ሁለት…ሶስት..አራት.. እባካችሁ ተኙ እናንተ ልጆች---መሸ እኮ-- ነገ ትምህርት ቤት ወየውላችሁ..›› ብሩ ከእጄ ይንጠባጠባል፡፡

የሽልማቱ ብር ነው?

ሽልማቱ ተይኝ ይረግፍ ጀመር፡፡ ማን አውቆት ቁጥሩን ----ከትራሴ ስር አድርጌው ነው የማድር --- ልጆቼ በጠዋት ሲነሱ ----ገንዘቡን ለቃቅመው እየሳቁ ‹‹..አንቺን ብሎ ቆጣሪ›› ብለው ይሰጡኛል፡፡

መኖሪያሽም የስራ ቦታሽም አንድ ቦታ ነበር ማለት ነው?

መጀመርያ አዎ፡፡ በኋላ ግን ሃብት መጣ --- ካሳንቺዝ እርሻ ሚኒስቴር አካባቢ ቤት ገዛሁ፡፡ ዛሬ ንብ ባንክ ሆኗል፡፡ ታሪኩ ብዙ ነው ባክሽ…በመሃል ታመምኩ፡፡ ሶስት ወር ሙሉ እጅና እና እግሬ ተይዞ ፓላራይዝድ ሆኜ ተኛሁ፡፡ (የቤት ስልክ ጮኸና ጨዋታችንን አቋረጠን፡፡ ከካናዳ ወንድ ልጅዋ ነበር የደወለው) ከዚያልሽ --- በጠበሉም በምኑንም ብዬ ተሻለኝ፡፡

በመሃል ስራሽን አቁመሽ ነበር?

አዎ ሙሉውን አቁሜ ቤቱን አከራየሁት። መጨረሻ ላይ ያከራየኋት ሴት እገዛዋለሁ ብላ ስሙን አዛውሬላት ነበረ---በቼክ አንድ ነጥብ አምስት ሚሊዮን ብር ሰጥታኝ ነበር---ከዚያ እዛ ዱባይ የሚባል አገር ተነስታ ሄደች፡፡ ቤቱ በሃራጅ ተሸጠና ለእኔ ስድስት መቶ ሺ ብር ተሰጠኝ፡፡ ከባንክ በቀኝ እና በግራ እጄ ሶስት መቶ ሺ፣ ሶስት መቶ ሺ ብር ይዤ ስወጣ በጣም ከበደኝ፡፡ ‹‹ፈጣሪዬ በአቅሜ ነው የሰጠኸኝ..ያንን አንድ ሚሊዮን አምስት መቶ ሺ ብር..አግኝቼ ቢሆን እንዴት ነበር የምይዘው..ተመስገን ጌታዬ ይሄንኑ በረከቱን ረድዔቱን ስጠው›› ብዬ--- (በድጋሚ የቤት ስልክ ጮኸ፡፡ አሁንም ከካናዳ ሌላኛዋ ልጅዋ ደወሎ፤ ሰላምታ ሰጥታ ቆይቶ እንዲደውል ነግራው ዘጋች) የካሳንቺሱ ስራ ቆመ ማለት ነው -- አንድ ዓመት ይህል ቁጪ አልኩኝ ያለ ስራ። ከዛም ለምንድን ነው ቁጪ የምትይው ብሎ ቁምላቸው የሚባል የፋሲካ ባለቤት ተቆጣኝ፡፡ ከዛ ኦርጋኔንና የራሴን ባንድ ይዤ እዚያ ሄድኩኝ፡፡ አብረውኝ የሚጫወቱትን ሳክሲፎኒስትና ኦርጋኒስት ይዤ ማለት ነው፡፡ ‹‹ራሄል እዚህ ገብታለች›› ሲባል…ተይኝ አልኩሽ --- ሰው እንደጉድ ይጎርፍ ጀመር፡፡ ደንበኞችሽ ታዋቂ ሰዎች፣ ባለሥልጣናትና ባለሃብት--- ነበሩ ይባላል፡፡ እንደውም አንዴ ፕሬዚዳንት ግርማ ወልደ ጊዮርጊስን ቃለ መጠይቅ ስናደርግላቸው---.የአንቺን የምሽት ክበብ በጣም ይወዱት እንደነበር ነግረውናል --- እጣ ክፍሌም እንደዛ ነገር ነው፡፡ የአዲስ አበባ መሳፍንት መኳንት፣ የራስና የደጃዝማች ልጆች፣ ማን ይቀራል…እገሌ ከእገሌ አልልሽም፡፡ የጨዋ ልጆች ይመጡ ነበር፡፡ ስርዓት ለሌለው እንኳን ስርዓት አስተምሬ ነው የምለከው፡፡ በጃንሆይም ጊዜ ከቤተመንግስት ሰዎች ጋር ነበር ቅርበቴ፡፡ በቃ ይወዱኛል፡፡ ዘፋኝ ሳልሆንም እኮ ነው፡፡

እንዴት ወደ ቤተመንግስት ለመቅረብ ቻልሽ?

ያኔ ቤተመንግስት ቱሪስቶች ሲመጡ አጉራሽ ይፈለግ ነበር፡፡ ቤተ-መንግስት ሄደን እንጀራ እናጎርሳለን፡፡ የቤተመንግስት እንጀራ እንደዚህ ሶፍት ነጭ ነበረ(በእጅዋ የያዘችውን ሶፍት እያሳየችኝ) ፈረንጆቹ ናፕኪን እየመሰላቸው እንጀራውን እንደ ሶፍት ይጠቀሙበታል፡፡ ቤተመንግስት ውስጥ በጣም ስለተቸገሩ--- እስኪ ቆነጃጅትን ፈልጉ ተባለ። አንድ እኔን በጣም የሚያውቅ ሰው ነበረ…ነፍሱን ይማርና ኮማንደር እስክንድር ‹‹ዋይን ገርል ራሄልን ጥሩ›› አለ፡፡

ዋይን ገርል ነበርሽ እንዴ?

አዎ፡፡

ዋይን ስፔሻሊስት ነኝ፡፡ እንዴት--- የት ተማርሽው? ታሪኬ ብዙ ነው አላልኩሽም፡፡ እስቲ አውጊኛ ---- ዛሬ እንግዲህ አብረን ማደራችን ነው፡፡ ግዴለም አጫውቺኝ ---- ስሚ----.ድሮ ሁለቱን ልጆቼን እንደወለድኩ ባሌን ፈታሁ ከዛ ‹‹ራስ ሆቴል ኮርስ መውሰድ አለብኝ›› ብዬ አሰብኩና ለሶስት ወር ያህል የገበታ ዝግጅት (tabel set up) የእንግዳ መስተንግዶ አሰጣጥ (how to serve the guest) ሰለጠንኩ፡፡ እንግሊዝኛውም ሌላ ነው--- እንደ አሜሪካን ነው የምናወራው፡፡ የእኛ ትምህርት ቤት እንደአሁኑ ቀላል መስሎሻል---ከሶስተኛ ክፍል በኋላ በእንግሊዝኛ ነው የምታወሪው፡፡ በተለይ በእንግሊዝኛ አስተማሪ በኩል----እኛ የተማርንበት ዘመን ሌላ ነበር፡፡ በጣም ቆንጆ ትምህርት ቤት ነው የተማርነው ግን አልሰራንበትም፡፡ እኔን ያልሽ እንደሆነ ግን በጣም የገባኝ አራዳ ስለነበርኩ በወቅቱ ሰርቼበታለሁ፡፡ እና የ‹‹ዋይን ገርል›› ኮርስ ስጨርስ ምርጫ ተሰጠኝና ጊዮንን መረጥኩ፡፡ ያኔ የነበሩት ሆቴሎች በጣም ትንሽ ናቸው፡፡ ዋቢ ሸበሌ ገና እየተጠናቀቀ ነበር፡፡ በተረፈ ጊዮን ሆቴልና ኢትዮጵያ ሆቴል ናቸው፡፡ እኔ ጊዮን ሆቴል ገባሁ፡፡ በአስተናጋጅነት ነው? ስለ በቬሬጅ (መጠጥ) ነበር ያጠናሁት፡፡ ስለ ኮክቴል አሰራር አውቃለሁ --- አንድ መጠጥ ከአንድ መጠጥ ጋር ኮክቴል ይደረጋል፡፡ አፕሬቲቩ፣ ዳይጄስቲቩ----የተለያዩ የዋይን ዓይነቶች አሉ--- ሬድ፣ ዋይት፣ ሮዜ፣ ድራይ፣ስዊት፣ ሚዲየም… ከምን ከምን ምግብ ጋር እንደሚወሰዱ አውቃለሁ። ካስተመሮቹ በጣም ይደነቁ ነበር፡፡ የት ነው የተማርሽው፤ የት አወቅሽው ይሉኛል፡፡ ስንት ዓመት ሰራሽ በዋይን ገርልነት? አራት ዓመት ከስድስት ወር ነው የሰራሁት። ስራውን ብወደውም እየሰለቸኝ መጣ፡፡ አንድ ቀን አኩርፌ ተቀምጬ አንድ ደንበኛችን አዩኝ። የአርጀንቲና አምባሳደር ነበሩ፡፡ ስሚ----ብዙ ካስተመሮቼ የሚያውቁኝ በጣም ሳቂታ፣ ደስተኛ፣ ተጫዋች መሆኔን ነው፡፡ የሚያኮርፍም ሰው አልወድም፡፡ ኩርፊያም አልወድም፡፡ ስለዚህ ‹‹ምነው ዛሬ አልሳቅሽም?›› አሉኝ፡፡ ‹‹ደከመኝ የሌሊት ስራ ደከመኝ›› አልኳቸው፡፡ “So?” አሉኝ፡፡ ‹‹በቃ ሰለቸኝ አስጠላኝ…›› መለስኩላቸው “Why don’t you come to my embassy, I am going to move by next week.” (ለምን ወደ እኔ ኤምባሲ አትመጪም? በሚቀጥለው ሳምንት እገባለሁ) እሽ ብዬ ሄድኩ፡፡ እቃ ግዢ ክፍል (ፐርቼዘር) አደረጉኝ፡፡ ከዚያ የጣሊያን ክልስ ፀሃፊና አራት ዘበኞች ቀጠርኩለት፡፡ ሁለት የማታ፣ ሁለት የቀን። የዘበኞች ዩኒፎርም(የቤተመንግስት ልብስ ሰፊ ነበር) እሱ ጋ ሄጄ አሰፋሁ፣ ባርኔጣቸውን አሰራሁ። ሁለት ሾፌሮችም ቀጠርኩ፡፡ የኤምባሲ ሾፌሮች የሚለብሱትን አውቃለሁ፡፡ ወጥ ቤትም ቀጠርኩ---የፅዳት ባለሙያ (ሃውስ ኪፐር) እንዲሁም አትክልተኛ ሁሉ ቀጠርኩ፡፡ ሥራ ብቻ ነው ወይስ ሌላም ግንኙነት ነበራችሁ? ኦኦ---ባለትዳር እኮ ነው፡፡ እኔ ስራውን ነው የፈለግሁት፡፡ (የቤቷ ስልክ ለሦስተኛ ጮኸ…) እንግዲህ ቻይው---- ልጆቼ አሜሪካና ካናዳ ነው ኑሮዋቸው…ልክ ሲነጋ የኔን ድምፅ ሳይሰሙ ቀናቸውን በስመዓብ አይሉም…(ከአሜሪካ ሴት ልጅዋ ነበረች የደወለችው)---ከተወሰነ ጊዜ በኋላ የአምባሳደሩ ሚስት መጣች፡፡ ይሄኔ ችግር ተፈጠረ። ‹‹ምንድን ነች?›› ብላ አፈጠጠች፡፡ ‹‹ይሄን ሁሉ የሰራችው እስዋ ናት›› አሏት፡፡ ‹‹ሰዎችን ከመቅጠር ጀምሮ..ፈረስ ቤቱን፣ አበባውን …የቤቱን ቀለም..ይሄን ሁሉ የሰራች እስዋ ናት›› በማለት አስረዷት፡፡ በጣም ሃርድ ወርከር ናት…ብላ ብታደንቀኝም ከጥቂት ጊዜ በኋላ አልተመቸኋትም መሰለኝ---ደሞዜም በጣም ብዙ ነበር፡፡ ምን ያህል ይደርሳል? 2ሺ ብር--- ይሄ ሁሉ ከሙዚቃው በፊት ነው አይደል-- ሙዚቃ ባልታሰበበት ጊዜ እኮ ነው የማወራሽ። እዚህና እዚያ አስረገጥሺኝ እኮ፡፡ እንዳልኩሽ የሰውየው ሚስት አልተመቸኋትም፡፡ ስርዓት አለኝ---ሰው አከብራለሁ---ሰው ስነሥርዓት ከሌለው አልወድም---ወዲያውኑ ነው የማስወግደው። ሁለተኛ ማየት አልፈልግም፡፡ እናም‹‹..በቃ ወደ ውጪ መሄዴ ነው ….›› ብዬ ስነግረው አምባሳደሩ በጣም ደነገጠ፣ ተጨነቀ፡፡ እኔ ግን ትዕግስቴና ፍላጎቴ ተዘግቶ ስለነበር ትቼው ወጣሁ፡፡ ይሄን ሁሉ ያስታወሰን እኮ ለአጉራሽነት ወደቤተመንግስት መግባትሽ ነው----.የአጉራሽነቱስ ጉዳይ--- አጉራሽነትማ----ጃንሆይ ጥሩ ጥሩ ልጆችን አምጡ ብለው አዘዙ፡፡ ‹‹እንደውም ጊዮን ሆቴል ሁለት ዌይትረስ አሉ አምጡዋቸው›› ተባለ፡፡ ቤተመንግስት ገብተን ፈረንጆችን እናጎርስ ጀመር፡፡ ፈረንጆቹ.. “Oh my God. What is this? Is this napkin or what?...’” እያሉ ይወናበዱ ነበር፡፡ ስናጎርሳቸው ደስ እንዲላቸው ብለን ፊታቸው እጃችንን እንታጠብ ነበር----ከዛ ስናጎርሳቸው ተደስተው ሊሞቱ፡፡ ቆንጆ ነሽ----አድናቆት ምናምንስ አልነበረም? “you have a beautiful smile, you Ethiopians are beautiful” ይላሉ (ውብ ፈገግታ አለሽ--እናንተ ኢትዮጵያውያን ውብ ናችሁ) ----ምን ልበልሽ--- አድናቆት በአድናቆት ነው----ልዕልቶቹም ያዩናል፡፡ የሆነ ዝግጅት ሲኖር በመካከላቸው ካናፒ እናዞራለን፡፡ ‹‹እንዴት ቆንጆ ናት›› ይሉኝ ነበር፡፡ የአልጋ ወራሽ ሚስት በጣም ያደንቁኝ ነበር፡፡ ልዕልት ተናኘ ወርቅ ነፍሳቸውን ይማረው፡፡ …አረ ተይኝ---አድናቆታቸው ራሱ ገንዘብ ነው፡፡ አክብሮታቸው…ሰላምታቸው…አመለካከታቸው..ነገረ ስራቸው ሌላ ነበር፡፡ በነገስታቱ ተሸልመሽ ታውቂያለሽ?

እጅግ በጣም ብዙ ሽልማት እንጂ…የአንገት ወርቅ፣ የእጅ ወርቅ አምባር፣እንዲሁም ሰንጋ መግዣ ተብሎ 500 ብር ተሰጥቶኛል፡፡..የእኔ ልጅ---- ባሳለፍኩት ዕድሜ ቁጭ ማለትን አልወድም፣ የሰው እጅ መጠበቅን አልወድም፣ ስራ መስራት ያስደስተኛል፣ መጫወት መደሰት ቁምነገር መስራት---እጅግ ሰው እወዳለሁ..ስራ አልንቅም፡፡ የሚገባኝን ነገር አውቃለሁ፡፡

የሰው ነገር አልነካም፡፡ ለዚህም ነው ያልነካሁት የስራ ዓይነት የለም የምልሽ----.ቆይ ልቁጠርልሽ አርጀንቲና ኤምባሲ፣ ታንዛኒያ ኤምባሲ፣ ፊሊፕስ… ሾው ሩም ውስጥ ሁሉ እሰራ ነበር፡፡ የዋቢሸበሌ ፐርሶኔል አንዴ መብራት ሊገዙ መጥተው ‹‹ምን ልትሰሪ ያለ ፊልድሽ መጣሽ?›› ብለው ዋቢሸበሌ ወሰዱኝ..እዚያ ስሰራ ደግሞ የሂልተን ሆቴል ..“ፉድና ቤቨሬጅ ማኔጀር” መጡ፣ የውጪ ዜጋ ዋናው የሂልተንን ሃላፊ ጭምር ይዘው፡፡ ‹‹ምንድን ነው የምትበሉት?›› አልኳቸው፡፡ ‹‹አዘናል›› አሉ፡፡ ያዘዙትን ጠየቅሁ - ስጋ፣ ዶሮ፣ አሳ ነበር ያዘዙት፡፡ ሁለት ዓይነት ወይን ማዘዝ አለባቸው፡፡ አንድ ቀይ ዋይን፣ አንድ ነጭ ዋይን አልኩኝ፡፡ አለበለዚያ ሁለቱንም የሚያባላ ሮዜ ዋይን..አልኩና ሄጄ ጠየቅኋቸው፡፡

‹‹ምንድን ነው የምትጠጡት?

ምን ዓይነት ዋይን ላምጣላችሁ?›› አልኳቸው፡፡ ‹‹የምንበላውን ካወቅሽ አንቺ ጠቁሚን ምን ይሻለናል?›› አሉኝ፡፡ ሞያዊ ትንታኔ ሰጠኋቸው፡፡ በጣም ተገረሙ። ኢትዮጵያ ውስጥ እንደዚህ ዓይነት ባለሞያ አለ ብለው ተደንቀዋል፡፡ ከመሄዳቸው በፊት ‹‹ፈቃድሽ ከሆነ..ሰኞ ጠዋት ሂልተን ሆቴል እንድትመጪ›› አሉኝ፡፡ ‹‹የት ነው ሂልተን ሆቴል?›› ብዬ ጠየኳቸው፡፡ ‹‹እዚህ እዚህ ቦታ….›› ብለው ነገሩኝ፡፡ ‹‹እኔ የሆቴል ስራ ሰልችቶኛል..ሆቴል እንዳይሆን ስላቸው..›› ‹‹ኖኖ እንደዚህ አይባልም..ስራ እንደዚህ አይባልም እንድትመጪ..›› አሉኝ፡፡ ሂልተን ሆቴል ሄድኩኝ---“.አይዞሽ ሲደክምሽ ማረፊያ ክፍል እንሰጥሻለን” አሉኝ፡፡ “መቼሽ ቲፑ ሌላ ነው----በጣም ቆንጆ ቦታ ነው፡፡ የተወሰነ ቦታ ነው የምትሰሪው” ብለው አግባቡኝ፡፡ (አዲስ አበባ ሂልተን ሆቴል) የሚል እንዴት ያለ የሚያምር የአበሻ ቀሚስ ተሰራልኝ መሰለሽ ---ላይት ብራውን እንደ ጎልዲሽ ዓይነት --- አቤት መልክ---አቤት ቁመና…፡፡ ሂልተንስ ስንት ዓመት ሰራሽ? ከአራት ዓመት በላይ ሰርቻለሁ፡፡ በዘፈኖችሽ ላይ ንጉሶችን ማነሳሳት ትወጂያለሽ ---.የጣይቱ ጠጅ ነው…የምኒልክ እልፍኝ-- ትያለሽ እኔ የሰርቶ አደር ልጅ ነኝ፡፡

ግን እነዚህ አብሬያቸው ያሳለፍኳቸው እንግዶች..ክብር ያላቸው፤ ለሰው ልጅ ጥሩ የሚመኙ፤ ደጎች ናቸው። እግዚአብሄር ደግሞ የሰውን ልጅ ሲፈጥረው አንድ ነገር ይሰጠዋል…ሁሉን በፕሮግራም ነው የሚፈጥረው፡፡ እግዚአብሄር እኮ እኔን አድሎን ነው እንጂ---እኔ ማን ነኝ I am no body after all. ከማንም አልበልጥም፡፡ ሰው ስለምወድና ስለማከብር…አባቴ ሰርቶ አደርም ቢሆን አስተዳደጋችን እንዴት ሸጋ ነበር --- ልጆቼንም በዛ መንገድ ነው ያሰደግኋቸው፡፡

ውጪ አገር ስራዎችሽን አቅርበሽ ታውቂያለሽ?

በፍጹም፡፡ አንድ ጊዜ ብቻ አምባሰል የሚባል ሙዚቃ ቤት ዋሺንግተን ናይት ክለብ ነበረው። ለስድስት ወር ለመስራት ተስማምቼ ሄጄ ---.ለአራት ወር ያህል ከሰራሁ በኋላ ኢትዮጵያኖች በግል ጠብ እርስ በእርስ ተጋደሉ፡፡ ስራውን ትቼ ወደ አገሬ መጣሁ፡፡ ብዙም እንደዚህ ዓይነት ቦታ አይመቸኝም--- የትዳርሽ ጉዳይስ--- ልጆቼን ብቻዬን ነው ያሳደግሁት.--- ጠንካራ እናት ነኝ፡፡ .ባሎች ትንሽ አስቸጋሪዎች ነበሩ፡፡ ምን ይጎለኛል---ልጆቼን ለማሳደግ ብዬ “ልውሰድም” ቢሉ እሽ አልልም---.ይሄው ልጆቼን አሳደግሁኝ ዳርኩኝ--እግዚአብሄር ይመስገን፡፡

የዘመኑን ዘፈኖች ትሰሚያለሽ? እንዴት ነው ዘፈን ድሮ ቀረ ትያለሽ ወይስ ----

ድምፁ የወጣው አሁን ይመስለኛል፡፡ ወጣቶቹ ቆንጆ ቆንጆ ድምጽ አላቸው፡፡ ሲዲውን ስሰማው ጥሩ ነው፡፡ ብዙ ጊዜ የምሰማው ወይ ስለ ሃገር፣ ስለ አንድ ታሪክ፣ ወይም ስለኢትዮጵያ ሊሆን ይችላል። ኢትዮጵያ ታሪክዋ ሰፊ ነው፡፡ አንዳንዱን እያነሱ አንስቶ መስራቱ ጥሩ ነው፡፡ የፍቅር ነገር መቼም እንዳለ ነው አያረጅም፡፡ ፍቅር ትልቅ ነገር ነው። ሁልጊዜ ግን ስለ ፍቅረኛ፣ ስለ ባል፣ ስለ ሚስት--- ተጣላኝ ታረቀኝ አባረርከኝ…መለስከኝ…እንደዚህ ዓይነት በጣም ሲበዛ ጥሩ አይደለም። አንችዬ አርጅቼ ይሆን እንዴ? ግን አይደለም…ድሮም ይሄው ነው ስሜቴ…ሁሉም ይቅር እያልኩ አይደለም፡፡ በየመሃሉ ቁምነገር ቢገባበት ማለቴ ነው፡፡ እንጂ ድምፅማ የመጣው አሁን ነው፡፡ በድሮና በአሁን ዘፈኖች መካከል ያለው ልዩነት ምንድን ነው ትያለሽ?

ምርጫቸውና የደረሱበት ቴክኖሎጂ ነው። በአብዛኛው የፈረንጅ መዚቃ፤ የፈረንጅ ሲኒማ፤ የፈረንጅ ዘፋኞች የሚሆኑትን ነው የሚሆኑት። ከአሁኑ ዘፋኞች ቴዲ አፍሮን ---- ጎንደር ብዙ የተጫወቱ ልጆች አሉ --ማዲንጎ እስከ ወንድሙ…ግሩም ናቸው፡፡ ማዲንጎን ያየሽ እንደሆን የበላይን ታሪክ አስቀምጦታል--- በደንብ --- ታምር ነው መቼም፡፡ እኔማ ያሳዝነኛል ያንን ሲጫወት፡፡ እነዚህ ቁም ነገር ያላቸው ነገሮች ናቸው፡፡ የኢትዮጵያ ባህል እኮ ተወርቶም አያልቅ፡፡ መጽሐፍም አይችለው፡፡ አስተማሪዎች ያስፈልጋሉ፡፡ እኛ እኮ ድሮ ትምህርት ቤት ስንማር መጀመርያ ስለሃገራችን ጋራ ሸንተረር..ተምረን ነው ወደ ውጪ የምንሻገረው፡፡ አሁን ማን ያስተምራል….እዚህም አገር አማርኛ እንደ ሁለተኛ ቋንቋ እየታየ ነው፡፡ እኛ ድሮ በትምህርት ቤት ውስጥ ባንዲራ አውርደን ክፍል እንደገባን ፀሎት እናደርጋለን፤ ከፀሎት በኋላ የሚገባው አስተማሪያችን የግብረገብ ነው፡፡ ከዛ በኋላ ነው ትምህርቱ የሚቀጥለው፡፡ ኢትዮጵያ ከአለም አንደኛ ናት ብል----.አላፍርም። ስለ ሃገሬ ተናግሬም አልጨርሰው፤አቅሜም አይችለው፡፡

አገራችን፣ ህዝባችን፣ አለባበሳችን፣ ምግባችን፣ አየሩ…በክረምቱ ሰዓት ክረምቱ የታወቀ ነው፤ በበጋው ሰዓት በጋው የታወቀ ነው፣ በበልግ ሰዓት በልጉ የታወቀ ነው፤ አለቀ፡፡ አየራችን ደግሞ ልዩ ነው፡፡ የምታኮራ አገር የሚያኮራ ህዝብ ነው ያለን..ይሄ ራሱ ቢዘፈንለት አይበቃም፡፡ ስንት ካሴት በነጠላ እና በጋራ ሰራሽ.. ወደ 12 ካሴቶችን ሰርቻለሁ፡፡ “ምኒልክ” የሚለው ዘፈኔ ዜማውን የሰራሁት እኔ ነኝ፡፡ የሁሉም ካሴቶቼ ግጥም ድርሰት የይልማ ገብረ አብ ናቸው፡፡ የድምፅሽን ለዛ ስለሚያውቀው ነዋ ይልማ መርጦ የሚሰጥሽ... አዋ፡፡ ይልማ በአንድ ወቅት አንድ ስራ ገጥሞት አንድ ካሴቴ ላይ ብቻ ሶስት ዘፈኖች የሌላ ሰው ነበሩ፡፡ ከይልማ ጋር ስንሰራ ግጥሞችን መክረንባቸውና ተነጋግረን ነው - ይሄ ይውጣ ይሄ ይግባ ብለን፡፡

አንድ ጊዜ ምን ሆነ…‹‹በደሳሳ ጎጆ ቁጭ ብዬ ብቻዬን ሳለቅስ..›› ምናምን የሚል ግጥም ..መጣልኝ…እኔ እንደዚህ አይነት ነገር …ምንድን ነው በፍፁም አልዘፍንም አልኳቸው፡፡ ችግርም የለብኝ..ይቅርታ አድርጉልኝ የእኔ ስሜት ለእንደዚህ ዓይነት ነገር አይሰራም አልኳቸው፡፡ በጣም ሳቁ..ጭንቅ አልወድም ሌግዠሪ ነገር ነው የምወደው…ዝም ያለ ቆፍጠን ያለ…ለሰውም ቀለል ሲል..ነው፡፡ የእኔን ለቅሶና ሃዘን ህዝብን ስማልኝ ማለት ምንድን ነው፡፡ የሆነ ድባብ እኮ ይፈጥራል፡፡ ይቅርታ እንግዲህ እኔ እንደዚህ አይነት ታይፕ የለኝም፡፡ ከተሸመ አሰግድ፤ ጋሽ ባህሩ፣ ጋሽ ይርጋ፣ ከተማ መኮንን፣ ዳምጠው…ኡፍ ለዛ አላቸው እኮ፡፡ my God!! የማይሰለቹ እኮ ናቸው፡፡ ስሚ የዛን ዘመን ዘፋኞች..እነ ወረታው…የወረታው ድምፅ እኮ..ራሱ ጊታር ነው፤ ራሱ ሳክስፎን ነው፤ራሱ ቤዝ ጊታር ነው፤ በጣም ጎልደን ድምፅ እኮ ነው ያለው፡፡ ከብዙዎች ጋር ሰርቻለሁ፡፡ ልረሳ ነው እንዴ..እረ አንቺ ልጅ ይሄ ነገር ያሰጋል----

እርጅና መጣ መሰለኝ ዕድሜሽ ግን ስንት ሆነ?

63 ዓመቴን ባለፈው የፋሲካ ዕለት አከበርኩ.---.ገና ልጅ እኮ ነኝ፡፡ መልካም ልደት፣ ረጅም ዕድሜ ተመኝተንልሻል። በሶስት መንግስታት ውስጥ በአርቲስትነት ትታወሻለሽ-- የደርግ ጊዜን ሳልነግርሽ፡፡ በምሽት ክበቤ ውስጥ ..እረ ገዳዬ፣ እንደው ዘራፌዋ፣ እንደ ኮሜዲ አድርጌ የምጫወተው ስራ ነበረኝ፡፡ እረ ገዳዬ የሚለውን በእንግሊዝኛ እለው ነበር--- እስኪ አሁን በይልኝ-- Oh killer oh killer The useless goat give birth to nine She is died and her children I love the killer I love the killer As well as the shooter When I feel tired I rest under the umberella of ጀግናዬ hair. ብታይ ሰው ይሄን እንደ ኮሜዲ ነው የሚሰማው----.ትርጓሜው ደግሞ ትክክል ነው፡፡ እረ ገዳዬ አረ ገዳዬ የማትረባ ፍየል ዘጠኝ ትወልዳለች ልጆችዋም ያልቃሉ እስዋም ትሞታለች፡፡ ስሚ እኔ ጀግና እወዳለሁ፡፡ ዘፋኝ ባልሆን ወታደር ነበር የምሆነው፡፡ በጣም በጣም ነው ወታደር መሆን.. ለመዝመት አስበሽ አታውቂም ታዲያ-- አይ ልጄቼን ከወለድኩ በኋላ ..ሃላፊነቱም አለ..።

የአሁኑ አልበምሽ..ከስንት ጊዜ በኋላ ወጣ?

ከ7 ዓመት በኋላ…ሰርቼው ቁጭ አድርጌው ነበር…ኮፒ ራይቱም አስጨናቂ ስለነበረ..ሰርቼ ቁጭ አደረኩት የሚገዛ ሲጠፋ፡፡ አቶ ቁምላቸው ገብረስላሴ የፋሲካ ባለቤት/የሚሞ ባለቤት…የተፈጠረውን አጫወትኩት፡፡ ከፈቃደ ዋሬ የአምባሰል ሙዚቃ ቤት ባለቤት ጋር እንደ ወንድም ነው የሚተያዩት፡፡ ተነጋገሩና ይሄው ባለፈው ለሰው አፍ አበቁልኝ፡፡

ምን ያህል ገቢ አገኘሽበት ?

እሱን ተይው ከአሁን በኋላስ ምን ታስቢያለሽ?

አገሬ ላይ ቁጪ ብዬ እግዚአብሄርን ማመስገን ነው…የምስጋና መዝሙር ነው ሃሳቤ፡፡ ደስተኛ ነኝ…እንምታይው ሁሉ ሙሉ ነው..ተመስገን ለእግዚአብሄር ምን ይሳነዋል፡፡ አይንሽን አሞሽ ነበር? አዎ…ሼክ ሙሃመድ አሊ አሙዲ ናቸው ያሳከሙኝ…፡፡ የኢትዮጵያን ህዝብ በሙሉ እወዳቸዋለሁ…እንኳን ለፋሲካና ለዳግማይ ትንሳኤ በዓል አደረሳችሁ ብዬ እጅ እነሳለሁ፡፡

Published in ጥበብ
Saturday, 11 May 2013 14:02

የፋሲካ ሰሞን

ጊዜው አመሻሽ ላይ ነው፡፡ ቀኑን ሙሉ ጠቁሮ የዋለው ሰማይ የዝናም ሸክሙን አራግፎ ፀጥ ብሏል። ጨረቃ ደምቃ ወጥታለች፡፡ ኮከቦችም በጠራው ሰማይ ላይ ተዘርተዋል፡፡ ከጭቃ ጭቃ እያማረጥኩ ከቤቴ መዳረሻ ወዳለችው ቡና ቤት እንደልማዴ አመራሁ፡፡ በጠጪዎች መሀል አልፌ ጥግ አካባቢ ተቀመጥኩና የምጠጣውን አዘዝኩ፡፡ የቀረበልኝን ድራፍት እያጣጣምኩ ዙሪያዬ እቃኛለሁ፡፡ ሁለት ወጣቶች ተከታትለው ገቡና በተለምዶ ባለጌ ወንበር የሚባለውን ስበው ተቀመጡ፡፡ ያዘዙት ድራፍት እንደመጣላቸው የተመካከሩ ይመስል ባንድ ትንፋሽ ጨለጡትና ድጋሚ አዘዙ፡፡ በመካከላቸው ንግግር የለም፡፡ አንደኛው ፀጉሩን እያፍተለተለ መሬት መሬት ይመለከታል፡፡ አንደኛው ደግሞ በመስኮቱ አሻግሮ ሰማዩን ይቃኛል፡፡ “አየህልኝ?” የሚል ድምፅ ሰማሁ፡፡

ዘወር አልኩ፡፡ ፀጉሩ ገብስማ የሆነ ጠና ያለ ሰው ካጠገቤ ተቀምጧል። ሌላ ሰው በቅርበት የለም፡፡ ጥያቄው ለኔ መሆኑ ነው፡፡ “ምኑን?” አልኩት “እነዚህን ሁለት ወጣቶች” አለኝ ወደተቀመጡበት በጣቱ እየጠቆመ፡፡ በዚያ ቅዝቃዜ የመጀመሪያውን ድራፍት እንዴት በፍጥነት እንደጨለጡት እሱም እንደኔ ታዝቧቸው ኖሯል፡፡ “እና?” አልኩት “ምልከታቸውን ልብ ብለህልኛል?” “ምልከታቸውን ስትል … ” “አንደኛው በመስኮት አሻግሮ ሰማዩን፣ ሌላኛው ጫማው የተሸከመውን ጭቃ ሲመለከት ታያለህ? እናማ ወዳጄ በነሱ እይታ ሁለት ነገሮችን አስተዋልኩ።” “ምንና ምን?” “ትዝታና ተስፋን” “እንዴት?” “እንዴት ማለት መልካም! ትዝታ ያ ወጣት ጫማው ላይ እንደተሸከመው ጭቃ ነው፡፡ እንደ ልብ አያራምድህም፡፡ ያስጐነብስሃል፡፡

ትናንትህን እየቆዘምክ ልራመድ ብትል ያዳልጥሃል … ብትነሳም በትዝታህ ተጨማልቀህ ነው፡፡ ምክንያቱም ዛሬህን አልተጠቀምክበትማ … ዛሬህን አልሰራህበትማ! … ትርፍ ከተባለ ከትዝታህ የምታተርፈው ፀፀት ብቻ ነው፡፡” አለኝና ቢራውን አንስቶ ተጐነጨ፡፡ “እውነት ነው “አንድ ሰው ማርጀቱን የሚያውቀው በተስፋ መኖሩን ትቶ በትዝታ መኖር ሲጀምር ነው” የሚል አባባል አለ!” ሰውየው ግንባሩን እያኮሳተረ አፈጠጠብኝና “ከመኖርህ ያተረፍከው የራስህ የሆነ አባባል የለህም?” አለኝ፡፡ አከርካሪዬን የተመታሁ ያህል ተሰማኝ፡፡ በድንጋጤ የምናገረው ጠፋኝ፡፡ ሰውዬው ቀጠለ። “…ለነገሩ አንተን እንዲህ አልኩህ እንጂ እኔም ከኖርኩት ህይወት እንደ ጥፍጥሬ ፈልቅቄ ያወጣሁት የራሴ የሆነ አባባል የለኝም፡፡ እነዚያ ሁለት ወጣቶች እንደተቀመጡበት ባለጌ ወንበር በሰብዕናችን ስንባልግ፣ በየዕለቱ ሌላውን ለመምሰል ስንጥር የኛን ማንነት ቀብረነዋል…” ቢራውን ጨልጦ ድጋሚ አዘዘ። “የዚያኛውስ ወጣት ምልከታ ?” “እ … ያኛውን ወጣት ደግሞ ተመልከተው---- ቀና ብሎ ሰማይ ሰማዩን ይመለከታል … በሰማዩ ላይ ምን አለ? … ኮከብ … የተስፋ ተምሳሌት ነው፣ ቀና ብለህ በዘመንህ ሰማይ ላይ የሚያበራ የተስፋ ኮከብህን ፈልግ እንጂ … በትዝታህ ብቻ እየቆዘምክ በፀፀት ጊዜህን አትግፋ … ደግሞ አስተውል … ፋሲካን ልናከብር ሽር ጉድ ስንል ትርጓሜውንም ይዘን መሆን አለበት” “እንዴት?” “እንዴት ማለት መልካም … አየህ ወዳጄ ከሁለት ሺ ዓመት በፊት ክርስቶስ ሞትን ድል ነስቶ ተነሣ! አይደለም? “አዎን!” “አየህ ስለኛ ኃጢያት ሆኖ በመስቀል ላይ ሲፈፀም፡፡

ሞትን ለዘልዓለም ድል ነስቶታል፡፡ ለኛም ትንሣዔ ሆኖለታል፡፡ ይህ ማለት በኛ ሕይወት ውስጥ ትንሳዔ ዕለት በዕለት ነው፡፡ በኛ ውስጥ የተዋረደውን ማንነታችንን ወደ ክብር ለመመለስ ቀና ብለን በዘመናችን ሰማይ ላይ የተስፋችንን ኮከብ ከፈለግን ለሞተው ማንነታችን ትንሣዔ አለ፡፡ የትንሣዔን ኃይል ደግሞ ሞት ሊቋቋመው አይችልም … ተስፋ መቁረጥን … ተስፋ በማድረግ … እያሸነፈን … የክፋትን ምንጭ በመልካምነት እየጠረግን … ጥላቻን በፍቅር እየለወጥን … በመስቀል ላይ የተሠራውንና የተቀበልነውን ፍቅር ዕለ በዕለት ሕይወታችን ካደረግነው በየዕለት ኑሯችን ትንሣኤ አለ፡፡” ቢራውን ጨልጦ ተነሣ፡፡ የሰውዬው ጨዋታ ጥሞኛል፡፡ በኔ ግብዣ ጥቂት እንዲቆይ ጠየቅሁት፡፡ ስለ ግብዣዬ አመስግኖኝ ፣ መቆየት እንደማይፈልግ ነግሮኝ ወጣ፡፡ ይህ ከሆነ ሶስት ዓመት አለፈው፡፡ በዚህ ሶስት ዓመት ውስጥ ትንሣዔ በየዕለቱ መሆኑን ተረዳሁ፡፡ በፋሲካ ሰሞን ግን ያንን ሰው አስታውሰዋለሁ፡፡

Published in ጥበብ

በአዲስ ተስፋ የተዘጋጀ “የፊልም ድርሰት አፃፃፍ ብልሃት” የተሰኘ አዲስ መጽሐፍ ሰሞን ለንባብ በቅቷል፡፡ ረዳት ፕሮፌሰር ሙሉጌታ ጀዋሬ በመጽሐፉ ጀርባ ላይ በሰጡት አስተያየት፤ “የአገራችን የፊልም ኢንዱስትሪ በእውቀት የሚጽፉ ሙያተኞች እጅጉን ያስፈልጉታል፡፡

አሁን አሁን በፊልም ጥበብ ላይ የተዘጋጁ መፃሕፍት ታትመው ለንባብ እየበቁ ነው… የፈጠራ ጽሑፍ ተሰጥኦ እያላቸው አቅጣጫው (ቴክኒኩ) ለጠፋቸው ሁሉ እነሆ አቅጣጫው እላለሁ” ብለዋል፡፡ መጽሐፉ ከያዛቸው አብይ ርዕሰ ጉዳዮች መካከል “የድራማ ምንነትና ታሪክ”፣ “ፊልም ምንድነው?” “ፊልም እንዴት ይፃፋል” እና ሌሎችም ይገኙበታል፡፡ በ171 ገፆች የተቀነበበው መጽሐፉ በ55 ብር እየተሸጠ ነው፡፡

ተወዳጅነትን ያተረፈው “ግጥም በጃዝ” ፕሮግራም 22ኛ ዝግጅቱን የፊታችን ሪቡዕ ምሽት በራስ ሆቴል እንደሚያቀርብ አዘጋጆቸ አስታወቁ፡፡ አንጋፋው አርቲስት ተፈሪ ዓለሙን ጨምሮ አንዱዓለም ተስፋዬ፣ ምንተስኖት ማሞ፣ ደምሰው መርሻና ይሄነው ቸርነት የግጥም ሥራቸውን ሲያቀርቡ ሀብታሙ ስዩም ወግ ያቀርባል ተብሏል፡፡ በኃይሉ ገ/መድህን በበኩሉ ዲስኩር እንደሚደሰኩር ታውቋል፡፡

ጥበብ ኢትዮጵያ የጥበባት ማዕከል አምስተኛውን “ኢትዮጵያ ታንብብ” የንባብ ፌስቲቫል ከትላንት በስቲያ የጀመረ ሲሆን ፌስቲቫሉ ለአምስት ቀናት በተለያዩ ዝግጅቶች እንደሚቀጥል ታውቋል፡፡ በተለያዩ የንባብ ፕሮግራሞች በሚካሄደው በዚህ ፌስቲቫል፤ በአንደኛ ደረጃ ት/ቤቶች ታላላቅ ደራሲያን የንባብ ልምዳቸውን የሚያካፍሉበት መድረክ የተዘጋጀ ሲሆን ስለአገራችን የንባብ ባህል ጥናታዊ ጽሑፍ እንደሚቀርብም ተገልጿል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ መጽሐፍ አሳታሚዎች፣ አታሚዎች፣ አከፋፋዮች፣ ቤተመፃሕፍትና ማተሚያ ቤቶች የሚሳተፉበት ለአምስት ቀን የሚቆይ የመጽሐፍ አውደርዕይ እና ባዛር እንደተዘጋጀም ለማወቅ ተችሏል፡፡

Page 8 of 14