Monday, 08 August 2016 05:40

ትናንት በጎንደር በተከሰተ ግጭት የሰው ህይወት አለፈ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(65 votes)

       በጎንደር በፖሊስ ቁጥጥር ስር የዋሉትን የወልቃይት ኮሚቴ አባላት የፍርድ ጉዳይ ለመከታተል ትናንት ፍ/ቤት አካባቢ ተሰብስበው በነበሩ ነዋሪዎችና የፀጥታ ኃይሎች መካከል በተፈጠረ ግጭት የሰዎች ህይወት መጥፋቱን ምንጮች ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡ የወልቃይት ኮሚቴ አባላትን የፍርድ ቤት ውሎ ለመከታተል ጎንደር ፒያሣ አካባቢ በሚገኘው ፍ/ቤት በጠዋቱ በሺዎች የሚቆጠሩ  የከተማዋ ነዋሪዎች ተሰብስበው የነበረ  ሲሆን ፍ/ቤቱ የተጠርጣሪዎቹን ጉዳይ ለነሐሴ 4 ቀን 2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ መስጠቱ እንደተሰማ ግርግር መፈጠሩን ምንጮች አስረድተዋል፡፡ ፖሊስ በአስለቃሽ ጭስ ተቃውሞ የሚያሰሙትን ነዋሪዎች ለመበተን ሙከራ ማድረጉን የጠቆሙት ምንጮች፤ ከቆይታ በኋላ በከተማዋ የተለያዩ አካባቢዎች የመሳሪያ ተኩስ መሰማቱንና ተኩሱ በየአቅጣጫው እስከ አመሻሹ ድረስ መዝለቁን ተናግረዋል፡፡  
የከተማዋ ዋና ዋና መንገዶች በድንጋይ መዘጋጋታቸውንና ወጣቶች በቡድን እየሆኑ ተቃውሞ ሲያሰሙ መዋላቸውንና ከቀኑ 5 ሰዓት ጀምሮ በከተማዋ የትራንስፖርት አገልግሎት ሙሉ ለሙሉ መቋረጡን ምንጮች አስረድተዋል፡፡ በጉዳዩ ላይ የከተማዋን ከንቲባ ለማነጋገር ያደረግነው ጥረት የሞባይል ስልካቸው ዝግ በመሆኑ ሳይሳካልን ቀርቷል፡፡ በግጭቱ የሰዎች ህይወት ማለፉን ምንጮች ቢጠቁሙም ከፖሊስ ለማረጋገጥ አልቻልንም፡፡
ባለፈው እሁድ በከተማዋ መንግስትን የሚቃወም ሰልፍ ተካሂዶ እንደነበር ይታወሳል፡፡

Read 9293 times