Saturday, 19 September 2015 09:13

የቻይናው ኩባንያ የባቡር ሃይል አቅርቦቱን አስተማማኝ አደርጋለሁ አለ

Written by 
Rate this item
(2 votes)

ባቡሩ ነገ ማለዳ ስራውን ይጀምራል
   በነገው ዕለት ስራ ለሚጀምረው የአዲስ አበባ የቀላል ባቡር ፕሮጀክት የሃይል አቅርቦት የማሟላት ሃላፊነቱን የወሰደው “ቻይና ኤሌክትሪክ ፓዎር ኢኩፒመንት ኤንድ ቴክኖሎጂ” የተባለው ኩባንያ የሃይል አቅርቦቱን ያልተቆራረጠና አስተማማኝ አደርጋለሁ ሲል ቃል መግባቱን ዥንዋ ዘገበ፡፡
የኩባንያው ምክትል ጄኔራል ማናጀር ቼን ዊ፤ ኩባንያው በአዲስ አበባ ከተማ በሚገኙ አምስት ቦታዎች የገነባቸውን የቀላል ባቡሩ የኤሌክትሪክ ሃይል ማስተላለፊያ ንኡስ ጣቢያዎች ባስጎበኙበት ወቅት እንዳሉት፣ ምንም እንኳን ኩባንያው የጊዜ መጣበብና በአገር ውስጥ ገበያ የቁሳቁስ አቅርቦት እጥረት ቢያጋጥመውም ንኡስ ጣቢያዎቹን በወቅቱ ገንብቶ የጨረሰ ሲሆን፣ የባቡር ኤሌክትሪክ ሃይል አቅርቦቱን አስተማማኝ ለማድረግ በቻለው አቅም ሁሉ መዘጋጀቱን ገልጸዋል፡፡ቻይና ኤሌክትሪክ ፓዎር ኢኩፒመንት ኤንድ ቴክኖሎጂ ኩባንያ በአዲስ አበባ ያስገነባቸው የቀላል ባቡር የኤሌክትሪክ ሃይል ማስተላለፊያ ንኡስ ጣቢያዎች አምስት ሲሆኑ በቃሊቲ፣ አያት፣ ሚኒልክ፣ መስቀል አደባባይ፣ እግዚያብሄርአብ ቤተ ክርስቲያንና በጦር ሃይሎች አካባቢ እንደሚገኙ ለማወቅ ተችሏል፡፡ በሌላ በኩል ተሳፋሪዎች በጉዞ ወቅት እስከ 10 ኪሎ የሚመዝን እቃ ብቻ ይዘው ለመጓዝ እንደሚፈቀድላቸው የተገለፀ ሲሆን አንዳንድ በባቡሩ ላይ እንዳይጫኑ የሚከለከሉ እቃዎች እንደሚኖሩ ታውቋል፡፡
የባቡር ትራንስፖርቱ ክፍያ እስከ 4 ኪሎ ሜትር ሁለት ብር፣ እስከ 8.8 ኪሎ ሜትር 4 ብር እንዲሁም ከመነሻ እስከ መጨረሻ ፌርማታ 6 ብር ነው ተብሏል፡፡ ትኬት ሳይዙ መጓዝ ከፍተኛ ቅጣት እንዳለውም ተጠቁሟል፡፡

Read 4328 times