የዛምቢያ መንግስት፤ በህገ ወጥ መንገድ የሃገሬን ድንበር ጥሰው ገብተዋል ያላቸውን 77 ስደተኛ ኢትዮጵያውያን ማሰሩን የሀገሪቱ የመገናኛ ብዙሃን ዘግበዋል፡፡
የሀገሪቱ ፖሊስ እንደሚለው፤ በመጀመሪያ የተያዙት 10 ኢትዮጵያውያን መነሻቸውን ከዛምቢያ ዋና ከተማ ሉሳካ በማድረግ በክፍት መኪና ተጭነው ለመውጣት ሲሞክሩ፣ በአካባቢው ሰዎች ጥቆማ የተያዙ ሲሆን በምርመራ ወቅትም ሌሎች 67 ኢትዮጵያውያን በአንዲት ጠባብ ክፍል ውስጥ ታጭቀው እንደሚገኙ በመግለፃቸው በክትትል ተይዘዋል፡፡ ከታሰሩት 77 ኢትዮጵያውያን መካከል 19 ያህሉ ህጋዊ ፓስፖርት እንዳላቸው የገለጸው ፖሊስ፤እንዲያም ሆኖ ሁሉም ወደ ሀገሪቱ የገቡት በህገወጥ መንገድ በመሆኑ በህግ ከመጠየቅ አያመልጡም ብሏል፡፡
ኢትዮጵያውያኑ በሉሳካ ማዕከላዊ እስር ቤት ውስጥ እንደሚገኙ ያስታወቀው ፖሊስ፤በአገሪቱ ህግ መሰረት ፍ/ቤት ቀርበው ተገቢው ቅጣት እንደሚተላለፍባቸው ጠቁሟል፡፡
Monday, 11 January 2016 11:51
የዛምቢያ መንግስት 77 ስደተኛ ኢትዮጵያውያንን አሰረ
Written by አለማየሁ አንበሴ
Published in
ዜና