የተሰበቀ የህይወት ጦር፤
ቄጠማ ሆኖ ሚቀር፤
‹‹በቃኝ!›› ያሉ እለት ነው እታለም፤
‹‹ደከምኩ!›› አትበይ! ግዴለም፡፡
አጥር አልባ ነው ህይወት፣
አጥር አልባ ነው ጎጆ፣
አጥር አልባ ነው አለም፤
አትሄጂበት መንገድ፣
አትከፍቺው በር የለም፤
‹‹በቃኝ!›› አትበይ ግዴለም፡፡
ከወነጨፍሽው ቀስት ፊት፣
ኢላማሽን ለነጠቀ፤
ሕይወት፣ ጎጆ፣
አለምሽን ባሜከላ ለጨፈቀ፤
ህይወትሽን ለህይወቱ እርካብ፣
አድርጎ ለሚመኘው፤
ሞራውን አታንብቢለት፣
ፍጹም ‹‹ደከምኩ!›› አትበዪው፡፡
የሚቧጥጥሽ ቆንጥር፣ የማያሻግርሽ ፈፋ፤
ከጀምበርሽ ጋር በርክቶ፣
ከእድሜሽ ጋር እየፋፋ፤
ቢመስል የማይገፋ፤
ቆንጥርና ፈፋው ነው፣
የተስፋሽ መቅኒ እታለም፤
ያለዚያ ህይወት ይሉት ጣእም፣
ኑሮ ይሉት ገድል የለም፡፡
‹‹በቃኝ!›› አትበይ ግዴለም፡፡
በእናትሽ!
(በድሉ ዋቅጅራ)
Published in
ጥበብ