ለስድስት ወር ብቻ ታግዶ የነበረው ወደ አረብ ሃገራት የሚደረግ የሥራ ጉዞ አንድ ዓመት ያስቆጠረ ሲሆን ጉዞውን እንደ አዲስ ለመጀመር ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲጸድቅ የቀረበው አዋጅ እየተጠበቀ ነው ተብሏል፡፡ የዛሬ ዓመት ገደማ ለስራ ወደ ውጭ ሃገር በተለይም ወደ መካከለኛው ምስራቅ የሚደረግ ጉዞ ለ6 ወራት እንዲታገድ የተወሰነው ለስራ ብለው ወደ አረብ ሃገራት የሚጓዙ ዜጎችን በህጋዊ ማዕቀፍ አጠቃላይ ከለላ ለመስጠት የሚያስችልና በተጠናከረ ህግ የተደገፈ አሰራር ለማስፈን ነው ያሉት የሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ግርማ ሸለመ፤ እገዳው ሳይነሳ እስከ ዛሬ የዘገየው አዲስ የህግ ረቂቅ በማዘጋጀትና አጠቃላይ ጠንካራ ዝግጅት ለማድረግ ታስቦ ነው ብለዋል፡፡

ከሰራተኛና ስራ አገናኝ ኤጀንሲዎች፣ ከሰራተኞች መብት፣ ደህንነትና ክብር፣ ከዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት እንዲሁም ከስልጠና ጋር የተያያዘ የህግ አንቀፆችን አካቷል የተባለው ረቂቅ አዋጁ፤ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ውይይት ተደርጎ እንዲፀድቅ መቅረቡንና ሰሞኑን መደበኛ ስራውን የጀመረው ምክር ቤቱ ያጸድቀዋል ተብሎ እንደሚጠበቅ የገለፁት አቶ ግርማ፤ አዋጁ እንደፀደቀ ታግቶ የነበረው የአረብ ሃገራት ስራ ስምሪት ይጀመራል ብለዋል፡፡

አዋጁን የማሻሻል ስራ ሰፊ ጊዜ እንደወሰደ የጠቆሙት አቶ ግርማ፤ የህግ ባለሙያዎችና ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላት በማሻሻል ሂደቱ እንዲሳተፉ ተደርገዋል ብለዋል፡፡ረቂቅ አዋጁ ለስራ የሚሄዱ ግለሰቦች ተገቢውን ስልጠና ማግኘት እንዳለባቸው የሚገልፁ አንቀፆች እንደተካተተበት የተናገሩት አቶ ግርማ፤ ሰራተኞች ሰልጥነው መሄዳቸው የተሻለ ደሞዝ ተከፋይ ያደርጋቸዋል ይላሉ፡፡ ያልተማሩ ሰዎች እንዴት ይስተናገዳሉ የሚለው ጉዳይም በአዋጁ መካተቱን የጠቆሙት አቶ ግርማ፤ አዋጁ ከመፅደቁ በፊት ዝርዝሩን ለመግለፅ አልችልም ብለዋል፡፡ወደ 40 የሚጠጉ የቴክኒክና ሙያ ማሰልጠኛ ተቋማት ተመርጠውና ስርአተ ትምህርት ተቀርፆ፣ በቤት አያያዝና አጠቃላይ እንክብካቤ (care giving) ላይ ስልጠና ለመስጠት ዝግጅቱ መጠናቀቁን ኃላፊው ጠቁመዋል፡፡

ከአረብ አገሩ የሥራ ጉዞ እገዳ በፊት ዜጎችን ወደ ተለያዩ የአረብ ሃገራት ይልኩ የነበሩ ኤጀንሲዎች ሰራተኞችን መላክ የተከለከሉ ቢሆንም ቀደም ሲል የላኳቸው ዜጎች የኮንትራት ስራቸውን ጨርሰው እስኪመለሱ ድረስ ደህንነትና መብታቸውን የማስከበርና የመከታተል ግዴታ አለባቸው ያሉት ኃላፊው፤ ኤጄንሲዎቹም ይሄን ግዴታቸውን እየተወጡ ነው፤ ችግሮች ሲያጋጥሙም ሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር እያነጋገረ ችግሩ እንዲፈቱ እያደረገ ነው ብለዋል፡፡ ኤጀንሲዎቹ የላኳቸውን ሰራተኞች መብት ሁለት ዓመት ከአራት ወር ድረስ የማስከበር ግዴታ እንዳለባቸው አቶ ግርማ ጠቁመዋል፡፡ ይጸድቃል ተብሎ በሚጠበቀው አዋጅ ላይም ኃላፊነትና ግዴታቸውን በማይወጡ ኤጀንሲዎች ላይ ሊወሰዱ የሚችሉ እርምጃዎች እንደተካተቱ ገልፀዋል፡፡ የእገዳው መዘግየት ህገ ወጥ ፍልሰትን አባብሷል የሚል ቅሬታ እንዳለ ያነሳንላቸው አቶ ግርማ፤ ህገወጥ ፍልሰት ህጋዊ ጉዞው ከመታገዱ በፊትም የነበረ መሆኑን ጠቅሰው በአሁን ሰዓት የሚመለከታቸው የህግ አካላት በድንበር አካባቢዎች እንዲሁም በአየር መንገድ አካባቢ ጠንካራ ቁጥጥርና ክትትል እያደረጉ በመሆናቸው የፍልሰት መጠኑ እየቀነሰ እንደሆነ ገልፀዋል፡፡

Published in ዜና

             የኢትዮጵያ፣ የግብጽና የሱዳን የውሃ ሚኒስትሮችና ባለሙያዎች የሚሳተፉበትና በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ዙሪያ የሚመክረው ሁለተኛው ዙር የሶስትዮሽ የቴክኒክ ውይይት፣ በመጪው ሃሙስና አርብ በካይሮ እንደሚቀጥል የግብጹ አሃራም ድረገጽ ዘገበ፡፡የግብጹን የውሃና የመስኖ ሚኒስትር ሆሳም አልሞሃዚን ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ በውይይቱ ላይ የሚሳተፉት 12 የአገራቱ ባለሙያዎች፣ ግድቡ በግብጽና በሱዳን ላይ የሚያደርሰውን ማህበራዊ፣ አካባቢያዊና የውሃ ተጽእኖዎች በተመለከተ ተጨማሪ ጥናት የሚያደርግ አለማቀፍ አማካሪ ኩባንያ ይመርጣሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ሚኒስትሩ ከትናንት በስቲያ በሰጡት መግለጫ እንዳሉት፣ ለሁለት ቀናት በሚካሄደው ውይይት ሶስቱ አገራት የግድቡን ተጽዕኖ በተመለከተ ያገኟቸውን አዳዲስ የጥናት ውጤቶች አቅርበው ይወያዩባቸዋል፡፡አገራቱ ባለፈው ነሃሴ በግድቡ ተጽዕኖዎች ዙሪያ የሚሰሩ ተጨማሪ ጥናቶችን በስድስት ወራት ጊዜ ውስጥ ለማጠናቀቅ መስማማታቸውንና የመጀመሪያው ዙር የሶስትዮሽ ውይይት ባለፈው መስከረም 10 ቀን በአዲስ አበባ መካሄዱ ያስታወሰው ዘገባው፣ በውይይቱ የተገኘው ውጤትም በአገራቱ መካከል የተጀመረው ድርድር ወደተሻለ ደረጃ እየተሸጋገረ መሆኑን የሚያመላክት እንደሆነም አክሎ ገልጧል፡፡

Published in ዜና

ዕቅዱ የተለጠጠ ነው ተብሏል

        የኢትዮጵያ ከርሰ ምድራዊ ሁኔታ እንደሌሎች የአፍሪካ አገራት አዋጭ ነው በሚል ግምት አማካኝ ገቢው ቢሰላ፣ ኢትዮጵያ ከማዕድን ዘርፍ በእምቅ ሀብቷ በዓመት 5 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘት እንደምትችል አንድ የዳሰሳ ጥናት ሪፖርት አመለከተ፡ ሌሎች ገቢዎችን በንግድ ገቢ ግብርና የሮያሊቲ ክፍያ በመለካት አገሪቱ እስከ 2024 (እኤአ) ከ100 እስከ 500 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘት እንደምትችልና የማዕድን ልማት ዘርፉ ከ1,400 እስከ 8000 ለሚደርሱ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር እንደሚችል ሪፖርቱ አመልክቷል፡፡ የኢትዮጵያን የማዕድን ልማት ዘርፍ ለመደገፍ ከዓለም ባንክና አጋሮቹ፣ ከዓለም አቀፍ የፋይናንስ ኮርፖሬሽን፣ ከካናዳ የውጭ ንግድና ልማት ተቋም፣ ከአውስትራሊያ መንግስትና ከእንግሊዝ ዓለም አቀፍ የልማት ተቋም በተገኘ የገንዘብ ድጋፍ፣ ከግንቦት 2013 እስከ መጋቢት 2014 በኢትዮጵያ የማዕድን ዘርፍ ዕቅድ ላይ የዳሰሳ ጥናት መደረጉን ሪፖርቱ ጠቅሶ፣ ኢትዮጵያ፣ ከወርቅ፣ ከታንታለምና ከኦፖል በተጨማሪ በኢንዱስትሪ ማዕድናትም በተፈጥሮ የታደለች መሆኗን አመልክቷል፡፡ ከፍተኛ ማዕድን አምራቶች በኢትዮጵያ የሉም ያለው ሪፖርቱ፤ የሲሚንቶ ምርት ጥሬ ግብአቶችና የማዕዘን ድንጋዮች በአነስተኛ ኢንዱስትሪዎች፣ ሌሎች የኢንዱስትሪ ማዕድናት በጥቃቅንና አነስተኛ ድርጅቶች በልማዳዊ አሰራር ይመረታሉ ብሏል፡፡

ዘርፉን ሊያበረታታ የሚችል ሁኔታ ላይ ያለው የኦላና ፓታሽ ክምችት ሲሆን አሁን ባለው ዕቅድ መሰረት ወደ ምርት ሲገባ በቀን 1 ሚሊዮን ቶን እያመረተ ለ24 ተከታታይ ዓመታት ይዘልቃል፤ ለ800 ሰራተኞችም የሥራ ዕድል ይፈጥራል ብሏል፡፡ የአገሪቷ ከርሰምድራዊ ሁኔታዎች፣ በሰሜን፣ በምዕራብና በደቡብ የአገሪቷ ክፍሎች እምቅ አዳዲስ የማዕድን ሀብቶች እንደሚኖሩ ያመለክታሉ ያለው ሪፖርቱ፤ ይኖራል ተብሎ የሚገመተው የማዕድን መጠን፣ በሌሎች የአፍሪካ አገሮች ከሚገኙ የማዕድን አካባቢዎች የላቀ እንደሆነ ገልጿል፡፡ ማዕድን ከመፈለግ እስከ ግዙፍ ማዕድን ማውጣት ያለውን ሥራ ለማከናወን ቀዳሚ ክንውኖች የሚካሄዱበት ጊዜ ረዥም ሲሆን ከ10 እስከ 15 ዓመት ይፈጃል ያለው ሪፖርቱ፤ አሁን ባለው የአገሪቱ ፖሊሲ ማዕቀፍ መሰረት (እ.ኤ.አ ከ2022-2023) ድረስ የአገሪቱ የኢንዱስትሪ ዘርፍ የኢኮኖሚው የጀርባ አጥንት እንዲሆን ታቅዷል፡፡

ነገር ግን አገሪቷ ያለመችው ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት ላይሳካ ይችላል፡፡ የማዕድን ዘርፍ ልማት ውጤት ሊያመጣ የሚችለው በመለስተኛ የዕድገት አቅጣጫ የረዥም ጊዜ እቅድ ሲቀረፅ ነው በማለት አስረድቷል፡፡ በማዕድን ዘርፍ ልማት ለመጠቀም፣ አሁን የሚታዩትን ችግሮች ለመቅረፍ፣ የማዕድን ፍለጋና የማዕድን ማውጣት የሥራ ፈቃድ የሚሰጥበት ግልፅ ፖሊሲ፣ ህጎችና ደንቦች ማስቀመጥ፣ የማዕድን ሚ/ርን ተቋማዊ አቅም መገንባት፣ የተቆጣጣሪ ተቋማትን የአቅም ውስንነት ከግምት በማስገባት የማዕድን አልሚ ኩባንያዎችን በዘርፉ ንቁ ተሳታፊ ማድረግ፣ ኢኮሎጂካዊ አዋጭ ስለሚባሉ አካባቢዎች በቂ መረጃ ማቅረብ፣ የማዕድን ገቢ ክፍፍል ሥርዓትን መቅረጽ፣… ያስፈልጋል ብሏል ሪፖርቱ፡፡ በረዥም ጊዜ ከፍተኛ የማዕድን ዘርፍ ከመፍጠር አኳያ፣ ፖሊሲ አውጪዎች ከዘርፉ የሚገኝን ጥቅም በበለጠ ማሳደግ የሚችሉበትን ዕቅድ ማጥናት ያስፈልጋል ያለው ሪፖርቱ፤ ምንም እንኳ መንግሥት ያስቀመጠው የተለጠጠ ዕቅድ በቀጣዩ 10 ዓመት ይሳካል ተብሎ የሚገመት ባይሆንም በዘርፉ ልማት የተገኙ ውጤቶችን የእሴት ሰንሰለቶች ለመፍጠር የግድ ማበረታታት ያስፈልጋል በማለት አሳስቧል፡፡

Published in ዜና

         የሰንደቅ አላማውን ክብር ለማስጠበቅ የወጣው አዋጅ ግንዛቤ ሲሰጥበት እንደቆየ የተናገሩት የሰንደቅ አላማ ቀን አከባበርና ብሄራዊ ኮሚቴ የቴክኒክ ቡድን ሰብሳቢ የተከበሩ አቶ ዳዊት ተፈራ፤ ህጉን ሙሉ ለሙሉ በማያከብሩት ላይ ህጋዊ እርምጃ ሊወሰድ እንደሚችል ገለፁ፡፡ አረንጓዴ፣ ቢጫ፣ ቀይ ቀለማት ላይ የሃይማኖትና የብሄረሰቦችን እኩልነት የሚያንፀባርቀውን ብሄራዊ አርማ በአግባቡ በማይጠቀሙ፣ በሰንደቅ አላማ አዋጅ ላይ ስለሰንደቅ አላማው ክብርና አያያዝ በዝርዝር የተመለከቱትን አንቀፆች በማያከብሩ ላይ ከዚህ በኋላ የሚመለከተው አካል ህጋዊ እርምጃ ይወስዳል ተብሎ እንደሚጠበቅ የተከበሩ አቶ ዳዊት አስታውቀዋል፡፡

ሰንደቅ አላማን በተመለከተ በተለያዩ ጊዜያት ሶስት አዋጆች ወጥተው እንደነበረ የጠቆሙት የተከበሩ አቶ ዳዊት፤ በስራ ላይ ያለው አዋጅ ቁጥር 654/2001 የአሁኑን የኢፌድሪ ሰንደቅ አላማ አለመጠቀም የህግ ጥሰት መሆኑን ይደነግጋል ብለዋል፡፡ የሰንደቅ አላማ ቀን መከበር ከጀመረ ወዲህ ህብረተሰቡ አሁን በስራ ላይ ስላለው ሰንደቅ አላማ ያለው ግንዛቤ እየዳበረ መምጣቱን የጠቀሱት የቴክኒክ ቡድኑ ሰብሳቢ፤ እንዲያም ሆኖ ህንፃዎችንና አውቶብሶችን በባንዲራ ማልበስ፣ በተገቢው ሰዓት አለመስቀልና አለማውረድ የመሳሰሉት ችግሮች እንደሚስተዋሉ ተናግረዋል፡፡

Published in ዜና

             እንደ ሀገር አብረውን የሚኖሩትን ችግሮች ለመቅረፍ መንግስት ዘመቻን መፍትሔ አድርጎ ሙጥኝ ካለ እነሆ በርካታ ዓመታት አለፉ፡፡ በዘመቻ ብቻ የምር የተቀየሩና ችግሮቻቸውን በዘላቂነት የቀረፉ ሀገሮች ይኖሩ ይሆን? አይመስለኝም!
ለእኛ ለኢትዮጵያውያንና በየዘመኑ ሀገሪቱን ለገዙ መሪዎች ዘመቻ እንግዳ አይደለም፡፡ “ይሄን ለማስወገድ፣ ይሄን ለማስቀረት፣ እንዲህ ለመፍጠር…” ለየችግሩ “ዘመቻ፣ ዘመቻ…” ሲባል ኖሮአል፡፡ አሁንም እዚያው ውስጥ ነን፡፡ ለየችግሩ የምንጠራው ዘመቻን ነው፡፡ ልብ ብላችኋል? በዘመቻ ለመፍታት የማይሞከርና ዘመቻ የማይገባበት ነገር የለም፡፡
ዘመቻ ፈጽሞ አስፈላጊና ጠቃሚ አይደለም፡፡ ወይንም በዘመቻ የሚፈቱ ችግሮች የሉም እያልኩ አይደለም፡፡ በዘመቻ የሚፈቱ ችግሮች ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ያም ሆኖ ግን በዘመቻ የሚደረግ እንቅስቃሴ ወቅታዊ ሆኖ እንዳይቀርና ግልብ የቡድን መንፈስ እንዳያሸንፈው የራሱ የሆነ ከፍተኛ ዝግጅትንና ጥንቃቄን ይፈልጋል፡፡ ከዚያ ባለፈ ግን ዘመቻ የሁሉም ነገር መፍትሔ አይደለም፡፡ በፍጹም!
እንግዲህ ተሸክመናቸው የምንኖረው አብዛኞቹ ችግሮችም ለዘለቄታው መቀረፍ ያልቻሉት (ሌሎችም ምክንያቶች መኖራቸው እሙን ሆኖ) ችግሮቹን ለመፍታት የሚሞከረው በዘመቻ በመሆኑ ነው፡፡ ችግሩን በጥልቀት በማጥናትና መፍትሔውን በማርቀቅ፣ በተረጋጋ መልኩ በሂደትና በዘላቂነት ለመፍታት ከመሞከር ይልቅ በጥድፊያና በዘመቻ ለመፍታት ይሞከራል፡፡ እናም ሥር ያልያዘና መድረሻው የማይታወቅ የአንድ ሰሞን እንቅስቃሴ ሆኖ ይከስማል፡፡
እንዳለመታደል ሆኖ እንቅስቃሴያችን ሁሉ በዘመቻ የተቃኘ ሆኖአል፡፡ በየጊዜው ተጀምረው የትም ሳይደርሱ የቀሩ ብዙ ጉዳዮችን ተመልከቱ፡፡ ልብ ብላችሁ ከሆነ ብዙዎቹ በዘመቻና በ“በል በል” ስሜት የተጀመሩ ናቸው፡፡ እናም የትም አልደረሱም፡፡ ዘመቻ ዘመቻ ነው፤ ጥልቀትና ዘላቂነት የለውም፡፡
ንጽሕናን ለመጠበቅ ዘመቻ፣ የትራፊክ አደጋን ለማስቀረት ዘመቻ፣ ዛፍ ለመትከል ዘመቻ….. ሁሉም ነገር የሚደረገው በዘመቻ ነው፡፡ ታዲያ ዋናው የዘመቻ ችግር ምን መሰላችሁ? የአንድ ሰሞን እንቅስቃሴ በመሆኑ በፍጹም ዘላቂነት የለውም፡፡ ዘላቂነት ስለሌለውም በዘላቂነት ችግርን መፍታት አይችልም፡፡ ዘመቻ ምን አልባት አንድ ጥቅም ይኖረው ይሆናል- ለፕሮፓጋንዳ  ፍጆታ ማገልገሉ፡፡
የዘመቻ ባህል ምን ያህል ችግራችንን መቅረፍ እንዳልቻለ ጥቂት ማሳያዎችን እያነሳን እንመልከት፡፡ በዘመቻ ለመፍታት ከምንታገለው ችግር አንዱ የትራፊክ አደጋ ነው፡፡  በርካቶችን ህይወትና ንብረት የሚያሳጣ ችግር ለመቅረፍ በሀገራችን የሚደረገውን እንቅስቃሴ ልብ ብላችኋል፡፡ ለጥቂት ቀናት የትራፊክ ፖሊሶችና የመንገድ ትራንስፖርት ሠራተኞች በየመንገዱና አደባባዩ ላይ ቆመው መንገደኛውን ስርዓት ለማስያዝና ደንቡን ለማስከበር በሞራል ሽር ጉድ ሲሉ እንመለከታለን፡፡ ሰዉም እነሱ አድርግ የሚሉትን ሲያደርግ ይታያል፡፡ ሆኖም ይሄ የሚሆነው እጅግ ለጥቂት ቀናት ብቻ ነው፡፡
ከዚያስ? ከዚያማ ህይወት በነበረችበት ትቀጥላለች፡፡ መንገደኛውም እንደፈለገው ይሄዳል፡፡ እነዚያ ከቀናት በፊት ስርዓት ለማስከበር ጎንበስ ቀና ሲሉ የነበሩት አካላትም ሁሉን ትተው ሰዉ እንዳሻውና እንደፈቀደው ሲተራመስ በዝምታ መመልከታቸውን ይቀጥላሉ፡፡ ለምን?
ምክንያቶችን ማስቀመጥ ይቻላል፡፡ አንደኛ ባለሙያዎቹ በዘመቻው ላይ የተሳተፉት ታዘውና በወቅቱ ቁጥጥር ስለሚኖር ከቅጣት ለመዳን ነው፡፡ ሌላ ብዙም ከዚህ የዘለለ ምክንያት የላቸውም፡፡ ሁለተኛ ህዝቡም እነሱን በመፍራትና ከቅጣት ለመዳን ሲል ነው እንጂ አድርግ ያሉትን ያደረገው በችግሩ ላይ የጠራ ግንዛቤ የለውም፤ እንዲኖረውም አልተደረገም፡፡ እናም ሁለቱም አካላት እንደምንም ብለው በማስመሰል ያቺን የዘመቻ ወቅት ያሳልፏታል፡፡ ይኸው ነው፡፡ ምክንያቱም ችግሩን ለመፍታት የተኬደበት መንገድ ቀጣይና ዘላቂነት ያለው ሳይሆን በጥቂት ቀን የሚከስም ዘመቻ ነበር፡፡ እናም አደጋውና ጥፋቱ ባለበት ይቀጥላል፡፡ ዘመቻ የአንድ ወቅት እንቅስቃሴ እንጂ ቀጣይና ዘላቂ አይደለም፡፡  
ሌላ ማሳያ እናንሳ፡፡ የችግኝ ተከላ፡፡ እንደ መንግስት ሚዲያዎች “ዘገባ” ባሳለፍናቸው ጥቂት ዓመታት ውስጥ በዘመቻ የተተከሉት ችግኞች ብዛታቸው ያህላል የለውም፡፡ በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠሩ ችግኞች ተተክለዋል፡፡ የጸደቁት ምን ያህሉ ናቸው? ብለን ብንጠይቅ ግን መልሱ እጅጉን አስደንጋጭ እንደሚሆን አያጠራጥርም፡፡ ለምን መሰላችሁ? ችግኞቹ የተተከሉት ለአንድ ቀን ታይቶ በሚጠፋ ዘመቻ ነው፡፡ እርግጥ ነው ችግኞችን በዘመቻ መትከል ይቻል ይሆናል፤ በዘመቻ እንዲጸድቁ ማድረግ ግን አይቻልም፡፡ ስለማይቻልም ይደርቃሉ፡፡ ይህንን ያህል ሚሊዮን ችግኞች ተተከሉ የሚለው ዜና ግን አሪፍ የፕሮፓጋንዳ ግብአት ሆኖ ያገለግላል፡፡ ዘመቻ ከዚህ ያለፈ ጥቅም የለውም፡፡
የጽዳት ዘመቻውን ተመልከቱ፡፡ “ከዚህ ቀን እስከ እዚህ ቀን ድረስ የጽዳት ዘመቻ ነው” ይባላል፡፡ ነዋሪውም አምኖበትም ሳያምንበትም በዘመቻው ይሳተፋል፡፡ እናም በአስገራሚ መልኩ ዘመቻው የተካሄደበት አካባቢ ፍጹም ንጹህ ሆኖ ይጸዳል፡፡ አበቃ፡፡ ሁሉም “ዘማች” ወደቤቱ ይመለሳል፡፡ ከዚያስ? ከዚያማ በቀጣዩ ቀን አካባቢው መቆሸሹን ይቀጥላል፡፡ የሰው ልጅ ቆሻሻን የሚፈጥረው በዘመቻ አይደለም፡፡ በእለት ተእለት እንቅስቃሴው ውስጥ ነው፡፡ በመሆኑም የንጽህና ግንዛቤ ኖሮት፣ አካባቢውን በንጽህና መጠበቅ ያለበትም በዘመቻ ሳይሆን በእለት ተእለት እንቅስቃሴው ነው፡፡
የዘመቻ እንቅስቃሴ በርካታ ችግሮች አሉበት፡፡ አለመሳካቱም ከእነዚህ ችግሮቹ የሚመነጭ ነው፡፡ ሲጀመር በዘመቻ ላይ የሚሳተፉት ሰዎች የሚሳተፉት ስላመኑበትና በችግሩ ጉዳት ላይ የጠራ ግንዛቤ ስላላቸው ሳይሆን፣ አንድም ስለታዘዙ አሊያም ከሌሎች ተነጥለው መቅረት ስለማይፈልጉ ነው፡፡ እናም በዘመቻው ላይ በመሳተፍ ከጥራት ይልቅ ቁጥር ላይ ትኩረቱን ያደረገ ተሳትፎ ያደርጋሉ፤ በቃ፡፡ አሁንም በሌላ ዘመቻ ተጠርተው ወይም ተመልምለው እስከሚገኙ ድረስ በድርጊቱ ውስጥ አይኖሩም፤ የሉም፡፡ እናም ችግሩም ላይ ላዩን ይጠረግና ከስሩ ሳይነቀል ባለበት ይቀጥላል፡፡
በየመስኩ በዘመቻ ሊከወኑ የሚሞከሩ ሆኖም ተነካክተው የሚቀሩ ሌሎች ብዙ ማሳያዎችን ማንሳት ይቻላል፡፡ ብዙ ብዙ! በዘመቻ ለመፍታት የምንሞክረው ችግር ያህላል የለውም፡፡ ግን ለምን? ባለፈው ስርዓትም ሆነ አሁን ባለንበት ስርዓት የዘመቻ ባህል ችግሮቻችንን በዘላቂነት አልፈታም፡፡ ዘመቻ ትርፉ ምንም ነው፡፡ ምንም! ሆኖም ግን አሁንም እሱኑ የሙጥኝ ብለናል፡፡ እናም ከችግሮቻችን ጋር እያዘገምን አለን፡፡
ታዲያ መንግስት ይህንን እያወቀ ዘመቻን ለምን ባህል አደረገው? መልሱ ቀላል ነው፡፡ ለመንግስት የሚያስገኝለት “ያልተገባ ጥቅም” ስላለ፡፡
ይህንን እንመልከት፡፡ ደጋግመን እንዳልነው ዘመቻ በአብዛኛው ቁጥር ላይ ትኩረቱን ያደረገና በአንድ ወቅት ታይቶ የሚከስም እንዲሁም በርካታ ሰዎች የሚሳተፉበት እንቅስቃሴ ነው፡፡ እንግዲህ መንግስትም የሚያገኘው ጥቅም ከእነዚህ ከላይ ከጠቀስናቸው ሦስት የዘመቻዎቻችን መልኮች (ቁጥር ላይ ትኩረቱን ያደረገ፣ ወቅታዊ የሆነ እና በርካታ ሰዎች የሚሳተፉበት) የሚመነጭ ነው፡፡
አንደኛ ተሳታፊዎቹ አምነውም ይሁን ሳያምኑ በሚሳተፉበት ዘመቻ ውስጥ ገዢ የሚሆነው የቡድን መንፈስ በመሆኑ የዘመቻው ተሳታፊዎች ከዚህ መንፈስ ውጪ አይደሉም፡፡ እናም ቆይቶ በማይኖር ትኩስ ወኔ ይንቀሳቀሳሉ፡፡ በዚህም በዘመቻው በከፍተኛ ቁጥር ሊገለጽ የሚችል ስራ ይከናወናል፡፡ የዘመቻው ትኩረት (ከጥራት ይልቅ) ቁጥር በመሆኑም እሱን ያሳካል፡፡ እንግዲህ ይኸው ቁጥርም “ዜና” ሆኖ እንደሚታወጅ አንዘንጋ፡፡
ሁለተኛው ጉዳይ ዘመቻ በአንድ ወቅት ታይቶ የሚከስም (ወቅታዊ) መሆኑ ነው፡፡ እንደዚህ አይነት እንቅስቃሴዎች የህዝብን ትኩረት በማስቀየር ረገድ ያላቸው ሚና ከፍተኛ ነው፡፡ እናም ትኩረታችን ተቀይሮ ማሰብ ያለብንን ሳይሆን የሌለብንን እንድናስብ እንሆናለን፡፡
ሦስተኛውና መንግስት ከዘመቻዊ እንቅስቃሴዎች የሚያገኘው ጥቅም፣ ዘመቻ በባህሪው በርካታ ሰዎች በአንድ ላይ የሚሳተፉበት እንቅስቃሴ ከመሆኑ የሚመነጭ ነው፡፡ በዘመቻ ላይ በርካታ ሰዎች በአንድ ላይ እንዲሳተፉ ይደረጋል፡፡ በርካታ ሰዎችን በአንድ እንቅስቃሴ ውስጥ ማሰለፍ ደግሞ በመንግስት የሚደረጉትን እንቅስቃሴዎች የህዝብ ድጋፍና ይሁንታ ያላቸው አስመስሎ ያሳያል፡፡ እንዲሁም ሌሎችም ልብ የማንላቸውና ልብ ብንላቸውም ነገሬ የማንላቸው በርካታ ጥቅሞች አሉት- ለመንግስት፡፡
የምር የዚህችን ሀገር እድገት የምንናፍቅ፣ ለዘመናት ተተክለውባት የኖሩትን ችግሮቿንም መንቀል የምንፈልግ ከሆነ፣ አንዱ መፍትሔ ከ“ዘመቻ አስተሳሰብ” መውጣት ነው፡፡ ለዚህም ችግሮቹን በጥልቀት ማጥናት፣ በችግሮቹና በጉዳታቸው ላይም የጠራ ግንዛቤ እንዲኖር ማድረግ፤ መፍትሔዎቹን አጥንቶ መለየትና ዘላቂና ታይቶ የማይከስም እንቅስቃሴ ማድረግ ይገባናል፡፡ መፍትሔው ይኸው ነው፡፡ ሌላው ሌላው ከንቱ ነው፤ ከወቀሳና ከታሪክ ተጠያቂነት አያድንም፡፡
መልካም ሰንበት!  

           ባለፈው ሳምንት በተካሄደው 41ኛው የበርሊን ማራቶን የ31 ዓመቱ ኬንያዊ ዴኒስ ኪሜቶ ርቀቱን ከ2 ሰዓት ከ03 ደቂቃዎች በታች በመግባት የመጀመርያው ሰው ተብሎ ተደነቀ፡፡ ማራቶን መሮጥ ከጀመረ ገና የ5 ዓመታት ልምድ ያለው  ዴኒስ ኪሜቶ፤ ያስመዘገበው አዲስ የማራቶን ክብረወሰን 2 ሰዓት ከ02 ደቂቃዎች ከ57 ሴኮንዶች ነው፡፡ በ2013 እኤአ ላይ በሌላው ኬንያዊ ዊልሰን ኪፕሳንግ ተይዞ ከነበረው ሪከርድ ላይ 26 ሰከንዶችን አሻሽሏል፡፡   ከ2 ሰዓት ከ4 ደቂቃዎች በታች በመግባት የመጀመርያው ሰው የነበረው በ2008 እኤአ ላይ ኃይሌ ገብረስላሴ ነበር፡፡
በ41ኛው በርሊን ማራቶን ላይ ዴኒስ ኪሜቶ በሪከርድ ሰዓት ሲያሸንፍ የተሳትፎ እና የስፖንሰር ክፍያዎችን ሳይጨምር እስከ  154ሺ ዶላር ክፍያ ማግኘቱን የዘገበው ዴይሊ ኔሽን ነው፡፡ በውድድሩ አሸናፊነት 40ሺ ዶላር፤ ከ2 ሰዓት 4 ደቂቃዎች በታች ስለገባ የ30ሺ ዶላር ቦነስ እንዲሁም ለሪከርዱ 50ሺ ዶላር ተከፍሎታል፡፡ ከወር በኋላ በሚደረገው የኒውዮርክ ማራቶን ላይ ከሚሳተፈው የቀድሞ ሪኮርድ ባለቤት እና የልምምድ አጋሩ ዊልሰን ኪፕሳንግ ጋር ለማራቶን ሊግ የ500ሺ ዶላር ሽልማትም ይፎካከራል፡፡ ዊልሰን ኪፕሳንግ በኒውዮርክ ማራቶን ካላሸነፈ ኪሜቶ የማራቶን ሊጉን በመሪነት ማጠናቀቁ የማይቀር ይሆናል፡፡ እንደኬንያው ዴይሊ ኔሽን ጋዜጣ ዘገባ በኤልዶሬት ከሰፈር ሰዎች ጋር ውድድሩን ትመለከት የነበረችው ካሮሊን ቼፕኩሪር የተባለች ሚስቱ ሪከርዱን በሰበረበት ወቅት ከደስታ ብዛት ራሷን ስታለች፡፡በማራቶን ስኬቱ ያገኘውን ሃብት በትውልድ አገሩ ትምህርት ቤት በመገንባት እና ወጣት የቤተሰቡ አባላት ከፍተኛ ትምህርታቸውን እንዲከታተሉ እደግፍበታለሁ ብሏል፡፡ከዴኒስ ኪሜቶ አዲስ የዓለም ማራቶን ሪከርድ በኋላ ርቀቱ ከ2 ሰዓት በታች ይገባል የሚለው አጀንዳም  በይበልጥ ማነጋገር ጀምሯል፡፡ በዚሁ ጉዳይ ላይ አስተያየት የተጠየቀው ዴኒስ ኪሜቶ የራሱን ሪከርድ የማሻሻል አቅም እንዳለው ተናግሮ፤  በሚቀጥለው ውድድር 2 ሰዓት ከ1 ደቂቃ ልገባ እችላለሁ ብሏል፡፡ በበርካታ ጥናቶች በተሰሩ ትንታኔዎች 42.195 ኪሎሜትሮች (26 ማይሎች እና 385 ያርዶች) የሆነውን የማራቶን ርቀት ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት  እስከ 30 ዓመታት ሊፈጅ ይችላል ተብሎ ነበር፡፡ ሰሞኑን ግን ቢያንስ በ10 ቢበዛ በ15 ዓመታት ውስጥ ሊሳካ እንደሚችል በተለያዩ ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች ተገልጿል፡፡
ይህን አስደናቂ የስፖርት ውጤት እንደሚያሳኩ ግምት ያገኙት ሁለቱ የምስራቅ አፍሪካ አገራት ኬንያና ኢትዮጵያ ቢሆኑም ግምቱ ወደ ኬንያ አጋድሏል፡፡በተያያዘ በ41ኛው የበርሊን ማራቶን በወንዶች ምድብ ለሶስትኛ ተከታታይ ጊዜ የዓለም ማራቶን ሪከርድ በኬንያ አትሌቶች ሲሰበር በውድድር አይነቱ ከኢትዮጵያውያን ያላቸው ብልጫ በጋሃድ ተረጋግጧል፡፡ በሴቶች ግን ኢትዮጵያውያን እንደሚሻሉ የበርሊን ማራቶን አመልክቷል፡፡ በሴቶች  ያሸነፈችው ትርፌ ፀጋዬ በ2 ሰዓት ከ20 ደቂቃዎች ከ18 ሰከንዶች ሲሆን ፈይሴ ታደሰ በ9 ሰከንዶች ዘግይታ ሁለተኛ ታደለች በቀለ እና አበበች አፈወርቅ አራተኛ እና አምስተኛ ደረጃ በማግኘት የተሻለ ውጤት አስመዝግበዋል፡፡ በራድክሊፍ በለንደን ማራቶን የተመዘገበው ክብረወሰን 10 ዓመት ሆኖታል፡፡ ይህ ሪከርዷ 2 ሰዓት ከ15 ደቂቃዎች ከ25 ሰኮንዶች ነው፡፡
ዴኒስ ኪሜቶ ማነው?
በ14 ዓመቱ ትምህርቱን ያቋረጠው ዴኒስ ኪሜቶ አዘውትሮ አትሌቲክስን በቴሌቭዥን ይመለከት ነበር፡፡ በተለይ በ10ሺ ሜትር ኃይሌ ገብረስላሴና ፖል ቴርጋት በሲድኒ ኦሎምፒክ የነበራቸው ትንቅንቅ ወደ ስፖርቱ በደንብ አተኩሮ ለመግባት ምክንያት ሆኖታል፡፡ ከዚያ በፊት ግን ገበሬ እና እረኛ ነበር፡፡በግብርናው  ድንች እና በቆሎ እያመረተ የሚተዳደር ሰው ነበር፡፡ ከአምስት አመት በፊት አንድ የቺካጎ ትሪቡን ጋዜጠኛ ወደ ማራቶን እንዲገባ ከመከረው በኋላ ግን ግብርናውን ትቶ በሳምንት እስከ 250 ኪሎሜትሮች በመሮጥ በከፍተኛ ትጋት ይለማመድ ነበር፡፡ የሚመገበው ደግሞ ጓሮ ያፈራውን ፍራፍሬ እና አታክልቶችን ብቻ ነው፡፡ ዴኒስ ኪሜቶ የማራቶን ስልጠናውን በመደበኛነት የሚያከናውነው ከኤልዶሬት ወጣ በምትገኝ ካፓንግኡቱኒ በተባለች የገጠር ከተማ ነው፡፡ ከ2008 እኤአ ጀምሮ  አብረው ልምምድ የሚሰሩት ደግሞ የማራቶንን የምንግዜም ፈጣን ሰዓት በ2ኛ እና በ3ኛ ደረጃ የያዙት ኬንያውያኑ ጂኦፍሪ ሙታይ እና ዊልሰን ኪፕሳንግ ናቸው፡፡ የእነዚህ ሶስቱ አትሌቶች ማራቶንን መሮጫ አማካይ ሰዓት 2 ሰዓት ከ03 ደቂቃዎች ከ07 ሰከንዶች ነው፡፡ ዴኒስ ኬሚቶ ከ2012 ጀምሮ የማራቶን ሊግ አካል የሆኑ እና ሌሎች ትልልቅ ውድድሮችን ሮጧል፡፡ በ2012 በበርሊን ማራቶን ሁለተኛ ነበር፡፡ በ20014 የቦስተንን ማራቶንን አቋርጦ ወጥቷል፡፡ በ2013 የቶኪዮና የቺካጎ ማራቶኖች አሸንፏል፡፡ እንዲሁም ዘንድሮ የበርሊን ማራቶንን በሪከርድ ሰዓት በማሸነፍ በአጭር ግዜ የተሳካለት ዓለም አቀፍ ማራቶኒስት ሆኗል፡፡
ከ2 ሰዓት በታች የት እና መቼ?
ማራቶን ከ2 ሰዓት በታች ይገባባቸዋል ተብለው የተጠበቁ ውድድሮች የበርሊን እና የለንደን ማራቶኖች ናቸው፡፡ በተለይ የበርሊን ማራቶን ለውድድሩ አዳዲስ ሪከርዶች በተደጋጋሚ የሚመዘገቡበት አመቺ መድረክ ሆኖ  ቀጥሏል፡፡ ባለፉት 11 ዓመታት 6  የዓለም ማራቶን ሪከርዶች በበርሊን ማራቶን ተሰብረዋል፡፡ በተለይ ያለፉት አምስት የማራቶን  ሪከርዶች ደግሞ የኬንያ እና የኢትዮጵያ አትሌቶች የተፈራረቁባቸው ናቸው ፡፡ በ2003 እኤአ ላይ ኬንያዊው ፖል ቴርጋት በ2 ሰዓት ከ04 ደቂቃዎች ከ55 ሴኮንዶች፤ በ2007 በ2 ሰዓት ከ04 ደቂቃዎች ከ26 ሴኮንዶችና በ2008 እኤአ 2 ሰዓት ከ03 ደቂቃዎች ከ59 ሴኮንዶች በኢትዮጵያዊው ኃይሌ ገብረስላሴ በርሊን ላይ የተመዘገቡ የሪከርድ ሰዓቶች ነበሩ፡፡ ከዚያ በኋላ ኬንያውያን የሪከርድ መዝገቡን ተቆጣጥረውታል፡፡ በ2011 እኤአ በ2 ሰዓት ከ03 ደቂቃዎች ከ38 ሴኮንዶች  ፓትሪክ ማኩ፤ በ2013 እኤአ 2 ሰዓት ከ03 ደቂቃዎች ከ23 ሴኮንዶች  ዊልሰን ኪፕሳንግ እንዲሁም በ2014 እኤአ በ2 ሰዓት ከ02 ደቂቃዎች ከ57 ሴኮንዶች ዴኒስ ኪሜቶ ናቸው፡፡ መረጃዎች  እንደሚያመለክቱት ባለፉት 30 ዓመታት ከተመዘገቡ የማራቶን ሪከርዶች ስምንቱ በበርሊን ማራቶን  የተገኙ ናቸው፡፡ አራቱ በቺካጎና በለንደን አራት ሪከርዶች እንዲሁም  በሮተርዳም 3 የዓለም ማራቶን ሪኮርዶች ተመዝግበዋል፡፡
የዓለም ማራቶን ሪከርድ በአይኤኤኤፍ እውቅና ተሰጥቶት መፅደቅ የጀመረው በ2004 እኤአ ነው፡፡ ስለዚህም ባለፈው ሳምንት በዴኒስ ኪሜቶ የተመዘገበው በአይኤኤፍ የሚታወቅ እውቅና የሚያገኝ የዓለም ማራቶን ሪኮርድ ይሆናል፡፡ ከዚያን በፊት ክብረወሰኑ ይመዘገብ የነበረው ምርጥ ሰዓት እየተባለ ነበር፡፡ በ1908 እኤአ ላይ የተመዘገበው የመጀመርያው የማራቶን ምርጥ ሰዓት  2 ሰዓት ከ55 ደቂቃዎች ከ18 ሴኮንዶች ሲሆን ከዚያን በኋላ እስከ ዴኒስ ኪሜቶ ክብረወሰን ድረስ ከ45 በላይ የማራቶን ክብረወሰኖች ተመዝግበዋል፡፡
የማራቶን ሪከርድ በ1900  2፡40 ፤ በ1920ዎቹ 2፡32፤ በ1950ዎቹ 2፡15፤ በ1960ዎቹ 2፡08 ነበር፡፡ ከ1999 እኤአ ወዲህ በ3 ደቂቃዎች ተሻሽሎ 2፡05 ደረሰ፡፡ ከ2004 እኤአ ጀምሮ 2፡04 እና 2፡03 እያለ ቀጥሏል፡፡  ከ10 ዓመታት በፊት ከ2 ሰዓት 5 ደቂቃዎች በታች ማራቶን የሚገቡ ሁለት አትሌቶች ነበሩ፡፡ ባለንበት ጊዜ ግን በዚያ  ሰዓት የሚገቡት ከ35 በላይ ናቸው፡፡ ከ2 ሰዓት ከ06 ደቂቃዎች በታች የሚገቡ ከ50 በላይ ማራቶኒስቶች ይገኛሉ፡፡ በ2013 እኤአ ላይ ከ2 ሰዓት ከ10 ደቂቃዎች በታች ከገቡ 149 አትሌቶች 80ዎቹ የኬንያ ሲሆኑ የኢትዮጵያ 47 ናቸው፡፡
ብዙዎቹ የሁለቱ አገራት አትሌቶች በመጀመርያ ውድድራቸው ከ2 ሰዓት 4 ደቂቃዎች ውስጥ የሚገቡት 20 ደርሰዋል፡፡
ስፖርት ሳይንቲስት በድረገፁ በሰራው ትንተና የማራቶን ርቀትን ከ2 ሰዓት በታች የሚገባ አትሌትን ለማግኘት ከ35 እሰከ 40 ዓመታት እንደሚፈጅ ገምቶ ነበር፡፡ ይህ እንዲሆን ደግሞ በየዓመቱ የማራቶን ሪከርድ ሰዓት በአማካይ በ15 ሰከንዶች እየተሻሻለ መቀጠል አለበት የሚል ድምዳሜ ላይም ደርሷል፡፡በርግጥ የማራቶን ሪከርድ ሰዓትን ከ20 ሰከንዶች በላይ ማሻሻል ትልቅ የማራቶኒስት ስኬት ነው፡፡
ከዴኒስ ኪሜቶ አዲስ የማራቶን ሪከርድ በኋላ ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት 157 ሴኮንዶች ይቀራሉ፡፡ እነዚህን ሴኮንዶች በማራገፍ ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት በርካታ ሁኔታዎች ወሳኝ ይሆናሉ፡፡ በመጀመርያ ደረጃ የማራቶኑን ርቀት ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት የሚችሉት አትሌቶች ኬንያዊ ወይንም ኢትዮጵያ ዜገነት ያላቸው መሆኑ ይጠበቃል፡፡ ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት የሚችል አትሌት በሰዓት 13.1 ማይሎችን መሸፈን ይጠበቅበታል፤ ይህ ብቃት ያላቸው የሁለቱ አገራት አትሌቶች ብቻ መሆናቸውን ባለሙያዎች ያስረዳሉ፡፡
ከእነዚህ ሁለት የምስራቅ አፍሪካ አገራት የሚወጣ አትሌት ከ7ሺ እስከ 8ሺ ጫማ ከፍተኛ አልቲትዩድ ባለበት አገር መኖሩ፤ ከ4ሺ ጫማዎች በታች ባለ ስፍራ  ልምምዱን መስራቱ ለሚያስፈልገው ብቃት አስፋላጊ ነው፡፡ ከዚያም አትሌቱ  ከባህር ጠለል በታች ዝቅተኛ በሚባል አገር ውድድሩን ማድረጉ ከ2 ሰዓት በታች የመገባቱን ሁኔታ ያጠናክረዋል፡፡
በሌላ በኩል ማራቶንን ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት እንደ ዩሴያን ቦልት አይነት የላቀ ብቃት ያለው አትሌት መፈጠሩም ትረጉም ይኖረዋል፡፡ ከዩሴያን ቦልት በፊት መቶ ሜትርን በ9.6 ሰከንዶች ለመሸፈን ይቅርና በ9.7 ሰከንዶች አይገባም ይባል ነበር፡፡ በአጠቃላይ የሰው ልጅ በሚችለው ብቃት ማራቶንን ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት  የስልጠና ሳይንስ እና ቴክኖሎጂም ለውጥ ይፈጥራል፡፡ 40 አመት በፊት የነበረው ስልጠና አሁን በከፍተኛ ደረጃ ማደጉ እንደ አጋዥ ምክንያት ሊጠቀስ የሚችል ነው፡፡አዲዳስ ለማራቶን ሯጮች የሚሰራቸው የመሮጫ ጫማዎች ለሪከርድ ሰዓቶች መመቸታቸው ሌላው አስተዋፅኦ ነው፡፡ ባለፈው ሳምንት እንኳን ዴኒስ ኪሜቶ ለሰበረው ሪከርድ አዲዮስቡስት የተባለው መሮጫ ጫማ ጠቅሞታል ተብሏል፡፡ ሌላው ኬንያዊ ፓትሪክ ማኩ ከ2 አመት በፊት ሪከርድ ያስመዘገበው በዚሁ መሮጫ ጫማ የነበረ ሲሆን በአሁኑ ጊዜ የማራቶንን የምንግዜም ፈጣን ሰዓት ያስመዘገቡት አራት የኬንያ አትሌቶች እና ኃይሌ ገብረስላሴ ጨምሮ የሚጠቀሙት አዲዮስቡስት መሆኑ ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት የሚደረገውን ጥረት የአዲዳስ ምርት ሊያግዘው እንደሚችል እምነት አሳድሯል፡፡  አሯሯጮችም የሚያከናውኑት የቡድን ስራ ምክንያት እንደሚሆንም ተጠቅሷል፡፡ አሯሯጮቹ  ሙሉ ለሙሉ ማራቶን ቢሮጡ ሪከርዶች እና ፈጣን ሰዓት የማስመዝገብ ብቃት አላቸው፡፡ በ2011 እኤአ ላይ የኃይሌን ሪከርድ የነጠቀው ፓትሪክ ማኩ በፊት አሯሯጩ እንደነበር ይታወቃል፡፡ አንዳንድ አስተያየት ሰጭዎች ብራዚል በሪዮዴጄኔሮ ከተማ ከምታዘጋጀው 30ኛው ኦሎምፒያድ በፊት አዲሱ የዴኒስ ኪሜቶ የማራቶን ሪከርድ ሊሰበር እንደሚችል ይገልፃሉ፡፡ ከ2 ሰዓት በታች የሚገባ አትሌት ደግሞ ከ10 እስከ 15 ዓመታት ጊዜ ውስጥ ይገኛል እየተባለ ነው፡፡
እነማን ታጭተዋል ኬንያዎች፤ ቀነኒሳ እና ሌሎች
ከሶስትና አራት የውድድር ዘመናት በፊት ከ2 ሰዓት ከ5 ደቂቃ በታች ከሚገቡ 10 አትሌቶች ሰባቱ እድሜያቸው በአማካይ 24 የሆኑ ነበሩ፡፡ ባለፉት አምስት አመታት የታየው ግን ሪከርድ የመስበር እድል ያላቸው በእድሜያቸው በሰል ያሉ አትሌቶች ናቸው፡፡ በ2011 እኤአ ላይ የኃይሌን ሪከርድ የሰበረው ፓትሪክ ማኩ 29፤ አምና የፓትሪክ ማኩን ሪከርድ ያሻሻለው ሌላው ኬንያዊ ዊልሰን ኪፕሳንግ 31 ዓመታቸው ነበር፡፡ በ2007 እና በ2008 እኤአ በቅደም ተከተል ለሁለት ጊዜ ሪኮርዶቹን የሰበረው ኃይሌ ገብረስላሴ በ34 እና 35 አመት እድሜው ነበር፡፡
እንደኦልአትሌቲክስ ድረገፅ ስታስቲካዊ መረጃ እና ደረጃ በረጅም ርቀት የአትሌቲክስ ውድድሮች ኬንያውያን በወንዶች ምድበ ከፍተኛ ብልጫ ሲኖራቸው ኢትዮጵያውያን በሴቶች ምድብ ይሻላሉ፡፡ በ2012 እና በ2013 ከተመዘገቡ የማራቶን ፈጣን ሰዓቶች ኬንያውያን በወንዶች ምድብ ሲበዙ በሴቶች ኢትዮጵያውያን ይበዛሉ፡፡  በአሁኑ ጊዜ በ2 ሰዓት ከ03 ደቂቃዎች ከ23 ሰከንዶች እስከ 2 ሰዓት ከ4 ዲቃዎች ከ05 ሰከንዶች የተመዘገቡ አራት ፈጣን ሰዓቶች የኬንያውያን ናቸው፡፡ ኢትዮጵያን ከእነዚህ ፈጣን ሰዓቶች በመቀጠል የተመዘገቡትን አምስት ፈጣን ሰዓቶች አስመዝግበዋል፡፡ ብዙዎቹ የኢትዮጵያ አትሌቶች ከኬንያውያን አንፃር ብልጫ ያላቸው ትልልቅ ማራቶኖችን ደጋግሞ በማሸነፍ እንጅ ምርጥ ሰዓት በማስመዝገብ አይደለም፡፡ በማራቶን ሪከርዶች ታሪክ 90 በመቶው ድርሻ በኬንያ እና ኢትዮጵያ አትሌቶች የተመዘገበ መሆኑ ከእንግዲህ ለሚመዘገቡ የማራቶን ሪከርዶች ዋና እጩ ተደርገዋል፡፡
ከ2 ሰዓት በታች ማራቶንን ለመግባት ወይንም አዲስ የማራቶን ክብረወሰን ለማስመዝገብ ቅድሚያ ግምት ካገኙ አትሌቶች የመጀመርያው ቀነኒሳ በቀለ ነው፡፡ በፓሪስ የመጀመርያ ማራቶኑን በመሮጥ 2 ሰዓት ከ05 ደቂቃዎችች ከ03 ሰከንዶች አስመዝግቦ የቦታውን ክብረወሰን ያሻሻለው የ31 ዓመቱ ቀነኒሳ በቀለ ማራቶን ልዕልቷን ወደ ኢትዮጵያ ይመልሳል ተብሎ በብዙ ሚዲያዎች ግምት ተሰጥቶታል፡፡ ቀነኒሳ በርሊን ላይ ከሮጠ ለሪከርዱ እድል ይኖረዋልም ተብሏል፡፡ ከቀነኒሳ ባሻገር ግምቱ ወደ ኬንያውያን አትሌቶች በብዛት ያጋደለ ነው፡፡
ከሳምንት በፊት በበርሊን ማራቶን ሁለተኛው የዓለም ፈጣን ሰዓ ያስመዘገበው ሌላው ኬንያዊ ጄፍሪ ሙታይ ግንባር ቀደም ግምቱን በመውሰድ ይጠቀሳል፡፡
በቆጂእና አካዳሚዎቻችን  የኬንያን ብልጫ እንዲመልሱ
የዓለም ምርጥ ማራቶኒስቶች ከሁለቱ የምስራቅ አፍሪካ አገራት ከኬንያ እና ከኢትዮጵያ እየወጡ ናቸው፡፡ በኢትዮጵያ በቆጂ የምትባለዋ የክልል ከተማ በኬንያ ኤልዶሬት እና ኢቴን የተባሉ ከተማዎች ማራቶኒስቶችን በማውጣት በመላው ዓለም የሚስተካከላቸው የለም፡፡ ኦሮምያ ክልል አርሲ ውስጥ የምትገኘው የበቆጂ ገጠር ከተማ የትልልቅ የዓለም ማራቶኒስቶች መፍለቂያ በመሆኗ በየጊዜው ከፍተኛ ትኩረት እያገኘች በመላው ዓለም በሚሰራጩ ሚዲያዎች ተዳስሳለች፡፡ የበቆጂ ለጥ ያለ መልክዓ ምድር እና ተስማሚ  እና ተስማሚ አየር ንብረት  በርካታ የውጭ አገር አትሌቶችን እየሳበም ነው፡፡  ከወራት በፊት አንድ የቱርክ ጋዜጠኛ የበቆጂ ከተማን በመጎብኘት ያቀረበው ዘገባ ያቀረበው አሃዛዊ መረጃ የሚያስገርም ነው፡፡  17ሺ ነዋሪዎች ያሏት የበቆጂ ከተማ በረጅም ርቀት የአትሌቲክስ ውድድሮች ታሪክ ከፍተኛውን ውጤት ያስመዘገቡ የዓለም ምርጥ አትሌቶች መገኛ ስትሆን፤ 7 የኦሎምፒክ ሻምፒዮኖችን አፍርታለች፡፡ ቀነኒሳ በቀለ እና ታናሽ ወንድሙ ታሪኩ በቀለ፤ ደራርቱ ቱሉ እና የእህቷ ልጆች የሆኑት የዲባባ እህትማማቾች፤ ፋጡማ ሮባ እና ቲኪ ገላና ትውልዳቸው ከበቆጂ መሆኑን የዘረዘረው የቱርኩ ጋዜጠኛ፤ የበቆጂ ሯጮች ባለፉት 20 ዓመታት በዓለም አትሌቲክስ 16 ሜዳልያዎች 10 የወርቅ፤ ከ30 በላይ የዓለም ሻምፒዮና ሜዳልያዎችን መሰብሰባቸውን ጠቅሷል፡፡ የበቆጂን አትሌቶች ስኬት በንፅፅር ሲያስቀምጠው 17ሺ ህዝብ ያላት የገጠር ከተማዋ በኦሎምፒክ የወርቅ ሜዳልያዎቿ ብዛት 1.2 ቢሊዮን ህዝብ ካላት ህንድ ትበልጣለች፤ 247 ሚሊዮን ህዝብ ያላት ኢንዶኔዥያ በሁሉም ኦሎምፒኮች በሁሉም ውድድሮች ባላት ተሳትፎ ካገኘችው የሜዳልያ ስብስብ በእጥፍ የሚል የሜዳልያ ስብስብም ካላት አሳይቷል፡፡ የዲባባ እህትማማቾች በኦሎምፒክ መድረክ ያገኟቸው የወርቅ ሜዳልያዎች ብዛት 22 ሚሊዮን ህዝብ ካላት ሲሪያ እና 28 ሚሊዮን ህዝብ ያላት ሳውዲ አረቢያ በድምር የሰበሰቡትን እንደሚበልጥ አመልክቶም ጥሩነሽ ዲባባ የሰበሰበችውን የወርቅ ሜዳልያ ብዛት 179 ሚሊዮን ህዝብ ያላት ፓኪስታን አለማግኘቷን አውስቷል፡፡  አሁን በዓለም የጎዳና ሩጫዎች እና ማራቶኖች ከፍተኛ ውጤት እያስመዘገቡ ያሉ አትሌቶች ከበቆጂ የተገኙ መሆናቸው የከተማዋን የማራቶን ሯጮች መፍለቂያነት ያረጋግጣል፡፡ ስለዚህም የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌደሬሽንና የኢትዮጵያ ኦሎምፒክ ኮሚቴ በዚህች ከተማ በስፋት አትሌቶችን ለማፍራት መንቀሳቀሳቸው ማራቶን ልዕልቷን ወደ ኢትዮጵያ ለመመለስ ወሳኝ ተግባር ይሆናል፡፡ እንደበቆጂ ሁሉ ኬንያም ምርጥ የረጅም ርቀት ሯጮቿንና ማራቶኒስቶቿን የምታገኝባቸው ሁለት ልዩ አካባቢዎች ኤልዶሬት እና ኢቴን የተባሉት የገጠር ከተሞች ናቸው፡፡ በተለይ ኢቴን ከቅርብ አመታት ወዲህ የማራቶን ሯጮች መገኛ ብቻ ሳይሆን የዓለም ማራቶን ሯጮች መናሐርያ መሆንም ጀምራለች፡፡   ከሁለት ዓመት በፊት የኬንያ ምርጥ ማራቶን ሯጮች በሚፈልቁባት ኢቴን የተባለችው ከተማ በለንደን ማራቶን አዘጋጆች የሚደገፍ የማሰልጠኛ ትራክ ተሰርቶ ስራ ጀምሯል ባለፉት አምስት አመታት በርካታ የእንግሊዝ እና የአውሮፓ ሯጮች ከተማዋን መቀመጫቸው በማድረግ ትልልቅ የልምምድ ፕሮግራሞችን ያከናወናሉ፡፡ አንዳንድ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት በማንኛውም ወቅት በዚህች ኢቴን በተባለች ከተማ ቢያንስ እስከ 30 የውጭ አገር ሯጮች ይሰራሉ፡፡
በአጠቃላይ የኢትዮጵያን አትሌቲክስ የሚመሩ ተቋማት በስፖርቱ ከፍተኛ ስኬትን ማግኘት፤ በኬንያ የተወሰደውን ብልጫ ለማስተካከል እንዲሁም በሪከርድ ሰዓቶች ውጤቱን የሚያጅብ ትውልድ ለመፍጠር በትጋት መንቀሳቀስ ይገባቸዋል፡፡ ለዚህም በአገሪቱ የተለያዩ ክልሎች ያሉ አዳዲስ አካዳሚዎች በሙሉ ራእይ እና አቅም መስራታቸው ግድ ይላል፡፡ የኢትዮጵያ ወጣቶች ስፖርት አካዳሚ በተለይ ለአትሌተክስ ስፖርት ውጤታማነት ጉልህ አስተዋፅኦ እንደሚኖረው በተግባራዊ እንቅስቃሴዎች መታየቱ ይጠበቃል፡፡ ታዳጊዎች ጥቅም ይኖረዋል፡፡ ከአካዳሚዎቹ በ2016 ሪዮዲጂኔሮ እስከምታስተናግደው 31ኛው ኦሎምፒያድ ድረስ ምርጥ ወጣት አትሌቶችን በማፍራት የኢትዮጵያን አትሌቲክስ ከኬንያ እጅግ ወደኋላ እየራቀ የመጣበትን ሁኔታ መለወጥ  ይጠበቃል፡፡ አካዳሚዎቹ ዓለም አቀፍ የአትሌቲክስ እድገት እና እንቅስቃሴን በሙሉ ፍላጎት በመከታተል በብሩህ ራዕይ የሚሰሩ ብቁ ባለሙያዎች ኖሯቸው መስራት አለባቸው፡፡ በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የተሠሩት አካዳሚዎች ከመሠረተ ልማት ግንባታው ባሻገር ወደተግባራዊ ስልጠና መግባት ይጠበቅባቸዋል፡፡ የአርሲ አካዳሚዎች የአትሌቶች መገኛ ለሀገራቸው በቆጂ እና በአርሲም ከተማ አሰላ ሁለት አካዳሚዎች በስፖርት ሚኒስትር ተገንብተዋል፡፡ ከ600 በላይ ታዳጊ አትሌቶችን ሲያሰለጥኑ የቆዩ ናቸው፡፡ እነዚህ ታዳጊ አትሌቶች የኬንያን የበላይነት ለመስተካከል ትኩረት ተሰጥቶ ከተሰራባቸው ስኬታማ ለመሆን አይቸግርም፡፡ ይህ ካልሆነ ግን ማራቶን ልዕልቷ ተብሎ ሲዘመር የኖረው የበላይነት ማራቶን ሃራምቤ ተብሎ በኬንያውያን የበላይነት ይቀጥላል፡፡

አብዛኞቹ የአገሪቱ ባለስልጣናት ፖሊሲ ሲያወጡ ጠንቋይ ያማክራሉ
የታይላንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ፕራዩዝ ቻኖቻ፣ ወደ ጠንቋዮች ጎራ ብሎ የመጪውን ጊዜ ዕጣ ፋንታ በተመለከተ የሚሰጡትን ትንቢትና ምክር መስማት ክፋት የለውም፤ ጥንቆላም ራሱን የቻለ ጥበብ ነው ሲሉ መናገራቸውን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
“ጠንቋዮች የሚነግሩኝን ትንቢት ልብ ብዬ እሰማለሁ፡፡ ምክራቸውንም እቀበላለሁ፡፡ እንዲያውም በቅርቡ በአገሪቱ ከሚገኙ መገናኛ ብዙሃን ጋር ግጭት ውስጥ ልገባ እንደምችል አስጠንቅቀውኛል” ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ መገናኛ ብዙሃን መሪያችን ጠንቋይ ቤት ይሄዳሉ ሲሉ ያሰራጩት ዘገባም ትክክለኛ እንደሆነ አረጋግጠዋል፡፡
ቻኖቻ በመገናኛ ብዙሃን ስለጠንቋይ አማኝነቴ የሰማችሁት ትክክል ነው ሲሉ ባለፈው ማክሰኞ መናገራቸውን የገለጸው ዘገባው፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጠላቶቻቸው ካሰሩባቸው ድግምትና አስማት ለመንጻት ሲሉ፣ ከእግር እስከ ራሳቸው ጠበል መጠመቃቸውን በወሩ መጀመሪያ ላይ በይፋ መናገራቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡
የአገሪቱን የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ታክሲን ሺንዋትራን ጨምሮ በርካታ ደንበኞችን ወዳፈራው ኢት የተባለ የማይናማር ታዋቂ ጠንቋይ በመሄድ ምክር ይሰማሉ መባሉን ያስተባበሉት ቻኖቻ፣ ይሄም ሆኖ ግን ወደ ጠንቋዩ የመሄድ ፍላጎት እንዳላቸው አልደበቁም፡፡
ከአገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣናትና ፖለቲከኞች አብዛኞቹ፣ የፖሊሲ ለውጥ ለማድረግ ሲያስቡ ወደ ጠንቋዮች ሄደው፣ “ይበጃል፣ አይበጅም?” ብለው የማማከር ልማድ እንዳላቸው የጠቆመው ሮይተርስ፣  ታይላንድ ወደዘመናዊነት እየተሸጋገረች ያለች አገር ብትሆንም፣ ለረጅም ዘመናት የዘለቀው ጥንቆላና መሰል የባዕድ አምልኮ አሁንም ድረስ በስፋት እንደሚከናወንባት አመልክቷል፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

እየጮሁ ማውራትና መጨቃጨቅ ተከልክሏል
በሞባይል ወደ ውጭ አገራት መደወል አይፈቀድም
የሞባይል ባለቤት መሆን የሚችሉት ከፍተኛ ደረጃ ላይ የሚገኙ ብቻ ናቸው

የሞባይል ስልክ ተጠቃሚዎች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ በሚገኝባት ደቡብ ኮሪያ፣ በተጠቃሚዎች ላይ የሚታየውን የስነ-ምግባር ጉድለት ለመቅረፍ ሲባል አዲስ የአጠቃቀም መመሪያ መውጣቱን ቢቢሲ ዘገበ፡፡ዮንሃፕ የተባለውን የደቡብ ኮሪያ የዜና ተቋም ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ በአገሪቱ የሞባይል ተጠቃሚዎች ላይ ከሚታዩ የስነ-ምግባር ጉድለቶች መካከል፣ ሰው በተሰበሰበባቸው አካባቢዎች ጮክ ብሎ ማውራትና መጨቃጨቅ ይገኙባቸዋል፡፡አዲሱ የአገሪቱ የሞባይል አጠቃቀም የስነ-ምግባር መመሪያ እንደሚለው፣ ተጠቃሚዎች ህዝብ በተሰበሰበባቸው አካባቢዎች ድምጻቸውን ቀነስ አድርገው በትህትና መነጋገር ይኖርባቸዋል፡፡በሞባይል ስልክ የሚደረጉ አላስፈላጊ ጭቅጭቆችን ለማስወገድ ሲባልም፣ የተደወለላቸው ሰዎች ጥሪያቸውን ሲመልሱ፣ ለደዋያቸው ማንነታቸውን ማስተዋወቅ ይጠበቅባቸዋል፡፡
 የደዋያቸውን ማንነት እንዳወቁ መግለጽም ይገባቸዋል፡፡ ይህም ደዋዩ ራሱን ለማስተዋወቅ ጊዜ እንዳይፈጅ ያግዘዋል ተብሏል፡፡
እ.ኤ.አ በ2008 የሞባይል ስልክ አገልግሎት ተጠቃሚ በሆነችው ደቡብ ኮሪያ፣ የአገልግሎቱ ተጠቃሚዎች ቁጥር ከ2 ቢሊዮን በላይ እንደደረሰ የጠቆመው ዘገባው፣ ይህም ሆኖ ግን አሁንም ድረስ አለማቀፍ ጥሪዎችን ማድረግ ክልክል ነው፡፡
የሞባይል ስልክ ባለቤት መሆን የሚችሉትም፣ በከፍተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ የማህበረሰብ ክፍሎች ብቻ ናቸው ብሏል፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

         አዲሱ ዓመት አደይ አበባ ነስንሶ፣ በጀንፈርዋ ትኩስ ፈገግታ ጣዕም ነፍሳችንን መቀነት እያስፈታ ማታለሉን ለምዶበታል፡፡ … ወንዞች እየሳቁ ተራሮች እየተጀነኑ ከፀሐይ ጋር ሲስቁ፣ እኛም ከበሮዋችንን ይዘን “አበባየሁ ወይ!... ለምለም!” እንላለን፡፡ እግዜርም ለደሀውም ለሀብታሙም ደስ ይበለው ብሎ ተፈጥሮ በዓመት አንዴ ፊቷን እንድትታጠብ ሳሙና ያቀብላታል፡፡ ውበት ስንል ታዲያ ሁሌ ተፈጥሮው ያመዝናል፡፡ ለምሳሌ ዮሐንስ አድማሱ ስንኞች ከርክሞ የሚናገርላት ውበት፤ ደስታን እንደክብሪት መጫርዋ ይቀራል እንዴ?
ቀስተ ደመናው፣
በህብሩ አሸብርቆ፣ ጎበብ ቀለስ ብሎ፣
ባድማስ በሰማዩ ሰፍኖበት ተንጣሎ፣
ይሰለቻል ወይ?
ጎበዝ ይሰለቻል? … አይመስለኝም፡፡ እንዲያውም የሰው ልጅ ማግባቢያ፣ ተስፋ መቋጠሪያው ይህ ሳይሆን አይቀርም፡፡ ከአንዱ ተራራ ግርጌ ሌላው ተራራ ግርጌ የተሰካው የነጠላ ጥለት የመሰለ ህብረ ቀለማዊ መቀነት እንዴት አያጓጓም! … እንዴት ይሰለቻል? … ከላይ እንዳልኩት ማዘጋጃ ቤት እንደሚሰቀል ባንዲራ በየዕለቱ እንዳንለምደው ቀስ እያለ ብቅ የሚለውም ለዚህ መሰለኝ! … እንደመስቀል ወፍም ባይሆን!
የልምላሜ ምሥጢር በልምላሜ ሰልቶ
አምሮ ተሰንግሎ በተፈጥሮ ጠርቶ
ይሰለቻል ወይ?
ይህ አሁን ያለንበትን ወቅት ነው የሚያሳየን፡፡ አረንጓዴ ምንጣፍ ለብሶ በእግር ሊረግጡት በሚያሳሳበት ጊዜ ነው፡፡ ታዲያ ይሰለቻል እንዴ?
የመፀው ምሽቱ
አብራጃው ሲነፍስ የህዳር የጥቅምት
የትሳስ አየር
ጨረቃ አደድላ ተወርዋሪ ኮከብ
ሲነጉድ ሲበር፣
ይሰለቻል ወይ?
በክንድ ላይ ሁና
ብላ ዘንጠፍ ዘና
ሶባ ቀዘባዋ የሚያፈቅሯት ልጅ
ፍቅር ሲፈነድቅ ሲሰራ ሲያበጅ
ይሰለቻል ወይ?
የውበት የፍቅር የሀሴት ሲሳይ፡፡
ውበትን ከየወቅቱ መዝዞ፣ የሌቱን ለሌት፣ የቀኑን ለቀን ማስጌጫ ያደረገው ገጣሚስ ውበት የሚያሸትበት አፍንጫ ረጅም አይደለም?
ተፈጥሮ ሁሌ ውበት አጥቅሳ፣ ቀለም ነክራ የምታስጨፍር ብቻ አይደለችም፡፡ በከሰል ፊትዋ ታሳርራለች፤ በፍም ገላዋ ታነፍራለች፡፡ በነደደ ገላዋ እምባ ትጠባለች፡፡ ይህንንም በጦፈ ስሜት ባዘነ ድምጸት የሚነግረን ገጣሚ ነቢይ መኮንን ነው፡፡
የተፈጥሮ ጥርሶች እየሳቁ ማሳቅ፣ እየፈነደቁ ማማለል ብቻ ሳይሆን፣ በተፋቀና በሚያምር ውበት ውስጥ ተደብቀው ይናከሳሉ፤ አጥንት ይቆረጥማሉ፡፡ የሎሌያቸውን ያዳም ልጅ እግር ነክሰው ሩጫውን ያቆማሉ - ይላል፡፡ ጎምላላው ደመናም ሲያሻው አናታችን ላይ እንደ ጦር መሪ ይጀነን እንጂ ሲለው በናፍቆት እስክንቃጠል ፊቱን ያሻሸናል፡፡ የነቢይ “የደመናው ሎሌ” እንዲህ ይላል፡-
ለወትሮው፤
ደመና
ፊቱ እየጠቆረ
ዐይኖቹን አሻሽቶ ያነባ ነበረ፡፡
ይዘንብ ነበረ፡፡
የዘንድሮ ሰማይ፤
እየሳቀ ገዳይ፤
ፈጋግ ሰማያዊ መልኩን አሳምሮ
ስንቱን ፈጀ በላ፣ ከራብ ተመሳጥሮ፡፡
የምድር ከርስ አረረ፡፡
ሀገር ጦም አደረ፡፡
ሰው ምጡ ጠናና ዐይኖቹን አቀና፡፡
እንደው ከርተት ከርተት፣ ሰማይ ለሰማይ
ዋ ምስኪን ገበሬ፣ ምን ውሃ እህል ሊያይ!
ውሃ - የለሽ ኅዋ፣ ጠብታ አልባ ጠፈር
ሰማይ አይታረስ ባይን ብሌን ሞፈር፣
የደመናው ሎሌ የደመናው አሽከር
የዕለት ግብሩ ሆነ ጦም ውሎ ጦም                ማደር …
እንግዲህ ውቡ የመስከረም ሰማይ፤ ቅድመ ዮሐንስ ያለው … የመጸውም ወራት ሁሉም ጀርባ ሰጥተው፤ ብሩህ ገፃቸውን የቁጣ እሳት፤ የፍርሀት ጠላሸት አልብሰው የሚከሰቱበትም ጊዜ አለ፡፡ ተፈጥሮ ቁማርተኛ ናት፡፡ ታባብልና ትበላለች፡፡ ታሳስቅና እግሯ ስር ትጥላለች፤ ታዲያ ገጣሚውም እንደየጊዜው ስሜቱ፣ እንደ ወቅቱ ትዝብት ነፍስ ያንከባልላል፤ ቃላት እንደጥይት ያቃጥላል፣ ብዕር እንደጠመንጃ ይወለውላል!
ሰማይ እየሳቀ፣ ገደለ፡፡ ከራብ ጋር ገጥሞ የአዳምን ዘር አጠቃ፡፡ የአዳምን ልጅ ደለለ፡፡ ቢለማመጠው እንኳ ጆሮ ዳባ ልበስ አለ ነው የሚለው፡፡ ሰማይ ስለከዳው ጦም አዳሪ ሆነ፡፡ ጦም ማደሩ ብቻ አይደለም፤ ጦማደሩ ግብሩ ሆነ፡፡ እንግዲህ ግብሩ ጦም ማደር ከሆነ፣ ለተከታዩ ክስተት ነቢይ ፍለጋ መሄድ አይሻም! … ተከታዩ እልቂት ነው፡፡
ወጣትዋ ገጣሚት ሰናይት አበራም ስለ አዲስ ዓመት ተፈጥሮ፣ ስለወፎች ዝማሬ፣ ስለነሐሴ ሰማይ መልክ ታወራለች በስንኝ፡-
ወፎች - ሲዘምሩ
ዛፎች - ሲሸልሉ
ሲደንስ - ተራራ
የነሃሴ ሰማይ
ሲሄድ - እየጠራ
ከርሞ - ተፋጠጠ
ሰው - ከራሱ ጋር
ይሄኛው የተለየ አተያይ ነው፡፡ ሰው ጉዱ ፈላ፣ ገመናው ተገለጠ፤ እያለች ነው፡፡ አምና የነበረው ተፈጥሮ ሌላ መልክ ይዞ ብቅ ሲል፣ መልኩን አሳምሮ ጠጉሩን አበጥሮ መስታወት ፊት ሲቆም፣ ሰው ግን ባለበት ሲረግጥ ወዮለት! እያለች ነው ታምቡር የምትመታው!...
ግጥሙ ከሌሎቹ ግጥሞቿም በደረጃ ዝቅ ያለ ነው፤ በውበትም በቋንቋ አጠቃቀም ጭምር፣ ዜማ ለመፍጠር እንኳ ተንገዳግዶ ነው፤ ግድግዳ የሚቧጥጥ ዓይነት ነው፡፡ ክረምትና በጋ እንደጨለማና ብርሃን ይታያሉ፡፡ ክረምቱ ደመና ቆልሎ፣ ሰማይን ጨፍጋጋና አኩራፊ ያደርገዋል፡፡ ያኔ ሰው ደግሞ ጭራሮ ቆልሎ እያነደደ ባንድ በኩል ብርዱን፣ በሌላ በኩል ጨለማውን እያሳደደ ይገርፈዋል፡፡ ያ ክረምት ደግሞ የተፈጥሮ እርግዝና ወቅት ነውና አበቦችን አርግዞ ይቆይና - መስከረም ብቅ ሲል ይወልዳቸዋል፡፡ ከዚያ ሰማይም ፈገግታ ለኩሶ ብቅ ይላል፤ ሰውም የሰማዩን ፈገግታ ሲያጅብ ችቦ ይዞ ይዘምራል፡፡ ሳቅ በሳቅ ነው፡፡ ገጣሚዎቹ እንደሚነግሩን፤ ተፈጥሮ ውበትዋንም ታሳይ ወይም ታሥቀይም ሰው አማካይ ሆኖ ድል መንሳት አለበት፡፡ እንደሰናይት ግጥም ባዶ መሆንም የለበት፡፡ ይልቅስ ሲሳይ ታደስ ሌላ የሚለው ነገር አለ፤ “ሰው ብርሃን ሰው ጨለማ” በሚለው ግጥሙ፡-
ብርሃን በለበሰች
ፅልመት በደረበች
በዚች ሰፊ ዓለም፣
ከራስ ጨለማ እና - ብርሃን በስተቀር
ሌላ ጨለማና - ሌላ ብርሃን የለም!
እና እሳቤውን - ሰው ማብራት ካወቀ፤
በእኩለ ሌሊትም - ብርሃን ባልጠለቀ፡፡
ምሽት ብሎ ነገር - ባልኖረ የቱም ጋ፣
ሰው ውስጡን ካበራ ሰው ልቡን ካነጋ!
ጨለማና ብርሃን ወይም የበጋና ክረምት ተምሳሌት ያለው እኛው ራሳችን ውስጥ ነው ባይ ነው ሲሳይ፡፡ ብርሃን ለብሳ ብርሃን የደረበችው ዓለም፤ በሰው የውስጥ ብርሃን ፈፅሞ የማያቋርጥ የብርሃን ጅረት ሊፈስስባት ይችላል በማለት፣ የሰው ልጅ ለችግሮቹ በተፈጥሮ ላይ ማሳበብ የለበትም ነው የሚለን፡፡
እንግዲህ ገጣሚዎቻችን ከፊሉ በተለይ ዮሐንስ አድማሱ፣ ተፈጥሮ ሸጋዋን በክንድዋ ስር አቅፋ፣ በውበትዋ እያማለለች ህይወት እንዳይሰለቸን የምታደርግ ቅመም ናት ይለናል፡፡ ነቢይ መኮንን ደግሞ ሰው የደመና አሽከር ነው ይላል፤ በተለይ ያገራችን ገበሬ፡፡ ደመና ሰማይ ላይ ተነስንሳ፣ ከሳሎን ወደ ጓዳ መሶብ ይዛ ሽር እንደምትል እመቤት እያስጎመዠች ምራቅ ታስውጠዋለች በማለት ቁጭቱን ፅፏል፡፡ ሰናይት አበራ ደግሞ ተፈጥሮ አንዴ ጸጉሯ ላይ አበባ ሰክታ፣ ሌላ ጊዜ ፊቷ ላይ አመድ ነፍታም ብትወጣ ሰው ካልተነቃነቀ ባዶ ነው የምትል ይመስላል፡፡ ሲሳይ ደግሞ የዓለም ሁሉ ብርሃን የተካተተበት ቋት ሰው ራሱ ነው እያለ ይወቅሳል! እና ማንን እንስማ? … ሁሉንም! … ሁሉም በየራሳቸው ዓይን የየራሳቸውን ቀመሩልን፣ የየራሳቸውን ችቦ አበሩልን!... እኛም በምርቃት አጀብ፡- ብርሃን ያውጣላችሁ እያልን እናጣጥም፤ እናስብ፤ እንሳቅ፤ … እንተክዝም ጭምር!


Published in ጥበብ

ውድ እግዚአብሔር፡-
ወንድሜ ቶሎ ቶሎ ሽንቱን ይሸናል፡፡ እኔ ግን አይመጣብኝም፡፡ ለእኔ ብዙ ያልሰጠኸኝ አልቆብህ ነው?
ናቲ- የ5 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
ኤሊዬ ሞታብኛለች፡፡ ጓሮአችንም ቀብረናታል፡፡ አሁን ካንተ ጋር ናት እንዴ ?
ከሆነች ሰላጣ በጣም ትወዳለች እሺ፡፡
ዴቭ- የ5 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
ትልቅ ስሆን ቅርጫት ኳስ መጫወት እፈልጋለሁ፡፡ በደንብ መጫወት እንድችል ቆዳዬን ጥቁር አድርግልኝ፡፡ ቁመቴንም በጣም አርዝምልኝ፡፡
አሌክስ- የ6 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
ወዳንተ ስፀልይ ደስ ይልሃል አይደል? እኔም ደስ ይለኛል፡፡
ጄሪ- የ7 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
የሰንበት ት/ቤት አስተማሪዬ አንተ ሁልጊዜ እንደምትወደኝ ነግራኛለች፡፡ እውነቷን ነው? ትላንት ሳራ ላይ ያንን ነገር ካደረኩም በኋላ ትወደኛለህ? አውቀኸዋል አይደል?! በጣም አዝናለሁ፤ አሁንም ብትወደኝ ግን ደስ ይለኛል፡፡
ቤቲ - የ7 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
አያቴ ልትሞትብኝ ነው፡፡ አንተ እንደምትፈልጋት ነግራኛለች፤ እኔ ግን እዚህ አብራኝ እንድትሆን እፈልጋለሁ፡፡ሌላ የፈለግኸውን ሰው መውሰድ ትችላለህ፡፡
ለእኔ ያለችኝ እሷ ብቻ ናት፡፡ እባክህን ከህመሟ ድና አብራኝ እንድትሆን አድርጋት፡፡
ጆኒ- የ6 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
ለምንድነው እባብና ሸረሪቶችን የፈጠርከው? በጣም እኮ ነው የምፈራቸው፡፡
ጄሪ- የ6 ዓመት ህፃን

Published in ጥበብ
Page 11 of 15