Monday, 11 September 2023 09:26

“ሱስ የምንከላከለውና ማገገም የሚችል የአንጎል ህመም ነው!”

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

መቋሚያ የማህበረሰብ ልማት ድርጅት፣ በባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ህጋዊ ሰውነት የተሰጠው፤ በአደገኛ እጾች ተጠቃሚነትና ሱሰኝነት ቅድመ መከላከልና የሱስ ህክምና ዙሪያ ከ15 ዓመታት በላይ የሰራ  አገር በቀል ግብረ ሰናይ ድርጅት ነው፡፡
ራዕዩ፡- ከአደገኛ እፅ ተጠቃሚነትና ሱሰኝነት የፀዳ ባለራዕይ ትውልድ በአፍሪካ ላይ ተሰርቶና ተነስቶ ማየት! የሚል ሲሆን ፤ የራዕዩ መነሻ የሆነው የድርጅቱ ፍልስፍናም ‹‹አገር ማለት ሰው ነው፡፡ የዜጎችን አዕምሮ ስንከባከብ ለአገር ልማትና እድገት ያለው አስተዋፅ ትልቅ እንደሆነ ሁሉ፤ የሚጎዱ ነገሮች ደግሞ አገርን አደጋ ላይ የሚጥሉ ስለመሆናቸው ጥርጥር የለውም። ስለዚህ አንጎልን አደጋ ላይ ከሚጥሉ ነገሮች ትውልዱን እየጠበቅን፤ በክብካቤና ማስተማር ላይ እናተኩር..›› የሚል ነው፡፡
ባለፉት አመታት ‹‹ሱስ  የምንከላከለውና ማገገም የሚችል የአንጎል ህመም ነው!›› በሚል አዲስ ማህበረሰባዊ ንቃተ-ህሊናን ለመፍጠር፤ ከመንግስት ጋር ማለትም፤ ከጤና ሚኒስቴር፣ ከኢትዮጵያ የምግብና መድሃኒት ቁጥጥር ባለስልጣን መስሪያ ቤት፣ ከትምህርት ሚኒስቴር፣ ከሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ ከባህል ሚኒስቴር እና ከተለያዩ የሚዲያ ተቋማት፣ ከከፍተኛ የትምህርት ተቋማትና ሌሎች መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት ጋር በመተባበር ሰፊ ስራዎችን ሲሰራ የቆየ ድርጅት ነው፡፡
ከዚህ በተጨማሪም በአድቮኬሲ ስራው በትምባሆና አልኮል ላይ ተጠናክሮ በወጣው ረቂቅ አዋጅ ላይ   ከሚመለከተው መንግስታዊ ተቋምና የግብረ ሰናይ ድርጅቶች ጋር በመተባበር፣ በምክር ቤት የህዝብ ውይይት ጊዜ የተጠናከረ የአቻ ምክረ-ሃሳቦችን  በማቅረብና አዋጁ ተጠናክሮ ከወጣ በኋላም፣ ለተፈፃሚነቱ ከመንግስት ጋር በመተባበር፣ ማህበረሰባዊ ሃላፊነቱን እየተወጣ የቆየ ተቋምም ነው፡፡
በግንዛቤና በቅድመ መከላከል ስራዎቻችን  በርካታ ሚሊዮኖች፣ ‹‹የሱስ ህመም የምንከላከለውና ማገገም የሚችል የአንጎል ህመም ነው!›› የሚለውን መሪ ቃል ሰምተዋል ብለን እናምናለን፡፡ በዚህ እንቅስቃሴያችን በ8 ዩኒቨርስቲዎች ከላይ ከተጠቀሱት የመንግስት ሚኒስቴር መስሪያቤቶች ጋር በመተባበር፣ ዩኒቨርስቲን መሰረት ያደረገ የፀረ - ሱስ ማህበረሰብ ንቅናቄ /University  Based Anti-Addiction Community Movement / መፍጠር  በሚል ዓላማ፣ ከትምባሆ ጭስ ተጋላጭነት የፀዱ ዩኒቨርስቲዎችን ለመፍጠር በስፋት  ሲሰራ ቆይቷል፡፡
ከሱስ የማገገም ህክምና ዙሪያ ከጤና ሚኒስቴርና ከመቀለ ዩኒቨርስቲ ጋር በመተባበር፣ ከ800 መቶ በላይ ለሚሆኑ ፍቃደኛ የሱስ ህመም ታካሚዎች እገዛ ማድረግ ተችሏል፡፡ በዘርፉም በአገር አቀፍ ደረጃ ያለውን የባለሙያ እጥረት ለመቅረፍ ከሱስ የማገገም አማካሪና አሰልጣኞችን ለማፍራት ከጤና ሚኒስቴርና ከአሜሪካ መንግስት ጋር በመተባበር፣ በተለያዩ አገራት ስልጠናዎችን በመውሰድና የተገኘውን ልምድና ተመክሮ  አገር ውስጥ ከተገኘው ልምድ ጋር በመቀመርና ዶክመንቶችን በማዘጋጀት ትልቅ ስራዎችን ሲያከናውን  ቆይቷል፡፡
ካለፉት ሦስት አመታት ወዲህ ደግሞ ከኢትዮጵያ  የምግብና መድኃኒት ባለስልጣንና ከአዲስ አበባ ምግብ፣ መድኃኒትና ጤና ክብካቤ ቢሮ ጋር በመሆን፣ አዲስ አበባን ከትንባሆ ጭስ ነጻ የማድረግ ተነሳሽነት (Addis Ababa Smoke Free Initiative) በሚል መሪ ሀሳብ በመስራት ላይ ይገኛል።
አዲስ አበባን ከትንባሆ ጭስ ተጋላጭነት ነጻ የማድረግ ተነሳሽነት ስራ በአራዳ ክ/ከተማ ውስጥ በ3 ወረዳዎች የጀመረው የፓይለት ስራ  በሂደት በማደግ፣ ሙሉ የአራዳ ክ/ከተማን፤ በኋላም ቂርቆስ ክ/ከተማን ከዚያ ልደታና ጉለሌ ክፍለ ከተሞችን በማካተት ወደ አራት ማሳደግ ተችሏል። በዚህ ስራ ውስጥ የመቋሚያ የማህበረሰብ ልማት ድርጅት ሚና፣ የኢትዮጵያ የምግብ መድሃኒት ባለስልጣንና የአዲስ አበባ ምግብ፣ መድኃኒት፣ ጤና ክብካቤ ቢሮን ማገዝ ሲሆን ፤ ይህን እገዛ እንድናደርግ በአሜሪካ አገር የሚገኘው Campaign For Tobacco Free Kids (CTFK) እያገዘን ይገኛል።
ድርጅታችን በአዲስ አበባ  ከትምባሆ ጪስ ተጋላጪነት የፀዳ አካባቢን ለመፍጠርና ከሌሎች ሱስ የመከላከልና የማገገም ስራ ጋር የተያያዙ ተግባራትን ለማከናወን  ልዩ ‹ፍኖተ ካርታ› አዘጋጅቶ ሲንቀሳቀስ ቆይቷል። ፍኖተ ካርታ ”Full Package” ያለው ሲሆን፣ ይህም አካሄድ ከተማዋን ከትንባሆ ጭስ ነጻ ከማድረግ  እንቅስቃሴ ጎን ለጎን፣ ትምባሆ ተጠቃሚውንና በጭሱ የሚጠቁ ሁለተኛ አጫሾችን ያካተተ ስራ መስራትን የሚከተል አካሄድ ነው ብለን እናምናለን። Full package ስንል የሚከተለውን ማለታችን ነው።
1ኛ- ለማህበረሰቡ ግንዛቤ ፈጣሪ በሆነ መልኩ ሰፊ ስራ መስራት። ስለትምባሆም ሆነ ስለ ሌሎች አደገኛ እፆች ጎጂነት በማስተማርና ቅድመ መከላከል በመፍጠር ማህበረሰብን ሊታደግ የሚችል ስራ መስራት ፤
2ኛ - እስከ አሁን እየተተገበረ ያለውን የአዋጅ ቁጥር 1112/2011 ቁጥጥር የህግ ማስከበር ስራ አጠናክሮ መቀጠል። እንዲሁም የአድቮኬሲ ስራውን በተቀናጀ መንገድ ማስኬድ። እንዲሁም፤
3ኛ- በትምባሆም ይሁን በሌሎች አደገኛ እፆች ሱስ ውስጥ ያሉትን የከተማችን የማህበረሰብ ክፍሎች፣ ከሱሳቸው ለመውጣት ፍቃደኛ ሲሆኑ፣ ህክምና ሊያገኙ የሚችሉበትን ሁኔታ ማመቻቸትና የማገገም ሂደታቸው ስኬታማ እንዲሆን የማገገሚያ ፕሮግራሞችን ማጠናከር።
በተጨማሪም ማህበረሰቡ ከትንባሆ ጭስ ተጋላጭነት የመጠበቅ ሕጋዊና ተፈጥሯዊ መብት እንዳለው እንዲገነዘብ ስለሚፈለግ፣ ማህበረሰቡ “ከትንባሆ ጭስ በጸዳ አካባቢ መኖር ተፈጥሯዊና ህጋዊ መብቴ ነው!” በሚል መሪ ሀሳብ፣ ላለፉት ሁለት አመታትና ከዚያ በላይ ግንዛቤ ሲሰጥበት ቆይቷል፡፡
በአንጻሩም፤ ትልቅ አበረታች ለውጥ ታይቶበታል። ይሁን እንጂ እየተሰራ ያለው ስራ ሰፊ የሚዲያ ሽፋን ተሰጥቶት ለሰፊው ማህበረሰብ ተዳርሷል ብለን አናምንም፡፡ ይህንን ለመቅረፍም ከሚዲያ ተቋማት ጋራ መስራት ወሳኝ መሆኑ ታምኖበታል፡፡
ኤልያስ ካልአዩ
የመቋሚያ የማህበረሰብ ልማት ድርጅት
ኤክስኪዩቲቭ ዳሬክተር

Read 1414 times