Saturday, 09 September 2023 00:00

2015 እንዴት አለፈ? ግጭት፣ ጦርነት፣ ቀውስ፣ ሞትና መፈናቀል የነገሰበት ዓመት

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

ሊጠናቀቅ ቀናት የቀሩት 2015 ዓ.ም ለኢትዮጵያውያን እጅግ የከፋ ዓመት ነበር። ዓመቱ በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ግጭት፣ ጦርነት፣ ሞትና መፈናቀል ተባብሶ የቀጠለበት፣ በርካቶች ለብዙ መከራና ሰቆቃ የተዳረጉበት፤ ፈታኝ ዘመን ነበር፡፡
በዚህ ዘገባ በ2015 ዓ.ም በአገራችን በፖለቲካው፣ በኢኮኖሚው፣ በማህበራዊና ሃይማኖታዊ እንዲሁም በኪነጥበቡ ዘርፍ የተከናወኑ አንኳር ጉዳዮች እንዳስሳለን፡፡
በፖለቲካው ዘርፍ
የህውሃት ታጣቂ ሃይሎች በመከላከያ ሃይሉ ላይ ጥቅምት 23 ቀን 2013 ዓ.ም በፈፀሙት ጥቃት ሳቢያ በመንግስት የመከላከያ ሰራዊትና በህውሃት ሃይሎች መካከል የተጀመረው ደም አፋሳሽ ጦርነት እንዲያበቃና የህውሃት ሃይሎችን ትጥቅ ማስፈታት በሚቻልበት ጉዳይ ላይ ሁለቱ አካላት በደቡብ አፍሪካው ፕሪቶሪያ ጥቅምት 23 ቀን 2015 ዓ.ም ከስምምነት ላይ ደረሱ፡፡ በሁለቱ ወገኖች መካከል የተደረሰው ስምምነት ለ2ዓመት የዘለቀውን ጦርነት ለማስቆም ቢችልም ስምምነቱ በአግባቡ ተግባራዊ የተለያዩ የተቃውሞ ድምፆች ሲሰሙ ሰንብተዋል። የስምምነቱ ዋንኛ አካል የሆነው የህውሃት ታጣቂ ሃይሎችን ትጥቅ የማስፈታቱ ተግባር ሲያወዛግብ ቆይቶ ከወራት በኋላ ታጣቂ ሃይሉ ከባድ የጦር መሳሪያዎችን ለመንግስት ማስረከቡ ተገለፀ፡፡ ከዚሁ በማስቀጠልም ክልሉን በጊዜያዊነት ሲያስተዳድር ከነበረው የፌደራል መንግስት ስልጣኑን የሚረከብ አካል ለመምረጥ የህውሃት ማዕከላዊ ኮሚቴ አርብ መጋቢት
8 ቀን 2015 ዓ.ም ባካሄደው ምርጫ፣ አቶ ጌታችው ረዳን የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዚዳንት አድርጎ መረጣቸው። ሆኖም ክልሉን የመምራት ሃላፊነቱ ለአቶ ጌታቸው ረዳ አልጋ ባልጋ አልሆነላቸውም። ርእሰ መስተዳደሩ ከሰሞኑ በሰጡ ጋዜጣዊ መግለጫ፤ ክልሉን በአግባቡ ለማስተዳደር እንዳይችሉ የሚያደርጉ በርካታ ፈተናዎች እንደገጠሟቸው ጠቁመው፤ ከህውሃት አመራሮች መካከል ጊዜያዊ አስተዳደሩ ተቀባይነት እንዳይኖረው ለማድረግ የሚታትሩ መኖራቸውን ይፋ አድርገዋል፡፡ በወረዳዎችና በታችኛው እርከን ያሉ አስተዳደራዊ መዋቅሮች የጊዜያዊ አስተዳደሩ አካል እንዳይሆኑ የተደራጀ ንቅናቄ እንዳለም ተናግረዋል ይህ በእንዲህ እንዳለም በትግይ ክልል የተንሰራፋውን ጭቆናና የአንድ ፓርቲ ስርዓትን እታገላለሁ የሚል “ትንሳኤ 70 እንዳርታ (ትስአፓ)” የተባለ ክልላዊ ፓርቲ መስራች ጉባኤውን በአዲስ አበባ ከተማ አካይዷል፡፡ ፓርቲው በክልሉ “ህብረ ብሔራዊ ስርዓት” እንዲፈጠር እንደሚታገልና ይህ ካልሆነ ግን የራሱን ክልላዊ መንግስትም እንደሚመሰርት አስታውቋል፡፡
ከትግራይ ክልል ሳንወጣ በክልሉ ጳጉሜ 2 ቀን 2015 ዓ.ም የተደረገውና በክልሉ ውስጥ በሚንቀሳቀሱ 3 ተቃዋሚ ፓርቲዎች ተጠርቶ የነበረው ሰላማዊ ሰልፍ በክልሉ የፀጥታ ሃይሎች ተበትኗል፡፡
“የትግይ ህዝብ ስቃይ አላበቃም” በማለት ሰልፍ ወጥተው የነበሩ የትግራይ ክልል ወጣቶች፤ በክልሉ የፀጥታ ሃይሎች እንዲበተኑ መደረጋቸውን ከቀናት በፊት ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
እንደ ሰሜን ሁሉ ደቡባዊው የአገሪቱ ክፍልም በፖለቲካ ውዝግብ በተቃውሞና በግጭት ነበር አመቱን ያሳለፋው፡፡ 2015 ዓ.ም በኢትዮጵያ ህገመንግስት  ከተጠቀሱት ዘጠኝ ክልሎች መካከል የደቡብ ብሄር ብሄረሰቦችና ህዝቦች ክልል ህልውናው በይፋ ያከተመበት አመት ነው፡፡
ለሁለት አስርት አመታት በዚህ ስም ሲጠራ የኖረው ክልል፣ በአራት ክልሎች እንዲዋቀርም ጸደርጓል፡፡ ከክልሉ ቀድሞ የወጣው የሲዳማ ክልል ነበር፡፡ በመቀጠልም የደቡብ ምእራብ ህዝቦች ክልል በተመሳሳይ አዲስ ክልል ሆኖ ተቋቁሟል፡፡ ከጥቂት ሳምንታት በፊት ደግሞ ሶስተኛው ደቡቡ ኢትዮጵያ ክልል የተመሰረተ ሲሆን፤ አራተኛው ማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ሆኖ ተዋቅሯል፡፡ ይሁን እንጂ አዲስ የተመሰረቱት ክልሎች በውስጣቸው የየራሳቸውን ክልል ለማቋቋም ጥያቄ ያቀረቡ የተለያዩ ብሄሮችን የያዙ በመሆናቸው ጉዳዩ ማቆሚያ እንደሌለው የፖለቲካ ምሁራን ይናገራሉ፡፡
አገሪቱ ብሄር ተኮር ፌደራሊዝም እስከተከተለች ድረስ የህብረተሰቡን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ትስስር ከግምት  ውስጥ በማስገባት የክልልነት ጥያቄው አይቀሬ እንደሆነም ይገልጻሉ፡፡
2015 ዓ.ም በአማራ ክልልም በተከሰተው ግጭትና ጦርነት ሳቢያ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ህይወት የጠፋበትና ዓመት ሆኗል። አመቱ በተለይ በአማራ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች በመንግስትና በፋኖ ታጣቂ ሃይሎች መካከል ከፍተኛ ግጭትና ጦርነት ተቀስቅሶ በመቶዎች የሚቆጠሩ ንፁሃንን ለሞት የዳረገ ሆኗል፡፡
በክልሎች ስር ተዋቅረው የሚገኙት ልዩ ሃይሎች እንዲፈርሱና በፌደራል የፀጥታ መዋቅር ውስጥ እንዲካተቱ የተወሰነውን ውሳኔ ተከትሎ፣ ታጣቂዎችን ትጥቅ ለማስፈታት የተደረገውን ሙከራ ባልተቀበሉ ወገኖችና በመንግስት  መካከል  ላለፉት 5 ወራት ከባድ ጦርነት ሲደረግ ቆይቷል፡፡
ግጭቱ የተባባሰው ሚያዝያ 19 ቀን 2015 ዓ.ም የገዥው ብልፅግና ፓርቲ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባልና የአማራ ብልፅግና ፓርቲ ፅ/ቤት ኃላፊ አቶ ግርማ የሺጥላ በታጣቂዎች መገደላቸውን ተከትሎ ነበር፡፡ በሰሜን ሸዋ መሃል ሜዳ የተጀመረው ግጭት ተቀጣጥሎ በአማራ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች በመድረሱ በሰሜን ጎንደር በደብረማርቆስ፣ በፍኖተሰላም በሰሜን ወሎና በሰሜን ሸዋ ዞኖች አንዳንድ አካባቢዎች በመከላከያ ሰራዊትና በታጣቂዎች መካከል ግጭት ተካሂዷል በዚህም በርካታ ንፁሃን ዜጎች ህይወታቸውን አጥተዋል፡፡ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን በከባድ መሳሪያ ጭምር የታገዘ ነው ያለው ግጭትና ጦርነት በሲቪል ሰዎች ላይ የሞት የአካልና የንብረት ጉዳት ደርሷል ብሏል፡፡
በሁለቱ ወገኖች መካከል ተባብሶ በቀጠለው ጦርነት ሳቢያም የትራንስፖርት አገልግሎት ተቋርጦ የቆየ ሲሆን የመንግስት ቢሮዎችም ለአገልግሎት ዝግ ሆነው ሰንብተው ነበር። ክልሉ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ስር እንደሆነ ከተወሰነበት ሐምሌ 28/2015 ዓ.ም ጀምሮ በክልሉ አንፃራዊ መረጋጋት ቢኖርም ዛሬም ድረስ በክልሉ አንዳንድ አካባቢዎች ውጥረት መንገሱንና ዛሬም ድረስ ግጭቶች መኖራቸውን ምንጮች ይገልፃሉ፡፡ ክልሉን እጅግ ለበዛ ችግርና መከራ የዳረገው የሰላም እጦት በቀጣይም አመት እንዳይከተለው ይሰጋል።
አሮጌውን ዓመት በግጭትና በሰላም እጦት ያሳለፉት የአዲስ አበባና ዙሪያዋ አካባቢ ከተሞችም ከግጭትና አለመረጋጋት አላመለጡም። በኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳቱ አቶ ሺመልስ አብዲሳ “በኦሮሚያ ታሪክ ውስጥ አዲስ ምዕራፍ” ነው በተባለለት የሸገር ከተማ ምስረታ ሳቢያ በተቀሰቀሱ ግጭቶች በርካታ ንፁሃን ዜጎች ህይወታቸውን አጥተዋል፡፡
በአዲስ አበባ ዙሪያ ያሉ አምስት ከተሞችን በመያዝ በ12 ክፍለ ከተሞች በኦሮሚያ ክልል ስር የካቲት 19 ቀን 2015 የተመሰረተችው የሸገር ከተማ ለአመታት ጎጆ ቀልሰው ልጆች ወልደው ኑሮአቸውን የመሰረቱ በርካቶችን አፈናቅላለች። የከተማ አስተዳደሩ “ያለ ፕላንና ህጋዊነት ተሰርተዋል” ያላቸውን በሺዎች የሚቆጠሩ ቤቶችንና የእምነት ተቋማትን አፍርሷል። ከዚህ ከከተማው ቤት ፈረሳ ጋር በተያያዘ 100 ሺ አቤቱታዎችን መቀበሉን የህዝብ እንባ ጠባቂ ተቋም ገልጿል፡፡
አስተዳደሩ ህገወጥ ናቸው እያለ ለሚያፈርሳቸው የመኖሪያ ቤቶች ምትክ ቦታ አለመስጠቱንና ለተፈናቃዮችም ጊዜያዊ መጠለያ አለማዘጋጀቱንም ተቋሙ ገልፆ ነበር፡፡ ያለፕላንና ህጋዊነት ተሰርተዋል ተብለው በከተማ አስተዳደሩ 22 መስጊዶችም መፍረሳቸውንም የኢትዮጵያ እስልምና ጠቅላይ ምክር ቤት ሰኔ 1 ቀን 2015 ዓ.ም ባወጣው መግለጫ ላይ ገልጿል።
ሌላው የአመቱ አስገራሚ ክስተት በአገሪቱ ከሚንቀሳቀሱ ተቃዋሚ ፓርቲዎች መካከል ዋንኛ የሚባለው የኢትዮጵያ ዜጎች ለማህበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) የአመራሮችና አባላቱ ከፓርቲው መልቀቅና የፓርቲው መዳከም ነው፡፡ የፓርቲው ሊቀመንበር የነበሩትን አቶ የሺዋስ አሰፋንና ለኢዜማ መሪነት ከፕሮፊሰር ብርሃኑ ነጋ ጋር ተወዳድረው የነበሩትን አቶ አንዱአለም አራጌን ጨምሮ በርካታ የፓርቲው አመራሮችና አባላት ኢዜማን ለቀው መውጣታቸውን ይፋ ያደረጉት በዚህ አመት ሚያዝያ ወር ላይ ነበር ይሁን እንጂ የእነዚህ ጎምቱ የፓርቲው አመራሮችና አባላት ከፓርቲው መልቀቅ ፓርቲውን ለመሰንጠቅ እንደማይዳርገው በቀሪዎቹ የፓርቲው አመራሮች መግለጻቸው ይታወሳል።
በማህበራዊ ጉዳዮች
አብዛኛው በአመቱ ያሳለፍናቸው ማህበራዊ ችግሮች የፖለቲካ ቀውሱን ተከትለው የመጡ ችግሮች ናቸው የሚሉት የፖለቲካ ምሁራን ህዝቡን ለተለያዩ ማህበራዊ ቀውሶች የዳረጉት የመልካም አስተዳደር ችግር፣ ግጭትና መፈናቀሎች እንደሆነ ይገልጻሉ።  ችግሮቹም ፖለቲካዊ መፍትሄዎች የሚሹ መሆናቸውንም ምሁራኑ ይገልጻሉ። ለዜጎች መፈናቀል፣ ስደትና ሞት መነሻ የሚሆኑ ችግሮች በጊዜው መፍትሄ ካላገኙ ማህበራዊ ቀውሶችን ማስከተላቸው አይቀሬ መሆኑን የሚገልፁት የፖለቲካ ምሁሩ አቶ ታረቀኝ ደጀኔ በአገሪቱ በተለያዩ አካባቢዎች የሚደረጉ ህጋዊነትን የማስጠበቅ ህገወጥ ድርጊቶች ዜጎችን ለከፋ ችግር የዳረጉ ናቸው ብለዋል፡፡ በኦሮሚያ ክልል ስር በተመሰረተው አዲሱ የሸገር ከተማ አስተዳደር የተፈፀመው ቤቶችን የማፍረስና ዜጎችን በግዳጅ የማንሳት እርምጃ ለዚህ ጥሩ ማሳያ ነውም ብለዋል፡፡ የቤት ማፍረሱ ተግባር ተገቢ እይታ ያልተደረገበት ህጋዊነትን ያልተከተለ ያለበቂ ማስጠንቀቂያ የተከናወነ አድሏዊ እርምጃ መሆኑንና ይህም ከፍተኛ ማህበራዊ ቀውስ ያስከተለ መሆኑንም ገልፀዋል፡፡
እገታ
ባሳለፍነው አመት በተለይ በማህበራዊ ሚዲያው መነጋገሪያ አጀንዳ ሆነው ከዘለቁ ጉዳዮች መካከል አዲስ አበባ ከተማን ጨምሮ በአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች የሚካሄዱ የእገታ ተግባራት ይገኙበታል፡፡
ይኸው ከቤት ሰራተኞች ጀምሮ እስከ ታጣቂዎች ድረስ ለገንዘብ ሲባል የሚፈፀመው ሰዎችን ማገት በርካቶችን ለማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ምስቅልቅል ዳርጓል፡፡ ታጋቾችን ለማስለቀቅ ከጥቂት ሺ ብሮች ጀምሮ እስከ ሚሊዮኖች ድረስ መክፈል የተለመደ እየሆነ መጥቷል፡፡ ይህ ከጊዜ ወደ ጊዜ ከገጠር አካባቢዎች ወደ ከተሞች አድማሱን ያሰፋው የእገታ ተግባር የሁሉም አካባቢ ህዝብ ዋንኛ የስጋት ምንጭ ሆኖ ከርሟል፡፡ ይሁን እንጂ ስለዚህ አሳሳቢ ጉዳይ የፌደራል መንግስቱም ሆነ ድርጊቱ በተደጋጋሚ የሚፈፀምባቸው ክልል አስተዳዳሪዎች ምንም ያሉት ነገር የለም፡፡
በሃይማኖት ተቋማት ዘርፍ
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ዕውቅናና ከቤተክርስቲያኒቱ ስርዓትና ቀኖና ውጪ ጥር 14/2015 በተደረገ ህገ-ወጥ የጵጵስና ሹመት የተሾሙ 26 ጳጳሳትን ሹመት በመቃወም ቤተክርስቲያኒቱ ባወጣችው መግለጫና ለምህመናኑ ባቀረበችው ጥሪ መሰረት በአገሪቱ ከፍተኛ ተቋውሞ ተቀስቅሶ ነበር፡፡ በዚህ ተቃውሞም በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች ንፁሃን ዜጎች ተገድለዋል ይህንኑ የቤተክርስቲያኒቱን ጥሩ የተቀበሉ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ የእምነቱ ተከታዮች የካቲት 5/2015 ዓ.ም በመስቀል አደባባይ ሊያደርጉ የነበረውን ታላቅ ሰላማዊ የተቃውሞ ሰልፍ በመንግስት ጣልቃገብነት እንዲሰረዝ የተደረገ ሲሆን ህገ-ወጡ የጳጳሳት ሹመትና የሲኖዶስ ምስረታ እንዲታገድም ተደርጓል፡፡
ይህ ችግር በቅጡ ባልተቋጨበት ሁኔታ በቅርቡ ደግሞ በትግራይ ክልል የተቀሰቀሰውን ጦርነት ተከትሎ፣ የትግራይ ቤተክህነት ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ሲኖዶስ ጋር ያለውን ግኑኝነት በማቋረጥ በመንበረ ሰላማ ከሳቴ ብርሃን ቤተክህነትን መመስረቱን አስታውቆ፤ ዘጠኝ ጳጳሳትን ሾሟል፡፡ ይህንን ሹመት ተከትሎም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን “ህገ-ወጥ ነው” ያለውን የጳጳሳት ሹመት ተቃውሞ አውግዟል፡፡ በእነዚህ ተደጋጋሚ የቤተክርስቲያኒቷን ስርዓትና ቀኖና የሚጥሱ ተግባራት ሳቢያ ያሳለፈፍነው አመት የውጥረትና የግጭት ዓመት ሆኖ አልፏል፡፡
ከሸገር ከተማ ምስረታ ጋር በተያያዙ የፈረሱት 22 መስጊዶች ባሳለፍነው አመት በመንግስት የጸጥታ ሃይሎችና በእምነቱ ተከታዮች መካከል ግጭት እንዲቀሰቀስ ምክንያት ከሆኑ ጉዳዮች መካከል ዋንኛው ሆኖ ይገለፃል፡፡ ባለፈው ግንቦት ወር በኦሮሚያ ክልል ሸገር ከተማ ውስጥ ከተከናወነው የመስጊድ ፈረሳ ጋር በተያያዘ ድርጊቱን የተቃወሙ የእስልምና እምነት ተከታዮች በታላቁ አንዋር መስጊድ ተቃውሞአቸውን ባሰሙበት ወቅት ከመንግስት የፀጥታ ሃይሎች ጋር በተቀሰቀሰ ግጭት ንፁሃን መገደላቸው ይታወሳል፡፡ ተቃውሞው በየሳምንቱ ቀጥሎ በርካታ የእምነቱ ተከታዮች ለሞት ለእስርና ለአካል ጉዳት መዳረጋቸውም ተዘግቧል።
ከሁለት ቀናት በኋላ የሚጠናቀቀውን 2015 ዓ.ም ከጦርነትና ግጭት፣ ከሞትና ሰቆቃ ውጭ እንዲታወስ የሚያደርጉ ብቸኛ ምክንያቶች ጀግኖቹ የኢትዮጵያ አትሌቶች ናቸው። አገር በጦርነትና መከራ እየታመሰችም ሰንደቃችን በዓለም አደባባይ ከፍ ብሎ እንዲውለበለብ አድርገውልናል።

Read 1184 times