Saturday, 23 August 2014 11:50

የልብ በሽታ ገዳይነት በካንሰር ተተክቷል

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

          ባለፉት አስርት ዓመታት በልብ በሽታ ሳቢያ የሚጠፋው የሰዎች ህይወት በከፍተኛ መጠን እየቀነሰ መምጣቱ ተገለፀ፡፡ በከፊል አውሮፓ በቀዳሚ ገዳይነቱ ይታወቅ የነበረው የልብ በሽታ በሰዎች ህይወት ላይ ሲያደርስ የቆየው የሞት አደጋ በከፍተኛ ደረጃ እንደቀነሰ በቅርቡ የወጣ ጥናት ጠቆመ፡፡ በምስራቅ አውሮፓ አገራት ግን የልብ በሽታ በግንባር ቀደም ገዳይነቱ እንደቀጠለ ጥናቱ አመልክቷል፡፡
“European Heart Journal” ላይ የወጣ ሪፖርት እንደሚጠቁመው ደግሞ ዴንማርክን በመሳሰሉ አንዳንድ አገሮች በአሁኑ ሰዓት የልብ በሽታን ተክቶ ካንሰር ትልቁ ገዳይ በሽታ እየሆነ መጥቷል ተብሏል፡፡
በከፊል አውሮፓ የልብ ህመም ገዳይነት የቀነሰው ከአኗኗር ዘይቤ መሻሻል ጋር ተያይዞ ነው ያለው ጥናቱ፤ በዋናነት የሲጋራ ማጨስ መቀነስና የተሻሻሉ ህክምናዎች ተጠቅሰዋል፡፡
የኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ የጥናት ትንተና እንደሚያሳየው፤ በአስር አውሮፓ አገራት ወንዶችን በከፍተኛ ደረጃ ለሞት እየዳረገ ያለው ከልብ ህመም ይልቅ ካንሰር ነው፡፡ በዴንማርክ ደግሞ ካንሰር የልብ ህመምን ቦታ ተክቶ በከፍተኛ ደረጃ ህልፈት እያስከተለ የሚገኘው በሴቶች ህይወት ላይ ነው ይላል፤ የጥናት ውጤቱ፡፡
ምስራቅ አውሮፓውያን ግን ከአቻዎቻቸው በእጅጉ ወደ ኋላ እንደቀሩ የጠቆመው ጥናቱ፤ በአንዳንድ የምስራቅ አውሮፓ አገሮች የልብ በሽታ አሁንም ከፍተኛ የሞት አደጋ እያስከተለ ነው ብሏል።
ከተመራማሪዎቹ አንዱ የሆኑት ዶ/ር ማይክ ራይነር ለቢቢሲ ሲናገሩ፤ “በልብ በሽታ የሚከሰተው አጠቃላይ የሞት መጠን እየቀነሰ ነው፤ በአንዳንድ አገራት ከሌሎች አገራት ፈጣን ነው፤ አሁንም ግን በአውሮፓ ትልቁ ገዳይ ነው” ብለዋል፡፡
የብሪቲሽ ኸርት ፋውንዴሽን ዋና ሥራ አስፈፃሚ ሲመን ጊሌስፒ በበኩላቸው፤ “በልብ ህመም በአጭር ጊዜ ውስጥ ይሞቱ የነበሩ በርካታ ሰዎች ቁጥር በመላው አውሮፓ መቀነሱ መልካም ዜና ነው” ሲሉ ተናግረዋል፡፡

Read 3544 times