Saturday, 10 May 2014 11:43

የሃረማያ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች በቤተክርስቲያንና በመስጊድ እንደተጠለሉ ናቸው

Written by  አበባየሁ ገበያው
Rate this item
(4 votes)

         የአዲስ አበባና ኦሮሚያ ልዩ ዞን የጋራ ማስተር ፕላንን ጨምሮ የተለያዩ አስተዳደራዊ ጥያቄዎችን በማንሳት ተቃውሟቸውን የገለፁ የሃሮማያ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች፤ “ጥያቄያችን አልተመለሰም” በሚል እስከ ትላንትና ድረስ በተለያዩ አብያተ ክርስቲያናት እና መስጊዶች እንደተጠለሉ መሆናቸውን ምንጮች ገለፁ፡፡ ተማሪዎች ከአነሷቸው ጥያቄዎች መካከል የአዲስ አበባ ኦሮሚያ ልዩ ዞን የጋራ ማስተር ፕላንና በፌደራል መንግስት ከሚተዳደሩ የኦሮሚያ ከተሞች ጋር የተያያዙ ጉዳዮች ይገኙበታል ተብሏል፡፡

በሌላ በኩል በዘር የተቧደኑ የዩኒቨርሲቲው ተማሪዎች የፈጠሩትን ረብሻ ተከትሎ፣ የፌደራልና የክልል ከፍተኛ ባለስልጣናት እንዲሁም የአገር ሽማግሌዎች ካለፈው ቅዳሜ ጀምሮ ከተማሪዎቹ ጋር ውይይት ማካሄዳቸውን ምንጮች ገልፀዋል፡፡ የትራንስፖርት ሚኒስትሩ አቶ ወርቅነህ ገበየሁ፣ የኦሮሚያ ምክትል ፕሬዚዳንት አብዱላዚዝ አህመድን ጨምሮ የሐረሪ ክልል ም/ፕሬዚዳንት አቶ ረጋሣ ከፈለ ከተማሪዎች ጋር የተወያዩ ሲሆን ጥያቄያቸውን በሰላማዊ መንገድ በተማሪዎች ጉባኤ ማቅረብ እንጂ በረብሻ መግለፅ እንደሌለባቸው ተነግሯቸዋል - ምንጮች እንደገለፁት፡፡

Read 1510 times Last modified on Saturday, 10 May 2014 13:30