Saturday, 14 February 2015 13:01

ጦማሪያኑንና ጋዜጠኞቹን በተመለከተ ለተባበሩት መንግስታት አቤቱታ ቀረበ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(1 Vote)

            በሽብርተኝነት የተከሰሱትን የዞን 9 ጦማሪያንና ጋዜጠኞችን አስመልክቶ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ተቋማት ለተባበሩት መንግስታት አቤቱታ አቀረቡ፡አቤቱታውን ያቀረቡት መቀመጫቸውን ኬንያ - ናይሮቢ ያደረጉት “የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ፕሮጀክት” እና “ፍሪደም ናው” የተባሉት የሰብአዊ መብት ተቋማት እንደሆኑ ታውቋል፡፡ለተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብት ቡድን የቀረበው አቤቱታ፤ ጦማሪያኑና ጋዜጠኞቹ አላግባብ መታሰራቸውን፣ እስሩ አለማቀፍ መብቶችንም ሆነ የወንጀል ህግ መሰረቶችን የጣሰ መሆኑን የሚያመለክት ሲሆን ጦማሪያኑና ጋዜጠኞቹ በእስራቸው ወቅት እየደረሰባቸው ነው የተባሉ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን በዝርዝር ያካተተ እንደሆነ በድርጅቶቹ ድረገፅ ላይ ከሰፈረው ባለ 23 ገፅ አቤቱታ ሰነድ ለማወቅ ተችሏል፡፡ጦማሪያኑና ጋዜጠኞቹ በሽብርተኝነት ተጠርጥረው ከታሰሩ ጊዜ ጀምሮ ለ19 ጊዜያት ያህል ፍ/ቤት መቅረባቸውን የጠቀሰው አቤቱታው፤ ተገቢውን ፍትህ ሳያገኙ በህግ የተሰጣቸው ሰብአዊ መብት እየተጣሰ ነው ብሏል፡፡ ከወራት በፊት የተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብት ኤክስፐርቶች ቡድን፤ የኢትዮጵያ መንግስት የጸረ - ሽብርተኝነት ህጉን ሃሳብን በነፃነት የመግለፅ መብትን ለማፈኛነት እንዳይጠቀም ጠይቆ ነበር፡፡ “ሽብርተኝነትን መዋጋት በአሁን ወቅት አስፈላጊ ነው፤ ነገር ግን አለማቀፍ የሰብአዊ መብት ድንጋጌዎችን በሚጥስ መልኩ መሆን የለበትም” ማለቱ ይታወሳል፡፡
በእነ ሶሊያና ሽመልስ መዝገብ በሽብር ተከሰው በእስር ላይ የሚገኙት 6 ጦማሪያን እና 3 ጋዜጠኞች፤ ጥር 26 ቀን 2007 ዓ.ም ፍ/ቤት ቀርበው ሰብሳቢ ዳኛው እንዲነሱላቸው መጠየቃቸው የሚታወስ ሲሆን ፍ/ቤቱም በጉዳዩ ላይ ብይን ለመስጠትና በክሱ የተጠቀሱትን ድርጊቶች ፈፅመዋል አልፈፀሙም በሚለው ላይ የእምነት ክህደት ቃላቸውን እንዲሰጡ ለየካቲት 11 ቀን 2007 ዓ.ም
ቀጠሮ መስጠቱ የሚታወስ ነው፡፡

Read 1781 times