Monday, 23 December 2013 09:51

የሻምፒዮንስ ሊግ የበላይነት የዓለም ዋንጫን ድል ይወስናል

Written by  ግሩም ሠይፉ
Rate this item
(0 votes)

የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ላይ የሚገኝ ስኬት የዓለም ዋንጫን ኃይል ሚዛን እንደሚወስን ታወቀ፡፡ የእንግሊዙ ፕሪሚዬር ሊግ፤ የስፔኑ ላሊጋ፤ የጀርመኑ ቦንደስ ሊጋና የጣሊያኑ ሴሪ ኤ ክለቦች በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ላለፉት 10 ዓመታት የነበራቸው የበላይነት የየብሔራዊ ቡድኖቻቸውን ጥንካሬ በዓለም አቀፍ ውድድሮች አሳይቷል፡፡ በዘንድሮው ዓለም ዋንጫ በሚሳተፉ 32 ብሄራዊ ቡድኖች የአውሮፓ ታላላቅ ሊጐች ልምድ በውድድሩ የሚገኝ ውጤትን ማንፀባረቁ የማይቀር ይሆናል፡፡
የዘንድሮው የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ጥሎ ማለፍ ምእራፍ ድልድል ሰሞኑን ሲወጣ ማንችስተር ዩናይትድ ከግሪኩ ክለብ ኦሎምፒያኮስ፤ ፓሪስ ሴንትዠርመን ከጀርመኑ ክለብ ባየር ሌቨርኩዘን፤ ሪያል ማድሪድ ከጀርመኑ ክለብ ሻልከ፤ ቦርስያ ዶርትመንድ ከራሽያው ዜኒት ፒተርስበርግ፤  ቼልሲ ከቱርኩ ክለብ ጋላታሰራይ፤ አርሰናል ከአምናው የሻምፒዮንስ ሊግ አሸናፊ ባየር ሙኒክ፤ ማንችስተር ሲቲ ከባርሴሎና እንዲሁም አትሌቲኮ ማድሪድ ከኤሲ ሚላን  ተገናኝተዋል፡፡ የጥሎ ማለፉ ምእራፍ በፌብርዋሪ ወር የመጨረሻ ቀናት የመጀመርያ ጨዋታዎች ሲደረጉ የመልስ ግጥሚያዎች በማርች ወር መግቢያ ላይ ይደረጋሉ፡፡ከጥሎ ማለፉ ተፋላሚዎች ከፍተኛ የሻምፒዮንስ ሊግ ልምድ ያለው ባርሴሎና ሲሆን በ1102 ጨዋታዎች በማድረግ ነው፡፡ ማን ዩናይትድ 952 ፤ቼልሲ 899 ፤ሪያል ማድሪድ 825 ፤ባየር ሙኒክ 768፤አርሰናል 594፤ ኤሲ ሚላን 558፤ ማንችስተር ሲቲ 500 እንዲሁም ፓሪስ ሴንትዠርመን 491 የሻምፒዮንስ ሊግ ጨዋታዎች  ልምድ አላቸው፡፡ ዘንድሮ በዝውውር ገበያ ከፍተኛ ወጭ በማውጣት አንደኛ የሆነው በ163.5 ሚሊዮን ዩሮ  ሪያል ማድሪድ ሲሆን፤ ማን ሲቲ 116 ሚሊዮን ዩሮ፤ ፓሪስ ሴንትዠርመን 111 ሚሊዮን ዩሮ፤ ቼልሲ 75.4 ሚሊዮን ዩሮ፤ እንዲሁም ባርሴሎና 70 ሚሊዮን ዩሮ ወጪ አድርገዋል፡፡ 16ቱ  ክለቦች  በአጠቃላይ የቡድን ስብስባቸው በትራንስፈር ማርኬት የዋጋ ተመን ሲወጣላቸው አንደኛ ደረጃ ያለው 583.5 ሚሊዮን ዩሮ የተተመነው ሪያል ማድሪድ  ነው፡፡ ባርሴሎና በ582.3 ሚሊዮን ዩሮ ፤ ባየር ሙኒክ በ487.2 ሚሊዮን ዩሮ፤ ማን ሲቲ በ472.75 ሚሊዮን ዩሮ፤ ቼልሲ በ458.75 ሚሊዮን ዩሮ፤ ማን ዩናይትድ በ404 ሚሊዮን ዩሮ ፤ ፓሪስ ሴንትዠርመን በ361.3 ሚሊዮን ዩሮ ፤አርሰናል በ355.5 ሚሊዮን ዩሮ፤ ቦርስያ ዶርትመንድ በ293.8 ሚሊዮን ዩሮ ፤አትሌቲኮ ማድሪድ በ255 ሚሊዮን ዩሮ፤ ኤሲ ሚላን በ219.5 ሚሊዮን ዩሮ ፤ዜኒት ፒተርስበርግ በ205 ሚሊዮን ዩሮ ኤፍሲ ሻልካ 04 በ184.3 ሚሊዮን ዩሮ ፤ጋላታሰራይ በ157.4 ሚሊዮን ዩሮ ፤ባየር ሌቨርኩዘን በ137.1 ሚሊዮን ዩሮ እንዲሁም ኦሎምፒያኮስ በ72.3 ሚሊዮን ዩሮ በሚያወጡ የተጨዋቾች ስብስብ ተገንብተዋል፡፡
የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር በስሩ የ54 አገራት ፌደሬሽኖችን ቢያቅፍም ባለፉት 8 የሻምፒዮንስ ሊግ የውድድር ዘመናት ለግማሽ ፍፃሜ የሚደርሱ ክለቦች ከአራት የዓለማችን ታላላቅ ሊጐች ከሚካሄድባቸው ከስፔን፤ ከእንግሊዝ፤ ከጣሊያንና ከጀርመን ብቻ የሚገኙ ሆኗል፡፡ በዘንድሮው የሻምፒዮንስ ሊግ ጥሎ ማለፍ ምእራፍ ከሚገኙ 16 ክለቦች አራት ከእንግሊዝ፤ አራት ከጀርመን እንዲሁም ሁለት ከስፔን ሊጎች ተወክለዋል፡፡ ከእነኚህ አገራት ውጭ ሌላ ክለብ ከሌላ አገር ለመጨረሻ ጊዜ የነበረው ከ9 አመት በፊት የሆላንዱ ፒኤስቪ አየንድ ሆቨን ለግማሽ ፍፃሜ የደረሰበት ሲሆን ከፍተኛውን ውጤት ደግሞ በ1995 እኤአ ላይ አያክስ አምስተርዳም እና በ2004 እኤአ ላይ የፖርቱጋሉ ኤፍሲ ፖርቶ ዋንጫውን በማንሳት ያስመዘገቧቸው ታሪኮች ናቸው፡፡ድሮ የየአገሩ ትልልቅ ክለቦች ውጤታማ ይሆኑበት የነበረው የሻምፒዮንስ ሊግ መድረክ አሁን ለተወሰኑ አገራት ስኬታማነት የተመቹ መሆኑ የእግር ኳስን የኃይል ሚዛን አዛብቶታል፡፡
የአራቱ አገራት ክለቦች በሻምፒዮንስ ሊግ ውጤታማነት መቀጠል የሊግ ውድድራቸውን አጠናክሮታል፡፡ የሊጎቻቸው መጠናከር ደግሞ በየብሄራዊ ቡድኖቻቸው ስኬት ላይ እየተስተዋለ ነው፡፡ የክለቦች ስኬት በእነዚህ አገራት መሰረቱን ሊይዝ የበቃው ባላቸው የአካዳሚዎች እና በወጣቶች ላይ ያተኮረ ስልጠና ነው፡፡ በትልልቅ ዓለም አቀፍ ውድድሮች ከእንግሊዝ በስተቀር የጀርመን፤ የጣሊያንና የስፔን ክለቦች በአህጉራዊ ውድድሮች ያላቸው ስኬት ለብሄራዊ ቡድኖቻቸው ጥንካሬ መገለጫ ሆኗል፡፡ ከ2006 እኤአ ወዲህ የስፔን ብሄራዊ ቡድን ሁለት ጊዜ የአውሮፓ ዋንጫ እንዲሁም አንድ ጊዜ የዓለም ዋንጫ ድሎችን ሲያስመዘግብ ባለፉት ሁለት ኮንፌደሬሽን ካፕ ውድድሮች በሁለተኛ እና ሶስተኛ ደረጃ የብርና የነሐስ ሜዳልያ ተሸላሚ ሆኗል፡፡
የጣሊያን ብሄራዊ ቡድን በ2006 እኤአ የዓለም ዋንጫን ሲያሸንፍ በ2012 እኤአ ላይ በአውሮፓ ዋንጫ ሁለተኛ ደረጃን እንዲሁም በ2013 በኮንፌደሬሽን ካፕ የሶስተኛ ደረጃን ማግኘት ችሏል፡፡ በ2006 እና በ2010 እኤአ ላይ በተደረጉት ሁለት የዓለም ዋንጫዎች ሶስተኛ ደረጃ ያገኘው የጀርመን ብሄራዊ ቡድን በ2008 እኤአ በአውሮፓ ዋንጫ በሁለተኛ ደረጃ ጨርሷል፡፡
ከ1996 እኤአ ወዲህ በዓለመ አቀፍ ውድድር ዋንጫ አግኝቶ የማያውቀው የጀርመን ብሄራዊ ቡድን በብራዚል 20ኛው ዓለም ዋንጫ ዋንጫውን በማንሳት የመጀመርያው በደቡብ አሜሪካ የዓለም ሻምፒዮን ለመሆን የበቃ አውሮፓዊ ቡድን ለመሆን በከፍተኛ መተማመን ደረጃ ላይ ይገኛል፡፡በ20ኛው ዓለም ዋንጫ በደቡብ አሜሪካ እና በአውሮፓ ቡድኖች መካከል የሚኖረው ፉክክር ትኩረት መሳቡ የማይቀር ቢሆንም ጀርመን፣ ስፔንና ጣሊያን በሊጐቻቸው ጥንካሬ እና በክለቦቻቸው ውጤታማነት ከፍተኛ ግምት ይወስዳሉ፡፡
ከዚሁ ጋር ተያይዞ በእንግሊዝ፤ ስፔን፤ ጀርመንና ጣሊያን የሚካሄዱት አራቱ ታላላቅ ሊጎች በሻምፒዮንስ ሊግ ውጤታማነት የያዙት ብልጫ በቅርብ ጊዜ የሚቀናቀነው አይኖርም መባሉ የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበርን አስጨንቆታል፡፡ በሻምፒዮንስ ሊጉ በክለቦች የፋይናንስ አቅም የተፈጠረው የብቃት ልዩነት እና የቡድን ስብስብ መጠናከር የዓለም ዋንጫን የበላይነት መወሰኑን ለመገደብ ክለቦች በፋይናንስ እንቅስቃሴያቸው ስፖርታዊ ጨዋታነት እንዲኖራቸው ያወጣውን ገደብ የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር መፍትሔ እንደሚሆን ይገልፃል፡፡ በቲቪ መብት፤ በስፖንሰርሺፕ እና ከተለያዩ የዓለም ክፍሎች የባለሃብት ትኩረትን በመሳብ ያለው ልዩነት እየሰፋ መምጣቱ በሻምፒዮንስ ሊግ ያለውን የበላይነት ፈጥሮታል፡፡
ከ10 ዓመት በፊት ሩስያዊው ሮማን አብራሞቪች ቼልሲን በባለቤትነት ከያዙ ጀምሮ ዘንድሮ ኤንዶኖዢያዊ የሚዲያ ኢንቨስተር ኢንተርሚላንን በባለቤትነት እስኪገዛ በርካታ ባለሃብቶች ለአራቱ ምርጥ ሊጎች ያላቸውን ፍላጎት አሳይተዋል፡፡ በእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ተወዳዳሪ ከሆኑ 20 ክለቦች 11 በውጭ ባለሃብቶች ተይዘዋል፡፡ በስፔን እና ጣሊያን  ክለቦች እዳ በማብዛታቸው እና በጀርመን  ክለቦች የባለሃብት ድርሻ በ49 በመቶ ድርሻ መወሰኑ ወደ እንግሊዝ እንዲያመዝን ምክንያት ነው፡፡ በአጠቃላይ ግን የኤሽያ ከበርቴዎች፤ የዓረብ ሼኮች፤ የሩስያ ነዳጅ ቆፋሪዎች እንዲሁም የአሜሪካ ነጋዴዎች በተለይ ለአራቱ ሊጎች የሰጡት ትኩረት ክለቦቹን አጠናክሯቸዋል፡፡ በቅርብ ተፎካካሪነት እየተከተለ የሚገኘው የፈረንሳዩ ሊግ 1 ነው፡፡ ባለፉት ሶስት የውድድር ዘመናት ከፈረንሳይ ክለቦች መካከል ፓሪስ ሴንትዠርመንና ሞናኮ በሃብታም ሰዎች ባለቤትነት መገዛታቸው ይታወቃል፡፡ በእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ተሳታፊ የሆኑ ክለቦች 504 ተጨዋቾች  በዝውውር ገበያ አጠቃላይ ዋጋቸው እስከ 3.8 ቢሊዮን ዩሮ ይገመታል፡፡ በስፔን ላሊጋ ክለቦች 481 ተጨዋቾች  2.6 ቢሊዮን ዩሮ፤ በጣሊያን ሴሪኤ 574 ተጨዋቾች 2.4 ቢሊዮን ዩሮ እንዲሁም በጀርመን ቦንደስ ሊጋ ክለቦች 511 ተጨዋቾች  2.05 ቢሊዮን ዩሮ  ይተመናሉ፡፡

Read 1680 times