Saturday, 16 July 2016 12:54

የሰሎሞን ፍርድ “አስተሳሰቡ ከሌለ ድርጊቱ አይመጣም”

Written by  ዲ/ን ዳንኤል ክብረት
Rate this item
(19 votes)

   ሦስት ነጋዴዎች ድንገት አንድ ቀን በንጉሥ ሰሎሞን የዘውድ ችሎት ተገኙ፡፡ ሦስቱም ለብዙ ዘመን አብረው ለመነገድ ተማምለው፣ ግመል ጭነው፣ ገንዘብ ቋጥረው፣ ስንቅ አንጠልጥለው፣ ሀገር ጥለው የሄዱ ናቸው፡፡
‹ንጉሥ ሆይ› አለ አንዱ በዙፋኑ ፊት እጅ ነሥቶ፡፡ ‹እኛ አብረን ለመነገድ ተስማምተን መንገድ የጀመርን ጓደኛሞች ነን› አለ፡፡
ሁለተኛውም ነጋዴ ተቀብሎ ‹ቃላችንንም አክብረን ለንግድ ሩቅ ሀገር ስንጓዝ ድንገት የሰንበት በዓል ደረሰብን› ሲል ቀጠለ፡፡
ሦስተኛውም ነጋዴ ‹ሰንበትን አክብረን ለመዋል ስለፈለግንም ድንኳን ከተከልንበት ቦታ ራቅ አድርገን ጉድጓድ ቆፍረን ገንዘባችንን በከረጢት ቀበርነው፡፡ ከመካከላችን ማናችንም ገንዘቡን ተደብቀን ላንወስድ መሐላ ፈጽመን ነበር፡፡ በማግሥቱ ግን ወደ ጉደጓዱ ሄደን ስንቆፍረው ገንዘባችንን አጣነው› አለና አስረዳ፡፡ የመጀመሪያው ነጋዴም አንገቱን ከነቀነቀ በኋላ ‹ንጉሥ ሆይ ጉድጓዱን ስንቆፍርም ሆነ ገንዘቡን ስንደብቅ ሌላ ሰው ያየን የለም፡፡ ከሰረቅነው እኛው ነን፡፡ ነገር ግን ማናችን እንደሰረቅን ልንተማመን አልቻልንም› አለ፡፡
ንጉሥ ሰሎሞን በልቡ ‹መስረቅ የቻለ ሰው መዋሸትና መሐላን ማፍረስ አያቅተውም› ብሎ አሰበና  ነገሩን ቀለል አድርጎ ‹ነገ ተመልሳችሁ ስትመጡ ማን እንደሰረቀው እነግራችኋለሁ› ሲል አሰናበታቸው፡፡
በማግሥቱ ሦስቱ ጓደኛሞች መጡ፡፡ ችሎቱም ተጀመረ፡፡
ንጉሥ ሰሎሞን፤ ‹የእናንተን ጉዳይ ከመመልከቴ በፊት ሦስታችሁም ጠቢባን መሆናችሁን ማወቅ እፈልጋለሁ፡፡ በመሆኑም በሚከተለው ታሪክ ላይ ያላችሁን አስተያየት እንድትሰጡ እፈልጋለሁ፡፡ ነገሩ እንዲህ ነው፡- አንዲት ሴትና አንድ ወንድ ከልጅነታቸው ጀምሮ አብረው እየተማሩና እየተጫወቱ አደጉ፡፡ ወደፊት ትልቅ ሰው ሲሆኑ ተጋብተው አብረው ለመኖር ቃል ተግባቡ፡፡ ከተወሰነ ጊዜ በኋላ የኑሮ መሥመር አለያያቸውና በተለያዩ ቦታዎች መኖርና መሥራት ጀመሩ፡፡ በዚህ መካከልም ሴቷ ቃል ኪዳንዋን ረሳችውና ሌላ ባል አገባች፡፡ ጋብቻው በተፈጸመበት ቀን ማታ የገባቺው ቃል ኪዳን ትዝ አላት፡፡ ደነገጠች፡፡ ነገሩን ለባልዋ ነገረቺው፡፡ ባልዋም ለቃል ኪዳን ትልቅ ቦታ የነበረው ሰው ነበርና ‹በይ ተነሺ ቃል የገባሺለትን ሰው እንፈልገው፤ ስናገኘውም ቃል ኪዳኑን ማፍረሳችንን ነግረነው፣ የገንዘብ ካሣም ከፍለነው ይቅርታ ያድርግልን፡፡ ያለበለዚያ ትዳራችን ይበላሻል› አላት፡፡
ሁለቱ አዲስ ተጋቢዎች ልጁ ይገኝበታል ወደሚባለው ቦታ ሩቅ መንገድ ተጉዘው አገኙት፡፡ የሆኑትንም ነገር ሁሉ ገለጡለት፡፡ ይቅርታ እንዲያደርግላቸው፣ ገንዘቡን እንዲቀበላቸው ለመኑት፡፡ ልጁ ቀና ሰው ስለነበር ይቅርታ አደረገላቸው፡፡ ‹ያልሠራሁበትን ገንዘብ አልቀበልም› ብሎ ገንዘቡን ለመቀበል ፈቃደኛ አልሆነም፡፡ እነርሱም አመስግነውት ተመለሱ፡፡ ሲመለሱ በመንገድ ላይ አንድ ዘራፊ አጋጠማቸውና የያዙትን ገንዘብ ነጠቃቸው፡፡ ልጂቱም ገንዘቡ በምን ምክንያት እንደተያዘ ታሪኩን እያለቀሰች ለዘራፊው ነገረቺውና እንዲመልስላቸው ለመነቺው፡፡ ዘራፊውም በታሪኩ ተደንቆ የወሰደውን ገንዘብ መለሰላቸው፡፡
ንጉሥ ሰሎሞን ይህን ታሪክ ከተረከ በኋላ ‹ከባልየው፣ ከሚስቱ፣ ከቀድሞ ወዳጇና ከዘራፊው የትኛው ሰው የበለጠ ምስጋና ይገባዋል ብላችሁ ታስባላችሁ?› ሲል ጠየቃቸው፡፡
የመጀመሪያው ነጋዴም፤ ‹ለእኔ የበለጠ ምስጋና የሚገባት ሴቲቱ ናት፡፡ ቃል ኪዳንዋን አስታውሳ፣ ይቅርታ ለመጠየቅ መነሣቷ ያስመሰግናታል› ሲል ሐሳቡን ሰጠ፡፡
ሁለተኛው ነጋዴም፤ ‹ለእኔ ግን የበለጠ ምስጋና የሚገባው ባልዋ ነው፡፡ ምክንያቱም ሚስቱ ቃል ኪዳንዋን ማፍረሷን ስትነግረው ቃልዋን ተቀብሎ፣ ቤት ንብረቱን ትቶ፣ ገንዘቡን ይዞ ወደ እጮኛዋ ዘንድ መሄዱና ይቅርታ መጠየቁ ያስመሰግነዋል› ሲል አስተያየቱን ሰጠ፡፡
ሦስተኛውም ነጋዴ፤ ‹ባልና ሚስቱ ያደረጉት ነገር የሚገርምና የሚያስመሰግን ነው፤ ነገር ግን የቀድሞ እጮኛዋ ሞኝ ሰው ነው፤ ገንዘቡን መቀበል ነበረበት› ሲል ሐሳቡን ለገሰ፡፡
ንጉሥ ሰሎሞንም ሐሳባቸውን ከሰማ በኋላ ሦስተኛውን ነጋዴ፤ ‹ገንዘቡን የሰረቅከው አንተ ነህ› አለው፡፡ ሰውዬውም ደነገጠና ወደ ንጉሡ ተመለከተ፡፡ ንጉሥ ሰሎሞንም ‹ያልደከመበትን ገንዘብ የሚመኝ አእምሮ ባይኖርህ ኖሮ፤ ያንን ልጅ ሞኝ አትለውም ነበር፡፡ አስተሳሰቡ ከሌለ ድርጊቱ አይመጣም፡፡ አንተ ውስጥ ተጣምሞ የበቀለ ነገር አለ፡፡ ሁለቱ ጓደኞችህ ታማኝነትን ዋጋ ሰጥተውታል፤ አንተ ግን ለታማኝነት ዋጋ አልሰጠኸውም፡፡ ስለዚህ ካንተ በቀር ይህን ሊያደርግ የሚችል ሰው የለም፡፡
የአንተን አእምሮ ሳየው የተሠራበትን ነገር አየሁት፡፡ አእምሮ ሲሰጠን ተሠርቶ አልተሰጠንም፡፡ እንዲሠራ ተሰጠን እንጂ፡፡ ሰው በርስቱ ላይ እንዴት ያለ ቤት እንደሚሠራ መወሰንና ቤቱን መገንባት የእርሱ ድርሻ ነው፡፡ የሚጠቀመው ዕቃ፣ የሚገነባበትም መንገድ የቤቱን ጥንካሬ ይወስነዋል፡፡ አእምሮም እንዲሁ ነው፡፡ በሕግ፣ በምግባር፣ በትምህርት፣ በጥበብ፣ የተገነባ አእምሮ ያንተን ዓይነት አስተሳሰብ አይኖረውም፡፡ አሁን የሰጠኽው ሐሳብ ያሳለፍከውን ሕይወት፣ የተዘራብህን ዘርና የተሠራህበትን ነገር አሳይቶኛል፡፡ ወላጆችህን አየኋቸው፤ ጓደኞችህን አየኋቸው፣ መምህሮችህን አየኋቸው፡፡ እነዚህ ሁሉም ወይም ከእነዚህ አንዱ የዘራብህ ዘር ትክክል አይደለም፡፡ ምናልባትም ይህ ዘር ባንተ ላይ መዘራቱን አታውቀው ይሆናል፡፡ ግን ተዘርቶብሃል፡፡
‹አንድ ታሪክ ልንገራችሁ› አላቸው ጠቢቡ ሰሎሞን፡፡ እንዲቀመጡ ተፈቀደላቸው፡፡ ሁሉም ሌባውን ያወቀበት መንገድ አስደንቋቸዋል፡፡ ምንጣፍ ላይ ቁጭ አሉ፡፡
አንድ ቀን አንድ ልጅ እኔ ዘንድ ለፍርድ ቀረበ፡፡ የመጣው አባቱን ገድሎ ነው፡፡ ረበናቱ ሁሉ ‹አባቱን የገደለ ፈጽሞ ይሙት ይላልና ይገደል› ብለው ወሰኑበት፡፡ እኔ ግን ይህንን ነገር ያደረገበትን ምክንያት ለመረዳት ስለፈለግኩ ጠየቅኩት፡፡ ነገሩም እንዲህ ነበር፡፡ አንድ አባት ልጁን ሁል ጊዜ አንድ ነገር ያስተምረዋል፡፡ ጓደኞቼ መቱኝ ሲለው ‹በላቸው› ይለዋል፡፡ ፍየሉ ወጋኝ ሲለው ‹በለው› ይለዋል፡፡ ዕንቅፋት መታኝ ሲለው ‹በለው› ይለዋል፡፡ የአባቱ መፍትሔ ሁልጊዜ ‹በለው› ብቻ ነበር፡፡ ልጁ በዚህ ትምህርት ነበር ያደገው፡፡ አደገ፡፡ ጎለመሰ፡፡ ፈረጠመ፡፡ ያገኘውን ሁሉ እየደበደበ፡፡
አንድ ቀን የአባቱን በጎች ወስዶ አባቱ ሳይፈቅድለት ሸጠና መጣ፡፡ አባቱ ለምን እንደሸጠ ሲጠይቀው ‹ገንዘብ ያስፈልገኛል› አለው፡፡ አባቱ ተናደደና በበጎች መጠበቂያ ጅራፍ መታው፡፡ ያን ጊዜ ልጁ ድንጋይ አንሥቶ፣ እንደ ቃየል አባቱን አናቱን መትቶ ገደለው፡፡ ልጁን ለምን አባቱን እንደገደለ ስጠይቀው፤ ‹አባቴ ያስቸገረኝን ሰው ሁሉ እንድመታ አስተምሮኛል፡፡ አባቴም ስላስቸገረኝ መታሁት፡፡ ለመሆኑ ከመምታት በቀር ምን ማድረግ እችል ነበር?› ሲል ጠየቀኝ፡፡ ይህ ልጅ ሌላ ነገር አልተማረምና ያደረገው የተማረውን ነው፡፡ ሰው የትምህርቱ ውጤት ነውና› አለው፡፡ ሰውዬውም በነገሩ ተገርሞ ገንዘቡን መለሰ ይለናል፤ ሚድራሽ የተባለው የአይሁድ የትውፊት መጽሐፍ፡፡
ይህንን ታሪክ ሳነብ፣ ዛሬ በልጆቻችን ኅሊና እየገነባን ያለነው የዘረኛነትና የጠባብነት፣ የጽንፈኛነትና የአምባገነንነት ጡብ ይታወሰኛል፡፡ እያንዳንዳችን ለሌላው ብለን የምናስታጥቃቸው ነገር አፈሙዙ ወደ ራሳችን ሊዞርብን እንደሚችል ያሰብንበት አልመሰለኝም፡፡ የተጣመመ ሐሳብ እየሰጠን፣ የተጣመመ ትውልድ አፍርተን፣ የተስተካከለች ሀገር እንደመመኘታችን ያለ ሞኝነት ከወዴት ይገኛል?

Read 17339 times