Saturday, 07 November 2015 09:19

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝን እንዳንጠይቅ ተከለከልን ሲሉ ቤተሰቦቹ አመለከቱ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(13 votes)

የሰብአዊ መብት ኮሚሽን ችግራቸውን እንዲፈታላቸው ጠይቀዋል

       በእስር ላይ የሚገኘውን ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ላለፉት 20 ቀናት መጠየቅና ማግኘት እንዳልቻሉ የጠቆሙት ቤተሰቦቹ፤ የጤንነቱ ጉዳይ እንዳሳሰባቸው በመግለፅ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ለችግራቸው እልባት እንዲሰጣቸው በደብዳቤ አመለከቱ፡፡
የጋዜጠኛው ቤተሰቦች በደብዳቤያቸው እንደገለፁት፤ ከጥቅምት 7 ቀን 2008 ዓ.ም ጀምሮ  ምክንያቱን ባላወቁት ሁኔታ ተመስገን በሚገኝበት ዝዋይ ማረሚያ ቤት ቤተሰብም ሆነ ወዳጅ ዘመድ እንዳይጠይቀው መከልከሉ መላው ቤተሰቡን ስጋት ላይ ጥሎታል፡፡
የጤናው ጉዳይ በእጅጉ ያሳስበናል ያሉት ቤተሰቦቹ፤ በተለይ ቀደም ብሎ የነበረበት ህመም ተባብሶ የግራ ጆሮው መስማት እስከመቸገር እንዳደረሰውና የወገብ ህመሙ እረፍት ነስቶ አላስተኛ እያለው መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
በተደጋጋሚ ወደ ዝዋይ ማረሚያ ቤት ቢመላለስም ተመስገንን ማግኘት እንዳልቻለ የሚናገረው የተመስገን ታናሽ ወንድም ታሪኩ ደሳለኝ፤ የማረሚያ ቤቱ ጥበቃዎች “ለምን መጠየቅ ተከለከልን?” ስንላቸው፤ “የበላይ ትዕዛዝ ነው” ይሉናል፤ ብሏል፡፡ በዚህም የተነሳ ተመስገንን ላለፉት 20 ቀናት እንዳላዩትና ቤተሰቡንም ለጭንቀት እንደዳረገ ይገልፃል፡፡
“የቤተሰባችን አባል በሆነው ተመስገን ላይ በተለየ ሁኔታ ተደጋጋሚ የህግ ጥሰት እየደረሰ ነው” ያሉት ቤተሰቦቹ፤ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ከዚህ ቀደም እንዳደረገው ጣልቃ በመግባት ችግሩን እንዲፈታላቸው ጠይቀዋል፡፡
ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ቀድሞ ይሠራበት በነበረው “ፍትህ” ጋዜጣ ላይ በወጡ ጽሑፎች ምክንያት፣ ተከሶ የ3 አመት እስራት ተፈርዶበት፣ ማረሚያ ቤት እንደሚገኝ ይታወቃል፡፡ 

Read 3864 times