በአዲስ አበባ ከተማ አዲሱ ገበያ ሸገር መናፈሻ አካባቢ የተገነባውና ከ200 ሚሊዮን ብር በላይ የግንባታ ወጪ ተደርጎበታል የተባለው ናሁሰናይ ኢንተርናሽናል ሆቴል፤ ከነገ ወዲያ ቅዳሜ የካቲት 23 ቀን 2016 ዓ.ም ይመረቃል።
የሆቴሉ ባለቤቶች አቶ እሱባለው ናሁሰናይና ባለቤታቸው ወ/ሮ ሒሩት ምህረቴ እንዲሁም የሆቴሉ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ መላኩ ካሳሁን በጋራ በሰጡት መግለጫ፤ ሆቴሉ ደረጃውን የጠበቀ፣ ምቹ ስፍራ ላይ የተገነባና ለደንበኞቹ የተሟላ አገልግሎት ለመስጠት በሚያስችል መልኩ የተደራጀ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ሆቴሉ 46 የመኝታ ክፍሎች ያሉት ሲሆን፤ እንግዶች ምግባቸውን እዚያው እያበሰሉ የሚመገቡበት የተሟላና የተደራጀ የገስት ሃውስ ክፍሎችንም ያካተተ ነው። አገልግሎቱንም ከአካባቢው አንፃር ተመጣጣኝ በሆነ ዋጋ ለማቅረብ በሚያስችል መልኩ መደራጀቱ ተጠቁሟል፡፡
የሆቴሉ ግንባታ ሦስት ዓመታትን እንደፈጀ የተገለፀ ሲሆን፤ ናሁሰናይ ኢንተርናሽናል ሆቴል ሙሉ በሙሉ ሥራ ሲጀምር ከ70 እስከ 100 ለሚሆኑ ሠራተኞች የሥራ ዕድል እንደሚፈጥር ተነግሯል፡፡
ሆቴሉ ከነገ ወዲያ ቅዳሜ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት እንደሚመረቅ ተገልጿል።
Published in
ንግድና ኢኮኖሚ