ትንሽ ስለግጥም
ግጥም ምንድን ነው? ቅኔስ? ዜማ፣ ምት፣ ለዛ፣ ውበትስ? በመዋሸት እና በመቅጠፍ፤ በመሳቅ እና በምፀት፤ በራዕይ እና በቅዠት፤ በሙገሳ እና ውደሳ ምን መለያየት አለ? ማወቅ እና አለማወቅስ ምን ያመሳስላቸዋል?
ግጥም ወዳጅ መሆን እና መግጠም ሌላ ናቸው፡፡ መጥበብም መጠበብም፡፡ ጥበብ ሕይወት ተስፋ እምነትና ፍቅር በሚስጥር ይመራሉ፡፡ የነዚህን መምሪያ ሚስጥር ማወቅ እና ያወቁ መምሰል ግን ለየቅል ናቸው፡፡
እስቲ ግጥምን በኩራዝ እንመስል፡፡ እኔ ከየት እንደተሰለፍኩ አላውቅም፡፡ ሁለት ወገን ግን አያለሁ፡፡ አንደኛው ወገን ኩራዙን በመቅረዙ ላይ ለማንገስ፤ አንደኛው ከመቅረዙ አውርዶ ለመከስከስ የሚፋተጉ፡፡ አቅሜ ቢፈቅድ ኩራዙን መቅረዙ ላይ ለማንገስ እመኛለሁ፡፡ ለመከስከስ ለሚማስኑት ደግሞ ማዘን አለብኝ፡፡ “ወሎሙ በሙስናሆሙ ዐስበ ዓመጻ፡፡ (ለከንቱ ማስተማራቸው ደሞዝ ይቀበላሉና”፡፡ የሰራሁት ቢያስችለኝ ይህንን ማህበር መቀላቀል አልፈልግም፡፡
ችሎታን በሚመለከት
ከኩነኔ ጽድቅ ይሻላል፡፡ ከውሸትም እውነት፡፡ ግጥም እወዳለሁ እችል እንደሆነ ግን አላውቅም፡፡ ይችን መጽሐፍ ይዤ /የቅርቦቹን ብቻ ልጥራ/ በእነጌትነት እንየው፤ ነቢይ መኮንን፤ አበባው መላኩ፤ በድሉ ዋቅጅራ ...ጐዳና ስገባ እፍረት ነው ኩራት ነው ለእኔ?
እንዲህ ማለት ግን እችላለሁ፡፡
ፀጋየ ገ/መድህን፤ ዮሐንስ አድማሱ፤ ሰሎሞን ዴሬሳ፤ ሰይፉ መታፈሪያ ፍሬው...ግጥምን ለማሳደግ እየጣሩ፣ አዲስ አመጣጥ አገጣጠም አስተሳሰብ የሚፈበርኩ ናቸው፡፡ እኛ ግን እነሱን እንድንተካ ተስፋ ከቆረጥን እንድንመስላቸው እንፀልይ፡፡
ጥንትም የነበርን እኛ አሁንም ያለን እኛ
እንዴት ያን ሁሉ ወኔ ለደዌ ሰጥተን እንተኛ
እንዳለ ገጣሚ አበባው መላኩ
(“ደም የተፋ ብዕር” በሚል በደሳለኝ ስዩም ከወጣው የግጥም መድበል መግቢያ ላይ መጠነኛ ማስተካከያ ተደርጐበት የወጣ)