በድምፃዊ ዘለቀ ገሰሰና በአቶ አዲስ ገሰሰ የተሰራው የታዋቂው የሬጌ አቀንቃኝ የቦብ ማርሌ ሐውልት ከሁለት ወር በኋላ በሚደረግ ታላቅ ሥነ-ስርዓት እንደሚቆም አዘጋጆቹ ገለፁ፡
ድምፃዊ ዘለቀ ገሰሰ ለአዲስ አድማስ እንደተናገረው፤ ሐውልቱ ቀደም ሲል የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ በነበሩት አቶ አርከበ እቁባይ በተሰየመውና ገርጂ ኤምፔሪያል ሆቴል ፊት ለፊት በሚገኘው የቦብ ማርሌ አደባባይ ላይ ለማቆም ዝግጅቱ ተጠናቋል፡፡
ሚያዚያ 11 ቀን 2007 ዓ.ም የዳግማይ ትንሳኤ ዕለት በሚደረገው ታላቅ ኮንሰርትና የሀውልት ማቆም ሥነ-ስርዓት ላይ ሪታ ማርሌን ጨምሮ የቦብ ማርሌ ሁለት ልጆች እንደሚገኙና ልጆቹ በኮንሰርቱ ላይ እንደሚዘፍኑ ተገልጿል፡፡
ቀደም ሲል ሃውልቱ በሚከበረው የቦብ ማርሌ የልደት በዓል ወቅት እንዲቆም ታስቦ የነበረ መሆኑን የተናገረው ድምፃዊ ዘለቀ ገሰሰ የቦብ 70ኛ ዓመት የልደት በዓል በጃማይካ ኪንግስተን ከተማ እንዲከበር በመወሰኑና የቦብ ቤተሰቦችም ለበዓሉ ወደ ስፍራው በማምራታቸው ፕሮግራሙ ተሰርዞ ለዳግማይ ትንሳኤ እንዲካሄድ መወሰኑን አስታውቋል፡፡ የቦብማርሌ 70ኛ ዓመት የልደት በዓል ዓመቱን ሙሉ በተለያዩ ዝግጅቶች እንደሚከበርም ድምፃዊው ጨምሮ ገልጿል፡፡  

በእውነት ፊልም ፕሮዳክሽን የተሰራውና በወንድወሰን ይሁብ ተደርሶ በእውነት አሳሳህኝና በደራሲው የተዘጋጀው “የገጠር ልጅ” የተሰኘው ፊልም ነገ ከቀኑ 11፡30 በብሔራዊ ቲያትር በሚካሄድ ሥነ ስርአት ይመረቃል፡፡ ቤተሰቦቿን ለመርዳት ወደ አረብ አገር በስደት ሄዳ ወደ ሀገሯ የተመለሰች አንዲት ወጣት የሚደርስባትንና የሚያጋጥማትን አሳዛኝ የህይወት ፈተና የሚያሳየው ልብ አንጠልጣይ ፊልም ሙሉ ቀረፃው የተካሄደው በአዲስ አበባ ከተማና ሰንዳፋ አካባቢ መሆኑን የፊልሙ ፕሮዲዩሰሮች ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡ በፊልሙ ላይ ተሻለ ወርቁንና ሰለሞን ሙሔን ጨምሮ ከ90 በላይ ወጣትና አንጋፋ ተዋንያን የተሳተፉበት መሆኑ ተገልጿል፡፡

በደራሲ ቃልኪዳን ኃይሉ የተፃፈውና “ለምን አትቆጣም?” የተባለው አዲስ መፅሐፍ ዛሬ ከቀኑ 10 ሰዓት በኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴል እንደሚመረቅ የኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበር አስታውቋል፡፡

ከአዲስ አበባ በቅርብ ርቀት ላይ በምትገኘው ሰንዳፋ ከተማ “ዋን ስቶፕ ሲኒማ” የተሰኘ ዘመናዊ ሲኒማ ቤት ባለፈው ሳምንት ተመርቆ አገልግሎት ጀመረ፡፡ ሲኒማ ቤቱ በ1.7 ሚሊዮን ብር ወጪ የተገነባ ሲሆን ለከተማዋና ለአካባቢው ነዋሪዎች አማራጭ የመዝናኛ ማዕከል ይሆናልም ተብሏል፡፡ ሲኒማ ቤቱ እስከ 500 የሚደርሱ ተመልካቾችን የመያዝ አቅም እንዳለው ተገልጿል፡፡ በከተማው ከንቲባ አቶ ዘገዬ ካሳ የዛሬ ሳምንት ተመርቆ የተከፈተው ዋን ስቶፕ ሲኒማ፤ ለአገሪቱ የፊልም ኢንዱስትሪ እድገት የበኩሉን ድርሻ እንደሚያበረክት የድርጅቱ ባለቤት አቶ ዘላለም ተመስገን ተናግረዋል፡፡

13ኛው የጋለሪያ ቶሞካ ፖርትሬይት አርት የስዕል ኤግዚቢሽን በሚቀጥለው አርብ “ስዕላዊ ቀልድ እና ስዕላዊ ምፀት” በሚል ርዕስ ይከፈታል፡፡ የሰዎችን ምስል በማጋነን አስቂኝና አዝናኝ በማድረግ በሚታወቀው ቴዎድሮስ መስፍን (ቴዲ ማን) የተሰሩ 30 ያህል የሰው ምስሎች በአዝናኝ መልክ የሚቀርቡ ሲሆን ታዋቂ የውጭና የአገር ውስጥ ሰዎች ምስል ተካቶበታልም ተብሏል፡፡ በመጪው አርብ ረፋድ ላይ የሚከፈተው ይህ ፖርትሬት አርት ኤግዚቢሽን፤ ሳር ቤት ካናዳ ኤምባሲ ፊት ለፊት በሚገኘው ቶሞካ አርት ጋለሪ ውስጥ ለቀጣዮቹ ሁለት ወራት ለእይታ ክፍት ሆኖ ይቆያል ተብሏል፡፡

Saturday, 24 January 2015 13:31

ሮሚዮዘ ጁሊየት እና ኢያጎ

12፡ July Face book
ፎቶ …፡- ወጣት ልጃገረድ ሚኒ እስከርት ቀሚስ አድርጋ ትልቅ ሶፋ ላይ እግሯን አጣምራ ትታያለች፡፡
ጓደኞቿ ወዲያው በ Like መዓት አጀቡዋት፡፡
150 Like – 70 Comments
Leul and 69 others have commented
ኮሜንት ሲከፈት፡-
Abebe:- Wow! መቲ እንደዚህ የተሽቀረቀርሽው የት ለመሄድ ነው?
Sol:- እቺ ልጅ የሆነ ሰው cook ሳታደርግ አልቀረችም
Leul:- የጠበስሽውን ቶሎ አግቢውና ጥሬውን እንደኔ ቀቅለሽ አብስይው!...
መቲ:- How dare you insult me on face book ቀንተህ ነው አይደል…እርር ድብን በል!
 Leul:- ቅናት?! Hahaha….ቅናት ፍቅር በተቀናበት ቀናት ነው ባክሽ…እኔ ረስቼሻለሁ! አርፈሽ ጠበሳሽን አጧጡፊ!!!
አበበ :- ሁለታችሁም እረፉ…መነጋገር ካለባችሁ ከ face book ውጭ ተገናኙና አውሩ፡፡ አንተ ልዑል ደግሞ የፈለገ ቢሆን ምናለ…ዝም ብለህ አምሮብሻል ብትላት…ምን ይጐዳሀል?
ልዑል :- ስልኬን አላነሳም ማለቷን እንጂ ታውቃለህ፤ ፌስቡክ ላይ አተካሮ አይመቸኝም፡፡ በአንተ ፊት አሁኑኑ ትንገረኝ Is she seeing somebody?
መቲ:- ከሌላ ሰው ጋር ብሆንስ…ምን ልታደርግ ነው? በአለፈው እንደፈጠርከው አይነት የዱርዬ አንባጓሮ ልትፈጥር ነው? አልፈልግህም ተወኝ!!
አበበ :- ልዑል በእናትህ ተረጋጋ…ነገ እኔ እና አንተ ተገናኝተን እናወራለን፤ አሁን ዝም ብለህ ለመተኛት ሞክር… ከቤት የትም እንዳትሄድ Please
መቲ:- አቤ: በአለፈው ያደረገውን ነግሬሀለሁ አይደል…
አበበ:- አይ ከሰው ሰምቼአለሁ…በቃ አሁን ተረጋጊ I will talk to him tomorrow…sleep tight
(በቴክስት መልዕክት አበበ ለመታሰቢያ:- ግን “Are you seeing somebody else?” ብሎ ላከላት፡፡ መልስ ሳትሰጠው ቀረች፡፡)
“የሆነ ልጥጥ ሰው cook አደረግሽ እንዴ?” ብሎ ደገመላት
መቲ :- አንተም እንደ ሌላው ሰው ወሬ መፍተል ጀመርክ (መለሰችለት)
2፡00 PM Dec 21
 ፎቶ :-
ወጣት፤ ሸበላ…ጠይም መቲን እቅፍ አድርጐ ሲስማት ይታያል፡፡ መቲ እየተሳመች በአንድ አይኗ ወደ ካሜራው እየተመለከተች፣ ግራ እጇን ወደ ፊት ወጣ አድርጋ እየሳየች ነው፡፡ በጣቷ ላይ የጋብቻ ቀለበት ጠልቋል፡፡
ከፎቶው በላይ የሰፈረ መልዕክት :- It is official!
Like – 665  Comment – 50
Comments
ሜሮን - ስለ ሰውዬሽ ሰምቻለሁ…ቀናሁብሽ
ተረፈ :- ሜሪ ከመቅናት …ቀልጠፍ ብለሽ እኔን ማግባት [p]
ሰላም:-   አንተን ማን ያበስላል…አንተ ምግብ አብሳይ (LoL)
መቲ፡- የኔ ቆንጆ ኮንግራ
አበበ “Chat” ላይ መቲን አግኝቶ ስለ ፎቶው አወራት፡፡
አበበ :- አቤት ደስ የሚል ነገር ነው፡፡ አቤት ሰው ሲጠፋ አለመጠየቅ… አቤት እንዴት ያምርባችኋል! አቤት የLike ሽ መብዛት…
እኔ ላይክ ስልሽ ስድስት መቶ ስልሳ ስድስተኛ መሆኔ የታወቀኝ ከተጫንኩት በኋላ ነው፡፡ I hope you will not consider it as a bad omen (p) መቼ ነው ሰርጉ? አንጠራም እንዴ?
መቲ:- ጥር ላይ ነው ብለን እያሰብን ነው ከአቢ ጋር፤ ወደዚህም ቀረብ ሊል ይችላል፡፡
…እ…You know what I want to ask you…ስለዚህ ለምን አንተ ሳልጠይቅህ በፊት አትነግረኝም (በናትህ ስለምን ልትጠይቂኝ ፈለግሽ ብለህ እንዳትለኝ!)
አበበ:- I think you mean about leul (I know) ልዑል ደህና ነው፡፡ በፊት…ከነበረበት ሁኔታ በጣም ይሻላል…Don’t worry ሜዲኬሽኑን እየተከታተለ ነው፡፡
መቲ:- ቤት ሄጄ ልጠይቀው ፈልጌ ነበር…ግን የተወሳሰበ ነገር ሆነብኝ…ቤተሰቦቹ እኔን ምን አድርገው እንደሚያስቡኝ ታውቃለህ አይደል? በኔ ምክንያት የታመመ ነው የሚመስላቸው፡፡ ማንም የእኔን እውነት አይረዳም…Its sad
አበበ:- I think he knows it too…I am sure he doesn’t hate you…
መቲ:- (እያለቀሰች ነው ሞባይሏ ላይ የምትፅፈው) በናትህ እኔ ራሴ ግራ ግብት ብሎኛል፡፡
አበበ:- አንቺ አትጨነቂ…እሱ ምንም አይሆንም…በቃ ፍቅር ይሰምራል ወይ አይሰምርም፡፡ የአንቺና የልዑልን ፍቅር ፈጣሪ አልፈቀደውም፡፡ አሁን ተረጋግተሽ ህይወትሽን በሙሉ መንፈስ ጀምሪ ወይንም ቀጥይ
መቲ:- Is he with his mom and dad
አበበ:- ብዙ ነው ታሪኩ፤ አሁን ግን ሆስፒታል ገብቷል፤ ዛሬ ሄጄ አይቼው ነበር፡፡ አትጨነቂ በጣም ተሽሎታል…እንዲያውም በሌሎቹ በሽተኞች ላይ ሙድ እየያዘ ሲያስቀኝ ነበር…you can’t begin to imagine the Varity of… (ጠሾች) In that አማኑኤል place…በጣም ያሳዝኑሻል…ልብሽ ያነባል፤ ከዛ ደግሞ የሚያደርጉት ነገር ስታስቢው ያስቅሻል፡፡
መቲ:- በናትህ አትንገረኝ…እኔ ራሴ አቢ ከጐኔ ባይኖር…በእነዛ የመጀመሪያዎቹ ወራት አብጄ እዛው መግባቴ አይቀርም ነበር፡፡
አበበ :- አቢ?!...Is that your new man…your husband?
መቲ:- እሱ ባይኖር ከዛ አይነት ስብራት አላገግምም ነበር
አበበ :- (ሊፅፍ የቃጣውን ገታው “I heard your man is stinking rich” ሊላት ነበር፡፡  “I think you deserve a painless life` ብሎ ለውጠው)   
መቲ:- Yes I think so too…የልዑል ፍቅር ህመሙ አይቻልም፡፡ ህመሙ ብሶ ሊያጠፋፋን ሆነ I had to move away
አበበ፡- Any way let me know about the “big day”
መቲ፡- I will … ደውልልኝ … ቢያንስ የልዑልን ሁኔታ ማወቅ አለብኝ  
አበበ፡- He will pull through, ልዑል “ሰርቫይቨር” መሆኑን መቼም እኔ ላንቺ አልነግርሽም
መቲ፡- I blame myself
አበበ፡- ምን ማለትሽ ነው? ኧረ በፈጠራችሁ ሮሚዮ እና ጁሊየትን አትሁኑብኝ … ልዑል ራሱን በመኮነን ነው ለዚህ አሳዛኝ ደረጃ የበቃው … አንቺ ይሄንን ሀሳብ ከጭንቅላትሽ አውጭው
መቲ ፡- እንደማይሆን ስለሆነብኝ እንጂ እንደምወደው ታውቃለህ .. ክጄው አይደለም
አበበ ፡- አቦ ጠንከር በይ … ከፊት ለፊትሽ ያለውን ህይወት ተመልከቺያ… እንዴ!!! በተረፈ ስራ አሸወይና ነው አይደል? አዎ እንደምትይኝ ስለማውቅ በዚሁ ልቀንጠስ cheers!
04፡00 Nov – face book
ፎቶ:-
ሙሽሮች እጅ ለእጅ ተያይዘው በሜዳ ላይ እየሮጡ፡፡ ሴቷ (መቲ) ቀሚሷ እንዳያደናቅፋት ሰብስባዋለች፡፡
Just married!
Like - 830 comments – 100
አበበ ፎቶውን እየተመለከተ እንባ ተናነቀው፡፡ በስንት ቀኑ ነው የፌስ ቡክ ገፁን የከፈተው፡፡ ያመለጡትን የወሬ ቀናት ያህል ወደ ኋላ ተመልሶ የመቲን መልዕክቶች ተመለከተ፡፡ ስታፈላልገው ከርማለች፡፡ ወደሱ መልዕክት ሳጥን ብዙ አረፍተ ነገሮች ሰዳለች፡፡
ልዑል መሞቱን ከሰማበት ቅፅበት ጀምሮ ስልኩን በጥንታዊ አገልግሎቱ እንጂ በፌስቡክ የወሬ ፋሲካነቱ ስለጠላው ፆመው፡፡ የማንንም ትርኪ ምርኪ ወሬ ሲለቃቅም … አብሮ አደግ ጓደኛው ራሱን አንጠልጥሎ ሞቶ ጠበቀው፡፡ ፌስ ቡክን ጠላው፡፡ ፌስ ቡክ ውስጥ ስሜት የለም … ፡፡ ወሬ እና ማስታወቂያ በእያይነቱ ብቻ፡፡ ሞትም ማስታወቂያ ነው ለፌስ ቡክ፡፡
ከቀናት በኋላ አላስችል አለው፡፡ ፌስ ቡክ አካውንቱን በሚንቀጠቀጥ እጁ ከፈተው፡፡ በሞባይሉ ካሜራ ከዚህ ቀደም አጥምዷቸው ከነበሩት የልዑል ፎቶዎች መሀል የሱን ማንነት እንደ ቀድሞው የጉብዝና ዘመኑ … አንገቱን ሳይደፋ በፊት እንደነበረው ይገልፀዋል ብሎ ያሰበውን በገፁ ላይ አኖረ፡፡
“ልዑል … እግዜር በገነት ነብስህን ያኑራት”
Post
የከፈተውን በፍጥነት ዘጋ፡፡
ፌስ ቡኩ ተዘግቶም … መልዕክቶች … likeዎች R.I.Pዎች እየተከታተሉ ሲገቡ በምናቡ ተሰማው፡፡ ተጋድሞ ለተወሰነ ጊዜ ታገሰ፡፡
መቲ የልዑልን ፎቶ ተለጥፎ አይታ ምን ልትል እንደምትችል ለመገመት አልፈለገም፡፡ አይታ ልታደርግ የምትችለው ምን እንደሆነ ማሰብ ከአቅሙ በላይ ነው፡፡ ልቡ ያውቀዋል፤ እውነተኛ ፍላጐቱን፡፡ የፈለገው የማህበረሰቡን ሀዘን (የፌስ ቡክ ሀዘን) በLike ደረሰኝ መልክ መልቀም ብቻ ነው፡፡
መቲ ምናልባት የጫጉላ ሽርሽር ላይ ልትሆን ትችላለች፡፡ ሽርሽር ላይ ያሉ ሙሽሮች ፌስ ቡክ እንዳይጠቀሙ የሚከለክል ኮስታራ ባህል ቢኖር ምናለበት ብሎ ተመኘ፡፡ ግን በቤተመቅደስ ውስጥም በቅዳሴ መሀል ፀሎታቸውን ከፌስቡክ ጋር አጣምረው Post ሲያደርጉ የታዘባቸው ምዕመናን ትዝ አሉት፡፡
ለምን የልዑልን ሞት ለፌስቡክ ማህበረሰብ ማወጅ እንዳስፈለገው ለራሱም አልገባውም፡፡ መሞቱ በማህበረሰቡ ላይ የሚያመጣው አንዳችም ለውጥ የለም፡፡ ለአንዲት የማህበረሰቡ አባል ብቻ ግን ትልቅ ጉዳት ያደርሳል፡፡ በብዙ ሰው የማይጠቀም አንዲቷን ሙሽራ ግን መስበር የሚችል ዜና … Like ለመቁጠር ሲል ሞባይሉ ላይ ለጠፈ፡፡
ምናልባት በፊት፣ በዛ ምሽት ለመቲ .. የላከው ስድስት መቶ ስልሳ ስድስተኛ ውዴታ (Like) ትሆናለች መጥፎ እርግማን ሆና ተመልሳ የመጣችው፡፡ ግን እንደዛ እንዳልሆነም እርግጠኛ ነው፡፡ እንደው ራስህን ርገም ሲለው እንጂ፡፡
ከራሱ ማንነት ውጭ የወሬ አመላላሽ ባህሪን በቅልጥፍና እንዲወጣ ያስቻለው ቴክኖሎጂ በእጁ ላይ አለ፡፡ ፌስ ቡክ ሮሚዮ እና ጁሊየትን ከማገናኘት አገዳድሎ ለማለያየት የበለጠ የሚጠቅም ፈጠራ መሆኑን አመነበት፡፡
አምኖም ስም አወጣለት፡፡ “እያጎ” ብሎ መሰለው፡፡ እያጎ፤ ከኦቴሎ የድራማ ገፀ ባህሪነት ወጥቶ ሮሚዮ እና ጁሊየት መሀል በምን ምትሀት እንደገባ ለመተንተን ግን አቅም አጣ፡፡
እያጎ ግን እኩይ ባህሪውን የሚወተው በሰዎች እጅ ከተገፋ ነው፡፡ Like, Share, Comment .. ብለው ካልነኩት እያጎ ተግባሩን ብቻውን ማከናወን አይችልም፡፡ መሳሪያ ነው፡፡
አበበ ፌስ ቡክን እርም ብሎ ሊተው እንደማይችል ጠንቅቆ አውቋል፡፡ እያጎነትን ለምዷል፡፡ “የበሰበሰ ዝናብ አይፈራም” አለ ለራሱ፡፡ ስልኩን መልሶ አበራ፤ ጥይት መኖሩን አረጋገጠ፡፡ ጥይት የለም፤ ካርድ ገዝቶ ሞላ፡፡
ገፁን ከፍቶ የሚከተለውን ላከ፡፡
2፡00 Dec
አበበ ዘሩ
“ሮሚዮ እና ጁሊየት የሞቱት እጣፈንታቸው ጠማማ ስለሆነ ሳይሆን፣ እያጎ መንገድ አቋርጦ መሀላቸው ገብቶ ነው፡፡ የዘመናችን ምርጥ ወሬ አመላላሽ እያጓችን Face book ተብሎ ይጠራል፡፡ Post!
Like – 10 comment – 1
ብዙም ምላሽ አላገኘም፤ የተወሰኑ “ውዴታዎች” ቆጠረ፡፡ ግን ከሰጪዎቹ ልብ ተፈንቅለው የወጡ እንዳልሆኑ ያስታውቃሉ፡፡ አስር ውዴታዎች .. እየተንጠባጠቡ በእሱ ገፅ ላይ ተጠራቀሙ፡፡ አላረኩትም፡፡ የሳይበሩ ሰማይ ተበስቶ በLike መአበል ተጠርጎ ሲወሰድ ለማየት ጓጉቷል፡፡
እንደገና ገፁን ከፈተ፡፡ እንደገና ፃፈ፡፡
2፡10 Dec
አበበ ዘሩ
ልዑል እና መቲን የገደልኩት እያጎ እኔ ነኝ፡፡ ለመግደል የተጠቀምኩበት መሳሪያ ደግሞ ይኼ ፌስ ቡክ የተባለ ፈጠራ ነው፡፡
Like – 100 comment 28
መቲ ሰምታ ምን ታደርግ ይሆን እያለ እያሰበ … ስልክ ደወለችለት፡፡ የለጠፈውን አንብባለች፣ የልዑልንም ሞት ተረድታለች፡፡ የልዑልን ሞት በለዘብታ አስተዛዘነች፡፡ አሁን መጨረሻ ላይ የላከው መልዕክት ግን አልገባትም፡፡ ከዚህ በተረፈ ያወራችለት ከራሷ ሰርግ ጋር ስለተያያዙ ነገሮች ብቻ ነው፡፡ ብዙም አላካበደችም፡፡ ሮሚዮ እና ጁልየት በፌስቡክ ዘመን ያን ያህል ትራጀዲ አይፈጥሩም፡፡ የፍቅረኛሞች መለያየት…የአፍቃሪ ማበድ…አብዶም መሞት…ለፌስ ቡክ ትውልድ ቀለል ብሎ የሚታይ ነው፡፡ ሁሉም እለታዊ … ወረታዊ ወሬዎች ናቸው፡፡
እያጐም የሚፈጥረው አሻጥር በተወሰኑ “ላይክ” እና “ኮሜንቶች” ውስጥ ተድበስብሶ ይመክናል፡፡
በአንዱ ስቃይ ላይ ሌላው ልደቱን ያውጃል፡፡ ሞቱም ውልደቱም ሰርጉም ሀዘኑም ስድቡም ሙገሳውም እንደ ቀላል በአዲስ ወሬ ታጥበው ያልፋሉ፡፡ አዲስ ወሬ ይመጣል፣ አዲስ ቁጣ፣ አዲስ ግጥም፣ አዲስ ፎቶ፣ አዲስ ቀልድ…ለእያንዳንዱ አዲስ ገፅ የሚሰጡ ውዴታዎችም ሆነ አስተያየቶች አያልቁም…፡፡
ለፌስ ቡክ ማህበረሰብ ነገም ሌላ ቀን ነው፡፡
Like   Comment   Share
ለፌስቡክ ማህበረሰብ ነገም ሌላ ቀን ነው፡፡

Published in ልብ-ወለድ

ኢ.ኤ ግሩንግ ላምቦርን፤ ግጥምን በዜማ የተነከረ ስዕል አድርገው ያዩታል፤ ነፍስ በሙዚቃው ዳንስ ሰክራ ካልተንገዳገደች፣ በስሜት ደም ቀልማ ካልተዥጎረጎረች ግጥም ህያው አይደለም ብለው ያስባሉ፡፡ እናም የብዙዎቻችን ችግር ግጥም ከሙዚቃ መወለዱን መዘንጋታችን ነው፤ ይላሉ፡፡
ይሁንና በገጣሚያን መካል የዘዬ፣ የፍልስፍናና የአተያይ ጥልቀት ልዩነት እንዳለ ብዙዎች ይስማማሉ፡፡ በተለይ ሒሊየር እንደሚሉት፤ ግጥም እንደ ወንድ ዘር ፍሬ ቀድሞ አእምሮ ላይ ዋኝቶና ደንሶ ሲያበቃ ነው ዕንቁላል ሰብሮ ነፍስ የሚዘራው፡፡
ሰሞኑን በካፒታል ሆቴል የተመረቀው የብሩክታዊት ጎሳዬ “ፆመኛ ፍቅር” የግጥም መድበል ነው ለዚህ ጽሁፍ መነሻ የሆነኝ፡፡ ግጥሞቿን ሳነበው፣ ይህቺ ከሀገር ውጭ የምትኖር ገጣሚ፣ ስደትን እንዴት እንዲህ አየችው? ማለቴ አልቀረም፡፡ ስደት ላይ ያተኮርኩት ሰባት ያህል ግጥሞቿ፣ ለዚያውም ረዘም ረዘም ያሉት እዚያ ላይ በማነጣጠራቸው ነው፡፡ እርግጥ ነው በአብዛኛው የጥበብ ሰው ትኩረት ሁሌ ከሕይወቱ ይነሳል፤ ደግሞም የአካባቢውን ቀለም ያጠቅሳል፡፡ ለዚህ ደግሞ የእነ ሔሚንግዌይ፣ ቶልስቶይ፣ ዩዶራ ዌልቲንና ሌሎች ሥራዎችን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ከገጣሚያንም እነ ጆን ሚልተን አሉ፡፡ ሚልተን ስለ ዕድሜ ድንገት መብረር፤ ኋላም ስለ ዓይኑ ብርሃን መጥፋት የነገረን በግጥሞቹ ነው፡፡
ብሩክታዊትም ይህንኑ የእውነት ምህዋር ተከትላ ነው የሄደችው፡፡ ሕይወት አበባ የተነሰነሰባት ሳትሆን እሾህ የተነጠፈባትም ሸለቆ እንደሆነች ነው የምታሳየው፡፡ ለምሳሌ እንደ ማዕበል ሰይፍ ስሜቷ በስደት ዘመኗ ከፍ እያለ፣ እንደገና መሬት የነካበትን ሌሊት በተራኪዋ  አንደበት በዜማ ትነግረናለች፡፡
“ማንነት” የሚለው ግጥሟ እንዲህ ይላል፡-
ሲነጋ -- ከቆመ እድሜዬ ላይ አንድ ቀን ሲሸረፍ
ልቤ በትዝታ ወዳገሬ ሲከንፍ
“ከነድህነቴ ከነመከበሬ
ምነው እግሬን ሰብሮ ባኖረኝ ሀገሬ እልና--”
በእነዚህ  ስንኞች ውስጥ በሀገሯ ያላትን ክብር፤ … ከሺህ ቀን ባርነት ያንድ ቀን ነፃነት በሚል ዓይነት ታስበውና ከሀገሯ የወጣችበትን ቀን ትረግማለች፡፡ ሁሉም በአገር ያምራል ብላ፡፡ ይህንን ያሰበችው ማታ ነው፡፡ (ገፀ ባህሪዋ ወይም ገፀ ባህሪው)
ሲነጋ ደግሞ ወፎች
ሲነጋ … ወፎች ሲንጫጩ
ደርሶ ሲንፎለፎል … የተስፋዬ ምንጩ
ሀገሬን ኮንኜ - ሳሞግስ ስደቴን
ሳበሸቃቅጠው ያምና ድህነቴን
“ሳልኖር እሞት ነበር …” እልና በዕለቱ
ሊቀር በማግስቱ …
ስሜቷ ሲቀየር ተስፋ አፍንጫዋ ሥር መጥቶ ሽቶውን ሲረጭባት፣ የተሻለ ኑሮ፣ የተሻለ ሕይወት፣ የተሻለ ትራንስፖርት፣ የኮረንቲ አለመጥፋት፣ ከወያላ ስድብ ማምለጧ ትዝ ሲላት፣ እንኳን መጣሁ --- እዚያ አንገፍጋፊ ድህነት ውስጥ ልሞት ነበር ትላለች፡፡ ሁለት ማንነት!
ይሄኔ - ስንኞች እየተሳሳሙ በዜማ ባህር ላይ ሲደንሱ፣ የፌሽታ ጅራፍ ይጮሃል! … የገደል ማሚቶው ድምፁን ያስተጋባል፡፡ ርዝቅና ክብር - ነፃነትና የሰው ሀገር ስርፀት - ይጋጫሉ፡፡ ይህ ሁሉ ግን የግጥም ድንኳን ድምቀት ነው፡፡ ሳቅ ብቻ ግጥምን አያደምቃትም፣ ለቅሶም ውበት አይሆናትም፡፡ ሁለቱንም አቅፋ፣ ሁለት ጡቶቿን ታጠባለች፡፡
ከብሩክታዊት ግጥሞች  በርከት ያሉት ፍቅርና ሀገር ላይ ያጠነጥናሉ፡፡ ለምሳሌ “ቅብጥብጥ ፍቅር”፡-  
ኤቨረስት እንውጣ ነፋስ እንቀበል
በጨረቃዋ ፍም ድንቻችን ይብሰል
ከዐባይ ፏፏቴ ዋና ተፎካክረን
ከሳይቤሪያ ላይ እንረፍ ተቃቅፈን
እንዳሻን እንሁን አሁን አሁኑኑ
የመፋቀር ዘመን አጭር በመሆኑ፡፡
ፍቅርም ግጥምም ዕብደት የሚሆነው ይሄኔ ነው፡፡ ላፈቀረ ሰው ኤቨረስት መውጣት ቀላል ነው፡፡ በጨረቃ ብርሃን ድንች መቀቀልም ይቻላል፡፡ በተለይ የሳይቤሪያን ቅዝቃዜ የሚያሸንፍ ፍም ያለው ፍቅር ነው፡፡ ግነቱ ጣዕም ያለው ነው፡፡ ለመዘርዘር ገፁ አይፈቅድምና ልተወው፡፡
“ህልም ምኞት” የሚለው ግጥምም ዜማውና ምቱ የልብ ትርታን መስመር ባይከተልም ሃሳቡ ጠለቅ ያለ ይመስላል፡፡
እጥፍ ብለህ
ሀረግ መስለህ
  አይሃለሁ
ልደግፍህ እመኛለሁ
ግን ሃሜታን እፈራለሁ፤
እንደኪኒን መዋጥ ብችል
ውስጥህ በቆምኩ ቀጥ እንድትል፡፡
ራስን ለፍቅር የመስጠትን ብርታት የሚያሳይ ምትሀት ነው፡፡ ተራኪዋ ሴት ትመስላለች፡፡ ወንዱ ገፀ ባህሪ እንደ ሀረግ እጥፍ ያለ ነው፤ አጥንት የለውም፣ … አጥንት የምለው ምናልባት ሌላ ጉድለት፣ አንገት የሚያስደፋ ነገር ይሆናል - ድህነትንም ልንጠረጥር እንችላለን፡፡ ልትደግፈው አስባ ሃሜታው ግን መከራ ሆኖባታል፡፡ ስለዚህም ከሰውነት ተራ ወርዳ፣ ለርሱ ስትል ኪኒን መሆን ተመኘች፡፡ እርሱ እርሷን ውጦ፤ ቀጥ ብሎ እንዲኖር ጓጓች፡፡  ሕልውናዋን አጥታ ህልውናው ሙሉ እንዲሆን! … ይህ ነው የፍቅር ጣት! ይህ ነው የፍቅር ሰማይ!
ገፅ 39 ላይ “የተከለከለ” የሚል በቁጭት ጥርስ የሚያስነክስ ግጥም አለ፡፡
“መማር ነው” እያሉ ይሸነግሉናል
“መጣር ነው” እያሉ ያንከራትቱናል
    ሲገባን ሀሰት ነው
በልጦ ለመገኘት ሌላ መንገድ አለ
ላልበቃን ላልነቃን የተከለከለ፡፡
እዚህ ግጥም ውስጥ ተራኪዎቹ መማርንም መጣርንም ሞክረውታል፤ ግን በልጦ ለመገኘት፣ ጅራት ሳይሆን ራስ ለመሆን ሌላ መንገድ እንዳለ ተረድተዋል፡፡ የሚያሳዝነው ግን ያንን እንዲያውቁ አልተፈቀደላቸውም፡፡ ተከልክለዋል፡፡ በምን መስፈርት እንደሆነ ባይታወቅም ይህን መንገድ የሚጠቀሙበት ሌሎች ናቸው…. ስለዚህ ግጥሟ በቁጭት ቁንጥጫ እርር ያለ ልብ የወረወራት ማስታወሻ ናት፡፡
“ጾመኛ ፍቅር” ውስጥ በርካታ ግጥሞች በተቃርኖ የተሞሉ ናቸው፡፡ ውስጣቸው ግብግብ አለ፡፡ እንደ “አፍና ልብ”፤ “ወይ ጉድ”፣ “አለፈ”፣ “እምነት አልባ ፍቅር” ወዘተ… የመሳሰሉት፡፡
ገፅ 13 ላይ “ሁለት ቅጠሎች” የሚለው ግጥም ደግሞ ተምሳሌታዊ መልዕክት ያለው ይመስላል፡፡ እዚህ ግጥም ላይ የምናደምጠው ከአንድ ትልቅ ዛፍ ስር ያለች ጥገኛ ዛፍ ቅጠል፣ ለትልቁ ዛፍ ቅጠል - የምትለውን  ነው፡፡ እንዲህ፡-
እኔ ተነቃይ ነኝ አንቺ አብሮ ነዋሪ
አንቺ ሁሌ ቁጡ እኔ ሁሌ ፈሪ፡፡
--- ትላለች የትንሹ ዛፍ ቅጠል፡፡ ሸምቃቃ ናት፡፡ ፈሪ ናት፡፡ እንባ ያነቃትም ትመስላለች፡፡ ግን ደግሞ ወደ ቀጣዩ ቀን የምታየው ተስፋ፣ የምትጠረጥረው ነገር አለ፡፡ ቅጠልን ለመጣል ንፋስ ይመጣልና ማን ያውቃል? ዓይነት!  
ግን እኮ ታውቂያለሽ?
አንዳንድ ነፋስ አለ
ለለውጥ የሚነፍስ
ወፍ ዘራሿን ትቶ
ከትልቁ ዛፍ ላይ ቅጠል የሚበጥስ …
የተወሰኑትን ስንኞች ስናይ የምናገኘው ጠቅላላ ሀሳብ፣ ማንም የቆመ ቢመስለው እንዳይወድቅ ይጠንቀቅ! የሚለውን የወንጌል ቃል ነው፡፡ አንቺ “ተደላድያለሁ” ብለሽ እኔን ከዚህችም ኑሮዬ ለመንቀል ሙከራ ታደርጊያለሽ፣ ትሳደቢያለሽ፣ ትቆጫለሽ፣ ግን ደግሞ እንዳይመስልሽ አንዳንዴ‘ኮ እንዳንቺ በትዕቢት  በተወጠሩት ላይ የሚነፍስ አለ፤ ያ - ንፋስ ድንገት ከላይ በጥሶ መሬት ላይ ይጥላል ነው የምትላት፡፡ ይህ በብዙ አቅጣጫ ሊመነዘር ይችላል፡፡ አዳዲስ ሃሳቦች፣ ልዩ ልዩ የሀሳብ ጌጦች እንደፈርጥ ሊያበሩበት መንገዱን ከፍቷል፡፡
“አፍሪካዊ” የሚለው ግጥምም ውስጥን የሚነካ ትልቅ ሃሳብ ያለው ነው፡፡
ረሃብ ካልሆነ … ጦርነት ይሆናል
ጦርነት ከጠፋ … እብድ ፖለቲካ
ገርፎ ያስወጣዋል
ሰበብ የሌለውን …. እውቀት ይጠራዋል
ሃገሩ ቢወለድ … በሃገሩ አያድግም
ሃገሩ ላይ ቢያድግ … ሃገሩ አያረጅም
አፍሪካዊ ማለት ሲሰራ ከጥንቱ
ተበይኖበታል እንዳይገናኙ
እንጀራና ቤቱ፡፡
የምናውቀው እውነት ቢሆንም እንደገና ነፍሳችንን በቁንጥጫ ያሳርራታል፡፡ በተለይ የእንጀራና የቤት መራራቅ፡፡ በስደት ምክንያት ከእናት አባት፣ ከወንድም እህት መለየት፣ በሰርግና በለቅሶ ያለመገኘት፡፡ ለቅሶን እንኳ መንገድ ላይ መጨረስ … ጉዳችን ብዙ ነው፡፡
የብሩክታዊት “ጾመኛ ፍቅር” የዜማ ስብራት፣ የአጨራረስ ችግርም ይታይበታል፡፡ ግን ደግሞ ሞገስ ያላቸው ደማቅ ዜማና ምት ይዘዋል፡፡ ስደቱ ያላዳፈነው የጥበብ እሳት ወደፊት የተሻለ እየፈካ እንደሚሄድ እጠብቃለሁ፡፡ መሻሻል ያለባቸውን ጉድለቶች ተረጋግቶ ላጣጣመ፣ መቼም ቢሆን ለጥበብ የተፈጠረ ሰው እያደገ እየጎለበተ መሄዱ የሚጠበቅ ነው፡፡ ሌሎች እህቶቻችንም የእሷን ዱካ ተከትለው ብቅ ቢሉ ደስታችን ነው፡፡

Published in ጥበብ
Saturday, 24 January 2015 13:27

ሞኝ እንደነገሩት

ሞኝ እንደነገሩት
“ፍቅር ያሸንፋል” ስትለኝ አምኜህ
በጦርነት ሁሉ ልሰለፍ አብሬህ
ደብተሬን ቀድጄ
አድርቄ ወጥሬ ጋሻ ሰርቼበት
ብዕሬን ፈልፍዬ ጦር አስቀርጬበት
ጠላትን ወግቼ
ለፍቅር ደምቼ…
ካቀረቀርኩበት ቀና ብል የለህም
ያሸንፋል ባልከኝ አንተ አልተሸነፍክም
እኔ ነኝ ብቻዬን ፍልሚያውን አውጄ
ጦሬን አበጅቼ
እኔው ተማርኬ ራሴን የሰጠሁ
ሙሉው ጦርነቴን
ሙሉ መሸነፌን
ሙሉ መሰጠቴን
ያንተ ድርሻ ቢኖር ልቤን የሰወረው
“ፍቅር ያሸንፋል” ማለትህ ብቻ ነው፡፡
    (ከብሩክታዊት ጐሳዬ “ፆመኛ ፍቅር”
    የተሰኘ የግጥም መድበል የተወሰደ)

Published in የግጥም ጥግ
Saturday, 24 January 2015 13:24

ፀሎቴ

እንዳላዝን … እንዳልባባ
ለኔ ሲሉ፡- እያነቡ
የኔን ዕንባ
 እኔኑ
በኔው፡- ዕንባ
እያሉኝ እሹሩሩ … እሹሩሩ
ለኔ ሲሉ ፡- ሁልዜም እንደኖሩ
እስከዛሬም .. የሚኖሩ  
ነበሩ፡፡
እንዳላዝን … አባብለውኝ
እንዳልስቅም ፡- አዝነውልኝ
ከርቱዕ አንደበታቸው
ዕንባዬ ፈሶ ከዕንባቸው
ለኔ ብለው
እውነት ለኔ ብለው
የኔን ቁስል ቆስለውልኝ
የኔን ህልም ታመውልኝ፣ ታመውልኝ፡፡
ሞቴንም እንዳይሞቱልኝ
ፀሎት ላይ ነኝ
ለኔ ሲሉ፡- ያልሆኑትን እንዳይሆኑልኝ
(1994 ዲላ)

Published in የግጥም ጥግ

እንደ ማስተማሪያ የሚቆጠሩት የአምስቱ ምሁራን አስተሳሰቦች ምን ያህል እርስ በርስ የማይጣጣሙና የቱን ያህል ዝብርቅርቅ ሃሳቦችን እንደሚፈጥሩ ማሳየት ነው የፈለግሁት። ከዚህ ጋር አብሮ የሚመጣው ሌላው ጥያቄ፣ “በዩኒቨርስቲ የቋንቋና የስነፅሁፍ ተማሪዎች በስነግጥም ዙሪያ ዝብርቅር ሃሳቦችን እየተጋቱ እንዴት ቅጥ ያለው እውቀት ሊገበዩ ይችላሉ?” የሚል ነው።

እዮሐ አበባዬ የሚለውን የአዲስ አመት ዘፍን የምታውቁት ይመስለኛል። የዘፈኑ ግጥም፣ ባለ አስር ቀለም እንደሆነ መንግስቱ ለማ ይገልፃሉ። “እዮሐ አበባዬ ቤት” በሚል የሚታወቀው ይሄው የግጥም ስልት፣ ሌሎች መሰረታዊ የግጥም ስልቶችን በማደባለቅ የሚፈጠር መሆኑን መንግስቱ ለማ ሲገልፁ፤ የሰንጎ መገን ቤት፣  የቡሄ በሉ ቤት እና የወል ቤት ድብልቅ ነው ይላሉ። ምሳሌ ሲጠቅሱም፣ “አይዞሽ ነፍሴ/ ደረሰልሽ ገብሴ” የሚሉ ቃላትን በአንድ ስንኝ አያይዘው ካቀረቡ በኋላ፣ የስንኙ የመጀመሪያ ሐረግ ባለ አራት ቀለም እንደሆነ አመልክተዋል፤ [አይ’ዞሽ’ - ነፍ’ሴ’]። ይህን ሐረግ ከመሃል ለሁለት የሚከፍል ሰረዝ የተጠቀሙት፣ ቃላትን ለመለየት እንዳልሆነ ልብ በሉ። ቀለማቱን በሁለት በሁለት ማቧደናቸው ነው። ለዚህ ማስረጃ ሁለተኛው ሐረግ ባለ ስድስት ቀለም መሆኑን በመግለፅ ቀለማቱን እንዴት እንዳቧደኗቸው ተመልከቱ፡ [ደ’ረ’ - ሰ’ልሽ’ - ገብ’ሴ’]። “የአማርኛ ግጥም፤ ዓይነቱ፣ ሥሪቱ፣ ሥርዓቱ” በሚል እ.ኤ.አ 1963 በኢትዮጵያ ጥናቶች ጆርናል በገፅ 148 – 149 ካሰፈሩት ትንታኔ የተወሰደ ነው።
ከመንግስቱ ለማ በፊት አለማዮህ ሞገስ በ1954 ዓ.ም ባሳተሙት “ያማርኛ ግጥምና ቅኔ ማስተማሪያ” ደግሞ ሌላ ገለፃ እናገኛለን። “እዮሐ አበባዬ ቤት” ተብሎ ለሚታወቀው የግጥም አይነት እንደ መንግስቱ ለማ ተመሳሳይ ምሳሌ የጠቀሱት አለማዮህ ሞገስ፤ በአንድ ስንኝ ሳይሆን በሁለት ስንኝ አድርገው አቅርበውታል፤ በየስንኙ ስድስት ቀለማት እንደተካተቱም ገልፀዋል።
አይዞሽ ነፍሴ
ደረሰልሽ ገብሴ
“አይዞሽ ነፍሴ” የሚሉት ቃላት፣ ባለ አራት ቀለም የስንኝ ክፋይ ናቸው በማለት መንግስቱ ለማ ሲገልፁ፣ አለማዮህ ሞገስ በበኩላቸው ባለ ስድስት ቀለም ሙሉ ስንኝ ናቸው ይላሉ። ሦስት መሰረታዊ የግጥም አይነቶችን ያደባለቀ የግጥም ስልት መሆኑን መንግስቱ ለማ ሲጠቅሱ፣ አለማዮህ ሞገስ በበኩላቸው ከወል ቤት ግጥም ጋር ያመሳስሉታል - የወል ቤት ግማሽ ያህል እንደሚሆን በመጠቆም።
ከመንግስቱና ከአለማዮህ በፊት ብላታ መርስዔኀዘን ወልደቂርቆስ በበኩላቸው፤ በ1948 ዓ.ም ባሳተሙት “ያማርኛ ሰዋስው” መፅሐፍ ውስጥ የ“እዮሐ አበባዬ ቤት” ግጥም ከስንት ቀለማት እንደሚዋቀር ሳይጠቅሱ፣ በደፈናው ሐረጉና ስንኙ አጫጭር ነው ብለዋል - “አይዞሽ ነፍሴ/ ደረሰልሽ ነፍሴ” የሚለውን በምሳሌነት በማካተት። ነገር ግን እንደ አንድ ስንኝ አልያም እንደ ሁለት ስንኝ ሊቀርብ ሊታይ ይችላል ብለዋል።
ተሾመ ይመር በ1989 ዓ.ም በኢትዮጵያ ጥናቶች ጆርናል፤ “የአማርኛ ግጥም አይነቶች” በሚል ባቀረቡት ፅሁፍ ደግሞ፣ “እዮሐ አበባዬ ቤት” በመርስዔኀዘን፣ በመንግስቱና በአለማዮህ የግጥም ዓይነቶች ዝርዝር ውስጥ በስም እንደተጠቀሰ ገልፀዋል። ነገር ግን፣ የግጥም አይነቶችን በአዲስ መልክ በመዘርዘር ሲያቀርቡ፣ “እዮሐ አበባዬ” ከየትኛው ምድብ እንደሚካተት አላስረዱም። ብርሃኑ ገበየሁ በ1993 ዓ.ም “ምጣኔ በአማርኛ ስነግጥም” በሚል በኢትዮጵያ ጥናቶች ጆርናል ባቀረቡት ፅሁፍ እንዲሁም በ1999 ዓ.ም የአማርኛ ሥነግጥም በሚል ባሳተሙት መፅሐፍ ውስጥ፣ ስለ ግጥም የምጣኔ አይነቶች ብዙ ቢናገሩም፣ “እዮሐ አበባዬ” የሚል አንድም ቦታ ሳይጠቅሱ አልፈዋል።
በአማርኛ የግጥም አይነቶች ዙሪያ በብዛት የሚጠቀሱት ሰዎች በአንድ የግጥም አይነት ላይ እርስ በርስ የማይጣጣም አስተያየት መስጠታቸውና ከፊሎቹም ከግጥም አይነት ዝርዝር ውስጥ ሳያስገቡት መቅረታቸው ወይም እስከነጭራሹ በስም ሳያነሱት ማለፋቸውን አይተናል። ይህም ብቻ አይደለም። ሌሎች የተለመዱ የግጥም አይነቶችም ላይ የተዘበራረቀ አስተያየት ታገኛላችሁ። “ቡሄ በሉ”፣ “ሆያ ሆዬ” እና “አበባዬ ሆይ” የተሰኙትን ግጥሞች ወይም የግጥም አይነቶችን ተመልከቱ።
መርስዔኀዘን፣ ከስምንቱ የግጥም አይነቶች አንዱ፣ “ቡሄ በሉ ቤት” መሆኑን ጠቅሰው፣ ስንኙ አጫጭር እንደሆነና ሕፃናት ለቡሄ እንደሚጨፍሩበት ገልፀዋል።   
እዚያ ማዶ ጭስ ይጨሳል
አጋፋሪ ይደግሳል
ያንን ድግስ ውጨ ውጨ
በድንክ አልጋ ተገልብጨ...
ሌላኛው የግጥም አይነት “ሆያሆዬ ቤት” እንደሚባል መርስዔኀዘን ጠቅሰው፣ “አበባዬ ሆይ” የተሰኘው የሴቶች ዘፈንም ከዚሁ ቤት እንደሚመደብና አንዳንድ ጊዜ ከ“ሰንጎ መገን ቤት” ጋር እንደሚገጥም አውስተዋል።
አለማዮህ ሞገስ ግን፣ “ሆያሆዬ” እና “አበባዬ ሆይ” ከሰንጎ መገን ቤት ጋር አንድ ናቸው በማለት እዚያው ቤት መድበዋቸዋል። የ“ቡሄ በሉ ቤት” ግን በአለማዮህ ከተዘረዘሩት 14 የግጥም አይነቶች ውስጥ አልተካተተም። መንግስቱ ለማ፣ በአንድ በኩል ከአለማዮህ ጋር ይስማማሉ - ሆያሆዬ እና አበባዬ ሆይ በባህሪያቸው በሰንጎ መገን ቤት ውስጥ የሚመደቡ ናቸው በማለት። እንደ ሌሎች የሰንጎ መገን ግጥሞች ሁሉ፣ ሆያሆዬ እና አበባዬ ሆይ ባለ አስር ቀለም ስንኞችን የያዙ፣ እያንዳንዱ ስንኝም ሁለት ሐረጋትን ያቀፈ፣ በየሐረጉ የሚገኙ አምስት ቀለማትም “ነ-ነነ-ነነ” ወይም “ነነነ-ነነ” በሚል ስልት የተቀናበሩ (የተቧደኑ) ናቸው ሲሉ መንግስቱ ለማ ያስረዳሉ።
[የ’-ኔ’ማ’ - ጌ’ታ’/ የ’-ሰ’ጠኝ’ - ሙ’ክት’]
[በ’-ለ’ጭ’ - ማ’ነው’/ ባ’- ለ’ም’-ል’ክት’]
አበባዬ ሆይ የሚለውንም  ግጥም እንደ ሆያሆዬ በተመሳሳይ የ(ነ-ነነ-ነነ) ስልት ቢያቀርቡትም፣ በ[ነነነ-ነነ] ስልት ቢሆን ይመረጣል።
[ባ’ልን’ጀ’-ሮ’ቼ’/ ቁ’ሙ’በ’-ተ’ራ’]
[እን’ጨት’ሰ’-ብ’ሬ’/ ቤት’እስ’ት’-ሠ’ራ’]   
የመንግስቱ ለማ ትንታኔ ከሌሎቹ ለየት የሚለው፣ ከቀለማት ብዛት ባሻገር የቀለማት አወቃቀር (ቀለማት በቡድን የተደራጁበት ስልት) ላይ ማተኮራቸው ነው። በዚሁ አቅጣጫ፣ መሰረታዊዎቹ የግጥም አይነቶች ሦስት ናቸው የሚል መደምደሚያ ላይ የደረሱት መንግስቱ ለማ፣ ከእነዚህም መካከል “ነነነ-ነነ” የሚለው የሰንጎ መገን ስልት አንዱ መሆኑን ያብራራሉ። በእርግጥ፣ “የሰንጎ መገን ስልት” ከሚለው ትክክለኛ አገላለፅ በተጨማሪ፣ አንዳንዴ “የሰንጎ መገን ስንኝ”፣ ሌላ ጊዜ ደግሞ “የሰንጎ መገን ቤት” የሚሉ አገላለፆችን በዘፈቀደ እያቀያየሩ መጠቀማቸው ለስህተት የሚዳርግ ነው። የሰንጎ መገን ስልት “ነነነ-ነነ” ሲሆን፣ ስንኙ ግን ስልትንና ምጣኔን በማካተት “ነነነ-ነነ/ ነነነ-ነነ” የሚል ይሆናል። የሰንጎ መገን ቤት ሲባል ደግሞ፣ ከእንደዚህ አይነት የስንኝ አወቃቀር የተበጁ ግጥሞችን የሚወክል የአይነት ስያሜ ነው። እነዚህን ልዩነቶች ማምታታት ስህተት ቢሆንም፣ መንግስቱ ለማ ከሌሎቹ ምሁራን በተለየ ሁኔታ ከቀለማት ብዛት ባሻገር፣ የቀለማት አወቃቀር (ስልት) ላይ ያተኮረ ትንታኔ ማቅረባቸው፣ በአገራችን የሥነግጥም ዘርፍ ከሁሉም የላቀ ከፍ ያለ ቦታ ሊያሰጣቸው ይገባልም። ምክንያቱም፣ ከግጥም ዋና ባሕርያት መካከል አንዱ የሆነውን ምት (ሪዝም)፣ በቀለማት ብዛት ሳይሆን በቀለማት ስልት ላይ የተመሰረተ ነው። ሎሬት ፀጋዬ ገብረመድህንም ይህንን የግጥም ባህርይ በተመሳሳይ መንገድ ነበር የሚገነዘቡት። አሳዛኙ ነገር፣ መንግስቱና ፀጋዬ ወደፊት ያራመዱት የግጥም ስልትና የምት ትንታኔ፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተረሳ፣ በተለይ ደግሞ በብርሃኑ ገበየሁ ጨርሶ ትርጉም አልባ እንዲሆን ተደርጓል ማለት ይቻላል - ምት የተመሳሳይ ድምፆች ድግግሞሽ ነው ብለዋል (የአማርኛ ስነግጥም ገፅ 206)። በአንድ ስንኝ ውስጥ ‘ሮ’ እና ‘ሎ’ የሚሉ ሳብዕ ድምፆች መኖራቸው እንደ ዋና የምት ምሳሌ ማቅረባቸው፣ የምትን እሳቤ እጅጉን በሩቁ እንደሳቱት ያረጋግጣል። በሚገባ አንጥረው ባያወጡትም፣ “ስልት” ላይ ያተኮረው የመንግስቱ ለማ ትንታኔ፣ በንፅፅር ሲታይ የቱን ያህል የቀደመ እንደሆነ በዚሁ አጋጣሚ መረዳት ይቻላል።
ወደ ጀመርነው ውጥን ስንመለስ፣ ቡሄ በሉ ቤት በአለማዮህ ሞገስ የግጥም አይነቶች ባይካተትም፣ መንግስቱ ለማ ግን፣ ከሰንጎ መገን በተጨማሪ፣ ከዋና ዋናዎቹ ሦስት መሰረታዊ የግጥም ስልቶች መካከል አንዱ፣ የቡሄ በሉ ስልት እንደሆነ ይገልፃሉ። በባለ 8 ቀለም ስንኞችንና በየስንኙም ሁለት ሐረጋትን የያዘው የቡሄ በሉ ቤት ግጥም፣ በየሐረጉ በሁለት በሁለት የተቧደኑ ቀለማት እንዳሉ መንግስቱ ለማ ሲያስረዱ፣ “የስንኙ ስልት፣ ነነ-ነነ/ ነነ-ነነ የሚል ነው” ብለዋል።
[እ’ዚያ’ - ማ’ዶ’/ ጭስ’ ይ’-ጨ’ሳል’]
[አ’ጋ’ - ፋ’ሪ’/ ይ’ደ’-ግ’ሣል’]
ተሾመ ይመር በበኩላቸው፤ ግጥም ተመጥኖ የሚያልቀውና የግጥሙ ምትና ዜማ የሚዋቀረው በሐረግ ውስጥ እንደሆነ ገልፀው፤ የግጥም ዓይነቶችን መለየት የሚቻለው በስንኝ ስልት ሳይሆን በሐረግ ስልት ነው ይላሉ። በእርግጥ መንግስቱ ለማ፣ የስንኝ ስልት፣ የቤት ስልት፣ የሐረግ ስልት የሚሉ አገላለፆችን አላግባብ በማደበላለቅ ቢጠቀሙም፣ የግጥም ዓይነቶችን ለመፈረጅ የተጠቀሙት የሐረግ ስልትን ነው። ለምሳሌ፣ የቡሄበሉ ስንኝ ስልት ከነምጣኔው “ነነ-ነነ/ ነነ-ነነ” የሚል ባለ 8 ቀለም ቢሆንም፣ የቡሄበሉ ስንኝ ስልት “ነነ-ነነ” የሚል ነው ብለዋል - የአንድ ሐረግን ብቻ በማሳየት። እንግዲህ ተሾመ ይመርም በስንኝ ላይ ሳይሆን በሐረግ ላይ ማተኮር አለብን ስለሚሉ፣ አካሄዳቸው ከመንግስቱ ለማ ጋር ተመሳሳይ እንደሚሆን ልንጠብቅ እንችላለን። ነገር ግን ይለያያል። እንዴት? የግጥም ዓይነቶችን የምንፈርጀው፣ “በሐረግ ውስጥ ያለውን የቀለማት ብዛት መሰረት አድርገን” ነው ይላሉ ተሾመ ይመር። እናም “እዚያ ማዶ/ ጭስ ይጨሳል” የሚለው ባለ 8 ቀለም ስንኝ፣ ከባለ አራት ቀለም ሃረጋት የተዋቀረ መሆኑን ይጠቅሳሉ (ገፅ 109)። መንግስቱ ለማ ግን፣ ከቀለም ብዛት ባሻገር ቀለማቱ የተቧደኑበትንም ስልት ያጣመረ ነው - አራት ቀለማት ያሉት የቡሄበሉ ሐረግ “ነነ-ነነ” በሚል ስልት የተዋቀረ ነው ይላሉ።
ብርሃኑ ገበየሁ ደግሞ፣ የሐረግ ቀለማት ብዛትም ሆነ የሐረግ ቀለማት ስልትን አይቀበሉም። በስንኝ የቀለማት ብዛት ነው ግጥሞችን የሚፈርጁት አቶ ብርሃኑ፤ ቡሄበሉ ቤት በአንድ ስንኝ ከሶስት እስከ አምስት ቀለማት ይይዛል ብለዋል - “እዚያ ማዶ” ባለ አራት ቀለም ስንኝ መሆኑን፣ እንዴት አድርገው እንዳነበቡት ባይታወቅም “ጭስ ይጨሳል” የሚለው ደግሞ ባለ አምስት ቀለም ስንኝ እንደሆነ ገልፀዋል (ገፅ 239)። ብርሃኑ ገበየሁ፣ የምት እሳቤን ብቻ ሳይሆን ከመነሻው የቀለም ምንነት ላይ ከዚያም የስንኝ ምንነት ላይ ከፍተኛ የግንዛቤ ችግር እንዳለባቸው መፅሐፋቸው ውስጥ በተደጋጋሚ ይታያል። በእርግጥ፣ የዚህ ፅሁፍ ትኩረት፣ ከሌሎቹ ተጠቃሽ ምሁራን በተለየ ሁኔታ በአይነትና በብዛት ገንነው የሚታዩ የብርሃኑ ገበየሁ ስህተቶችን ለመዘርዘር አይደለም። ይልቅስ፣ እንደ ማስተማሪያ የሚቆጠሩት የአምስቱ ምሁራን አስተሳሰቦች ምን ያህል እርስ በርስ የማይጣጣሙና የቱን ያህል ዝብርቅርቅ ሃሳቦችን እንደሚፈጥሩ ማሳየት ነው የፈለግሁት። ከዚህ ጋር አብሮ የሚመጣው ሌላው ጥያቄ፣ “በዩኒቨርስቲ የቋንቋና የስነፅሁፍ ተማሪዎች በስነግጥም ዙሪያ ዝብርቅር ሃሳቦችን እየተጋቱ እንዴት ቅጥ ያለው እውቀት ሊገበዩ ይችላሉ?” የሚል ነው።
ከላይ እንደጠቀስኩት፣ ከባለ 8 ቀለም ስንኞች የሚዋቀር የ“ቡሄበሉ” ግጥም፣ ራሱን የቻለ መሰረታዊ የስንኝ ስልትን እንደሚከተል የገለፁት መንግስቱ ለማ፣ ከባለ 10 ቀለም ስንኞች የሚዋቀሩ የሆያሆዬ እና የአበባዬ ሆይ ግጥሞች ደግሞ፣ በሌላኛው መሰረታዊ የስንኝ ስልት በሰንጎ መገን ውስጥ እንደሚመደቡ ጠቅሰዋል። የስንኝ እና የቀለም ምንነት ላይ የግንዛቤ ጉድለት የሚታይባቸው ብርሃኑ ገበየሁ በበኩላቸው፣ አንዱን ስንኝ እንደ ሁለት ስንኝ እየቆጠሩ ስለሚከትፉት፤ የቡሄበሉ፣ የሆያሆዬ እና የአበባዬ ሆይ ግጥሞች፣ በአንድ ስንኝ ውስጥ ከአምስት በላይ ቀለም እንደሌላቸው ይገልፃሉ - በጋራ “ቡሄ በሉ ቤት” በማለት ይጠሯቸዋል። ተሾመ ይመር፣ የስንኝ እና የቀለም ምንነትን ባይስቱም፣ ከቀለም ብዛት ባሻገር የስልት ልዩነትን ለማካተት ባለመቻላቸው፣ ቡሄበሉ፣ ሆያሆዬ እና አበባዬ ሆይ የተሰኙትን ግጥሞች በአንድነት የህፃናት ግጥም በሚል ፈርጀዋቸዋል።    
ሁሉም በጋራ እንደ የግጥም አይነት ወይም እንደ ስልት የሚጠቅሱት አለ - የወል ቤት የተሰኘ።
ፀጋዬ ገብረመድህን በድምፅ ባስቀረፁት የግጥም ንባብ እና ማብራሪያ፣ ስለ ግጥም የምጣኔና የስልት አይነት ተናግረዋል። አንድ ግጥም በወል ቤት እንዲሁም አራት ግጥሞች የፀጋዬ ቤት እንደተቀናበሩ ጠቅሰው፤ የሁለቱ ልዩነት በአጭሩ፣ የወል ቤት ስንኝ ባለ 6 ምት፣ የፀጋዬ ቤት ስንኝ ባለ 8 ምት መሆናቸው ብቻ ነው። የወል ቤትን ምጣኔ ከነስልቱ ለማስረዳት፣ [ተ’ተ’ተ’ - ተ’ተ’ተ’ - ተ’ተ’ተ’ - ተ’ተ’ተ’] በማለት በድምፅ ካሰሙ በኋላ፣ በተጨባጭ ምን እንደሚመስል ለማሳየትም፣ ከከበደ ሚካኤል ግጥም አንድ ስንኝ በመምዘዝ በምሳሌነት አቅርበዋል፤ [አ’ቻም’ና’ - ቅ’ዳ’ሜ’ - በ’ክእ’ረምት’ - ወ’ራ’ትእ’]። (እዚህ ላይ፣ “በክረምት” የሚለውን ቃል ስንናገር፣ “ክ” ራሱን የቻለ ቀለም ሆኖ ተረግጦ የሚወጣ ድምፅ መሆኑን ለማመልከት “እ” የሚል አናባቢ ተጨምሮበታል። ወራት የሚለው ቃል፣ በትክክለኛው አነጋገር፣ ባለ ሁለት ቀለም ነው - ወ’ ራት’። “ት” ለብቻው ሳይሆን የ“ራ” ቅጥያ ሆኖ የሚወጣ ድምፅ በማድረግ። ነገር ግን፣ የግጥሙን የምት ስልትና ምጣኔ ላለማጓደል፣ “ት” ራሱን የቻለ ቀለም እንዲሆን ይረገጣል - “እ” የሚል አናባቢ ይጨመርበታል ማለት ነው። በነገራችን ላይ፣ “ይረገጣል” ማለት ሌላ ትርጉም የለውም “እ” የሚል አናባቢ አለው ማለት ነው። “ይጠብቃል” ወይም “ጠብቆ ይነገራል” ማለት ግን፣ ቀለም ከመሆንና ካለመሆን ጋር ግንኙነት የለውም። በእንግሊዝኛው ጀሚኔሽን የሚባለው ነው። በተደጋጋሚ ከሚጠቀሱ ምሳሌዎች ማየት ይቻላል። ተናገረ በሚል ትርጉም “አለ” ስንል ለ አይጠብቅም። መኖርን ለማሳየት “አለ” ስንል ግን ይጠብቃል - “አልለ” የማለት ያህል ነው።)
ለወል ቤት ያቀረቡት ምሳሌ፣ ምጣኔውን ከነስልቱ የሚያሳይ ነው። ምጣኔውን ለማሳየት ሙሉ ስንኙን ማየት ያስፈልጋል። ስልቱን ለማሳየት ግን የስንኙን የተወሰነ ክፍል ብቻ ማሳየት በቂ ነው። “ተተተ - ተተተ... እያለ የሚቀጥል ወይም ራሱን የሚደግም ነው” ብሎ አሳጥሮ እንደ መግለፅ ቁጠሩት። ለዚህ ነው የወል ቤት ባለስድስት ነው ብለው የገለፁት። ግን በዚህ አያቆሙም፣ ስድስቱ አንድ ላይ የታጀሉ አይደሉም - በሶስት በሶስት የተሰደሩ መሆናቸውን በግልፅ አስገንዝበዋል። ይህንንም “ሁለት ባለ ሦስት” ሲሉ ይጠሩታል።         

Published in ጥበብ
Page 5 of 18