የኢትዮጵያ ፖስታ አገልግሎት ድርጅት ከኢትዮጵያ ደራስያን ማህበር ጋር በመተባበር ለቀደምት አንጋፋ ደራስያን የመታሰቢያ ቴምብሮች አዘጋጀ፡፡ በአንጋፋው ሠዐሊ እሸቱ ጥሩነህ እና አገኘሁ አዳን ድልነሳሁ የተሳሉት ቴምብሮች የነጋድራስ አፈወርቅ ገብረኢየሱስ፣ የቀኝ ጌታ ዮፍታሔ ንጉሤ፣ የብላቴን ጌታ ሕሩይ ወልደ ሥላሴ እና የአቶ ተመስገን ገብሬ ናቸው፡፡ ቴምብሩ ትናንት ከሰዓት በኋላ የጥበብ ሰዎች፣ የመንግስት ባለሥልጣናት፣ ቴምብሮቹ የታተሙላቸው ቤተሰቦች በተገኙበት በአዲስ አበባ ትያትርና ባህል አዳራሽ የተመረቀ ሲሆን ትናንትናውኑ ለገበያ እንደቀረበ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ድርጅቱና ማህበሩ ካሁን ቀደም በተመሳሳይ መልኩ ለክቡር ዶክተር ስንዱ ገብሩ፣ ለክቡር ዶክተር ሃዲስ አለማየሁ፣ ለባለቅኔ ሎሬት ፀጋዬ ገብረመድህን እና ለክቡር ዶክተር ከበደ ሚካኤል መታሰቢያ ቴምብሮች ማሳተማቸው ይታወቃል፡፡