Saturday, 09 September 2023 00:00

ባይደን በባለስልጣናት ላይ ያስተላለፉትን ፕሬዚዳንታዊ ትዕዛዝ አራዘሙ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ጆ ባይደን፣ በሰሜን ኢትዮጵያ ያለው የጸጥታ ሁኔታ መሻሻል ባለማሳየቱ ከዚህ ቀደም  በኢትዮጵያና በኤርትራ ባለስልጣናት ወታደራዊና ደህንነት አባላት እንዲሁም በአማራ ክልል  ሃይሎችና በህውሃት አባላት ላይ የተላለፈው ፕሬዚዳንታዊ ትዕዛዝ፣ በአንድ ዓመት እንዲራዘም መወሰናቸው ከሰሞኑ ታውቋል፡፡
 ፕሬዚዳንቱ ከሁለት ዓመት ገደማ በፊት መስከረም 7 ቀን 2014 ዓ.ም. በሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት ላይ ጥሰቶችን ፈጽመዋል በተባሉ ግለሰቦችና ተቋማት ላይ ያነጣጠረ ማዕቀብ መጣል የሚያስችል ፕሬዚዳንታዊ ትዕዛዝ ያስተላለፉ  ሲሆን፤ ፕሬዚዳንታዊ ትዕዛዙ በሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት ተሳታፊ በሆኑት የኢትዮጵያ መንግሥት፣ የኤርትራ መንግሥት፣ የአማራ ክልል አስተዳደርና የህወሓት አባላት ላይ ማዕቀብ መጣል የሚያስችል ነው።
ለኢትዮጵያ ደህንነት ስጋት የፈጠሩ፣ ጦርነቱ እንዲራዘም አስተዋጽኦ ያደረጉ፣ የሰብዓዊ እርዳታ ተደራሽነትን ያደናቀፉ፣ የሰብዓዊ መብት ጥሰት የፈጸሙ፣ ተኩስ አቁም እንዳይደረስ እንቅፋት የሆኑ፣ እንዲሁም ሰላማዊ ሰዎችን ዒላማ ያደረጉና ሌሎች ላይ ማዕቀብ መጣል ያስችላል፤ ፕሬዚዳንታዊ ትዕዛዙ፡፡
ፕሬዚዳንቱ ከትላንት በስቲያ ሐሙስ ጷጉሜ  2 ቀን 2015 ዓ.ም. ባወጡት መግለጫ፤ በሰሜን ኢትዮጵያ አሁንም ያለው ሁኔታ የአገሪቱንና የመላው የአፍሪካ ቀንድን ሰላም፣ ደኅንነትና መረጋጋት ስጋት በመሆን በመቀጠሉ አሜሪካ በቀጠናው ያላትን ብሔራዊ ደኅንነትና የውጭ ፖሊሲ አደጋ ውስጥ የሚከት ነው ብለዋል። በዚህም ሳቢያ ፕሬዚዳንቱ ከዚህ ቀደም የፈረሙትን ፕሬዚዳንታዊ ትዕዛዝ በአንድ ተጨማሪ ዓመት እንዲራዘም መወሰናቸው ታውቋል፡፡  
በሰሜኑ ጦርነት በትግራይ፣ አማራና አፋር ክልሎች በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ከቀያቸው ተፈናቅለው የሰብዓዊ እርዳታ ጠባቂ የሆኑ ሲሆን በጦርነቱ የተሳተፉት የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት፣ የኤርትራ ሠራዊት፣ የአማራ ክልል ኃይሎችና የህወሓት ኃይሎች ከጦር ወንጀል ጋር ሊስተካከል የሚችል የሰብዓዊ መብት ጥሰት ስለመፈጸማቸው የተባበሩት መንግሥታት አስታውቆ ነበር።
ጆ ባይደን ከሁለት ዓመት በፊት በዚህ ፕሬዝዳንታዊ ትዕዛዝ ላይ ፊርማቸውን ማኖራቸውን ተከትሎ፣ የኢትዮጵያ መንግስት አሜሪካ በያዘችው አቋም የተሰማውን  ቅሬታ መግለጹ ይታወሳል፡፡  


Read 1291 times