የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ የግል አሽከርና አልባሽ ስዩም ጣሰው በ14 ዓመት የቤተመንግስት አገልግሎታቸው፣ በዕለት ማስታወሻቸው ላይ ሲያሰፍሩ የቆዩትን መረጃ ጋዜጠኛ ግርማ ለማ አስተካክሎ በ2006 ዓ.ም “የንጉሡ ገመና” በሚል ለንባብ አብቅቶታል፡፡ የጃንሆይ የመጨረሻ ሰዓት ምን እንደሚመስል ለማስታወስ ከዚሁ መጽሐፍ ላይ ተከታዩን ቀንጭበን አቅርበናል፡፡ ጃንሆይ ከስልጣን የወረዱት መስከረም 2 ቀን 1967 ዓ.ም ነው - የዛሬ
40 ዓመት፡፡

…እርሳቸውም የተቀበሉት ከልብ ነው፡፡ ማታ የሻምበል ደምሴ የክብር ዘበኛ ንዑስ ኮሚቴ ሊቀመንበር ከጀ/ፍሬሰንበት ቢሮ ድረስ መጥቶ አቶ ክበበው ኃይሌንና አቶ ወንደሰን አንዳርጌን አነጋግሮአል፡፡ ይኸውም ግርማዊነታቸው ምናልባት ሕይወታቸውን በገዛ እጃቸው እንዳያጠፉ በአጠገባቸው የሚገኘውን መሣሪያና መድኃኒቶች በሙሉ እንዲያሸሹ ነግሮአቸው ሄደ፡፡ እነርሱም መድኃኒት ይኑር አይኑር ስለማያውቁ፣ መሳሪያው ብቻ ከአጠገባቸው ወደሌላ ኰሜዲኖ ውስጥ ተዛውሮ እንዲቀመጥ አደረጉ፡፡ እኔም ወደ ቤቴ ሄድኩ፡፡
በ2/1/67 ዓ.ም ጠዋት አድሚራል እስክንድር መጥተው፤ “አዋጅ ስለአለ ሬዲዮ ይከፈትላቸው” ስላሉ ገብተው፣ ሬዲዮ በ1፡30 ሰዓት ሲከፈት ሳይሠራ ትንሽ ቆየት ብሎ ግርማዊነታቸው ከሥልጣን መውረዳቸውን ሲያውጅ፣ ጃንሆይም “ወይ አንተ እግዚአብሔር” ብለው በጥሞና እስከመጨረሻው ድረስ አደመጡ፡፡ ከዚያም ትንሽ ቆይተን ከመኝታ ቤት ወደ ውጭ ወጣን፡፡
ከትንሽ ደቂቃዎች በኋላ አድሚራል እስክንድር መጥተው ጠሩንና ገባን፡፡ ከዚያም ልብስ መልበስ ጀመሩ፡፡ በሚለብሱበት ጊዜ ከመጥቆራቸው በስተቀር ከሰሞኑ ምንም ለውጥ አላሳዩም፡፡ ለብሰው ከጨረሱ በኋላ ፀሎት ለማድረስ ስለቆሙ ትተናቸው ወጣን፡፡ ፀሎት እንደጨረሱ 2፡10 ሰዓት ሲሆን በረንዳ ወጥተው ከተንሸራሸሩ በኋላ፣ ወደ ውስጥ ተመልሰው ከአሽከሮች መኝታ ቤት ሲደርሱ ልዕልት ሰብለ ደስታና ወ/ሮ ሜሪ አበበ ከአድሚራል እስክንድር ጋር ሲመጡ አገኙዋቸው፡፡ እጅ ነስተው ሳሙዋቸው፡፡ ከዚያም ተያይዘው ወደ መኝታ ቤት ገቡ፡፡ ከዚያም አድሚራል መጡና “ቁርስ ገበታ ቤት ከሚሆን መኝታ ቤት ቢሆን ይሻላል” ስላሉ ለቦዮቹ ነገርንና ወደዚያው ተዘጋጅቶ፣ ቁርስ በተለመደው ሰዓት 2፡20 ሰዓት ቀረበ፡፡
እርሳቸውም ከተዘጋጀላቸው ከመልበሻ ቤት ገቡና ተቀመጡ፡፡ ሲያዩዋቸው ታዲያ የመዝናናት መልክ ነበራቸው፡፡ ቁርሳቸውንም ከወትሮው ባልተለየ ሁኔታ በሉ፡፡ እንደውም ከውሻቸው ጋር እየቀለዱ ሥጋ ሲያጐርሱ፣ ሲስቁ በጣም ገረመኝ፡፡ እንኳን ከሥልጣን የወረዱ ምንም የሆኑ አልመሰላቸውም ነበረ፡፡ ቁርስ በልተው እንደጨረሱ ፀሎት አደረሱና በ 2፡38 ወደ ሳሎን ወጡ፡፡
በ2፡43 ሰዓት ደግሞ ከመኝታ ቤት ተመለሱና እቢሮአቸው ቁጭ ብለው “ቦርሳዬን አምጣልኝ” አሉኝና ወስጄ ሰጥቼ ሲከፍቱት ወጣሁ፡፡ ትንሽ እንደቆየሁ አንድ ነገር ተሰማኝ፡፡ ይኸውም ምናልባት መድኃኒት ከቦርሳቸው ውስጥ አስቀምጠው እንደሆነ አውጥተው የጠጡ እንደሆነ ብዬ ስለተጠራጠርኩ፣ አድሚራልን ጠርቼ ገብተው ከእርሳቸው ጋር እንዲቆዩ ስለነገርኳቸው፣ ከእህቶቻቸው ጋር ተያይዘው ገቡ፡፡
እነርሱም ሲገቡ ቦርሳቸውን ከፍተው ከውስጡ ዕቃ ይፈልጉ ነበር፡፡ መሳሪያቸውን ግን ማታ ካደረበት ቦታ አንስተው ከዱሮው ቦታ አሽከሮቹ መልሰው አስቀምጠውት ስለነበር፣ ለፀሎት እንደቆሙ ተመካክረን፣ እኔ ሁለት ሽጉጥና አንድ በቦርሳ ውስጥ ያለ አውቶማቲክ ሽጉጥ (በጣም ትልቅ ነው) አወጣሁና፣ ከተረኛው አሽከር መኝታ ቤት ካለው የወረቀት መመርመሪያ ውስጥ አስቀመጥኩት፡፡ ስለዚህ ከመድኃኒት ሌላ መሳሪያ ስለሌለ የሰጋሁት መድኃኒት ይጠጣሉ ብዬ ነበር፡፡
ጃንሆይና ልዑል ራስ እምሩ ቢሮ ገብተው ትንሽ ቆይተው፣ በ4፡00 ሰዓት የደርጉ አባሎች በጀ/ኃይለጊዮርጊስ ተጠርተው ከቢሮ ገቡ፡፡ ወደዚያው ሠላምታ ሰጡና አንድ የፖሊስ ሠራዊት ባልደረባ ሻለቃ አዋጁን አነበበላቸው፡፡ ይኸው ሻለቃ በቀደም ስለውጭ አገር ገንዘብ መመለስ ጉዳይ ለመነጋገር የመጡት የደርጉ አባሎች መሪና ወረቀቱንም ያነበበው ደበላ ዲንሳ ነበር፡፡ አዋጁን ለማንበብና ጃንሆይን ይዘው ለመሄድ በገቡ ጊዜ፣ ከ8 ቀን በፊት የክብር ዘበኛ መረጃ ሠራተኞች በሻምበል ኃይሉ አዴሳ ኃላፊነት ለውስጥ ጥበቃ ተብሎ የገቡት፣ ከአሽከሮች መካከል እደርጐቹ ላይ አደጋ እንዳይጣል ቁጥጥራቸው ፍፁም ሌላ ነበር፡፡ ከውጭ ደግሞ ዙሪያውን ከፎቅ ሆኖ እንዳይተኮስባቸው መሳሪያዎቻቸውን ወደላይ አድርገው ይጠብቁ ነበር፡፡
ደርጐቹም ገብተው ጃንሆይን እስከተገናኙ ድረስ የነበራቸው መረበሽ ከባድ ነበር፡፡ ከቢሮ ተጠርተው ሲገቡ እያንዳንዳቸው ሙሉ ትጥቅ ነበራቸው፡፡ ፊልም አንሺዎች፣ ፎቶግራፍ አንሺዎች፣ የድምጽ መቅረጫ የያዙ ጋዜጠኞች፣ ሪፖርተሮችና የወታደር ጋዜጠኞች ጭምር አብረው ገብተዋል፡፡ ከጋዜጠኞች የማውቃቸው አቶ ማዕረጉ በዛብህ፣ አቶ ደበበ እሸቱ (የድምጽ መቅረጫ) የያዘ፣ አቶ ተፈሪ ብዙአየሁ (የቴሌቪዥን ፊልም አንሺ) መብራት የሚያበራውን ስሙን አላውቀውም እንጂ ለዚሁ ሥራ ብዙ ጊዜ ይመጣል፡፡ ሻለቃውም አዋጁን አነበበ፡፡ በሚያነብበት ጊዜ ኡዚውን ከደረቱ ላይ አንግቶ ነው፡፡
አዋጁ ሲነበብ ግርማዊነታቸው በጽሞና በደንብ ሁነው ያዳምጡ ነበረ፡፡ ከዘወትሩ አሁንም ምንም ለውጥ አላሳዩም ነበር፡፡
አዋጁን አንብቦ ሲጨርስ፣ ግርማዊነታቸው የተገለለ ቦታ እንደተዘጋጀላቸው ስለሆነ ከልዕልት ተናኘ ጋር እንዲቀመጡ ስለተወሰነ አብረዋቸው እንዲሄዱ ጠየቃቸው፡፡ እርሳቸውም ተዝናንተው ተቀመጡና “እኛ ለሀገራችን በጦርነትም ሆነ በሰላም ጊዜ ሠርተንላታል፡፡ እናንተም ይህን ጠንቅቃችሁ ታውቁታላችሁ” ብለው ንግግራቸውን ሳይጨርሱ፣ ወታደሮቹ አንድ ጊዜ ግር ግር አሉና ጋዜጠኞቹን በሙሉ አስወጡዋቸው፡፡ ጋዜጠኞቹ ከወጡ በኋላ ንግግራቸውን በእርጋታ በመጀመር፣ “መጀመሪያ የጦር ኃይላችንን በዘመናዊ መልክ ስናዘጋጅ፣ ይህ አሁን የደረሰው የመሳሰሉ ነገሮች እንደሚደርሱ አስቀድመን የተገነዘብነው ስለሆነ ለኛ አዲስ አይደለም፡፡ ነገር ግን የወታደር ተግባሩ ጠረፍን ከአጥቂ ጠላት መጠበቅ ሲሆን፤ አሁን እናንተ በከተማ ተቀምጣችሁ አላማችሁን በመርሳት የምታደርጉት ትክክል አይደለም፡፡
“ወታደር ለጠረፍ እንጂ መቼ ለከተማ” አሉዋቸውና አንዳንዶቹን እየጠሩ መጠየቅ ጀመሩ፡፡
አንዱን የአየር ኃይል ባልደረባ “ና” ብለው፤ “ዕድሜህ ስንት ነው? አገልግሎትህስ?” እያሉ ሲጠይቁ፣ እኛንም በዚያ አካባቢ የነበርነውን አባረሩን፡፡
ወደዚያው አድሚራል እስክንድር ከእህቶቻቸው ጋር ፎቅ ላይ ስለነበሩ አስጠሩኝና ወጣሁ፡፡ እርሳቸውም ጀ/ፍሬሰንበት ከአጠገባቸው በምንም ዓይነት እንዳይለይ ንገረው ብለውኝ እሺ አልኳቸውና ቆምኩ፡፡ ወደዚያው ወደ መኝታ ቤት ከወሰኔ ጋር ገብተን፣ በመስኮት ቁልቁል ስናይ አንዲት ቮልስዋገን መኪና ስትቀርብ አየንና ሊወስዱዋቸው ነው ብለን ሮጠን ስንወርድ፣ አድሚራል ተጠርተው ወርደው ጃንሆይም ሲወጡ ደረስን፡፡ ወደዚያው ጃንሆይ የሚረዳዎት አሽከር ስለሚያስፈልግ፣ እርስዎ ደስ የሚልዎትንና የሚረዳዎትን ይምረጡ ሲሉ፣ እርሳቸውም “ወሰኔ ይሁንልኝ” አሉና መንገዳቸውን ቀጠሉ፡፡ ሲወጡም ዘወትር ለሽርሽር እንደሚወጡ ነበር፡፡
ወታደሮቹም ከግራና ቀኝ እንዲሁም ከኋላ አጅበዋቸው ነበር፡፡ ውጭ እንደወጡም የሹፌራቸው የጀ/ሉሉ ቮክስዋገን ቆማ ስለነበር፣ አጠገቧ ሲደርሱ ግራ ገባቸውና ቆሙ፡፡ ወደዚያው በሩ ሲከፈትላቸው ስለገባቸው ገቡ፡፡ በዚህ ጊዜ ውሾቻቸው አብረው ገቡ፡፡ ጐትተው አስወጡዋቸው፡፡ ከእሸቱ ጋር ጭቅጭቅ ተፈጠረ፡፡ በመጨረሻ ውሾቹን ታቅፎ ወደ ውስጥ አስገባቸው፡፡ በማግስቱ ዶክተር ግርማ መጥቶ ወሰዳቸው፡፡ በፊትም የሚያክማቸውና ሲያማቸውም እርሱ ቤት ነበር የሚሄዱት፡፡ እርሳቸው በቮክስዋገንዋ ሲሄዱ፣ አድሚራልን ደግሞ በትልቁዋ ኩምቢ ቮክስዋገን (የፖሊስ ናት) አስገብተው ወሰዱዋቸው፡፡ እኛም ተመልሰን እኔና ወሰኔ ዕቃ መክተት ጀመርን፡፡ ለኛ የመሰለን፣ የወሰዱዋቸው ግርማዊት ቪላ/የልዕልት ቤት/ ወይም ልዑል መኰንን ቤት እንጂ 4ኛ ክፍለ ጦር አልመሰለንም፡፡ ምክንያቱም የወጡት በ2ኛ በር ስለነበረ ነው፡፡ እኛም የሚያስፈልገውን ልብስ አዘጋጀን፡፡ ብዙውንም አውጥተን ከተትን፡፡ በዚህ ጊዜ የተቀሩት ቁጭ ብለው ይተክዙ ነበረ፡፡ አንዳንድ የሴት አሽከሮች ለዚያውም ድሆቹ ከሚያለቅሱ በስተቀር ከሌሎቹ አንድም የሚያለቅስ አልነበረም፡፡
በዚያ አካባቢም የተገኙት የበሉት ሳይሆኑ ድሆቹ ነበሩ፡፡ የበሉትማ ገና ዱሮ ወጥተው ዙሪያውን ያንዣብባሉ፡፡ በ5፡30 ሌሎች የደርግ አባሎች መጡና በጀ/ወርቁ የክብር ዘበኛ ተጠባባቂ አዛዥ አማካኝነት ከመኝታ ቤት ገቡ፡፡ ወደዚያው ቤቱንና ዕቃውን እየተመለከቱ፣ ግማሾቹ “መታሸግ አለበት” ሲሉ፣ ግማሾቹ ደግሞ የተለየ ሃሳብ ሲያቀርቡ፣ እኔና ወሰኔ ጀ/ወርቁን ዕቃ መክተት ያስፈልግ እንደሆነ ፈቃድ ጠየቅናቸው፡፡ እርሳቸውም “የሚያስፈልጋቸውን ሁሉ ቶሎ ቶሎ አውጡ” ብለው ፈቀዱልንና ጨርሰን አወጣንና ከተትን፡፡ እነርሱም ቤቱ በመታሸጉ ተስማሙና ታሸገ፡፡ ለጃንሆይ የሚያስፈልግ ዕቃ ሲኖር ከእኛ ዘንድ ሁለት ወይም ሦስት ሰው እየመጣ፣ ከአሽከሮቹ ጋር ከፍተው ዕቃው ከወጣ በኋላ እንደገና ይታሸጋል ብለው ተስማሙና አሸጉት፡፡
ከመኝታ ቤት የደርጉ አባሎች በገቡ ጊዜ አብዛኛዎቹ የሐዘን ስሜት ነበራቸው፡፡ በተለይም አንድ የጦር ሠራዊት ባሻ እንባው መጥቶ ግጥም ሲልበት፣ እንዳይታይ ዞር ብሎ እንባውን ሲጠርግ አይቻለሁ፡፡ የዕቃውንም መመሰቃቀል አይተው፣ “ይኸ ሳይነካ እንዳለ መሆን አለበት” በማለት ምንም ሳይነኩ ወጡ፡፡ ከዚያም ወደ ሳሎንና ገበታ ቤት ሄደው ዕቃውን እያዩ ሲያሽጉ፣ በ6፡45 ሌሎች የደርጉ አባሎች አቶ መንበረ ወልደማርያምን ይዘው መጡ፡፡ ከዚያም በፊት መጥተው ያሽጉ የነበሩትን የደርጉ አባሎች ጠርተው እሽጉን አስከፍተው ከመኝታ ቤት ገቡ፡፡ ከዚያም ትልቁን የገንዘብ መያዣ ቦርሳ ከፍተው፣ ከውስጡ ያለውን ብርና ልዩ ልዩ ዶክሜንት ማየት ጀመሩ፡፡ ታዲያ የቦርሳው ቁልፍ ከጃንሆይ ቀለበት ሥር ነበርና ቀለበቱን አምጥተው ነው የከፈቱት፡፡ ከአንድ ፊት ያለው ግን በቁጥር የሚከፈት ስለሆነና ስለላላወቁት ግማሾቹ “ይቀደድ” ሲሉ፣ አንድ መኰንን ግን “ይህ መቀደድ አይገባውም፣ ለታሪክ መቀመጥ አለበት” ስላለ፣ በመፈልቀቅ በእጃቸው እየገቡ በጐን በኩል አወጡ፡፡ በ7፡10 ሰዓት ልብሱና ምግቡ ጃንሆይ ወደአሉበት ቦታ ሄደ፡፡ …ለዘመን መለወጫ በዓል የተዘጋጀው ግብር የቀረበው ለደርጉ አባሎች ነበር፡፡ በዚህ ጊዜ እነዚያ ሲያማቱና ለዚህ ውድቀት ያበቁዋቸው፣ ሲዘርፉ የነበሩት አንደኛቸውም አልነበሩ፡፡ እዚያ ተኩራምተው ሲያለቅሱና ሲያዝኑ የነበሩት ምንም ያልተደረገላቸው ድሆቹ ብቻ ነበሩ፡፡ የጦር ሠራዊት ባልደረባ፣ ወታደር፣ ሹፌር፣ መጡ፡፡ ከዚያም እኔ ዘንድ መጥተው ምንም የሄደ “ዕቃ ስለሌለ ልንወስድ ነው የመጣነው፡፡ በተለይም የሚያርፉበት አልጋ ስለሌለ ቶሎ ቢሰጠን” ብለው ጠየቁኝ፡፡ እኔም “አቶ ጥላሁን እኮ ገና ከሰዓት በፊት ሄዶአል” ብለውኛል፤ ምናልባት አላስገባ ብለዋቸው እንደሆነ ብላቸው “የለም ውሸት ነው!” አለኝ፡፡
በተለይም የ10 አለቃው በጣም በማዘን “እስከ አሁን እኮ ከአንዲት ትንሽ ወንበር ላይ ቁጭ ብለው ነው ያሉት፤ ምነው እንደው የሚያስብ ሰውም የለ እንዴ?” አለኝ፡፡ እኔም ወደዚያው ወደ ዕቃ ክፍሉ ያሉትንና የሚያሽጉትን የደርጉ አባሎች ሄጄ ባነጋግራቸው፤ “ለምን እስከአሁን አልሄደላቸውም?” ቢሉኝ ሰው ቸልተኛ ስለሆነ ከእናንተ ዘንድ የሚያስገድድ ይሰጠኝ፡፡ በተለይም የዚህን ሥራ/ፕሮሲጀር/ የሚያውቀው ሻለቃ ሳህሌ ስለሆነ ከአለበት ቦታ ተፈልጐ እንዲወሰድ ብዬ ለአንድ የክብር ዘበኛ ሻለቃ ስነግራቸው፣ እርሳቸውም አንድ መቶ አለቃ ከላይ ግቢ ወጥቶ ለወታደሩ ትዕዛዝ እንዲሰጥና ዕቃ የሚወስዱ ሰዎች እንዳይቸገሩና በተለይም የሚስቸግሩ ሰዎች እንዳሉ እንዲያስገድዱ ብለው ሰጡኝ፡፡
ግርማዊነታቸው 4ኛ ክፍለ ጦር እንደደረሱ ኪሳቸው ተፈትሾ ብዕር፣ ክራቫት፣ ብራስሌት፣ ቀበቶ… ቀለበታቸውን፣ የአንገት ሐብላቸውን አውልቀው ወሰዱባቸው፡፡ ከዚህም ሌላ የማስታወሻ ደብተራቸውን ጭምር ወሰዱባቸው፡፡
በማስታወሻቸው ላይ ከመያዛቸው ሦስት ቀን በፊት ለአቶ መንበረ 10ሺ ብር ሰጥተው ኖሮ፣ ያን የሰጡትን ገንዘብ በማስታወሻቸው ላይ ጽፈውት ስለተገኘ፣ አቶ መንበረን ከታሰሩበት ቦታ ሄደው ገንዘቡን ለምን እንደወሰዱ ጠይቀው፣ “ለልጆቼ ማሳደጊያ ነው” ሲሉ፤ “አምጡ” ተብለው ያንን 10ሺ ብር መልሰው ለደርጉ አስረከቡ፡፡ ጃንሆይ የገቡባት ክፍል አራት በሦስት ስፋት ያላት ክፍል ስትሆን በውስጧም የነበሩት ሁለት ጥቋቁር የቆዳ ወንበሮች ብቻ ነበሩ፡፡ ክፍሉንና ወንበሮቹን ራሴ አይቻለሁ፡፡ ያን ጊዜ ጊዜ የነበሩት ከበረንዳ ላይ ነበር፡፡ የልዕልት ተናኘወርቅም ቦርሳ እንደዚሁ ተይዞ ከውጭ ቀርቶአል፡፡ በ12 ሰዓት አልጋና ምንጣፍ ስለሄደ ሊነጠፍላቸው ሲል፤ “ምንም አልፈልግም” ብለው ምንጣፉን አስወጥተው ጣሉት፡፡ አልጋው ደግሞ ሁለት ፍራሽ ስለነበረው፣ የላይኛውን ፍራሽ አንሱ ብለው አስነስተው እታችኛው ላይ ተኙ፡፡ ብርድ ልብሳቸውም አንድ ብቻ እንዲሆን አድርገው ከዚያው አደሩ…
=====
“…እኛ እኮ እጃችንን የሰጠነው አውቀን ነው፡፡ ይህ ሁሉ እንደሚመጣ አስቀድመን የተረዳነው ጉዳይ ነው፡፡ እኛ በሰላም እጃችንን የሰጠነው የህዝቡ ደም እንደራሺያና ፈረንሳይ ሪቮሉሲዮን በከንቱ እንዳይፈስ በማሰብና መከራችንን እኛው እንቀበል በማለት ነው፡፡ የሩሲያንም ሆነ የፈረንሣይን ሪቮሉሲዮን ደህና አድርገን ስለምናውቅ ነው፡፡ ከዚህ በላይ የወታደሩ እንቅስቃሴ ሶሺያሊስት እንደሚሆን አስቀድመን ተገንዝበነዋል፡፡ ስለዚህ ከላይ ባሉት አገሮች የደረሰው እልቂት በእኛም አገር እንዳይደርስ በማሰብ ነው፡፡ ነገሩ ሁሉ ሲጀመር ይህ በቀጥታ እንደሚመጣ እናውቀው ነበር፡፡ እግዚአብሔር ያመጣው ስለሆነ መታገል አይቻልም፡፡ የወደፊቱንስ ማን ያውቃል፡፡ ሁሉ በእርሱ እጅ አይደል?”…

Published in ህብረተሰብ
Saturday, 13 September 2014 13:15

ዕርቅና ፍቺ…

‘እውነት’ ይህን ያህል ‘አኩርፋናለች’ እንዴ! ልክ ነዋ… አይደለም ቤተኛችን ልትሆን አልፎ፣ አልፎ እኛ ዘንድ ‘ለቡና ብቅ ማለቱን’ ሁሉ ትታዋለች፡፡ እንደውም እውነት መናገር “ለክርና ማተቤ…” ምናምን ማለት የሀቀኝነት መለኪያ ሳይሆን ‘ከዘመኑ ጋር አብሮ መሄድ አለመቻል’ ነው፡፡

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
እንኳን ከዘመን ወደ ዘመን አሸጋገራችሁማ!
የማያልቅ የለም አይደል የሚባለው! 2006 እንደ ምንም ብሎ አለቀ፡፡ የተሳካለትም አጨብጨቦ ይዘፍናል፣ ያልተሳካለትም አጨብጭቦ ይቀራል! አጨብጭቦ የቀረው ህዝብ ብዛት በቁጥርና በመቶኛ ተሰልቶ ይነገረንማ!
በቀደም ዕለት በሸገር ኤፍኤም ላይ ‘የዓለም ቋንቋ’ ፕሮግራምን እየሰማሁ ሳለ የገረመኝን ነገር ስሙኝማ…አንዷ ከባለቤቷ ጋር ባለመግባባት የተለያየች አድማጭ ስለ 2007 ዕቅዷ ስትጠየቅ ምን አለች መሰላችሁ… “ከባሌ ጋር መታረቅ…” አይነት ነገር ነው ያለችው፡፡ አሪፍ አይደል!
“መቼ ምክንያት አግኝቼ በተለየኋት/በተለየሁት!” በሚባልበት ዘመን ከባሏ ጋር ለመታረቅ የምታቅድ ሴት ማግኘት የምር ደስ ይላል፡፡
አንድዬ ምኞቷን ያሳካላትማ!
እናማ… በርካታ ትተውን የሄዱ፣ ያባረርናቸው፣ ያባረሩን፣ ትተናቸው የሄድናቸው…ወዘተ ብዙ ልንታረቃቸው የሚገቡ ነገሮች አሉ፡፡
ከ‘ራሳችን’ ጋር መታረቅ አለብን፡፡
የምር እኮ…አለ አይደል… እንደው ነገሬ ብላችሁ ነገረ ሥራችንን ስታዩ…ከራሳችን ጋር ‘የቁርጥ ቀን ጠብ’ ላይ የገባን ነው የሚመስለው፡፡ ራሳችንን መሆን ትተን ሌሎችን ለመሆን የምንሞክረው ከራሳችን ጋር ፍቅር ስላለን ሳይሆን…አለ አይደል…ከራሳችን ስለተጣላን ነው፡፡ የራሳችንን ጓዳ ትተን የሌላውን ሰው ጓዳ የምንናፍቀው ከራሳችን ጋር ስለተጣላን ነው፡፡
2007 ከራሳችን ጋር የምንታረቅበት ዘመን ይሁንልንማ!
ከ‘እውነት’ ጋር መታረቅ አለብን፡፡
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…‘እውነት’ ይህን ያህል ‘አኩርፋናለች’ እንዴ! ልክ ነዋ… አይደለም ቤተኛችን ልትሆን አልፎ፣ አልፎ እኛ ዘንድ ‘ለቡና ብቅ ማለቱን’ ሁሉ ትታዋለች፡፡ እንደውም እውነት መናገር “ለክርና ማተቤ…” ምናምን ማለት የሀቀኝነት መለኪያ ሳይሆን ‘ከዘመኑ ጋር አብሮ መሄድ አለመቻል’ ነው፡፡ እናላችሁ…‘እውነት’ የምትለካው ጉዳዩ ለግለሰቡ ይጠቅማል አይጠቅምም በሚለው ነው፡፡ ‘የሚጠቅም’ ከሆኑ ሁለትና ሦስት ዘጠኝ የማይሆንበት ምክንያት የለም፡፡
2007 ከ‘እውነት’ ጋር የምንታረቅበት ዘመን ይሁንልንማ!
ከ‘ትህትና’ ጋር መታረቅ አለብን፡፡
የምር ‘ትህትና’ ምን አድርገናት እንደዘጋችን ይመርመርልንማ፡፡ ከትንሹ እስከ ትልቁ፡ እውቀት ካጠረው እውቀት እስከተረፈው፣ ከ‘ቺስታ’ እስከ ዲታ…ምን አለፋችሁ… ‘ትህትና’ ከሁሉም ጋር “መቃብሬ ላይ ብትቆም…” ምናምን የተባለች ይመስላል፡፡ እናላችሁ…ብዙ ቦታዎች ሰዎች የሚያናግሯችሁ በትህትና ሳይሆን “ጠብ ያለሽ በዳቦ…” አይነት ነው፡፡
የሆነ መሥሪያ ቤት ዘበኛ ልትገቡ ስትሉ “ወዴት ነው?” ሲላችሁ ዱላውን ጠበቅ አድርጎ ይዞና ዓይኖቹን የየተኮሰ የአሜሪካ ፓትሪዮት ሚሳይል አስመስሎ ነው፡፡
2007 ‘ትህትና’ን ይቅርታ ጠይቀናት ቢሆንም የምንታረቅበት ይሁንልንማ!
ከ‘አክብሮት’ ጋር መታረቅ አለብን፡፡
ስሙኝማ…ይቺ አገር እኮ ምን የመሰለ የመከባበር ባህል የነበረባት አገር ናት! በዕድሜ ትልልቅ የሆኑ ሰዎች ወደ ሆነ ክፍል ሲገቡ ከወንበር ብድግ ማለት፣ ታክሲ ወይ አውቶብስ ውስጥ ለአዛውንቶች ወይም ለነፍሰ ጡሮች ወንበር መልቀቅ፣ ለማንም ሰው በትህትና ሰላም ማለት…የመሳሰሉ አክብሮት የተሞላባቸው ባህሪያት ነበሩ፡፡
ዘንድሮ… አይደለም በዕድሜ የገፉ ሰዎች የሆነ ክፍል ውስጥ ሲገቡ ወንበር መልቀቅ፣ ቀድመው ወንበር የያዙ አዛውንቶችን “ተነስ!” ለማለት የሚቃጣን ዘመን ላይ ደርሰናል፡፡ አውቶብስና ታክሲ ላይ ወንበር የመልቀቅን ነገር ተዉት፡፡ አይታሰብም ማለት ይቻላል! “ለጤናሽ እንደምነሽ ከርመሻል?” “ሰላምና ጤና ለአንተ ይሁን…” ምናምን አይነት የመልካም ምኞት ሰላምታዎች ‘ከዕለታት አንድ ቀን…” የተለመዱ መሆናቸው ሁሉ ሊረሳ ምንም አልቀረውም፡፡
2007 ከ‘አክብሮት’ ጋር የምንታረቅበት ዘመን ይሁንልንማ!
ስሙኝማ…እግረ መንገዴን፣ እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ… ተከታዩዋን የምትመስል ቀልድ ሳትሰሙ አልቀራችሁም፡፡ ሰወዬው ማታ ሲጨልጥ ያድርና ቤቱ ገብቶ ለሽ ይላል፡፡ በማግስቱ ጠዋት ስላሳለፈው ምሽት ለማስታወስ ሲሞክር ሁሉም ነገር ይደባላለቅበታል፡፡ እናላችሁ…በበፊተኛው ምሽት ወዳመሸበት መጠጥ ቤት ተመልሶ ይሄዳል፡፡ ባሬስታውን “ጆን ማታ እዚህ መጥቶ ነበር እንዴ?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡ ባሬስታውም “አዎ፣” ብሎ ይመልስለታል፡፡ ሰውየው ምን ቢል ጥሩ ነው…“እኔ አብሬው ነበርኩ?”
“እኔ አብሬው ነበርኩ?” እስኪመስልብን ድረስ ከመጠጣት ይጠብቀንማ!
እናላችሁ…ከ‘ተፈጥሮ’ ጋር መታረቅ አለብን፡፡
‘ከዕለታት አንድ ቀን…’ በሚባል ጊዜ ይቺ አገር ጥቅጥቅ ባሉ ደኖች፣ በአረንጓዴ መስኮችና ተራራዎች የተሞላች ነበረች፡፡ (ደግ፣ ደግ ለሆኑ ነገሮች “ነበር…” “ነበረች…”፣ ምናምን አይነት የኃላፊ ጊዜ ቃላት ከመጠቀም አላቆ “ነው…” “ነች…” ለማለት ያብቃንማ!”)
እናላችሁ… ድፍን አገር መጥረቢያ ይዞ ይዞር ይመስል መለ መላችንን እየቀረን ነው፡፡
2007 ከተፈጥሮ ጋር የምንታረቅበት ዘመን ይሁንልንማ!
ደግሞላችሁ…ከ‘ምቀኝነት’ ጋር መለያየት አለብን፡፡ስሙኝማ…ከበፊት ጀምሮ የምንሰማት “ሀበሻ ምቀኛ ነው…”፣ የሚሏት ነገር አለች፡፡ እንግዲህ…እንደ ብዙ ነገሮች ይህንንም ጥናት አድርጎ በመቶኛ በምናምን የነገረን ስለሌለ (ምናልባት የሚነግረንም ስለማይኖር!) በአጠቃላይ ማውራቱ አሪፍ ላይሆን ይችላል፡፡ ግን…አለ አይደል…የማይካደው ነገር ምቀኝነት በዝቷል፡፡ የሆነ ጎረቤታችን ፈረንካ ስላገኘ እንመቀኛለን፣ የሆነ ጓደኛችን ሸሚዝ ስለገዛ እንመቀኛለን፣ የሆነች ወዳጃችን ‘አማሪካን ልትሄድ’ ስለሆነ እንመቀኛለን፡፡2007 ከ‘ምቀኝነት’ ጋር ‘የምንፋታበት’ ዘመን ይሁንልንማ! ከ‘እብሪት’ ጋር መለያየት አለብን፡፡ደጋግመን እንደምንለው እብሪት በዝቷል፡፡ ስልጣን ያለውም ስልጣን የሌለውም፤ ገንዘቡ ባንኮችን ያጨናነቀውም ባንክ ምን እንደሆነ የማያውቀውም፤ መአት ኮሌጆች የበጠሰውም፣ በኮሌጅ አጥር ጎን አልፎ የማያውቀውም…እብሪት በሽ፣ በሽ ነው፡፡ በምንም መለኪያ እብሪት ትክክል ሊሆን አይችልም (ይቅርታ፣ ላስተካክልና…“…ትክክል ሊሆን የማይችልበት ሁኔታ ነው ያለው…”) 2007 ከ‘እብሪት’ ጋር ‘የምንፋታበት’ ዘመን ይሁንልንማ!ከ‘ሸር’ ጋር መለያየት አለብን፡፡
ሸር በዝቷል፡፡ የሚገርማችሁ ነገር…አለ አይደል… ዘንድሮ የሆነ ሰው ላይ ሸር ለመፈጸም ምክንያት እንኳን የማያስፈልግበት ዘመን የደረስን ይመስላል፡፡ በአንድ ወቅት እንደተባለው “የዓይናቸው ቀለም ስላላማረን…” ብቻ ክፉ የምናስብባቸው ሰዎች ሞልተዋል፡፡
2007 ከ‘ሸር’ ጋር ‘የምንፋታበት’ ዘመን ይሁንልንማ! ብቻ ምን አለፋችሁ…በርካታ እርቅ ልንፈጽምባቸው የሚገቡ፣ በርካታ ፍቺ ልንፈጽምባቸው የሚገባቸው ነገሮች አሉ፡፡ አንድዬ ሁሉንም ያሳክልንማ!
መልካም አዲስ ዓመት!
ደህና ሰንብቱልኝማ!

 

Published in ባህል

“ይማሯል እንደ አካልዬ! ይዋጉዋል እንደ ገብርዬ!”

         ይህን የተናገሩት ዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ ናቸው፡፡ በዘመናቸው የነበሩ ካህናትና የእስልምና መሪዎች “እኔ እበልጣለሁ ሊቁም እኔ ነኝ” እየተባባሉ ያስቸገሩ ነበርና ሁለቱን ወገኖች የሚፈትኑበት አጋጣሚ ሲፈልጉ ዘመን መለወጫ ደረሰ፡፡ የዘመን መለወጫ ዕለት ደግሞ ክርስቲያኑም ሙስሊሙም በፌስታ የሚያከብሩት ቀን ነው፡፡
እናም አፄ ቴዎድሮስ የእስልምናም ሆነ የክርስትና ሊቃውንትን ቦሩ ሜዳ (ወሎ) ላይ ሰበሰቡና “እንደምታውቁት አገሬ ድሃ ናት፤ እኔም ድሃ ንጉስ ነኝ፤ ብችል ኖሮ ለክርስቲያኑና ለሙስሊሙ ወገን ብቻ ሳይሆን ለእያንዳንዱ ዜጋ አንዳንድ ሰንጋ ባድለው ደስ ይለኝ ነበር፡፡ ግን አልቻልሁም፡፡ ስለዚህ ለበአል መዋያ እንዲሆናችሁ ይህን ሰንጋ ሸልሚያችኋለሁና ተካፍላችሁ ብሉ” ይሏቸዋል፡፡ ፈተናው የሚጀመረውም እዚህ ላይ ነው፡፡
ከየቦታው በአዋጅ የተሰበሰበው ቃዲና ቄስ “እኔ ነኝ የምባርክ፣ እኔ ነኝ የምባርክ” በማለት ሽኩቻ ይጀምራል፡፡ በመሃሉ ግን መምህር አካለ ወልድ ሰርፀወልድ ድምፃቸውን ከፍ አድርገው፣ ነጭ ጭራቸውን በመነስነስ መናገር ሲጀምሩ፣ የካህናቱ ሁካታ ወደ ሌላ ጉርምርምታ ተሸጋገረ፡፡ የንግግራቸው ፍሬ ሃሳብ “ቀድሞ ለመባረክ ጠብ አያስፈልግም፡፡ ስለዚህ ካህናት ቢላዋውን ለሙስሊሞች ስጡ እነሱው ይባርኩት” የሚል ነው፡፡
በዚህ ንግግራቸው ሙስሊሞቹ በአሸናፊነት ስሜት ሲደሰቱ፣ የካህናቱ ወገን በበኩሉ በ “ተጠቃን” ባይነት መንፈስ ጉርምርምታና እርግማኑን በመምህር አካለ ወልድ ላይ አዥጐደጉደው፡፡ በሙስሊሞች የተባረከው ሰንጋ ቆዳው ከተገፈፈ በኋላ በንጉሱ ትዕዛዝ መሰረት ግማሹ ለካህናት ተሰጠ፡፡ ሊቃውንቱ ግን “ያለ ዛሬ ጥቃት ደርሶብን አያውቅም፡፡ ሃይማኖታችን በንጉሳችን ተዋረደ…” በማለት ወደየመጡበት ጉዞ ሲጀምሩ፣ አሁንም አካለ ወልድ መስቀላቸውን ከበርኖሳቸው ውስጥ አወጡና ድምፃቸውን ከፍ አርገው “በስመአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሃዱ አምላክ በእግዚአብሔር ስም የተባረከ ይሁን!” ብለው ከበሬው ስጋ መብላት ጀመሩ፡፡ አከታትለውም “ለመሆኑ ከእስልምናም ሆነ ከክርስትና ሊቃውንት መሃል ይህን ጥያቄ የሚመልስልኝ አለ?” አሉና ጥያቄያቸውን ለሁሉም ወገኖች አቀረቡ፡፡ ጥያቄው “ክርስቲያን ያረደውን ሙስሊም አይብላ፣ ሙስሊም ያረደውን ክርስቲያኑ አይቅመስ የሚል ትዕዛዝ በመጽሐፍ ቅዱስ ወይም በቅዱስ ቁርዓን ተጽፎ እንደሆነ ንገሩኝ” የሚል ነው፡፡
ሙስሊምም ሆነ ክርስቲያኑ ራሱ በራሱ ላይ የፈጠረው የመራራቂያ ድንበር እንጅ በተለይ በስጋ ላይ የተደነገገ ህግ ባለመኖሩ፣ የሁለቱም ወገን ሊቃውንት በትዝብትና በባዶነት ስሜት መተያየት ጀመሩ፡፡
አፄ ቴዎድሮስ የሁለቱን ወገን ምሁራን መፈተን የፈለጉበት ነጥብም ይኸው ነበርና የመምህር አካለ ወልድን ሊቅነት በማድነቅ “ስሚኝ አንች ቆማጣ ቆመጥማጣ ሁሉ ሁልሽም በየፊናሽ ተምሬያለሁ እያልሽ በወገኔ ላይ ትደነፊያለሽ፤ ዕውቀት ማለት የአካልዬ ነው፤ ይማሯል እንደ አካልዬ ይዋጉዋል እንደ ገብርዬ!” በማለት የሊቁን አካለወልድን ዕውቀት ከጀግናው ፊታውራሪ ገብርዬ የጦር ሜዳ ውሎ ጋር በማነፃፀር አወድሰዋል፡፡ ፈተናውን ያለፉ መምህር አካለ ወልድ ብቻ ናቸዋ! በማንኛውም የዓለም ክፍል ሃይማኖት በምግብ ላይ የሚያሳድረው ልዩነት የለም፤ ግን እኛ አገር ላይ ሲደረግ ነበር፤ ይደረጋልም፡፡
ከመንዜው ሊቅ አባታቸው መምህር ሰርፀ ወልድና ከመርሃቤቴዋ እናታቸው ወ/ሮ ወለተ ኪሮስ በ1824 ገድመ ፋራ (ገዳመ ፋራ) ልዩ ስሟ ውቢት በተባለች አምባ የተወለዱት አካለ ወልድ ዜማ ለመማር፣ ከትውልድ ቀያቸው ርቀው የእናት አባታቸውን ግቢ ለቀው አልሄዱም፡፡ እስከ 12 አመታቸው ፆም ድጓ ድረስ ያለውን የዜማ ትምህርት እዚያው ተማሩ፡፡
ከዚያ በኋላ ግን ገና በልጅነት ዘመናቸው ዕውቀት የጠማቸው አዕምሮ ብሩሁ አካለወልድ ቅኔ ለመማር አኩፋዳቸውን አዝለው፣ ቅላቸውን አንጠልጥለው ወሎ ክ/ሀገር ወደምትገኘውና ዳባት ማርያም ወደ ተባለችው የቅኔ አምባ ተጓዙ፡፡ በዚያም አባጫልቱን ከሚባሉ የቅኔ ሊቅ ቅኔን ከእነ አገባቡ ተምረው፣ በቤተ ክህነት ትምህርት ውስጥ ኃይለኛነቱ (ከባድነቱ) የሚነገርለት የቅኔ መምህር ለመሆን በቁ፡፡
የአዳራሹን ምሰሶዎች ጨብጦ “ነፍሴ ከኢሎፍላዊያን ጋር ትውጣ” እንዳለው ሶምሶን ቅኔን ያህል ከባድ ዕውቀት ይዘው ነፍሳቸው ከትምህርት ጋር እንድትተሳሰር ገና ከጥዋቱ በመወሰናቸው፣ ለሌላ ትምህርት ወደ ጐንደር ተጓዙ፡፡ ጐንደር ከተማ ውስጥ ከሚገኘውና ዮሐንስ ወልደ ነጐድጓድ በተባለው ቦታም ቅኔ እያስተማሩ በአታ ከነበሩት ሊቃውንት የመጻሕፍተ ብሉያትን ትርጓሜ አጠኑ፡፡
የመፃሕፍት ትርጓሜ ትምህርት ይበልጥ እየሳባቸው ፍልስፍናው እየማረካቸው በመሄዱም እዚያው ጐንደር ከተማ ውስጥ በሚገኙት በአጣጣሚ ሚካኤልና እልፍኝ ጊዮርጊስ የመጻሕፈተ -ሃዲሳትንና ሊቃውንትን ትርጓሜ እስከ አንድምታው ተማሩና በሊቅነታቸው ላይ ሌላ የዕውቀት ካባ ደረቡ፡፡
ገና ከጉብልነት ዘመናቸው ጀምሮ “የቀለም ቀንድ” የሚል ቅጽል የተሰጣቸው አካለወልድ፤ በዚህ ሳይወሰኑ የመፃሕፍተ መነኮሳትን ትርጓሜ “መምህር ሃብቱ” ከተባሉ ዕውቅ ምሁር አጥንተው የአራቱ ጉባዔያት ወይም የሰማንያ አንዱ መፃሕፍት ቅዱሳት ማህደር በአሁኑ አጠራር “ስፔሻሊስት” መሆናቸውን አረጋገጡ፡፡
አካለ ወልድ በዕውቀት የዳበሩ በሊቃውንት ዘንድ የተከበሩ ቢሆኑም የሹመት አባዜ፣ ወይም እዩኝ፣ እዩኝ ባይነት ያልነበራቸው ይልቁንም የአባቶቻቸውን ፈለግ የተከተሉ ትሁት፣ ሰውን አክባሪና እግዚአብሔርን ፈሪ በመሆናቸው ሊቃውንቱ ትዕግስታቸውን ከኢዮብ፣ ቸርነታቸውንና ሃይማኖታቸውን ከአብርሃም፣ ሊቅነታቸውን ከጐጃሜው አራት አይና ጐሹ እያመሳሰሉ በቅኔ ያወድሷቸው ነበር፡፡
በዚህ የተነሳ ከካህናት ጋር እምብዛም ተዛምዶ ያልነበራቸው ዳግማዊ ቴዎድሮስ ሳይቀሩ ከሌሎች ሊቃውንት በተለይ ሲያደንቋቸው፣ ሲንከባከቡዋቸውና ሲያከብሯቸው ኖረዋል፡፡ ብዙውን ጊዜ አፄ ቴዎድሮስ ችሎት ሲቀመጡም ሆነ ሃይማኖታዊና ስጋዊ ጉዳዮች ላይ ለሚነሱ ክርክሮች መፍትሔ የሚሆኑ የፍትሃ ነገስት አንቀፆችን በመጥቀስ ያግዙ እንደነበር ታሪክ እማኝነቱን ይሰጥላቸዋል፡፡ ለዚህም አይደል አፄ ቴዎድሮስ ከጀግና ገብርዬን ፣ ከሊቅ መምህር አካለ ወልድን ማድነቅ ይቀናቸው የነበረው!
በወቅቱ ካህናት ሸፍጥና ቴዎድሮስ እንደ “ወደል ጋለሞታ” ሲቆጥሮአቸው በነበሩ መሳፍንት ሴራ ተከታይ እየራቃቸው፣ ጉልበት እያነሳቸው በሄዱበት ወቅት በጀኔራል ናፒር በተመራው ወራሪው የእንግሊዝ ጦር “እጄን አልሰጥም” በማለት ቴዎድሮስ የጀግና ሞታቸውን ከሞቱ በኋላ ሊቁ አካለ ወልድ ወደ ትውልድ አካባቢያቸው ሸዋ ሄዱ፡፡
የመምህር አካለ ወልድን ሸዋ መግባት የሰሙት ንጉስ ምኒልክ፤ ድሮ አፄ ቴዎድሮስ ግቢ በምርኮኛነት ለ10 አመታት ሲኖሩ የአካለ ወልድን ሊቅነት አሳምረው ያውቁ ነበርና በታላቅ አክብሮት ተቀበለው መጀመሪያ የቁንዲ ጊዮርጊስ ቀጥሎም የፍርኩታ ኪዳነ - ምህረት አስተዳዳሪ አድርገው ሾመዋቸዋል፡፡
በማስተማር ችሎታቸው የሚደነቁት አካለ ወልድ፤ ፍርኩታ ላይ ሳሉ በንጉስ ምኒሊክና በአፄ ዮሐንስ መካከል ፖለቲካዊ ችግር በመፈጠሩ ምኒልክን ግራ ገባቸው፡፡ ጦርነት እንዳይገጥሙ ሃይላቸው ከአፄ ዮሐንስ ጋር የማይመጣጠን በመሆኑና ይልቁንም ዮሐንስ እንግሊዞች በአስታጠቋቸው መስሪያ በመመካት፣ ያዙኝ ልቀቁኝ የሚሉበት ወቅት በመሆኑ ለምኒልክ የሚበጀው መንገድ ችግሩን በውይይት መፍታት ብቻ ነበር፡፡ ለአስታራቂነት ደግሞ በወቅቱ ከካህናት የበለጠ ከዮሐንስ ፊት የሚቀርብ ሃይል አልነበረም፡፡
ስለዚህ ምኒልክ በሸዋ ውስጥ አሉ የሚባሉትን ሊቃውንት ሰብስበው፣ ወደ ዮሐንስ አራተኛ ሲልኩ መምህር አካለ ወልድ ሰርፀወልድም የቡድኑ መሪ በመሆን ተመረጡና ወደ መቀሌ ገሰገሱ፡፡
ጦር ሊያማዝዝ ጥቂት ቀርቶት የነበረው የዮሐንስ 4ኛና የንጉስ ምኒሊክ ጠብ በዕርቅ እንደደመደም ካደረጉት ሊቃውንት መሃል አካለ ወልድ ቀዳሚው መሆናቸውን ዮሐንስ በመርዳታቸውም ከዚያን ጊዜ ጀምረው አይናቸውን በሊቁ ላይ ጣሉ፡፡ እናም መምህር አካለ ወልድ በወሎ ክፍለሀገር የክርስትና ዕምነትን እንዲያስፋፉ በአፄው ትልቅ ሃላፊነት ተጣለባቸው፡፡
መምህር አካለ ወልድ በወሎ ውስጥ በሚገኙ አውራጃዎች እየተዘዋወሩ፣ ህዝብ በማስተማር በርካታ ምዕመናንን በማፍራታቸው፣ ከፃድቁ አባ ኢየሱስ ሞአ ቀጥለው በክፍለሀገሩ ውስጥ ታላቅ ሃዋርያዊ ተልዕኮ የተወጡ የዘመኑ ፃድቅ እስከመባል በቅተዋል፡፡
ሊቁ አካለ ወልድ አስተማሪ፣ ዮሐንስ 4ኛ የአገር መሪ በነበሩበት ወቅት ወሎ ውስጥ አንድ ተአምር መታየቱም ከታሪካቸው ላይ በዝርዝር ተጽፏል፡፡ በአጭሩ እንዲህ ይነበባል:- “ከእምባቦ ጦርነት በኋላ አፄ ዮሐንስ፤ ንጉስ ተክለ ሃይማኖትና ንጉስ ምኒሊክ ለምክክር በተሰባሰቡበት በቦሩ ሜዳ ምስራቃዊ ክፍል በሚገኘው በአፄ ዮሐንስ ቤተ መንግስት ላይ ከፍተኛ ተአምር ታዬ፡፡
“መስከረም 10 ቀን 1876 ዓ.ም በዘመነ ሉቃስ ከሌሊቱ በአምስት ሰአት ንጉስ ምኒሊክ ከእነሰራዊታቸው ሶስት ገደል ከሚባለው ቦታ ላይ ሰፍረው ሳለ፣ በአፄ ዮሐንስ ቤተመንግስት ላይ ብርሃን ሰፍሮበት ታዬ፡፡ ከዚያ በዚያው የነበሩ ሁለቱ ንጉሶች፣ ሶስት ጳጳሳትና እጨጌ ቴዎፎሎስ ቤተመንግስቱ የተቃጠለ መስሏቸው እየተሯሯጡ ሄደው ቢመለከቱ፣ እሳት የሌለው ብርሃን ብቻ እንደ ታላቅ ቃጠሎ ሲንቦገቦግ አዩና በምስጢሩ ተደነቁ፡፡
“በዚህም አፄ ዮሐንስ ከእንግዲህ በኋላ ይህ ቤት የእግዚአብሔር አንድነትና ስስትነት መንገሪያ፣ የመስዋዕት መሰዊያ እንጅ የእኔ ሊሆን አይገባም ብለው ወዲያውኑ ቡራኬ እንዲደረግበት አዝዘው፣ ቦታው በጳጳሳቱና በእጨጌው ተባረከ፤ ያ ብርሃንም ሌሊቱ ሲያልፍ ከቀኑ ብርሃን ጋር ተቀላቀለ እንጅ ሌሊት ታይቶ አልጠፋም፡፡ ከዚያም አፄ ዮሐንስ ግምጃ ድንኳን አስተክለው፣ የስላሴን ታቦት አስገቡና የደብሩን ስም አበራ ስላሴ አሉት፡፡ ለዚያ ቅዱስ ስፍራ አስተማረና አስተዳዳሪ ይሆኑ ዘንድም የወሎን ህዝብ በማስተማር ላይ የሚገኙት መምህር አካለ ወልድ በንጉሱ ትዕዛዝ ተሾሙ”
እዚህ ላይ ልብ ልንለው የሚገባ ቁምነገር፣ ሊቁ ፊት በአፄ ቴዎድሮስ በኋላም በንጉስ ምኒሊክና በአፄ ዮሐንስ የነበራቸው ተቀባይነት የቱን ያህል የጐላ እንደነበር ነው፡፡
አበራ ስላሴን በማስተዳደር ላይ ሳሉ፣ ቤተክርስቲያኑን ንጉስ ሚካኤል አሳምረው መስራታቸውንም የቤተ-ክርስቲያኑ ታሪክ ይመሰክራል፡፡
መምህር አካለወልድ አበራ ስላሴ ላይ በቆዩባቸው ጊዜያት ታላቁ ተግባራቸው ማስተማር ነበርና ከ500 በላይ ደቀመዛሙርት ለማፍራት ችለዋል፡፡ “የቦሩ ሜዳዎቹ ባይሆን ኖሮ ያን ሁሉ ተማሪ ምን ይችለው ነበር?” ሲሉ በወቅቱ አድናቆታቸውን የሰጡ ተመልካቾች የሰጡት ቃል ዛሬም በዕማኝነት ይገኛል፡፡
ያን ሁሉ ወፈ ሰማያት ተማሪ ሲያስተምሩ ቀለብና ልብስ የሚችሉት ራሳቸው መምህር አካለ ወልድ ነበሩ አሉ፡፡ ይህ ማለት ደግሞ የመጀመሪያው የአዳሪ ት/ቤት በአገራችን የተመሰረተው በመምህር አካለ ወልድ ነው ማለት ነው፡፡ የሊቆች ሊቅ አካለ ወልድ ጉባዔ ዘርግተው ቦሩ ሜዳ በሚገኘው አበራ ስላሴ ደብር በርካታ ሊቃውንትን ለፍሬ ከማብቃታቸው በተጨማሪ ቁጥራቸው የት የለሌ የሆኑ የተለያዩ የግዕዝ መጻሕፍትን ብራና እየለመፁ፣ ብዕር እየቀረፁ ጽፈዋል አስጽፈዋል፡፡ የሰማንያ አሃዱ መፃሕፍት ትርጓሜ በአግባቡ እንዲጠና እንዲጠበቅና ይበልጥ እንዲራቀቅ የቅኔ ትምህርት እንዲመጥቅ ካደረጉት ከእነ ኤስድሮስ፣ ተዋነይ፣ ያሮድና አራት አይና ጐሹ ጋር የሚመደቡ የሊቆች ቀንድ መሆናቸውን የህይወት ታሪካቸውና የተለያዩ ሊቃውንት ስራዎች ይመሰክራሉ፡፡ ይህን ታላቅ አገልግሎታቸውን ለማዘከርም ደሴ ውስጥ አንድ የአንደኛና መለስተኛ 2ኛ ደረጃ ት/ቤት በስማቸው ተሰይሟል፡፡ በ1942 የተመሰረተው ይህ ት/ቤት፤ ታሪካቸውን በጽሑፍ ከመያዝ አልፎ ፎቶ ግራፋቸውን ከዘመድ አዝማድ አፈላልጐ በቅርስነት ማስቀመጡን ሳይ ለሊቁ የተሰጠውን ክብር እንድገነዘብ ረድቶኛል፡፡ “መልካም ስም ከማር ትጣፍጣለች” የሚባለው ለአካለ ወልድ ሰርፀ ወልድ አይነቱ የአገር ሃብት የተነገረ አይደል?! መልካም በዓል!

 

Published in ባህል

           ራሳቸውን ከመቻል አልፈው ሌሎችን ለመርዳት የሚችሉ ስኬታማ ሃብት ፈጣሪዎችን በማፈላለግ ልምድ ከማቃመስና በአርአያነታቸው ከማነቃቃት ይልቅ፤ የሚስኪኖችን ጓዳ ጎድጓዳ እያነፈነፈና እንባ እያራጨ በሬዲዮ ወይም በቲቪ ለአደባባይ የሚያቀርብ የ“ልመና ሾው”፣ እንደ ትልቅ ስራ መታየት አለበት? የሰው ልጅ ትልቅነትን በማንኳሰስ፣ ሚስኪንነትን ማምለክ ይመስለኛል። የመርካቶ ጉሊቶች (“ባህላዊ ገበያ”) በአዳዲስ ሕንፃዎች እንዳይጠፋ በመጠበቅ ለትውልድ ለማስተላለፍ የሚመኝ ወይም፣ ኮንዶምኒየም ቤት ለማግኘት እየናፈቀ የአራት ኪሎ ጭርንቁስ ሰፈር በኮንዶምኒዬም ይጥለቀለቃል ብሎ የሚሰጋ የ“ድህነት ጠበቃ” ሲናገርስ፣ እንዴት ከቁም ነገር ይቆጠራል? ወይስ “ወገኛ” እንበለው?
አዳሜ ልጆቹን በግል ትምህርት ቤት ለማስመዝገብ ሲሟሟት፣ “የግል ትምህርት ቤቶች የሬዲዮ ትምህርትን ስለማይጠቀሙ መዘጋት አለባቸው” ብሎ ባለስልጣናትን የሚያፋጥጥ የመንግስት ጋዜጠኛንም ተመልከቱ። “ጀግናው ተቆርቋሪ ጋዜጠኛ” ልንለው ነው? ይሄም “ወገኛ” ቢባል ሳይሻል አይቀርም። ይህም ብቻ አይደለም። መንግስት፣ በርካታ ፕሮጀክቶቹ መጓተታቸውን ሙሉ ለሙሉ ሳይሆን በከፊል በማመን “ፕሮጀክቶቹ በታቀደላቸው አቅጣጫ እየተከናወኑ ነው” የሚል አባባል ሲፈጥር፣ በሌላ በኩል ግን በድርቅናም ይሁን በሌላ ምክንያት “ፕሮጀክቶቹ በታቀደላቸው ጊዜ እየተገነቡ ነው” የሚለውን አባባል የሙጢኝ የያዘ የመንግስት ሚዲያ ታገኛላችሁ። “ፕሮጀክቶች ተጓተቱ” ብሎ የሚዘግብ የግል ጋዜጣ ካጋጠማቸው፣ “ጨለምተኛ” ብለው ሲያዋክቡትስ? ይሄ “ወገኛነት”ም የባሰ ሳይሆን አይቀርም። እውነትንና አእምሮን ካለማክበር ጋር አብሮ የሚመጣ ፕሮፓጋንዳን የማራገብ አመልና ነፃነትን የማፈን ዝንባሌ ይመስላል።
ምን ይሄ ብቻ! የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ከመንግስት ስራ ሳይጠብቁ የራሳቸውን ህይወት ለማሻሻል የቢዝነስ ፈጣሪ (አንተርፕረነር) እንዲሆኑ እየተመኘ፣ በሌላ በኩል 150ሺ ተማሪዎችን ሰብስቦ ከራሳቸው ሕይወት በፊት ለአገር ልማት የ“ሚጠበቅባቸውን” እንዲሰሩ የሚሰብክ፣ ... የቢዝነስ ሰዎችንም “ስግብግብ” እያለ የሚያሳድድ ፓርቲና መንግስት ምን ይባላል? በራስ ጥረት የራስን ሕይወት ማሻሻልና ሃብት ማፍራት...፣ ትክክለኛና ጠቃሚ፣ ተገቢና ቅዱስ ተግባር አይደለም እንዴ?...
አገራችን እነዚህን በመሳሰሉ የተምታቱና የተጣመሙ፣ ወገኛና ጭፍን ሃሳቦች የተሞላች ናት። ከሃሳብነት አልፈው የማይሻገሩና ኑሯችንን የማይነኩ ብናኞች ሊመስሉን ይችላሉ። በእርግጥም፣ የተምታቱና ወገኛ ሃሳቦች በዙሪያችን ቢንሰራፉም፣ ዞር ዞር ብለን በአይን የሚታዩና የሚዳሰሱ ተግባራትን ስንቃኝ፣ ተስፋ የሚሰጡ የሥራ ጥረቶችንና የእድገት ጅምሮችን እንመለከታለን። ስለዚህ፣ የተምታቱ ወገኛ ሃሳቦች ችግር አይፈጥሩም ማለት ነው? “አዎ ችግር አይፈጥሩም” የምንል ከሆነ፣ ከአገሪቱ የቅርብ ጊዜ ታሪኮች ላይ ዋናውንና ትልቁን ትምህርት ስተነዋል ማለት ይቻላል። እንዴት?
እስቲ በቅድሚያ፣ አንዳንዶቹን ቀረብ ብለን እንመልከታቸው። በአዲስ አበባ የሬዲዮ ትምህርት የማይሰጡ የግል ትምህርት ቤቶች ለምን አልተዘጉም ብሎ ባለስልጣናትን የሚያፋጥጥ “ጀግና” ጋዜጠኛ ማን ነው? የኢቲቪ ጋዜጠኛ ነዋ! እና ደግሞ “ብዙዎቹ የግል ትምህርት ቤቶች፣ ለማስተማሪያነት ታስቦ የተገነባ ህንፃ እንደሌላቸው መረጃዎች ያመለክታሉ። እነዚህን ለመዝጋት እርምጃ መውሰድ ነበረባችሁ፤ እናንተ ግን ማስታመም ታበዛላችሁ፤ ይሄ ሃላፊነትን አለመወጣት ነው” ... በማለት ባለስልጣናቱን ወጥሮ ይዟቸዋል - “መረጃዎችን” እየጠቀሰ። በእርግጥም፣ ስልጣኔን የምንፈልግ ከሆነ የመጀመሪያው ቁምነገር፣ አእምሮን መጠቀም፣ ለእውነት ክብር መስጠትና የማሰብ ነፃነትን ማስፋፋት ነው። እናም፣ ሃሳቦቻችንን በሙሉ በመረጃ ወይም በእውነታ ላይ የተመሰረቱ መሆን ስላለባቸው፤ ጋዜጠኛው መረጃዎችን መጥቀሱ ያስመሰግናል።
አዎ፤ ብዙ የግል ትምህርት ቤቶች፣ በሬዲዮ የሚሰራጨውን ትምህርት አይጠቀሙበትም። ለትምህርት ታስቦ የተሰራ ህንፃም የላቸውም። ነገር ግን ሌሎች መረጃዎችም አሉ። አንደኛ በቅርቡ በሰቆጣ የሻዳይ በዓል ሲከበር እንደተጠቀሰው፣ በአንድ ዞን ውስጥ ከሚገኙ የመንግስት የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች መካከል በርካታዎቹ፣ የዛፍ ጥላን እንደመማሪያ ክፍል ይጠቀማሉ። ከ500 በላይ የዛፍ ጥላ ክፍሎች! ከ10ሺ ተማሪዎች በላይ መሆኑ ነው። ይህም ብቻ አይደለም። በአዲስ አበባና በየክልሉ፣ የመማሪያ መጽሐፍ ሳያገኙ አመቱ የሚጋመስባቸው የመንግስት ትምህርት ቤቶችን ስናይ አልነበረም እንዴ? ሌሎች መረጃዎችም አሉ። ለአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች በሬድዮ፣ ለሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ደግሞ በፕላዝማ ቲቪ የሚቀርቡት ትምህርቶች፣ ይህ ነው የሚባል ጥቅም እንዳላስገኙ በርካታ ጥናቶች አረጋግጠዋል - የትምህርት ሚኒስቴር ጥናት ጭምር።
በዚያ ላይ ለመንግስት ትምህርት ቤቶች የተሰራጩት ሬዲዮኖችና የፕላዝማ ቴሌቪዢኖች በአብዛኛው አገልግሎት አይሰጡም። ይህም መረጃ ነው። በአዲስ አበባ የመንግስት ትምህርት ቤቶች፣ ግማሾቹ የፕላዝማ ቲቪዎች በብልሽት ወይም በአጠቃቀም ችግር አገልግሎት አለመስጠታቸውስ መረጃ አይደለም? አንዳንዶቹን የአጠቃቀም ችግሮች ማስተካከል ይቻል ይሆናል። አብዛኞቹን ብልሽቶች መጠገን ግን አይቻልም። የመለዋወጫ እቃዎች ዋጋ በጣም ውድ ስለሆነ፣ ከምርት አለም የወጡና ጊዜ ያለፈባቸው ስለሆኑ መለዋወጫ እቃ አይገኝላቸውም፤ ከተገኘም የጥገና ወጪው ከቴሌቪዢኑ ዋጋ የሚበልጥ ይሆናል።
ኧረ ለመሆኑ፣ የተሻለ የትምህርት ውጤት የሚመዘገበው የት ነው? በግል ትምህርት ቤቶች! ወላጆች ልጆቻቸውን የት ለማስተማር ይሟሟታሉ - በግል ትምህርት ቤት - ለዚያውም በሺ ብር የሚቆጠር ገንዘብ በየሴሚስተሩ እየከፈሉ። ታዲያ ይሄ ሁሉ መረጃ በግላጭ እየታወቀ፣ “የግል ትምህርት ቤቶች የሬዲዮ ትምህርት አይጠቀሙም” በሚል እንዲከረቸሙ ባለስልጣናትን ማፋጠጥ ምን ይባላል? “ጋዜጠኛ የመንግስት ባለስልጣናትን ሊያፋጥጥ ይችላል” ሲባል የሰማ ሰው፤ “እኔም ወግ ይድረሰኝ” ሊል ይችላል። ነገርዬው፣ “ወገኛነት” አይደለም የምንል ከሆነ ግን፣ ከወገኛነት የባሰ “ክፋት” ይሆናል።
“የመርካቶ ጉሊቶችና የቆርቆሮ ሱቆች እየፈረሱ ህንፃዎች እየተገነቡ ነው” ብሎ የሚደሰት ሳይሆን “ባህል ጠፋ” እያለ የሚጨነቅ ሰውስ ምንድነው ችግሩ? “ሲሉ ሰምታ...” እንደሚባለው ይመስለኛል። “አካባቢ ጥበቃ”፣ “ባህል ጥበቃ” ሲባል የሰማ ሰው፣ “የጉሊቶች ጥበቃ” ብሎ ሊናገር ይችላል። ከወገኛነት አልፎ፤ የምር ከሕንፃዎች ይልቅ አቧራና ጭቃ የሚፈራረቁበት የጉልት ተራ የሚመርጥ ከሆነ ግን፣ ነገርዬው ከወገኛነትም የባሰ ነው። “የድህነት ጠበቃ” ቢባል ይሻላል - የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ የአካባቢ ጥበቃ ቡድኖችን ለመተቸት የተጠቀሙበት አባባል ነው።
በአዲስ አበባ እየተዘረጋ ስላለው የኤሌክትሪክ ባቡር መስመር፣ በከተማዋ መስተዳድር የቲቪ ፕሮግራም የተላለፈ ሌላ “ወገኛ ዜና” ልጨምርላችሁ። እንደምታውቁት፣ የታክሲ ስምሪት ቁጥጥር የተጀመረ ሰሞን፣ “ይሄ ነገር የትራንስፖርት እጥረትን ያባብሳል” ብለው ምክር የለገሱ ሰዎች ሰሚ አላገኙም። እንዲያውም፣ “የታክሲ ስምሪት ቁጥጥሩ የትራንስፖርት እጥረትን ያቃልላል” በማለት እልፍ ጊዜ “ዜና” ሰርተዋል - የመንግስት ሚዲያ ተቋማት። ዛሬ ግን ቅኝቱ ተቀይሯል። የአዲስ አበባ ቲቪ ሰሞኑን እንደዘገበው፣ የትራንስፖርት እጥረቱ ተባብሷል - 11 ሰዓት ላይ ከስራ የወጡ ሰዎች፣ ታክሲ የሚያገኙት ማታ 1 ሰዓት እየሆነ ብዙ ሰው መቸገሩን ዘገባው ይገልፃል። የዚህ ሁሉ መጨረሻ ምን መሰላችሁ? “አይዟችሁ - የባቡር መስመሩ እየደረሰላችሁ ነው” የሚል መልእክት ለማስተላለፍ ነው። ቀልጣፋ የትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጥ የባቡር መስመር ከተገነባ ማን ይጠላል? ባቡሮቹ በኤሌክትሪክ የሚሰሩ መሆናቸው ትልቅ ጥቅም እንዳለው አዲስ ቲቪ ሲያስረዳ፣ “የአካባቢ ብክለትን ይከላከላል” በማለት አብስሯል። ወገኛ ይሉሃል ይሄ ነው። ምናለ፣ “የነዳጅ ወጪን ያስቀራል” ብሎ ቢናገር?
እንዲሁ ስታስቡት፣ እዚህ አገር መኪና በዝቶ ነው፣ በመኪና ጭስ አየር እየተበከለ የተቸገርነው? አንድ ቢሊዮን መኪኖች ባሉበት አለም፣ የኢትዮጵያ ድርሻ፣ “አንድ በመቶ” እንኳ አይሆንም። ኧረ “ከሺ መኪና አንድ” ለመድረስ አልቻለም። ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉት ሁሉም የመኪና አይነቶች 350ሺ ገደማ ናቸው። እንዲያው፣ ብንጨነቅ ብንጨነቅ፣ በመኪና ጭስ እንጨነቃለን? መኪና በበዛና፣ አዲስ አበባ እንደ ኒውዮርክና ለንደን፣ እንደ ቤጂንግና ቶኪዮ በሆነች። ይልቅ ሊያስጨንቀን የሚገባው ብክለት፣ በየደጃፋችን ያለው የቆሻሻ ቱቦ ወይም በየከተማው እንደጥላሸት የሚጠቁረው ወንዝ ነው። ለነገሩ ከዚያ በፊት የምንጠጣው ውሃ ንፁህ እንዲሆንና ተቋርጦ እንዳይሰነብት ማድረግ ይቀድማል። በገጠር ደግሞ፣ በእንጨትና በኩበት ጭስ መታፈንን፣ የደፈረሰ የመጠጥ ውሃና ከከብት ጋር ተዳብሎ ማደርን ለማሻሻል ብንመኝ አይሻልም? ወይስ ባህል ስለሆነ፣ ጠብቀን ልናቆየው ይገባል?
የአረንጓዴ ልማት በተሰኘው ሰነድ ደግሞ ምን አየሁ መሰላችሁ? የነዳጅ መኪኖችን በኤሌክትሪክ መኪኖች የመተካት እቅድ! አውሮፓ ውስጥ ሲነገር የሰሙት መሆን አለበት። የወገኛ ነገር! አሊያማ፣ በተራሮች የምትታወቀው ኢትዮጵያ ውስጥ፣ በየዳገቱ አቅም አንሷቸው የሚቆሙ የኤሌክትሪክ መኪኖች ምን ይሰራሉ? ለዚያውም ከሌላው መኪና በሶስትና በአራት እጥፍ ዋጋ ነው ተገዝተው የሚመጡት። የኤሌክትሪክ መኪኖች ነዳጅ ስለማይጠቀሙ ወጪ የሚቆጥቡ እንዳይመስላችሁ። የባትሪያቸው ወጪ ከፍተኛ ነው። የሞባይል ባትሪ መቀየር እንኳ፣ ቀላል አይደለም።
ወገኛ ሃሳቦች፣ እንዲሁ ለወሬ ያህል የሚነገሩ ቢሆኑ እንኳ ጥሩ አይደለም። ከእውነታ ጋር ያጣሉናል። ግን፣ የወገኛ ሃሳቦች ጉዳት ይህ ብቻ አይደለም። በወሬ ብቻ አይቀሩም። ግልገል ጊቤ 3 የተሰኘው ግዙፍ የኤሌክትሪክ ማመንጫ ግድብ ግንባታ የተጓተተው ለምን እንደሆነ አታውቁም? “ሁሉንም አካባቢ፣ ተራሮችንና ወንዞችንም ጭምር እንደድሮአቸው ሳንነካቸው ልንጠብቃቸው ይገባል። በጠረፎች አካባቢ በጥንታዊ አኗኗር ውስጥ የሚገኙ ጎሳዎችም አኗኗራቸው ሳይቀየር መቀጠል አለበት” የሚሉ የአካባቢ ጥበቃ ቡድኖች፣ ግድቡን ስለተቃወሙ ነው። ቢቃወሙ የት ይደርሳሉ? በአካባቢ ጥበቃ ቡድኖች ዘመቻ ምክንያት፣ የአውሮፓ ህብረት ለግድቡ ግንባታ ሊሰጠው የነበረውን ብድር ሰርዟል። ከዚያ በኋላ ደግሞ፣ ብድር ለመስጠት ተቃርቦ የነበረው የአፍሪካ ልማት ባንክ፣ ጫፍ ከደረሰ በኋላ ብድር ሳይሰጥ ቀርቷል። ይሄውና የግድቡ ግንባታ ለአመታት ይንፏቀቃል - እስካሁን 3 ዓመት ገደማ የተጓተተው ግንባታ፣ ቢያንስ ተጨማሪ ሁለት አመታት ያስፈልጉታል።
በአዳማ ናዝሬትና መቀሌ፣ በነፋስ የሚሰሩ የሃይል ማመንጫ ተርባይኖችን ለመትከል ስንት ወጪ እንደወጣበት ታውቃላችሁ? ሁለት መቶ ሜጋ ዋት ገደማ ለማመንጨት ከ550 ሚሊዮን ዶላር በላይ ገደማ። ወንዝን በመገደብ ተመሳሳይ አቅም ያለው የኤሌክትሪክ ማመንጫ ለመገንባት በአማካይ 200 ሚሊዮን ዶላር፣ በዛ ቢባል ደግሞ 250 ሚሊዮን ዶላር ነው። በሌላ አነጋገር፣ 300 ሚሊዮን ዶላር በከንቱ ባክኗል (6 ቢሊዮን ብር መሆኑ ነው)። ለምን? የአካባቢ ጥበቃ ቡድኖች የግድብ ግንባታ ስለሚቃወሙ፣ እነሱን ለማባበል የነፋስ ተርባይኖችን መጠቀም ግዴታ እየሆነ መጥቷላ። 6 ቢሊዮን ብር ቀልጦ ሲቀር ግን በኢትዮጵያ አቅም ቀላል አይደለም። እስካሁን በአመት ለነዋሪዎች የሚተላለፉ የኮንዶምኒየም ቤቶች ወደ 15ሺ ገደማ አይደሉ? የእነዚህን እጥፍ ለመገንባት የሚያስችል ገንዘብ ነው፣ በነፋስ ተርባይኖች ሳቢያ ነፋስ የበላው።
በአጠቃላይ፣ ወገኛ ሃሳቦች ከእውነት ጋር በማጣላት በቀጥታ ወይም በተዘዋዋሪ፣ ኑሮና ሕይወትን ሊያበላሹ ስለሚችሉ፣ እውነታ ላይ በተመሰረተ ትክክለኛና ቀና ሃሳብ ልናስተካክላቸው ይገባል - ብቅ ብቅ የሚሉ የስልጣኔና የብልፅግና ፍንጮች ተመልሰው እንዳይጠፉና እንዲያድጉ የምንፈልግ ከሆነ ማለቴ ነው።
አዎ፤ በየቦታው የግንባታ ሩጫና የቢዝነስ ሙከራዎች፣ በየአካባቢያችን የብልፅግና ጥረቶችና ጅምሮች፣ ከታች እስከ ዩኒቨርስቲ የትምህርት ተቋማትና የተማሪዎች ብዛት፣ ቴክኖሎጂዎችን የመጠቀምና መረጃ የመለዋወጥ ጉጉት... እንዲሁም ተመሳሳይ የስልጣኔ ፍንጮችንና የብልፅግና ጭላንጭሎችን ማየት ራሱ መልካም ነው። ነገር ግን፣ እነዚህ ፍንጮች በታሪክ ታይተው የማይታወቁ አዲስ አጋጣሚዎች እንዳልሆኑና ሊጠፉ እንደሚችሉ ከታሪክ መማር ይኖርብናል።
በየጊዜውና በየዘመኑ፣ የስልጣኔ ጭላንጭሎች ታይተዋል። ከሚኒልክ ዘመን አንስቶ ተፈሪ መኮንን ስልጣን ይዘው የጣሊያንን ወረራ እስከተፈፀመበት ድረስ ያለውን ጊዜ በምሳሌነት መጥቀስ ይቻላል። የሳይንስና የነፃነት፣ የብልፅግናና የነፃ ገበያ፣ የሰብዕና ክብርና የህግ የበላይነት ሃሳቦችን ያነገቡ እንደ ገብረሕይወት ባይከዳኝ በመሳሰሉ የስልጣኔ ምሁራን የተለኮሰ የብርሃን ችቦ በድምቀት የፈነጠቀበት ዘመን ነው፤ በጣሊያን ወረራ ተስተጓጎለ እንጂ። በ1950ዎቹ ላይ ደግሞ፣ ዘመናዊ ትምህርት ለሴቶችም ጭምር በፍጥነት መስፋፋት የጀመረበት፣ የቢዝነስ ግንባታዎችና የኢኮኖሚ እድገት ቡቃያዎች የተፈጠሩበት፣ ሕገመንግስት ተሻሽሎ የምርጫ ስርዓትን ለመቀማመስ የተሞከረበት፣ በሁሉም የኪነጥበብ መስኮች ድንቅ ስራዎች ብቅ ብቅ ለማለት የበቁበት የስልጣኔ ፍንጭ ታይቷል። ነገር ግን፣ አልዘለቀም። እነ ገብረሕይወት በትክክለኛ አስተሳሰብ የለኮሱት የስልጣኔ ችቦ እየከሰመ ስለነበረ፣ በትምህርት፣ በኢኮኖሚ፣ በፖለቲካና በኪነጥበብ የታየው የስልጣኔ ጅምርና ፍንጭም፣ ቀስ በቀስ እየደከመ የዛሬ አርባ አመት ከሰመ። እንዴት?
በወረራ ሳይሆን፣ በተሳሳተና በተምታታ አስተሳሰብ ሳቢያ ነው፣ የ1950ዎቹ የስልጣኔ ጅምር የከሰመው። በእነማን አማካኝነት? ስለ ሳይንስ እያወሩ፣ የግለሰብ አእምሮንና ነፃነትን የሚያንቋሽሹ፣ ስለ ብልፅግና እያወሩ ሃብት ማፍራትን እንደ ትልቅ ወንጀል የሚቆጥሩና ንብረት ለመውረስ የሚቋምጡ፣ ራስን በማሳነስና በማዋረድ ለአንድ ሶሻሊስት ፓርቲ ሙሉ ለሙሉ ተገዢ መሆንን የሚያወድሱ ኮሙኒስት ምሁራን የተበራከቱበት ዘመን ነዋ። ምን ያህል እንደተበራከቱ ለመገመት ከፈለጋችሁ፤ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ዝነኛ ኮሙኒስት የነበረው ዋለልኝ መኮንን፤ በ1962 ዓ.ም ባሰራጨው ፅሁፍ ውስጥ፣ የኮሙኒዝም አስተሳሰብ በዩኒቨርስቲ ውስጥ ሙሉ ለሙሉ እንደሰፈነ መግለፁን መጥቀስ ይቻላል። በዘመናችን አነጋገር አብዛኛው ምሁር በመሰረታዊ የፖለቲካ ጥያቄዎች ላይ ተመሳሳይ አስተሳሰብ በመያዝ፣ “አገራዊ መግባባት” ወይም “ብሔራዊ እርቅ” የተፈጠረበት ዘመን ነው ማለት ይቻላል። ምሁራኑ “የተግባቡት”፣ የተሳሳተና አጥፊ የኮሙኒዝም አስተሳሰብን በጋራ በመያዝ መሆኑ ነው መጥፎነቱ።በዚያን ዘመን የነበረው የሃሳብ ልዩነት፣ በካፒታሊዝም ደጋፊዎችንና በኮሙኒዝም ደጋፊዎች መካከል ሳይሆን፣ በኮሙኒስቶች መካከል እንደሆነ ዋለልኝ በኩራት ይገልፃል። “እኛ ሃቀኛ ኮሙኒስት፤ እናንተ አስመሳይ ኮሙኒስት” እያሉ እርስ በርስ በሚናቆሩ ቡድኖች መካከል ካልሆነ በቀር ሌላ የሃሳብ ልዩነት እምብዛም አልነበረም። ታዲያ፣ በዩኒቨርስቲ የሰፈነው የጥፋት አስተሳሰብ፣ አገሪቱን ለማዳረስና የመንግስት ስልጣን ላይ ለመውጣት ጊዜ አልፈጀበትም። ልክ የዛሬ አርባ አመት፣ መስከረም 1967 ዓ.ም መሆኑ ነው። ከዚያ በኋላ ያለው ታሪክ በስፋት ይታወቃል። ለማሽቃበጥና ለማጨብጨብ ካልሆነ በቀር፣ ሃሳብን ለመግለፅ መተንፈስ የማይሞከርበት ዘመን! “ያሰበ፣ ያሳሰበ...” ሁሉ፣ በገፍ ለእስር፣ ለስቃይና ለግድያ የሚዳርግ አስተሳሰብ! ሃብት ማፍራት እንደወንጀል ተቆጥሮ፣ ንብረት መውረስና መዝረፍ የአገር መተዳደሪያ ህግ ሆኖ አረፈው። በዚህም ሰበብ፣ ድህነት ተባብሶ፣ ረሃብና እልቂት የአገር መለያ ለመሆን ደረሱ። አንዱ ባለስልጣን ወይም ኮሎኔል፣ አንዱ የቀበሌ ሊቀመንበር ወይም ታጣቂ በማንኛውም ሰዓት መጥቶ ሊያስረው፣ ሊገርፈው፣ ሊገድለው፣ ቤቱን ነጥቆ ቤተሰቡን ሊደፍራቸው እንደሚችል የሚያውቅ ሰው፣ በአቅመ ቢስነት አንገቱን ደፍቶ የሚገፋው ደንባራ ኑሮ ምኑ ሕይወት ይባላል? የሰው ክብር ከእንሰሳ በታች የተዋረደበት ዘመን! ምን ለማለት ፈልጌ ነው? ሃሳቦቻችንን በስልጣኔ አቅጣጫ ካላስተካከልን በቀር፤ በአይን የሚታዩና የሚዳሰሱ የስልጣኔ ጭላንጭሎች ይበልጥ እየፈኩና እየበዙ ከመሄድ ይልቅ፣ ለመዳፋን አፈትልከው ወይም ብን ብለው ሊጠፉ ስለሚችሉ፣ ከተምታቱና ከተጣመሙ ወገኛ ሃሳቦች እንራቅ ለማለት ፈልጌ ነው።

 

በኢቲቪ ዶክመንታሪ ላይ ለተሰነዘረ አስተያየት ምላሽ

     ባለፈው ሳምንት ቅዳሜ የወጣው አዲስ አድማስ፣ በ“ነፃ አስተያየት” አምዱ፣ “ያልተገሩ ብዕሮችን ለመግራት” በሚል ርዕስ መድሃኔ ግደይ የተባሉ የአምቦ ዩኒቨርስቲ የጋዜጠኝነትና ኮሙኒኬሽን መምህር ከአንድ ወር በፊት ኢሬቴድ (ኢብኮ) በግል ፕሬሱ ላይ ለሚያዘጋጀው ዶክመንታሪ ለሰነዘሩት አስተያየት በማስተባበል ይሁን በአድርባይነት የሰጡትን ሃሳብ አስተናግዷል፡፡ እኔም ከሰነዘሩት ሃሳብ ተነስቼ፣ በባለሙያ ስም የተሸፈነውን አድርባይ አቋማቸውን እንዲያስተካክሉና አንባቢ ሚዛናዊ ፍርዱን እንዲሰጥ በማሰብ ምላሽ ልሰጥ ወደድኩ፡፡ 

መምህሩ በጋዜጣው ላይ በሰጡት “የእምነት ክህደት ቃል” ይሁን “ኑዛዜ” ልጀምር፡፡ “ብዙ ነገር የምትቆራርጡ ከሆነ ግን…”፣ “በግምት ለአርባ ደቂቃ የሰጠሁት ሃሳብ ተቆራርጦ ተጣለ”፣ “ያልተገሩ ብዕሮች የመግራት ስልጣን ለኢቲቪ ማን ሰጠው?” ይሉና ተመልሰው ኢቲቪ ፍሬም አውጥቶ መስራቱ ከሙያ አንጻር ትክክል ነው በማለት፣ ሁለት ቦታ ላይ የሚረግጥ ውሉ ያልለየ ሃሳብ ያራምዳሉ፡፡
የሚዛናዊ ጋዜጠኝነት አዘጋገብ መርህን በተመለከተ የአገራችን የግል ሚዲያዎች አብዛኞቹ (ሁሉም አይደሉም) ሚዛናዊ አለመሆናቸውን እንዲሁም የጋዜጠኝነት አዘጋገብ መርህ የሆነው ገለልተኝነትን (Objectivity) በተመለከተ የግል ሚዲያው ከፍተኛ ችግር እንዳለበት መናገራቸውን ጠቁመው፣ በኢቲቪ መቅረቡ ግን እንዳንገበገባቸው ይገልጻሉ፡፡ የሚዲያና ዲሞክራሲ ግንኙነት በተመለከተም የሚዲያው ተቋም አራተኛው የመንግስት ክንፍ ተደርጐ እንደሚወሰድ፣ በመንግስትም ሆነ በሌሎች አካላት የሚፈፀሙ የአሰራርና የአስተዳደር ችግሮችን ማጋለጥ እንዳለበት የሰጡት ሃሳብ በአርትኦት መቆረጡ (ከሙያ አንፃር ሳይሆን መንግስትን በነገር ሸንቆጥ ሳያደርጉ በመቅረታቸው) እንዳስቆጫቸውም ሳይሸሽጉ ጽፈዋል፡፡

በነገራችን ላይ መንግስት ከአስር አመት በፊት ባዘጋጀው ፖሊሲ ላይም ጉድለቶችንና ችግሮችን እየነቀሱ ችግሩን ለማባባስና ለማቀጣጠል ሳይሆን የመፍትሔ አቅጣጫ ለመጠቆም የጋዜጠኝነት ምርመራ ስራ መስራት የሚቻልና የሚገባ እንደሆነ ተገልጽዋል፡፡ ክፋቱ ግን አንዳንድ የአገራችን ምሁራን የአሜሪካንን “ፈርስት አሜንድመንት” በቃላቸው ሸምድደው ለመስበክ የሚጥሩትን ያህል ለአገራቸው ፖሊሲዎችና ህጐች ደንታቢስ መሆናቸው ነው፡፡ መምህሩ ግለኝነትን (ፕራይቬሲ) በተመለከተ የሰጡት አስተያየት ተቆርጦ እንደወጣባቸውም ስሞታ አቅርበዋል፡፡ አንድ በከፍተኛ ተቋም ውስጥ በመምህርነት የሚያገለግልና ሙያውን ቢያንስ በንድፈ-ሃሳብ ደረጃ ጠንቅቆ ያውቃል የተባለ ሰው ቀርቶ ማንም ተራ አንባቢ በቀላሉ እንደሚረዳው፣ የትኛውም ሚዲያ በተለያዩ ምክንያቶች (ለምሳሌ የቦታና ጊዜ እጥረት) የቀረበለትን አስተያየት ሁሉ እንደማያቀርብ ይታወቃል፡፡ አርትኦት የሚባል የጋዜጠኝነት የዕለት ተዕለት ስራ እንዳለ መምህሩ ይዘነጉታል ብዬ አላስብም፡፡ ቃለ መጠይቅ እንዳለ ላይተላለፍ ይችላል፡፡ የትኛው መልዕክት መተላለፍ እንዳለበትና እንደሌለበት የሚወስነው ዋና አዘጋጁ ወይም ኤዲተሩ እንደሆነ ከአንድ የጋዜጠኝነትና ኮሙኒኬሽን ምሁር የተሰወረ ነው ብዬ አላምንም፡፡
ኢቲቪ ያቀረበውን ዘገባ ከመርህ አኳያ አንስተው መሟገት ሲገባዎ፣ ከዶክመንተሪ ፊልሙ ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት የሌለውን የፖለቲካ ገለልተኝነት እሳቤ ያለቦታው ደንቅረውታል፡፡ እኔ እንዳየሁት፣ የዶክመንተሪ ፊልሙ አዘጋጆች፣ የገለልተኝነት መርህን ለመጠበቅ ረዥም ርቀት ተጉዘው እውነታውን ለማስጨበጥ ጥረት አድርገዋል፡፡ በፅንፈኛና አክራሪ ሚዲያው ጉዳት የደረሰባቸውን የህብረተሰብ ክፍሎች አስተያየት በገለልተኝነት አቅርበዋል፡፡ የተለያዩ ምሁራን በጉዳዩ ላይ ያላቸውን አስተያየትም ሚዛኑን በጠበቀ መልኩ ለማስተናገድ ጥረዋል፡፡ መንግስትም እንደ አንድ የጉዳዩ ባለቤት፣በተወካዮቹ አማካኝነት ሃሳቡ ተካትቷል፡፡ መምህር ሆይ፤ የቱ ጋ ነው ታዲያ የገለልተኝነት መርህ የተጣሰው? እኔ የተናገርኩት በሙሉ ካልቀረበ ብሎ ያዙኝ ልቀቁኝ ማለት ለአገራችን የግልም ሆነ የህዝብ ሚዲያ መጎልበት የሚያበረክተው ፋይዳ ያለ አይመስለኝም፡፡ የግለሰቦችን ሰብዕና በማይነካ መልኩ የግል ሚዲያው ምርመራ ማድረግ አለበት የሚል መርህ ቢያስቀምጡም በአንዳንድ ፅንፈኛ የግል ሚዲያዎች የተሳሳተና መርህ የሳተ ዘገባ ምክንያት ሰብዕናቸው ተጐድቶ ቤት ለመዋል ስለተገደዱትና በዶክመንተሪ ፊልሙ ስለቀረቡት የግል ተበዳይ (ግለሰብ) አንስተው የፅንፈኛውን ሚዲያ አካሄድ ለመኮነን አልደፈሩም፡፡ ይህም ሌላው የአድርባይነትዎ መገለጫ ነው፡፡ ይልቁንም ኢቲቪን ለመወንጀልና እርስዎ እንደ ጦር የፈሯቸውን ሦስተኛ ወገኖች ለማስደሰት ኑዛዜ አቀረቡ፡፡ እርስዎ ለማስተላለፍ የፈለጉት “የግል ሚዲያው ምንም እንከን የሌለው ቅዱስ ነው” የሚል ሃሳብ እንደሆነ የጻፉትን ያነበበ ሰው ሁሉ በቀላሉ ይረዳዋል፡፡ ይህም ገና ከጅምሩ የተከበረውን የመምህርነት ሙያ ለድርድር እንዳቀረቡትና የአድርባይነት ሰለባ እንደሆኑ የሚያሳይ ነው፡፡
ለእውነት መቆምና ስለእውነት መመስከር እርስዎን ከመሠለ ምሁር የሚጠበቅ ቢሆንም እንደአለመታደል ሆኖ ግን ያንን ማሳየት አልቻሉም፡፡ ሁሉንም ነገር ኢቲቪ ላይ ደፍድፈውና ለጉዳዩ ፖለቲካዊ ትርጉም ሰጥተው ከመከራከርዎ በፊት ግራና ቀኙን ከሙያዎ አኳያ መርምረው፣ ሚዛናዊ በሆነ መንገድ ቢያሳዩን ተገቢ ነበር፡፡ ሆኖም የምሁር አድርባይነትዎ እውነታውን በትክክለኛው መነፅር ለማየት አላስቻልዎትም፡፡

 

 

ለሁለት አስርት ዓመታት በተቃውሞ የፖለቲካ ጎራ ውስጥ ንቁ ተሳትፎ ሲያደርጉ የቆዩት ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ፤ በተለያዩ ጊዜያት የተቃዋሚ ፓርቲዎችን እየመሰረቱ መርተዋል፡፡ ከስድስት ዓመታት ወዲህ መድረክን የተቀላቀሉት ፕሮፌሰሩ፤ ላለፉት ሁለት ዓመታት ከፖለቲካው ንፍቀ ክበብ ጠፍተው ከርመዋል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ኤልሳቤጥ እቁባይ፤ ፕሮፌሰሩ የት ጠፍተው እንደከረሙ፣ ስለተቃዋሚ ፓርቲዎችና ኢህአዴግ ወቅታዊ እንቅስቃሴ፣ ስለመጪው ምርጫና ሌሎች ተያያዥ ፖለቲካዊ ጉዳዮችን በተመለከተ አነጋግራቸዋለች፡፡ የፕሮፌሰር በየነ፤ የት እንደጠፉ በመመለስ ይጀምራሉ፡-

ትንሹንም ትልቁንም ማሰር ለምን እንዳስፈለገ እኔ አላውቅም
አገራችሁ የጋዜጠኞች እስር ቤት ነው መባል አያስከብርም
መንግስትን እንወያይ ብለን ከጠየቅን ዓመት ሆኖናል

 ሁለት አመት የተባለው በዝቷል፡፡ ለአንድ ዓመት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ “ሳባቲካል ሊቭ” (ለጥናትና ምርምር እረፍት መውሰድ ማለት ነው) ወስጄ አሜሪካን አገር ዩኒቨርሲቲ ውስጥ ሳስተምርና ምርምር ሳደርግ ቆይቼ ነው የተመለስኩት፡፡ ያ ማለት ግን ከፖለቲካው እንቅስቃሴ ውጪ ሆኛለሁ ማለት አይደለም፡፡ ውጪም ሆኜ በዘመናዊ ቴክኖሎጂ እገናኝ ነበር፡፡ ምናልባት ደጋግሜ አገር ውስጥ በሚታተሙ የግል ጋዜጦች ላይ አለመታየቴ ይሆናል እንጂ የያዝነውን አጀንዳ ለማራመድ የጊዜው ሁኔታ በሚፈቅደው ደረጃ እየተንቀሳቀስኩ ነኝ፡፡ 

በእርግጥ እዩኝ እዩኝ የሚል አካሄድ የለኝም፡፡ ድሮውንም በተቃውሞ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ውስጥ የገባሁት በድንገት ወይም በግርግር አልነበረም፡፡ ኢህአዴግን ስለምጠላም አይደለም፡፡ የመርህ ልዩነት ስላለኝ ነው፡፡ እኔ በሌለሁ ጊዜ ታዲያ ትግሉን ሌሎች ያራምዱታል፡፡ የፖለቲካ እንቅስቃሴውን እየተከታተሉ የቆዩኝ ታጋዮች አሉ፡፡ በተረፈ ይሄው አለሁ፤ መጥቻለሁ፡፡
እንደዚያ ከሆነ እስቲ የወቅቱን የተቃዋሚ ፓርቲዎች እንቅስቃሴ ይግለፁልኝ …
እኔ መናገር የምችለው ስለመድረክ ነው፡፡ ብዙዎቻችን ተሰባስበን ፕሮግራማችንን በዝርዝር አስቀምጠን መንቀሳቀስ ከጀመርን አመታት አልፈዋል፡፡ በአጠቃላይ የተቃውሞ እንቅስቃሴ ሲባል ዝም ብሎ ኢህአዴግን ከመጥላት ወይም በጣም ስላናደደን፣ አሊያም ስለበደለ (እንወክለዋለን የምንለውን ህዝብ ጨምሮ) … የፖለቲካ ድርጅቶች አቋቁሞ “ለስሟ መጠሪያ ቁና ሰፋች” ዓይነት በቂ አይደለም፡፡ ብዙ የተቃዋሚ ድርጅቶች፣ ዝም ብለው ተቃዋሚ ነን ብለው እንደሚቀመጡ አወቃለሁ፡፡ እኔ ባለፉት ሀያ ዓመታት በተቃዋሚው አካባቢ ስንቀሳቀስ ያለኝ ግንዛቤ፣ ተቃዋሚ ድርጅቶች የሚባሉት የተለያየ አላማ ያላቸው ናቸው፡፡ አንዳንዶቹ ኢህአዴግ ይጠቅሙኛል፣ ከኔ ፈቃድ ውጪ አይንቀሳቀሱም ብሎ የሚረዳቸው መሆናቸውን እናውቃለን፡፡ በተለያየ ደረጃና በተለያየ አላማ የተቋቋሙ የፖለቲካ ፓርቲዎች እንደቁጥራቸው የተለያዩ፣ በሚያግባባቸው መለስተኛ ፕሮግራም ዙሪያ እንኳን መሰባሰብ የማይችሉ ናቸው፡፡
በቁጥር የበዙ ቡድኖች ናቸው ያሉት፡፡ መድረክ ባስቀመጠው ራዕይ ዙሪያ ዲሞክራት ከሆኑ፣ አማራጭ አጀንዳ ካላቸው፣ ከኢህአዴግ ጋር የተደራጁ ፓርቲዎችን ጭምር አሰባስቦ የመጓዝ ፍላጐት አለን፡፡ እስከአሁን ባለው ሁኔታ ግን በመድረክ ዙሪያ ከተሰበሰቡት ወጣ ያሉቱ የጋራችን የሚሉት መለስተኛ ፕሮግራም ቀርጸው መንቀሳቀስ ያልቻሉ እንደሆኑ እውነታው ያሳያል፡፡ እርግጥ ነው ሙከራዎች ይደረጋሉ፤ ነገር ግን በሙጫ እንኳን ያልተጣበቀ ስብስብ ይሆንና ውዝግቡና መበታተኑ ይመጣል፡፡ እስካሁን ያለው የተቃዋሚው አካሄድ ወጥ አይደለም፡፡
መድረክስ ጤናው እንዴት ነው? በአንድ በኩል የ“አንድነት” እግድ አለ፤ ሰሞኑን ደግሞ “አረና” አቶ አስገደ ገ/ስላሴን ጨምሮ ያገዳቸው አባላት አሉ…
ከ“አንድነት” ፓርቲ በቀር የመድረክ አባላት አካባቢ ምንም ችግር አይታየኝም፡፡ አረና ውስጥ የተፈጠረው የሀሳብ አለመግባባት ነው፡፡ የሃሳቦች ልዩነት፡፡ ያንንም የአረና አመራር አጥርቶት አልፏል፡፡ የማዕከላዊ ኮሚቴው ተሰብስቦ የተወሰኑቱ በድርጅቱ ደንብና ስርአት መሰረት ራሳቸውን የማያርሙ ስለሆኑ እንዲገለሉ ተደርጓል፤ የተወሰኑት ደግሞ እንደታገዱ ታውቋል፡፡ የታገዱት አቋማቸውን አስተካክለው፣ የእገዳ ጊዜያቸውን ጨርሰው፣ ቆመንለታል ላሉት አላማ በጋራ መታገል ይኖርባቸዋል፡፡ በማዕከላዊ ምክር ቤቱ ታገዱ የተባሉት የትግል ተመክሮ የሚያንሳቸው አይደሉም፤ በትግል ያደጉ ናቸው፡፡ መገለላቸውን የምንወደውና የምንፈልገው አይደለም፡፡ ነገር ግን አዙረው አይተው፣ ወዳቋቋሙት ፓርቲያቸውና ወደ ትግሉ ይመለሳሉ የሚል ምኞት አለኝ፡፡ ከዚያ ውጭ ከአረና ጋር የተያያዘ ችግር መድረክ ውስጥ የለም፡፡
“አንድነት” ከመኢአድ ጋር የውህደት ሂደት ላይ ነው፡፡ ይህ ከመድረክ ጋር ካለው ግንኙነት አንፃር እንዴት ይታያል?
ይሄ ፈጽሞ የማይጣጣም ነገር ነው፡፡ የ“አንድነት” የእገዳ ጊዜ አልፏል፤ ነገር ግን አንድነት በዚህ መሀል ማሟላት ያለበትን ማሟላት እንዳልቻለ ተግባሩ ያሳያል፡፡ ልዋሀድ የሚለው አካል መኢአድ፣ ወደ መድረኩ ገብቶ እንዲጣመር በጠየቅነው ወቅት፣ “በኢትዮጵያዊነት ላይ ያላችሁን አቋም በፅሁፍ ግለፁልን” የሚል የትምክህትና የትእቢት ደብዳቤ የፃፈ ቡድን ነው፡፡ ያ አካል ከመድረክ ጋር አብሮ ሊሄድ አይችልም፡፡ ለእኛ የኢትዮጵያዊነት ሰጪና ከልካይነት፣ የትምክህት አስተሳሰብ ያለው ነውረኛ ደብዳቤ የሰጠ ድርጅት ነው፡፡ ከዚያን ጊዜ ወዲህ ቁምነገር ከሌለው ቡድን ጋር ጊዜያችንን አናባክንም ብለን ትተነዋል፡፡ በእኔ ግምገማ፣ አንድነት ከመኢአድ ጋር እዋሃዳለሁ ማለቱ፣ ከመድረክ ጋር ያለው ግንኙነት እንዳበቃ ነው የሚያሳየው፡፡ መድረክን ከሚኮንን ወገን ጋር መዋሃድ ማለት ምን ማለት ነው? መድረክን መኮነን ማለት ነው፡፡
ተቃዋሚዎች ኢህአዴግ ያደርስብናል ከሚሉት ጫና ባልተናነሰ በእርስ በርስ ሽኩቻ ይበልጥ እየተዳከሙ ነው… የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡ እርስዎ በዚህ ሃሳብ ይስማማሉ?
አንደኛ፤ ይሄ ተቃዋሚ የሚባለው አንድ አይነት መለስተኛ ፕሮግራም ኖሮት እስካልሰራ ድረስ እንደው ዝም ብሎ ተቃዋሚ ስለተባለ ብቻ እነሱ መሀል አንድነት አለ ብሎ ማሰብ ትክክል አይደለም፡፡ ምናልባት መድረክ ከኢህአዴግ ጋር ካለው ልዩነት የበለጠ ልዩነት ያለው የተቃዋሚ ድርጅት ሊኖር ይችላል፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ማዕከላዊ ስርአት ይቋቋም፤ ፌደራሊዝም ይፈራርስ የሚል ፓርቲ ቢመጣ፣ ምን ያህል ከኢህአዴግ ይሻላል በማለት መለየት አለብን፡፡ ልክ ከኢህአዴግ ጋር የምንታገለውን ያህል ከሌላም ህዝባዊ አጀንዳ የላቸውም ከምንላቸውም ጋር እንታገላለን፡፡
ተቃዋሚ ብሎ ራሱን በዚያ ፈርጅ ላይ ስላስቀመጠ “የጠላቴ ጠላት ወዳጄ ነው” ብለን አብረን አንቆምም፡፡ ጥራዝ ነጠቅ የሆነ፣ አገሪቱን ወደ ሌላ አቅጣጫ ለመውሰድ የሚንቀሳቀስ ፓርቲ ቢኖር እንቃወመዋለን፡፡ ምክንያቱም ለኢትዮጵያ ችግር መፍትሄ አይሆንም፡፡ ሁላችንንም ቀፍድዶ ስልጣን ላይ እንዳንወጣ ያደረገንን ኢህአዴግን ተረባርበን መጣል ብቻውን መልስ አይሆንም፡፡ ይሄ ዓይነቱ ሽኩቻ ግን ያለ ነው፡፡ ባይኖር ነበር የሚገርመኝ፤ የመድብለ ፓርቲ ስርአት ግንባታ ላይ ባለ አገር የሚኖር ተፈጥሮአዊ ጉዞ ነው፡፡
የገዢውን ፓርቲ ወቅታዊ ሁኔታስ እንዴት ይገመግሙታል?
ገዢው ፓርቲ በፖለቲካው ጉዳይ አመራር መስጠት አልቻለም፡፡ የስርአቱ አካሄድ የአደባባይ ሚስጥር ነው፡፡ ሙሰኝነት ተንሰራፍቷል፡፡ የሀገሪቷና የህዝቡ ንብረት ተበዝብዞ ካለቀ በኋላ “ጅብ ከሄደ ውሻ ጮኸ” አይነት ነገር ነው የሚሯሯጠው፡፡ አንድ ሰሞን ግርግር ይጀምርና ወዲያው ይተወዋል፡፡ ይሄን ህዝብ እየታዘበው ነው፡፡ ካድሬዎቻቸው ህዝብ ላይ ምን ያህል እንደሚባልጉ፣ ምን አይነት ተንኮል እንደሚፈጥሩ፣ እያንዳንዱን ቡድንና ግለሰቦችን እንዴት እያሰቃዩ ወደ ጥላቻ እንደሚገፉ የታወቀ ነው፡፡ ህዝቡ “ሆድ ይፍጀው” እያለ በከፍተኛ ምሬት ውስጥ ነው ያለው፡፡
የውጪ መንግስታት በተለይ ለጋሾቹ፣ “መንግስት የፖለቲካ አያያዙ ጥሩ አይደለም፤ በኢኮኖሚው ግን ደህና ነው” ይላሉ፡፡ የሰው ልጅ መቼም ዝም ብሎ በእንጀራ ብቻ አይኖርም፡፡ ልማት ተብላ የምትታየው ብቻ ሳትሆን ለአንድ አገር ቋሚ የሆነ ዋስትናው ፖለቲካው ላይ መስማማት ሲኖር ነው፡፡ ስልጣን እንዴት ይሸጋገራል የሚለው ላይ አሁንም ስምምነት የለም፡፡ የዚህ ስምምነት ያለመኖር በብሶት ላይ ብሶት እየጨመረ፣ የአገራችን መፃኢ ዕድል ላይ ትልቅ ችግር ፈጥሯል የሚል ስጋት አለን፤ እኔም በግሌ በእጅጉ ያሰጋኛል፡፡
በእርስዎ አተያይ አገሪቱ ያለችበት አጠቃላይ ሁኔታ ምን ይመስላል?
ያለነው የሚነድ ፍም ያለበት ሁኔታ ውስጥ ነው፡፡ እሳተ-ጎመራ ቆይቶ ይፈነዳል አይደል? የታመቀ ፍም እሳት አለ ማለት ነው፡፡ በግልም በቡድንም የማገኛቸው ሰዎች ይህን ነው የሚሉት፡፡ አሜሪካ ደውለው ምነው መላ ጠፋ? የሚሉኝ ነበሩ፡፡ ከመጣሁ ጀምሮ ብዙ ጥሪዎችን እቀበላለሁ፡፡ ሌሊት ከእንቅልፌ የሚቀሰቅሱኝ አሉ፡፡ መምጣቴን እንደትልቅ ነገር ቆጥረው፣ “ምን ይዘህ መጣህ?” ሲሉኝ “እስቲ እንግዲህ አንድ ላይ እናያለን” እላለሁ፡፡ ድምፃቸውን ሰጥተው የመረጡኝ ህዝቦች፤ “የምንችለውን ሰጠን፣ ነገር ግን ለውጥ አልመጣም፤ ከዚህ በላይ ምን እንስጥ?” ይሉኛል፡፡ የኔ መልስ “በአገር ጉዳይ ተስፋ አይቆረጥም” ነው፡፡ ባለፈው ካልሆነልን አሁን ደግሞ እንሞክራለን እላለሁ፡፡ ምርጫ ምርጫ እያላችሁ በየጊዜው ሰውን መማገድ ነው፤ መብት ማስከበር ካልቻልክ፣ ምርጫ ውስጥ ተሳተፉ፣ ለምን ትላለህ እባላለሁ፡፡ እኔ ግን ለዚህ ሁሉ የምለው፤ እኔ በአገሬ ጉዳይ ተስፋ አልቆርጥም ነው፡፡ ኢህአዴጎችም ሰብአዊ ፍጡር ናቸው፤ ይህንን ሁኔታ ወጥረው ይዘው ከመኖር መለስ ቢሉ መልካም ነው፡፡ እነሱ ከሚያስቡበት ክብ ውስጥ መውጣት ባለመቻላቸው አገሪቱ ችግር ላይ ናት፡፡ ህዝባችን ተረባርቦ በሚያሳየው ጥረት አንዳንድ እድገቶችና ለውጦች እናያለን፤ ይሄም ትንሽ ከፈት ስለተደረገ ነው፡፡ ሌላውን ተፅዕኖም ቢያነሱት ይህ አገር ምን ያህል ተንቀሳቅሶ፣ ምን ያህል የህዝቡ ህይወት ይቀየር እንደነበር መገመት እችላለሁ፡፡ አሁን እኮ ከበርቴው ሁሉ “እያበላሁ ነው የምንቀሳቀሰው” ነው የሚለኝ፤ ይሄ ቢወገድ ውጤቱ ምን ያህል ይሆን ነበር፡፡ ኢትዮጵያ መንታ መንገድ ላይ ናት፤ ኢህአዴጎች “በዚህ አይነት መንገድ አርባ ስልሳ ዓመት እንመራለን” ከሚለው ስነልቦና መውጣት አለባቸው፡፡
በሩቅ ምስራቅ ወጥ የሆነ ህዝብ ላይ ተግባራዊ የሆነ ሞዴል፣ ስብጥሩ በበዛ ህዝብ ላይ መሞከሩን ቢተውት ጥሩ ነው፡፡ ገና ህገመንግስቱን ያልተቀበሉ ቡድኖች ያሉበት አገር ላይ ይሄ አያዋጣም፡፡ እኛ ፓርላማ በነበርን ጊዜ ህዝቡ ማለት የሚፈልገውን ስለምንናገርለት ተንፈስ ይል ነበረ፤ ያንንም ዕድል አሁን ዘጉት፡፡ በመድረክ ግምገማ መሰረት፤ አሁን ወደ 1983 ዓ.ም መልሰውናል፡፡ ኢሰፓ ብቸኛ ፓርቲ ወደ ነበረበት ዘመን ማለት ነው፡፡ የሰላማዊ ትግል በሮች በመዘጋታቸው ወደ ሌላ የትግል ስልት ለመሄድ የሚያደፋፍር፣ ሰላማዊ የፖለቲካ እንቅስቃሴን ዋጋ ቢስ የሚያደርግ ሁኔታ እየተፈጠረ ነው፡፡ “እናንተ በሰላማዊ፣ ፓርላሜንታዊ ሂደት ለውጥ ማምጣት እንችላለን ብላችሁ የትግል መንፈሳችንን ገደላችሁት” ብለው የሚኮንኑን በርካታ ወገኖች አሉ፡፡
ከመንግስት ጋር ችግሮችን ተቀራርቦ በውይይት የመፍታት ዕድል አለ ብለው ያስባሉ?
እኔ ከእነዚህ ሰዎች ጋር በሽግግር ወቅትም አብሬያቸው ሰርቻለሁ፡፡ ስነልቦናቸውን አውቀዋለሁ፡፡ ከጠቅላይ ሚ/ር መለስ ዜናዊ ማለፍ በኋላ አልፎ አልፎ የነበረው የመነጋገር ዕድል ከእነ አካቴው የተዘጋ ይመስለኛል፤ እስከአሁን ምልክት አላየንም፡፡ የሚቀጥለው ምርጫ በተቻለ አቅም ለሁሉም ተደራሽ እንዲሆን፣ ተገናኝተን እንወያይ፤ በምርጫው ያሸነፈ ወገንን “እንኳን ደስ አለህ” ብሎ የመለያየት ባህል እንጀምር ብለን የሚያዳምጠን አጣን፡፡
መንግስትን ለውይይት ጠይቃችሁት ነበር?
የሚያከብሩት ለጋሽ አገሮቹን ነው፤ በእነሱ በኩል ብዙ ጥረት አድርገናል፤ የሚሠጠን ምላሽ ግን የአገሪቱ ህግ አካል የሆነውን የስነምግባር ደንብ አልፈረሙም ነው፡፡ ይሄ “የሞኝ ለቅሶ መልሶ መላልሶ” ነው፡፡ እኛ ደግሞ “ፓርላማ ወስዳችሁ ህግ አድርጋችሁታል፤ ፓርላማ በሚያወጣው ህግ ላይ አንፈርምም፤ የአገሪቱ ህግ ስለሆነ በሱ እንገዛለን” አልን፡፡ እኛ የምንለውን በግድ ተቀብላችሁ ካላንበረከክናችሁ ከሆነ ስህተት ነው፡፡
ዋናው ነገር መነጋገር አለብን፤ ዘግተን ከተቀመጥን ያው ጠላትነት ብቻ ነው ትርፉ፡፡ የምርጫ ስነምግባሩም ሶስት ነጥቦች አሉት፤ በምርጫ ወቅት እንዴት እንወዳደራለን፣ የምርጫ አስተዳደር እና የምርጫ ታዛቢዎች ጉዳይ ነው፡፡ እነሱ ከሶስቱ የመጀመሪያው ላይ ብቻ ነው የሚያተኩሩት፡፡ ሁሉንም ለምን አናይም በሚል ጥያቄ ነው የተፋረስነው፡፡ እንነጋገር ብለን ከጠየቅን አመት አልፎናል፤ እስከአሁን መልስ አልሰጡም፡፡
3 ጋዜጠኞችና 6 ጦማሪዎች በሽብርተኝነት ተከሰው በእስር ላይ ናቸው፡፡ 6 ያህል የግል መፅሄቶችና ጋዜጣ ክስ ተመስርቶባቸው፣ አሳታሚዎችና ጋዜጠኞችም ከአገር ወጥተዋል፡፡ በእዚህ ላይ የእርስዎ አስተያየት ምንድን ነው?
ይሄንን ለምን እንዳደረገው የሚያውቀው ኢህአዴግ ነው፡፡ ትንሹንም ትልቁንም ማሰር ለምን እንዳስፈለገ እኔ አላውቅም፡፡ አንድ ቤት ውስጥ አጥፊ ልጅ ካለ ተገቢ ዲሲፕሊን እንዲኖረው የሚደረግበት ሁኔታ አለ፡፡ አሁን እየወሰዱ ያሉት እርምጃ ግን አገራዊ ሃላፊነት የሌለበት ነው፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘም በአለም አቀፍ ድርጅቶችና በአንዳንድ መንግስታት የምንታይበት አይን ጥሩ አይደለም፡፡ በዚህ ድርጊት ማናችንም አንከበርም፤ አገራችሁ የጋዜጠኞች እስር ቤት ነው መባል አያስከብርም፡፡ ኢህአዴግ ለነገሮች የተጋነነ ምላሽ ይሰጣል፡፡ አንዳንዴ የሚደነግጡበት ሁኔታ ያለ ይመስለኛል፡፡ ኢህአዴግ የዋህ ቡድን አይደለም፤ መሠሪ ነው፡፡ መክሰስ ከፈለገ ቀደም ብሎ ነው የሚያቅደው፡፡ ጋዜጠኛ ልኮ መረጃ ሰብስቦ ኬዝ ይሠራል፡፡ የህጉ ፍትሀዊነትና ተገቢነት ብዙ ጥያቄ ያለበት ነው፡፡ ከተለያዩ አገሮች የተወሰደ ነው ይላል፡፡ ነገር ግን የአገሪቱን ተጨባጭ ሁኔታ ማገናዘብ ያስፈልጋል፡፡ አሜሪካን አገር ያለው የሽብርተኛ ትርጉምና እዚህ ያለው በጣም ይለያያል፡፡ እዚህ የወጡ ህጐች ተለክተው የተሠፉ ስለሆኑ፣ የታሠሩ ልጆች በጥንቃቄ ጉድለት በዚያ ወጥመድ የወደቁበት ሁኔታ ሊኖር ይችል ይሆናል፤ ዝርዝር ክሱን አላየሁም፤ ነገር ግን ኢህአዴግ ቀደም ብሎ ህግ ያወጣል፤ ከዚያ ኬዝ ይሠራል፡፡ ይህ ስርአት በሌላ እስከሚተካ ድረስ አንቀፆቹን ማወቅ ይኖርብናል፡፡ አንቀጽ ተጠቅሶ ስለሚከሰስ፣ ህዝባዊና አገራዊ ጥቅም የሌላቸውን ህጐች እስከምናሳርም ድረስ ጥንቃቄ ይጠይቃል፡፡ ብዙ ነገር ሊሠሩ የሚችሉ ልጆች እንደማይሠሩ ሆነው በየእስር ቤቶቹ መታጨቃቸው ያሳዝነኛል፡፡
ሌላው ጉልህ የአገሪቱ ችግር ሆኖ የዘለቀው የ “ሙስሊሞች ጉዳይ” ነው … በየጊዜው በሚነሳ ተቃውሞ ጉዳት ይደርሳል፣ ሰዎች ይታሰራሉ፡፡ መፍትሄው ምንድነው ይላሉ?
ጥያቄያቸው መንግስትና ሃይማኖት ይለያዩ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ከቻርተሩ ጀምሮ ህገመንግስታዊ መብት ነው፡፡ መንግስት የራሱን አመራር ለመምረጥ ሲሞክር የተፈጠረ ችግር ነው፡፡ ኢህአዴግ የተጠናወተው የመቆጣጠር አባዜ ውጤት ነው፡፡ ሁሉንም በሱ ቁጥጥር ስር እስካላደረገ ድረስ አያርፍም፡፡ ይህ አባዜ እኮ ነው ለችግሮቹ ሁሉ መንስኤ የሆነው፡፡
ከመጪው ምርጫ ምን ይጠብቃሉ?
ህዝቡ እንዲያውቅ የምፈልገው የ92ቱ ምርጫ በተወሰነ አካባቢ በተለይ በሀዲያ ዞን እኔን ጨምሮ የሌሎችን ቁርጠኝነት ህዝቡ ተቀብሎ፣ ለውጥ ይመጣል ብሎ ውጤት መገኘቱ፣ ኢህአዴግንም ሆነ ሌሎች ተቃዋሚዎችን አቅንቷል፡፡ ለ97 መሠረት የሆነው የ92 ምርጫ ነው፡፡ የሚወራው ስለ 97 ምርጫ ነው፡፡ እንግዲህ “አፍ ያለው ጤፍ ይቆላል” ነው፡፡ የ97ቱ ምርጫ የኢትዮጵያ ዲሞክራሲያዊ ሀይሎች ህብረት፣ ከኢህአዴግ ጋር ቁጭ ብሎ የምርጫውን ሜዳ፣ የምርጫውን ህግ መደራደሩን ተከትሎ የመጣ ውጤት ነው፡፡ አሁን ግን ሁሉም ህጐች ተለውጠዋል፡፡ ቀድሞ ወደ ነበሩበት ተመልሰዋል፡፡ የ97ቱ ምርጫ ኢህአዴግንም አስደነገጠ፤ ተቃዋሚዎችንም መድረስ እንችላለን ካሉት በላይ ስሜት ውስጥ ከተታቸው፡፡ ያኔ የውጪ ታዛቢዎች ነበሩ፤ የሲቪል ማህበራት እንደ አሸን የፈሉበት ወቅት ነው፤ ታች ድረስ ወርደው እያንዳንዱን ነጥብ ያዩበት ጊዜ ነበር፡፡ ከ97 ምርጫ በኋላ ኢህአዴግ “ይህቺ እንደገና አትደገምም” ብሎ እኛ እዚያው ፓርላማ ተቀምጠን የተደራደርንባቸውን ነገሮች ከልሶታል፡፡ አመቺ ሁኔታ እንዲፈጠር እንደገና ቁጭ ብለን እንነጋገር እያልን ነው፡፡ ኢህአዴግ ተቀምጦ ወደ መደራደር መግባት አለበት፤ የምርጫው ምህዳር ላይ እንስማማበት እያልን ነው፡፡ ይሄ ለአገሪቱ በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ በየቦታው ያለው የብሶት ስሜት አስቸጋሪ ነገር እየወለደ ነው፡፡ አንዳንዱ ደፋር ተስፋ ከመቁረጡ የተነሳ፣ እኛን “የኢህአዴግ ካድሬዎች ናቸው” ለማለት ሁሉ ይዳዳዋል፡፡
አንዳንድ ወገኖች እርስዎን በለዘብተኛነት ይፈርጅዎታል…
ለአላማዬ ጽኑ ነኝ፡፡ የአቋም ለዘብተኛ አይደለሁም፡፡ ሰው መዝለፍ ላይ ግን የለሁበትም፡፡ የሰውን ሃሳብ አጥላላለሁ እንጂ ግለሰብን አላጥላላም፡፡ ሰብዕና መንካት፣ መሳደብ አልወድም፡፡ ብዙ ጭብጨባ ፈላጊም አይደለሁም፡፡ የቴሌቪዥን ክርክር ላይ ስድብ ምናም ሲመጣ፣ ተቃዋሚንም ኢህአዴግንም አደብ ግዙ ብዬ አውቃለሁ፡፡
በ2007 አገራዊ ምርጫ ይወዳደራሉ?
ድርጅቴ መወዳደር አለበት ብዬ አምናለሁ፡፡ እነማን የት ጣቢያ ይወዳደሩ የሚለው ድርጅታዊ ውሳኔ ነው፡፡ በሚቀጥለው ምርጫ ድርጅቴን አወዳድራለሁ ማለት ግን ተገቢ እወጃ አይደለም፡፡ ድርጅቴ እንዲወዳደር ቀዳዳ ፍለጋ ላይ ነኝ፡፡
ድርጅትዎ እጩ ቢያደርግዎትስ …?
እሱንም አሁን መናገሩ ተገቢ አይደለም፡፡ የምናሠማራቸው አባሎች እንዲመረጡ አቅሜ የቻለውን ዕገዛ አደርጋለሁ፡፡ እኔ በግሌ ገባሁ አልገባሁ ልዩነት አያመጣም፡፡ የህዝብን አላማ በብቃት ሊያቀርቡ የሚችሉ ወገኖች ምርጫ ውስጥ ገብተው የህዝብ ይሁንታ እንዲያገኙ ለማብቃት ግን ጉልበቴን አልቆጥብም፡፡
ፕሮፌሰር በየነ ምን አይነት አስተማሪ ናቸው?
ሄደሽ ተማሪዎቼን ጠይቂያቸው፡፡
ውጤት ሲሰጡ “ኤ ለእግዚአብሔር”፣ “ቢ ለአስተማሪ”፣ “ሲ ለተማሪ” የሚሉ ዓይነትነዎት?
(ረጅም ሳቅ) እኔ ራሴን የምቆጥረው የተማሪዎች አገልጋይ አድርጌ ነው፡፡ ምክንያቱም ቀጣሪዎቼ ተማሪዎቼ ናቸው፤ ሁሌም ተማሪዎቼን “አለቆቼ ናችሁ” ነው የምለው፡፡ እኔ የምኖረው ተማሪዎቼ እስካሉ ድረስ ነው፡፡ የአስተዳደር ሰራተኛ ከመሆኔ በፊት ሥራዬ ምርምር መስራትና ማስተማር ነበር፡፡ ከተማሪዎቼ ጋር ውድድር የለብኝም፡፡ ፈተና ሳወጣም ከተማሪዎቼ ጋር ውድድር ውስጥ አልገባም፡፡ የዚህን ጥያቄ መልስ ሊያገኙት አይችሉም በሚል ፈተና አላወጣም፡፡ የማወጣው ጥያቄ ተማሪ አስቦ እንዲመልስ የሚያደርግ ነው፡፡ በፈተና ዜሮ የማያገኙበት አማራጭ ያለው ጥያቄ ነው የማወጣው፡፡
ምን አይነት የፈተና አወጣጥ ይጠቀማሉ?
በመምህርነት ባሳለፍኩባቸው ከ30 አመታት በላይ ጊዜ ውስጥ “ምርጫ” እና “አዛምድ” የሚሉትን የፈተና ዓይነቶች አውጥቼ አላውቅም፡፡ “እውነት ወይም ውሸት” አይነት ጥያቄ ካወጣሁ፣ ተማሪዎቼ እውነት ካሉ ለምን እንዳሉ፤ ውሸት ካሉም እንደዚያው ምክንያት እንዲያስቀምጡ እጠይቃቸዋለሁ፡፡ ተማሪ ማስታወሻ ያዘ አልያዘ አያስጨንቀኝም፡፡ ማዳመጥ እንዳለባቸው ግን እነግራቸዋለሁ፡፡
ተማሪ ክፍል መጣ አልመጣ የሚለውንስ ይቆጣጠራሉ?
ተማሪ ለራሱ እጠቀማለሁ ሲል ይመጣል የሚል እምነት ስላለኝ አቴንዳንስ አልወስድም፡፡ ግን ክፍሌ ባዶ ሆኖ አያውቅም፡፡ ብትመጡ ይመከራል እላለሁ:: አሜሪካን ኢሊያኖስ ውስጥ ያስተማርኩበት ዩኒቨርሲቲ “ገቨርናንስ ስቴት ዩኒቨርሲቲ” ይባላል፡፡ የትምህርት ቤቱ ህግ አቴንዳንስ ግዴታ (Compulsory) ነው ይላል፡፡ እኔ ግን አቴንዳንስ ይመከራል (Advised) እያልኩ ነው ያስተማርኩት፡፡
ከመጣችሁ ትጠቀማላችሁ እላለሁ፡፡ ካልመጣችሁ ኤፍ ታገኛላችሁ ግን አልልም፡፡ የቀረ ተማሪ ውጤቱን በራሱ መንገድ ያገኘዋል፡፡

የራሺያው መሪ ስታሊን ከዕለታት አንድ ቀን እንዲህ አደረገ አሉ፡፡
ሰዉን ስብሰባ ጠርቷል፡፡
ተሰብሳቢው ፀጥ ብሎ ያዳምጣል፡፡
ከተሰብሳቢው መካከል ድንገት አንድ ሰው አስነጠሰው፡፡
ስታሊን ንግግር ከሚያደርግበት ምስማክ ቀና ብሎ፤ በቁጣ፣ ኮስተር ባለው ድምፁ፡-
“ማነው አሁን ያስነጠሰው?” አለና ጠየቀ፡፡ ማንም አልመለሰም፡፡ ሁሉም ጭጭ አለ፡፡ ሰው ሁሉ አቀርቅሯል፡፡ በየሆዱ “ማንን ፈልጎ ይሆን?” ማን ይሆን የፈረደበት? እኔን ይሆን? እሷን ይሆን” ይላል፡፡ ያስነጠሰውም ሰው ተፈጥሮአዊ ጉዳይ ስለሆነ “እኔ ነኝ ብል ምን እሆናለሁ?” ብሎ መልስ አልሰጠም፡፡ ስታሊን ሆዬ አንጋቹን ጠራና፤
“እሺ ከኋለኛው መስመር ሁለቱን ተርታ ሰው አስወጣና ግደልልኝ!” አለና አዘዘ፡፡
አንጋቹም እንደታዘዘው ሁለቱን ተርታ ሰው እያንጋጋ ወስዶ ረሸነና ተመለሰ፡፡
ስታሊን ቀጥሎ፤ “እሺ ማነው ያስነጠሰው? አሁንም ተናገሩ!” አለ፡፡
አሁንም ዝም ዝም ሆነ፡፡ መናገር ቀርቶ ቀና ብሎ የሚያይ ሰው ጠፋ፡፡ አሁንም ወደ አንጋቹ ዞሮ፤
“ከኋለኛው መስመር ሁለቱን ተርታ ሰው አስወጣና ረሽንልኝ!” አለ፡፡
አንጋች ሁለት ተርታ ሰው አስወጣ፡፡
የጥይት እሩምታ ድምፅ ተሰማ፡፡ አለቁ ማለት ነው፡፡
ስታሊን እንደገና፤ “ማነው ያስነጠሰው? ተናገሩ!!” አለ እያንባረቀ፡፡
አሁን የቀረው ሁለት ተርታ ሰው ነው፡፡
ይሄኔ፤ አንድ መነፅር ያደረጉ አዛውንት እጃቸውን አነሱ፡፡
“እሺ ምን ይላሉ?” አላቸው ስታሊን፡፡ አዛውንቱም፤ በኮሰሰ ድምፅ “እኔ ነኝ ጓድ!” አሉ፡፡ “ይማርዎት!” አላቸው፡፡
አዛውንቱም፤ “ያኑርህ!” አሉ፡፡
* * *
ከስታሊን በትር ይሰውረን!
መሪና ተመሪ፣ አለቃና ምንዝር፣ ኃላፊና የሥራ ሂደት ኃላፊ ወዘተ. የሚፈራሩበት ሥርዓት ዲሞክራሲያዊነት ይጎድለዋል፡፡ የበላይን ከልኩ በላይ የመፍራት ልማድ፣ የበታቹን ማርበትበት፣ ቅጥና፣ አቅል-ማሳጣቱ፤ አልፎ ተርፎም ውሉን ስቶ፣ ቦታውን ስቶ ወደሌላ፣የሱ ወዳልሆነ ቦታ ወይም አገር፤ እስከመሰደድ ሊያደርሰው ይችላል፡፡ ኢፍትሐዊ ወይም የፈሪና የተፈሪ፣ ዘልቆም የጌታና - የሎሌን ዓይነት ግንኙነት፣ ከቶም ከዐይነ-ውሃው ስናየው ጤናማ አለመሆኑን ለማየት ብዙ ፀጉር ማከክን አይፈልግም፡፡ የባሰ ሥጋት የሚሆነው ነገር፣ የተገዢው ፈሪ መሆን ገዢው ላይ የሚፈጥረው የተዓብዮ ስሜትም ነው፡፡ ሥልጣንና ኃላፊነት ከሚፈቅደው ለከት በላይ “ለካ እንዲህ ይፈሩኛል” የሚል የማስፈራራት፣ የመቆጣት፣ የማርበድበድ… እርካታ፤ ሆዱ ውስጥ ያድራል፡፡ ከእንዲህ ያለው ጉልላት ወርዶ ትህትናን ተላብሶ፣ ህዝባዊ የሆነ ተዋህዶ መፍጠርና ሰው መሆንን መገንዘብ፣ ረዥም ጊዜ የሚጠይቅ ኢወገናዊ፤ ኢክፋታዊ፣ ኢአምባገነናዊ አሰራርን የመቀበልን ግለ-ሰባዊና ቡድናዊ፣ አልፎ-ተርፎም ጀማዊ ሥነ-ምግባርና ሙያዊ ብቃትን፣ እንዲሁም፤ የተጠያቂነትን መርህ የመቀበልንና ቅን ሥነ-ልቦናን የመዋሐድን ሥነ-ሥርዓት ይሻል፡፡
በዚህ አዲስ ዓመት፤ በተደጋጋሚ የተከሰቱ ችግሮችን፣ በተደጋጋሚ አውስተን፣ በተደጋጋሚ እንፈታቸዋለን ብለን ፎክረን፣ በተደጋጋሚ እዚያው እተነሳንበት ሥፍራ (Back to square – one እንዲሉ) የተመለስንባቸውን ጉዳዮች የምናስተውልበት፤ ያንን በማጤን፣ በመመርመርና ዘላቂ ዘዴ በመፍጠር፣ ጥበቡን የምንቀዳጅበት ያድርግልን!
መጪው ዘመን፤
ነገን የማንፈራበት፣ በልበ-ሙሉነት የምንጓዝበት፣ በዕውቀት እንጂ በጉልበት የማንራመድበት፣ አፈጮሌ፤ ሚዲያ አገኘሁ ብሎ ‹ያለእኔ ማን አለ?›፣ የማይልበት፣ አድር-ባይ ቀን ሞላልኝ ብሎ መቀመጫውን ለማደላደል በፍየል መሳይ ምላሱ የባጥ -የቆጡን የማይቀባጥርበት፣ “ሰው ባንበደቱ ውሻ በምላሱ” ይኖራል የማይባልበት ዘመን፤ ያድርግልን!
በሀገር ጉዳይ ንቅንቅ የማንልባቸው እንደኢትዮጵያዊነት፣ ሉዓላዊነት፣ የሀገር ህልውና፣ የዜግነት ክብር፣ ሥረ-መሰረታዊ ማንነት ወዘተ. ዛሬም የማይነኩ፣ የማይደፈሩና የማይገሰሱ ይሆኑ ዘንድ፤ ይሄ ዘመን ዐይናችንን ይክፈትልን!
ዛሬም ሙስናን የምንዋጋበት፣ ዛሬም ወገናዊነትን ሽንጣችንን ገትረን የምንፋለምበት ዘመን ያድርግልን! በየተቋሙ፣ በየቡድኑ፣ በየቢሮው “ሰው -አለኝ” የምንልበትን አሰራር ይህ ዘመን ያስወግድልን!
እንደታሪክ ስላቅ ሆኖ፤
“የአሜሪካ የሀገር ደህንነት አማካሪ ለእስራኤል የፍትህ ሚኒስትር የ“AIPAC” (የአሜሪካና የእስራኤል ህዝብ ጉዳይ ኮሚቴ) ውስጥ ያለ የሚረዳኝ ሰው ታውቃለህ ወይ?” ብለው ጠየቁ አሉ፡፡ ዋናው እንጀራ ጋጋሪ አሜሪካ ሆና ሳለ የውስጥ ሰው ከእስራኤል ፈለገች ማለት ነው፡፡ የሙስና ጥልቀቱ ኃያላኑም ውስጥ አለ፡፡ ሥር - ከሰደደ መመለሻ የለውም! ሆኖም ትግሉ ጥንቃቄና ትግስት ይጠይቃል፡፡ የሀገራችን ጣጣ አላልቅ ያለው ሁሉን ባንድ ቀን ፈተን፣ ሁሉን ባንድ ጀንበር አሸንፈን፣ ለዘመናት ያጠራቀምነውን ሕመም ባንድ ሌሊት ካልፈወስን ብለን፤ ዘራፍ በማለታችን ነው፡፡ “ዐባይን በአንድ ጊዜ ከመነሻውም ከመድረሻውም መጨለፍ አይቻልም”፤ ይለናል “ራስ ኤላስ መስፍነ - ኢትዮጵያ”፡፡ ሁሉን ችግር ባንድ ቅፅበት እንፈታለን ካልን አንዱንም ሳንጨብጥ እንቀራለን ነው ነገሩ፡፡ ማንም ቢሆን ማን፤ በብልህነት፣ በጥንቃቄና ደረጃ በደረጃ እንጂ በሁሉም ነገር ላይ ባንድ ጊዜ አብዮት ማፈንዳት አይችልም፡፡ በጥድፊያ የተካሄዱ፣ ሆይ ሆይ ተብለው ሥር-ሳይሰዱ መክነው የቀሩ አያሌ ጅምሮች እናውቃለንና ልብ እንበል፡፡ “ከላሟ፤ በአንድ ጊዜ ሥጋዋንም፣ ወተቷንም፣ ጥጃዋንም ማግኘት አይቻልም” የሚባለው ለዚህ ነው፡

 

Published in ርዕሰ አንቀፅ

*የኪነጥበብ ባለሙያዎች ሽልማት የተራዘመው “ለበጎ” ነው

 

       የአዲስ አበባ ከንቲባ የተከበሩ አቶ ድሪባ ኩማ፣ የከተማዋ ነዋሪ የትራንስፖርቱን ችግርና የታክሲውን ወረፋ በትዕግስት ችሎ መቆየቱን በማድነቅ፣ይቅርታና ምስጋና በአንድ ላይ ማቅረባቸውን ሰማሁ፡፡ (ኧረ ሽልማትም ይገባን ነበር!) በዚህ አጋጣሚ ግን ኢህአዴጎች የትም ዓለም ላይ ቢሄዱ እንደዚህ ያለ “ቻይ ህዝብ” እንደማያገኙ ልጠቁማቸው እወዳለሁ (“አያውቁንም” አለ ዘፋኙ?!) በነገራችሁ ላይ ይቅርታ መጠየቅና ማመስገን እንደሽንፈት በሚቆጠርባት አገር፣ከንቲባው ላሳዩት ድፍረት ምስጋና ይገባቸዋል (አድናቂያቸው ነኝ!) ሌሎች የመንግስት ባለሥልጣናትና የተቃዋሚ አመራሮችም ከሳቸው እንደሚማሩ ተስፋ እናደርጋለን፡፡ (“ተስፋ ርቆ የተሰቀለ ዳቦ ነው” እንዳትሉኝ!)
ወደ ጉዳያችን ስንመለስ--- ነዋሪው እኮ ያልቻለው ነገር የለም! የመልካም አስተዳደር ችግር (ራሱ ኢህአዴግ ያመነው እኮ ነው!) የመብራት፣ የኔትዎርክ፣ የኢንተርኔትና የውሃ መጥፋት--- ሌላም ሌላም ችሎ ነው የሚኖረው፡፡(“ዓለም አቀፍ የቻይነት አዋርድ” የለም እንዴ?) ለቻይነታችን እኮ ዓለም አቀፍ ሽልማት ይገባናል፡፡ እኔ የምለው ግን---የከንቲባው “ይቅርታና ምስጋና” ላለፈው ብቻ ነው ወይስ ለመጪውም ጊዜ ነው? (የ“ይቅርታ” ቀብድ የለውም ብዬ እኮ ነው!) ወደ ሌላ ወቅታዊ አጀንዳ ደግሞ እንለፍ፡
በዓመቱ ማብቂያ (ጳጉሜ 5 ላይ) ለኪነጥበብ ባለሙያዎች ሊሰጥ ታስቦ የነበረው ሽልማት ምን ደረሰ? (በባህልና ቱሪዝም ሚ/ር የተዘጋጀውን ማለቴ ነው!) ተራዘመ ሲባል ሰማሁ ልበል፡፡ (ኧረ በደንብ ይራዘም!) መራዘም ብቻ ሳይሆን መክረም ያለበት ጉዳይ እኮ ነው፡፡ በተለያዩ የኪነጥበብ ዘርፎች (በተለይ በሥነጽሁፍ) የተመረጡትን እጩ ተሸላሚዎች ስመለከት ግርም ነው ያለኝ፡፡ (እጣ የወጣላቸው እኮ ነው የሚመስሉት?) እንዴ --- ጊዜ ወስዶና የዘርፉን ባለሙያዎች አማክሮ እጩዎችን በቅጡ መምረጥ ማንን ገደለ? (“እርሟን ብታፈላ…” አሉ!) እስቲ አስቡት… ስለአገሪቱ ደራሲያን እያወራችሁ እነ አዳም ረታን (የአጭር ልብወለድ ቁንጮ እኮ ነው!) ይስማዕከ ወርቁን (“ዴርቶጋዳ” የተባለ ልብወለዱ ከ150ሺ ኮፒ በላይ ተቸብችቦለታል!) አለማካተት ምን ይባላል? (“ወይ እቺ አገር” አሉ አቦይ!)
አንጋፋዎቹን እነሃዲስ አለማየሁ፣ በዓሉ ግርማ፣ ብርሃኑ ዘሪሁን፣ አቤ ጉበኛ … ተዋቸው፡፡ ያስታወሳቸው የለም፡፡ ለነገሩ እንኳን በህይወት የሌሉት በህይወት ያሉትስ መች በወጉ ታወሱ?! እውነቴን ነው--- የእጩዎቹን ዝርዝር ስታዩ እኮ መለኪያው ግራ ይገባችኋል (በኮታ ይሆን እንዴ?) ግን እኮ ኮታውንም ቢሆን በወጉ ማድረግ ይቻል ነበር - በካታጎሪ (በዘርፍ በዘርፉ) በመከፋፈል፡፡ (“ለተቀማጭ ሰማይ ቅርቡ ነው” እንዳትሉኝ!) ከምሬ እኮ ነው … “ምርጥ ወጣት ደራሲ”፣ “ምርጥ የህይወት ዘመን ደራሲ”፣ “ምርጥ ፈርቀዳጅ ደራሲ”፣ “ምርጥ የኦሮሞኛ ልብወለድ ደራሲ” … ኧረ ቀላል ነው (ሮኬት ሳይንስ እኮ አይደለም!)
ሌላው ያስገረመኝን ደግሞ ልንገራችሁ (ላላያችሁት ነው ታዲያ!) በስነጥበብ ዘርፍ ከአስሩ እጩ ተሸላሚዎች (ሰዓሊዎች ማለት ነው) ውስጥ አንደኛው የስእል ጋለሪ ነው፡፡ ይታያችሁ---ሰዓሊዎችና የስዕል ጋለሪ በአንድ ዘርፍ ሲወዳደሩ? (እንዳይሆን እንዳይሆን ነው ልበል!) ለማንኛውም ግን አዘጋጆቹ ይሄን ተሞክሮ ከየትኛው አገር እንደቀዱት ቢነግሩን ሸጋ ነው (ከስህተት ለመማር እኮ ነው!)
በነገራችን ላይ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎችን የመሸለም ኃላፊነት የባህልና ቱሪዝም መሆኑን ያወቅሁት ዘንድሮ ነው፡፡ መቼም በአዋጅ የተሰጠው ሥራው ከሆነ እስከዛሬ የት ሄዶ ነው ያስብላል፡፡
(ብዙ ሽልማቶች አምልጠውናል ማለት ነው!) ዕድላችን ሆኖ ነው መሰለኝ ይሄ የሽልማት ነገር ብዙ ጊዜ አይዋጣልንም (“ምን ተዋጥቶልን ያውቃል?” ብትሉኝ መልስ የለኝም!)
ከዚህ ቀደም ስንቶቹ የሆሊውድ ዓይነት “ኦስካር” እንጀምራለን ብለው የውሃ ሽታ እንደሆኑ አልነግራችሁም፡፡ (ስፖንሰር አድራጊዎችን ተስፋ ለማስቆረጥ ይመስላል!) በሥነጽሑፍም----በተለይ በአጭር ልብወለድ ዘርፍ ለአንድ ዙር እንቁልልጬ ብለውን የውሃ ሽታ የሆኑ አሉ፡፡ (በምን ኃጢያታችን ይሆን?) እኔ የምለው ግን … ሰው ሁሉ “ገጣሚ” በሆነባት አገር፣ እንዴት ገጣሚያንን የሚሸልም ጠፋ? (የግንዛቤ ማስጨበጫ ዎርክሾፕ የግድ ነው!)
በነገራችሁ ላይ በባህልና ቱሪዝም የእጩ ተሸላሚዎች ዝርዝር ውስጥ እነ ግጥም፣ አጭር ልብወለድና ቲያትር .. ከእነመኖራቸውም ተዘንግተዋል (በ“ኪራይ ሰብሳቢነት” ተፈርጀው ነው አልልም!) ከሁሉም የሚደንቀው ደግሞ በእድሜ አንጋፋ የሆነው ትያትር ተዘንግቶ ፊልም መታጨቱ ነው (“ከኋላ የመጣ አይን አወጣ” አሉ!) ሌላው ቢቀር ጥቂት ትያትሮችን ከአንድ ትያትር ቤት ጋር ማጨት እንዴት ተሳናቸው? (ሰዓሊያኑና ጋለሪው በአንድ ዘርፍ እንደታጩት ማለቴ ነው!)
እኔ የምለው ግን … አንጋፋው የኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበር በዚህ በዚህ ወሳኝ ጊዜ የት ነው የሚጠፋው? የሥነ-ፅሁፍ ሥራዎችን የመሸለም ወግና ማዕረግ የሚያገኘውስ መቼ ነው? ትላንት የተጀመረው “ፔን ኢትዮጵያ” እንኳን የእንግሊዝኛ ልብወለዶችን በሦስት ዙር ሸለመ እኮ! (“ከልብ ካለቀሱ እንባ አይገድም” ለማለት ነው!) እናላችሁ--- አርአያ መሆን ቢያቅት አርአያ መከተል ይቻላል እኮ!
የሆኖ ሆኖ ግን የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የ2006 የኪነጥበብ ባለሙያዎች ሽልማት የተራዘመው ለበጎ ነው ብዬአለሁ፡፡ (እውነት ተራዝሞ ከሆነ ማለቴ ነው!) ለምን መሰላችሁ? በያዛቸው እጩ ተሸላሚዎች ዝርዝር ቢቀጥል እኮ “ሽልማቱ ተጭበርብሯል፤ይደገም!” የሚል ቅሬታ አይቀርም ነበር፡፡ (ከመጭበርበርና ከማጭበርበር ያውጣን!!)

        የተቃዋሚ ፓርቲዎች አዲሱ ዓመት ዲሞክራሲያዊ ስርአት የሚያብብበት፣ የህግ የበላይነት የሚረጋገጥበትና የፖለቲካ ምህዳር የሚሰፋበት ዓመት እንዲሆን በመመኘት፣ ለኢትዮጵያ ህዝብ የመልካም ዘመን ምኞታቸውን አስተላልፈዋል፡፡የኢትዮጵያ ዲሞክራሲውያን ፓርቲ (ኢዴፓ) ለአዲስ አድማስ በላከው የመልካም ምኞት መግለጫ፤ መጭው ዘመን የመድብለ ፓርቲ የፖለቲካ ስርአት የሚጠናከርበት፣ የጥላቻና የኩርፊያ ፖለቲካ ታሪክ የሚሆንበት፣ የመቻቻልና የመከባበር ፖለቲካ የሚጎለብትበት፣ የጭፍን ተቃውሞና ድጋፍ በአማራጭ የፖለቲካ ሃሳብ የሚተካበት እንዲሁም፣ ምክንያታዊ ፖለቲካ የሚያብብበት እንዲሆን ተመኝቷል፡፡
ህዝቡ በመጭው አገራዊ ምርጫ በተሳትፎው ስልጡን መሆኑን ዳግም የሚያረጋግጥበትና የፖለቲካ ምህዳሩ ሁሉንም አሳታፊ በሆነ መልኩ የበለጠ የሚሰፋበት እንዲሆን የተመኘው ኢዴፓ፣ የሀገር ዳር ድንበር በማስከበር ስራ ላይ ለተሰማሩ የመከላከያ ሰራዊት አባላት፣ ለህግ ታራሚዎች እንዲሁም ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብ መልካም አዲስ ዓመት ይሁንላችሁ ብሏል፡፡
ቅንጅት ለአንድነትና ለዲሞክራሲ ፓርቲ (ቅንጅት) በበኩሉ፤ ለ2007 ምርጫ ሰፊ ዝግጅት እያደረገ መሆኑን ጠቁሞ አዲሱ ዓመት የህግ የበላይነት የተረጋገጠበት፣ የዜጎች ሰብአዊ መብት ያለገደብ የሚከበርበት፣ ድህነት ተወግዶ ብልፅግና የሚመጣበት እንዲሁም ዜጎችን እኩል የሚያደርግ ዲሞክራሲዊ ስርአት የሚሰፍንበትና በህዝብ ለህዝብ” የቆመ መንግስት የሚመሰረትበት ይሆን ዘንድ ተመኝቷል፡፡ የኢህአዴግ አንዳንድ ካድሬዎች በቅንጅት አባላት ላይ ወከባ እየፈፀሙ ነው ያለው ቅንጅት፤ ነፃነትን ገድቦ የምርጫ በእንቅስቃሴ ውስጥ መግባት ተገቢ ባለመሆኑ፣ ኢህአዴግ በአዲስ ዓመት ጉዳዩን በአንክሮ ሊያስብበት እንደሚገባ አሳስቧል፡፡
አንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ፓርቲ (አንድነት)፤ በበርካታ የሃገሪቱ ከተሞች ህዝባዊና ሰላማዊ ሰልፍ በማድረግ ከ97 ዓ.ም ወዲህ በህብረተሰቡ ውስጥ የሰረፀውን ፍርሃት ፖለቲካ ድባብ በማስወገድ ከፍተኛ ጥረት ማድረጉን የጠቆሙት የፓርቲው ፀሐፊ አቶ ስዩም መንገሻ፤ የአባላት እስርና እንግልትን ጨምሮ በርካታ ተግዳሮቶች ቢገጥሙትም አላማውን አሳክቷል ብለዋል፡፡
ፓርቲው ከመላው ኢትዮጵያውያን አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ጋር ውህደት ለመፈፀም ከጫፍ ላይ ደርሶ እንደነበር አቶ ስዩም አስታውሰው፤ ሂደቱ ቢሳካ ኖሮ 2006 ዓ.ም ይበልጥ ስኬታማ ዓመት ይሆንልን ነበር ብለዋል፡፡ ውህደቱም በአዲሱ ዓመት በአጭር ጊዜ ውስጥ ይሳካል ብለን እናምናለን ሲሉ ተስፋቸውን ገልፀዋል፡፡ ቀጣዩ አመትም ሰብአዊና ዲሞክራሲዊ መብቶች እንዲሁም ኢኮኖሚያዊ ጥቅሞች ፍትሃዊ በሆነ መንገድ የሚከበሩበት፣ ማህበራዊ ፍትህ የሰፈነበት፣ እንዲሆን ከመንግስት በርካታ ስራዎች እንደሚጠበቁ ጠቁመው፤ ለኢትዮጵያ ህዝብ አዲሱ ዓመት የሰላም፣ የጤናና መልካም ምኞቱን ገልጿል፡፡ አገሪቱ ለሁሉም ኢትዮጵያውያን በእኩልነት የምትመች፣ ዜጐች ስደትን የማይመርጡባት አገር እንድትሆንም አንድነት ተመኝቷል፡፡ የኢህአዴግ የህዝብ ተሳትፎ አደረጃጀት ፅ/ቤት ኃላፊና የጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካሪ አቶ ደስታ ተስፋው በበኩላቸው፤ ያለፈው ዓመት ኢህአዴግ የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅዱን ተግባራዊ በማድረግ በርካታ ውጤት እያስመዘገበ ያሳለፈበት ዓመት መሆኑን ጠቅሰው፤ በተለይ ከድህነት ለመውጣት እየተደረገ ያለው ርብርብ አይቻልም የሚለውን መንፈስ የሰበረ ነው፡፡
2007 ዓ.ም የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅዱ የመጨረሻ ዓመት በመሆኑ ከምንጊዜውም በላይ ለላቀ ውጤት የምንነሳበትና የምንረባረብበት ዓመት ነው” ያሉት አቶ ደስታ፤ በዚህ ዓመት ምርጫ እንደሚካሄድ አስታውሰው፤ ህዝቡ ህገ-መንግስቱ የሰጠውን መብት ተግባራዊ የሚያደርግበት ዓመት ነው ብለዋል፡፡ ለኢህአዴግ ልዩ ትርጉም የሚሰጠው ዓመት መሆኑን የገለፁት አቶ ደስታ፤ ለመላው የኢትዮጵያ ህዝቦች የሰላም፣ የብልፅግናና የእድገት ዓመት እንዲሆን፣ ልዩነቶችን በሰለጠነ መንገድ እየፈቱ፣ በሃገራዊ መግባባት እጅ ለእጅ ተያይዘን ሃገራችንን ለላቀ ውጤት የምናበቃበት ዓመት ይሁን ሲሉ ተመኝተዋል፡፡ ያለፈው ዓመት ለመኢአድ አባላት ከባድ ጊዜ እንደነበር አስታውሰው ፓትሪውንም የተለያዩ አካላት ለማፍረስ ጥረት ያደረጉበት አመት ነበር ብለዋል፡፡ አክለውም የዲሞክራሲው ሂደት ወደ ኋላ እንጂ ወደፊት የሚሄዱበት ዓመት አልነበረም ብለዋል፡፡
“የ2007 ዓ.ም ደግሞ ህዝቡ በንቃት መሪዎቹን የሚመርጥበት ዓመት ይሁን፣ መንግስትና ምርጫ ቦርድ ቦታ ከሰጡን ለመወዳደር እንዘጋጀለን፤ ካልሰጡን ይቀራል” ያሉት አቶ አበባው፤ ዓመቱ ለኢትዮጵያ ህዝብ የሰላምና የብልፅግና እንዲሆን በፓርቲያቸው ስም መልካም ሞኞታቸውን አስተላልፈዋል፡፡
የመድረክ ስራ አስፈፃሚ አቶ ጥላሁን እንደሻው በበኩላቸው፤ መድረክ ለኢትዮጵያ ህዝብ አዲሱ ዓመት የሰላም፣ የብልፅግናና የጤና ዓመት እንዲሆን ተመኝተው በሃገሪቱ ያለው የፖለቲካ ምህዳር ችግር በሰላማዊ ውይይት ተፈትቶ ህዝቡ የስልጣን ባለቤት ለመሆን በፍትሃዊ ምርጫ ድምፁን የሚጥበት አመት ይሆን ዘንድ ተመኝተዋል፡፡

Published in ዜና

      በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፍልስፍና መምህር የሆኑት ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ፤ የዩኒቨርሲቲው የአመት ፍቃድ አሰጣጥን በተመለከተ የተፈጠረው አለመግባባት ሊፈታ ባለመቻሉ በመ/ቤታቸው ላይ ክስ ሊመሰርቱ እንደሆነ ተናገሩ፡፡
በዩኒቨርስቲው ህጋዊ አሠራር መሰረት 6 አመት ያስተማረ አንድ አመት ፍቃድ የሚሰጠው ቢሆንም የጠየቁት ፍቃድ ከተሰጣቸው በኋላ መነጠቃቸውን የገለፁት ዶ/ር ዳኛቸው፤ አቤቱታቸውን እስከ ዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ድረስ ለሚመለከታቸው ሁሉ ቢያቀርቡም ምላሽ እንደተነፈጋቸው ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡
“በአሜሪካ የሚገኙት ቤተሰቦቼ ስለናፈቁኝ እነሱን ሄጄ ማየት እፈልጋለሁ” ያሉት ዶ/ር ዳኛቸው፤ ከዚህ በኋላ መብታቸውን ለማስከበር ያላቸው ብቸኛ አማራጭ ጉዳዩን ወደ ፍ/ቤት መውሰድ ብቻ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
ዶ/ር ዳኛቸው ባለፈው ዓመት ሚያዚያ ወር ከአዲስ አድማስ ጋዜጣ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፤ “እድሜህ ስልሳ አመት ስለሞላና የጡረታ ሂደቱ በደንብ ተካትቶ ፋይልህ ውስጥ ስለሌለ የአመት ፍቃድህን ሠርዘነዋል” እንደተባሉ ገልፀው የነበረ ቢሆንም ከኮንትራት ውልና ከደሞዝ እግድ ጋር በተያያዘ ከዩኒቨርስቲው ጋር የነበራቸው ውዝግብ እልባት ማግኘቱን መናገራቸው ይታወሳል፡፡
ዶ/ር ዳኛቸው በኢህአዴግና በመንግስት አሰራር ላይ የሰላ ትችት በመሰንዘር የሚታወቁ ምሁር ቢሆኑም የማስተማር ሥራዬን ሳላቆም የየትኛውም ፓርቲ አባል መሆን አልፈልግም በሚል ራሳቸውን ከፓርቲ ፖለቲካ አግለው መቆየታቸው ይታወቃል፡፡

Published in ዜና
Page 10 of 14