Saturday, 20 April 2024 11:07

የብልፅግና ‘የሚዲያ ሠራዊት’ ሐሰተኛ መረጃ በማሰራጨት መሳተፋቸውን ቢቢሲ አረጋገጠ

Written by 
Rate this item
(4 votes)

ብልፅግና “የሚዲያ ሠራዊት” አደረጃጀት የለም ሲል አስተባበለ

በገዢው ብልፅግና ፓርቲ በተለይም በአዲስ አበባ ከተማ ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት ስር የሚንቀሳቀሱና ‘የሚዲያ ሠራዊት’ የሚል ስያሜ የተሰጣቸው የፓርቲው አባላት፤ መንግሥትን በሚተቹና በሚቃወሙ ግለሰቦች

ላይ ሐሰተኛ መረጃ የማሰራጨት ዘመቻ ሥርጫትላይ መሳተፋቸውን   ቢቢሲ ባደረገው ምርመራ ማረጋገጡን አመለከተ።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የወረዳ አመራሮችም በፓርቲው የወረዳ መዋቅሮች ትዕዛዝ በተለይም የመንግሥትን ገፅታ በሰው ሰራሽ መንገድ ለመገንባት ፌስቡክ ላይ በሚደረጉ አሳሳች ዘመቻዎች ላይ እንደሚሳተፉ

የቢቢሲ ምርመራ ያሳያል። ቢቢሲ ለዚህ ምርመራ በአዲስ አበባ ከተማ የወረዳ አመራር፣ የፓርቲ አባል እንዲሁም በከተማዋና በፌደራል መንግሥት መሥሪያ ቤቶች ውስጥ የሚሰሩ የኮሚዩኒኬሽን ኃላፊዎችና

ባለሙያዎች አነጋግሯል።
በተጨማሪም  በአዲስ አበባ ከተማ ሰባት ክፍለ ከተሞች ውስጥ የሚገኙ የፓርቲው የወረዳ መዋቅሮች በዋትስአፕና ቴሌግራም ግሩፖች ውስጥ ለሶሻል ሚዲያ ዘመቻዎች የተለዋወጧቸውን መልዕክቶች ተመልክቷል።

በግሩፖቹ ውስጥ ለወረዳ አመራሮችና ሚዲያ ሠራዊት አባላት የሚሰጡ ትዕዛዞችንና አፈጻጸማቸውን የተከታተለ ሲሆን የፌስቡክ ዳታዎችን በመውሰድም መተንተኑን ይጠቅሳል።
ሜታ (ፌስቡክ) ለቢቢሲ በሰጠው ምላሽ፤ “ሐሰተኛ አካውንቶችን” በመጠቀም “በኢትዮጵያ መንግሥት” የፌስቡክ ልጥፎች ላይ “ብዛት ያላቸው አዎንታዊ አስተያየቶች” መሰጠታቸውን በምርመራ እንደደረሰበት

አስታውቋል። ሜታ፤ በዚህ ድርጊት ላይ በተሳተፉ ሐሰተኛ አካውንት እና ገፆች ላይ እርምጃ መውሰዱን የገለጸ ሲሆን፣ ቢቢሲ ሲከታተላቸው የነበሩ አካውንቶችም እንዲወገዱ ተደርገዋል።
የብልፅግና ፓርቲ በበኩሉ፤ ‘የሚዲያ ሠራዊት’ የሚባል አደረጃጀት “አለመኖሩን” በመግለፅ ለቢቢሲ በሰጠው የፅሁፍ ምላሽ፤ ጉዳዩን አስተባብሏል። የፓርቲው ዋና ፅህፈት ቤት፤ “በተለይ ‘ሐሰተኛ መረጃና የጥላቻ

ንግግር ተብለው ሊቆጠሩ የሚችሉ ጽሑፎችና ምስሎች ተሠራጭተዋል’ በሚል የተገለጸው ፍጹም ተቀባይነት የሌለው አገላለጽ ነው” ብሏል።
የብልፅግና ፓርቲ ‘የሚዲያ ሠራዊት’ አባላት ፌስቡክ ላይ የሚያርጓቸውን ዘመቻዎች በተመለከተ ለሦስት ወራት ያካሄደውን ምርመራ ውጤት በዝርዝር አስነብቧል።
ከሦስት ወራት በፊት ጥር 2 ቀን 2016 ዓ.ም. ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ገደማ ጀምሮ “አቡነ ጴጥሮስ ከሀገር ኮበለሉ” የሚሉ ልጥፎች በበርካታ የኢትዮጵያውያን የፌስቡክ አካውንቶች እና ገጾች መሠራጨት ጀመሩ።
በፎቶና ጽሁፍ ከተቀናበረ ምስል ጋር የተሠራጩት እነዚህ ልጥፎች ፌስቡክ ላይ የወጡት፤ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ሲኖዶስ ዋና ፀሐፊ አቡነ ጴጥሮስ ከአዲስ አበባ ወደ አሜሪካ መጓዛቸውን ተከትሎ

ነበር። የፌስቡክ አካውንትና ገጾች እንደተለጠፈ ቢቢሲ አረጋግጧል። ከግራፊክስ ምስሎች ጋር የተለጠፈው ይህ ጽሁፍ፤ ጥር ሁለት ቀን ብቻ  ቢያንስ 898 ጊዜ ፌስቡክ ላይ ተጋርቷል።
የምስሉ መግለጫ, አቡነ ጴጥሮስ “ኮብልለዋል” በሚል ፌስቡክ ላይ ከተሠራጩት ልጥፎች ውስጥ አብዛኛዎቹ “ፅንፈኝነት_ይውደም” እና “መከላከያ_የሀገር_ጋሻ” የሚል ሀሽታግ ተያይዞባቸዋል ይላል- የቢቢሲ

ምርመራ።
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን “የማኅበራዊ ሚዲያዎች ላይ እየተናፈሰ ያለው ወሬ እጅግ የተሳሳተ” መሆኑን በመጥቀስ፣ ጉዳዩን ያስተባበለችው በማግስቱ ነበር ያለው ቢቢሲ፤ ስለጉዳዩ ጥያቄ የቀረበላቸው

አቡነ ጴጥሮስ፤ አስተያየት መስጠት እንደማይፈልጉ መግለፃቸውን አስታውሷል።
ይህ መረጃ ከተሰራጨ ከአንድ ወር ገደማ በኋላ “ኮብልለዋል” የተባሉት አቡነ ጴጥሮስ ወደ ኢትዮጵያ ቢመለሱም፣ ከአዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ወደ መጡበት እንዲመለሱ መደረጋቸውን

አስታውሷል።
በዕለቱ ስለ ሲኖዶሱ ዋና ፀሐፊ “መኮብለል” ፌስቡክ ላይ የተሠራጩት መረጃዎች፤ በመደበኛ የፌስቡክ ተጠቃሚዎች የተሰራጩ የተለመደው ዓይነት የሐሰተኛ መረጃ አልነበሩም። ቢቢሲ ባደረገው ክትትል፤ የመረጃዎቹ

ሥርጭት ካለፈው ዓመት ጥር ጀምሮ ከቤተክርስቲያኒቱ ጋር ቅራኔ ውስጥ የገባውን መንግሥት ከመሠረተው ገዢው ብልፅግና ፓርቲ ጋር ግንኙት እንዳለው የሚያሳዩ ማስረጃዎችን አግኝቷል። የብልፅግና የሚዲያ

ሠራዊት አባላት በዚህ ዘመቻ እንዲሳተፉ ያደረገው የቂርቆስ ክፍለ ከተማ የወረዳ የፓርቲ መዋቅር ብቻ አልነበረም። በቦሌ ክፍለ ከተማ ውስጥ የሚገኙ የብልፅግና ፓርቲ አባላትም የአቡኑን “መኮብለል” የሚገልጹ

ጽሁፎችና ምሥሎች እንደተላኩላቸው በቦሌ ክፍለ ከተማ የወረዳ አመራር የሆኑ ግለሰብ ለቢቢሲ አረጋግጠዋል።
በወረዳው የፓርቲ ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት አመራር አባላት የዋትስአፕ ግሩፕ ላይ እነዚህ ምሥልና ጽሁፎች የተላኩት፤ “ዘመቻ አድርጉ” ከሚል ትዕዛዝ ጋር መሆኑን ለማወቅ ተችሏል።
“ግሩፑ ላይ የተላከው ጽሁፍ የአቡነ ጴጥሮስን ዜግነት ይገልጽና ‘ከሀገር ወጡ፣ ኮበለሉ’ ይላል። ‘የውጭ ዜግነታቸውን ሽፋን አድርገው የተለያዩ የሐሰት ሰነዶችን በማዘጋጀት ከሀገር በሕገ ወጥ መንገድ ወጥተዋል’

ይላል” ሲሉ፣ በዋትስአፕ ግሩፑ ላይ የተለቀቀው ጽሁፍ በዕለቱ በፌስቡክ ላይ ከተሠራጨው ጋር ተመሳሳይ እንደሆነ ለቢቢሲ አረጋግጠዋል።
የአቡነ ጴጥሮስ ጉዳይ፤ በአዲስ አበባ ከተማ ብልፅግና ፅህፈት ቤት የወረዳ መዋቅሮች አስተባባሪነት የተደረገ ብቸኛው የፌስቡክ ዘመቻ አይደለም ብሏል- በምርመራው ውጤት።
ሆኖም የብልፅግና ፓርቲ ለቢቢሲ በሰጠው ምላሽ፤ “የሚዲያ ሰራዊት” የሚባል አደረጃጀት የለም ሲል ጉዳዩን ሙሉ በሙሉ አስተባብሏል።

Read 849 times