Saturday, 06 January 2024 21:19

ጃዋር መሃመድ - ትናንት እና ዛሬ

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

ትንታጉ ጋዜጠኛ ደረጀ ኃይሌ ኬንያ ናይሮቢ ተሻግሮ ከቀድሞው አወዛጋቢ አክቲቪስትና ፖለቲከኛ ጃዋር መሃመድ ጋር ያደረገውን ቃለመጠይቅ አርት ቲቪ አቅርቦልናል፡፡ ጋዜጠኛው በቃለ መጠይቁ እንደለፀው ሰሞኑን ያየነው ጃዋር ድሮ የምናውቀው አይደለም፤ ግንፍል ግንፍል የሚለው ጃዋር አልተገኘም፡፡ እንደ ጎረምሳ እምቡር እምቡር የሚለው ጃዋር የለም፡፡ የረጋ - የሰከነ - የሰላ - የበሰለ አዲስ ጃዋር ነው የተዋወቅነው፡፡  ከእስር ከተፈታ በኋላ ድምፁ የጠፋው (ያለበትም ጭምር)  ጃዋር መሃመድ፤ ድንገት ለአገሩ የሚቆረቆር፣ ለህዝቡ የሚያስብና የሚጨነቅ፣ ሰላምን አጥብቆ የሚሰብክ፣ ወቀሳና ትችት ከመሰንዘር ይልቅ ሃሳቦችና ምክሮች ማቅረበ  የሚቀናው ሆኖ ነው ያገኘነው፡፡ በተለይ ደግሞ ጦርነትን ደጋግሞ ሲነቅፍ ሰምተናል (ሁላችንም መንቀፍ አለብን)፡፡ ከግጭት ይልቅ ምክክርን፣ ውይይትን ድርድርን ደጋግሞ መክሯል፡፡
ለኢትዮጵያ ሰላምን - ብልፅግናን - ዲሞክራሲን እኩልነትን ወዘተ (በጎ በጎውን) የሚመኝና የሚሻ ሆኖ ነው ያገኘነው - በጋዜጠኛ ደረጀ ሃይሌ ቃለ መጠይቅ፡፡  
አንዳንዶች “ሲያስመስል” ነው የሚል አስተያየት ቢኖራቸውም፣ ማስረጃ ወይም ማረጋገጫ ግን አያቀርቡም፡፡
 በይፋ ከፖለቲካው ሜዳ መውጣቱን ከተናገረ በኋላ የሚያስመስልበት ምክንያት ብዙም አያሳምንም፡፡ የሆኖ ሆኖ፣ ከዚህ ቃለመጠይቅ ጋር በተያያዘ የደረስኩበትን የጥናት ውጤት የሚመስል ግኝት ልንገራችሁ፡፡ አንደኛ፤ ኢትዮጵያውያን (ከሊቅ እስከ ደቂቅ) ትንሽ በጎ ነገር ካየ ይቅርታ ሳይጠየቁ ይቅርታ የሚያደርግ ጨዋ ህዝብ ነው - በፍጥነት ተበደልኩ የሚለውን የሚረሳ፡፡ ጃዋር ከመታሰሩ በፊት በሚሰጣቸው ቃለመጠይቆችና አስተያየቶች ላይ መሳ ለመሳ ድጋፍና ነቀፌታ የሚጎርፍለት ፖለቲከኛ ነበር፡፡ በአማርኛ በሚሰጣቸው ቃለ መጠይቆች ከድጋፍ ይልቅ ነቀፌታ ይበዛበት ነበር፡፡ ይሄ ደግሞ በአብዛኛው ከራሱ ንግግር ወይም አንደበት አሊያም ሃሳብ ምክንያት ተንኳሽነት የሚመጣ ይመስለኛል ነበር፡፡ እሱና የፖለቲካ ባልደረቦቹ (“የአማራ ኢሊቶች”) የሚሏቸው ላይ በሚሰነዝሯቸው የሚያስቆጡ ፍረጃዎችና አስተያየቶች የተነሳ አያሌ የሚነቅፉትና የሚቃወሙት ቢፈለፈሉ አይደንቅም፡፡ የሆነውም እንደዚያ ነው፡፡ በዚህም የተነሳ ዲጂታል ሚዲያ ላይ እሱ በተናገረ ቁጥር የስድብና ዘለፋ ዶፍ ይወርድበታል (በአብዛኛው ጨዋነት የጎደላቸው)፡፡ ግን ምንም ላይመስለው ይችላል፡፡ አላማው የድጋፍ መሰረቱን ማስደሰት ነው፡፡ እነሱ ያሞግሱታል ሌላው ደግሞ ጭራቅ አድርጎ የእርግማን መዓት ያወርድበታል፡፡
ይሄ ግን በጃዋር ላይ ብቻ የሚከሰት ልዩ ነገር አይደለም፡፡ በሁሉም የኢትዩጵያ ፖለቲከኞች ላይ የተለመደ ነው በተለይ ፅንፈኛ የብሄር ፖለቲካ በሚያራምዱት ላይ ይብሳል፡፡ ባለፈው እሁድ በአርት ቲቪ ቀርቦ ዩቲዩብ የተለቀቀው የጃዋርና የጋዜጠኛ ደረጀ ክፍል አንድ ቃለ መጠይቅው በ24 ሰዓት ውስጥ 1 ሚሊዮን ሰው አይቶታል - እስካሁን በዘፈንም ድራማም ከተመዘገበው ሪከርድ ሳይበልጥ አይቀርም፡፡ እኔን ግን ከተመልካቹም በላይ የገረመኝ ጃዋር የተሰጡት አስተያየቶች ናቸው ኮሜንቶች ዓይነት ነው፡፡ በርካታ አጫጭርም ረዣዥምም አስተያየቶች ሰፍረዋል፡፡ በሚገርም ሁኔታ  አንድም ነቀፌታ፣ ትችት፣ (ቢያንስ እስከ ትላንት በስቲያ) አልገተመኝም ልብ አድርጉ የዘፈን ክሊፕ አይደለም የተለቀቀው ልብ አንጠልጣይ ፊልም ወይም ድራማ አይደለም፡፡ ከቀድሞ አወዛጋቢ ፖለቲከኛ (ደጋፊም ተቃዋሚም መሳ ለመሳ ያለው) ጋር የተደረገ ኢንተርቪው ነው - ወይም ወይይት በሉት፡፡ ሆኖም አድናቆት - ውደሳ - ምስጋና ማበረታቻ ያዘሉ አስተያየቶ ነው እኔን የገጠመኝ፡፡ ይሄ እንዴት ሊሆን ቻለ? ዝርዝር ማብራሪያ ያለው ምላሽ ለመስጠት ጥናት ይፈልጋል፡፡ እኔ ግን የተሰጡትን ኮሜንቶች ደጋግሜ ካነበብኩና በእንግሊዝኞቹን የተፃፉትን ክፍሎቹን ወደ አማርኛ ከመለስኩ በኋላ የደረስኩበት ድምዳሜ ሁለት ነው፡፡
አንድም ቃለ መጠይቁን የተከታተለው ሰው በቀድሞ አወዛጋቢ ፖለቲከኛ ጃዋር ድንገተኛ የባህርይ ለውጥ ደንግጧል - ጨርሶ ያልጠበቀው ሆኖበታል፡፡ አሊያም ደግሞ የጃዋር መረጋጋ - መስከን መብሰል እንዲሁም እነሱንም እንዲቆጠቡ እንዲረጋጉ አድርጓቸዋል፡፡ ከዩቲዩቡ ስር ከሰፈሩ ኮሜንቶች ሶስት ያህሉን ከዚህ በታች አቅርቤላችኋለሁ፡፡ ፖለቲከኛውም ደጋፊውም ከተረጋጋ አገር ትረጋጋለች፡፡
 “ዋው! ቃለመጠይቁ ዕፁብ ድንቅ ነው! የጃዋር ልባዊ የሰላም ጥሪ ከምር ልቤን ነክቶታል፡፡ ጠንካራና ጥልቅ ውይይት ነበር! ጃዋር፤ ስለ ሰላም ስለሰበክኸንና የራስህን አርበኝነት ስላሳየኸን እናመሰግናለን፡፡ ይህ ደግሞ ጠባብ አለመሆንህን ያረጋግጣል፡፡ ጋዜጠኛ ደረጀም ለውይይቱ ጥልቀትና ርቀት ወሳኝ፣ ደፋርና ወቅታዊ ጥያቄዎች በማንሳቱ እኩል ምስጋና ይገባዋል፡፡
“ለውጥ” ተብዬዉ ከመምጣቱ በፊት በኦሮሚያ አብዮት ወቅት፣ ጃዋርን እንደፅንፈኛና ለዚህች አገር እንደ አደጋ ነበር የማስበው፡፡ ሆኖም ወደ ኢትዮጵያ በተመለሰ ጊዜና የፖለቲካ አቋሙን ከፈተሽኩት በኋላ እይታዬ ተቀየረ፡፡ በሰሜኑ ጦርነት ወቅት የሰጠው ቃለመጠይቅ ኹነቶችን በትክክል የመተንበይ ብስለትና የፖለቲካ ልህቀትን አሳይቷል፡፡ ከጦርነቱ በኋላ ጃዋር፣ አስደናቂ እድገት ያሳየ ሲሆን ወደ ብስለትና ብልህነት አድጓል፡፡ ጋዜጠኛ ደረጀ ሃይሌ ግንዛቤ የሚያስጨብጡ ውይይቶች በጥበብ በማሳለጥ የጥራትና ሙያዊ ብቃትን ምንነትን አሳይቷል፡፡ ይህም በሚገባ የተዘጋጀ የተደራጀና ሥነምግባራዊ ጥረት የታከለበት ጋዜጠኝነት ምን እንደሚመስል ያሳያል፡፡ አርት ቲቪ እንደዚህ ያለ የሚበረታታ ፕሮግራም በማቅረብ  ለእንግዶች ጥልቅና ተስማሚ የሆነ መድረክ በማሰናዳቱ እናመሰግናለን፡፡ ቃለ መጠይቁ ግሩም ነበር የጋዜጠኝነት ብቃትን አጉልቶ ያሳየ፡፡ ሁለተኛውን ክፍል በጉጉት እጠብቃለሁ”
“ቃለ መጠይቁ በዩቲዩብ በተለቀቀ በ24 ሰዓት ውስጥ 1ሚ. እይታዎች አግኝቷል፡፡ ይህም ሰውየው (ጃዋርን ማለት ነው) ምን ያህል ተፅዕኖ ፈጣሪ እንደሆነ የሚያመለክት ነው፡፡ ብዙ ጊዜያቸውን ሳይንሱን በማጥናት ያሳለፉ ሃቀኛ ሰዎች ፖለቲካ ሲያወሩ መስማት ደስታ ይሰጣል፤ ቃላቶቻቸው ይማርካል”

Read 1404 times