አንድ አፍሪካዊ የዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰር ለብዙ ዓመታት በምዕራብ አገራት ትምህርቱን ሲከታተልና ሲያስተምር ቆይቶ ወደ ትውልድ ቀዬው ይመለሳል፡፡
የትውልድ መንደሩ እንደደረሰም አንድ የመንደር ልጅ ሃይቅ ዳር ቆሞ ይመለከታል፡፡ ልጁ ሰዎችን በታንኳ እያሳፈረ የዕለት ጉርሱን የሚቃርም ነው፡፡ ፕሮፌሰሩ ጀልባው ላይ ተሳፍሮ አፍታ እንኳን ሳይቆይ ልጁን በጥያቄ ያጣድፈው ገባ፡፡
ፕሮፌሰር ፡- ፍልስፍና አንብበሃል?
ልጁ ፡- አላነበብኩም
ፕሮፌሰር ፡- ከንቱ ነህ!
ፕሮፌሰር - ሥነ ልቦናስ አንብበሃል?
ልጁ፡- በፍጹም!
ፕሮፌሰር፡- ውዳቂ ነህ!
ፕሮፌሰር ፡- እሺ ታሪክስ?
ልጁ፡- አላነበብኩም
ፕሮፌሰር፡- ለምንም የማትሆን አልባሌ ሰው ነህ!
ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ አደገኛ ማዕበል ተነሳና ጀልባዋን እንደ ጉድ ይንጣት ጀመር፡፡
ፕሮፌሰሩ በታላቅ ፍርሃት እየራደ ልጁ እንዲረዳው ይጮህ ገባ፡፡ ልጁ ፕሮፌሰሩን በትዝብት እያየው፤ “ፕሮፌሰር፤ ዋና አልተማሩም?” ሲል ጠየቀው፡፡ (አሁን ከንቱው ማነው? በሚል ቅላፄ)

Saturday, 31 January 2015 12:48

ዝብርቅርቅ ጥያቄ

….. (እኔ ላንቺ ማሬ)
አበባ ሞልቶልኝ - ዕድሜዬን ቀጥፌ
ቄጤማ እያለ - እኔኑ አንጥፌ
ወፎች ስላልበቁኝ - ጥርሶቼን አርግፌ .....
እኔ ቀልጬልሽ -
ሜዳ ላይ ፈስሼ - ለፍቅሬ ሳበራ
በገዛ መብራቴ -
ልብሽ ሌላ ‘ያየ - ለግብዣ ከጠራ .....”
.
አይጣልብሽ አንቺው - ያ’ይምሮዬ ነገር
አንቺን እያሰብኩኝ - ትዝ የሚለኝ ሀገር
አሁን የኔን ነገር - ምን ይሉታል ማሬ?
ምን ያገናኝሻል - እስቲ አንቺን ካ’ገሬ?
“…..(እኔማ ላ’ገሬ - )
.
“ሀገሬ ተራራሽ” - እያልኩኝ ዘፍኜ
ያ ቀዳዳነቷን - በአፌ ደፍኜ
እየፆምኩ ስጸልይ - ለሀገሩ ጌታ
ሁሌ እያሰርኩኝ - ሁል ጊዜ ስፈታ ..... ”
.
ግድ የለሽም በቃ -
የምር አብጃለሁ - ሙች ለይቶልኛል
እንዴት “ሀገር” ሳስብ -
እግዜር ከነግርማው - ይደቀንብኛል?
.
“ ….(እግዜር ደ’ሞ እኔን - )
ደካማዋ ነፍሴ - ከእቅፉ ርቃ
ነገር ሲጋጭባት - ሺህ ጊዜ ጠይቃ
እሱ እንደሩቅ ሰው - ዝም - ጭጭ - በቃ
ይህን ጊዜ ነፍሴ - በሃሳቧ ደርቃ ....”
.
ገላጋይ እንቅልፌ - አፋፍሶኝ ይነጉዳል
ያ ባካኙ ልቤም - እንቅልፉን ይወዳል!
.
ማሬ
እኔና እግዜሩ - አንቺና ሀገሬ
ጥያቄዎች ነን - በልቤ ‘ስከዛሬ
ስላ’ንዳችን ሳስብ -
ሌላው ብቅ እያለ - እዛው ላይ ነኝ ዞሬ!!

Published in የግጥም ጥግ

   ሰሞኑን ጌታቸው አበበ የሚባሉ ጸሐፊ የአማርኛ ቋንቋን አስመልክቶ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ በአራት ተከታታይ ክፍሎች ውይይት ሊከፍቱ የሚችሉና ቀላል የማይባሉ ጭብጦችን ለመፈንጠቅ ጥረዋል፡፡ በፊደል ላይ ዘመቻ ይቁም፣ አማርኛ የራሱ ፊደል አለውን?፣ የአማርኛ ፊደል ይሻሻል ማለት ተገቢ ነውን? እና ሌሎችንም ርዕሰ ጉዳዮች በማንሳት በራሳቸው መንገድ የሚሰማቸውን ሀሳብ አጋርተውናል። ምንም እንኳን በአማርኛ ቋንቋና ፊደል ዙሪያ ያሉት አጠቃላይ አመለካከቶች በጋዜጣ፣ በመጽሔቶችና በመጻሕፍት በተለያዩ ሰዎች እየቀረቡ እንደነበር ቢታወቅም፣ እልባት ያላገኙ ጉዳዮች በመኖራቸው አሁንም ሆነ ወደፊት ልዩ ልዩ ሀሳቦች መቅረባቸው ተገቢ ይሆናል። በመሆኑም የጌታቸው አበበን ትጋትና ተቆርቋሪነት በማድነቅ ለጥረታቸው የምሥጋና ዋጋ መስጠት ተገቢ ነው፡፡
በዚህ ዐቢይ በሚባል ርዕሰ ጉዳይ ዙሪያ እኔም የበኩሌን እንደሚከተለው ሰንዝሬአለሁ፡፡ ለማንም አንባቢ ግልጽ የሆነው ጉዳይ “ቋንቋ” እጅግ የተወሳሰበ ትርጉም የሚሰጠው ሳይሆን በሁሉም ዘንድ ግልጽና ቀላል ግንዛቤ እንደሆነ ማስረገጥ ተገቢ መሆኑ ነው፡፡ በመሆኑም “ሰዎች እርስ በርሳቸው ለመግባቢያነት የሚገለገሉበት፤ ሃሳባቸውን፣ ስሜታቸውን የሚገልፁበት፤ ሥርዓት ያለው የድምፆች፣ የቃላት…ጥንቅር፤” የሚለው የአማርኛ መዝገበ ቃላት ትርጓሜ ሁሉንም ያስማማል። የቋንቋ ትርጉም ይህን ያህል ቀላልና በዓለም ሕዝብ በሙሉ ተቀባይነት ያገኘ መሆኑ ከታወቀ በእኔ ሀገር ጓዳና ጐድጓዳ “የችግር መንስዔ” ሆኖ ለምን ይታያል? የሚለው ጥያቄ አስደማሚ ሊሆን ይችላል፡፡ ይህንኑ ዓለም አቀፍ የትርጉም ተቀባይነት አለማመንም አዋቂነትን የሚያላብስ አይመስለኝም። ለማንኛውም የቋንቋ ትርጉም የአገልግሎቱንም መሠረታዊ ድርሻ ከመመልከቱም በላይ ቋንቋ የፍልስፍና አንድ ይዘርፍ አለመሆኑን ያስገነዝባል፡፡ ይልቁን የሕብረተሰብ የተለያዩ ፍልስፍናዎች በቋንቋ መሣሪያነት ይቀመራሉ፡፡ ስለ ቋንቋ በአጭሩ ይህችን ካሰፈርኩ ወደ ዋናው የጽሑፌ ሀሳብ ልሸጋገር፡፡
መቼም ሁላችንም እንደምንገነዘበው አማርኛ ቋንቋችን እንዴት ዘመናትን ተሸጋግሮ ለዚህ ዘመንና አሁን ላለበት ደረጃ እንደበቃ ለማወቅ ካልተፈለገ በስተቀር በድንቁርና አተያይ ጉዳዩ የትናንትና እንደሆነ መቁጠር ቀላል ነው፡፡ ነገሮች ከማንነት ታሪክ ጋር ሲገናዘቡ ደግሞ በዘመናት ሂደት የተጠራቀሙትን ኩነቶች መካድ “እራስን ከመካድና ከማዝቀጥ” ሌላ ምንም ትርፍ የለውም፡፡ በዚህ ረገድ ማንም ሰው መረዳት ያለበት መሠረታዊና ቁልፍ ጉዳይ የአንድ ሀገር ታሪክ፣ ታሪካዊ ቅርሶችና ትውፊቶች፤ የአንድን ሰው ወይም ሕዝብ ማንነት የሚያሳዩ ብቻ ሳይሆኑ የክብርና የልዕልናውንም ደረጃ የሚወስኑ መሆናቸውን ነው፡፡ የአማርኛ ቋንቋን ሥረ - መሠረት በአግባቡ መመርመርና ግልብ ያልሆነ፣ ነገር ግን ዘመንና ትውልድን ተሻጋሪ የሆነ ሀሳብ መሠንዘር መቻል ከጠቀስኩት ሃሳብ ጋር የሚያቆራኝ ይሆናል፡፡
በ1951 ዓ.ም አሥመራ ኮከበ ጽባሕ ማተሚያ ቤት የታተመ፣ የአስረስ የኔሰው መጽሐፍ “የካም መታሰቢያ” ቋንቋና ፊደልን ከታሪክና ከቅርስ በላይም ትርጉም ይሰጠዋል፡፡ “ፊደል መልክ ነው። መልክም ፊደል ነው፡፡ ፊደል ልጅ ነው። ልጅም ፊደል ነው ወዘተ” በዚህ ትርጓሜና አስተሳሰብ ፊደል እራስን መሆኑን ያመለክታል። በመሆኑም ሀገራችን ኢትዮጵያ በዓለም ላይ የፊደልን ሃብትነትና ቅርስነት ከታደሉ ጥቂት (ከአሥር እስከ 12 የሚደርሱ) ሀገራት አንዷ መሆኗን የዚህ ታሪክ ተጋሪ የሆነ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በኩራትና በክብር ምልአት እራሱን መግለጽና ማላቅ ሲገባው ለውርደት ዝቅታን ይመርጣል የሚል እምነት የለኝም፡፡ ፊደሉንና ቋንቋውንም እንደ ራሱ ማየት ያለበት ከዚሁ ዐቢይ ቁምነገር በሚመነጭ ምክንያት ነው፡፡
በዓለማችን ላይ ታሪክ በቋንቋ መገለጽ ወይም መዘከር ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ በእያንዳንዱ አህጉርና አገር ቀጥ ያለና ያለውጣ ውረድ የተቀረፀ ታሪክ መኖሩ ያጠራጥራል፡፡ በየአህጉራቱና በየሀገራቱ የሚኖረው ሕዝብ በተፈጥሮ ወይም በሰው ሠራሽ ችግሮች ሲመሰቃቀልና ከወዲያ ወዲህ ሲዛክር የኖረ መሆኑ በበርካታ የታሪክ ድርሳናት ተዘግቧል፡፡ በዚህም መሀል የሕዝብ ሀብት፣ ቅርስና ታሪኮቹ ጠፍተዋል፣ ተቀብረዋል ወይም ተዳቅለዋል። የአንዱ ሀገርና ሕዝብ ቅርስና ታሪክ ሲጠፋ የሌላው ወገን እየገነነ፣ እንደገናም ገናናው በተራው እየጠፋ ሂደቱ በቀጠለበት ዓለም በማንኛውም ዘርፍ ታሪክ አይዛባም ብሎ ለማመን ይከብዳል፡፡ ጉዳዩ ከግዕዝ ፊደልና ከአማርኛ ቋንቋ አኳያም ሲታይ ሀቁ ከዚህ የሚርቅ አይመስለኝም፡፡ ይህንኑ ለማስረገጥ ይመስለኛል አስረስ የኔሰው ከላይ በጠቀስኩት መጽሐፋቸው ላይ “እስከዛሬ በካም ቤት ከወረደው መንግሥትና ፊደል የንጉሠ ነገሥቱ ስምና ግዕዝ ሳይደመሰሱ በመቆየታቸው የማይቀና የለም፡፡ ከካም ዘመነ መንግሥት ጀምሮ እስከ ዛሬ 4600 ዘመን የቆየውን ታሪክ ሁሉ ለመደምሰስ ታስቦ “በኢትዮጵያ ፊደልን ያመጡ የደቡብ ዓረቦች ግዕዝን አመጡ ያንንም አባ ሰላማ ከካዕብ እስከ ሳብዕ ያሉትን የፊደል ደረጃዎች አሰናዳ፡፡ መጽሐፍተ ብሉያትም በአባ ሰላማ ከጽርዕ ወደ ግዕዝ ተገላበጡ” ይላሉ። መጽሐፍተ ብሉያት ከልደተ ክርስቶስ በፊት በኢትዮጵያ መኖራቸውን ይክዳሉ፡፡” በማለት አብራርተውታል፡፡
በዚህ የታሪክ ግንዛቤ መሠረት በዓለማችን ላይ የካምና የኩሽ ዘመናት በአፍሪካ ልዕለ ኃይል እንደነበሩና በኢኮኖሚና በባሕል እድገትም ቀደምት እንደነበሩ ሲታወስ፣ በዚህም ውስጥ የኢትዮጵያውያን ሚና ከፍተኛ እንደነበር ሲታወቅ፣ የኋላ ኋላ በእምነት ጥግ ከግብፅ ወደ ኢትዮጵያ የመጡትን አባዎች በዚህ የቋንቋና የፊደል ዘርፍ ባለቤት አድርጐ ማሰብ እንዴት ተቀባይነት እንዳገኘ በእጅጉ መመራመርን ይሻል። “የኢትዮጵያን ታላቅነትና ገናናነት” የማይሹት እነማን ነበሩ? ለምን? በመሪጌታ ፈቃዱ መንገሻ የተዘጋጀው “መዝገበ አኃዝ ዘ ኢትዮጵያ” የተሰኘ መጽሐፍ ስለዚሁ ዐቢይ ጉዳይ ፈንጥቋል። “የአንድ አገር ሕዝብ ታላቅነቱና ቀደምትነቱ የሚለካው፤ የሚመዘነው በራሱ ፊደል፣ ቋንቋና በራሱ አኃዝ የተመዘገቡ በዓለም የታወቁ አስደናቂ ቅርሶች ሲኖሩት ብቻ ነው፡፡” በእርግጥ እንዲያ መሆኑ አይጠረጠርም። ይሁንና በሌላ በኩል ደግሞ ለአንድ አገርና ሕዝብ ታላቅነት ወይም ጥንታዊነት የተፃፈ ብቻ ምንጭ ይሆናል ሊባል አይችልም፡፡ የታሪክ ምንጮች በሌላም ማዕዘን ሊገኙ ይችላሉና፡፡
ዶ/ር ዲበኩሉ ዘውዴ የተባሉ ተመራማሪ፤ “ፍትሐ ነገሥት፣ ብሔረ ሕግ ወቀኖና” የተሰኘ የምርምር መጽሐፍ በሚያዘጋጁበት ጊዜ ለሥራቸው በምንጭነት የተጠቀሙባቸው ዘርፎች መልካም ስለመሰሉኝ እኔም አልፎ አልፎ ልፈነጥቃቸው ስላሰብኳቸው መነሻ ሀሳቦቼ በምንጭነት ዋቢ ባደርጋቸው ብዬ አሰብኩ፡፡ የምንጮቹ ዓይነቶች:-
ሰነዳውያን (በሠነድ ወይም በጽሑፍ)
ትውፊታውያን (ከልማድና ከልብ የመነጩ)
አምሳላውያን (በተመሳሳይነት የሚታዩ)
ሥነ - አእምሮአውያን (ልቦና ያስገኛቸው) ናቸው፡፡
እነዚህ ምንጮች ከሞላ ጐደል ለፊደልና ቋንቋችን ጥንታዊነትና የአፍሪካ በተለይም የኢትዮጵያ ስለመሆኑ ለማጣቀስ ይጠቀሙ ይመስለኛል፡፡ በዚህም መሸጋገሪያ ለጽሑፌ ዋነኛ ጉዳይ ወደሆነው ወደፊደላችን አመራለሁ፡
ስለ ፊደላችን አመጣጥና መሠረት ጠንቅቆ ለማወቅ የሰውን አፈጣጠር፣ ዝግመተ ለውጥና በየጊዜው ወደተሻለ የሥልጣኔ ደረጃ የተሸጋገረባቸውን የታሪክ ሂደት አምዶች ለይቶ ማወቅ ይጠይቅ ይመስለኛል፡፡ ታሪክ ሠሪው ሕዝብ እንደመሆኑ በየትኛው አሕጉርና ሕዝብ ምን ዓይነት የእድገት ዝግመተ ለውጥ ተካሄደ? ብሎ መጠየቅም ጠቃሚ ይሆናል፡፡ በእኔ ግንዛቤ ፊደልም ሆነ ቋንቋ የመገኛ ምንጩ አፍሪካ ነው፡፡ እስካሁንም ባሉ መረጃዎች መሠረት የሰው ዘር መገኛ ኢትዮጵያ ስለሆነች የፊደልና ቋንቋም የመጀመሪያ ውልደት እዚሁ ነው፡፡ ከዚያም ከሰው አስተሳሰብ እድገት ጋር በረጅም ዘመናት የዝግመተ ለውጥ ሂደት ለዚህ ደረጃ መድረስ መቻሉን ማመን ይቻላል። ይህን አስተሳሰብ ምናልባትም እንደ እብደት የሚቆጥሩ ወገኖች እንደሚበረክቱ ይገባኛል፡፡ እስከ አሁን ድረስ ስለ ፊደል አፈጣጠር መጠነኛ ምርምር ያደረጉ ምሑራን የፊደል ፈጣሪነትን ለሴማውያን ሰጥተዋል። የአገራችንም ፊደል የተወረሰው ከነዚሁ ባሕር ተሻግረው በመጡ ስደተኛ ሴማውያን እንደመሆነ ያስረዳሉ፡፡ ማስረጃ ሲያቀርቡ ደግሞ ፈረንጆቹ የጻፏቸውን ሐተታዎች ነው፡፡
ዶ/ር ፍቅሬ ዮሴፍ ባዘጋጁት፤ “ብቸኛው አፍሪካዊ ፊደል” በሚል መጽሐፋቸው (ገጽ 15) “ፊደል ለመጀመሪያ ጊዜ በዓለም ላይ የፈለሰፉት ሰመራዊያን የሚባሉ፣ ከአምስት እና ስድስት ሺህ ዓመታት በፊት በዛሬዋ ኢራን አገርና አካባቢ ይኖሩ የነበሩ ሕዝቦች መሆናቸው በፈረንሳይኛ መዝገበ ቃላት ውስጥ ተብራርቶ ይገኛል፣ ወቅቱም በ4ኛው በርኩሜ (ሚሊኒየም) መጨረሻ አካባቢ…” በማለት ይገልፃሉ፡፡
እንደተለመደው ፈረንጆች የፃፉት እንደ ትክክለኛ መረጃ መወሰዱ ላይደንቅ ይችላል። በዚሁ መጽሐፍ ገጽ 16 ደግሞ “ፊደል፤ ለመጀመሪያ ጊዜ የተፈለሰፈው የግብፅን ሒሮግሊፍ (ሥዕላዊ ጽሑፍ) መሠረት በማድረግ ከ1800-1500 ከክርስቶስ ልደት በፊት በሴማውያን እንደሆነ ይነገራል፡፡” በማለት ተጽፏል፡፡
የላቀና የሰከነ ምርምር ቢደረግ ምናልባትም በግብፅ አካባቢ ፊደል ተፈለሰፈ የሚለው ሃሳብ ሚዛን የሚያነሳ ይመስለኛል፡፡ ምክንያቱም ከአባይ ወንዝ መነሻ እስከ መድረሻው ባለው ረጅም ሸለቆ፣ የካምና የኩሽ ሥልጣኔ ከዓለም ማንኛውም ሥልጣኔ በፊት የተንሠራፋና ገናና እንደነበር ስለሚታወቅ ነው፡፡ በዚያን ዘመን ደግሞ በግብጽ የበላይ ገዥዎች ኢትዮጵያውያን እንደነበሩ ማስረጃዎች ማቅረብ ይቻላል፡፡
የሰውን ዝግመተ ዕድገት በመከተልና ዘመናትን ዋቢ በማድረግ የረጅም ሥልጣኔ ባለቤት አፍሪካ እንደሆነች የሚያጠራጥር ጉዳይ አይደለም፡፡ በሰው ዘር መገኛነትም ሆነ በሥነ - ልሳን አጀማመር ወደፊት የሚገኙ ማስረጃዎች የአፍሪካን በተለይም ደግሞ የኢትዮጵያን ክብርና ልዕልና ወደነበረበት ትክክለኛ ቦታው ይመልሱታል፡፡ የአፍሪካም ልሒቃን የፈረንጅን ተረት ተረት እያጣቀሱ ከሚቆዝሙበት ድብርት የሚላቀቁበት ጊዜ ሩቅ እንዳልሆነ መገመት ይቻላል፡፡ በሌላም በኩል ትፊታዊውንንና ሥነ - አእምሮአውያኑን የማስረጃ ፈለግ መከተል የሚቻል ከሆነም የቋንቋም ሆነ የፊደል የልደት ቦታ አፍሪካ እንደሆነ አያጠራጥርም፡፡ በዚህ ሀሳብ ላይ የአስረስ የኔሰውን “የካም መታሰቢያ” መጽሐፍ (ገጽ 2) መጥቀስ ይቻላል፡፡
“መልአኩ ለሙሴ እየነገረው እንደጻፈው ሲመረመር፣ አንድ የነበረው ቋንቋ እስከ ባቢሎን ግምብ እስከ 2827 ዓ.ዓ ነው፡፡ በዚያን ጊዜ በ72 አለቆች ልክ 72 ቋንቋ ተለይቷል፡፡ የኢትዮጵያን ፊደል እናስተካክላለን የሚሉ ከ72ቱ ቋንቋዎች ጀምረው እስካሁን ሳይለወጥ የቆየ ቋንቋ አምጡ ተብለው ቢጠየቁ በቂ መልስ የላቸውም፡፡” ይላል፡
እዚህ ላይ ግዕዝ ቋንቋና የእርሱም ፊደል የመጀመሪያና ሳይለወጥ የቆየ መሆኑን እኚሁ ሊቅ አብራርተዋል፡፡ ግዕዝ የተሰጠው አለቃ ደግሞ ካማዊ እንጂ ሴማዊ አልነበረም፡፡ በዚህ እሳቤ መሠረትም በተለይ በኢትዮጵያ ባጠቃላይም በአፍሪካ የካም ሥረ-ቋንቋዎች ተጠናክረው ወደ ሌሎች አገሮች ተዛምተዋል በሚል አመክኖአዊ ሃሳብ መከራከር ይቻላል፡፡  በእርግጥም ካምና ሴም ወንድማማቾች መሆናቸው እየታወቀና ሊገለገሉበትም የሚገባው ቋንቋ ዝምድና ሊያጠራጥር እንደማይችል እንደማብራራት “ግዕዝ ከሴም ቋንቋዎች አንዱ እንደሆነ” ቀንጭቦ ታሪክን ማዛባት ጠቃሚ አይሆንም፡፡ ይልቁንስ ሴም ከአፍሪካ ወደ ሌላ አህጉር ሲሰደድ የቤተሰቡን ትውፊቶች ይዞ እንደሄደና በሂደትም ዘሮቹ ታሪክና ትውፊቶቹን እንዳሻሻሏቸው መገመት የሚቀል ይመስለኛል። ስለሆነም አሁን አማርኛ የሚጠቀምበት የግዕዝ ፊደል አፈጣጠሩም ሆነ እድገቱ አፍሪካዊ በተለይም ኢትዮጵያዊ መሆኑን ማስረገጥ ይገባል፡፡
በዓለም ላይ በርካታ ቋንቋዎች ይገኛሉ፡፡ የራሳቸው ፊደልና ቋንቋ የታደሉት ግን የጥቂቱ አገራት ሕዝቦች ናቸው፡፡ ከነዚህም ውስጥ አገራችን ኢትዮጵያ አንዷ ነች፡፡ እንዲያውም ለሌሎቹ የፊደል ባለቤት አገሮች ፊደል እንዲቀዱ ምንጭ መሆኗን በድፍረት መናገር ይቻላል፡፡
የራስ ፊደልና ቋንቋ ባለቤት መሆን ማለት በአንደኛው የታሪክና የትውፊት ዘርፍ ልዕለ ሃያል መሆን ማለት ነው፡፡ በመሆኑም ስለ ፊደልም ሆነ ስለ ቋንቋ ሲነሳ “ሀገሬ ኢትዮጵያ በታሪክ የከበረ፣ የጥንታዊ ታሪክ ባለቤትና የሰው ዘር መገኛ፣ መራቢያና የጥንታዊ ሥልጣኔ ማዕከል ነች፡፡ እኔም የዚህች ሃያልና ታላቅ አገር ዜጋ ወይም ልጅ በመሆኔ በዓለማት ፊት ግዙፍ ስብዕና አለኝ፡፡” ብሎ መነሳት ታላቅነት ነው፡፡ በፊደልና በቋንቋ ሳቢያ እዚህና እዚያ የሚነሱ የጓዳ አሉባልታዎች ላይ ከማተኮር አድማስ ተሻጋሪ አስተሳሰቦች ላይ ተከራክሮ አገርንና ሕዝብን ወደነበሩበት ክብርና ልዕልና መልሶ ማስቀመጥ ራስንም ማግዘፍና ማላቅ የተሻለ ነው፡፡
በዓለማችን ዙሪያ ያሉ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ውጤቶች፤ በሀብት፣ በመሳሪያ ጥንካሬና ሌሎችን በመዝረፍ የሚታዩ ታላቅነቶችና ክብሮች በሕዝብ ፊት ሊጠፉ ይችላሉ፡፡ ሕዝብ ራሱ ካልጠፋ የማይጠፋ፣ ዘላቂ የታላቅነትና የማንነት ታሪካዊ ቅርስ ፊደልና ቋንቋ ብቻ መሆኑን በመገንዘብ፣ ራስንም በማወቅ ወደ ላቀ ምርምርና እሳቤ ለመግባት ያስችላል፡፡ በሚቀጥለው ጽሑፌ የግዕዝ ፊደል በአፍሪካ ብቸኛ መሆን አለመሆኑን፣ የፊደል ቅነሳ ወይም እንዳለ መቀጠሉ ስለሚኖረው ፋይዳ፣ ለፊደላችን ስለሚገባው ክብርና ጥበቃ ከአንዳንድ ታሪካዊ ኩነቶች ጋር በመጠኑ በማዛመድ ያለኝን ሃሳብ ለመፈንጠቅ እሞክራለሁ፡፡ መልካም ጊዜ፡፡  

Published in ህብረተሰብ

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
በቀደም አንድ መዝናኛ ቦታ ስለሆነች ልጅ ያወሩ የነበሩ ወዳጆች በምን ይጣላሉ መሰላችሁ…ቆንጆ ነች፣ ቀንጆ አይደለችም በሚል! በጨዋታና መበሻሸቅ መልክ የተጀመረው ጨዋታ ወደ ስድብ ተለወጠ፡፡ ምን አይነት ዘመን ላይ እንደተደረሰ አያሳዝናችሁም! የምንጣላበት አጣንና ደግሞ “እከሊት ቆንጆ ነች! ቆንጆ አይደለችም! በሚል ‘ጦር እንማዘዝ’! ኮሚክ እኮ ነው…እንቅፋት ‘ከመታን ድንጋይ ጋር ወደምንራበሽበት’ ዘመን እየደረስን ይመስላል፡፡ ከዚህ ይሰውረንማ!
ስሙኝማ… እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ… የቁንጅናን ነገር ካነሳን አይቀር…እዚህ አገር ቀደም ሲል የነበሩት ‘የውበት መለኪያዎች’ በማን ነው የተለወጡት? አሀ…ግራ ገባና! ድሮ…  “ውይ ይቺ ምስኪን ስታሳዝን! በልታ የምታድር አትመስልም እኮ!” ይባል የነበረው ሁሉ… አሁን ልጄ ‘የጨዋታው ህግ’ ተለውጧል፡፡ በርበሬና ሚጥሚጣ ‘የሚወደው’ የሀበሻ ልጅ የውበት መለኪያ ተለወጠና…አለ አይደል…“እንዴት ስሊም እንደሆነች አይተሀታል! ሞዴል ነው እኮ የምትመስለው!” መባል ተጀምሯል፡፡
በፊት እኮ ውበት ማለት… “ሞላ ያለ ዳሌ፣ ሞንደል ያለ ባት…” ምናምን ነገር ነበር። አለ አይደል… የእንትናዬ ዳሌ እንደ ድሮዎቹ የአሜሪካ ‘ቴክሶች’ በግራና በቀኝ ሁለት ሽጉጥ የታጠቀች ካላስመሰላት ማን ዘወር ብሎ ሲያይ! ያኔ ኮሌስተሮል የለ፣ ቅብጥርስዮ የለ…‘ሞላ’ ማለት የሚያሸልልበት ዘመን ነበር፡፡
እናላችሁ…እንደው ቀጠን ያለች እንትናዬ ከታየች…ከንፈር እየተመጠጠ “ምነው እንዲህ ጭር አልሽ! የሚያምሽ ነገር አለ እንዴ!” እኮ ምናምን ነገር ይባል ነበር፡፡ ዘንድሮ ግን ቀጠን ያለች እንትናዬ ከታየች… “ጂም ገባሁ እንዳትይ! ስታምሪ! ለምን ሞዴል አትሆኝም!” ምናምን ይባላል፡፡ ታዲያላችሁ…ዘንድሮ የ‘ስሊምነት’ ዘመን መጣና እንትናዬዎቹ ሁሉ አንድ ይሁኑ! ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ… አንዳንድ እንትናዬዎችን ታዩና የተወሰኑ የሰውነት ክፍሎች ‘ወዴት እንደገቡ’ ሁሉ ይጠፋችኋል (ለልማት ተብሎ ካልተነሱ በስተቀር! ቂ…ቂ…ቂ…) ታዲያላችሁ… ዘንድሮ እንትናዬዎቹን በተርታ ሆነው ራቅ ብላችሁ ስታዩዋቸው አለ አይደል… በሁለት ጦሰኛ አገሮች መሀል የተተከለ የአጠና አጥር ሊመስሉ ይችላላ!
እኔ የምለው እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ስሙኝማ…ነገሬ ብላችሁልኛል…ከተማ ውስጥ ብዙ ቦታ የሆነ ግርግር የሚመሳስል ነገር አታጡም፡፡ ብቻ ትንሽ ነገር ስናይ መክበብ ለመደብንሳ! ጫማ ጠራጊዎች በሆነ ነገር ሲጣሉ እንከባለን፡ መኪኖች ተጋጭተው ሾፌሮች እንካ ስላንትያ ምናምን ሲባባሉ እንከባለን፡፡  ብቻ የሆነ የተበላሸ ነገር አለ፡፡ ለምንድነው ሰዉ ሁሉ ሰከን ብሎ ከመነጋገር… አለ አይደል… “ሦስት ቀን ክፍቱን ያደረ ሊጥ እንዳላስመስልህ!” አይነት ነገር ውስጥ የሚገባው! ለምንድነው በትንሹም፣ በትልቁም ጠብ፣ ጠብ የሚለን! አንዳንዴ … ኑሮ ራሱ የሌለ የጠበኝነት ባህሪይ አምጥቶ የከመረብን አይመስላችሁም!
ጥያቄ አለን…የጂም ቁጥር ይቀንስልን፡፡ ልክ ነዋ…አንድ ሳምንት ብረት ገፍቶ በሁለተኛው ክንዱን የሚነቀስ፣ በሦስተኛው መጋንጭሌ ካላጣመምኩ የሚል በዛብና!
የምር አስቸጋሪ ነው… በጂም ያበጠውም፣ በጂን ያበጠውም…ቡራከረዩ የሚል ሲበዛ አስቸጋሪ ነው፡፡
ምነው መቻቻል አቃተንሳ! ሁሉንም ነገር ለእኛ እንዲስማማ ልናገኘው አንችልም፡፡ ደግሞላችሁ…ከግርግር ጠብ ሌላ የጥላቻ ንግግር በዝቷል፡፡ ሚዲያ ላይ ፊት ለፊት ከሚነገረው ውጪ በተዘዋዋሪም የሚነገሩ የጥላቻ ንግግሮች በዝተዋል፡፡
እናማ…የጥላቻ ንግግሮችን የሚያስወግድ ሶፍትዌር ምናምን አንድዬ ካልፈጠረልን አስቸጋሪ ይሆናል፡፡
ፊት ለፊት የጥላቻ ንግግሮች አሉ፡፡ ገራገር ሀሳብ እየመሰሉ የሚቀርቡ የጥላቻ ንግግሮች አሉ፡፡ እናማ…የጥላቻ ንግግርን ከሌላው መለየት ካልተቻለ የአንዳንዶቻችን አያያዝ ደስ አይልም፡፡
ለምሳሌ የሆነ ሰው ከሆነች እንትናዬ ጋር ….ማለት ፈልጎ ለጓደኛው ያማክረዋል፡፡
“ስማ እንትናን ታውቃት የለ!”
“እንትና…እንትና…ማን ናት እሷ?”
“ይቺ ከወፍጮ ቤቱ በላይ…”
“እ!…እሷንማ አወቃታለሁ፡፡ ምን ሆነች?
“ምንም አልሆነች፡፡ በቃ… ቅዳሜ ‘ዴት አለን። ‘የቁርጥ ቀን ዘመቻ’ ምናምን ታውቅ የለ!”
“እኮ ያቺ ሲንቢሮዋ…”
“አንተ ሁልጊዜ አቃቂር ማውጣት ትወዳለህ። እኔ እኮ እንዴት ‘ሀንድል’ እንደማደርጋት ታማክረኛለህ ብዬ ነው እንጂ…”
አሁን እንግዲህ ጓደኛ ሆዬ የጥላቻና የምክር ንግግርን ካልለየ አስቸጋሪ ነው የሚሆነው፡፡
“እሺ ልምከርህ…ቢያንስ፣ ቢያንስ አጫጭር ቀሚስ እንዳትለብስ ንገራት፡፡ አያምርባትም፡፡”  
ይሄ ‘ምክር’ ሊባል ይችላል፡፡
“እሷን! እሷን! እንደው ምን አይተህባት ነው… ለራሷ እግሯ መቅረጫ የተፋው እርሳስ የመሰለ!”  ይሄ ደግሞ ‘ጥላቻ’ ሊባል ይችላል፡፡ ቂ…ቂ…ቂ…
የምር ግን መቼም ነገረ ሥራችን ሁሉ መላ የጠፋብን ይመስላል፡፡
በ‘ቦተሊካው’ ሆነ፣ በሥራ ግንኙነት ሆነ፣ በማህበራዊ ግንኙነት ሆነ… “ቢያንስ አጭር ቀሚስ እንዳትለብስ ንገራት!” ከሚል ‘ምክር’ ይልቅ… “ለራሷ እግሯ መቅረጫ የተፋው እርሳስ የመሰለ…” ይሄ ‘የጥላቻ’ ንግግር እየበዛ ነው፡፡
በቀደም ዕለት የሆነ ሠርግ ቤት ቅልጥ ያለ ጠብ እንደነበር በሬደዮ ስንሰማ ነበር፡፡ አያስገርምም!  የፈለገ ነገር ይሁን በሰው ሠርግ ሄዶ ረብሻ ማንሳት ምን የሚሉት ነው! ምክንያቱ ምንም ይሁን ምንም የሆነ ነገር እየተበላሸ እንደሆነ ያሳያል፡፡
ደግሞላችሁ…በሰሞኑ በዓላት ላይም አንዳንድ ቦታ ለደስታ ብለው በወጡት መሀል ጠብ ነበር ሲባል ሰምተናል፡፡
ስሙኝማ… እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ድሮ ብይ፣ ጠጠር ምናምን ስንጫወት…አለ አይደል… ተሸናፊ ሁልጊዜ አሸናፊን ‘እንኮኮ’ ይሸከማል፡፡ (የሰው ልጅ ታሪክ እንዲሁ ነው…የእንኮኮ አድራጊና ተደራጊ ቂ…ቂ…ቂ…
እኔ የምለው…አንድ ጥያቄ አለን፡ ዘንድሮ መቻቻል የሚባለው አንዱ እንኮኮ አድራጊ አንዱ ተፈናጣጭ መሆን ነው እንዴ! አዬ…ግራ ስለገባን ነው፡፡
ስለ ትዳር ካነሳን አይቀር…እንግዲህ የሙሽሪት እናቶች ልጆቻቸው ሲያገቡ ያለቅሱ የለ፡፡ ለምን መሰላችሁ…የሚያለቅሱት… “አምላኬ፣ ብቻ የአባቷን አይነት ባል እንዳትሰጣት!” ብለው እየተላመመኑ ነው የሚያለቅሱት አሉ፡፡ ቂ…ቂ…ቂ…
ይችኛዋን ኮሚክ ነገር ስሙኝማ…አንዲት ሴት በፍቅር የተሞላ ህይወት የሚያደርጉት አምስቱ ምስጢራት የሚከተሉት ናቸው፡፡
ማብሰል፣ ዕቃዎችን ማጠብና የቤት ሥራዎች የሚሠራ ወንድ ፈልጊ፡፡
የሚያስቅሽ ሰው ፈልጊ፡፡
ታማኝ፣ እምነት የሚጣልበት፣ ጨዋና ልጆችን የሚወድ ወንድ ፈልጊ፡፡
ጥሩ አፈቃሪና የምተፈልጊውን ሁሉ የሚፈጽምልሽ ወንድ ፈልጊ፡፡
እነኚህ አራት ወንዶች በምንም አይነት እንዳይገናኙ አድርጊ፡፡
ቂ…ቂ…ቂ… ልክ ነዋ! እነኚህ ሁሉ ክህሎቶች አንድ ወንድ ላይ ሊገኙ አይችሉም ለማለት ነዋ!
እናላችሁ…በሆነ ባልሆነው ጠብ ያለሽ በዳቦ ስለበዛ አንድዬ ሰከን ያድርገንማ!
“ለራሷ እግሯ መቅረጫ የተፋው እርሳስ የመሰለ…” ከመባባል የጥላቻ አነጋገርና አስተሳሰብ ይሰውረንማ!
ደህና ሰንብቱልኝማ!

Published in ባህል

ባራክ ኦባማ - አዛሪያስ ረዳ - የአሜሪካ ፖለቲካ
አዛሪያስ ረዳ ማን ነው?
“ከ12 የዘመናችን ወጣት ጥቁር አሜሪካዊያን መሪዎች አንዱ” -  (ታይም መፅሔት፣ የዚህ ሳምንት የጥር 18 እትም)
“በፖለቲካና በህግ ዘርፍ ብቅ ካሉ 30 አዳዲስ መሪዎች አንዱ” -  (ፎርብስ መፅሔት፣ ከሳምንት በፊት የጥር 11 እትም)
“እውቀት ኃይል ነው የሚል የኢትዮጵያ ተወላጅ አሜሪካዊ” - (ዎል ስትሪት ጆርናል፣ ዘንድሮ የመስከረም 10 ዘገባ)
“የአሜሪካን ፕሬዚዳንት ለማስመረጥ እንዲረዳ በሪፐብሊካኖች የተጠየቀ” - (ብሉምበርግ፣ አምና የመጋቢት 29 ዘገባ)


   የአሜሪካ ፕሬዚዳንቶች፣ ባለፈው ሳምንት ባራክ ኦባማ እንዳደረጉት፣ የፓርላማ አባላት ዘንድ በመቅረብ “ስቴት ኦፍ ዘ ዩኒዬን” የተሰኘ ንግግር በማሰማት ነው የአመቱን ስራ በይፋ የሚጀምሩት። ታክስ ለመጨመር ወይም ለመቀነስ፣ የንግድ ማዕቀብ ለመጣል ወይም ነፃ ንግድ ለማስፋት፣ የቢዝነስ ማደናቀፊያ ቁጥጥሮችን ለመፈልፈል ወይም ለመሻር፣ ጦርነት ለማወጅ ወይም ሰላም ለማውረድ ... በተለምዶ አንድ ሰዓት ገደማ በሚፈጀው ንግግር ዋና ዋና የአመት እቅዶችን ይዘረዝራሉ። እስቲ ከኦባማ ንግግር ጥቂቱን ልጥቀስላችሁ - ከፓርላማ (ከኮንግረስና ከሰኔት) አባላት ካገኙት ምላሽ ጋር።
አንዳንድ የታክስ ጭማሪዎችን በመተግበር ለምሳሌ በቋሚ ንብረት ላይ ታክስ በመጫን) ድሆችን መደጎም እንደሚፈልጉ የተናገሩት ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ፣ የባንኮችን አሰራር ለመቆጣጠር የወጡ ሕጎች በኮንግረስና በሰኔት ሊሻሩ አይገባም ብለዋል። የፓርቲያቸው (የዲሞክራቲክ ፓርቲ) ተመራጮች ከወንበራቸው ተነስተው ሲያጨበጭቡ፣ በአመዛኙ ለታክስ እና ለድጎማ ፍቅር የሌላቸው የሪፐብሊካን ፓርቲ ተመራጮች ከወንበራቸው ንቅንቅ አላሉም።
ከኩባ ጋር ለግማሽ ምዕተዓመት የዘለቀውን ጠላትነት ማብረድ ይኖርብናል በማለታቸው ከብዙዎቹ ዲሞክራቶች የድጋፍ ጭብጨባ የተቸራቸው ኦባማ፤ በሶሪያና በኢራቅ ሰዎችን እየፈጀ የሚገኘው አይሲስ የተሰኘውን አሸባሪ ቡድን ለማጥቃት ኮንግረስ ጦርነት ማወጅ እንዳለበት በመጠቆምና የአሜሪካን ጦር ሠራዊት በማሞገስ ሪፐብሊካኖችም እንዲያጨበጭቡ አድርገዋል።
ዩክሬንን በወረረው የራሽያ መንግስት ላይ የተጣለው የኢኮኖሚ ማዕቀብ የቭላድሚር ፑቲንን እብሪት ማብረክረክ እንደጀመረና ወደፊትም እንደሚገፉበት ኦባማ ጠቅሰው፤ ከኤሺያ አገራት ጋር ነፃ ንግድ ለማስፋፋት የኮንግረስንና የሰኔትን ድጋፍ ጠይቀዋል። ይሄኔ፣ የጭብጨባው አቅጣጫ ተቀየረ። ከራሳቸው ፓርቲ ይልቅ ከተቃዋሚያቸው ፓርቲ ነው ከፍተኛ ድጋፍ ያገኙት። የሪፐብሊካን ፓርቲ ተመራጮች ከወንበራቸው ተነስተው አዳራሹን በጭብጨባ አደመቁት - በአብዛኛው የነፃ ንግድ ደጋፊዎች በመሆናቸው። ኦባማ የዲሞክራቲክ ፓርቲ አባል ቢሆኑም፣ አብዛኞቹ የፓርቲው ተመራጮች ከወንበራቸው ሊነሱ ይቅርና፣ ለወጉ እንኳ አላጨበጨቡም። ለምን ቢባል፤ ዲሞክራቶች በአመዛኙ በሌሎች አገሮች እንደተለመደው ያፈጠጠና ያገጠጠ የነፃ ንግድ ጠላትነት ባይጠናወታቸውም፤ የነፃ ንግድ ፍቅርም አይታይባቸውም። እናም፤ ከተወሰኑት በስተቀር አብዛኞቹ ዲሞክራቶች ድጋፋቸውን አልገለፁም። በአጭሩ ከፓርቲ ትዕዛዝ እየተቀበሉ የሚያጨበጭቡ ወይም የሚቃወሙ አይደሉም፡፡ የአሜሪካዊያን ነፃነት እንዲህ ነው!
በእርግጥ ባራክ ኦባማ  ከኤሽያ አገራት ጋር የነፃ ንግድ ስምምነት ለመፈራረም ያቀዱት የነፃ ንግድ ደጋፊ ስለሆኑ አይደለም። እንደ አብዛኞቹ ዲሞክራቶች፣ ለነፃ ንግድ ብዙም ፍቅር የላቸውም። ነገር ግን፤ ከሌሎቹ ዲሞክራቶች የተለየ ሃላፊነት አለባቸው፤ ፕሬዚዳንት ናቸው። ከነፃ ንግድ የሸሸ አገር፤ ወደ ኋላ እየተንሸራተተ እንደሚቀር እያወቁ፣ የነፃ ንግድ ስምምነት ላለመፈረም ቢወስኑ፤ የኋላ ኋላ ፓርቲያቸው ሳይሆን ራሳቸው በግል ተወቃሽ ይሆናሉ። ለዚህም ነው፤ ከፓርቲያቸው ተመራጮች ድጋፍ ባያገኙም፤ የነፃ ንግድ ስምምነት ለመፈረም ያቀዱት።
በዚያ ላይ፣ ከዚህ ስምምነት ውጭ ሌሎቹ የኦባማ እቅዶች ከእቅድነት ያለፈ እጣፈንታ አይኖራቸውም። ለምን? የዲሞክራቲክ ፓርቲው ባራክ ኦባማ በቀሪው የስልጣን ዘመናቸው፣ አንዳች ቁምነገር መስራት የሚችሉት ከሪፐብሊካን ፓርቲ ተመራጮች ድጋፍ ካገኙ ብቻ ነው። ለምን? በኮንግረስና በሰኔት አብላጫውን ወንበር የያዙት ሪፐብሊካኖች ናቸዋ። ፕሬዚዳንቱ ያረቀቁት ህግ፣ ኮንግረስና ሰኔት ካላፀደቁት ዋጋ አይኖረውም። በኮንግረስ የፀደቀ ህግም እንዲሁ በሰኔት ወይም በፕሬዚዳንቱ ተቀባይነት ካላገኘ፣ መክኖ ይቀራል። እንዲህ አይነቱን አሰራር፣ check and balance ይሉታል።  ብልሆቹ የአሜሪካ መስራቾች፣ ሆን ብለው የፈጠሩት አሰራር ነው - መንግስት መረን ከተለቀቀ፣ እዚህም እዚያም እጁን እያስገባ አገሪቱን የሚያቃውስ፣ ዜጎችን የሚያሰቃይ አቻ የማይገኝለት አደገኛ የወንጀል ተቋም እንደሚሆን በመገንዘብ። በተለይ፣ ተቀናቃኝ ፓርቲዎች የኋይት ሃውስ፣ የኮንግረስና የሰኔት ስልጣን ሲቆጣጠሩ፣ እርስ በርስ ተቆላልፈው አንዱ ሌላውን አስሮ ይይዛል። ልክ አሁን እንደሚታየው ማለት ነው።
የዛሬን አያድርገውና (የዛሬን ያድርገውና)፤ ባራክ ኦባማ የዛሬ ስድስት ዓመት በመላው ዓለም “ጉድ” በተባለለት የምርጫ ዘመቻ አሸንፈው የታላቋ የነፃነት አገር የአሜሪካ ፕሬዚዳንት የሆኑ ጊዜ፤ ደስታቸው እጥፍ ድርብ ነበር። እሳቸው ኋይት ሃውስ ሲገቡ፣ ፓርቲያቸው በኮንግረስና በሰኔት አብላጫ ወንበሮችን አሸንፎ ነበር - ከ100 የሰኔት ወንበሮች 57ቱን፤ እንዲሁም ከ435 የኮንግረስ ወንበሮች 257ቱን። በእርግጥ፣ ከላይ እንደገለፅኩት፤ ሁሉም የሪፐብሊካን ፓርቲ ተመራጮች፤ በሁሉም ጉዳይ ላይ ሁልጊዜ ፕሬዚዳንቱን ይቃወማሉ ማለት አይደለም። የዚያኑ ያህል፣ ሁሉም የዲሞክራቲክ ፓርቲ ተመራጮች ፕሬዚዳንቱን ሁልጊዜ ይደግፋሉ ተብሎ መታሰብ የለበትም። ስለዚህ ፓርቲያቸው በኮንግረስና በሰኔት አብላጫ ወንበር ቢይዝም፤ ሁሉም ነገር አልጋ ባልጋ ይሆንላቸዋል ማለት አይደለም። እንዲያም ሆኖ፤ የትኛውም ፕሬዚዳንት ከዚህ የተሻለ እድል ሊመኝ አይችልም። እናም፣ ለባራክ ኦባማ ትልቅ ፌሽታ ነበር - የዛሬ ስድስት አመት።
ዛሬ ግን፣ ነገሮች ተለውጠዋል። የሪፐብሊካን ፓርቲ ተመራጮች በኮንግረስ እና በሰኔት አብላጫ ወንበር ይዘዋል። እንዲያውም፣ በዘንድሮው የኮንግረስና የሰኔት ምርጫ ላይ ሪፐብሊካን ፓርቲ ያገኘው ድል፣ ባለፉት 85 ዓመታት ያልታየ ትልቅ ድል ነው ተብሎለታል። ነገሮችን እንዲህ የሚለውጥ ምን አዲስ ነገር ተፈጠረ?
ምን አዲስ ነገር ተፈጠረ?
በቀውስ የተመታው የአሜሪካ ኢኮኖሚ፤ ከአውሮፓና ከጃፓን በተሻለ ሁኔታ ቢያገግምም በፍጥነት ለማንሰራራት አለመቻሉ፣ ኦባማንና ዲሞክራቶችን የሚያሳጣ ትልቁ ችግር ነው። የመንግስት ጣልቃ ገብነት እየተስፋፋ፣ ሃብትን የሚያባክኑ የድጎማ አይነቶች መበራከታቸው፣ በዚያው ልክ የመንግስት ወጪ እያበጠ የታክስ ጫናዎች መክበዳቸው፣ እንዲሁም የቢዝነስ ሥራን የሚያደናቅፉ አላስፈላጊ ቁጥጥሮች እንደ አሸን መፍላታቸው ለብዙ አሜሪካዊያን እጅጉን አሳሳቢ እየሆኑ መምጣታቸውም ሌላው ለውጥ ነው። መንግስት በየአመቱ የሚያብጠውን ወጪ በታክስ መሸፈን ሲያቅተው፣ በየአመቱ በቦንድ ሽያጭ ብድር እየሰበሰበ የእዳ ክምር እየገነነ መምጣቱም እንዲሁ ብዙዎችን እያሳሰበ ኦባማንና ዲሞክራቶችን እንዲቃወሙ አድርጓቸዋል፡፡
የዛሬ 35 ዓመት ከአንድ ትሪሊዮን በታች የነበረው የመንግስት እዳ፣ በአስር አመት ውስጥ ወደ ሦስት ትሪሊዮን፣ እንደገና በአስር ዓመት ወደ አምስት ትሪሊዮን መጨመሩን ስትመለከቱ፣ በሽታው አዲስ እንዳልሆነ ያመለክታል። ነገር ግን፣ እንደ ካንሰር ፍጥነቱን እየጨመረ መጥቷል። ባራክ ኦባማ ስልጣን በያዙበት አመት፣ የመንግስት እዳ አስር ትሪሊዮን ደርሶ ነበር። ባለፉት ስድስት ዓመታት ደግሞ፣ በየአመቱ ከአንድ ትሪሊዮን ዶላር በላይ እየተበደረ፣ የእዳው ቁልል ወደ 18 ትሪሊዮን አድርሶታል። ይህ አልበቃ ብሎ፤ እንደገና የመንግስትን ጣልቃ ገብነትን የሚያስፋፋና የመንግስትን ወጪ የሚያባብስ የጤና ኢንሹራንስ ህግ ፀድቆ ተግባራዊ ሆኗል። ከዚህ ከዚህ ጋር በተያያዘ፣ መንግስት መረን ተለቋል የሚል ፀረ ኦባማ ተቃውሞ፣ “ቲ ፓርቲ” በተሰኘ የነፃ ገበያ እንቅስቃሴ መፈጠሩ ሌላ ለውጥ ነው፡፡ በዚህም የተነሳ፣ እንደ ቴድ ክሩዝ፣ ራንድ ፖል እና ማርኮ ሩቢዮ የመሳሰሉ የታዋቂዋ ደራሲና ፈላስፋ አየን ራንድ አድናቂ አዳዲስ ሪፖብሊካን ሴናተሮች መበራከታቸውን መጥቀስ ይቻላል።
ባለፉት ስድስት ዓመታት ከተፈጠሩት ከእነዚህ ለውጦች በተጨማሪ፣ኦባማንና ዲሞክራቶችን የሚያሳጣ  ምን አዲስ ነገር ተከሰተ?
አዛሪያስ ረዳ አሜሪካ ውስጥ ተከሰተ
በኢትዮጵያ ደሴ ተወልዶ ያደገው አዛሪያስ፤ አሜሪካ የገባው የዛሬ 12 ዓመት ነው። በእነዚህ 12 ዓመታት ግን፤ ስንት ነገር ሰርቷል! እዚህ ያቋረጠውን የዩኒቨርስቲ ትምህርት ማጠናቀቅ የመጀመሪያው ስራ ነው - አራት ዓመት ተኩል ፈጅቶበታል። ግን ለአንድ ዲግሪ ብቻ አይደለም። በኮምፒዩተር ሳይንስ፣ በሂሳብ እና በቢዝነስ አስተዳደር ... በአንድ የምረቃ ስነስርዓት ሶስት ጊዜ ስሙ እየተጠራ ሶስት ዲግሪ ይዞ ከወጣ በኋላ፤ ለግማሽ ዓመት ያህል፣ ሥራ ተቀጥሮ በሶፍትዌር ዝግጅት ሰርቷል። ወደ ትምህርት ተመልሶ የማስተርስ ጥናት መከታተል ከመጀመሩ በፊት ማለት ነው። በዚያውም የፒኤችዲ ጥናት። ሦስት ዓመት አልፈጀበትም - ዶ/ር አዛሪያስ ረዳ ለመሆን።
እግረመንገዱን፤ ኢትዮጵያ መጥቶ የቴክኖሎጂ ፋኩልቲ ውስጥ ለግማሽ አመት አስተምሯል፤ ህንድ ሄዶም ለተወሰነ ጊዜ ለማይክሮሶፍት ማዕከል ጥናት ሰርቷል። አሜሪካ ተመልሶ፣ ከፌስቡክና ከቲውተር ጋር አብሮ ስሙ የሚነሳ LinkedIn በተሰኘው የኢንተርኔት ኩባንያ ውስጥም በሶፍትዌር ዝግጅት የራሱን አሻራ አሳርፏል። ከዚህ በኋላ ነው የራሱን የኢንተርኔት ኩባንያ ለመመስረት ወጥሮ መስራት የጀመረው።
በዚህ መሃል ግን፤ ሕይወትን የሚቀይር ነገር ተፈጠረ - በአጭር ጊዜ በአሜሪካ ታላላቅ የሚዲያ ተቋማት አፍ ውስጥ እንዲገባ ከሚያደርግ የሥራ ሃላፊነት ጋር ተገናኘ። ቀላል ነገር አይደለም።
በአንድ በኩል መልክ እየያዘ የነበረ የራሱ ኩባንያ እና ጅምር ሥራ አለ። በሌላ በኩል ደግሞ፣ ሌላ አዲስ ትልቅ ሥራ! ከባድ ምርጫ ነው። ቡልምበርግ እንደዘገበው፤ አዛሪያስ ከኦስቲን ቴክሳስ ዘመድ ጥየቃ ወደ ዋሽንግተን ጎራ ሲል ያነጋገሩት ሰዎች፣ ጊዜ አላባከኑም። እቅጩን ነው የነገሩት። ጊዜው አምና ህዳር ወር ገደማ ነው። ሰዎቹ የሪፐብሊካን ፓርቲ ተወካዮች ናቸው - “በጀመርከው መንገድ ምርጥ የኢንተርኔት ፕሮግራም ወይም ዌብሳይት መፍጠር ትችላለህ፤ ወይም ቀጣዩን የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ለመምረጥ ልትረዳን ትችላለህ” አሉት። ታይም መጽሔት ሰሞኑን እንደገለፀው የቀረበለት የሃላፊነት ቦታ የዋዛ አይደለም፡፡
በአሜሪካ ፖለቲካ ውስጥ ቁልፍ ተዋናይ ለመሆን የሚያስችል ሃላፊነት ነው፡፡ አዛሪያስ ከራሱ ኩባንያ እና ከሪፖብሊካን ፓርቲ አንዱን መምረጥ ነበረባት፡፡ የፓርቲውን እንቅስቃሴ በአገር አቀፍ ደረጃ ከሚያስተባብረው ብሔራዊ ሪፐብሊካን ኮሚቴ መሪዎች ጋር ተነጋገረ። እናም፤ በ2016ቱ ምርጫ ሪፐብሊካን ፓርቲ እንዲያሸንፍ ለመርዳት... ዶ/ር አዛሪያስ ረዳ፣ የዛሬ አመት ጥር ወር ሃላፊነቱን ተቀብሎ አዲሱን ስራ ጀመረ - የፓርቲው ቺፍ ዳታ ኦፊሰር በሚል ስያሜ። ዎል ስትሪት ጆርናል እና ብሉምበርግ እንደዘገቡት፤ ይህ የሪፐብሊካን ፓርቲ እና አዛሪያስ ረዳ ውሳኔ በአገሪቱ ፖለቲካ ላይ ለውጥ የሚያመጣ ውሳኔ ነው፡፡
በ2008 ከዚያም በ2012 የዘመኑን የኮምፒዩተር ቴክኖሎጂ፣ የመረጃ አሰባሰብና ትንታኔ፣ የኢንተርኔትና የሞባይል ቴክኖሎጂዎችን በስፋት ተጠቅመው የምርጫ ዘመቻ ባካሄዱት ባራክ ኦባማ ክፉኛ የተሸነፉት ሪፐብሊካኖች፣ በአንድ አስተማማኝ እመርታ ብልጫ ለማግኘት ታጥቀው ለመነሳት መወሰናቸው አይገርምም። ወደ ተግባር ለመግባት ጊዜ አልፈጀባቸውም። በዲጂታል ሚዲያ (በኢንተርኔትና በሞባይል) የፓርቲውን የምርጫ ዘመቻ የሚያስተባብር የኮሙኒኬሽን ባለሙያ ቀጥረዋል - በጆርጅ ቡሽ የምርጫ ዘመቻ የዲጂታል ሚዲያ ዋና መሪ የነበረ ባለሙያ። የቴክኖሎጂ መረጣ የሚመራ ሌላ ባለሙያም መርጠዋል - የፌስቡክ ኢንጂነር የነበረ። ከዚህ በኋላ የሚያስፈልገው፣ ቴክኖሎጂውን በመጠቀም እልፍ አእላፍ ጥሬ መረጃዎችን የሚሰበስብና የሚተነትን፣ በወግ በወጉ የሚያደራጅና ለሚዲያ አመቻችቶ የሚያቀርብ ምርጥ የዳታ ባለሙያ ነው - አዛሪያስ ረዳ።
በጭፍንና በግምት ሳይሆን በመረጃ ላይ የተመሰረተ አስተማማኝ የምርጫ ዘመቻ ለማካሄድ፣ ትልቁን ቁልፍ የሃላፊነት ቦታ የተረከበው አዛሪያስ፣ በየአመቱ ከሚገሰግሰው የኮምፒዩተርና የኢንተርኔት ቴክኖሎጂ ጋር የሚራመድ ዘመናዊ ስራ ለማከናወን ከፈለገ ወጣት ባለሙያዎችን መቅጠርና ማደራጀት ነበረበት። እናም በኮምፒዩተር ሳይንስና በሂሳብ ትምህርት ስመጥር ዩኒቨርሲቲዎችን አሰሰ፡፡ በኮምፒዩተርና በኢንተርኔት ማዕከልነቱ በሚታወቀው የካሊፎርኒያው ሲልከንቫሊ ምርጥ ምርጦችን ለመመልመል ዞረ። ከዚያ በኋላ ለቁጥር የሚያስቸግሩ የጥሬ መረጃ ክምሮችን በወጉ ማበጃጀት፣ ተጨማሪ መረጃዎችን መሰብሰብ፣ በየእለቱና በየደቂቃው አዳዲስ መረጃዎችን እየተከታተለ ለማካተት የሚያስችል ስርዓት መዘርጋት... ከዚህ ስፍር ቁጥር የሌለው መረጃ ውስጥ ቁምነገርና ፍሬነገር አጣርቶ ለማውጣት ሌት ተቀን የሚሰሩ የትንታኔ ዘዴዎችን መፍጠር፣ በዚህም ለፓርቲውና ለምርጫ ተፎካካሪዎች የገንዘብና የድምፅ ድጋፍ ሊያስገኙ የሚችሉ መንገዶችን እየመረጠ ማቅረብ... እንዴት መሰላችሁ?
የፌስቡክ ደንበኛ ስትሆኑና ድረገፅ ስትከፍቱ፣ ያደጋችሁበትን ከተማ ወይም የተማራችሁበትን ዩኒቨርስቲ ትመዘግቡ የለ? ፌስቡክ የበርካታ ሚሊዮን ሰዎችን መረጃ በማሰስና በመተንተን፣ እገሌና እገሊትም እዚህ ዩኒቨርስቲ ተምረዋል፣ እነ እንትና እዚህ ከተማ የሚኖሩ ናቸው፤ ታውቃቸው ይሆን? ብሎ በርካታ ስሞችን ያቀርብላችኋል። አማዞን ዌብሳይት ገብታችሁ አንድ የመፅሐፍ ርዕስ ስትፈልጉ፣ የዚህ መፅሐፍ ደራሲ’ኮ ሌሎች መፅሐፍት አሳትሟል ብሎ ይዘረዝርላችኋል፤ “ይሄን መፅሐፍ የወደዱ ሰዎች ይሄንንና ያንንም መፅሃፍ አንብበው ተደስተዋል፤ እስቲ አንቺም ተመልከቻቸው” ብሎ ያቀርብላችኋል። በመረጃ ላይ የተመሰረተና ለእያንዳንዱ ሰው ታልሞና ተለክቶ የተዘጋጀ ማስታወቂያ ልንለው እንችላለን።
የፖለቲካ የምርጫ ዘመቻም እንዲህ፣ በመረጃ ላይ ተመስርቶ፤ ለእያንዳንዱ መራጭ እና ለለጋሾች በተመቸ ሁኔታ መቅረብ ይችላል። ለምሳሌ፣ የምርጫው እለት ሳይደርስ ከቀናት በፊት ድምፅ መስጠት የሚቻልበት አሰራር እየተስፋፋ ከመምጣቱ የተነሳ፣ ዛሬ ዛሬ ሩብ ያህሎቹ መራጮች ከምርጫው እለት በፊት ነው ድምፅ የሚሰጡት። እንግዲህ በምርጫው እለት ስልክ እየደወሉ፣ ኢሜይል እየላኩ፣ በፌስቡክ እየፃፉ ወይም በየቤቱ እየዞሩ መራጮች ድምፅ እንዲሰጡ የሚቀሰቅሱ ደጋፊዎችን አስቧቸው። ከወዲሁ ድምፅ የሰጡ መራጮች ላይ ጊዜያቸውን ማባከን የለባቸውም። ለተቀናቃኝ ፓርቲ ድምፅ የሚሰጡ ሰዎችን ለመቀስቀስ ጊዜ ማባከን ደግሞ ድርብ ኪሳራ ነው። ስለዚህ ባለፉት ምርጫዎች በተደጋጋሚ የሰጡትን ድምፅ ማወቅ ቢቻል፤ በምርጫ ዘመቻው ወቅት በቤት ለቤት ቅስቀሳ የእያንዳንዱን መራጭ አዝማሚያ ወዴት እንደሚያዘነብል ማወቅ ቢቻል፣ ከምርጫው እለት በፊት ድምፅ መስጠት አለመስጠቱን ማወቅ ቢቻል... የት ላይ ማተኮር እንዳለብህ አወቅክ ማለት ነው፤ የምርጫ ዘመቻው ይበልጥ ውጤታማ ይሆናል። ይሄን ይሄን እና ተመሳሳይ ቁልፍ ጉዳዮችን በማወቅ የዘመቻ አቅጣጫ ለፓርቲው ማሳየት የአዛሪያስ ረዳ ስራ ነው፡፡
ድንቅ ነው፡፡ ግን ይሄው የአዛሪያስ ረዳ ሃላፊነት ከሃሳብነት አልፎ በእውን ውጤት ያመጣ ይሆን? ሪፓብሊካኖች በ2016 ዓ.ም የፕሬዚዳንት ምርጫውን እንዲያሸንፉ ይረዳቸው ይሆን? አዛሪያስ አጭር ምላሽ አለው፡፡
ስራውን ከጀመረ አመት ባይሞላውም፤ ገና ከወዲሁ ውጤት እንደምናስገኝ በዘንድሮው የኮንግረስና የሰኔት ምርጫ ታያላችሁ ብሎ ነበር - መስከረም ወር ላይ፡፡ የምርጫው ቀን ደረሰ፡፡ ህዳር ወር ምርጫው ሲካሄድ…እውነትም አዛሪያስ እንደተነበየው ሪፐብሊካኖች ለ85 ዓመት ያላዩት ትልቅ ድል ተቀዳጁ፡፡

“ተመጣጣኝ እርምጃ ነው የተወሰደው” - የአ.አ ፖሊስ ኮሚሽን

  የከተማ አስተዳደሩ እውቅና ሣይሰጠው ሊካሄድ ተሞክሯል በተባለው የባለፈው እሁድ የአንድነት ፓርቲ ሠላማዊ ሠልፍ ላይ ፖሊስ በወሰደው የሃይል እርምጃ በርካታ ሠልፈኞች ጉዳት እንደደረሰባቸው ፓርቲው አስታውቋል፡
ፓርቲው ሰሞኑን “ሠላማዊ ትግሉን በጭፍጨፋና በውንብድና ለማቆም መሞከር ሃላፊነት የጐደለው ተግባር ነው” በሚል ርዕስ ባወጣው መግለጫ፣ “በእሁዱ ሠልፍ በፀጥታ ሃይሎች የተፈፀመው አሠቃቂ ድብደባ ወደር የማይገኝለት ነው” ብሏል፡፡ በድብደባው የፓርቲው አባላት የአጥንት መሠበርን ጨምሮ ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰባቸውና በየሆስፒታሉ ህክምና እየተደረገላቸው መሆኑን የፓርቲው አመራሮች ለጋዜጠኞች ተናግረዋል፡፡
የፀጥታ ሃይሎች ፈፅመውታል በተባለው ድብደባ የፓርቲው የኤዲቶሪያል አባልና “የሚሊዮኖች ድምፅ” ጋዜጣ አዘጋጅ ስለሺ ሃጐስ በድብደባው በደረሠበት ከፍተኛ ጉዳት ለሰአታት ራሱን ከመሣቱም በላይ በተለያዩ የሰውነት ክፍሎቹ ላይ ጉዳት ደርሶበት በህክምና ላይ እንደሚገኝ ተጠቁሟል፡፡ የጋዜጠኛ ስለሺ የግራ እጅ አጥንትም መሠበሩ በህክምና መረጋገጡን የፓርቲው አመራሮች ለጋዜጠኞች አስረድተዋል፡፡
ጉዳት የደረሰባቸው የፓርቲው አባላትም ጉዳት የደረሰበትን የሰውነት ክፍላቸውን ለጋዜጠኞች አሳይተዋል፡፡ የፓርቲው የብሔራዊ ም/ቤት ምክትል ሰብሳቢ አቶ ፀጋዬ አላምረው፤ በእለቱ ፖሊስ በአራት አቅጣጫዎች እንደመጣባቸውና፣ ሲቪል የለበሱ የደህንነት ሃይሎችም በስፍራው እንደነበሩ አስረድተው፣ ያለምንም ማስጠንቀቂያ ፋታ ሣይሰጡ ሰዎችን እየመረጡ መደብደብ ጀመሩ ይላሉ፡፡ “ፖሊሶች ሲደበድቡም ጭካኔ በተሞላበት ሁኔታ የአካል ክፍል ሣይመርጡ” ነው የሚሉት አቶ ፀጋዬ፤ ጭንቅላቴ እንዳይመታ ጥረት ባደርግም እግሬና ጀርባዬ ላይ ከፍተኛ ጉዳት ደርሶብኛል ብለዋል።
አንድነት ፓርቲ ሲመሠረት ጀምሮ በፓርቲው የተለያዩ ሃላፊነቶች ላይ ስታገለግል መቆየቷን የገለፀችው ወ/ት ልዕልና ጉግሣ በበኩሏ፤ በድብደባ የበለዘ የአካል ክፍሏን ለጋዜጠኞች ያሳየች ሲሆን በሆዷ፣ በትከሻዋና በእግር ጡንቻዎቿ ላይ የድብደባ ምልክቶችን ለመታዘብ ተችሏል፡፡ “በጣም ያጠኑኝ በሚመስል መልኩ ነው ተረባርበው የደበደቡኝ” የምትለው ተጐጂዋ፤ “የአለም ህዝብ በሀገሪቱ ያለው ኢ-ሰብአዊ ድርጊት የደረሰበትን ደረጃ እንዲታዘብ እፈልጋለሁ፡፡” ብላለች፡፡
የፀጥታ ሃይሎቹ ሆዴን ሲመቱኝ እንዲተውኝ ለምኛቸዋለሁ ያለችው ወ/ት ልዕልና፤ “አቅሌን ስቼ ከወደቅሁ በኋላ መሬት ላይ ጐትተው ወደ አንድ ጥግ አስቀምጠውኝ ሄደዋል” ስትል አማራለች፡፡ ሞባይሏን ጨምሮ የተለያዩ ንብረቶቿን የያዘው የእጅ ቦርሣዋ መነጠቁንም አክላ ገልፃለች፡፡
ሌሎች ጉዳት የደረሰባቸው የፓርቲው አባላትም የቆሠለ አካላቸውን ለጋዜጠኞች በማሳየት የጉዳታቸውን መጠን በዝርዝር አስረድተዋል፡፡ እንዲያም ሆኖ ድብደባው ፓርቲው በሚያዘጋጃቸው ቀጣይ ሠልፎች ላይ ከፊት ተሠልፈው ድምፃቸውን ከማሰማት እንደማይገድባቸው ተጐጂዎቹ በመግለጫው ላይ ተናግረዋል፡፡
የፓርቲው የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ አስራት በበኩላቸው፤ በድብደባው ከፍተኛ የአካል ጉዳት በትከሻቸውና በጀርባቸው እንዲሁም በእግራቸው ላይ መድረሱን አመልክተው ድብደባውን ሲፈፅምባቸው የነበረው ፖሊስ በቴሌቪዥን ተደበደብኩ ብሎ መግለጫ ሲሰጥ መመልከታቸው አግራሞትን እንደፈጠረባቸው ጠቁመው፤ የፓርቲው አባላት ተቃውሟቸውን በሠላማዊ መንገድ ከማካሄድ ውጭ ጠቁመው፤ በፀጥታ አካላቱ ላይ ድብደባ አለመፈፀሙን አስረድተዋል፡፡
የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን በበኩሉ፤ ሠልፈኞቹ ያልተፈቀደ ሠልፍ እያደረጉ በመሆኑ በተደጋጋሚ እንዲያቆሙ በፀጥታ ሃይሎች የተነገራቸውን ማሳሰቢያ ቸል ብለው የፀጥታ ሃይሎችን ጥሰው ለመውጣት ባደረጉት ህገወጥ እንቅስቃሴ ተመጣጣኝ እርምጃ መውሰዱን አስታውቋል፡፡ ሠልፈኞቹ ከፖሊሶች ጋር በፈጠሩት ግብግብም ሁለት የፀጥታ ሃይሎች ድብደባ እንደተፈፀመባቸው ተገልጿል፡፡
ከ2006 ዓ.ም ጀምሮ የሠላማዊ ሠልፍ ጉዳይ የአዲስ አበባ አስተዳደርና ፓርቲዎችን እንዲሁም የፀጥታ ሃይሉን እያወዛገበ ሲሆን በየጊዜው የሚካሄዱት ሠልፎች ገደብ ሊኖራቸው እንደሚገባም ከዚህ ቀደም ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሣለኝ መግለፃቸው ይታወሣል፡፡ በግንቦት የሚካሄደውን ብሔራዊ ምርጫም የሚያውኩ ማናቸውም እንቅስቃሴዎች በገደብ የለሽ ትዕግስት እንደማይታለፉም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ማሳሰባቸው ይታወሳል፡፡
በሀገሪቱ ያለው የመሰብሰብና ሠላማዊ ሠልፍ የማድረግ መብት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተሸረሸረ ነው የሚሉት የመድረክ አመራርና የፖለቲካል ሣይንስ ምሁሩ ዶ/ር መረራ ጉዲና፤ የመናገር፣ የመፃፍ፣ ሠላማዊ ሠልፍ የማድረግ መብቶች በህገ መንግስቱ ነፃ ሆነው የተደነገጉ እንደሆኑ ጠቁመው መንግስት በአሠራር ደረጃ የተደነገጉትን ህጐች ይጥሣል ብለዋል፡፡ “ህጉና አሠራሩ እየተጋጩ ነው” የሚሉት ምሁሩ፤ “ማሣወቅ” የሚለው የህጉ ድንጋጌ በአሠራር ሌላ ትርጉም እየተሰጠው ነው ሲሉም ተችተዋል፡፡
“መንግስት ህገ መንግስቱን ማስከበር ሲገባው አሁን ተቃዋሚዎች ናቸው ህገመንግስቱን ለማስከበር እየጣሩ ያሉት” ብለዋል - ዶ/ር መረራ፡፡ ሌሎች ሃገሮች ሠልፍ አይከለክሉም፤ ሠልፈኞች ንብረት ሊያወድሙ ወይም ጥቃት ሊፈጽሙ ሲያቅዱ ብቻ ነው ወደ መበተን የሚኬደው የሚሉት ምሁሩ፤ ወደ ሌላ አቅጣጫ ያመራ ሠልፍ የሚበተነውም በዱላ ሳይሆን አስለቃሽ ጭስ፣ ውሃና የመሳሰሉትን በመጠቀም ነው ብለዋል፡
አለማቀፍ የህግ ምሁሩ ዶ/ር ያዕቆብ ሃይለማርያም በበኩላቸው፤ ሠላማዊ ሠልፍ የማድረግ መብትን መከልከል አለማቀፍ ህጐችን መፃረር ነው ብለዋል፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ ሠላማዊ ሠልፎች በተደረጉ ቁጥር ሠዎች መታሠራቸውና መደብደባቸው እነዚህን አለማቀፍ ህጐች የሚፃረር ነው ያሉት ዶ/ር ያዕቆብ፤ ሰዎች የጦር መሣሪያ ሣይዙ የተሠማቸውን ቅሬታ የመግለፅ ሰብአዊ መብት አላቸው” ብለዋል፡፡
በቅርቡ በአንድነት አባላት ላይ ተፈጽሟል የተባለው ድብደባ በህግ ከተረጋገጠ፣ ድርጊቱን የፈፀሙትም ሆኑ እንዲፈፀም ትዕዛዝ የሰጡት አካላት በህግ ያስጠይቃቸዋል ብለዋል ዶ/ር ያዕቆብ፡፡  


    ከዕለታት አንድ ቀን አንድ አይጥ ሁሌ እንደጉድ የሚጠላው ድመት ነበር አሉ፡፡ በዚህ ምክንያት ህይወቱ ይረበሻል፡፡ መንፈሱ እረፍት ያጣል፡
አንድ ቀን ድንገተኛ አውሎ ንፋስ መጣ - በሀገሩ!
የትም መሄጃ ያጣው አይጥ፣ ለድመቶች ጥቃት ተጋለጠ፡፡
አይጥ እንግዲህ ወደ ከተማው ታዋቂ ጠንቋይ ሄደ፡፡ ችግሩንም አዋየው፡፡
ታላቁ ጠንቋይ ሁኔታውን በመገንዘብ፤ አይጡን ከአይጥነት ይልቅ ድመት ቢሆን ይሻለዋል፤ በሚል እሳቤ ወደ ድመት ለወጠው፡፡
ሆኖም አይጡ ወደ ድመት መለወጡ፣ ብዙ አልለወጠውም! የእንስሳት ባህሪ ሆኖበት ውሻን ክፉኛ መፍራት ጀመረ!
ይሄን ያስተዋለው አዋቂ ድመቱን ወደ ውሻ ለወጠው፡፡
ቀጠለና ያ ከድመትነት ወደ ውሻነት የተለወጠው እንስሳ፤ አሁን ደግሞ ነብርን መፍራት ተማረ!
ያ ታጋሽ አዋቂም፤ አስቦ አስተውሎ የድመቱን የመጨረሻ ደረጃ በመገንዘብና ትዕግሥት የበዛው በመሆኑ ነብር ላድርገው ብሎ ወሰነና ነብር አደረገው!
ያም ሆኖ ያ ነብር አዳኝ ቢመጣብኝስ? ብሎ ሥጋት በሥጋት ሆነ!
ይህንን ሁሉ ዕድል ሰጥቼው ካልተለወጠ የራሱ ጉዳይ ነው አለ፡፡ ከዚያም መልሶ ወደ አይጥነቱ መመለስ ዋናው ጉዳይ ነው! አለ!
ከዚያም አይጡ ወደ አይጥነት መመለሱ ግድ ሆነና ዛሬ አምነን ወደተቀበልነው አይጥ ተመለሰ!!
*   *   *
ማንነትን በማናቸውም አጋጣሚና አስገዳጅ ሁኔታ መለወጥ፣ የመርገምት ሁሉ መርገምት ነው! የትኛውንም ዓይነት ፍጡር እንሁን ብለን መከራን እናሳልፍ ብንል፤ ከተፈጥሮአችን ውጪ የረባ ፍሬ አናገኝም ወይም ልዩ ፍሬ አናተርፍም፡፡
አንድ ግብ ጋ ለመድረስ የግድ ሁለት የፍሬ ምንትነት መኖር የለበትም፤ በዚህም ሆነ በዚያ ዘመን፤ በዚህም ሆነ በዚያ ቦታና ወቅት ልናገኝ የምንችለውን ነገር በዛሬ ሽኩቻ አናክሽፈው! ከህብረት ውጩ መከፋፈል ፋይዳ የለውም፡፡
ሙግታችንና ክርክራችን ተሰብስቦ ሲታሰብ ጥቅሙ “በግልፅም መረጃ” መንፈስ ታላቅ ነው ሊባል ቢችልም፤ “ለማን እየጠቀመ ነው?” የሚባለውን አንድምታ አለማሰብ ከንቱ ቦታ ይጥለናል! የፓርቲዎች ሁሉ ውክቢያና “ጫጫታ” ስለምን በአሁኑ ወቅት ሆነ? ብሎ መጠየቅ የአባት ነው፡፡ ስለማንስ ጥቅም? “ምርጫ አያስፈልግም!” ከሚል አስተሳሰብ እስከ “ምርጫ ከተሳተፍን ግልፅ አቋም፣ ግልፅ ማንነት፣ ግልፅ ውክልና ሊኖረን ይገባል!” እስከሚለው ድረስ መወያየት አለብን ማለት አገራዊ ጥያቄ ነው! ስንተዋወቅ - አንተናነቅ ድረስ ማሰብ ቢቻል ግን መልካም ነው!
የምረጡና ካርድ ውሰዱ ውትወታ ስሜት፣ የወጣት እንቅስቃሴ (በድሮው አባባል የአኢወማ ግዳጅ)፣ የሴቶች ጥያቄ፣ ድህነት ቅነሳና ልማት… ወዘተ፡፡ የእስከ ዛሬው እያንዳንዱ መንግስት ተደጋጋሚ (Replica) ነገሮች ቢመስሉም፣ ዲሞክራሲ ሂደት እንጂ ቁርጥ ክፍያ ስላልሆነ “ባመጣህበት ውሰደው” የሚለው የነጋዴ ቋንቋ የግሎባላይዜሽን አንዱ ገፅታ ነው እንለዋለን!
መተቸትንና መተቻቸትን ለማይቀበል ሥርዓት፤ ይሄን ተቀበል፣ ይሄንን አትሻ ለማለት ብዙ እንግልት እንዳለበት፣ ስለ ዲሞክራሲ ብለህ ይሄን እሻ፣ ይሄን አትሻ ብሎ አጉል እሰጣ ገባ ውስጥ መግባት ቢያንስ የዋህነት ነው፡፡ ስለዲሞክራሲ፣ ስለፍትህ፣ ስለሰብዓዊነና ህዝባዊ መብት፣ ስለሙስና አደጋ ለማውራት የተገፋው፣ የተበደለውና መብት አጣሁ የሚለው ወገን ተናጋሪ፣ ካልሆነና ብሶቱን ካላስረዳ፣ በገዢው ፓርቲስ፣ በተቃዋሚስ ወገን ማን አቤት ይላል? “ሁሉም ፈረስ ላይ ከወጣ ማን ገደል ያሳያል?” የሚለው ተረት ቁምነገሩ ይሄው ነው ጎበዝ!


Published in ርዕሰ አንቀፅ

የባቡር ሐዲዱን ያለ ጫማ ማቋረጥ ለከፋ አደጋ ያጋልጣል
የባቡር መስመሩ የዲዛይን ማሻሻያዎች ሊደረጉበት ይገባል -ባለሙያዎች

      የአዲስ አበባ ከተማ የቀላል ባቡር ፕሮጀክት ሥራ ከሞላ ጎደል በመጠናቀቁ በነገው ዕለት የቅድመ አገልግሎት ሙከራ ሊያካሂድ ነው፡፡ ታላላቅ የመንግስት ባለስልጣናትን፣ ታዋቂ ግለሰቦችንና የመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎችን በሚያካትተው የቅድመ አገልግሎት ሙከራ ቃሊቲ ጉምሩክ አጠገብ ከሚገኘው የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር ዲፓ ግቢ ተነስቶ እስከ መስቀል አደባባይ ባለው የባቡር መስመር ላይ ያደርጋል፡፡
በዚህ ዓመት አጋማሽ ላይ ግንባታው ሙሉ በሙሉ ተጠናቆ ወደ ስራ ይገባል የተባለው  የቀላል ባቡር ፕሮጀክት፤ በአንዳንድ አካባቢዎች የግንባታ ሥራው ገና ያልተጠናቀቀ ቢሆንም ግንባታው በተጠናቀቀባቸውና የኤሌክትሪክ መስመር ዝርጋታ ሥራው ባለቀባቸው አካባቢዎች በተለይም ከቃሊቲ ዲፓ እስከ መስቀል አደባባይ በሚደርሰው መስመር ላይ የኤሌክትሪክ ኃይል ተለቋል፡፡ የኤሌክትሪክ ኃይል በተለቀቀበት አካባቢ መግባትና የባቡር ሃዲዱን ያለ ጫማ በባዶ እግር ማቋረጥ እጅግ ለከፋ አደጋ ሊያጋልጥ እንደሚችል ተገልጿል፡፡
ህብረተሰቡ በባቡር መስመር አጠቃቀሙ ላይ በቂ ግንዛቤ እንዲኖረው ባለመደረጉና ስለ ጉዳዩ በበቂ ሁኔታ በመገናኛ ብዙሃን አለመነገሩ የሚያደርሰውን አደጋ የከፋ እንደሚያደርገውም አስተያየት ሰጪዎች ተናግረዋል፡፡
አዲሱ የቀላል ባቡር ፕሮጀክት የከተማዋን ውበት የሚያጠፉ፣ ለእግረኛም ሆነ ለተሽከርካሪዎች  የማያመች እንደሆነ የጠቆሙት አስተያየት ሰጪዎች ግንባታው በበቂ ጥናትና ባለሙያ የተሰራ ነው ለማለት እንደሚያስቸግር ተናግረዋል፡፡ የባቡር መስመር ግንባታው ከተማዋን ለሁለት የከፈለ፣ እግረኛውንም ሆነ ተሽከርካሪዎችን ግምት ውስጥ ያላስገባና በከተማዋ ነዋሪዎች ላይ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮችን የሚያስከትል እንደሆነም ነዋሪዎች ይገልፃሉ፡፡
ለሃያ ስድስት ዓመታት ኑሮአቸውን በካናዳ ያደረጉትና በያዝነው ወር መጀመሪያ ላይ ወደ አገራቸው መምጣታቸውን የገለፁልን አቶ አብርሃም ተስፋዬ፤ የቀላል ባቡር ትራንስፖርት በአገራችን መጀመሩ ደስ የሚያሰኝ መሆኑን ጠቁመው በከተማዋ ውስጥ የሚታየውን የትራንስፖርት እጥረት በእጅጉ የሚቀርፍ እንደሆነም ተናግረዋል፡፡ የባቡር መስመሩ ግንባታ የተካሄደበት መንገድ ግን በየትኛውም ዓለም የሌለና በእጅጉ ያስገረማቸው እንደሆነ ገልፀዋል፡፡
“በርካታ አገራትን የማየት ዕድሉን አግኝቻለሁ፡፡ በብዙዎቹ የባቡር ትራንስፖርቶችም ስጠቀም ኖሬአለሁ፡፡ እዚህ አገር እንዳየሁት አይነት የባቡር መስመር ግን አይቼ አላውቅም፡፡ በሌላ ዓለም የባቡር መስመሮች ዝርጋታ አብዛኛውን ጊዜ ከመኪና መስመሩ ጋር እኩል በሆነ ሌቭል የሚሠራ ነው፡፡ ተንጠልጣይ መስመሮች በተወሰኑ ቦታዎች ላይ ሊኖር ይችላል፡፡ ሙሉ በሙሉ ከተማውን ለሁለት ከፍሎ ግንብ አጥር እያደረጉ የባቡር ሃዲዱን በተንጠልጣይ ድልድዮች ላይ የሰሩ አገራት ግን ከኢትዮጵያ በስተቀር አላጋጠመኝም፡፡ ባለሙያ ባለመሆኔ ሙያዊ የሆኑ ነገሮችን ለመናገር ባልችልም ከተማውን ለሁለት ከፍሎ ያጠረው ግንብ ግን የህብረተሰቡን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ኑሮ በእጅጉ የሚጐዳ መሆኑን ለመናገር እችላለሁ” ብለዋል፡፡
ስማቸው እንዲገለፅ ያልፈለጉና በአንድ አለማቀፋዊ ድርጅት ውስጥ የሚሰሩ የኮሙኒኬሽን ኤክስፐርት ስለዚሁ ጉዳይ በሰጡን አስተያየት፤ የተለያዩ የአውሮፓንና በርካታ የአፍሪካ አገራትን በስራቸው አጋጣሚ የማየት ዕድሉን እንዳገኙ ጠቅሰው፤ በአገራችን የተሰራውን የባቡር ሃዲድ የሚመስል ግን በየትኛውም አገር እንዳላጋጠማቸው ተናግረዋል፡፡
“የባቡር መስመሮች እንዲህ እንደ አገራችን ከተማን ለሁለት በሚከፍልና ለእግረኛም ሆነ ለአሽከርካሪዎች አመቺ ባልሆነ መንገድ ተሰርተው አላየሁም፡፡ ባለሙያዎቹ ግንባታውን ሲያካሂዱ እነዚህ ጉዳዮች ላይ ትኩረት አድርገው ግንባታው የከተማዋን ውበትና የነዋሪውን ምቾት በጠበቀ መልኩ እንዲካሄድ ማድረግ ይገባቸው ነበር ብለዋል፡፡ በመኖሪያ አካባቢያቸው ባለ የህፃናት ማቆያ ውስጥ ህፃን ልጇን የምታውል እናት፤ ልጇን ወደ ማዋያው ለማድረስ ቀደም ሲል ከቤቷ በራፍ ላይ የሚገኘውን አስፋልት ማቋረጥ ብቻ ይጠበቅባት ነበር ያሉት ኤክስፐርቱ፤ በአሁኑ ወቅት ግን  በባቡር መንገዱ ምክንያት ልጇን በሁለት ታክሲዎች ሄዳ በወዲያኛው ማዶ በሚገኘው የህፃናት ማዋያ ውስጥ ለማስገባት መገደዷን በምሳሌነት ጠቅሰው ይህ ከጊዜ፣ ከገንዘብና ከጉልበት አኳያ በነዋሪው ላይ የሚያደርሰውን ጉዳት ያሳያል ብለዋል፡፡
ይህን ሃሳብ የጎጃም በረንዳው ነዋሪ አቶ አብዮት አሰፋም ይጋሩታል፡፡ “ለዓመታት በንግድ ቤትነት (በቡና ቤት ንግድ ድርጅትነት) ሳስተዳድረው ለቆየሁት ድርጅቴ እገለገልበት የነበረውና ከቡና ቤቴ ፊት ለፊት ይገኝ የነበረው መጋዘን በባቡር መስመር ዝርጋታው ምክንያት እንኳን በእግር በተሽከርካሪም የማይደረስበት ሩቁ ሆኗል፡፡ ለቡና ቤቱ የሚያስፈልጉ ነገሮችን ከመጋዘኑ ለመውሰድ በመኪና ሀብተጊዮርጊስ ድልድይ ድረስ ሄጄ መዞር ይኖርብኛል፡፡ ይህ ደግሞ በእጅጉ አስቸጋሪና ለስራዬም እንቅፋት የሆነ ጉዳይ ነው ብለዋል፡፡
በጦር ኃይሎች ሆስፒታል አካባቢ በስራ ላይ እያለ ያገኘሁት ዋና ሳጅን አበራ ድረስ የተባለ የትራፊክ ፖሊስ ስለጉዳዩ አስተያየት እንዲሰጠኝ ጠይቄው፤ በጦር ኃይሎች አካባቢ የግንባታ ስራው ገና አለመጠናቀቁን ገልፆ ግንባታው ለእግረኛም ሆነ ለአሽከርካሪ አመቺ በሆነ መንገድ የተሰራ አለመሆኑ የትራፊክ ፍሰቱን አስቸጋሪ ሊያደርገው ይችላል የሚል ግምት እንዳለው ጠቁሟል፡፡ በከፍተኛው ፍርድ ቤት ያገኘኋቸው የህግ ባለሙያ በበኩላቸው፤ “ፍርድ ቤቱ በርካታ አቅመ ደካሞች ሁሉ የሚስተናገዱበት መንግስታዊ ተቋም ነው፡፡ ባለጉዳዮች መረጃዎችን ፎቶኮፒ አድርገው እንዲያመጡ ሲነገራቸው የት ሄደው ማድረግ እንደሚችሉ ይጠይቁናል፡፡ የት እንበላቸው፡፡ ከተማዋ እንደሆነ በበርሊን ግንብ ታጥራለች፤ አንዲት ወረቀት ኮፒ ለማድረግ ታክሲ ይዘው ጦር ኃይሎች ድረስ መሄድ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ግንቡ በተመጣጣኝ ዋጋ ለፍርድ ቤቱ ሰራተኞችና ለባለጉዳዮች ምግብ ያቀርቡ የነበሩ ምግብ ቤቶችንም ጭምር ከጨዋታ ውጪ ያደረገ በመሆኑ ጉዳቱ ለባለጉዳይ፣ ለሰራተኛውና ለሆቴል ባለቤቶችም ተርፏል” ብለዋል፡፡
ከጦር ኃይሎች መስቀል አደባባይ፣ ዑራኤል፣ ሃያ ሁለት መገናኛ፣ ጉርድ ሾላ፣ ሲኤምሲና ሃያት ድረስ፣ ከጊዮርጊስ አውቶብስ ተራ ሰባተኛ፣ አብነትና ጦር ኃይሎች ድረስ የሚዘልቀው የቀላል ባቡር መስመሩ፤ በየሰባት መቶ ሜትር ርቀት የእግረኛና የተሽከርካሪ ማቋረጫ እንደሚኖረው ተገልፆ የነበረ ቢሆንም አሁን ባለው ሁኔታ የእግረኛም ሆነ የተሽከርካሪ ማቋረጫን ለማግኘት ከሁለት ኪሎ ሜትሮች በላይ መጓዝ ያስፈልጋል፡፡ የባቡር መስመር ግንባታውን አስመልክቶ ሙያዊ አስተያየት እንዲሰጡን የጠየቅናቸው አርክቴክት ሚካኤል ሽፈራው፤ የባቡር መስመሮች በበርካታ የዓለም አገራት ሲሰሩ የመሬቱን አቀማመጥ ተከትለው መሬት ለመሬት በመሄድ፣ ከአስፋልት መስመሮች ጋር እንዲሰሩ የሚደረጉ መሆኑን ጠቁመው፤ በአገራችን የተሰራውን ዓይነት ግንባታ ለመስራት የመሬቱ  ወጣ ገባነት የሚያስገድድ መሆኑን ገልፀዋል፡፡
“የአዲስ አበባ የመሬት አቀማመጥ ወጣ ገባነት ያለበት በመሆኑ፣ ይህንን ለመጠበቅ ሲባል የባቡር ሃዲዱን ከመሬት በላይ ማንጠልጠል ግድ ሊሆን ይችላል፡፡ ስሎፕ በባቡር መንገድ ግንባታ ላይ እጅግ አስፈላጊና ወሳኝ ነው፤ ሆኖም ሌሎች አርክቴክታል መንገዶችን ተጠቅሞ፣ መንገዱ ለባቡሩም ለእግረኛውም ሆነ ለተሽከርካሪ አመቺ ሊሆን የሚችልበትን መንገድ መጠቀም ይቻላል ብለዋል፡፡ የኤሌክትሪክ ባቡሮች በባህርያቸው ድምፅ አልባዎች ናቸው ያሉት አርክቴክቱ፤ በድንገት ሊደርሱና በሃዲዱ ላይ በሚያቋርጡ ሰዎች ላይ አደጋ ሊያደርሱ ይችላሉ፡፡ በዚህም ምክንያት መንገዶቹ ታጥረው እግረኞች እንዳይገቡበት መከልከሉ ተገቢ ቢሆንም የእግረኞችና የተሽከርካሪዎች ማቋረጫ መንገድ ያስፈልጋቸው ነበር ብለዋል፡፡ “የባቡር መስመሩ የዲዛይን ችግሮች አሉበት፤ የዲዛይን ችግሩ ደግሞ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮችን ማስከተሉ አይቀሬ ነው፤ እንደቀለበት መንገድ ማለት ነው፡፡ የዲዛይን ችግሮቹ ግን ዘለዓለማዊ ናቸው ማለት አይደለም፡፡ ሊሻሻሉና ሊቀየሩ የሚችሉ ናቸው፡፡” ያሉት አርክቴክቱ፤ በሂደት የባቡር ትራንስፖርት አገልግሎቱ እየተሰጠም ማሻሻያዎች ሊደረጉ የሚችሉበት መንገድ ይኖራል ብለዋል፡፡ በባቡር መስር ዝርጋታው ላይ የመንገድ መብራቶች ጉዳይ እየተዘነጋ ያለ ይመስላል ያሉት ባለሙያው፤ የመንገድ መብራት የሚመስሉ ነገሮች በመስመሩ ላይ አለመታየታቸው ያልተለመደ ነገር ነው ብለዋል፡፡ በተንጠልጣይ ድልድዮቹ ስር ያሉ ክፍት ቦታዎች ለእግረኛም ሆነ ለተሽከርካሪ የማይሆኑ መሆናቸውን የጠቆሙት አርክቴክቱ፤ በሌላው ዓለም እነዚህ ቦታዎች ለመዝናኛነት የሚያገለግሉ እንደሆኑ ተናግረዋል፡፡ “እነኚህን ቦታዎች በኃላፊነት ተረክቦ ለሚያስተዳድር አካል በመስጠት መዝናኛዎች፣ ሰዎች አረፍ ብለው ከተማውን እያዩ የሚጫወቱባቸው ቦታዎች ማድረግ እንደሚቻል፣ ይህ ካልሆነ ግን ቦታዎቹ የቆሻሻ መጣያና የወንጀል ፈፃሚዎች መሸሸጊያ በመሆን ለነዋሪው ከፍተኛ ስጋት ሊሆኑ ይችላሉ” ባይ ናቸው፡፡
በነገው ዕለት የቅድመ አገልግሎት ሙከራ የሚያደርገው የአዲስ አበባ ከተማ የቀላል ባቡር ፕሮጀክት፤ በተለያዩ አካባቢዎች በተለይም በጦር ኃይሎች፣ በአውቶብስ ተራ፣ በሰባተኛ፣ አብነት አካባቢ ግንባታው ያልተጠናቀቀ ሲሆነ ለአቅመ ደካሞችና ለህሙማን ይሰራል የተባለው የመወጣጫ (ሊፍት) ግንባታ ግን በየትኛውም መስመር አልተጀመረም፡፡ በእነዚህ ጉዳዮች ዙሪያ ማብራሪያ የጠየቅናቸው የኮርፖሬሽኑ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ደረጀ ተፈራ፤ ለባቡሩ የቅድመ አገልግሎት ሙከራ በስራ መወጠራቸውን ምላሽ ሊሰጡን እንደማይችሉ ገልፀውልናል፡፡

Published in ዜና

        ባለፈው ሚያዚያ የታሰሩት ሦስት ጋዜጠኞችና ስድስት የዞን ዘጠኝ ጦማሪዎች ላይ አቃቤ ህግ ያቀረበው የሽብር ክስ እንዲቀጥል ሰሞኑን በፍ/ቤት መፈቀዱ እንዳሳሰበው የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የገለፀ ሲሆን፤ የክሱ ሂደት በግንቦቱ ምርጫ ተአማኒነትና ዲሞክራሲያዊነት ላይ አሉታዊ ተፅእኖ ያሳድራል ሲል ነቀፈ፡፡ የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሐሙስ እለት ባወጣው መግለጫ፤ በኢትዮጵያ የፀረ ሽብር ህጉ ላይ ቀጥተኛ ትችት ባይሰነዝርም፤ የህጉ አተገባበር ግን በህገመንግስት የተረጋገጡ የፕሬስ እና የሐሳብ ነፃነቶችን የሚቃረን እንደሆነ ጠቁሟል፡፡ ከዘጠኙ ጋዜጠኞችና የኢንተርኔት ፀሐፊዎች በተጨማሪ፣ ካሁን ቀደም ሌሎች ጋዜጠኞች፣ የፖለቲካ አንቀሳቃሾችና የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮችም በፀረ ሽብር ህጉ እንዲከሰሱ መደረጋቸውን የሚኒስቴሩ መግለጫ አስታውሷል፡፡
ይህም፤ የህጉ አተገባበር፣ በህገ መንግስቱ የተረጋገጡ የፕሬስና የሃሳብ ነጻነቶች ላይ ጉልህ ጥያቄዎችን አስነስቷል ብሏል፡፡
የፕሬስ፣ የሃሳብ ነጻነቶች የአንድ ዲሞክራሲያዊ ማህበረሰብ መሰረታዊ ባህሪያት ናቸው ያለው መግለጫው፤ የኢትዮጵያ መንግስት ለእነዚህ ነጻነቶች መከበርና ለዲሞክራሲ ግንባታ ቁርጠኝነት እንዲያሳይ ጥሪ አቅርቧል፡፡
የዘጠኙ ጋዜጠኞችና የኢንተርኔት ፀሐፊዎች የፍርድ ሂደት ፍትሃዊነትና ግልፅነት የተላበሰ፣ እንዲሁም ከአገሪቱ ህገ መንግስቱና ከአለማቀፍ የሰብዓዊ መብት ስምምነቶች ጋር በማይጣረስ መልኩ እንዲካሄድም ሚኒስቴሩ በመግለጫው ጠይቋል፡፡ የፍርድ ሂደቱ ከፖለቲካዊ ተጽዕኖ የጸዳና ለህዝብ እይታ ክፍት እንዲሆን ማድረግ ይገባል ብሏል - መግለጫው፡፡

Published in ዜና

አዲሶቹ የአንድነትና መኢአድ አመራሮች ከቀድሞዎቹ ጋር በጋራ እንሠራለን አሉ
    እውቅና የተነፈገው በእነ አቶ በላይ በፍቃዱ የሚመራው የአንድነት ፓርቲ አመራር ትናንት 8 ሰአት ላይ በፓርቲው ጽ/ቤት መግለጫ ለመስጠት ጋዜጠኞችን ጠርቶ የነበረ ቢሆንም ከመግለጫው በፊት በፀጥታ ሃይሎች ፅ/ቤቱን ለቅቆ እንዲወጣ ተደርጓል፡፡
“የመድብለ ፓርቲ ስርአት እንዳበቃ አረጋግጠናል” በሚል ርዕስ መግለጫ ሊሰጥ እንደነበር የጠቀሱት የቀደሞው የፓርቲው የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ አስራት አብርሃ፤ መግለጫው የአንድነት አባላት ምርጫ ቦርድ ፓርቲውን እንዲመራ እውቅና ለሠጠው የእነ አቶ ትዕግስቱ አወሉ አመራር እውቅናና ድጋፍ እንዳይሰጡ የሚጠይቅ ነው ብለዋል፡፡
የአመራር ቡድኑ ሠላማዊ ትግሉን በልዩ ልዩ አቅጣጫዎች ለማከናወን ማቀዱን የገለፁት አቶ አስራት፤ አዲስ ፓርቲ መመስረት አሁን የማይቻል በመሆኑ “ትግሉን ወደ ኢትዮጵያ ህዝብ መልሰናል” ብለዋል፡፡ አመራሩ ቦርዱ ላይ ክስ እንደሚመሰርትም ተናግረዋል፡፡
በሌላ በኩል ምርጫ ቦርድ ዕውቅና የሰጣቸው አመራሮች፤ ከቀድሞዎቹ ጋር በጋራ ለመስራት ዝግጁ መሆናቸውን ገልፀዋል፡፡ “ከእነ አቶ በላይ ጋር አብሮ ለመስራት በኛ በኩል ሙሉ ፍቃደኝነት አለ” ያሉት አቶ ትዕግስቱ፤ የተቀየረው አመራሩ ብቻ በመሆኑ የአንድነት መዋቅሩም ሆነ የአባላቱ አደረጃጀትና ተሣትፎ ይቀጥላል ብለዋል፡፡ “ፓርቲው ሁለት ቦታ አልተከፈለም” ያሉት አቶ ትዕግስቱ፤ “አንድነትን ማን ይምራ? የሚለው ምላሽ በማግኘቱ ፓርቲው ወደ ምርጫው ለመግባት በተንጠቀቅ ያዘጋጃቸውን እጩዎች ያስመዘግባል ብለዋል፡፡ በእነ አቶ በላይ በፍቃዱ ቡድን ውስጥ ከነበሩት አመራሮች መካከልም በካቢኔያቸው የሚካተቱ የትግሉ ልምድ ያላቸው አመራሮች እንዳሉ አቶ ትዕግስቱ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡
“አንድነትን መምራት አይችሉም” ሲል ውሣኔ ያስተላለፈባቸው የእነ አቶ በላይ ካቢኔ አባልና የፓርቲው የህዝብ ግንኙነት ምክትል ሃላፊ የነበሩት አቶ አስራት አብርሃ በበኩላቸው፤ በነገው እለት ሊያከናውኑ አቅደው የነበረው ሠላማዊ ሠልፍ አመራሩ እውቅና በመነፈጉ መሠረዙን ጠቁመው፤ የአቶ በላይ ስራ አስፈፃሚ በፓርቲው ጉዳይ በቀጣይ እንደሚመክር አስታውቀዋል፡፡
የመላ ኢትዮጵያውያን አንድነት ድርጅት (መኢአድ)ን እንዲመሩ እውቅና የተሠጣቸው አቶ አበባው መሃሪ፤ የፓርቲውን ጽ/ቤት ለማስመለስ ጥረት እንደሚያደርጉ ጠቁመው ወደ ምርጫው በመግባት ጉዳይ ላይ አመራሩና የላዕላይ ምክር ቤት ተሰብስቦ ውሣኔ ይሰጥበታል ብለዋል፡፡
በፓርቲው አመራር መካከል ችግሩ ከተፈጠረ በኋላ የፓርቲው ህልውና ያሳሰባቸው ግለሰቦች ሁለቱን አካላት ለመሸምገል ጥረት አድርገው እንደነበር የጠቆሙት አቶ አበባው፤ በእነ አቶ ማሙሸት እምቢተኝነት ሊሣካ አልቻለም ብለዋል፡፡
ጥቅምት 27 ቀን 2007 ዓ.ም የተካሄደው የፓርቲው ጠቅላላ ጉባኤ እነ አቶ ማሙሸት ወደ ፓርቲው ሲመለሱ የባህሪ ለውጥ ስለማድረጋቸው ለመገምገም ለሁለት አመት በተራ አባልነት በፓርቲው እንዲቀጥሉ ወስኖ እንደነበርና ኢ/ር ሃይሉ የጉባኤውን ውሣኔ ሽረው ግለሰቦቹን ወደ አመራር እንዳመጧቸው የገለፁት አቶ አበባው፣ በቀጣይ እነ አቶ ማሙሸት በጉባኤው ውሣኔ መሠረት በፓርቲው ያላቸው ተሣትፎ የተራ አባልነት እንደሚሆን አስረድተዋል፡፡
በጉዳዩ ላይ አቶ ማሙሸት አማረ አስተያየታቸውን እንዲሰጡን በተደጋጋሚ ያደረግነው የስልክ ሙከራ ስልካቸው ዝግ በመሆኑ ሳይሳካ ቀርቷል፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ፤ ፓርቲዎቹ በውስጣቸው ተፈጥሯል የተባለውን የአመራር ክፍፍል ችግር ቀርፈው ወደ ቦርዱ እንዲቀርቡ ለ3 ጊዜያት ያህል የጊዜ ገደብ ሰጥቶ የነበረ ሲሆን፤ ለሁለት ሣምንት የሰጠው የመጨረሻው የጊዜ ገደብ ባለፈው ማክሰኞ መጠናቀቁን ተከትሎ ከትናንት በስቲያ ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ፣ ሁሉም ወገኖች ችግራቸውን ለመፍታት የሄዱበትን ርቀት ገምግሞ ውሣኔ ማሳለፉን አስታውቋል፡፡
ቦርዱ አንድነት ፓርቲን በተመለከተ ባሣለፈው ውሣኔ፣ እነ አቶ በላይ ፍቃዱ ፈጽመውታል ያለውን ግድፈት በ7 ነጥቦች ዘርዝሮ አስቀምጧል፡፡ አመራሮቹ በጠቅላላ ጉባኤ መመረጥ ሲገባቸው የምርጫ አዋጁን በመጣስ በብሄራዊ ምክር ቤት መመረጣቸው፣ ፓርቲው ያካሄደውን ጠቅላላ ጉባኤ ለ7 ወራት ለቦርዱ ሳያሳውቅ በቦርዱ ጥያቄ ተገዶ ማቅረቡ፣ አስመራጭ ኮሚቴ ሳይሰየምና የእጩ ጥቆማ ሳይቀርብ ሚስጢራዊ ባልሆነ ድምፅ አሰጣጥ የፓርቲው ፕሬዚዳንት መመረጣቸው፣ የቀድሞው ፕሬዚዳንት ስልጣናቸውን የለቀቁበት ምክንያት ሳይመረመር ወደ ሌላ ስራ አስፈፃሚ ምርጫ መገባቱ እንዲሁም፣ በፓርቲው ደንብ ላይ ፕሬዚዳንቱ ቢለቁ ምክትል ፕሬዚዳንቱ የፓርቲውን ስራ እንደሚያስቀጥል የተደነገገው ህግ መጣሱን ቦርዱ አስቀምጧል፡፡ የቦርዱን ትዕዛዝ ያለማክበርም እነ አቶ በላይ ፈፅመውታል ከተባለው ግድፈት አንዱ ነው፡፡
በሌላ በኩል እነ አቶ ትዕግስቱ አወሉ፤ የምርጫ ቦርድን ትዕዛዝ ተቀብለው ችግሩን ለመፍታት ጥረት ማድረጋቸው፣ የተጣሰው ደንብ ይከበር ማለታቸው ህጋዊ አካሄድ በመሆኑ፣ ጥር 16 ቀን 2007 ዓ.ም ያካሄዱት ጠቅላላ ጉባኤ የተሟላና ፕሬዚዳንቱ በሚስጥራዊ ድምፅ አሰጣጥ የተመረጠ በመሆኑ ቡድኑ ከእነ አቶ በላይ በፈቃዱ በተሻለ የምርጫ ቦርድን ትዕዛዝ አክብሮ ለመንቀሳቀስ በመሞከሩ አንድነትን እየመራ ወደ ምርጫው ይግባ ተብሏል፡፡
መኢአድን በተመለከተ ቦርዱ ባሳለፈው ውሳኔ ጥቅምት 28-30 ቀን 2007 ዓ.ም በተከናወነው ጠቅላላ ጉባኤ ተመርጠናል የሚሉት እነ አቶ ማሙሸት አማረ፤ በፓርቲው ህገ ደንብ መሰረት መዋጮ አለማዋጣታቸው፣ ከፓርቲው የተሰረዙ በመሆኑ የኃላፊነት መስፈርት አለማሟላታቸው፣ የጠቅላላ ጉባኤውን ውሳኔ በህጋዊ  ማህተም አረጋግጠው ለቦርዱ ባለማቅረባቸውና ህገ ወጥ ማህተም ማስቀረፃቸው እንዲሁም የፓርቲው አመራር ማንነት እስኪያስቸግር ድረስ ኢ/ር ኃይሉ ሻወል፣ አቶ አበባው መሃሪ እና አቶ ማሙሸት አማረ ያለ ቦርዱ እውቅና መፈራረቃቸው የህግ ጥሰት ነው ተብሏል፡፡
በሌላ በኩል አቶ አበባው መሃሪ የተመረጡበት የ2005 ዓ.ም ጠቅላላ ጉባኤ መስፈርቶችን ያሟላ በመሆኑ፣ ቦርዱ አቶ አበባው ፓርቲውን እየመሩ ወደ ምርጫው ይግቡ ሲል ወስኗል፡፡
የቦርዱ ውሳኔ በንባብ ከተሰማ በኋላ አንድ ጋዜጠኛ ብቻ ጥያቄ እንዲያቀርብ እድል የተሰጠ ሲሆን የቪኦኤው ጋዜጠኛ መለስካቸው አመሀ “አቶ ትዕግስቱ የተመረጡበት ጠቅላላ ጉባኤ ላይ የተገኙት ጉባኤተኞች የፓርቲው አባላት መሆናቸውን ቦርዱ ሊያረጋግጥልን ይችላል?” የሚል ጥያቄ ያቀረበ ሲሆን የቦርዱ ሰብሳቢ ፕ/ር መርጋ በቃና፤ “በአጠቃላይ ግድፈቶች በሁለቱም ተፈፅመዋል፡፡ የታዩትን ግድፈቶች ደረጃ ነው ቦርዱ ያመዛዘነው፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ የታየው የፓርቲው ህልውና የሚቀጥልበት ሁኔታ ነው፤ ስለዚህ አነስተኛ ግድፈት የፈፀመውና ከቦርዱ ጋር ጤናማ ግንኙነት ያለው፣ ቦርዱ ትዕዛዝ ሲሰጥ ለቦርዱ ትዕዛዝ የሚገዛ፣ የቦርዱን ገለልተኛነት ተቀብሎ የሚያከብረው ነው እውቅና የተሰጠው እንጂ በሁለቱም በኩል ግድፈቶች የሉም ማለት አይደለም” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ 

Published in ዜና
Page 3 of 18