Saturday, 07 May 2016 13:24

የደራሲ ስብሃት ገ/እግዚአብሔር 80ኛ ዓመት የልደት በአል ተከበረ

Written by 
Rate this item
(2 votes)

በጥበባዊ ዝግጅት የታጀበ ነበር

    የዛሬ ሁለት ዓመት ከዚህ ዓለም በሞት የተለየው የአንጋፋው ደራሲ ስብሃት ገ/እግዚአብሔር 80ኛ ዓመት የልደት በአል በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ድህረ ምረቃ አዳራሽ ከትናንት በስቲያ በድምቀት የተከበረ ሲሆን በእለቱ ደራሲውን የሚዘክሩ ሰፋ ያሉ ኪነጥበባዊ ዝግጅቶች ተካሂደዋል፡፡
“ሌቱም አይነጋልኝ”፣ “ትኩሳት”፣ “7ኛው መልአክ”፣ “5፣6፣7” በተሰኙ ድርሰቶችና አዲስ አድማስን ጨምሮ በበርካታ ጋዜጦችና መፅሄቶች ላይ በመፃፍ የሚታወቀው ደራሲ ስብሃት ገ/እግዚአብሔርን የሚዘክረውን ዝግጅት ያስተባበረው ኢጋ ሚዲያና ኮሙኒኬሽን ሲሆን የሃሳቡ አመንጪ አቶ ደምሰው ኃይለሚካኤል ነው ተብሏል፡፡
በዝግጅቱ ላይ ስብሃት ለመጨረሻ ጊዜ ከፃፋቸው “እሴት ያለው ህይወት ኑር” የሚለውን ደራሲ እንዳለጌታ ከበደና ጋዜጠኛ ጌጡ ተመስገን ለታዳሚው አቅርበዋል፡፡ ስብሃት ገ/እግዚአብሔር ከአብዮቱ በፊት ምን ይመስል ነበር የሚለውንና ከወዳጆቹ ጋር ያለውን ግንኙነት የተመለከተ ፅሁፍ ፕ/ር ሽብሩ ተድላ ያቀረቡ ሲሆን ደራሲና ሃያሲ አለማየሁ ገላጋይ በበኩሉ፤ ስብሃት ከአብዮቱ በኋላ ምን ያስብ ነበር የሚለውንና የስብሃት አንዳንድ እውነታዎች በሚል አቅርቧል፡፡
የቀድሞ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህር አቶ መሰረት አበጀ በስብሃት ስራዎች ላይ በተለይ በ“ሰባተኛው መልአክ” ላይ ዳሰሳዊ ፅሁፍ ያቀረቡ ሲሆን አቶ ሄኖክ በሪሁን ደግሞ “5፣6፣7”ን  በመድረክ ላይ ተውኖታል፡፡

Read 1170 times