በኢትዮጵያ ጤናና ሥነ ምግብ ምርምር ኢንስቲቲዩት ብሄራዊ የሣንባ በሽታ የዳሰሳ ጥናት ዋና ፕሮጀክት አስተባባሪ አቶ ዘለቀ አለባቸው፤ ጥናቱን ለማድረግ የታሰበው የዓለም ጤና ድርጅት የሰጠው ግምታዊ አሀዝ ትክክለኛነት ለማረጋገጥና በአገሪቱ በአሁኑ ወቅት ያለውን ትክክለኛ የTB በሽታ ስርጭት ለማወቅ እንደሆነ ገልፀዋል፡፡
የዓለም ጤና ድርጅት ጥናቱን በገንዘብ ከመደገፉም በላይ በየሶስት ወሩ ክትትል ያደርግ እንደነበር የገለፁት አስተባባሪው፤ ድርጅቱ የጥናቱን ውጤት መቀበሉን ተናግረዋል፡፡
2.8 ሚሊዮን ዶላር (ወደ 50 ሚሊዮን ብር ገደማ) ተመድቦለት በተካሄደው ጥናት፤ ከመላ ሀገሪቱ የተመረጡ 85 ወረዳዎች ውስጥ በሚገኙ 63 የገጠር፣ 14 የከተማና 8 የአርብቶ አደር ቀበሌዎች ውስጥ የሚኖሩና እድሜያቸው ከ15 ዓመት በላይ የሆኑ 4620 ሰዎች ተሳታፊ ሆነዋል፡፡
በአብዛኛው የጥናቱ ተሳታፊዎች ላይ የቀጥታ የማይክሮስኮፕ ምርመራ ሲደረግ በሽታው ሳይገኝ እየቀረ በካልቸር ውጤታቸው ላይ የቲቢ ተህዋስያን መገኘቱንና ይህም አሁን በጥቅም ላይ ያለው የቲቢ ምርመራ ስርዓት በአግባቡ እንዲፈተሽና ተጨማሪ የምርመራ ስልትም ሊጠናከር እንደሚገባው የጥናት ውጤቱ ይፋ አድርጓል፡፡ከሰው ወደ ሰው በቀላሉ ሊተላለፍ የሚችለውና በአክታ ውስጥ የሚገኘውን የቲቢ ተህዋስ በአክታ ምርመራ ብቻ ለመለየት አለመቻሉና የራጅ ምርመራ የቲቢ በሽታን ለመለየት በተጨማሪነት ማስፈለጉ በአሁኑ ወቅት ያለው የምርመራ ሥርዓት አስተማማኝ አለመሆኑን አመላካች እንደሆነም ጥናቱ አረጋጧል፡፡
የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ምክትል ሚኒስትር ዶ/ር ከሰተብርሃን አድማሱ በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት፤ ከዚህ ጥናት በፊት የሣንባ በሽታ በአብዛኛው ይገኛል ተብሎ ይገመት የነበረው እድሜያቸው ከፍ ባለና የኤችአይቪ ህመምተኛ በሆኑ ሰዎች እንዲሁም አቅማቸው ደካማ በሆኑና የመከላከል ሃይል በሌላቸው ሰዎች ላይ እንደሆነ ጠቁመው ጥናቱ እንዳመለከተው ግን አብዛኛው የበሽታው ተጠቂዎች በወጣትነት እድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ ሰዎች መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡በአብዛኛው የአገሪቱ ክፍሎች ቲቢ በፊት ከተገመተው ዝቅ ብሎ የተገኘ መሆኑን የጠቆመው የጥናቱ ሪፖርት፤ በአንዳንድ አካባቢዎች ግን በርከት ያሉ ህሙማን መገኘታቸውን ገልጿል፡፡
ጥናቱ ከዚህ በተጨማሪም በአቅራቢያቸው ነፃ የቲቢ ምርመራና ህክምና እያለ አገልግሎቱን ሳይጠቀሙ በከፍተኛ ሁኔታ እየተጐዱ ያሉ ቁጥራቸው በርከት ያሉ በወጣትነት የእድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ ሰዎች መኖራቸውን አመልክቷል፡፡የጥናቱ ውጤት ይፋ በሆነበት ወቅት በኢትዮጵያ የአለም ጤና ድርጅት ወኪል ዶ/ር ፋቶማታ ናፎትራኦር እንደተናገሩት፤ በኢትዮጵያ ጤናና ሥነ ምግብ ምርምር ኢንስቲቲዩት የተደረገው ጥናት፣ ባለፈው 50 ዓመት የአለም ጤና ድርጅት ካደረገው ጥናት ወዲህ የመጀመሪያ መሆኑን ጠቁመው ይህም አገሪቱን በስፋት ተካሂዶ በስኬት በተጠናቀቀ የTB ዳሰሳ ጥናት የመጀመሪያ እንድትሆን አስችሏታል ብለዋል፡፡
የዓለም ጤና ድርጅት የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር በሽታውን በመከላከልና በመቆጣጠር ረገድ የሚያከናውናቸውን ተግባራት ከጐን ሆኖ ማገዙን እንደሚቀጥልም ጨምረው ገልፀዋል፡፡