በሸገር ኤፍ.ኤም 102.1 የለዛ ፕሮግራም አድማጮች በሚሰጡት ድምፅ መሠረት የዓመቱን ምርጥ የኪነጥበብ ስራዎችና ባለሙያዎች በመለየት ለሚካሄደው ዓመታዊ የሽልማት ስነ-ስርዓት የመጨረሻ ዕጩዎች እንደታወቁ ተገለፀ፡፡ ዘንድሮ ለሁለተኛ ጊዜ ለሚካሄደው የሽልማት ስነስርዓት አድማጮች በYahoonoo.com ድምፅ ሲሰጡ የቆዩ ሲሆን በየዘርፉ ምርጥ ስራዎችና ጥበበኞች ተለይተዋል፡፡ አሸናፊዎቹን ለማወቅም የድምፅ አሰጣጥ ሂደቱ እንደሚቀጥል ታውቋል፡፡ እስካሁን በተሰጠው የአድማጮች ድምፅ በምርጥ አልበም የቴዲ አፍሮ “ጥቁር ሰው”፣ የታደለ ገመቹ “ገዳን ኬኛ”፣ የሀይሌ ሩትስ “ቺጌ”፣ የጃሉድ “የገጠር ልጅ”፣ የግርማ ተፈራ “እኔ አይደለሁም” ተመርጠዋል፡፡ በምርጥ ፊልም “የፍቅር abcd”፣ “ባላገሩ”፣ “ሼፉ”፣ “በልደቴ ቀን”፣ “ሜድ ኢን ቻይና” እና “MISTER X”. ይፎካከራሉ፡፡
በምርጥ ነጠላ ዜማ የጃሉድ “ድግስ”፣ የቤቲና ናቲ “ማን ካንቺ አይበልጥም”፣ የአስቴር አወቀ “ትዝታ”፣ የጐሳዬ “የሠርግ” እና የአስቴር አወቀ “የኔታ” ቀርበዋል፡፡ ምርጥ የሴት ተዋናይት፡- ሳህር አብድልከርም፣ በ”የፍቅር abcd” ማህደር አሰፋ በ”ሼፉ”፣ ኤልሻይዳይ ሳህሉ “በልደቴ ቀን”፣ ማህሌት ሹመቴ በ”ዲፕሎማት” ሮማን በፍቃዱ በ“City boys” ሲፎካከሩ፤ በምርጥ ወንድ ተዋናይ ሚካኤል ሚሊዮን “ሼፉ”፣ ቴዎድሮስ ስዩም በ”ሜድ ኢን ቻይና”፣ ነፃነት ወርቅነህ በ“ሚስተር X”፣ ታሪኩ ብርሃኑ በ“የፍቅር abcd”፣ ሰለሞን ቦጋለ በ“አሜን”፣ ዩንግ ኧ ሊ፣ በ“ሜድ ኢን ቻይና” በእጩነት ቀርበዋል፡፡ አሸናፊው የሚታወቀው የፊታችን መስከረም 12 ቀን 2005 ዓ.ም በእምቢልታ ሲኒማ በሚካሄደው የሽልማት ስነ-ስርዓት ነው፡፡