Tuesday, 29 December 2015 07:10

የመብራት መቋረጥ የባቡር አገልግሎቱን እያስተጓጐለ ነው ተባለ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(7 votes)

     የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር ትራንስፖርት በመብራት መቆራረጥ አገልግሎቱ እየተደናቀፈ ሲሆን ተጠቃሚዎች ላይም እንግልት እየፈጠረ ነው ተባለ፡፡
ባለፈው ሣምንት ቅዳሜና እሁድ ለረዥም ሰአታት አገልግሎቱ ተቋርጦ እንደነበር የጠቀሱት ተገልጋዮች፤ ማክሰኞ ዕለትም ተመሳሳይ ችግር ማጋጠሙን ጠቁመዋል፡፡
መብራት ሲጠፋ ባቡሩ ለረዥም ሰዓት ቢቆምም ለምን እንደቆመ ገልፆ ሌላ የትራንስፖርት አማራጭ ተጠቀሙ የሚል አካል እንደሌለ ተገልጋዮች ተናግረዋል፡፡
የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን በበኩሉ፤ የመብራት መቆራረጥ በአገልግሎቱ ላይ እንቅፋት እየሆነበት መምጣቱን ጠቁሞ ችግሩ በዚሁ የሚቀጥል ከሆነ ሌሎች አማራጮችን ለመጠቀም እያጠና እንደሆነ አስታውቋል፡፡
ከአዲስ አበባ ከተማ ውጭ ለብቻው ለባቡሩ የሃይል አቅርቦት መዘጋጀቱን ኮርፖሬሽኑ ጠቁሞ፤ የሃይል መቋረጡ እያጋጠመ ያለው ከምንጩ ነው ብሏል፡፡
ህብረተሰቡ በከፍተኛ መጠን የባቡር ተጠቃሚ እየሆነ በመጣበት ሰዓት በሃይል መቋረጥ አገልግሎት መስተጓጐሉ አግባብ አለመሆኑን የተናገሩት የኮርፖሬሽኑ የህዝብ ግንኙነት ምክትል ሃላፊ፤ ችግሩ ከአቅም በላይ በሆነ ምክንያት የተከሰተ በመሆኑ መፍትሔ እስኪገኝ ህብረተሰቡ  አገልግሎቱን በትዕግስት እንዲጠቀም ጠይቀዋል፡፡

Read 4338 times