Saturday, 12 December 2015 10:21

በድርቁ ሳቢያ በሞያሌ ከተማ የአተት ወረርሽኝ ተቀስቅሷል

Written by  መታሰቢያ ካሳዬ እና አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(3 votes)

      ከድርቁ ጋር በተያያዘ የኢትዮጵያና የኬንያ አዋሳኝ ከተማ በሆነችው ሞያሌ ከተማ፣ የአተት ወረርሽኝ ተከስቶ የአንድ ሰው ህይወት ሲያልፍ ወደ 90 ገደማ የሚሆኑ በበሽታው ተይዘው ህክምና እየተደረገላቸው መሆኑን የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ለአዲስ አድማስ አስታውቋል፡፡
በከተማው በአጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት (አተት) ተይዘው በጤና ተቋማት የታከሙት 91 ያህል ሲሆኑ 71 ህክምናቸውን ተከታትለው ወደ ቤታቸው ሲመለሱ፣ 18 ደግሞ እስከ ትናንት በስቲያ ድረስ ህክምና ሲወስዱ ነበር ተብሏል፡፡
እስከ ትላንት በስቲያ ወረርሽኙ ከሞያሌ ከተማ እንዳይወጣ የህክምና ርብርብ እየተደረገ እንደነበር የጠቆሙት በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ኃላፊው አቶ አህመድ አማኖ፤ ከተማዋ የንግድ ከተማ እንደመሆኗ የተጠቂዎች ቁጥር ሊቀንስም ሊጨምርም የሚችልበት ሁኔታ እንዳለ ገልፀው ጤና ጥበቃ የበሽታውን ስርጭት ለመቆጣጠር ሰፊ ርብርብ እያደረገ መሆኑን ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡
በድርቁ ምክንያት የውሃ እጥረት መከሰቱን ተከትሎ የንፅህና ጉድለት ስለሚፈጠር በቫይረስና በባክቴሪያ የሚፈጠሩ በሽታዎች በድርቁ ተጎጂ አካባቢዎች ሊቀሰቀሱ እንደሚችሉ የጠቀሱት አቶ አህመድ፤ እስካሁን መሰል ችግር ከሌሎች የድርቅ ተጎጂ አካባቢዎች ሪፖርት አለመደረጉንና መንግስት የሚከሰቱ ወረርሽኞችን ለመከላከል በዘረጋው የጤና ኤክስቴንሽን መርሃ ግብር ፕሮግራሙ ለመቆጣጠር እንቅስቃሴ እያደረጉ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡
የዓለም የጤና ድርጅት ሰሞኑን ባወጣው ሪፖርቱ፤ በተለይ ወቅቱን ባልጠበቀ ዝናብ የሚፈጠር ጎርፍ በኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች ውሃ ወለድ በሽታዎችን ሊያስከትል እንደሚችል ጠቁሞ ድርጅቱ ችግሩን ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር በጋራ ለመቋቋም ባለሙያዎችን ወደ ኢትዮጵያ ልኮ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን አስታውቋል፡፡
ከድርቁ ጋር ተያይዞም ከ400 ሺህ በላይ ህፃናትና ከ700 ሺህ በላይ እናቶች የተመጣጠነ ምግብ እንዲያገኙ በማድረግ ለወረርሽኝ ያላቸውን ተጋላጭነት መቀነስ እንደሚገባም የዓለም ጤና ድርጅት አሳስቧል፡፡ በተለይ ህፃናት የተመጣጠነ ምግብ ካላገኙና የጤና ክትትል ካልተደረገላቸው አደጋው የከፋ ይሆናል ያለው ድርጅቱ፤ አሁን ባለው ሁኔታ የተቀናጀ የጤና አገልግሎት ለማቅረብ ሀገሪቱ በቂ አቅም የላትም ብሏል በሪፖርቱ፡፡ ይሁን እንጂ የኢትዮጵያ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ችግሩን ለመፍታት ጥረት እያደረገ ነው ያለው ይኸው ሪፖርት፤ የተለያዩ የአለማቀፍ ድርቶችን ድጋፍ እንደሚሻም አስታውቋል፡፡
በአጠቃላይ ድርቁና የኢሊኖ ክስተት ባስከተለው ችግር ምክንያት የሚፈጠርን የጤና መታወክ ለመከላከል 8 ሚሊዮን ዶላር እንደሚያስፈልግ ተጠቅሷል፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥት ለጉዳዩ የበለጠ ትኩረት እንዲሰጥም የዓለም ጤና ድርጅት አሳስቧል።
ሰሞኑን መንግሥትና የአለማቀፍ ተቋማት የድርቁን ሁኔታ አስመልክቶ ባቀረቡት የዳሰሳዊ ቅኝት ሪፖርት፤ የድርቅ ተጎጂዎች 10.2 ሚሊዮን መድረሳቸው እስከ ቀጣይ አመት ለሚቆየው የድርቅ አደጋ መቋቋሚያም ወደ 30 ቢሊዮን ብር ገደማ በጀት እንደሚያስፈልግ የታወቀ ሲሆን 1.9 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን እህልም ያስፈልጋል ተብሏል፡፡
ድርቁ 189 ወረዳዎችን ክፉኛ የጎዳ ሲሆን በ89 ወረዳዎች ደግሞ መለስተኛ ጉዳት ማድረሱ ተገልጿል፡፡

Read 2115 times