Saturday, 06 September 2014 11:32

የእንቁጣጣሽ ስጦታ! “ክላሲካል ሙዚቃን በልምድ መጫወት አይቻልም”

Written by 
Rate this item
(4 votes)

የኒውዮርክ ታይምስ መጽሔት “From Chopin to Ethiopia and Part way Back Again (“ከቾፐን እስከ ኢትዮጵያ እና ደርሶ መልስ”) በሚል ባስነበበው የሙዚቃ ቅኝት ስቲቭ ስሚዝ ስለግርማ ይፍራሸዋ ያሰፈረው በከፊል ይሄን ይመስላል፡-
 “…በተነፃፃሪ ሲታይ፤ ስለክላሲካል ሙዚቃ በአፍሪካ፤ የሚያመላክቱ ጥቂት ማረጋገጫዎች ብቻ ይኑሩ እንጂ የምዕራቡ ክላሲካል ባህል በሌላው ዓለም ማለትም ከቬኔዝዌላ እስከ ቻይና እንደተንሰራፋው ሁሉ የአፍሪካንም ዙሪያ መለስ ማዳረሱ ገሀድ ነው፡፡ ለዚህ አስረጅ የሚሆነን የ45 ዓመቱ ኢትዮጵያዊ ፒያኒስትና ቀማሪ ግርማ ይፍራሸዋ በብሩክሉን “ኢሹ ፕሮጀክት ሩም” ቅዳሜ ምሽት ያቀረበው ምርጥ የፒያኖ ሥራ፤ እጅግ ብርቅ፣ ሥነ ውበታዊና ተምሳሌታዊ የክላሲካል ሙዚቃ መናኸሪያ መሆኑን የሚያሳይ ነው!
…. ግርማ “የኢትዮጵያዊያን በገና” ሊባል በሚችለው በክራር ነው የሙዚቃ ልጅነቱን የጀመረው፡፡ አዲስ አበባ ሙዚቃ ት/ቤት ሲገባ ከፒያኖ ጋር ተገናኘ፡፡ ከዚያ ነው በነቃ አዕምሮው በቡልጋሪያ የሶፊያ ስቴት ኮንሰርቫቶሪ መደበኛ ትምህርቱን ገፍቶ የተካነው…
“… ወደ ኢትዮጵያ በ1995 እ.ኤ.አ ከተመለሰ በኋላ ግርማ ደረጃውን የጠበቀ ክላሲካል ትርዒት ምን እንደሚመስል ደርዝ ያለው ግንዛቤ ማስጨበጥን ሥራዬ ብሎ ከመያያዙ ሌላ፤ አዳዲስ የሙዚቃ ስራዎችን ፅፏል፡፡ ለነዚህ አዳዲስ የጥበብ ስራዎች መቀመሪያ ይሆነው ዘንድ የአውሮፓን የጥበብ መላ ከኢትዮጵያ ሙዚቃና ሥነ-ትውፊታዊ ዕሴት ጋር በማጋባት ተጠቅሟል፡፡....››


ከፍተኛ ሽያጭ ያስመዘገበው አዲሱ አልበሙ በአሜሪካ በቢልቦርድ ሰንጠረዥ 23ኛ ደረጃ አግኝቷል ታዋቂው ፒያኒስት ግርማ ይፍራሸዋ በቅርቡ በአሜሪካ ያስመረቀው “Love and peace” የተሰኘ አዲስ አልበሙ፤ በቢልቦርድ ሰንጠረዥ 23ኛ ደረጃ ላይ እንደተቀመጠለት ይናገራል፡፡ በአሜሪካ ያቀረበው ኮንሰርት እንደተወደደለት የገለፀው ፒያኒስቱ፤ ኒውዮርክ ታይምስ ጋዜጣ በአድናቆት የተሞላ ጽሑፍ እንዳወጣለት ጠቁሟል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ኤልሳቤት ዕቁባይ ከግርማ ይፍራሸዋ ጋር ያደረገችው ቃለምልልስ እንዲህ ቀርቧል፡፡ ወደ ሙዚቃ እንዴት እንደገባ በመናገር ይጀምራል፡-  


ሙዚቃ የጀመርኩት በልጅነቴ ክራር በመጫወት ነው፡፡ ክራር ስጫወት ነው ያደግሁት፡፡ ፡፡ሙዚቃን በሳይንሳዊ መንገድ ለማጥናት ደግሞ  ያሬድ ሙዚቃ ትምህርት ቤት በመግባት፤ ከባህል ክራር፣ ከዘመናዊ ደግሞ ፒያኖን ለአራት አመት ተማርኩ፡፡ የያሬድ ሙዚቃ ትምህርት ቤት ትምህርቴን እንዳጠናቀቅሁ፣  በ1980 ስኮላርሺፕ አግኝቼ ወደ ቡልጋሪያ  አቀናሁ፡፡
እዚያ ከሄድክ በኋላ ግን ችግር ገጠመህ…
ፒያኖ ለመማር አልሜ ቡልጋሪያ በሚገኝ የሙዚቃ አካዳሚ ለሁለት አመት ከተማርኩ በኋላ በወቅቱ  በተፈጠረው የሶሻሊስት ካምፕ መፍረክረክና መፍረስ   ሳቢያ  የእኔና  በሙዚቃ ትምህርት ቤቱ የነበሩ ሌሎች ተማሪዎቸ እጣ ፈንታ ስደት ሆነ፡፡ ሁሉም በየፊናው ሲበተን እኔ  ጣሊያን ስደተኞች ካምፕ ውስጥ ገባሁ፡፡ ለስድስት ወራት ያህል  “ክርስቲያን ብራዘርስ” የተባሉ በጎ አድራጊዎች እየረዱኝ በካምፑ ተቀመጥኩ፡፡ ካምፑ ውስጥ ያሉ የተለያዩ አገር ስደተኞች በሞሉት ፎርም ላይ አሜሪካ ወይም ካናዳ መሄድ እንደሚፈልጉ ሲያሰፍሩ፣ እኔ  ግን ትምህርቴ  ለምን እንደተቋረጠ በመግለፅ የፒያኖ ትምህርቴን ቡልጋሪያ ሄጄ መቀጠል እንደምፈልግ ገለፅኩ፡፡ የበጎ አድራጎት ድርጅቱም የኔን ጥያቄ ከሌሎች በመለየት ነገሮች ሲረጋጉ የትምህርት ክፍያውን እየከፈሉ ትምህርቴን እንድጨርስ ቡልጋሪያ  መልሰው ላኩኝ፡፡ በአጠቃላይ ሰባት አመት የፈጀውን የፒያኖ ትምህርቴን አጠናቅቄ ማስተርሴን ካገኘሁ በኋላ ተመልሼ ጣሊያን ሄድኩ፡፡
ትምህርቴን እንድጨርስ የረዳኝ ድርጅት አሮጌ ፒያኖ ቢሰጠኝ እያልኩ እመኝ ነበር፡፡ ጣሊያን አገር በቆየሁበት ጊዜ ኮንሰርት ሰርቼ ስለነበር እሱን ተከትሎ ድርጅቱ አዲስ ፒያኖ በሽልማት ሰጠኝ፡፡ አሮጌ ቢሰጡኝ እያልኩ ስመኝ ፋብሪካ ድረስ ሄጄ መርጬ ባለፒያኖ ሆንኩ፡፡ ያ ለኔ ትልቅ ደስታ ነበር የፈጠረልኝ፡፡
ፒያኖዋ ግን ሌላ ስጋት ይዛ መጣች…
አዎ ፒያኖዋ በአውሮፕላን ከኔ ቀደም ብላ ነበር አዲስ አበባ የገባችው፡፡ እኔ ከመጣሁ በኋላ ፒያኖዋን ለመውሰድ ስጠይቅ፣ የቅንጦት እቃ ስለሆነ ታክስ መክፈል አለብህ በሚል ሁለት ወር ተያዘች፡፡ ሁለት ወር ሙሉ በየቀኑ አየር መንገድ እመላለስ ነበር፤ ምክንያቱም ፒያኖዋ የተቀመጠችው ደጅ ላይ ስለሆነ ፀሀይና ዝናብ እንዳያበላሻት በየቀኑ እየሄድኩ የምትሸፈንበትን ላስቲክ አስተካክላለሁ፣ እቀይራለሁ፡፡ እዚያ አካባቢ ያሉ ሰዎች እንዲንከባከቡልኝም አደራ እላለሁ፡፡ በመጨረሻ የጣሊያንና የቫቲካን ኤምባሲዎች ጣልቃ ገብተው በስጦታ እንደተሰጠኝ ለኢትዮጵያ መንግስት በደብዳቤ አሳውቀውልኝ እጄ ገባች፡፡ ፒያኖዋን ስረከብ ገልጬ ሳያት ከወገቧ በታች ዝናብ ገብቶባታል፡፡ በጣም አዘንኩና አለቀስኩ፡፡ በአካባቢው የነበሩ ሰዎች ለምን እንደማለቅስ ግራ ገባቸው፤ አንዳንዶች ደግሞ ለእንጨት ያለቅሳል እንዴ ብለውኛል፡፡ በነገርሽ ላይ ይህ ታሪክ የእንግሊዝ መንግስትና አዲስ አበባ የሚገኘው የእንግሊዝ ኤምባሲ፣ ለኢትዮጵያ ሚሊኒዬም  በጋራ ባወጡት ትልቅ መፅሀፍ ውስጥ ከተካተቱ ታሪኮች አንዱ ነው፡፡
ክላሲካል ሙዚቃ ምን አይነት ሙዚቃ ነው? እኛ አገር በመሳሪያ ብቻ ከተቀነባበረ ሙዚቃ ጋር የመቀላቀል ነገር ይስተዋላል…
የክላሲካል ሙዚቃ በ17ኛው ክፍለ ዘመን የተጀመረ የሙዚቃ ስልት ሲሆን በረጅም ጊዜ የትምህርት ሂደት የሚገኝ የሙዚቃ ክህሎት ነው፡፡ ክላሲካል ሙዚቃን በልምድ መጫወት አይቻልም፡፡ የክላሲካል ሙዚቃ ተብሎ ሲነሳ  እነ ሞዛርት፣ ሀይደን፣ ቤትሆቨን የመሳሰሉት የሰሯቸው ስራዎች ይጠቀሳሉ፡፡
እኛ አገር ያለው የክላሲካል ሙዚቃ ተቀባይነት ምን ይመስላል?
አድማጭ አለው፤ አቅርቦት ግን የለም፡፡ ፒያኖ ማግኘት እጅግ በጣም ከባድ ነው፡፡ በዚህ የሙዚቃ ዘርፍ መውጣት የሚፈልጉ ብዙ ልጆች አሉ፤ ግን የክትትል ችግር አለ፡፡ ቅድም እንዳልኩሽ የረጅም ጊዜ ስልጠና ይፈልጋል፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ተሰጥኦ ያላቸው ልጆች አሉ፡፡ እነሱን የሚፈልጉበት ለማድረስ ግን ብዙ ክትትል እና ድጋፍ ይፈልጋል፡፡
ያሬድ ሙዚቃ ትምህርት ቤት ማስተማሩን ለምን ተውከው?
እንዳልኩሽ ማስተማሩ በጣም ጊዜ ይጠይቃል፡፡ እኔ ደግሞ አጫጭር ኮርሶችን ስከታተልና ኮንሰርቶች ማሳየት ስጀምር፣ ቁጭ ብሎ የማስተማሩን ስራ እንዳያስተጓጉል በማለት ነው የተውኩት፡፡
 ቡልጋሪያ አስተማሪህ የነበሩትን ፕሮፌሰር አንተ በምታስተምርበት ያሬድ ሙዚቃ ትምህርት ቤት ኮንሰርት እንዲያሳዩ አድርገህ ነበር፡፡ እስቲ ስለሱ ንገረኝ…
ለእኔ እዚህ መድረስ የቡልጋሪያ አስተማሪዬ ፕሮፌሰር ኢታናስ ኮርቴሽ ትልቅ አስተዋፅኦ አድርጓል፡፡ እንደመምህሬ ሳይሆን እንደ ወላጄ ነው የማየው፡፡ እሱን ኢትዮጵያ አምጥቶ ኮንሰርት እንዲያሳይ ማድረግ ደግሞ የረጅም ጊዜ ህልሜ ነበር፡፡ በ2011 የሀንጋሪያዊው አቀናባሪ የፍራንስ ሊስታ 200ኛ አመት በአለም አቀፍ ፌስቲቫሎች ይከበር ስለነበር፣ ይህን አጋጣሚ ተጠቅሜ፣ እዚህ አገር ያሉትን የዲፕሎማቲክ ማህበረሰብ አግባብቼ ፕሮፌሰሩ አዲስ አበባ መጥቶ ኮንሰርት እንዲያቀርብ ጠየቅሁና ተሳካ፡፡ ኮንሰርቱም ተሰራ፡
አንተም ባለፈው ጥር ቡልጋሪያ በተማርክበት አካዳሚ ኮንሰርት አቅርበሃል…
አዎ፡፡ ከዚያም በተጨማሪ በቫዮሊን፣ በቼሎ እና በሌሎች የሙዚቃ መሳሪያዎች አዲስ ስራ ሰርቻለሁ፡፡ ቡልጋሪያ የሄደኩት እሱን ለማስቀረፅ ነበር፡፡ የተማርኩበት አካዳሚ ውስጥ በጥሩ ሁኔታ ተቀረፀ፡፡ ከዚያ እዚህ ያደረሰችኝን ቡልጋሪያን ኮንሰርት ሰርቼ ላመስግናት አልኳቸው፡፡ በጣም ደስ አላቸውና ኮንሰርቱን ሰራሁ፡፡ እነሱ የኔን የሙዚቃ እድገት እያንዳንዷን ደረጃ ይከታተሉ ነበር፡፡ ከኮንሰርቱ በኋላ “ቡልጋሪያን በተለያዩ የአለም መድረኮች እያስጠራህ ነው” ብለው  ትልቅ ሙያተኛና አስተዋፅኦ ላደረጉ ሰዎች የሚሰጠውን ከፍተኛ ሜዳሊያ ሸለሙኝ፡፡ በአሜሪካን በ2010 ዓ.ም ላይ  ትልቅ ኮንሰርት ተደርጎ ተሳትፌ ነበር፡፡ ሁለት የአሜሪካ ዩኒቨርሲቲዎች በሙዚቃ ዲፕሎማሲ የክብር እውቅና ሰጥተውኛል፡፡
የአሜሪካኑ የአልበም ማስመረቅ ፕሮግራም እንዴት ነበር?
የአሜሪካኑ ፕሮግራም  በጣም ውጤታማ ነበር፤ እንደምታይው ደስታው እስከአሁን ከፊቴ ላይ አልጠፋም፡፡ ሂደቱ ከተጀመረ ቆይቷል፡፡ “ኤምሲል ዎርልድ ሪከርድስ ሌብል”  በሚል የተባለ ኩባንያ ነው፡፡ ጥሩ ስራ የሰሩ ታዋቂ ሰዎችን ማስተዋወቅ ሲሆን ትልቁ ስራቸው ግን ያልታወቁ ሰዎችን መፈለግና ማስተዋወቅ ነው፡፡ “ስራህን በኢንተርኔት ላይ አይተነዋል፤ ጥሩ ነው እናስተዋውቅህ” ቢሉኝም ብዙዎች እንደዚያ እያሉ ተግባራዊ ስለማያደርጉት  አላመንኳቸውም ነበር፡፡ በኋላ ግን ስራዎቼን በአዲስ እንድቀርፅና ኮንሰርት እንዳደርግ የሚያስችል የስራ ፈቃድ እና ቪዛ ላኩልኝ፡፡ በ2013 ሄጄ ኮንሰርት አቀረብኩ፤ ስራዬንም ቀረፅኩ፡፡ በወቅቱ ኒውዮርክ ታይምስ ጋዜጣ በአድናቆት የተሞላ ፅሁፍ አወጣ፡፡ ሞራሌን በጣም ከፍ አደረገው፡፡ ከአንድ አመት በኋላ፣ ሰሞኑን ማለት ነው ሲዲዬን ለቀቅኩ፡፡ የአልበሙ መጠሪያ “ላቭ ኤንድ ፒስ” ነው፡፡ አልበሙ  ከፍተኛ ሽያጭ ነው ያስመዘገበው፡፡ በአሜሪካ የሙዚቃ ደረጃ በሚያወጣው የቢልቦርድ ሰንጠረዥም 23 ደረጃ ላይ ነበር፡፡ ከዚህ በፊት ከአርቲስት ሚካኤል በላይነህ ጋር የሰራሁት “መለያ ቀለሜ” የሚለው አልበምም በቢልቦርድ ሰንጠረዥ የገባ ሲሆን ለብቻዬ ከሰራኋቸው ውስጥ ግን የአሁኑ የመጀመሪያዬ ነው፡፡
የአሜሪካው ኮንሰርት ብዙ ኢትዮጵያውያን ታድመውት ነበር?
ብዙ ባይሆኑም ነበሩ፡፡ እንዲያውም ከኮንሰርቱ በኋላ እራት ጋብዘውኝ እንዴት አናውቅህም አሉኝ፡፡ ከጋባዦቼ አንዱ ደግሞ “አንተን የሙዚቃ ግርማ ሞገስ ብዬሀለሁ” አሉኝ፡፡ ይህ አባባል ለኔ ትልቅ ትርጉም አለው፡፡ አባቴ አስራ ሁለተኛ ክፍል ጨርሼ ዩኒቨርሲቲ ከተማርኩ በኋላ ወደ ስራ እንድገባ ነበር የሚፈልገው፡፡ የሙዚቃ ጉዞውን እንዳታደናቅፉት ብለው ብዙ እገዛ አድርገው ለዛሬ እኔነቴ የለፉት አጎቴ ናቸው፤ ስማቸው ደግሞ ሞገስ ነው፡፡ ግርማ ሞገስ ሲሉኝ በጣም ደስ አለኝ፡፡
ልጆችህን ፒያኖ እያስተማርክ ነው?
አዎ! የትምህርት ጊዜያቸውን ሳልሻማ በትርፍ ሰአት አስተምራቸዋለሁ፡፡
በሚቀጥለው ሐሙስ አዲስ አመት ነው፡፡ መጪውን  አመት እንዴት ትቀበለዋለህ?
እንግዲህ እድሜ አግኝቶ  አዲስ አመትን መቀበል  ትልቅ ነገር ነው፡፡ በተቻለ መጠን አዳዲስ ስራዎቼን እንዲሁም ተሰርተው የተቀመጡትን የማስተዋውቅበት አመት ይሆናል፣ ሌሎች ብዙ በሮችም ይከፈታሉ ብዬ በተስፋ እቀበለዋለሁ፡፡

Read 3569 times