Saturday, 24 January 2015 12:57

አርሾ በአራት የህክምና ምርመራ ዘርፎች እውቅና አገኘ

Written by  መታሰቢያ ካሳዬ
Rate this item
(0 votes)

በቅርቡ በ6 የክልል ከተሞች አገልግሎት ለመስጠት አቅዷል
   አርሾ ሜዲካል ላብራቶሪ በአራት የሀክምና ምርመራ ዘርፎች ማለትም በኬሚስትሪ፣ በሔማቶዘሎጂ፣ በኢንዶክሪኖሎጂና በሴሮሎጂ ከኢትዮጵያ ብሔራዊ አክሪዲቴሽን ጽ/ቤት የእውቅና ሰርተፍኬት አገኘ፡፡
ድርጅቱ ይህንኑ የእውቅና ሰርተፍኬት አቀባበል ሥነስርዓትን ከትናንት በስቲያ በኢንተርኮንትኔንታል ሆቴል ውስጥ ሲያካሂድ እንደተገለፀው እውቅናው አገር አቀፋዊና አህጉር አቀፋዊ የሆነ የላብራቶሪ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችል ጥርጊያ መንገድ ከፋች ነው ተብሏል፡፡
ላለፉት 42 ዓመታት እጅግ ዘመናዊ በሆኑ የላብራቶሪ መሣሪያዎችና በሰለጠኑ ባለሙያዎች ከ300 በላይ የሚሆኑ የላብራቶሪ ምርመራ አገልግሎቶችን ይሰጣል፡፡ በድርጅቱ ውስጥ የሚኙት አብዛኛዎቹ የላብራቶሪ መመርመሪያ መሣሪያዎች ዘመኑ የደረሰባቸውን የቴክኖሎጂ ደረጃዎች የጠበቁ መሆናቸውን የገለፁት የድርጅቱ የፋይናንስና አስተዳደር ዳይሬክተር አቶ ብቅአለ መስፍን በመሣሪያዎቹ ዋጋ ከፍተኛነትና በሰለጠነ የሰው ኃይል እጥረት ምክንያት በአገር ውስጥ ማድረግ የማይቻሉ አንዳንድ ምርመራዎችን ወደ እንግሊዝ፣ ጀርመንና ደቡብ አፍሪካ ናሙናዎችን በመላክ ውጤቱን በኢሜይል በመቀበል ለተመራማሪዎች የሚያስረክብ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡ ድርጅቱ አሁን የእውቅና ሰርተፍኬት ካገኘባቸው የህክምና ምርመራ ዘርፎች በተጨማሪ በሌሎች ዘርፎችም በተለይም በማይክሮ ባዮሎጂ የእውቅና ሰርተፍኬት ለማግኘት ጥረት በማድረግ ላይ መሆኑንም በዚሁ ወቅት ገልፀዋል፡፡ የድርጅቱ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ወ/ሮ ዘለዓለም ፍሰሃ ድርጅቱ ለረጅም ጊዜ ለህብረተሰቡ ጥራት ያለው የህክምና ምርመራ አገልግሎት ሲሰጥ የቆየ መሆኑን ገልፀው አሁን ያገኙት እውቅና በአራት ትላልቅ የምርመራ ዘርፎች ሆኖ በሥሩ በርካታ የምርመራ ሥራዎችን ለመሥራት የሚያስችላቸው እንደሆነና ይህም ቀደም ሲል በአገር ውስጥ የማይሰሩ ምርመራዎችን ለማድረግ የሚያስችላቸውና እየተሰሩ ያሉትንም የላብራቶሪ አገልግሎች የጥራት ደረጃ ከፍ የሚያደርግ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ አርሾ ሜዲካል ላብራቶሪ ከፍተኛ አቅምና ብቁ መሣሪያዎች ያሉት ድርጅት ነው ያሉት ዳይሬክተሯ በአሁኑ ወቅት እየተጠቀመ ያለው የአቅሙን 30 በመቶ ብቻ መሆኑንና ይህንን ለማሳደግም ከፍተኛ ጥረት በመዳረግ ላይ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በቅርቡ በ6 የአገሪቱ የክልል ከተሞች ማለትም በድሬዳዋ፣ አዋሣ፣ ባህርዳር፣ ጐንደርና ትግራይ ላይ አገልግሎት መስጠት እንደሚጀምሩም ገልፀዋል፡፡ በ1965 ዓ.ም በአርመናዊው ተወላጅ በዶ/ር አርሾቬር ቴሪዚያን የተመሰረተውና በአገሪቱ የመጀመሪያው የግል የህክምና ላብራቶሪ እንደሆነ የሚነገርለት አርሾ ሜዲካል ላብራቶሪ በአሁኑ ወቅት በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ በሚገኙ 6 ቅርንጫፎቹ የህክምና ምርመራ አገልግሎት በመስጠት ላይ ይገኛል፡፡

Read 4210 times