Saturday, 04 July 2015 10:55

ለደራሲ ችግር ተድላ ነው? ወይስ ተድላ ችግር?

Written by  ዓለማየሁ ገላጋይ
Rate this item
(1 Vote)

“እኔን ፅሁፍ ለማስጣል ይህ ሁሉ ጣጣ አያስፈልግም፡፡ ብትጠይቂኝ ዘዴውን እኔው እነግርሽ ነበር፡፡ ዘዴው ምን መሰለሽ? ቀላል ነው። ላንድ ወር በየቀኑ ዶሮ ማረድ፡፡ ያንን በእርጐ እያደረግሽ ማቅረብ፡፡ ክትፎም ቢጨመርበት ይበልጥ ፍቱን ይሆናል፡፡ በዚያ ላይ ቀዝቃዛ ቢራ በቃ፡፡ የጽሑፍ ነገር እርግፍ ብሎ ይቀራል፡፡  አረቦች እንደሚተርቱት፤ ‹ሆድ ሲሞላ ጭንቅላት ባዶ ይሆናል› ከዚህ የበለጠ ምን ዘዴ አለ?...”
(በዓሉ ግርማ “ደራሲው”)
በዓሉ ግርማ ደራሲን የደራሲነት “ትጥቅ” የሚያስፈታው ጥጋብ እንደሆነ እየነገረን ነው፡፡ ጥጋብ የሰው ልጆች ሁሉ የምንማስንለት ተፈጥሯዊ ግብ አይደለምን? ታዲያ ደራሲን ከሰው ልጆች ተርታ ምን አስፈንጥሮ ወረወረውና ረሃብ ሠራሽ ሆነ? ደራሲነትን ከግርንቢጥነት ያጋባ ገለፃ ነው፡፡ ለመሆኑ ደራሲ ምንድነው? ሰው ሁሉ በሚደርቅበት ቦና የሚለመልም? በሚያሸትበት የሚረግፍ ግርንቢጥ? እንዴት በሚበርደው ይሞቃል? በሚያቃጥለው ይንዘፈዘፋል? ደራሲን በደራሲነት የሚያተጋው ረሃብ ነው ማለት ነው? እንዲያ ከሆነ አንድ ነባር ብሒል እንዋስ፡-
“ከተራበ ደራሲ ለጠገበ ደራሲ አዝናለሁ!”
ይሄንኑ የበዓሉ ግርማን አባባል ከሌላ አቅጣጫ አይቶ የደገመ የሥነ - ልቡና ምሁር አለ፡፡ ስኮትላንዳዊው የፍካሬ - ልቡና (Psychoanalysis) መስራች ሲግመን ፍሩድ ነው፡፡ ጥበብን ከሆድ ሳይሆን ከወሲብ አቅጣጫ ያየዋል፡፡ አንድ የጥበብ ሰው የታመቀ የወሲብ ፍላጐት (Libido ወይም repressed sexual desire) ከሌለው ባሩድ እንዳነሰው ጥይት ቢተኮስም ይከሸፋል ባይ ነው። ጥበብ በወሲብ ረሃብ እንጂ በፍትወት ጥጋብ አትገኝም፡፡ የታመቀ የወሲብ ፍላጐትን ለጥበብ አላማ በማዞር (Sublimation) ግሩም ውጤት ማግኘት ይቻላል ብሎ ያምናል፡፡
የበአሉንም ሆነ የሲግመን ፍሩድን ብያኔ የሚፃረሩ ደራሲያን ዘንድ ተከስተዋል፡፡ ከሁለቱም አንድ አንድ ደራሲ ከ “ጣዝማ” መጽሐፍ እንጥቀስ፡፡ ፈረንሳዊ የልቦለድ ደራሲ ኖርማንድ ግራ የሚያጋባና የሚደንቅ የአመጋገብ ልምድ እንደነበረው እዚህ መጽሐፍ ላይ ይጠቀሳል፡፡ “መቶ የሼል አሣዎች ከቀማመሰ በኋላ ከጠቦት በግ አሥራ ሁለት ሙዳ ሥጋ ያክልበታል፡፡ በዚህ አያበቃም፡፡ ከጥሩ አትክልት ጋር የተዘጋጀች አንድ ዳክዬና የሁለት ቆቆች አሮስቶ ጨምሮ ሲጥ ያደርጋል፡፡ ከዚህ በኋላም የበላውን ምግብ ለማወራረድና በጐደለ ለመሙላት የተለያዩ ፍራፍሬዎችን እንዳመሉ ልክክ አድርጐ ቡናና ልዩ ልዩ መጠጦችን ደህና አርጐ በጉሮሮው ያወራርዳል።”
ከፆታ ግንኙነት አንፃር የተለዩ ደራሲዎች በሚወሱበት ንዑስ ርዕስ ሥር ደግሞ አሌክሳንደር ዱማስ ፔሪ ተጠቅሷል፡፡ ዱማስ ፔሪ የአምስት መቶ ዲቃላ ልጆች አባት ነበር፡፡ በቁጥር ልድገመው ይሆን? የ500 ልጆች አባት፡፡
ደራሲና ድርሰት “ሰው ሲሏቸው አፈር፣ አፈር ሲሏቸው ሰው” ናቸውና በተወሰነ ቅንብብ ውስጥ ከትሮ ማስቀመጥ ይከብዳል፡፡ የበዓሉን አቋም ሆነ የፍሩድን ሥነ - ልቦናዊ ግኝት በትክክልነት በህይወታቸው የተረጐሙ ደራሲዎች አይጠፉም፡፡ ከዚህ አንፃር እኔ የማውቀው እንግሊዛዊው ደራሲ ዲ ኤች ላውረንስ ነው፡፡ ላውረንስ የፍሩድን ፅንሰ ሀሳብ ሙሉ በሙሉ ከመቀበሉ የተነሳ “Psychoanalysis” የሚል አንድ የጥናት መፅሐፍ ጽፏል፡፡ ላውረንስ ከመጽሐፉ ያተረፈው ሽሙጥ ብቻ ሆነ እንጂ ሐያሲያን “ሲግመን ፍሩድን ከእንግሊዝኛ ወደ እንግሊዝኛ የተረጐመ” አሉት፡፡
ላውረስ እንደ በዓሉ ሁሉ “ሆድ ሲሞላ ጭንቅላት ባዶ ይሆናል” ያለ ደራሲ ይመስላል፡፡ በሥራው ብቻ ሳይሆን በህይወቱም እንደዚያ ነበር፡፡ እንክብካቤ ያስመመረው፣ ድሎት የጐፈነነው፡፡ ደራሲነቱ በእንክብካቤና በድሎት እየተዳፈነ እንደሆነ የተሰማው ላውረንስ፤ ለቤተሰቡ አራተኛ ልጅ ነው፡፡ የእሱ ታላቅ ወንድም ለእናታቸው ተወዳጅ ልጅ ነበር፡፡ እንክብካቤዋን በፍቅር የሚቀበል። ነገር ግን ባልታሰበ ሁኔታ ድንገት ታሞ፣ ድንገት ሞተ፡፡ ላውረንስ ወንድሙ ላይ አርፎ የነበረው ያ ሁሉ ፍቅርና እንክብካቤ ሲያርፍበት የደራሲነት      “ወገቡ” ተልመጠመጠ፡፡
“በላህ?”
“አዎ”
“ጠጣህ?”
“አዎ”
“እችን ድገምበት”
“በልቼ? ጠጥቼ?”
“እሺ እንዳይበርድህ ደርብ”
ላውረንስ እናቱን ሊዲያ ላውረንስን ጠላት፡፡ እንደውም አንዳንድ መጽሐፍ ላይ እንድትሞትለትና ነፃ እንዲወጣ ተመኘ ይሉታል፡፡ የተመኘው ተሳክቶለት እናቱ ስትሞት አንድም ሀዘን ልቡናውን አልዳሰሰውም፡፡
እስር ቤቱ እንደተሰበረ ቆጠረው እንጂ፡፡ እንዲህ የሚገምቱ ሰዎች ከላውረንስ ልቡና ጋር በተአምር ተማክረው አልነበረም፡፡ ከዚያ በኋላ በፃፈው “Sons and Lovers” ልቦለድ ውስጥ ህይወቱን ስለተረከው እንጂ፡፡
እዚህ ልቦለድ ውስጥ እናቱና ፍቅረኛው የድሎት እስር ቤት የሚሆኑበት ዋና ገፀ - ባህርይ አለ፡፡ በተለይ እናቱ እንድትሞትለት ይመኛል፤ ስትሞት ከማዘን ይልቅ ፈገግ ይላል፡፡ “ያ ገፀባህርይ ላውረንስ ነው” የሚሉ ሃያሲያን አሉ፡፡ የፃፈው ህይወቱን፣ ኑሮውን፣ ምኞቱን ነው…
…ይሆን እንዴ? እንዲያ’ኮ ከሆነ የደራሲ ግርንቢጥነት ተባባሰም አይደል? ተድላው ችግር፤ ችግሩ ተድላው መሆኑም አይደል?

Read 1393 times