Saturday, 18 July 2015 12:01

“ባቡሩ ሲመጣ...” በመጪው አርብ ይመረቃል

Written by 
Rate this item
(4 votes)

በደራሲና ጋዜጠኛ አንተነህ ይግዛው የተጻፈው “ባቡሩ ሲመጣ...” የተሰኘ የአጫጭር ልቦለዶች ስብስብ መጽሐፍ፣ የፊታችን አርብ ከ11፡30 ሰዓት ጀምሮ በኢትዮጵያ ሆቴል በሚከናወን ኪነጥበባዊ ዝግጅት ተመርቆ በገበያ ላይ ይውላል፡፡
የደራሲው ሁለተኛ ስራ የሆነው “ባቡሩ ሲመጣ...”  በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ዙሪያ የሚያጠነጥኑ 14 አጫጭር ልቦለዶችን በ210 ገጾች አካትቶ የያዘ ሲሆን፣ የመሸጫ ዋጋውም ለአገር ውስጥ 60 ብር፣ ለውጭ አገራት ደግሞ 16 ዶላር እንደሆነ ደራሲና ጋዜጠኛ አንተነህ በተለይ ለአዲስ አድማስ ገልጿል፡፡
ጋዜጠኛና ደራሲ አንተነህ ይግዛው፣ የመጀመሪያ ስራው የሆነውን “መልስ አዳኝ” የተሰኘ የአጫጭር ልቦለዶች ስብስብ መጽሃፍ በ2003 ዓ.ም ለንባብ ያበቃ ሲሆን፤ በቅርቡም የወጎች ስብስብ መጽሃፍ ለህትመት እንደሚያበቃና በአንድ ታዋቂ ኢትዮጵያዊ የቢዝነስ ሰው የህይወት ታሪክ ዙሪያ የሚያጠነጥን መጽሐፍ እያዘጋጀ እንደሚገኝም ገልጿል፡፡
አንተነህ ይግዛው፣ ከሁለት አመታት በፊት በፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን በኩል ለአንድ አመት ከአራት ወራት የተላለፈውን “ስውር መንገደኞች” የተሰኘ ተወዳጅ ሳምንታዊ የሬዲዮ ድራማ በደራሲነትና በተዋናይነት ለአድማጭ ማቅረቡም ይታወሳል፡፡

Read 3654 times