Sunday, 07 May 2017 00:00

የቴዲ አፍሮ “ኢትዮጵያ” አልበም እየተቸበቸበ ነው

Written by 
Rate this item
(20 votes)

የድምፃዊ ቴዎድሮስ ካሣሁን (ቴዲ አፍሮ) “ኢትዮጵያ” የተሰኘው 5ኛ ዓልበም ባለፈው ረቡዕ ከ50 ብር እስከ 100 ብር መሸጡ ታውቋል፡፡
አልበሙን በ10 ዶላር ለኢንተርኔት ሽያጭ ያቀረበው “cdbaby” የተሰኘው ድረ ገፅ በበኩሉ፤ የድምፃዊው አልበም የኢትዮጵያን የሙዚቃ አልበም በሽያጭ ክብረ ወሰን የሰበረ መሆኑን አስታውቋል፡፡
በአጠቃላይ በመጀመሪያው ዙር ግማሽ ሚሊዮን የሙዚቃ አልበም ታትሞ መሰራጨቱ የተገለፀ ሲሆን አልበሙ ለሲዲ አዟሪዎች መልካም የገበያ ዕድል እንደፈጠረላቸው ታውቋል፡፡
ቦሌ ድልድይ አካባቢ ረቡዕ ጠዋት 2 ሰዓት ገደማ የድምፃዊውን አልበም ሲሸጥ አግኝተን ያነጋገርነው አዟሪ፤ ቀደም ሲል መፅሃፍ እያዞረ ይሸጥ እንደነበረ ጠቁሞ፤ መደበኛ ስራውን ለጊዜው በመተው የድምፃዊውን አልበም እየሸጠ መሆኑን ገልጿል፡፡ ከማለዳው 11 ሰዓት ጀምሮ እስከ ጠዋቱ 1 ሰዓት ድረስ ከ50 በላይ አልበሞችን እያንዳንዱን በመቶ ብር ሂሳብ መሸጡንም ጠቁሟል፡፡ የተወሰኑ አልበሞችንም በ80 እና በ70 ብር መሸጡን ተናግሯል፡፡
አልበሙን ገዝቶ በታክሲ ውስጥ እያዳመጠ ያገኘነው የታክሲ ሹፌር በበኩሉ፤ ባለፈው ረቡዕ አልበሙ ሊያልቅ ይችላል በሚል ስጋት ጠዋት 12 ሰዓት ላይ አውቶብስ ተራ አካባቢ በ100 ብር መግዛቱን ገልፆ ይህን ያደረገውም ድምፃዊውን ስለሚያደንቀውና ታሪካዊውን አልበም እንዳያጣ በመስጋት መሆኑን ተናግሯል፡፡
“እውነተኛው የኦሮሞ እና አማራ ታሪክ” በተሰኘ አነጋጋሪ መፅሃፋቸው የሚታወቁት ፕ/ር ፍቅሬ ቶሎሣ በፌስቤክ ገፃቸው ባሰፈሩት አስተያየት፤ “ቴዎድሮስ ካሣሁንንና ሙዚቃውን ለምን ህዝብ ይወዳቸዋል?” በሚል ርዕስ ባሰፈሩት ማስታወሻ፤ ሙዚቃዎቹ ባለፉት 25 ዓመታት እንደ ሰደድ እሳት የተዛመተውን ዘረኝነት የሚቃወሙና ኢትዮጵያዊነትን የሚያቀነቅኑ በመሆናቸው ብለዋል።
በርካታ የፌስቡክ ተከታይ ያለው ዘውዳለም ታደሰ በበኩሉ፤ ድምፃዊው “አፄ ቴዎድሮስ” በሚለው ዘፈኑ፤ አፄ ቴዎድሮስን ዳግም እንዳነገሳቸው ፅፏል፡፡ በዚህ ዘፈን ኢትዮጵያዊነት ከፍ ብሎ እንደተሰበከም ገልጿል፡፡ አብዛኞቹ የአርቲስቱ አድናቂዎች ሀገራዊ ይዘት ያላቸውን ሙዚቃዎች እንደወደዷቸው በፌስቡክ ገፃቸው ላይ አስፍረዋል፡፡
ዱከም ኢንዱስትሪ ዞን ውስጥ አዲስ በተቋቋመው “ቆልያ ሲዲና ዲቪዲ አምራች” ድርጅት በተመረተውና በቀላሉ ኮፒ ለማድረግ ያስቸግራል በተባለው ሲዲ የታተመው የቴዲ አፍሮ “ኢትዮጵያ” አልበም ከወጣበት ካለፈው ረቡዕ ጀምሮ በሲዲ ማዞር ስራ ላይ ተሰማርተው የማያውቁ ግለሰቦች ሳይቀሩ ሲዲውን በፍጥነት እየሸጡ መሆኑን በተዘዋወርንባቸው ፒያሳ፣ አራት ኪሎ፣ መርካቶ፣ መስቀል ፍላወርና ካዛንቺስ አካባቢዎች ለማረጋገጥ ችለናል፡፡ አልበሙን ለማከፋፈል ባለፈው ማክሰኞ የክልልና የአዲስ አበባ ነጋዴዎች ረጅም ወረፋ ሲጠብቁ እንደነበር የገለፁት ምንጮቻችን፤ አልበሙን ለማከፋፈል ለምዝገባ ሲመጡ የሚፈልጉትን የሲዲ መጠን ግማሽ ክፍያ በባንክ ቅድሚያ ከከፈሉ በኋላ ለመውሰድ ሲመጡ ደግሞ ሙሉ ክፍያ የከፈሉበትን የባንክ ደረሰኝ ያሳዩ እንደነበር ምንጮቻችን ጨምረው ገልፀዋል፡፡
አልበሙ መውጣት ከነበረበት ሁለት ሳምንት ዘግይቶ መውጣቱ የሚታወቅ ሲሆን ለዚህም ምክንያቱ ሲዲው በተለመደው ከቨር ለገበያ ቢቀርብ ለአየር ብክለት ጉዳት ይጋለጣል በመባሉ አሁን ባለው የካርቶን ከቨር ለመለወጥ ሲባል ሁለት ሳምንት መዘግየቱን የጠቆሙት ምንጮቻችን፤ ይህንንም ስራ በፍጥነት ለመሰራት 200 ያህል ጊዜያዊ ሰራተኞች ተቀጥረው ከቨሩንና ግጥም የተፃፈበትን ቡክሌት ሲያጥፉ እንደቆዩ ምንጮች ገልፀዋል፡፡ 500 ሺህ ከቨርና ቡክሌቱ እያንዳንዱ በአራት አራት ብር የተሰራ ሲሆን የተቀጠሩት ጊዜያዊ ሰራተኞች አንዷን ከቨር ለማጠፍ በ20 ሳንቲም ሂሳብ መስማማታቸውንም ምንጮች ገልፀዋል፡፡ ለከቨሩ እና ለቡክሌቱ ስራ በጠቅላላ ወደ 5 ሚ. ብር መውጣቱም ተገልጿል፡፡

Read 11806 times