Saturday, 28 May 2016 15:15

“ለስነ - ስዕል ብሩህ ጊዜ መጥቷል”

Written by 
Rate this item
(0 votes)

(ሰዓሊ ሰይፈ አበበ፣ የኢትዮጵያ ሰዓሊያንና
ቀራፂያን ማህበር ዋና ፀሐፊ)

  በደርግ ስርዓት እኔ ልጅ ነበርኩኝ፤ ሆኖም የደርግ ዘመን ስዕል የሞተበትና በተወሰኑ ሰዎችና በጥቂት ቦታዎች ብቻ ተወስኖ እስትንፋሱ የቆየበት ወቅት ነበር፡፡ እርግጥ በኃይለስላሴ ጊዜ የተከፈተ አቶ አለፈለገ ሠላም የሚባል የስዕል ት/ቤት ነበር፤ ልጅ ሆኜ አባቴ እዛ ልኮኛል፡፡  እኔ በቤተሰብ እውቀትና ስዕል ይወዱ ስለነበር ተላኩ እንጂ ይህን ያህል የተመቻቸ ነገር ኖሮ አልነበረም፡፡ ህብረተሰቡም ለስዕል ትኩረትና አክብሮት ነበረው ለማለት እቸገራለሁ፡፡ “አርፈህ ትምህርትን ተማር” የሚባልበት ጊዜ ነበር፡፡ አርት ት/ቤት ስገባና ኢህአዴግ ሲገባ አንድ ሆነ፡፡ ከግንቦት ሃያ በኋላ በስዕሉ በኩል የመጣው ለውጥ የሚገርም ነው፡፡ ብዙ ጋለሪዎች ተከፈቱ፣ ብዙ እንቅስቃሴ ተጀመረ፡፡ በአሁኑ ወቅት ሰዓሊ ስቱዲዮ ከፎቶ፣ ጋለሪ ከፍቶ ስዕል እየሸጠ የሚኖርበት ጊዜ ነው፡፡ ቱሪስቶች ከውጭ ይመጣሉ፤ በጥሩ ዋጋ ስዕል ይገዛሉ፡፡ ብዙ ጥሩ ጥሩ ነገሮች፤ ምቹ ሁኔታዎች ተፈጥረዋል፡፡ ሰዓሊው በአገር ውስጥም በውጭም የስዕል ኤግዚቢሽኖች የማዘጋጀት፣ ስዕሉን የመሸጥ፣ በስዕል የሚሰማውን የመግለጽ ነፃነት ያገኘው ከግንቦት 20 ወዲህ ነው፡፡ ስርዓቱና አካሄዱ ያመጣው ለውጥ ነው፡፡ እንደምንሰማው ከግንቦት 20 በፊት በነበረው ስርዓት፤ ጥቂት አርት ስኩል የመማር እድል የገጠማቸው ሰዓሊዎች ከተመረቁ በኋላ ሀገር ፍቅር ቴአትር ነው የሚገቡት፡፡ ፖስተር ምናምን ለመስራት ማለት ነው፡፡ እንደ ነጋሽ ወርቁ፣ እነ ጥበበ ተርፋ ያሉ እግዚብሔር የረዳቸው ሰዓሊያን ብቻ… እነ አፈወርቅ ተክሌ ያሉት … በትግል አቆይተውታል፡፡ እነ ገ/ክርስቶስ ደስታም ተሰድደው ህይወታቸውን ያጡበት ጊዜ ነበር፡፡
በአሁኑ ጊዜ እንደ ኤሌያስ ስሜ፣ እነ ዳዊት አበበ፣ ፍቅሩ ገ/ማርያም ያሉ ጐበዝ ጐበዝ ሰዓሊዎች አሉ፡፡ እነ ኤሊያስ ስሜን ብትወስጂ፤ እንደ ኒዮርክ ታይምስና ዋሽንግተን ፖስት ላይ ሽፋን ያገኙ ሰዓሊያን ናቸው ይሄ ግንቦት ሃያ የፈጠረላቸው መልካም አጋጣሚ ነው፡፡ በግንቦት ሃያ፤ ቴክኖሎጂውም አስተሳሰቡም፣ ነፃነቱም አግዞናል፡፡ የኢትዮጵያ ሰዓሊያንና ቀራፂያን ማህበርን መስርተን፤ ህጋዊ ሰውነት አግኝተን እየተንቀሳቀስን ነው፡፡ ይህ ሁሉ የመጣው እንግዲህ በግንቦት 20 ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ በአሁኑ ሰዓት የጐዳና ላይ ስዕል ሁሉ ጀምረናል፡፡ ቦሌ መንገድ ላይ መመልከት ይቻላል፡፡ ይህ ስርዓቱ የሰጠን ነፃነት ነው፤ ስለዚህ ለስዕሉ ኢንዱስትሪ ግንቦት ሃያ በርካታ እድሎችን ፈጥሯል ማለት ይቻላል፡፡    

Read 1152 times