ሰሞኑን በህገወጥ መንገድ ሳኡዲ አረቢያ ከገቡ ብዙ ሺ ኢትዮጵያውያን ወጣቶች መካከል ዓለም አቀፍ የስደተኞ ተቋም ከ350 በላይ የሚሆኑትን ወደ አገራቸው መልሷቸዋል፡፡ ጋዜጠኛ አበባየሁ ገበያው በተቋሙ መጠለያ ጣቢያ ያገኘቻቸውን ሦስት ተመላሾች አነጋግራለች፡፡
“ሳኡዲ ወርቅ እየዘነበ ነው ቢሉኝ አልሰማም” አብዱ እንድሪስ
“ኢትዮጵያውያን በእስር ቤት እየተሰቃዩ ናቸው” እንድሪስ መሃመድ
“አበሻ ለእነሱ ርካሽ እቃ ማለት ነው” እንድሪስ የሱፍ

አብዱ እንድሪስ እባላለሁ፣ ከኮምቦልቻ ተነስቼ ከጓደኞቼ ጋር ነው የሄድኩት---መንገዳችን ጥሩ ነበር፡፡ የመን ከዛም ሳኡዲ ደረስን። ከስምንተኛ ክፍል ነው የሄድኩት..ቤተሰቦቼ ድሆች ነበሩ --- የእነሱን ችግር እያየሁ መቀመጥ አላስቻለኝም፡፡
ስንት ጊዜ ቆየህ ሳኡዲ?
አስር ወር ቆይቼ ነው የመጣሁት፡፡ አምስቱን ወር በእስር ቤት፣ አራት ወር ጎዳና ተዳዳሪ ሆኜ ስንከራተት---አንድ ወር ብቻ ነው ተቀጥሬ የሰራሁ፡፡
ምን ነበር የምትሰራው?
በግ እጠብቅ ነበር፡፡ ደሞዜ ስምንት መቶ ሪያድ ነበረ፡፡ ደሞዜ እንደነገ ሆኖ እንደዛሬ ፍተሻ ሲያደርጉ አገኙኝና ወሰዱኝ፣ አምልጫቸው ጎዳና ለጎዳና ስንከራተት---መንገድ ለመንገድ ስተኛ-- በመጨረሻ ምግብ እየለመንኩ መኖር ጀመርኩ፡፡ ለማኝ ነበርኩ፡፡
አራት ወር ጎዳና ተዳዳሪ ሆነህ ምግብ የሚሰጥህ ማን ነበር?
በህጋዊ መንገድ የመጡ የእኛ ሴቶች አሉ፣ ሥራ የሚሰሩ፡፡ አልፎ አልፎ ምግብ ደብቀው ይሰጡኛል፡፡ ሴቶችም ወንዶችም ብዙ ጎዳና ተዳዳሪዎች አሉ፣ ብዙ እብዶችም አሉ፡፡ ቆም ብለሽ ዞር ስትይ ኢትዮጵያዊ ለማኝ፣ ጎዳና ተዳዳሪ፣ እብድ---አለ በየመንገዱ፡፡ አንዳንዴ ፖሊሶች ከመንገድ አንስተው ያስራሉ፡፡
አንተም ጎዳና ላይ ተገኝተህ ነው የታሰርከው?
አምስት ወር ሙሉ በእስር ቤት ነበርኩ፡፡ እስርቤቱ እንዴት ነበር ብለሽ እንዳትጠይቂኝ--ማስታወስ አልፈልግም፣ ያመኛል፡፡ ዱላውንና ድብደባውን..ማንጓጠጡንና ማንቋሸሹን…አልነግርሽም፡፡ ግን የሰው ዘር ናቸው? እኔ አላውቅም፡፡ ኢትዮጵያኖች እኮ እስር ቤት ሁሉ ይሞታሉ፡፡ ረሃብማ ተይው፡፡ እንኳን ብቻ ለአገራችን አበቃን፡፡
ቤተሰብህ ያለህበትን ሁኔታ ያውቅ ነበር?
እንደገባሁ ደውዬ ነበር፡፡ ከዛ ግን አስር ወር ሙሉ የት እንዳለሁ --- ልሙት ልዳን የሚያውቁት ነገር የለም፡፡ አሁንም ዝም ብዬ ነው ተሳፍሬ የምሄደው፡፡
በአሁኑ ሰዓት ሳኡዲ ውስጥ ኢትዮጵያኖች እየተንገላቱ ነው ይባላል..
ድብደባ ቢሉሹ ድብደማ መሰለሽ፡፡ ዝግንን በሚል ሁኔታ ነው የሚደበድቡበት፡፡ ዱላ እኮ መፈንከት ብቻ ሳይሆን የደምስርሽ እንዲቋረጥ ያደርጋል፡፡ ሽባ ነው የሚያደርጉት---.በጣም ይጠሉናል፡፡
ከዚህ በኋላ ተመልሰህ አትሄድም?
እንኳንም መጣሁ፡፡ አላህ ለአገሬ ምድር አበቃኝ፡፡ አሁን አገሬ ስገባ የምሰራውን ስራ እኔ ነኝ የማውቀው፡፡ ለእኔ ብቻ ሳሆን ለጓደኞቼም ትምህርት ነው የምሆነው፡፡ ይጠቅመኛል ያለ ይከተለኛል፣ ያለዚያ የራሱ ጉዳይ፡፡
ምን ልትሰራ አሰብክ?
በንግድም ሆነ በሚያዋጣኝ ወጥሬ ነው የምሰራው፡፡ ሳኡዲ አረቢያ ወርቅ እየዘነበ ነው ቢሉኝ -- ከአሁን በኋላ ስሙን እንኳን መስማት አልፈልግም፡፡ የቅጣታቸው አከፋፍ ምን እንደሆነ ታውቂያለሽ… አውራ ጣትና አውራ ጣትን በገመድ ያስሩና ርቆ ከተሰቀለ ባላ ላይ ያቆማሉ፡፡ ከስር የተቆመበትን ወንበር ጎትተው ሲጥሉት ..ስቃዩና ሰቆቃው አይጣል ነው፡፡ ስንቱ የጀርባ ህመምተኛ፣ ስንቱ መሽናት አቅቶት እየተንፏቀቀ እንዳለ ብታይ …አየሽው /ክብዱን እያሳኝ ለምጥ/ ይሄ ለብዙ ጊዜ ያሰቃየኝ ቁስል ነው ደብድበውኝ፡፡ የእኔ ጓደኛ ተደብድቦ ተደብድቦ በሽተኛ ሲሆን ወደ ኢትዮጵያ መለሱት---በተመለሰ በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ሞተ። መቼም ብዙ መከራ አሳለፍን፡፡

=================

ስምህ ማን ነው ?
እንድሪስ መሃመድ፡፡
እድሜህ ?
ሀያ ዓመት ሆኖኛል፡፡
ወደ ሳኡዲ አረቢያ እንዴት ሄድክ ?
ገና የስምንተኛ ክፍል ተማሪ ሆኜ ከጓደኞቼ ጋር መከርን፡፡ ለምን እንደሌሎች ጓደኞቻችን ሳዑዲ አንሄድም አልን፡፡ ሳኡዲ ሄደው ለወላጆቻቸው ባጃጅ ስለገዙ፣ ቆርቆሮ ቤት ስለሰሩ፣ ንግዱን ስለሚያጧጡፉ --- የአካባቢያችን ልጆች ካወራን በኋላ ለመጓዝ ወሰንኩ፡፡ ለደላላ አራት ሺህ ብር ከፍዬ በእግሬ ዘጠኝ ቀን ተጉዤአለሁ - ባህር ድረስ፡፡ በመጨረሻ ሳኡዲ የገባሁትም በእግሬ ነው፡፡
መንገድ ላይ ችግር አልገጠማችሁም ?.
እሱ እንኳን ስቃይ ነበረው፡፡ የመን ድንበር ላይ ተኩሰውብን፣ ግማሾቹ ሲያዙ ግማሾቻችን አመለጥን፡፡
ሳኡዲ ከገባህ በኋላ ሥራ አገኘህ ?
አዎ የፕላስቲክ ማምረቻ ውስጥ ነበር የምሰራው፣ ፕላስቲክ ሰሃን፣ ፕላስቲክ ወንበር --- እነሱን ቅርፅ ማስያዝ ነበር የእኔ ሃላፊነት፡፡
ገንዘብ ለቤተሰብ ትልክ ነበር ?
አዎ---በወር 2ሺ ሪያድ እልክ ነበር፡፡ እሱስ የድካሜን ያህል ኮምቦልቻ ቦታም ገዝቻለሁ፡፡ እድሜ ለሳውዲ---.ያጠራቀምኳትን እየበላሁ ወጥሬ እሰራላሁ፡፡
አሁን እንዴት ነው የመጣኸው ?
ተይዤ ነው የመጣሁት፡፡
በመገናኛ ብዙኃን ብዙ ኢትዮጵያኖች ስቃይ ላይ እንደሆኑ ተዘግቧል ---
ከተማው ሰፊ ስለሆነ እዚህ ለቅሶ እዚያ ጩኸት ነው፡፡ እኔ አልተመታሁም ግን ሰምቻለሁ---በአይኔም አይቻለሁ፡፡ እስር ቤት ደግሞ መከራውና እንግልቱ ከባድ ነው፡፡ ጃዋዛ (ወታደሮች) እየጠረነፉ እስር ቤት ያስገቡ ነበር፡፡ በርካታ ኢትዮጵያውያን በእስር ቤት እየተሰቃዩ ናቸው፡፡
አንተም ታስረህ ነበር ?.
አዎ--- ወር ከሶስት ቀን
ከአሁን በኋላ ተመልሰህ መሄድ ትፈልጋለህ ?
በቃኝ ካላስ፡፡

=============

ስሜ እንድሪስ የሱፍ ይባላል፡፡ ትውልዴ ሃይቅ ነው፡፡ ወደ ሳኡዲ የሄድኩት ትንሽ ለውጥ ፈልጌ ነበር፡፡ በጅቡቲ በኩል ነው የሄድኩት- በባህር፡፡ ጅቡቲን የሚያሳልፈን መሪ ነበረን፡፡ ያውም እኮ የመጨረሻ ልጅ ነኝ፡፡ አባቴም እናቴም እያለቀሱ ነው የሰደዱኝ፡፡ የእነሱ እንባ ነው መሰለኝ አላስቆም አላስቀምጥ ብሎኝ ነበር፡፡
ጉዞው እንዴት ነበር?
ምን ትያለሽ? ድካሙንማ ተይው! ወንድም ሴትም በየመንገዳችን ስንቀብር ነበር፡፡ እየደከማቸው ሲወድቁ እየጣልናቸው ነው የሄድን። ባህር ድረስ ዘጠኝ ቀን ነው የፈጀብን፡፡ ለታመሙት እንኳን ውሃና ምግብ እንዳንሰጥ እልም ያለ በረሃ ነው፡፡ ሁላችንም ደግሞ ስንቃችንን ጨርሰናል፡፡ እኔ በበኩሌ የራሴን ነፍስ ማትረፍና ወርቅ እና ገንዘብ ይታፈስበታል ከተባለው አገር--- ሳኡዲ መድረስ ነበር የማስበው፡፡
ወርቅና ገንዘብ እንደሚታፈስ ማን ነገረህ?
እዛ የሄዱ ጓደኞቼ ሲደውሉሉኝ፣ ገንዘብ ለቤተሰቦቻቸው-- ለወገኖቻቸው ሲልኩ ሳይ እየተጎመጀሁ መጣሁ፡፡ ከዛ የመጣው ይምጣ ብዬ በረሃና ባህር ተሻግሬ ሄድኩ፡፡
ግን በህጋዊ መንገድ መሄዱ አይሻልም ነበር?
አይ አንቺ! በህጋዊ መንገድ የሄዱትስ ብትይ የትኛው ክብር ሲኖራቸው ..በባህር ሄድሽ በአየር ኢትዮጵያዊ እንደሆነ ኢትዮጵያዊ ነው፡፡ እስር ቤት አብረውኝ ሲማቅቁ የነበሩት እንደኛ ያሉት ብቻ መሰለሽ---በፓስፖርት በአየር ሄደውም እኮ ዋጋቸው የኛን ያህል ነው፡፡
ሁለት ሺህ ብር ከፍዬ ጅቡቲ ተሰብስበው ከሚጠብቁ ሌሎች ኢትዮጵያውያን ጋር በመርከብ ተሳፍረን ስንሄድ የነበረውን ድካም፣ የዘጠኝ ሰዓት ጉዞ ውስጥ የነበረውን ሰቆቃ---አልነግርሽም፡፡ ማዕበል ተነስቶ --- ጀልባዋ ልትደፋን ደርሳ --- ብታይ ልትጨርሰን፡፡ የመን ወደብ ስንደርስ መሸዋት ከተባለች ስፍራ በመኪና ተጭነን ተጓዝን፡፡ ግን የየመን ፖሊሶች አግኝተውን ቀጠቀጡን፡፡ ‹‹ጅዳ ወይንም ሌላ አገር ደውላችሁ ገንዘብ ሃዋላ አስደርጉ›› ብለው ደበደቡን፡፡ ደሞ ሴቶችን ሶስት አራት ሆነው ነው የሚደፍሩዋቸው፡፡
ከየመን ወደብ ተነስተህ እንዴት ሳኡዲ ወደብ ደረስክ?
ገንዘብ ያላቸው ከፍለው ነው በመኪና የሄዱት፡፡ እኔ ግን ገንዘብ ከሌላቸው ወጣቶች ጋር ሆኜ በረሃ ለበረሃ አስር ቀን ተጓዝን፡፡ በመሃል የሚሞት አለ፤ ለመቅበር እንኳን አቅም አልነበረንም፣ ጥለነው ነው የምናልፍ። ባለፍንበት መንገድ ክፉኛ ሽታ ያለበት ያጋጥመን ነበር፡፡ ምን መሰለሽ? እንደኛ ሳኡዲ ለመግባት ተሽሎክሉከው መንገድ የሚያሳብሩ ሰዎች ሞተው፤ የሚቀብራቸው አጥተው በየስፍራው ተጥለዋል፡፡ ውይ…አጥንታቸው ብቻ ቀርቶ--.ስናይ እናለቅስ ነበር፡፡ አብረውኝ የነበሩ ጓደኞቼም ሞተው አልቀዋል፡፡
/በረዥሙ ተንፍሶ ለአፍታ ቆዘመ/ አንዱ ከሃገሬ አብሮኝ ተነስቶ ሳኡዲ ድንበር ሲደርስ ሞተ፡፡ አሁን ለቤተሰቦቹ ምን እንደምናገር እንጃ?
እንዴት ወደ ሳኡዲ ገባህ?
እንደምንም ተሽሎኩልኬ ሳኡዲ ገጠር ገባሁና በእረኝነት ስራ ጀመርኩ፡፡
ስንት ይከፍሉህ ነበር ?.
አራት መቶ ሪያድ ተቀጥሬ ነበር፤ ግን የሰራሁት ለሁለት ወር ነው፡፡ እሱንም በኪሴ ይዤ ወደ ጓደኞቼ ስሄድ ሌባ ቀማኝ፡፡ ጓደኞቼ ጋ ስሰራም እንዲሁ ያገኘሁትን ገንዘብ ተነጠቅሁ፡፡ እና የሚመስለኝ አበሻ ለእነሱ ርካሽ እቃ ማለት ነው፡፡ ጢባ ጢቤ የሚሉት፡፡ አንድ ማዳም ‹‹ባሌን ልትቀማኝ ነው፣ ይዛብኛለች›› ብላ ያሰበቻትን ኢትዮጵያዊ ፣ እጅዋን እንደቆረጠቻት አውቃለሁ፡፡ አሰርተው ገንዘባቸውን ይከለክሏቸዋል፡፡ ስንቱ ኢትዮጵያዊ ነው መንገድ ለመንገድ እያደረ የሚኖር--
እስር ቤት ነበርክ ?
አዎ ሁለት ወር እስር ቤት ነበርኩ፡፡ ጠዋት አንድ ቂጣ፣ ማታ አንድ ቂጣ ነበር የሚሰጡን፡፡ ብዙ እስር ቤት አላቸው፣ ብዙ አበሻም እስር ቤቱን አጣቦታል፡፡ ስንናገር ‹‹ዝም በሉ ከብቶች›› ተብለን እንደበደባለን፡፡ ባህሬንና ፓኪስታኖች ሲያወሩ ያዳምጧቸዋል..እኛን ግን ንቀታቸው የትየሌሌ ነው።
አሁን ወደ ትውልድ አገርህ ነው የምትመለሰው?
ደውዬላቸዋለሁ፡፡ ወደ ቤት ነው የምመለሰው።

Published in ህብረተሰብ

              “እንደገና ፊደል እንደገና” የሚያሰኘን እያረፈ የሚነሳው የፊደል ማሻሻል ጥያቄ ጉዳይ ነው። ጥያቄውን የሚያነሱት ምሑራን ምክንያታቸው ምንድነው? በተለይ ጐልቶ የሚነሳው የሞክሼ ፊደላት ጉዳይ ነው፤ እነዚህንስ መነካካቱ ያስፈለጋቸው ለምንድነው የሚለውን በቅድሚያ መመልከቱ ተገቢ ይመስላል፡፡ ከሞክሼዎቹ የተወሰኑትን የማስወገዱ እርምጃ የሚያስከትለውን ጉዳት/ጉድለት ደግሞ ከዚያ በኋላ እንመለከተዋለን፡፡ 
አሁን እስኪ ሞክሼ ፊደላቱን ለማጉደል ምን ምን ዓይነት ምክንያቶች እንደሚሰሙ እያነሳን እንመልከት-
አንድ ድምጽ፣ አንድ ምልክት
ትክክል፡፡ አንድ ምልክት አንድን ድምጽ ወይም ክፍለ ቃል፣ አንድ ክፍለ ቃልም በአንድ ምልክት መወከል አለበት፡፡ ማንም ሊገምት እንደሚችለው፣ እነዚህ ምልክቶችም እያንዳንዳቸው አንድን ድምጽ ለመወከል የተሠሩ ናቸው፡፡ ብዙዎች አንዱን ድምጽ ሊወክሉ አልተሠሩም፡፡ በእርግጥም አልነበሩም፡፡
እንዲህ የሆነው ከጊዜ በኋላ ነው፡፡ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ከአባ ሰላማ ወዲህ ነው ይላሉ፡፡ ግን አይደለም፡፡ ከዚያ ወዲህ፡፡ ቢያንስ በጽሕፈት ላይ ሲቀያየሩ አይታዩም፡፡ ድምፃቸው አንድ ኾነ ተብሎ በጽሕፈትም የአንዱን ለአንዱ ማድረግ ይታይ ነበረ፡፡ ከዚህም ሌላ በአባ ሰላማ ጊዜ ኅርሙኅ ተጨምሯል። እነዚያ አንድ እየኾኑ ይሕን ይጨምራሉ አይባልም። ደሞም የዚህኛውም ድምጽ አንድ ሆኖ ተገኝቷልና በአባ ሰላማ ጊዜ ሲጨመርም አንድ ድምጽ ይዞ ተጨመረ ማለትን ይመስላል፡፡
በሚገባ የታወቀው ይህ የድምጽ አንድነት የታየው፣ በመጽሐፈ ጥበብ እንደተገለፀው፣ ከልብነ ድንግል ዘመን ወዲህ ነው፡፡ የአምስት መቶ ዘመን ዕድሜ አለው ማለት ነው፡፡ በዚሁ መጽሐፍ የየራሳቸው ድምጽም ተመዝግቧል፡፡ ፍሬ ነገሩ ግን ድምፃቸው በግዴለሽነት ተመሳሰለ ብሎ እንዲወገዱ መጠየቅ አለበት ወይ? የሚለው ይሆናል፡፡ ይህ ምልክቶቹን ድምጽን ለመወከል የተሠሩ በማድረግ፣ ሥነ ልሣናዊ ዕቃዎች ብቻ በማድረግ፣ ስንፍናን እና ጉድለትን በጉድለት መተካትና ማረም፤ ከሁሉም በላይ ደግሞ ምልክቶቹ ያላቸውን ሌሎች አገልግሎቶችና ውክልናዎች እንዳሉ መጣል መሆኑን ካለማየት የሚመጣ ጥያቄ ነው፡፡ በአጭሩ፣ የሰነፍ፣ የደካማና የታካች አቋራጭ መንገድ ነው፡፡
የፊደላት ብዛት
የፊደላት ብዛት ጥያቄ የሚነሣው ይበልጡን በአጠቃላይ ፊደሉን ከመነካካት ጥያቄ ጋር ነው። ከሞክሼ ፊደላት አንጻር አይደለም፡፡ ምናልባት “ፊደሉም ብዙ ምልክቶች ያሉት ነውና ሞክሼዎቹ ሲቀነሱ ያነንም ጥያቄ ይመልስልናል” በሚል ግንዛቤ እንደ አንድ ነጥብ ይነሳ ይሆናል፡፡ ከዚህ ውጭ ፊደሎቹ የበዙት አንዱን ድምጽ የሚወክሉ ከአንድ በላይ የሆኑ ፊደላት ስላሉ ነው የሚል የለም፡፡
እዚህ ላይ ግን ጠቅላላ በፊደል ላይ የሚነሱ ጥያቄዎችንም ለመመልከት ያህል አንስተነዋል፡፡
የፊደል ብዛት ጥያቄ በአማርኛም ሆነ በግዕዝ የሚጠየቀው ፊደላቱን ካለመለየት የተነሣ ነው። ፊደላት የገበታ እና የርባታ ተብለው ይለያሉ። የየትኛውም ቋንቋ ፊደል ምን ያህል እንደሆነ ሲጠየቅ የሚነገረውም የገበታው ፊደል ብዛት ነው። የኢትዮጵያው ፊደል በዝቷል ሲባል ግን በቁጥር የሚነገረው የገበታው ከርባታው ሳይለይ ነው፡፡ ለምሣሌ፣ የአማርኛውን ብንወስድ ጠቅላላ ብዛቱ ወደ ሦስት መቶ የሚጠጋ ተደርጐ ይነገራል፡፡ ይህም:-
እያንዳንዱ የገበታ ፊደል በ7 ተባዝቶ - 238
ዲቃሎቹ (4x5) = = 20
ፍንጽቆቹ = 21
ጠቅላላ 279 ይሆናሉ፡፡
እንዲህ በመሆኑ በዝቷል ነው የሚሉት። በዝተዋል ተብለው መቆጠር የነበረባቸው ግን እንዲህ አልነበረም፡፡ ለየትኛውም ባለ ጽሕፈት ቋንቋ የፊደላት ብዛት ሲጠየቅ ይህን ያህል ነው የሚባለው የገበታው ፊደል ብቻ ነው፡፡ እንግሊዝኛ 26 ፊደል አለው፤ ግሪክ 28 አለው፡፡
ዓረብ 29 አለው፤ የሩስያ 33 ፊደል የሚባለው የገበታ ፊደሉ ብቻ ተቆጥሮ ነው፡፡ የርባታ ፊደሎቻቸውን/ምልክቶቻቸውን/ እንደ አንድ እየቆጠርን እንጠቁም ቢባል፣ እንደ እንግሊዝኛ ያለው ለአማርኛ ከተቆጠረውም በእጥፍና ከዚያ በላይ የሆነ ብዛት ይኖረዋል፡፡
በኢትዮጵያ ያለው የርባታ ሥርዓት በነ ዳንኤልስ “አቡጊዳ” የተባለው ዓይነት ሆኖ፣ በመሠረታዊው ፊደል ላይ የተለያዩ ጭማሪዎች በማድረግ አንድ ምልክት እየተደረገ የሚሠራ በመኾኑ እነዚያንም ደርቦ በመቁጠር ቁጥሩን ማብዛቱ ተገቢ አይደለም። መሠረታዊዎቹ ስንት ናቸው ብሎ ነው መቁጠር፡፡ በዚህ መሠረት ለግዕዝ 26 ፊደላት፣ ለአማርኛ ደግሞ 34 ፊደላት ብቻ ይኖሯቸዋል፡፡
እንደዚያም ቢኾን የሞክሼ ፊደላቱ ቢቀነሱ ያን ያህል ወደ 300 የተጠጉ ናቸው ካሏቸው ውስጥ ምን ያህሉን ነው የሚቀንሱላቸው?... በአጠቃላይ፣ ከሞክሼ ፊደላቱም አኳያም ሆነ ከሌላ፣ የፊደል ብዛት ጥያቄው ተገቢ ጥያቄ አይኾንም፡፡ ፊደላቱም ብዙ አይደሉም፡፡
የቴክኖሎጂ ውጤት ለኾኑ መጻፊያዎች ቸገረ፡-
ይህ ጥያቄ አስቀድሞ “ታይፕ ራይተር” በነበረበት ወቅት፣ በተለይ መጀመሪያ ላይ እንደ አንድ ችግር ተነስቶ ነበር፡፡ በዚህ ፊደሉን የመነካካት፣ እንዲያውም የመለወጥ ጥያቄ እስከ ማንሳት ድረስ ያሳሰቡት፣ በአስፋው ዳምጤ “ጐምቱ አብዮተኞች” ተብለው የተጠሩ እነ መርስዔ ኀዘን ወልደ ቂርቆስ አንስተውት ነበር፡፡ ይህንን መነሻ አድርጐ የፊደል ነካኪዎችን ታሪክ የጠቃቀሰ የዶ/ር መርሻ አለኸኝ ጥናታዊ ወረቀት፣ ታይፕ ራይተሩ ራሱ ለፊደል እንዲመች ኾነና ፊደሉ ከመቀየር እንደተረፈ ጠቁሟል፡፡ አሁን ደግሞ እንደ አዲስ ለኮምፒውተሩ እንዲመች የሚል ሐሳብ ነው የሚነሳው፡፡ ለኮምፒውተሩ ያልተመቹ ፊደላት ሳይኖሩ ይህን ጥያቄ ለምን እንደሚያነሱት ለማንም አይገባም፡፡ ደግሞም የፊደላቱ ድምፅ አንድ መኾን በቴክኖሎጂው ላይ የሚያመጣው የተለየ ችግር ምን ሊኾን እንደሚችልም አይገባንም። በማንኛውም ቢኾን ስለቴክኖሎጂ ተብሎ ያለው ነገር ይቀነስ ማለት ደግሞ በጭራሽ ተገቢነት አይኖረውም፡፡ ቴክኖሎጂው ለእነዚያ ተብሎ ይሠራል እንጂ፣ እነዚያ ለቴክኖሎጂው አይሠሩም። ለእንግሊዝኛው ወይም ለላቴኑ ፊደላት እንዲኾኑ ተበጁ እንጂ ለቴክኖሎጂው ሲባል እንግሊዝኛው፣ ላቲኑ - ሌላውም በጭራሽ አልተነካም፡፡ ቴክኖሎጂ ያለውን በሚመጥንና በሚያካትት መጠን ይሠራል እንጂ ያለው ነገር ለቴክኖሎጂው ሲባል መሠረቱን እንዲለቅ አይደረግም፡፡ ስለዚህ ጥያቄውን የማይረባና ተገቢ ያልኾነ አድርገን እንጥለዋለን፡፡
የሥነ ጽሑፍ ዕድገት ጥያቄ፡-
“የእናቴ መቀነት አደናቀፈኝ” የማለትም ያህል ይሆናል፡፡ ከፊደላቱ የተወሰኑትን አጉድሎ የየትኛውም ቋንቋ ሥነ ጽሑፍ አልተመነደገም። በሞክሼ ፊደላት ሰበብ ይህ የስነ ጽሑፍ ዕድገት ይጠቀስ እንደኾነ አፍን ሞልቶ መናገር ባይቻልም፣ ከ2005 ዓ.ም ጀምሮ፣ ዘንድሮም የነዚህን የሞክሼ ፊደላትን ነገር የሚያነሳሱት ዶክተር በድሉ ዋቅጅራ፣ በአንድ የመጽሔት ጽሑፋቸው ላይ ፊደላቱ ከገበታው መገኘታቸውን በማማረር፣ “የድሮን ነገር ለመጠበቅ ወግ ሲባል የዛሬው ዘመኑ እንዲጋረድብን /እንዲጨልምብን” መደረግ እንደሌለበት በሚከብድ ኃይለ ቃል የጻፉትን በማሰብ፣ የእነዚህ ፊደላት መኖር እንዲያ ያለ ጽልመት ውስጥ እንደሚጨምረን የታሰበው ምናልባት ከዚህ የሥነ ጽሑፍ ዕድገት ጋር ታስቦ ይኾን እላለሁ፡፡
ይህ የስነ ጽሑፍ ዕድገት ጥያቄ በኢትዮጵያ ቋንቋዎች ጥናት ተቋም አስቀድሞ እንደ አንድ ነጥብ ሲጠቀስ እናስታውሳለን፡፡ ለሞክሼዎቹ ብቻ ሳይሆን በአጠቃላይ በፊደላቱ ላይ ለሚወሰድ እርምጃ የተጠቀሰ ነበር፡፡
የስነ ጽሑፍ ዕድገት ጥያቄ ፊደልን በማጉደልና በመለወጥ ረገድ ከሚነሣ ይልቅ እንዳሉ ቢቀመጡ ከሚናገረው ወገን ቢጠቀስ የበለጠ በተመቸ ነበር። ፊደልን በመነካካት (በመቀየር፣ በማጉደል …) ስነ ጽሑፍ እንዴትም ኾኖ እንደማይበለጽግ ሲታሰብ፣ ጥያቄው ጩኸትን የመቀማት ያህል ኾኖ ይታሰባል። ይልቅስ ዛሬ ድምፃቸው አንድ ኾነ ተብሎ እንዳሻ በመጻፍ የሚታየውን ጉድለት ለማስቀረት፣ የነዚያን አገባብ ለይቶ ዐውቆ፣ ማሳወቅና መጠቀም እንጂ፣ የነዚህ መኖርስ ስነ ጽሑፍን ሊበድለው አይችልም።
ለማጠቃለል፣ በሞክሼ ፊደላቱ ላይ የሚነሳው ጥያቄ ያሉት ሰበቦች እነዚህን የመሰሉ ሲኾኑ፣ አንዳቸውም ግን ሚዛንን ሊያነሱ ቀርቶ እንደ ምክንያት እንኳ ሊቆጠሩ አቅም ያላቸው አይደሉም። ይልቅስ በተቃራኒው፣ “ማሻሻል” በምትል መልካም ቃል የሚታሰበው የመቀየር፣ የማጉደልና ሌላም እርምጃ ቢፈጸም የሚደርሰው ጥፋትና ጉድለት ብሶ እንደሚገኝ ማስተዋል ይገባል፡፡

Published in ህብረተሰብ

               ዘንድሮ ብቻ ወደ ሳዑዲ አረቢያ የሄዱ ኢትዮጵያውያን ብዛት ከ160ሺ በላይ ናቸው፡፡ የሳኡዲ አረቢያ መንግስት በአገሪቱ ያሉ ህገወጥ ስደተኞች ህጋዊ የመኖሪያ ፍቃድ እንዲያወጡ ያስቀመጠው ቀነ ገደብ የሰባት ወራት እድሜ ነበረው፡፡ ቀነ ገደቡ ባለፈው ሳምንት እሁድ መጠናቀቁን ተከትሎ በኋላ የአገሪቱ ፀጥታ ሃይሎች ኢትዮጵያውያንን ጨምሮ ህገወጥ ያሏቸውን የተለያዩ አገራት ዜጐችን በማሳደድ በማቆያ ካምፕ ውስጥ እየሰበሰቧቸው ይገኛል፡፡ 
ይሄንን ሰዶ ማሳደድ በመቃወም በሳኡዲ የተለያዩ ከተሞች በተደረጉ የተቃውሞ ሰልፎች እስከ ትናንት በስቲያ ድረስ አራት ኢትዮጵያውያን ተገድለዋል፡፡ ከዋና ከተማዋ ሪያድ በስተደቡብ በምትገኘውና በርካታ ስደተኞች በሚኖሩባት ማኑፋሃ በተለይ ኢትዮጵያውያን አመፅ የተቀላቀለበት ከፍተኛ ተቃውሞ እንዳደረጉ ዘገባዎች ይጠቁማሉ፡፡ ስደተኞች ለተቃውሞ ሰልፍ ገጀራና የተለያዩ መሳሪያዎችን ይዘው የወጡ ሲሆን በመቶዎች የሚቆጠሩ ተሽከርካሪዎችንም አጋይተዋል፡፡ ይሄን ተከትሎም የፀጥታ ኃይሎች እርምጃ መባባሱን ለማወቅ ተችሏል፡፡
በተለያዩ ቦታዎች ከተደረጉ የተቃውሞ ሰልፎች ጋር በተያያዘ 60 ያህል የሳዑዲ ዜጎች ላይ ጉዳት የደረሰ ሲሆን ከ100 በላይ ስደተኞች ቆስለዋል ተብሏል፡፡
እስካሁን 23ሺ ያህል ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ለአገሪቱ መንግሥት እጃቸውን የሰጡ ሲሆን 10ሺህ የሚደርሱ ህገወጥ ስደተኞች ከፀጥታ ኃይሎች አደን ለመሰወር ሲሉ ስራቸውን አቁመው በተለያዩ ስፍራዎች እንደተሸሸጉ ተነግሯል፡፡
የሳኡዲ ፖሊስ፤ ህገወጥ ስደተኞች ይበዙባቸዋል የተባሉ የሸቀጣሸቀጥ ሱቆች፣ የግንባታ ሳይቶች፣ ምግብ ቤቶች እና የንግድ ማዕከሎችን በመክበብ አሰሳውን አጠናክሮ የቀጠለ ሲሆን፤ በቅርቡ ደግሞ የቤት ለቤት አሰሳ እንደሚጀምር ታውቋል፡፡ የሳዑዲ ዜጎች በ99 የስልክ ቁጥር በመደወል ህገወጥ ስደተኞችን እንዲጠቁሙም ጥሪ ቀርቧል፡፡
ባለፉት ሰባት ወራት በሳዑዲ የነበሩ ከ1 ሚሊዮን በላይ የተለያዩ አገራት ህገወይ ስደተኞች ወደየአገራቸው የተላኩ ሲሆን ዳግም ወደ ሳዑዲ እንዳይመለሱም እገዳ ተጥሎባቸዋል፡፡ ከ4 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ ስደተኞች ደግሞ የሳዑዲ መንግስት የሚሰጠውን የመኖርያ ፈቃድ በማውጣት፤ ህጋዊ የስራ ፈቃድ እና ውል ይዘው ኑሯቸውን ቀጥለዋል፡፡
የማሳደድ ዘመቻው ለምን?
ሳዑዲ አረቢያ ከ28 ሚሊዮን በላይ ህዝብ ያላት ሲሆን 9 ሚሊዮን የሚሆኑት የተለያዩ አገራት ስደተኞች ናቸው፡፡ ከእነዚህ መካከልም ከ3.5 ሚሊዮን በላይ ያህሉ ህገወጥ እንደሆኑ ይገመታል፡፡
ህገወጥ ስደተኞችን ከአገር የማባረሩ እርምጃ የተጠነሰሰው የስደተኞች ቁጥር መጨመር የሳኡዲ ዜጐችን ለስራ አጥነት ዳርጓል፣ የሥራ ተነሳሽነትንም አዳክሟል በሚል ቢሆንም ሳዑዲ ከራሷ ዜጐች ውጭ 1 ሚሊዮን ተጨማሪ የሰው ሃይል እንደሚያስፈልጋት መረጃዎች ይጠቁማሉ።
በህገወጥ ስደተኞች ላይ የሚደረገው ዘመቻ እንዲጠናከር የሚፈልጉት የሳኡዲ ህግ አውጭ አካላት፤ ስደተኞችን ከማሳደድ ባሻገርም በህገወጥ የሰዎች አዘዋዋሪ የሳዑዲ ዜጎች ላይም ጥብቅ እርምጃ እንዲወሰድ እየመከሩ ነው ተብሏል፡፡
ከሳዑዲ የወጡ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት፤ አብዛኞቹ ህገወጥ ስደተኞች በዝሙት እና በመጠጥ ንግድ፣ በዝርፊያ እና ሌሎች የወንጀል ተግባራት ላይ የተሰማሩ ሲሆን ይሄም ሳዑዲን ለከፍተኛ ማህበራዊ ቀውስ እንዲሁም ለባህልና ሃይማኖት ብረዛ ሊዳርጋት ይችላል የሚል ስጋት በንጉሳውያን ቤተሰቡና በመንግሥት ዘንድ እንደተፈጠረ ታውቋል፡፡
ሳዑዲን ጨምሮ በመካከለኛው ምስራቅ አገራት፣ በስደተኛ ሰራተኞች ላይ የሚደርሰው በደልና ስቃይ ከየትኛውም የዓለም ክፍል የከፋ እንደሆነ ይነገራል፡፡ ስደተኞች ላይ ፆታዊ ጥቃቶች እና ከፍተኛ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ይፈፀሙባቸዋል፡፡ ለስራቸው ተገቢውን ክፍያ እንደማያገኙና በቀን መስራት ከሚገባቸው ሰዓት እጥፍ እንደሚሰሩም ይታወቃል፡፡ በሳምንት ከ108 ሰዓታት በላይ የሚሰሩ ስደተኞች እንዳሉ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ከሃይማኖት ጋር በተያያዘም ለከፍተኛ እንግልት የሚዳረጉ ጥቂት አይደሉም ይባላል፡፡
ተቀማጭነቱን በአውስትራሊያ ያደረገው “ዎክ ፍሪ ፋውንዴሽን” የተባለ ተቋም ዘንድሮ ለመጀመርያ ጊዜ “ዘመናዊ ባርነት” በሚል በ162 የዓለም አገራት ላይ ባካሄደው ጥናት፣ ከ38 ቢሊዮን በላይ ህዝቦች ለህገ ወጥ ዝውውር፣ ለአስገዳጅ ስራዎችና፣ ለጉልበት ብዝበዛ መጋለጣቸውን ይፋ አድርጓል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ በመቶ ሺዎች የሚገመቱት በመካከለኛው ምስራቅ በከፋ ባርነት ውስጥ የሚገኙ ናቸው ብሏል - ተቋሙ፡፡
መሳደዱ ኢትዮጵያውያን ላይ በዝቷል
የሰዶ ማሳደድ ዘመቻው ፈተና ከእስያውያን ይልቅ በአፍሪካውያን ስደተኞች ላይ የበዛ ሆኗል። በተለይ ደግሞ ኢትዮጵያውያን አበሳቸውን እየበሉ ነው፡፡ የሩቅ ምስራቅ አገራት፡- ፊሊፒንስ፤ ስሪላንካና ኢንዶኔዥያ ዜጎችም መሰቃየታቸው አልቀረም - እንደ ኢትዮጵያውያኑ ባይሆንም፡፡ መሳደዱ በአፍሪካውያን ላይ ያየለው አብዛኞቹ በህገወጥ መንገድ ሳዑዲ የገቡ በመሆናቸው እንደሆነም ታውቋል፡፡
ኢትዮጵያውያን ስደተኞች በ13 የተለያዩ የመካከለኛው ምስራቅ አገራት ተበትነው የሚገኙ ሲሆን፤ በሳዑዲ፣ ኩዌት፣ ባህሬን፣ ዩናይትድ አረብ ኢምሬትስ፣ ኳታርና የመን የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ከግማሽ ሚሊዮን በላይ ይሆናሉ። ወደ መካከለኛው ምስራቅ ለስራ ከሚሰደዱ ኢትዮጵያውያን ውስጥ 40 በመቶ ያህሉ ህገወጥ ሲሆኑ በየዓመቱ ከ6ሺ በላይ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች በህገወጥነት ተጠርዘው ወደ አገራቸው እንደሚላኩ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡

ሳዑዲዎችም ተቸግረዋል
በአገሪቱ በሚኖሩ ህገወጥ ስደተኞች ላይ በተከፈተው የማደንና የማሳደድ ዘመቻ፣ የሳዑዲ ዜጐች ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎችም ተስተጓጉለዋል፡፡ ሱቆችና ምግብ ቤቶች እንዲሁም መዝናኛዎች በሠራተኞች እጦት እንደተቸገሩና የተዘጉም እንዳሉ ታውቋል። ትልልቅ የገበያ ማዕከላት ተዘግተዋል፤ በርካታ የግንባታ ስራዎችም እየተጓተቱ ነው፡፡ “አረቢያን ኒውስ” የተባለ ጋዜጣ እንደዘገበው፤ የሰዶ ማሳደድ ዘመቻው ሳምንት እንኳን ሳይሞላው በየቅጥር ግቢያቸው ያለልክ በተከመረ ቆሻሻ የተማረሩ ብዙ ሺ ትምህርት ቤቶች ቅሬታቸውን እያሰሙ ነው፡፡
በሳዑዲ ሴቶች መኪና ማሽከርከር አይፈቀድላቸውም፡፡ በሾፌርነት ተቀጥረው ሲሰሩ የቆዩ ስደተኞች ከሳዑዲ መባረራቸውን ተከትሎ፣ በርካታ የቤተሰብ አባላት ወደ ስራ ከመሄድ የተስተጓጐሉ ሲሆን ልጆቻቸውን ወደ ተማሪ ቤት መላክና ገበያ መውጣት እንዳልቻሉም ታውቋል፡፡ በሳኡዲ ከግማሽ ሚ. በላይ የሚሆኑ ስደተኞች በሾፌርነት ተቀጥረው ይሰሩ እንደነበር መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡

Published in ህብረተሰብ

የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) በቅርቡ
ከአንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ፓርቲ ጋር ውህደት፣ ከሌሎች 10 ፓርቲዎች ጋር ቅንጅት ለመፍጠር እየተንቀሳቀሰ ሲሆን ፓርቲው ከረጅም አመታት በኋላ
የፕሬዚዳንት ለውጥም አድርጓል፡፡
ከአዲሱ ፕሬዚዳንት አቶ አበባው መሃሪ ጋር ፓርቲው ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር እየፈጠረ ስላለው ውህደት እና ቅንጅት እንዲሁም በሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ፤ በፓርቲው ጽ/ቤት ተገኝቶ አነጋግሯቸዋል፡፡

ከ“መድረክ” ጋር ያለው ጥያቄ “አንድነት” ሊፈታው የሚገባው ነው
ፓርቲያችን ግራ የተጋባ አይደለም
መኢአድ በሀገሪቱ ካሉ ፓርቲዎች ጠንካራው ነው
ህዝቡ እውነተኛውንና ውሸታሙን መለየት አለበት

ከ“አንድነት” ፓርቲ ጋር ውህደት ለመፈፀም የጀመራችሁት ውይይት ምን ላይ ደረሰ? ውህደቱንስ በዚህን ወቅት መፈፀሙ ለምን አስፈለገ?
ህዝባችንን ካለበት ችግርና የሰብአዊ መብት ጥሰት ነፃ ለማውጣት የጋራ አላማ ያላቸው ተቃዋሚ ፓርቲዎች በአንድ ላይ መስራት ወሣኝነት አለው ብለን እናምናለን፡፡ ተለያይቶ ድምጽ ከመሻማት ይልቅ አንድ ላይ ሆኖ ሃብትንም ሆነ ሌላ ሌላውን አቀናጅቶ መንቀሳቀስ ጠቃሚ ነው፡፡ በህዝቡም ላይ በራስ መተማመንን ፈጥሮ ሃይል ያለው “ሊመራኝ የሚችል ፓርቲ አለኝ” ብሎ እንዲያምን አንድ መሆን ወሳኝ ነው ብለን እናምናለን፡፡ እኔ አሁን ባለው ደረጃ ማለት የምችለው፣ አንድነትና መኢአድ ለመዋሃድ ድርድር እያደረጉ ነው፡፡ ከዚህ ባለፈ ግን መግለጫ ለመስጠት ያስቸግረኛል፡፡ ምክንያቱም ሂደቱ በራሱ ኮሚቴ የሚመራ ነው፡፡ ኮሚቴው ማንም ሰው በጉዳዩ ዙሪያ መግለጫ መስጠት አይችልም የሚል ፕሮቶኮል ፈርሟል፡፡ የየፓርቲዎቹ ባለስልጣናትም ሆኑ ተደራዳሪዎች መግለጫ መስጠት አይችሉም፡፡
ከአንድነት ጋር ውይይት ጀምረናል ብላችኋል፣ አንድነት ደግሞ የመድረክ ግንባር አባል ነው፣ እናንተ ደግሞ መድረክን እንደማትፈልጉት በተደጋጋሚ ገልፃችኋል፡፡ ይሄ እንዴት ሊሆን ይችላል?
መኢአድ በኢትዮጵያ አንድነት ጥላ ስር ለመሄድ ከማይፈልጉ ፓርቲዎች ጋር በጋራ ለመንቀሳቀስ ይቸገራል፡፡ የመኢአድ አወቃቀሩም ሆነ አላማው ሁሉም ኢትዮጵያውያን በኢትዮጵያ ጥላ ስር መንቀሳቀስ አለባቸው የሚል ነው፡፡ በጐሣም ተደራጅተው በኢትዮጵያ ጥላ ስር ሆነን “አንዲት ሉአላዊት ኢትዮጵያ” በሚለው ስር አብረን እንሄዳለን ካሉ አብሮ ለመስራት ችግር የለውም፡፡
ስለዚህ አንድነት በመድረክ ስር ሆኖ እንዴት ይሆናል የሚለው የራሱ የአንድነት ጉዳይ ነው፤ የመኢአድ ጉዳይ አይደለም፡፡ መኢአድ እና አንድነት እየተደራደሩ ነው፤ ሁለቱም ተመሳሳይ ፕሮግራም፣ አላማ፣ ደንብ ያላቸው ፓርቲዎች ናቸው፡፡ ነገር ግን ከመድረክ ጋር ያለውን ጥያቄ አንድነት ሊፈታው የሚገባው ጥያቄ ነው እንጂ የመኢአድ አይደለም፡፡ ይሄ የድርድሩም አካል ነው፡፡
ውህደቱን ስትፈጽሙ አመራሩስ እንዴት ነው የሚደራጀው?
እንግዲህ እንደነገርኩህ በዚህ ላይ መግለጫ ለመስጠት ያስቸግረኛል፡፡ ተደራዳሪዎች ስላሉ ይሄ ነው ብሎ ለማለት ፕሮቶኮሉ ያስረኛል፤ ነገር ግን ውህደት ከተካሄደ ውህደት የሚፈልጋቸው ነገሮች ሁሉ ይፈፀማሉ ማለት ነው፡፡ ለዚህ ካለአመራሩ ይሄ ይሆናል ማለት አልችልም፡፡
መኢአድ ከሌሎች ፓርቲዎች የሚለየው በምንድነው?
ፓርቲያችን ተመሳሳይ ደንብ እና አላማ ካላቸው ፓርቲዎች የሚለይበት አንደኛ፣ ህብረ ብሔራዊ መሆኑ ነው፡፡ የመኢአድ እምነት ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በኢትዮጵያ፣ ጥላ ስር ሆኖ የእያንዳንዱ ዜጋ መብት ሲከበር፣ የሁሉም ዜጋ መብት ይከበራል ብሎ ያምናል እንጂ የአንድ ጐሣ መብት ሲከበር የጐሣው አባላት መብት ይከበራል ብሎ አያምንም። አሁን ለምሣሌ ገዢው ፓርቲ ውስጥ ያለው የብአዴን መብት ሲከበር፣ የእያንዳንዱ አማራ መብት ተከበረ ማለት አይደለም፡፡ የኦህዴድም በተመሳሳይ፤ ሌላው መኢአድ የሚመራው በሊበራል ዲሞክራሲ አስተሳሰብ ነው፤ ይሄ ከሌላው የሚለየን ይመስለኛል። ሌላው የምንለይበት ፓርቲያችን ግዙፍ የሆነ አደረጃጀት ያለው ነው፡፡ በመላው ሃገሪቱ በሚገኘው እያንዳንዱ ቀበሌ መኢአድ አለ፡፡
በአራቱም ማዕዘናት ቢኬድ መኢአድ የሌለበት ቀበሌ የለም፡፡ እንዲሁም ፓርቲው የእያንዳንዱ ብሔር ጥንቅር ውጤት ነው፡፡
ምናልባት የብሔር ተዋጽኦው ሲነሣ እርስዎ ከሚሉት በተቃራኒ የአማራው ሚና የሚጐላበት እንዲያም ሲል አመራሩ እና ማዕከላዊ ኮሚቴው ለሰሜን ሸዋ አካባቢ ተወላጆች ብቻ የተሰጠ ነው የሚል ወቀሳ ይቀርብበታል…
እዚህ ላይ አሁን የመኢአድን አመራር ጥንቅር ያየህ እንደሆነ ከአማራው፣ ከጐፋው፣ ከወላይታው ያለበት ነው፡፡ ለምሣሌ የፓርቲውን ምክትል ተቀዳሚ ሊቀመንበር ብንወስድ ከጐፋ ነው፣ የመኢአድን የስራ አስፈፃሚ ብትወስድ ኦሮሞች አሉ፤ ለምሣሌ ብሩ ደሲሣ ከአሶሳ አለ፣ ገለቱ ኤጀርሣም አለ፡፡ ስለዚህ ይሄ የጠላት ወሬ ነው። መኢአድን ለማዳከም የሚነዛ አሉባልታ ነው። አማራው ከሌላው ብሔር የበለጠ በዚህ ፓርቲ ውስጥ ተሳትፎ የለውም፡፡ ለምሣሌ የአባላት ጥንቅርን የወሰድን እንደሆን በሰሜን ካለው አባል የበለጠ በደቡብ ነው ያለው፡፡ ከ39 በመቶ በላይ በደቡብ አካባቢ ያሉ ናቸው፡፡ ከሰሜን ሸዋ የመጡ ናቸው የሚባለው የሰሜን ሸዋ ህዝብ ወይም በዚያ የሚገኝ የአማራ ተወላጅ እንዳጋጣሚ ሆኖ አማራው ይገደል በነበረ ጊዜ ፕ/ር አስራት ፓርቲውን ይመሩ ነበር፡፡ ይህ ማለት ግን አመራሩ በጠቅላላ ከሰሜን ሸዋ ነበረ ለማለት አይቻልም። እሣቸው እንደ ፕሬዚዳንት ከሰሜን ሸዋ ይሁኑ እንጂ ከተለያዩ የአማራ ክፍሎች የተውጣጣ የስራ አስፈፃሚ መዋቅር ነበር፡፡ ፕ/ር አስራት፤ የመላው አማራ ህዝብ ድርጅትን ሲያቋቁሙ የአማራው ወይም የአንድ ብሔር ፓርቲ አድርገው ለማቋቋም አልነበረም ፍላጐታቸው፤ ነገር ግን ይገደልና ይሰደድ የነበረውን አማራ ከጥቃቱ ለመከላከል ያህል ያቋቋሙት ነው፡፡ በወቅቱ ለጊዜው አማራው ላይ የሚደርሰውን ጥቃት እንከላከልና ኋላ ላይ ህብረ ብሔራዊ ሆኖ ሁሉንም ብሔሮች አሣትፎ ይቀጥል የሚል መርህ ነበራቸው፡፡ በዚህ መርህ አሁን ካለበት ደረጃ ደርሷል፡፡ አማራው በዚህ ውስጥ በምንም ሁኔታ የበላይነት የለውም፤ ይሄ የጠላት ወሬ ነው፡፡
ከዚህ ቀደም ከመድረክ ጋር አብረን አንሰራም ብላችሁ ነበር፡፡ አሁን ደግሞ 10 ፓርቲዎች ያሉበት ቅንጅት በመኢአድ ጉልህ ሚና እየተፈጠረ ነው ያለው፡፡ ከዚህ ፓርቲዎች አብዛኞቹ የጐሳ ፓርቲዎች ናቸው፡፡ ከመድረክ ጋር አብሮ አያስጉዘንም ያላችሁበት አጀንዳን ወደ ጐን ትታችሁ አሁን እንዴት ከነዚህ ፓርቲዎች ጋር ለመቀናጀት መረጣችሁ?
ትክክል ነው እነዚህ ድርጅቶች የጐሳ ናቸው። ኢህአዴግ ኢትዮጵያን በጐሳ ሲሸነሽን እነዚህ ፓርቲዎች በጐሳቸው… ተደራጅተው ነው፤ ነገር ግን በአሁኑ ጊዜ ፓርቲዎቹ የጐሣ ቢሆኑም በኢትዮጵያ ጥላ ስር ሆነን እንታገላለን ያሉ ናቸው። ስለዚህ ፓርቲዎቹ በኢትዮጵያዊነት ጥላ ስር መሆንን የሚሹ ናቸው፡፡ የጐሣ/ብሔር/ ፖለቲካ እንደማያዋጣ አምናለሁ፤ በኢትዮጵያ ጥላ ስር ሆነን ከመኢአድ ጋር እንታገላለን ስላሉ ነው የተቀበልነው፡፡ እንግዲህ የነበሩት 33 ፓርቲዎች ናቸው፡፡ ከ33ቱ አብዛኞቹ በጐሣችን ብቻ ነው የምንታገለው ስላሉ አማራጫቸውን ይዘው ሄደዋል፡፡ በኢትዮጵያዊነት ጥላ ስር ሆነን እንታገላለን ያሉት መኢአድ እንዲያታግላቸው ወደዚህ መጥተዋል፡፡ እዚህ ላይ ግልጽ መሆን ያለበት ከመጡት ውስጥ 70 በመቶ የሚሆኑት የብሔር /ጐሣ/ ድርጅቶች ሲሆኑ ቀሪዎቹ ህብረ ብሔራዊ ናቸው፡፡
ከመድረክ ስብስብ ጋር ያላችሁ መሠረታዊ ቅራኔ ምንድን ነው? ከስብስቡ ውስጥ በኢትዮጵያዊነት አያምኑም ብላችሁ የምትጠቅሷቸው ፓርቲዎች አሉ እንዴ?
በኢትዮጵያዊነት ጥላ ስር ካለማመን ባሻገርም በአንዳንድ ፖሊሲያችንም እኮ እንለያያለን፡፡ ለምሣሌ በመሬት ጉዳይ፤ መኢአድ መሬት የህዝብ ነው፤ መንግስት ሊያዝበት አይችልም ብሎ ነው የሚያምነው፡፡ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ጥሪት ሊኖረው ይገባል ብሎ ያምናል፡፡ ዜጐች መሬት ተከራይተው ሊኖሩ አይገባም፤ ይሄ የመኢአድ ፖሊሲ ነው፡፡ ነገር ግን የሌሎቹ የመድረክ አባላት ፕሮግራም በዚህ አያምንም፤ የኢህአዴግን ነው ይዘው የሚሄዱት፤ በነገራችን ላይ አንዳንዶቹ ኢህአዴግ ዲሞክራሲያዊ ስላልሆነ ነው እንጂ በፖሊሲ ደረጃ አንለይም ባይ ናቸው፡፡
መድረክ ውስጥ እንደዚያ የሚሉ ድርጅቶች አሉ?
አዎ! በሚገባ
የአስሩን ፓርቲዎች ፖሊሲና ፕሮግራም ካስቀመጡልን ነጥቦች አንፃር በሚገባ መርምራችኋል ማለት ነው?
መቶ በመቶ በሚገባ አጥርተን መርምረናል፣ ፕሮግራማቸውን አንብበን እና ተናበን ነው ይሄን ያደረግነው፡፡
በ1997 ስለተፈጠረው ቅንጅት አመሰራረትና ውድቀት ብዙ ተብሏል፡፡ የአሁኑን ቅንጅት ከፈረሰው ቅንጅት ምንድን ነው የሚለየው?
ቅንጅት ስንል ያው ቅንጅት ነው፡፡ አይለያይም። እያንዳንዱ ፓርቲ የራሱን ህልውና ጠብቆ ነገር ግን የሚመጣው ችግርና አደጋ በአንድ ላይ እንታገላለን ብሎ የሚያምን ነው፡፡ ስለዚህ አንድ ላይ ተጨፍልቆ አንድ እንደመሆን አይታሰብም፡፡ በ1997ም እያንዳንዱ ፓርቲ በዚህ አይነት ሁኔታ ራሱን የቻለ ነበር፡፡
ግን በአንድ ፕሮግራምና በአንድ የመወዳደሪያ ምልክት ነበር ለምርጫው የቀረበው…
ይሄም ልዩነት አይኖረውም፤ እንደዚያው ነው። ነገር ግን የአሁኑ በየክልሉ ያሉት ፓርቲዎች ቢሮ ካላቸው እንደ ግንኙነት መድረክነት ያገለግላል፤ በየክልሉ በቀላሉ ተደራሽ መሆን ይቻላል፡፡ ከዚያ በተረፈ ከ97 ዓ.ም ቅንጅት ልዩነት የለውም፡፡
ወደ አንድነት ድርድሩ እንመለስና የ97 ቅንጅት ሲፈርስ መኢአድ ህልውናውን ጠብቆ ሲጓዝ “አንድነት” ደግሞ የመኢአድ አባላት የነበሩትን ጨምሮ በቅንጅቱ መፍረስ ቁጭት ባደረባቸው ፖለቲከኞች የተቋቋመ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ያን ጊዜ በአንድነት መጓዝ ያልቻላችሁ አካላት ዛሬ ምን ታይቷችሁ ነው አንድ ካልሆንን እያላችሁ ያለው?
መቼም አንድ ላይ ስትሠራ ትጋጫለህ ትኮራረፋለህ፣ የሃሣብ ልዩነት ይፈጠራል። እያንዳንዱ አመራር ልዩነት ይኖረዋል፡፡ ይሄ እንግዲህ ያለ ነው፡፡ ችግራችን ምንድነው ልዩነት ሲመጣ የግለሰቦች ፀብ ነው ነጥሮ የወጣው፤ ነገር ግን ይሄ መሆን የለበትም፡፡ ግለሰቡን ሣይሆን ከተቃወምንም ሃሳቡን ነው መቃወም ያለብን። ኢትዮጵያውያን የሚጐደለን ይሄ ይመስለኛል። ስለዚህ እንዳልከው አንድነትን የመሠረቱት ብዙዎቹ ሰዎች ከዚህ አኩርፈው የሄዱ ናቸው። ያኔ በተለያዩ ምክንያቶች ሄደዋል፡፡ አሁን ግን ከስህተቶቻችን ተምረን አብረን ጠንክረንና ተባብረን እንሠራለን። አንድ ጊዜ ተጣልተናልና መልሰን አብረን መስራት አንችልም የሚል እምነት አይኖረንም፡፡ እየተጋጨንም ዞረን ደግሞ ስህተታችንን አምነንና ተማምነን መስራት ምንም ማለት አይደለም፡፡ ለወደፊትም አለመግባባቶች ቢኖሩ በዚህ መልኩ እየተማመኑና እየተወያዩ መሄዱ ይቀጥላል የሚል እምነት ነው ያለኝ እና ከዚህ አንፃር ቢታይ መልካም ነው፡፡
በየጊዜው ፓርቲዎች መድረክ፣ ትብብር፣ ህብረት፣ ቅንጅት እያሉ በጋራ እየተሰባሰቡ ሲወድቁ ሲነሱ የኢትዮጵያ ህዝብ ታዝቧል፡፡ መኢአድም የዚህ ሂደት አንዱ አካል ነው፡፡ ለወደፊትስ ፓርቲያችሁ በዚህ ሁኔታ እስከየት ድረስ ነው ሊጓዝ የሚችለው?
እንግዲህ ባለፉት 22 አመታት የፓርቲዎች ስብስብ አንድ ሲሆን ሲለው ደግሞ ሲፈርስ ኖሯል፡፡ እንደ እኔ አመለካከት ይሄ የሆነው ሁሉም ነገር በግለሰቦች ፍላጐት ላይ የተመሠረተ ስለነበረ ነው፡፡ ይሄ ኢትዮጵያንም ሆነ ዜጐቿን የጐዳ ትልቁ በደል ነው፡፡ አንዳንዱ የፓርቲ አመራር ለኢትዮጵያና ለኢትዮጵያውያን ቆሜያለሁ ካለ፣ ራሱን ለዚያ አላማ መሸጥ አለበት፡፡ ግቡ ወይም የሩቅ አላማው ኢትዮጵያውያንን ነፃ ማውጣት ወይም በኢትዮጵያ ዲሞክራሲ ሠፍኖ ማየት መሆን አለበት። ግን በዚህች ሀገር እስካሁን ሲደረግ የቆየው እኔ ሊቀመንበር ካልሆንኩ፣ የኔ ፓርቲ የበላይ ካልሆነ ሲባል ነው፡፡ ከዚህ አንፃር አሁንም ቢሆን መኢአድ ሊያደርግ የሚችለው የጋራ ትግል አስፈላጊነትን ያምናል፤ ስለዚህ እስከቻለው ድረስ ከአላማው ጋር ከሚስማሙት ጋር አብሮ ይሠራል፡፡ ይህ መሆኑ ጠቀሜታዎች አሉት፡፡ አንደኛ ድምጽ አይሻሙም፤ በሁለተኛ ደረጃ በህዝቡ ላይ በራስ የመተማመን ስሜትን መፍጠር ይቻላል። አለኝታ የሚሆን ፓርቲ አለኝ ብሎ እንዲያምን ይገደዳል፡፡ ደካማና የተነጣጠለ ፓርቲ ሆነው ካያቸው ግን ህዝቡ እምነት ሊጥልባቸው ይቸገራል እና መኢአድ አሁንም| ተመሳሳይ ፕሮግራም ካላቸው ድርጅቶች ጋር አብሮ ለመስራት ቁርጠኛ ነው፤ ግን ይሄ የሚሆነው በቅንነት፣ በእውነተኛነት ኢትዮጵያን እያሰበ ከሚመጣ አካል ጋር ነው፡፡ ሸር ይዞ ከሚመጣ ጋር ግን ለመስራት ይቸገራል፡፡
መኢአድ ራሱ አንዴ ሲቀናጅ፣ ሲዋሃድ፣ ሲተባበር ሲያሻው ደግሞ ቅንጅቱና ውህደቱን ሲያፈርስ የኖረ ፓርቲ ነው፤ አሁንም በዚህ አዙሪት ውስጥ መሆኑን ያዩ ወገኖች ፓርቲው ግራ የተጋባ ነው ሲሉም ይደመጣል…
ፓርቲያችን ግራ የተጋባ አይደለም፡፡ ግልጽ አላማ ግልጽ የሆነ ፕሮግራምና ደንብ ያለው ፓርቲ ነው። ፓርቲው ህብረ ብሔራዊ፣ ብዙ አባላትና ደጋፊዎች በውጭም በሀገር ውስጥም ያለው በመልካም አመራር የሚመራ ፓርቲ ነው፡፡ ስለዚህ ይህን አምነው ከሚመጡ ፓርቲዎች ጋር ለመስራት መኢአድ ዝግጁ ነው፤ ነገር ግን የሚመጡትን ፓርቲዎች ለመምራት የሚሞክር ሳይሆን አብሮ የሚሰራ ነው፡፡
በየክልሉ ያሉ ቢሮዎቻችሁ እየተዘጉባችሁ እንደሆነ ስትገልፁ ከርማችኋል፡፡ ከነዚህ ክልላዊ እና ጐሣዊ ፓርቲዎች ጋር ለመቀናጀት የወሰናችሁበት ሚስጥር ምናልባት ዳግም ለመጠናከር አስባችሁ ይሆን?
ይሄም ዝም ብሎ ግምታዊ አስተያየት ነው እንጂ ፓርቲው አሁን በየትም ቦታ ብትሄድ ቢሮ አለው ወይም መዋቅር አለው፡፡ እንደተባለው በተለያዩ ጫናዎች ምክንያት በተለይ የወረዳዎቹ ቢሮዎች ተዘግተው ነበር፡፡ ይሄ ደግሞ መኢአድን ብቻ ሣይሆን ሌሎችንም ጐድቷቸዋል፡፡ ስለዚህ አሁን መኢአድ በሃገሪቱ ካሉ ፓርቲዎች ጠንካራው ነው ብል ስህተት አይደለም። በሀገር ውስጥም በውጭም ያሉ ደጋፊዎቻችን ለፓርቲው መጠናከር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያደረጉ ነው። እዚህ ያለው አመራርም የተዘጉ ቢሮዎችን ለማስከፈት ጥረት እያደረገ ነው። እስከ 2007 ድረስ ሙሉ ለሙሉ እስከታችኛው መዋቅር ድረስ ቢሮ ይኖረናል ብለን ተስፋ እናደርጋለን። ይህን ካልኹ፣ አሁን የኢትዮጵያ ህዝብ፤ “አንድ ላይ ካልተባበራችሁ፣ ካልሠራችሁ ለትግሉ አስቸጋሪ ነው” በሚል ህብረት እንድንፈጥር እየጠየቀ ነው፡፡ ስለዚህ መኢአድ፤ የኢትዮጵያ ፖለቲካ ወደ አንድ መጥቶ፣ ጠንካራ ፖለቲካ ፓርቲ ተፈጥሮ፣ መወዳደር አለባቸው እንጂ መቶ ደካማ ፓርቲዎች ዝም ብለው መጮህ የለባቸውም የሚል እምነት አለው፡፡ ከዚህ አንፃር ነው እንጂ እኛ ድክመት ኖሮብን በእነሱ ለመሸፈን አይደለም፡፡ እነሱ ብዙም ይዘው የሚመጡት ነገር የለም፡፡
መኢአድ ከሌላው የተሻለ ሰፊ ህዝባዊ መሠረት ካለውና አደረጃጀቱም ጠንካራ ከሆነ በምርጫ ወቅት ለምን ተፎካካሪ ሊሆን አልቻለም?
ፓርቲው እየታገለ ያለው እሱ ብቻ የስልጣን ባለቤት እንዲሆን አይደለም፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ የስልጣን ባለቤት እንዲሆን ነው፡፡ እንደተባለው ፓርቲው ጠንካራ መሠረት ያለው ቢሆንም ከገዢው ፓርቲ የሚደርስበት ጫናም በዚያው ልክ የሰፋ ነው። አባላቱ ንብረታቸውን ይነጠቃሉ፣ ይታሰራሉ፣ ይደበደባሉ፤ ሰዎች የፓርቲው አባል ስለሆኑ ብቻ የተለየ ጥቃት ይደርስባቸዋል፡፡ እንደነዚህ አይነት ተጽእኖዎች ደግሞ ሊያራምዱ አይችሉም፡፡ በሌላ መንገድ ገዥው ፓርቲ የራሱን የደህንነት አባላት እና ካድሬዎች በየፓርቲዎቹ ውስጥ ሰግስጐ ያስገባል፡፡ በዚህም በፓርቲ ውስጥ መናወጥ ይፈጥርና የፓርቲውን አመራር ያዳክማል፡፡ ይሄ በማዕከል ብቻ ሳይሆን በዞንና በወረዳም ጭምር የሚደረግ ነው፡፡ እንደነዚህ አይነት ተጽእኖዎች ናቸው ከፍተኛ ችግር የፈጠሩት፡፡ ህዝቡም መወጣት ያለበትን ሃላፊነት መወጣት አለበት፡፡ እውነተኛውንና ውሸታሙን መለየት መቻል አለበት፤ ዳር ሆኖ መመልከቱ አይጠቅምም፡፡
ተቃዋሚዎች ለመዳከማቸው ገዢውን ፓርቲ ተጠያቂ ያደርጋሉ፤ ገዥው ፓርቲ ደግሞ ጠንካራ ተቃዋሚዎች ባለመኖራቸው ሸክሜ በዝቷል እያለ ነው…
እዚህ ላይ ሁለት ነገር ነው የሚታየኝ፡፡ አንደኛ አቶ መለስም በህይወት በነበሩ ጊዜ የተናገሩት ነው፡፡ ጠንካራ ተቃዋሚ ፓርቲ ቢመጣ ሩቅ መንገድ ሄደን እንቀበለዋለን ተብሎ ነበር፡፡ ነገር ግን ቅንጅት ተፈጥሮ ጠንካራ ፓርቲ ሲመጣ በጥይት ግንባሩን ነው ያሉት። ይሄ አባባል እንግዲህ ፖለቲከኞቻችን ለይስሙላ የሚጠቀሙት መሆኑን አረጋጋጭ ነው፡፡ “እንዳይበላ ግፋው እንዳያማህ ጥራው” አይነት ነገር ነው፡፡ አሁንም አቶ ኃይለማርያም የተናገሩትን ሰምቸዋለሁ “ሌሎቹ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ሃላፊነትን መሸከም ስላልቻሉ የሃገሪቱ ሸክም ሁሉ ኢህአዴግ ላይ ወድቋል። ተበራቱ” የሚል ነው፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ ኢህአዴግ ምንም አይነት ሃላፊነት ሊሸከም የሚችል ፓርቲ ነው ብዬ አላምንም፡፡ ለምን? የኢትዮጵያን ህዝብ ሰብአዊ መብት እየጣሰ ያለ ፓርቲ፣ ሃላፊነት እሸከማለሁ ቢል አይታመንም፡፡
በሁለተኛ ደረጃ የኢትዮጵያን ህዝብ አዎንታ የተቀበለ ፓርቲ አይደለም፡፡ በሃይል፣ በመሳሪያ ስልጣን የያዘ ፓርቲ ነው፡፡ እኔ የማዝነው አቶ ኃይለ ማርያም በጣም ክርስቲያን ናቸው ይባላል፤ ግን በእዚህ አይነት ጉዳይ ላይ የሚናገሩት ነገር ከእምነታቸው ይቃረንብኛል፡፡ እነሱ የሰብአዊ መብት ጥሰቶችን ያቁሙና ከዚያ በኋላ ጠንካራ ተቃዋሚ ካጡ ይሄን ነገር ሊናገሩ ይችላሉ፡፡
መኢአድን ጨምሮ ብዙዎቹ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በግለሰብ አውራዎች ላይ የተመሠረቱ ሆነው ይታያሉ። ከፕሮግራምና አላማቸው ይልቅ ፕሬዚዳንቶቻቸው ጐልተው ይወጣሉ፡፡ የሚሆነው ለምን ይመስልዎታል?
በእርግጥ ይሄ ነገር መሆን የሌለበት ነው፡፡ አመራር ብቻ አይደለም፤ አባላትም በሁሉም ነገር ላይ ተሣትፎአቸው መጠየቅ አለበት፡፡ የእነሱ ተሣትፎ ከሌለበት የኔ ነው የሚሉት ነገር ሊኖር አይችልም። በመጀመሪያ ደረጃ አባላቱ የኔ ነው ሊሉ የሚችሉት ፓርቲው አሣታፊ ሲሆን ነው፤ ስለዚህ እንደነዚህ አይነት ነገሮች በቀጣይ ሊታረሙ የሚገቡ ናቸው፡፡ አመራሩና አባላቱ የውስጥ እኩል ተሣትፎ ሊኖራቸው ይገባል። አንድ ሰው አንድ ፓርቲ ሊሆን አይገባም። የእከሌ ፓርቲ ሊባል አይገባም፡፡ መኢአድ ያንን ለማድረግ እየሰራ ነው፡፡ በአደረጃጀቱም ትልቁን ስልጣን የሚሰጠው ከታች ላለው ነው፡፡ የፓርቲ አመራሮች ራሳቸውን ለአባላቱ ተገዢ ካላደረጉ፣ ነገ ለሚመሩት የኢትዮጵያ ህዝብ ተገዢ ሊሆኑ አይችሉም።
የ2007 ምርጫ እየተቃረበ ነው፡፡ መኢአድ ከምርጫው ምንድን ነው የሚጠብቀው?
እኛ ስራችንን እየሰራን ነው፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ አዎንታውን ከሰጠን ስልጣን ለመያዝ ከመጓዝ የሚያግደን ነገር የለም፣ ነገር ግን የመጫወቻ ሜዳው በትክክለኛው መንገድ ካልሄደ የኢትዮጵያን ህዝብ ልናማው አንችልም፡፡
እኛንም ህዝቡ ሊያማን አይገባም፤ ማማት ያለበት ገዢውን ፓርቲ ነው፡፡ በጥይት በዱላ እየደበደበ አባላቶች እንዳይሳተፉ የሚያደርግ ከሆነ፣ በምርጫ ወቅት ካርድ እየሰረዘ አሽነፍኩ የሚል ከሆነ፣ በምርጫ ወቅት ታዛቢዎቻችንን እየደበደበ፣ በመድሃኒት እያሠከረ እያስተኛ የሚዘርፍ ከሆነ መታማት ያለበት ገዢው ፓርቲ ነው፡፡ መኢአድ በ2007፤ መቶ በመቶ አሸንፋለሁ ብሎ እየተራመደ ነው ያለው፤ ይሄን ደግሞ እርግጠኞች ነን። ለምን ካልን አሁን የኢትዮጵያ ህዝብ ለውጥ ፈልጓል፤ ግን ለውጡን የሚሸከምለት ፓርቲ ይፈልጋል፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ ዛሬ በብዙ መልኩ መብቱ ተጥሷል። የሃገሪቱን የኢኮኖሚ ትሩፋት መጠቀም ተስኖታል፡፡ የቀን ሠራተኛው፣ ብሎኬት ሠራተኛው፣ ዶሮ አርቢው ሣይቀር ከውጭ እየመጣ ነው፡፡ የሀገሪቱ ዜጋ መጠቀም አልቻለም፡፡

በዱሮ ጊዜ በአንድ መንደር አራት ክፉ ክፉ አለቆች ይኖሩ ነበር ይባላል፡፡ እነዚህም፤ አቶ ዓለም፣ አቶ ደመና፣ አቶ ሰማይ ነህ እና አቶ በላይ ይባላሉ፡፡
አቶ ዓለም ለምጣም ሲሆን ሰውን ከሥራ ማባረር የሚወድ ቂመኛና ክፉ ሰው ነው፡፡ በማርፈድ ከሥራ ያስወጣል፡፡ ቆማችሁ ስታወሩ አገኘኋችሁ ብሎ ከሥራ ያስወጣል፡፡ ስጠራችሁ ቶሎ አልመጣችሁም ብሎ ከሥራ ያባርራል፡፡
አቶ ዓለም ደግሞ ከባላገር መጥቶ የሠለጠነ፣ ከሁሉ የምበልጥ ነኝ ባይ፣ ትኩስ ዘናጭ ነው፡፡ ሆኖም ሌላው የለበሰው ማናቸውም ልብስ ያስቀናዋል። በዚህ ምክንያት ደህና የለበሰ ሰው ላይ መጮህ ነው፡፡ ሰበብ እየፈለገ መደንፋት ነው!
አቶ ሰማይ ነህ ደግሞ የሁሉ አለቃ ነኝ ባይ ነው፡፡ ዋና ሥራው መጠራጠር ነው፡፡ ምንም ነገር ይስማ “ይቺማ ነገር አላት” ይላል፡፡ አንድ ሰው ለጨዋታ ብሎ ቀና ነገር ሲነግረውም፤ “ከጀርባው ምን አለው? ምን ቢያስብ ነው?” ይላል፡፡
የመጨረሻው አቶ በላይ ነው፡፡ በላይ እንደስሙ የበላይ ነው፡፡ የመሥሪያ ቤቱ የመጨረሻ ጣሪያ እሱ ነው፡፡ ግን መሀይም ነው! የተማረ ሲያይ ደሙ ይፈላል፡፡ “ወረቀት አደለም! ወረቀት አደለም! ዋናው ሥራ ነው! እዚህ ወረቀት እያንጋጋችሁ አትጐለቱ!” ይላል፤ ጠዋት ገና ሥራ ሲገባ!
እነዚህን ሰዎች በቅጡ የሚያውቅ ባለቅኔ እንዲህ ሲል ገጠመ ይባላል
“ዓለም ቡራቡሬ፣ ሁሉን ሰው አታላይ
ደመናውን አልፎ፣ አለ ጥቁር ሰማይ
የተማረው ከሥር፣ ያልተማረው በላይ”
                                                              * * *
የሀገራችን ቢሮክራሲ በመልካም ሰዎች ሳይሞላ መልካም አስተዳደር ማምጣት አዳጋች ነው፡፡ ከመግዛት ባህሪያችን፤ ከአለቅነት ባህሪያችን በፊት ሰው የሚያደርግ ልዩና መልካም ባህሪ ሊኖረን ይገባል፡፡ ለዚህ ደግሞ ከቤተሰብ ጀምሮ ከተኮተኮትንበት ግብረገብነት እስከ ትምህርት ወግ -ማዕረግ ድረስ የሠለጠነ አዕምሮና የበሰለ የህይወት ልምድ ውስጣችን መገንባት ይኖርበታል። ከዚያ፤ በሥራ ዓለም የምናገኘው የዕለት ተዕለት ልምድ፣ ከየሰዉ ጋር ያለንን መስተጋብር (Interaction)፣ ትዕግሥትና ሆደ - ሰፊነት፣ ትህትናና ክህሎት፤ ብሎም የአመራር ብቃት እየሠረፀብን ይመጣል፡፡
በዚህ ላይ ነው እንግዲህ ቅጥ ያለው የፖለቲካ አመለካከት ሲጨመርበት፣ በግድ እኔ ያመንኩትን እመን፣ ያን ካላረክ ጠላቴ ነህ፤ የሚል ሰው አንሆንም፤ የምንለው፡፡ ያመንከውን አምነህ፣ ተቻችለን አንድ መሥሪያ ቤት መኖር አያቅተንም ብለን ማሰብ፤ ጤናማና ዲሞክራሲያዊ አስተሳሰብ ነው። ከማቃቃር ይልቅ ያቀራርበናል፡፡ ከማራራቅ ይልቅ ያስተቃቅፈናል፡፡ ከመጠፋፋት ይልቅ ያስተራርመናል፡፡
በእስተዛሬው የፖለቲካና የማህበራዊ ጉዞአችን ወይ “ብቆጣም እመታሻለሁ፣ ብትቆጪም እመታሻለሁ” ማለት፤ አለበለዚያ ደግሞ “አሸናፊ ነኝ ያለኔ አታውራ”፤ “ተሸናፊ ነህ ስላንተ እንዳይወራ!” እንዳንል ያደርገናል፡፡
መልካም የስፖርት ድጋፍ ባህል መዳበር አለበት፡፡ በስንት ዘመን ዛሬ ያጋጠመንን ዕድል ተመስገን እንበል፡፡ ተጨዋቾቻችን በምንም መመዘኛ ዛሬ የደረሱበት ደረጃ የሚመሰገን ነው፡፡ አንድ ከተመልካቾቻችን የሚጠበቅ ባህል አለ ዘላቂነት የሙሉ ጊዜ ድጋፍ የመስጠት ልምድ! ይሄ በአንድ ቀን ሊሆን የሚችል ባህሪ እንዳልሆነ ግልጽ ነው፡፡ ሆኖም በልቦናችን ይደር ብናሸንፍ ወይም ብንመራ ቴሌቪዢናችንን የበለጠ እንደማንከፍተው ሁሉ፤ ብንሸነፍ ቴሌቪዥናችንን አንዘጋውም፡፡
ከአንድ የጭብጨባና የጩኸት ድጋፍ ድምጽ በአንድ ጊዜ ወደሚደብት የድብርት ድባብ አንግባ፡፡ በየትኛውም ማህበራዊ መስክ፣ ፖለቲካችንን ጨምሮ፤ የሞቅ ሞቅና የለብለብ አካሄድ ደግ አደለም፡፡ ዘላቂ እንሁን በአቋማችን እንግፋ፡፡
አለበለዚየ “ያደሩበት ጭቃ፣ ከጭድ ይሞቃል” ዓይነት ይሆንብናልና በአዎንታዊ ጉዟችን እንግፋ ማናቸውም ውጤት የነገ መንገዳችን መትጊየ ነው፡፡ ፈረንጆች፤ “all that had gone before was a preparation to this; And this is a preparation to this” ይላሉ፡፡ “እስካሁን ያለፍንበት ሁሉ እዚህ ለመድረስ ነበር፡፡ ይሄ ደሞ ለነገ መዘጋጃችን ነው” እንደማለት ነው፡፡
ድል ለዋሊያዎቻችን!

Published in ርዕሰ አንቀፅ

  መጋቢት 20 ቀን 2001 ዓ.ም በ950ሺ ብር ካፒታል ሥራ የጀመረው “ጃካራንዳ ኢንተግሬትድ አግሮ ኢንዱስትሪ አክሲዮን ማህበር” የስራ አመራር ቦርድና ማኔጅመንቱ በውዝግብ ላይ ሲሆኑ ከሁለቱም ወገኖች የተለያዩ ቅሬታዎችና አስተያየቶች እየተደመጡ ነው፡፡ 
በመጀመሪያ የተነሳው ቅሬታ ከማህበሩ መስራችና ስራ አስኪያጅ ከነበሩት አቶ ደመላሽ ወጋየሁና ከሌሎች ሰዎችም ጭምር ሲሆን የስራ አመራር ቦርዱ በአመት ከተፈቀደለት 97ሺህ ብር በላይ በመጠቀምና ወደ 131 ሺህ ብር ከፍ በማድረግ ማህበሩን ለኪሳራ እየዳረጉ ስለመሆኑ፣ የቦርዱ ፀሐፊ አቶ ሙሉ ሸዋ ከስርዓትና ከደንብ ውጭ በየወሩ አምስት መቶ ብር ሊከፈለኝ ይገባል በሚል በፃፉት ደብዳቤ የ19 ወር 9500 ብር ያለ አላግባብ የተከፈላቸው ስለመሆኑ፣ አሁን እየሰራ ያለው ቦርድ መጋቢት 2 ቀን 2004 በተጠራ አስቸኳይ ስብሰባ ጊዜያዊ ቦርድ ሆኖ መመረጡንና ጥቅምት 9 ቀን 2005 ዓ.ም መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ ጠርቶ ስልጣኑን ማፀደቅ ሲገባው አለማፅደቁን፣ በየአመቱ ጠቅላላ ጉባኤ መጥራት ሲገባው እስካሁን ስብሰባው አለመጠራቱን፣ ባለአክሲዮኖች የሚያውቁትንና የሚገናኙበትን ሁለት የስልክ መስመሮች ቀይረው በአዲስ ስለተኩት ባለአክሲዮኖች ግንኙነት መፍጠር አለመቻላቸውን፣ ቦርዱ የማህበሩን መተዳደሪያ ደንብ አላዘጋጀም፣ የ2006 አመት በጀትም የለውም፣ ቦርድ ሲመረጥ በንግድ ህግ ቁጥር 349 መሰረት በስራ ዘመኑ ላጠፋቸው ጥፋቶች ዋስትና ማስያዝ ቢኖርበትም በስራ ላይ ያለው ቦርድ ምንም አይነት ዋስትና አለማስያዙን፣ ጠቅላላ ጉባኤ ጠርተው ሳያስታውቁና ንግድ ሚኒስቴር ሳያውቅ ቢሮ መቀየራቸውንና መሰል ችግሮች በቦርዱ እየተከሰተ ስለመሆኑ አንዳንድ ባለአክሲዮኖችና መስራቹ አቶ ደምመላሽ ወጋየሁ ይናገራሉ፡፡
ይህንን በተመለከተም ለፀረ - ሙስና ኮሚሽን፣ ለገቢዎችና ጉምሩክ የህግ ማስከበር ዘርፍ ጽ/ቤት፣ ንግድ ሚኒስቴር የንግድ ምዝገባና ፈቃድ ዳይሬክቶሬትና ለሌሎች የሚመለከታቸው አካላት በደብዳቤ ማሳወቃቸውን ይናገራሉ፡፡
“ከ2500 በላይ ባለድርሻዎች ያሉትን ጃካራንዳ፤ ማህበርን በማመን አካል ጉዳተኞች፣ አቅመ ደካሞችና ዕድሮች ሳይቀሩ አክሲዮን ገዝተዋል ግን ብሩ በህገ - ወጦች እየተመዘበረ ነው ይህን በማጋለጤና ለምን በማለቴ ከስራና ከደሞዝ አግደውኛል” ይላሉ አቶ ደምመላሽ፡፡
ግለሰቡ አክለውም አክሲዮን ማህበሩ ስራውን በማስፋፋት፣ በምዕራብ ሸዋ ዞን ባኮ ቲቤ ወረዳ፣ በ300 ሄክታር መሬት ላይ የእርሻ ስራ ልማት የጀመረ “ዩ ኤፍ ቢ ፋርም” የተባለ ድርጅት ለጃካራንዳ በሽያጭ ለማስተላለፍ ባቀረበው ጥያቄ መሰረት፤ 2.5 ሚሊዮን ብር ያለ ደረሰኝ ከፈፀመ በኋላ ቀሪውን ግማሽ ሚሊዮን ብር ህጋዊ ደረሰኝ ሲያቀርቡ ለመክፈል ስምምነት ላይ መደረሱን ተናግረዋል፡፡ ይሁን እንጂ የድርጅቱ ባለቤቶች ለተከፈላቸው 2.5 ሚሊዮን ብር ህጋዊ ደረሰኝ እንዲያመጡና ቀሪውን ግማሽ ሚሊዮን ብር እንዲወስዱ በቃልም በጽሑፍም ቢጠየቁም “ድርጅታችንን ዘግተናል፤ የምን ደረሰኝ ነው የምትጠይቁን” በሚል ማስቸገራቸውን የገለፁት አቶ ደመላሽ፤ ወደፊት እንዲከፈላቸው የተሰጣቸው ቼክ እንዲታደግ ማድረጋቸውን ጠቁመው አሁን በስራ ላይ ያለው ቦርድ ይህ ጉዳይ በሂደት ላይ መሆኑን እያወቀ እና ሪፖርት ተደርጐለት እያለ ከግለሰቦቹ ጋር በመመሳጠር እንዲሁም የመንግስትን ገቢና የድርጅቱን ጥቅም ለማሳጣት ቀሪ ገንዘባቸው እንዲከፈል ትዕዛዝ ለማኔጅመንቱ መስጠቱንና በዚህም አቶ ደመላሽ በግላቸው ቅራኔ ውስጥ መግባታቸውን ለኢፌድሪ ገቢዎችና ጉምሩክ የህግ ማስከበር ጽ/ቤት ለኢፌድሪ ፀረ ሙስና ኮሚሽን እና ለኢፌድሪ ንግድ ሚኒስቴር የንግድ ምዝገባና ፈቃድ ዳይሬክቶሬት በፃፉት ደብዳቤ አሳውቀዋል። “ለተከፈላቸው ክፍያ ህጋዊ ደረሰኝ ሳያቀርቡ ለምን ቀሪ ክፍያ ይፈፀማል በሚል ቅሬታ በማሰማቴ ቦርዱ በህግ ለመጠየቅ የማስጠንቀቂያ ደብዳቤ ጽፎልኛል” ያሉት አቶ ደመላሽ ነገር ግን ቦርዱ ለግለሰቦቹ ተባባሪ በመሆን እርሳቸውን ከስራና ከደሞዝ በማገድ ያለምንም ደረሰኝ 50ሺህ ብር የከፈላቸው መሆኑንና ይህም በህዝብ ንብረት ላይ መቀለድ መሆኑን በመግለጽ መቃወማቸውን ለሚመለከታቸው የመንግስት አካላት የፃፉት ደብዳቤ ያሳያል። ይህን ጉዳይ የተመለከተው በንግድ ሚኒስቴር የንግድ ምዝገባና ፈቃድ ዳይሬክቶሬት ጥቅምት 21 ቀን 2006 ዓ.ም ለጃካራንዳ ኢንተግሬትድ አግሮ ኢንዱስትሪ አክሲዮን ማህበር የስራ አመራር ቦርድ ሊቀመንበር “የአክሲዮን ማህበሩን አጠቃላይ አሰራር ዝርዝር የሚያሳዩ መግለጫዎች እንዲቀርቡ ስለመጠየቅ” በሚል ርዕስ ደብዳቤ የፃፈ ሲሆን፤ ጃካራንዳ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያገኙ ዘንድ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች አክሲዮን በመግዛት ያቋቋሙት ማህበር ሲሆን ማህበሩ ለአባላት ጥቅም ከማስገኘት ይልቅ በርካታ አስተዳደራዊ ችግሮች ያሉበት ስለመሆኑ ከመስራች አባላት በጽሑፍና በቃል ቀርበው ለመ/ቤቱ ከሰጡት መረጃ መረዳቱን፣ በተጨማሪም የስራ አመራር ቦርዱ ወቅቱን ጠብቆ አባላትን ለስብሰባ በመጥራት በችግሮች ዙሪያ ማወያየትና መፍትሔ ማፈላለግ ሲገባው እስካሁን ስብሰባ ለመጥራት ፈቃደኛ አለመሆኑን በመግለጽ ጥቅምት 25 ቀን 2006 ዓ.ም ከቀኑ በስምንት ሰዓት በጉዳዩ ላይ ጥልቅ ውይይት ለማድረግ በምዝገባና ፈቃድ ዳይሬክቶሬት እንዳገኙ ለቦርዱ ሰብሳቢ የፃፉት ደብዳቤ በዝግጅት ክፍላችን ይገኛል፡፡
“ያለ ደረሰኝ ሁለት ነጥብ አምስት ሚሊዮኑን ብር ለግለሰቦቹ እንዴት ልትሰጡ ቻላችሁ በሚል ለአቶ ደመላሽ ላነሳነው ጥያቄ “አሁን ካለው ቦርድ በፊት ስራ ላይ የነበረው ቦርድ ባስተላለፈው ትዕዛዝ መሰረት ክፍያ ፈጽመናል” ሲሉ መልሰዋል፡፡
የቦርድ አመራሮች ራሳቸው ቼክ ፈራሚ ራሳቸው ፈቃድና ወሳጅ በአጠቃላይ ፈላጭ ቆራጭ ሆነው የሚሰሩበት አካሄድ ፈጽሞ ከህግ ውጭ በመሆኑ አሁንም ተቃውሟቸውን እንደሚቀጥሉ የተናገሩት አቶ ደመላሽ በአሁኑ ሰዓት እኔን ተክተው የሚሰሩት አቶ ፍቅረማርያም ሃ/ጊዮርጊስ የቁጥጥር ኮሚቴ ሆነው በሚሰሩበት ጊዜ ከላይ በቦርዱ ላይ ባነሳናቸው ቅሬታዎች ዙሪያ አብረው ይሰሩ እንደነበር ጠቁመው የቁጥጥር ኮሚቴ ሆነው ሳለ ስራ አስኪያጅ ሆነው መሾማቸው ከህግ አሰራር ውጭ ነው በማለት ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል። “እስካሁን ከላይ የገለጽኳቸውን 11 ነጥቦች ለንግድ ሚኒስቴር፣ ለድርጅቱ የውጭ ኦዲተር እና ለሚመለከታቸው አቅርቤያለሁ” ያሉት የቀድሞው የድርጅቱ ስራ አስኪያጅ እና አደራጅ አሁንም ችግሮች ባለመቀረፋቸው የህዝብ ንብረትና ገንዘብ አደጋ ላይ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የእኔነት ስሜት ተሰምቷቸው የሚሰሩ ሰራተኞች በደሞዝ ማነስ ስለመሰናበታቸው በቦርዱ የተባረሩ ሠራተኞች ስለመኖራቸው እና በመሰል ጉዳዮች ስለተነሱት ቅሬታዎች በአስቸኳይ ምላሽ ካልተገኘ የድርጅቱ ህልውና አደጋ ላይ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
የማህበሩ ባለድርሻና የቀድሞው የማህበሩ የአዲስ አበባ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ሃላፊ የነበሩት አቶ ጌታቸው ገብረየስ በበኩላቸው በአዲስ አበባ በሃላፊነት በሚሰሩበት ወቅት 12.5 ሚሊዮን ብር መሰብሰባቸውን ገልፀው “እኛን አምነው ዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ያላቸው አካል ጉዳተኞች ሳይቀሩ አክሲዮን ገዝተው ጥቅም ሲጠብቁ ኩባንያው አሁን ያለበት ችግር ላይ መገኘቱ አንገት ያስደፋል” ይላሉ፡፡ ለድርጅቱ መቋቋም ደም የመስጠት ያህል መስዋዕትነት እንደከፈሉ የሚናገሩት አቶ ጌታቸው በዚህም ለጤና እክል ተጋልጠው በፈቃዳቸው ስራቸውን መልቀቃቸውን፣ ነገር ግን አሁን ያለው የቦርዱ አሰራርም ሆነ ኩባንያው ያለበት ሁኔታ ስጋት እንደሆነባቸው ይናገራሉ፡፡
“አሁን ሥራ ላይ ካለው ቦርድ በፊት የነበሩት ሁለት ጊዜ የተመረጡ የቦርድ አመራሮች በድርጅቱ ላይ ባደረሱት ጥፋት በጠቅላላ ጉባኤ ተሽረው አሁን ያለው ቢመረጥም ጥፋት እንጂ ልማት አላመጣም” ያሉት አቶ ጌታቸው፣ የመጀመሪያዎቹ ሁለቱ ቦርዶች ላይ መንግስት እርምጃ ቢወስድ ኖሮ ሶስተኛው ለእንዲህ አይነት ስህተት አይነሳሳም ነበር ሲሉ አማረዋል፡፡
“ይህንን በመቃወም እንቅስቃሴ እያደረገ ያለው አቶ ደመላሽ ከመስከረም ስድስት 2006 እስከ ጥቅምት 30 ቀን 2006 ዓ.ም ድረስ ከስራም ከደሞዝም መታገዱ የቦርዱን ችግር ያሳያል” ብለዋል፡፡
ከላይ የተቀሱትን ቅሬታዎች መነሻ በማድረግ የቦርዱ አባልና ፀሐፊ የሆኑትን አቶ ሙሉ ሸዋ ከበደን ያነጋገርን ሲሆን ቦርዱ በአስቸኳይ ስብሰባ የተመረጠ እንደመሆኑ ጠቅላላ ጉባኤ ጠርቶ ስልጣኑን ለምን አላፀደቀም የሚለውን ጥያቄ አስቀድመናል የቦርዱ ፀሐፊው መጋቢት 2 ቀን 2004 ዓ.ም በተጠራ ጠቅላላ ጉባኤ የቀድሞ የቦርድ አባላት ያጠፉት ጥፋት ተገልፆና የሚባረሩት ተባረው በተደረገ ምርጫ አሁን ስራ ላይ ያለው ቦርድ ሃላፊነት መረከቡን ገልፀው ይሁን እንጂ ይህ ቦርድ ሀላፊነት ሲረከብ ኩባንያው በብዙ ምስቅልቅል ችግሮች ውስጥ እንደነበረ ተናግረዋል፡፡ በተለይም የድርጅቱ መስራች እና ስራ አስኪያጅ የነበረው አቶ ደመላሽ ወጋየሁ ተናኜ የተባለው ግለሰብ ከ2002 ዓ.ም ጀምሮ በሀላፊነት እየተንቀሳቀሰ እንደነበርና መጋቢት ሁለት በተደረገው ጠቅላላ ጉባኤ ላይ መሳተፉን፣ ከዚያም በጉባኤው ምርጫ መሰረት አሁን 18 ወራት በመስራት ያስቆጠረው ቦርድ የመጀመሪያው ስራ ርክክብ ማድረግ እንደነበር ገልፀው የቀድሞው ቦርድ ጋር ርክክብ ከማድረግ ይልቅ ህጋዊ ቦርድ አይደላችሁም በሚል ወደ ፍርድ ቤት ሄደው ከፍተኛ ክርክር እንደነበርና ጉዳዩ በፍትህ አካል ታይቶ “ጉባኤው የመረጠውን አካል ህጋዊ አይደለህም ማለት አይቻልም” ሲባል ተፈርዶባቸው 36ሺህ ብርም እንደተቀጡ የቦርዱ ፀሀፊ ይናገራሉ፡፡
“ከዛን ጊዜ ጀምሮ የኩባንያውን ውስብስብ ችግሮች በመፍታት ረገድ ከፍተኛ እንቅስቃሴ ከማድረግ አልቦዘንም” የሚሉት ፀሀፊው አቶ ደመላሽም የቦርዱን ችግሮች ለመፍታት አብሮ ከቦርዱ ጋር ሲሰራ እንደነበረም አስታውሰዋል፡፡ ጉባኤው የቀድሞውን የድሬክተሮች ቦርድ ሲያሰናብት አቶ ደመላሽ በስራ አስኪያጅነት እንዲቀጥል ስምምነት ላይ መደረሱን የሚገልፁት አቶ ሙሉ ሸዋ፣ “አቶ ደመላሽ አልፀደቁም ህጋዊ አይደሉም ለሚለው እኛ ለሶስተኛ ጊዜ የተመረጥን እንጂ ለኩባንያው አዲስ አይደለንም” ካሉ በኋላ ግለሰቡ ከስራ የተሰናበተው ለአክሲዮን ማህበሩ አባላትም ሆነ ለሌሎች አካላት ውዥንብር የመንዛት እንቅስቃሴ ላይ በመሆኑ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ አቶ ደመላሽ “በኩርፊያ በገዛ ፈቃዱ ጳጉሜ አንድ ቀን 2005 የኩባንያውን ስራ ለቆ የተለያዩ ለማህበሩ ጐጂ የሆኑ እንቅስቃሴዎችን እያደረገ እንደሆነ ደርሰንበታል” ይላሉ አቶ ሙሉ ሸዋ፡፡
“የድሬክተሮች ቦርድ በወር አንድ ጊዜ እየተገናኘ ማኔጅመንቱን ይቆጣጠራል እንጂ ዝቅ ብሎ ኦፕሬሽናል ስራአይሰራም” የሚሉት የቦርዱ ፀሀፊ፣ “እኛ ስራውን ስንረከብ ከገጠሙን ፈተናዎች ውስጥ የ2002፣ የ2003 እና የ2004 ዓ.ም ሂሳብ አለመመርመሩ ነው” የሚሉት አቶ ሙሉ ሸዋ ከዚያም ቦርዱ በያዘው አቋም የ2003 እና የ2004 ዓ.ም ሂሳብ በውጭ ኦዲተር መመርመሩን ይናገራሉ። የውጭ ኦዲተሩም የማህበሩ አባላት የሰየሙት በመሆኑ በሂሳብ አያያዙም ላይ በርካታ ችግሮች እንዳሉበት አስተያየት ሰጥቷል ብለዋል፡፡ “ለረጅም ጊዜ ስራ አስኪያጅ ሆኖ እንደመስራቱ የውጭ ኦዲተሩ ችግሮች ብሎ በሰጣቸው አስተያየቶች ላይ ለጠቅላላ ጉባኤ ስራ አስኪያጁ ምላሽ እንዲሰጥ በማለት የስብሰባ ፈቃድ አውጥተን፣ የአዳራሽ ኪራይ ተነጋግረን ጨርሰን እያለ ጉዳዩ ወደ ውጥረት ሲገባ ጳጉሜ 1 ቀን 2005 ዓ.ም ከስራ እንድናሰናብተው ጠየቀን” ሲሉ አብራርተዋል፡፡
“አንድ አክሲዮን ማህበር ጠቅላላ ጉባኤ ሲጠራ ዋናውን እና አባለት መስማት የሚፈልጉት የፋይናንስ ሪፖርት ነው” ያሉት የቦርዱ ፀሀፊ፣ የፋይናንስ ሪፖርት በምናዘጋጅበት ጊዜ እንቅፋቶችን የፈጠረብን ያለው አቶ ደመላሽ ነው” ብለዋል። ፀሀፊው አክለውም ብዙ የአክሲዮኑ ባለ ድርሻዎች አዲሱን ቦርድ የአቶ ደመላሽ አሸርጋጅ አድርገው በመውሰድ “ሰውየው አጭበርባሪ ነው ለምን አትሰሙንም” በሚል ተቃውሞ ሲያሰሙ ነበር ይላሉ፡፡ ጳጉሜ አንድ ቀን ስራውን ሽባ አድርጐ ሲጠፋ ጠቅላላ ጉባኤ ተጠርቶ የፋይናንስ ሪፖርት ተደርጐ ጉባኤው የሚወሰነውን ሰምተህ መሰናበት አለብህ በሚል ደብዳቤ መፃፋቸውን እና የፃፉትን ደብዳቤ ኮፒ ሰጥተውናል፡፡
የቦርዱን አመታዊ በጀት በተመለከተ ከ97ሺህ ብር እንዴት 131ሺህ ብር አደገ ለሚለው ጥያቄ አቶ ሙሉ ሸዋ ሲመልሱ ቦርዱ እንደማንኛውም የአክሲዮን ማህበር ቦርድነቱ በንግድ ህጉና በአክሲዮን ማህበር መተዳደሪያ ደንቡ መሰረት ወርሀዊ አበልና የስብሰባ አበል እንዳለው ገልፀው፣ ወርሀዊ እና የስብሰባ አበሉን የሚከፍለውም አቶ ደመላሽ እንደሆነ ይገልፃሉ፡፡
“ማህበሩ በትክክለኛ በጀት የሚንቀሰቀስ አልነበረም ትክክለኛ በጀት በ2004 ዓ.ም የሰራነው እኛ ነን” የሚሉት አቶ ሙሉ ሸዋ ከመጠን በላይ ተከፈለ የሚባለው ሊሆን አይችልም ምክንያቱም በወር የሚከፈለው እና በስብሰባ የሚከፈለው አባል የታወቀ ነው ብለዋል፡፡ “ምናልባት ከፍ ብሏል ብሎ አቶ ደመላሽ የገለፀው በማህበሩ የተለያዩ ችግሮች ሳቢያ በርካታ ስብሰባዎች ይካሄዱ እንደነበር፣ በድርጅቱ ላይ የተመሰረቱ በርካታ ክሶች እንደነበሩ፣ አቶ ደመላሽን በየሳይቱ ለስራ በላክነው ቁጥር “ሰዎች ሊገድሉኝ እየተከታተሉኝ ነው” ሲል እሱን ለማዳን ወደ አዋሽ እንደሚሄዱ፣ ባኮቲቤ ላይም ሽፍቶች ሊገድሉኝ ነው ሲል ተነስተው እሱን ለማዳን እንደሚሄዱ ገልፀው ይህ ሁሉ ወጪ ሲወጣ ያውቃል ግን በደብቅና ለቦርዱ አባላት ጥቅም ተብሎ የባከነ ሳይሆን እርሱ ለፈጠራቸው ችግሮች መፍትሄ ለማምጣት ነው ይላሉ፡፡ “ከዚህ በተረፈ ላጠፋው ጥፋት ሽፋን ለመፍጠር በቦርዱ ላይ ስም የማጥፋት ዘመቻ ቢከፍትም ማንም ከህግ የሚያመልጥ ስለ ሌለ እኛም ካጠፋን እሱም ካጠፋ በህግ እንጠየቃለን” ብለዋል አቶ ሙሉ ሸዋ፡፡
“ጥቅምት ሰባት ቀን በስድስት ገፅ ደብዳቤ ቦርድ ደንቆሮ ነው በሚል ዘለፋ አካሂዷል” ሲሉም ተናግረዋል የቦርዱ ፀሀፊ፡፡
ቦርዱ እስካሁን ጠቅላላ ጉባኤ ለምን አልጠራም በሚል ላነሳነውም ጥያቄ ስራ ላይ ያለው ቦርድ መጋቢት ወር 2004 መመረጡን ፀሀፊው አስታውሰው፣ በንግድ ህጉ መሰረት የበጀት አመቱ ባለቀ በሶስት ወር ስብሰባ መጥራት ግድ መሆኑንና የበጀት አመቱ ባለቀ በሶስት ወር ስብሰባ ለማካሄድ የ2004 የበጀት ሪፖርት መጠየቃቸውን ሆኖም እንኳን የ2004 የ2002 እና የ2003 ሪፖርት እንደሌለ እንደደረሱበት ይህ ሁሉ ሪፖርት ሳይስተካከል ጠቅላላ ጉባኤ መጠራት እንደማይቻልና ይህን ሲያስተካክሉ ስብሰባውን እንዳልጠሩ ተናግረዋል። ከአቶ ደመላሽ ጋር የጠባቸውም መነሻ ይሄው እንደሆነ ያብራራሉ፡፡
“የ2003 የሂሳብ ሪፖርት አቅርብ ሲባል ሂሳብ ያዧ ዘግታበት ሄዳለች በሚል ማስመርመር አልቻልኩም አለ” የሚሉት ፀሀፊው ቦርዱ ለቦሌ ክ/ከተማ ፖሊስና ለፌደራል የመጀመሪያ ፍ/ቤት ፕሬዚዳንተ አመልክቶ ፖሊስና የፍትህ አካላት ባሉበት ሳጥኑ መከፈቱን፣ የ2003 እና የ2004 ዓ.ም በብዙ ውጣ ውረድ እንዲዘጋ ማድረጋቸውን ገልፀዋል። ጉባኤው ለሾመው የውጭ ኦዲተር እንዲመረመርም ተደርጓል ይላሉ፡፡
“ይሁን እንጂ የ2005ን ጠቅላላ ጉባኤ እንዳንጠራም አቶ ደመላሽ እንቅፋት ሆኖብልና” ይላሉ ምክንያቱንም ሲያስረዱ፣ ሂሳቦችን በማሳከርና ውዥንብር በመፍጠር እንዲሁም የ2005ን የፋይናንስ ሪፖርት ሀርድና ሶትፍ ኮፒ ወስዷል ከዚያም ኮምፒዩተሩ ውስጥ ቫይረስ በመክተት ድራሹን አጥፍቶታል ይላሉ። ተጠባባቂ ስራ አስኪያጁ አቶ ፍቅረማሪያም ሃ/ጊዮርጊስ ሲጠይቁትም ለማቅረብ ፈቃደኛ አልሆነም ይላሉ፡፡ ይህ ባለበት ሁኔታ ከ 2500 በላይ አባላትን ጠርቶ ምን ይነገራል” ሱሉ ጠይቀዋል የቦርዱ ፀሀፊ።
“ቦርዱ በትክክል የሰራው 13 ወር ነው ከዚያ በፊት ያሉትን ስምንት ክሶች ስናስተካክል ነበር” ያሉት አቶ ሙሉ ሸዋ ከነዚህ ክሶች ውስጥ አንዱ ገንዘብ ያዧ ሊደፍረኝ ነበር ያለ አግባብ ከስራ ተባርሬያለሁ” የሚል እንደነበር ያብራራሉ፡፡
በንግድ ሚኒስቴር የምዝገባና ፈቃድ ዳይሬክቶሬት ለቦርዱ የፃፈውን ደብዳቤ በተመለከተም ቦርዱ ለሚኒስቴሩ ምዝገባና ፈቃድ ዳይሬክቶሬት ምላሽ የሰጠበትን ደብዳቤ ከቦርዱ ፀሀፊ አግኝተናል፡፡ ደብዳቤው ለምን ስብሰባ እንዳልጠራ አቶ ወጋየሁ ፈፀሙ ያለውን ስህተትና እየተካሄዱ ያሉ ጉዳዮችን ለዳይሬክቶሬቱ ፅፏል፡፡
“አቶ ደመላሽ ወጣትና የሀሳቡ አመንጪ ነው በሚል እምነትና ሀላፊነት ጥለንበት ነበር” የሚሉት ፀሀፊው አሁን ጥሎ ሲሄድ የስድስት ወር የቤት ኪራይ፣ የሶስት ወር የሰራተኞች ደሞዝ፣ የስድስት ወር የቢሮ ስልክ ሂሳብ፣ ቀጥተኛ መስመር ያለው የተንቀሳቃሽ የሶስት ወር ሳይከፍል እጅግ በርካታ ኪሳራዎችን አድርሶ እንደሆነ ይናገራሉ። ገንዘቡን ለመክፈል ባደረግነው ጥረት ከዚህ በፊት ከቦርዱ እውቅና ውጭ በዱቤ 160 ከብቶችን ሸጦ በፍ/ቤት ግለሰቦቹን አሳስረው አክሲዮን ማህበሩን ሂሳብ በመሰብሰብ እየተንቀሳቀሱና እዳዎችን እየከፈሉ እንደሚገኙ ፀሀፊው ተናግረዋል፡፡
ከዚህም በተጨማሪ ቲኬ ህንፃ ላይ የተከራየው ቢሮ ከማህበሩ አቅም በላይ 40ሺህ ብር በወር እንደነበረ፣ ከዚያም ቦርዱ ወደ 20ሺህ ዝቅ የሚል ቢሮ መከራየቱን፣ አሁን ደግሞ የነገው ሰው ት/ቤት ፊት ለፊት ባለ 12ሺህ ብር ቢሮ በመከራየት ኩባንያውን ከወጪ እየታደጉ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡
ሰራተኞችን ቦርዱ እያባረረ ነው የሚባለውን በተመለከተ በየሳይቱ ያሉ ፕሮፌሽናል ሰራተኞችን እያባረረ የነበረው አቶ ደመላሽ መሆኑንና የቦርዱ አባላት ግን አግባብተው መመለሳቸውን ከነዚህም ውስጥ አንድ ሳይንቲስት እና አግሮኖሚስት እንደሚገኙበት ፀሀፊው ገልፀዋል፡፡
ሁለት የስልክ መስመሮችን መቀየር አስመልክቶም ፀሀፊው መስመሮቹ መቀየራቸውን አምነው እሱ ደውሎ በርካታ ገንዘብ በመቁጠሩ ቴሌ ሄደው ማዘጋታቸውን ሌላ አዲስ መስመር ቦርዱ ማውጣቱንና ለአባላት ማሳወቁን ገልፀዋል፡፡
ማህበሩ የመተዳደሪያ ደንብ የለውም የተባለውን በተመለከተ እርሱ ከስራ የለቀቀው ከሁለት ወር በፊት ነው ይህን ጥያቄ እስከ ዛሬ ለምን አላነሳም ሲሉ ጠይቀው ማህበሩ መተዳደሪያ ደንብ ያለው መሆኑን እንዲሁም የ2006 በጀት የለውም መባሉንም አስተባብለዋል፡፡
ያነጋገርናቸው አንድ ከፍተኛ አክሲዮን ያላቸውና ስማቸው እንዳይገለፅ የፈለጉ ግለሰብ በሁለቱ ወገኖች ውዝግብ በህዝብ ንብረትና ገንዘብ ላይ ኪሳራ እንዳይደርስ መንግስት በአፋጣኝ ጣልቃ ገብቶ እልባት እንዲያገኝ አሳስበዋል፡፡
ጉዳዩን ንግድ ሚኒስቴር እየተከታተለው እንደሆነ በደረሰን ጥቆማ መሰረት ንግድ ሚኒስቴር በተደጋጋሚ ከመደወል ባሻገር ሀላፊው በሰጡን ቀጠሮ ቢሯቸው ድረስ ብንሄድም አስቸኳይ ስብሰባ እንደገቡ የነገሩን በመሆኑ ምላሽ ማግኘት አልቻልንም፡፡


           ብራዚል የምታዘጋጀው 20ኛው የዓለም ዋንጫ የቀረው 7 ወራት አካባቢ ነው፡፡ እስከዛሬ ማለፋቸውን ያረጋገጡት አዘጋጇን ብራዚል ጨምሮ 21 ብሔራዊ ቡድኖች ናቸው፡፡ አፍሪካን በመወከል ወደ ብራዚል የሚጓዙት 5 ብሔራዊ ቡድኖች የሚታወቁት ደግሞ ዛሬ ፤ነገ እና ማክሰኞ በሚደረጉ 5 የመልስ ጨዋታዎች ናቸው፡፡ አፍሪካን የሚወክለው የመጀመርያ ብሄራዊ ቡድን የሚታወቀው ነገ 12 ሰዓት ከ10 ደቂቃ ላይ ዋልያዎቹ ከናይጀሪያ አቻቸው ጋር በካላባር በሚገናኙበት ወሳኝ ፍልሚያ ነው፡፡ ሌላው የዛሬ ጨዋታ ሴኔጋል በሜዳዋ አይቬሪኮስትን የምታስተናግድበት ይሆናል፡፡ ነገ ካሜሮን ከቱኒዚያ ሲጫወቱ ማክሰኞ እለት ግብፅ ከጋና እንዲሁም አልጄርያ ከቡርኪናፋሶ የመጨረሻዎቹ ሁለት የመልስ ጨዋታዎች ያደርጋሉ፡፡ ረቡዕ በኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴል ዋና አሰልጣኝ ሰዉነት ቢሻዉ መግለጫ በሰጡበት ወቅት‹‹ የዓለም ዋንጫ ጉዳይ ከዛሬ በኋላ ያበቃለታል፡፡ በመደጋጋፍ ተጫውተን ናይጄርያን በማሸነፍ ታሪክ ለመስራት ተዘጋጅተናል፡፡ ለወደፊቱ እንደ እርሳስ የሾለ ብሄራዊ ቡድን እንዲኖረን ከስር መሰረቱ መስራት ያስፈልገናል፡፡

በማለት ተናግረዋል፡፡ በሌላ በኩል አዲሱ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ፕሬዚዳንት ዶክተር ሙላቱ ተሾመ በሳምንቱ አጋማሽ ላይ አዲስ አበባ ስታዲየም በመገኘት ከናይጀሪያ ጋር ለሚጠበቀው ወሳኝ ጨዋታ በልምምድ ላይ የሚገኘውን የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በማበረታት ያላቸውን አድናቆት ነገረዋቸዋል፡፡ ፕሬዝዳንቱ ‹‹ ከናይጄሪያ ጋር ካላባር ላይ የምታደርጉትን የ90 ደቂቃ ወሳኝ ፍልሚያ እመለከታለሁ እንደምታሸንፉ እምነቴ ነው ፤ጎል ስታስቆጥሩ እያጨበጨብኩ ደስታዩን እገልፃለሁ …በድል እንንደምትመለሱ እምነቴ ነው›› ብለዋል። የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት አቶ ጁነዲን ባሻህ ደግሞ ‹‹ ስትመለሱ የጀግና አቀባበል በማዘጋጀት ባለፉት አንድ አመታት ላደረጋችሁት አስተዋፅኦ ምላሽ የሚሆን ማበረታቻ እንሰጣለን ›› ሲሉ ለእያንዳንዳቸው የመኪና ሽልማት እንደሚሰጥም በአቶ አብነት ገብረመስቀል ቃል ተገብቶላቸዋል፡፡ ለዓለም ዋንጫ ለማለፍ በቀረቡ የቦነስ ክፍያዎች ለግብፅ ተጨዋቾች በነፍስ ወከፍ 25ሺ ዶላር፤ ለአይቬሪኮስት 18 ሺ ዶላር፤ ለጋና 15ሺ ዶላር፤ ለናይጄርያ ደግሞ 5ሺ ዶላር እንደሚበረከትላቸው ዘገባዎች አመልክተዋል፡፡ ቋሚ አሰላለፉ እና የግብ እድሉ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን 30 ተጫዋቾች ወደ ካላባር ተጉዘዋል፡፡ ሁሉንም ተጨዋቾች ለመውሰድ የተወሰነው ከመልሱ ጨዋታ ለሴካፋ ውድድር እና ለቻን በቂ ተመክሮ እና ልምድ እንዲያገኙ ተብሎ ነው፡፡

በውጭ አገር የነበሩትን ዩሱፍ ሳላህ እና ሆነ ፉአድ ኢብራሂምን አልጠራሁዋቸዉም ያሉት አሰልጣኝ ሰዉነት ፤ ከቡድኑ ጋር አብረው ልምምድ ለመስራት በጠየቁት መሰረት እድሉን እንደሰጧቸው በማስረዳት እነ ጌታነህና ሳላሀዲንን የሚያስቀምጥ አቋም እንደሌላቸዉም ገልፀዋል፡፡ አሰልጣኝ ሰውነት እንዳረጋገጡት አዲስ አበባ ላይ በተደረገው የመጀመርያ ጨዋታ ላይ በጉዳት ያልተሰለፈው ወሳኙ የአጥቂ መስመር ተጨዋች ጌታነህ ሙሉ ለሙሉ ተሽሎታል፤ ስለዚህም በዛሬው ጨዋታ መሰለፉ የማይቀር ይሆናል፡፡ በአጠቃላይ ዝግጅቱ ብሄራዊ ቡድኑ ከጥቅምት 11 ቀን ጀምሮ ሰርቷል። በሳምንቱ አጋማሽ ላይ በውጪ የሚጫወቱትን ሳላዲን ሰዒድ፤አዲስ ህንፃ፤ጌታነህ ከበደ፤ፉአድ ኢብራሂም ፤የሱፍ ሳላህን ጨምሮ ሁሉም ተጨዋቾች ተሟልተው እስከ ረቡዕ በአዲስ አበባ ልምምዳቸውን ሰርተዋል፡፡ በሞቃታማው ካላባር ለሚደረግ ጨዋታ በራሳችን አየር ሰርተን አንድ ቀን ሲቀረው ብንሄድ ይሻላል በሚል ተመካክረው ነው፡፡ ብሄራዊ ቡድኑ ካላባር ከገባ በኋላ ከፍተኛ ባረፈበት የቻናል ቪው ሆቴል ጥበቃ እየተደረገለት ልምምዱን በ5 ደቂቃ ርቀት በሚገኝ ሜዳ ላይ ላለፉት ሁለት ቀናት ሰርቷል፡፡

ለዛሬው ወሳኝ የመልስ ጨዋታ አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው የሚከተሉትን አጨዋወት በተመለከተ ሲናገሩ አጥቅቶ መጫወትን እንደሚያተኩሩበት ቢያመለክቱም ግብ እንዳይገባብን ከፍተኛ ጥንቃቄ እናደርጋለንም ብለዋል፡፡ ዋና አሰልጣኝ ሰውነት በዋልያዎቹ አሰላለፍ 4-4-2 ወይንም 4-3-3 ፎርሜሽን ሊጠቀሙ ይችላሉ እየተባለ ነው፡፡ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የዓለም ዋንጫ የማጣርያ ጉዞ ከዋልያዎቹ አባላት በተለይ አንዳንዶቹ ከፍተኛ ሚና ነበራቸው፡፡ በሁሉም ዘጠኝ ጨዋታዎች በመሰለፍ 799 ደቂቃዎች የተጫወተው አበባው ቡጣቆ በከፍተኛው ግልጋሎቱ የሚጠቀስ ተጨዋች ነው፡፡ አምበሉ ደጉ ደበበ በ7 ጨዋታዎች ለ630 ደቂቃዎች፤ ስዩም ተስፋዬ በ8 ጨዋታዎች ለ655 ደቂቃዎች፤ አይናለም ኃይሉ በ6 ጨዋታዎች 540 ደቂቃዎች እንዲሁም አዳነ ግርማ በ7 ጨዋታዎች 417 ደቂቃዎች በመጫወት አስተዋፅኦ ነበራቸው። በዛሬው ጨዋታም እነዚህ ተጨዋቾች ወሳኝ አገልግሎት መስጠታቸው ይጠበቃል፡፡ የዋልያዎቹ ግምታዊ አሰላለፍ ግብ ጠባቂ ሲሳይ ባንጫ ተከላካዮች - አበባው ቡጣቆ፤ ደጉ ደበበ፤ አሉላ ግርማ፤ አይናለም ሃይሉ አማካዮች - አስራት መገርሳ፤ ሽመልስ በቀለ፤ ምንያህል ተሾመ፤ አዳነ ግርማ አጥቂዎች - ሳላዲን ሰኢድ፤ ጌታነህ ከበደ ዛሬ በካላባር በሚደረገው ጨዋታ ትልቁ እና አስፈላጊው ሚና ከዋልያዎቹ የአጥቂ መስመር ተሰላፊዎችም ይጠበቃል፡፡

በዓለም ዋንጫው 9 የማጣሪያ ግጥሚያዎች ኢትዮጵያ ያስመዘገበቻቸውን 14 ጐሎችን አምስት ተጨዋቾች አስመዝግበዋል፡፡ በ7 ጨዋታዎች 617 ደቂቃዎችን በመጫወት 4 ጐል ያስቆጠረው ሳላሃዲን ሰኢድ ሲሆን ጌታነህ ከበደም በተሰለፋቸው 5 ጨዋታዎች 317 ደቂቃዎችን በመጫወት እኩል 4 ጐሎች አስመዝግቧል፡፡ በ7 ጨዋታዎች 508 ደቂቃዎችን የተጫወተው ሽመልስ በቀለ ሁለት ጐሎችን አስቆጥሯል፡፡ በ4 ጨዋታዎች 192 ደቂቃ የተሰለፈውና ኡመድ ኡክሪ 581 ደቂቃዎችን የተጫወተው ምን ያህል ተሾመ በ5 ጨዋታ 204 ደቂቃዎች ያገለገለው ቀሪዎቹን ሦስት ጐሎች በነፍስ ወከፍ አስቆጥረዋል፡፡ ውጤቱ ምን ሊሆን ይችላል? የናይጄርያን ብሄራዊ ቡድን በካላባር በሚገኘው የዩኤስ ኡስዋኔ ስታድዬም በቅርብ ጊዜ ተሸንፎ አያውቅም፡፡ ለማሸነፍ ከጫፍ ደርሶ አንድ እኩል አቻ የወጣው የሃራምቤ ኮከቦች የተባለው የኬንያ ብሄራዊ ቡድን በዓለም ዋንጫው የምድብ ማጣርያ ነበር። በ1994፤ በ1998፤ በ2002 እና በ2010 እኤአ ላይ አራት ዓለም ዋንጫዎችን የተሳተፈችው ናይጄርያ ዛሬ ኢትዮጵያን ካሸነፈች አምስተኛው ተሳትፎዋን ስታረጋግጥ ኢትዮጵያ ደግሞ የመጀመርያ ታሪካዊ ስኬቷ ይሆናል፡፡ የቀድሞው የግብፅ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ ሃሰን ሺሃታ ለዓለም ዋንጫ የማለፍ እድል አላቸው ብለው በልበሙሉነት ግምት የሰጡት ለአይቬሪኮስት፤ ለአልጄርያ እና ለናይጄርያ ነው። ናይጄርያ ኢትዮጵያን ጥላ የምታልፈው በሁለቱ ቡድኖች ያለው ልምድ ከፍተኛ ልዩነት ስለሚፈጥር ነው ብለው ሃሰን ሺሃታ ተናግረዋል፡፡

የእንግሊዝ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ የሆኑት ሮይ ሆጅሰን በበኩላቸው 20ኛው የዓለም ዋንጫን የማሸነፍ እድል የሚኖረው ከአውሮፓ አገሮች ይልቅ ለአፍሪካ ተወካዮች ነው ብለው ተናግረዋል፡፡ የብራዚል አየር ንብረት የሚስማማው ለአፍሪካ ብሄራዊ ቡድኖች መሆኑን የጠቀሱት ሆጅሰን የአፍሪካ ብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች በአውሮፓ የክለብ እግር ኳስ ያላቸው ልምድንም እንደ ከፍተኛ አቅም ተጠቅመው ዓለም ዋንጫን ሊያሸንፉት ይችላሉ ብለዋል፡፡ነገ ዋልያዎቹ ከንስሮቹ ጋር በሚያደርጉት ትንቅንቅ ጨዋታው ስንት ለስንት ይጠናቀቃል? ቀድሞ ማን ጎል ያሰቆጥራል? ለዋልያዎቹ እነማን ያገባሉ? የሚሉት ጥያቄዎች በተለይ ባለፉት ሶስት እና አራት ቀናት በከፍተኛ ደረጃ መላው ኢትዮጵያዊን እያነጋገሩ ነበር፡፡ በዛሬው ጨዋታ ኢትዮጵያ 2ለ0 ወይም 3ለ2 ማሸነፍ ከቻለች በመደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ለዓለም ዋንጫ ማለፏን ታረጋግጣለች፡፡ በሜዳዋ የምትጫወተው ናይጀሪያ በጨዋታው አቻ ውጤትና በማንኛውም ውጤት ማሸነፍ፤ በ1 ጎል ልዩነት መሸነፍ እንዲሁም 0ለ0 ፣ 1ለ1 እና 3ለ3 አቻ መለያየት ይበቃታል፡፡ ኢትዮጵያ ከናይጄሪያ ዛሬ ካላባር ላይ በሚያደርጉት የመልስ ጨዋታ ውጤቱ ምን ሊሆን ይችላል ? በሚል ጥያቄ ኢትዮፉትቦል በድረገፁ አንባቢዎቹን አሳትፎ ነበር፡፡ 331 አንባቢዎች ድምፅ በመስጠት ተሳትፈዋል፡፡ ኢትዮጵያ ታሸንፋለች ያሉት 67.07 በመቶ ሲሆኑ ናይጄሪያ እንደምታሸንፍ የገመቱት 29.31 በመቶ ናቸው።

3.63 በመቶ ደግሞ አቻ ውጤት ተንብየዋል። በሌላ በኩል ታዋቂው ጐል ስፖርት ድረገጽ አንባቢዎችን በማሳተፍ በሠራው የውጤት ትንበያ በቀረቡ 3 የውጤት ግምቶች ሙሉ ለሙሉ አሸናፊነቱ የተሰጠው ለናይጀሪያ ነው፡፡ 12.46 % 2ለ0፣ 10.38 % 3ለ1 እንዲሁም 18.69 % ያህሉ 3ለ0 በሆነ ውጤት ናይጀሪያ በሜዳዋ ኢትዮጵያ እንደምታሸንፍ ገምተዋል፡፡ ሶከርዌይ በሰራው ትንበያ ደግሞ ናይጄርያ 73.4 በመቶ እንዲሁም ኢትዮጵያ 23.8 በመቶ የማሸነፍ እድል ሲኖራቸው አቻ የሚወጡበት ግምት ደግሞ 8 በመቶ ነው፡፡ በሶከርዌይ ድረገፅ ናይጄርያ 0 ኢትዮጵያ 2 ብለው የገመቱ 24.9 በመቶ፤ ናይጄርያ 3 ኢትዮጵያ 0 ብለው የገመቱ 20.97 በመቶ ናይጄርያ 2 ኢትዮጵያ 0 ብለው የገመቱ 12.9 በመቶ ናቸው፡፡ አስራት መገርሳ የሱፐር ሱፕርት ዘጋቢ አስራት መገርሳን ተወዳጁ የዋልያ ተጨዋች ብሎታል፡፡ አዲስ አበባ ላይ በተደረገው የመጀመሪያው ጨዋታ ላይ የነበረው ምርጥ ብቃት የናይጀሪያ ምክትል አሰልጣኝ ዳንኤል አሞካቺን አሳስቦት ነበር የሚለው ዘገባው በወቅቱ ንስሮቹ በከፍተኛ ሞገስ የመሃል ሜዳውን በተቆጣጠረው አስራት በኩል መጫወታቸውን ትተው በክንፍ እንዲንቀሳቀሱ ሲጮሆባቸው ነበር ብሏል፡፡ ስቴፈን ኬሺም በናይጀሪያ ቋንቋ “ቾይ” ወይም ዋው ብሎ አስራት መገርሳን አደንቆታል።

=======================

አበባው ቡጣቆ የዋልያዎቹ ወሳኝ የግራ መስመር ተመላሽ ተጨዋች የሆነውና በሁሉም የዓለም ዋንጫ የማጣሪያ ግጥሚያዎች ከፍተኛ አስተዋጽኦ የነበረው አበባው ቡጣቆ በበኩሉ ለሱፐር ስፖርት በሰጠው አስተያየት “እግዚአብሔር ከኛ ጋር ነው” ብሏል፡፡ ፀሎት ያደረግነው በካላባር ለኩራት የሚያበቃን ገድል ለመፈፀም ነው” ያለው አበባው ‹‹ለናይጀሪያውያን የማይቻል የመሰለውን ነገር ችለን እናሳያቸዋለን›› ሲልም ተናግሯል፡፡ እንደ ሱፐር ስፖርት ገለፃ አበባው ቡጣቆ በቅርብ ጊዜ በቱርክ ክለቦች ዓላማ ውስጥ መግባቱን ለማወቅ ተችሏል፡፡

=======================

ደጉ ደበበ የኢትዮጵያ ተከላካይ መስመር ምሰሶ ተብሎ በሱፐር ስፖርት የተሞካሸው አምበሉ ደጉ ደበበ ነው፡፡ “በካላባር ግዙፍ ተራራ መውጣት አለብን፡፡ እንደማንኛውም የእግር ኳስ ተጨዋች ውጤቱ በ90 ደቂቃዎች ይወሰናል ብለን ተስፋ አድርገናል፡፡ ናይጀሪያውን ጥንካሬያቸው ፈጣን የመልሶ ማጥቃት አጨዋወታቸው ስለሆነ ይህን በትኩረት እንከላከላለን” በማለት ደጉ ደበበ ለሱፐር ስፖርት በሰጠው አስተያየት ተናግሯል፡፡

=======================

አዲስ ህንፃ ያለውን ምርጥ የኳስ ችሎታ ሱፐር ስፖርት ያደነቀለት ሌላው የዋልያዎቹ ወሳኝ ተጨዋች አዲስ ህንፃ ነው፡፡ “የአፍሪካ ሻምፒዮን መሆናቸውን ብናከብርም በምንም ሁኔታ ዝቅተኛ ግምት ሊሰጡን አይችሉም” ብሎ ለሱፐር ስፖርት የተናገረው አዲስ ህንፃ፣ “ስለ ዓለም ዋንጫ የምናልመው ሁልጊዜ ነው፡፡ በሜዳችን ባደረግነው የመጀመያ ጨዋታ ህልሞችን መና የቀረ መስሎ ነበር፡፡ ግን ፍጻሜው ገና አልለየለትም” ብሏል።

  • “በኢትዮጵያ የፕሬስ ነፃነት ሙሉ በሙሉ ተከብሯል” - የጋዜጠኞች ማህበራት
  • “በኢትዮጵያ ሚዲያ ላይ ለውጥና ማሻሻያ እናደርጋለን” መንግስት
  • ኢህአዴግ ሌሊት ሌሊት የምረጡኝ ቅስቀሳ እያጧጧፈ ነው!

እንደኔ አላጋጠማችሁ እንደሆነ አላውቅም እንጂ ኢህአዴግ ሌሊት ሌሊት የምርጫ ቅስቀሳ ጀምሯል (ህገ መንግስታዊ መብቱ እኮ ነው!) እኔን የገረመኝ ግን ቅስቀሳው ሳይሆን ቀኑን ትቶ ሌሊትን መምረጡ ነው፡፡ (ቀንማ “ቢዚ” ነው!) ባለፈው ሳምንት ነው፡፡ ሰኞ ወይም ማክሰኞ ሳይሆን አይቀርም፡፡ ሌሊት ላይ እንቅልፍ እምቢ አለኝና ኢቴቪን ከፍቼ ቁጭ አልኩኝ (ብቸኛ “አጫዋቼ” ነው አላልኳችሁም!) ምናልባት ከሌሊቱ 9 ሰዓት ወይም 10 ሰዓት ገደማ ይሆናል፡፡ ኢቴቪ የኢህአዴግ የሴቶች ሊግ አባላትን የልማት እንቅስቃሴ የሚያስቃኝ ፕሮግራም ማቅረብ ጀመረ፡፡ (“የሴቶች ሊግ” የተሰኘ አዲስ ፕሮግራም ሳይሆን አይቀርም!) በኋላ ሲገባኝ ግን የልማት ሳይሆን የምረጡኝ ቅስቀሳ ነገር ነው፡፡ እኔ የምለው … በህዝብ ንብረት ቅስቀሳ ይቻላል እንዴ? (ኢህአዴግም እኮ የህዝብ ንብረት ነው!) አንድ ጥያቄ ግን አለኝ፡፡ የ2007 ምርጫ ወደ 2006 ተዛወረ እንዴ? ለቀጣዩ ዓመት ምርጫ ዘንድሮ ቅስቀሳ አይጀምርም ብዬ እኮ ነው! እናላችሁ … በኮብልስቶንና በሌሎች “ደሃ-ተኮር” ስራዎች ላይ የተሰማሩ ሴቶች አስተያየት ሲሰጡ፣ እንደሌላው ጊዜ ስማቸው ወይም የሥራቸው ዓይነት አይደለም ቲቪ ስክሪኑ ላይ የተጠቀሰው፡፡

ለእያንዳንዱ ተናጋሪ “ሊግ አባል” የሚል መግለጫ (Caption) ነው የተሰጠው። (መቼ የተጀመረች ግልፅነት ትሆን?) አንደኛዋ የሊግ አባል፤ ኢህአዴግ ከጓዳ (ማጀት) አውጥቶ ለአደባባይ እንዳበቃት ገለፀች፡፡ እሷም ብትሆን በጥቃቅን ሳትደራጅ በፊት ነው የሊጉ አባል የሆነችው፡፡ (ባለውለታ ናት ማለት ነው!) ቀጠለች-ሴትየዋ፡፡ “ለሴቷ አማራጭ ያለው ፓርቲ ነው” ስትል አውራ ፓርቲውን በደንብ አሞካሸችው (በእሷ ዓይን “ሲያንሰው” እኮ ነው!) ትንሽ ቅር ያለኝ ግን ምን መሰላችሁ? አባል ለመሆን መዘግየቷ ነው። “በ2001 ዓ.ም ነው አባል የሆንኩት” ብላናለች፡፡ (ያን ሁሉ ዓመት የማን አባል ነበረች?) በነገራችሁ ላይ …ከሴቶች ሊግ አባላት ውስጥ 99 በመቶ ያህሉ በሥራ ላይ የተሰማሩ (employed ወይም self employed) ሲሆኑ በቅርቡ አንድም ሥራ አጥ (zero unemployment) የሊግ አባል እንደማትኖር የሊጉ ሊቀመንበር ተናግረዋል፡፡

(ልብ አድርጉ! “አንድም የሊግ አባል” ነው የተባለው!) በነገራችሁ ላይ … ሊጉ የሚመራው “ሰጥቶ መቀበል” (ፈረንጆቹ Give and take ይሉታል) በሚለው መርህ ነው፡፡ በአበሽኛ “እከክልኝ ልከክልህ” የሚባለው መሰለኝ፡፡ እናላችሁ … የሊጉ አባላት በ2002 እና በአካባቢና ማሟያ ምርጫዎች ኢህአዴግን በመምረጥ ብቻ ሳይሆን እንዲመረጥ በመቀስቀስም ለፓርቲያቸው ያላቸውን የማይናወጥ “ታማኝነት” አሳይተዋል ብላለች - የሴቶች ሊግ ሊቀመንበሯ፡፡ (ካላሳዩማ አለቀላቸው!) እኔ የምለው … የሊግ አባል የመሆን ዕድል ላላገኙ የጦቢያ ሴቶች የሥራ ዕድልና ብድር የሚሰጣቸው ማነው? (ጥያቄ እኮ ነው!) እንደው ለጨዋታ ያህል ነው እንጂ… በኢቴቪ በውድቅት ሌሊት የተላለፈው የሴቶች ሊግ የምርጫ ቅስቀሳ ምንም ክፋት የለውም (አሳቻ ሰዓት ከመቅረቡ በቀር!) የሊጉን ቅስቀሳ ኮምኩሜ ልተኛ ስል ግን አንድ ሃሳብ መጣልኝ። “Drink Responsibly” ወይም “በሃላፊነት ስሜት ተጐንጩ” የሚለውን የቢራ ማስታወቂያ ታውቁታላችሁ አይደል? ኢህአዴግን ጨምሮ ሁሉም የጦቢያ ፓርቲዎች ራሳቸውን ሲያስተዋውቁና ሲቀሰቅሱ “Support Responsibly” ወይም “በሃላፊነት ስሜት ይደግፉ!” የሚል ማስታወቂያ ቢያክሉበት አልኩ-ለራሴ፡፡

(እንዴ … የፖለቲካ የአልኮል መጠን እኮ ከቢራ የአልኮል መጠን በብዙ እጅ ይልቃል፡፡) እኔ የምለው … ባለፈው ሳምንት በአፍሪካ ህብረት የተካሄደውን የአፍሪካ ሚዲያ መሪዎች ፎረም እንዴት አያችሁት? የአፍሪካ ነገር ሁሌ ችግሯን ሁሉ በፈረንጆቹ ላይ ማላከኳ አናደደኝ እንጂ ጋዜጠኞቹ መወያየታቸውና መወቃቀሳቸው የሚበረታታ ነው። አንድ ቀን ከምዕራባውያን ላይ ወርደው ራሳቸውን መቻላቸው አይቀርማ! የእኔን ትኩረት የበለጠ የሳበው ግን ጉባኤው እንዳይመስላችሁ! በፎረሙ መጠናቀቂያ ላይ ሦስት የጦቢያዋ “የጋዜጠኞች ማህበራት” ያወጡት “ድንቅ” የአቋም መግለጫ ነው። (ሦስቱ ማህበራት ለኢትዮጵያ ብቻ ነው ወይስ ለሶማሊያም?) እናላችሁ … የማህበራቱ መግለጫ የጋዜጠኞች ሳይሆን የ“አብዮታዊ መንግስት” ወይም “ድርጅት” ነበር የሚመስለው፡፡ ከአቋም መግለጫቸው መካከል አንደኛው ደግሞ ከኢህአዴግ ቃል በቃል የተኮረጀ ነው (ኮማ ሳይቀር!) ልዩነቱ ምን መሰላችሁ? ኢህአዴግ በተደጋጋሚ “በኢትዮጵያ ውስጥ ከሙያቸው ጋር በተያያዘ የታሰሩ ጋዜጠኞች የሉም” የሚል ምላሽ ሲሰጥ ደንፍቶ አያውቅም። እነሱ ግን ቀላል ቀወጡት! አገር ይያዝልን እኮ ነው ያሉት፡፡ ቦታው ስላልተመቻቸው ነው እንጂ ሽለላና ቀረርቶ ሁሉ ዳድቷቸው ነበር፡፡

(ኢህአዴግ ራሱ እኮ ሳይታዘባቸው አይቀርም!) እኔማ ምነው በገመገመልኝ ብዬ ነበር፡፡ ለካስ የኢህአዴግ አባል አይደሉም (ናቸው እንዴ?) የጋዜጠኞች ማህበራቱ ሁለተኛው የአቋም መግለጫ ደግሞ “በኢትዮጵያ የፕሬስ ነፃነት ከየትኛውም የአፍሪካ አገራት የበለጠ ተከብሯል” የሚል ነው፡፡ ይሄኛውም በድንፋታና በጩኸት የታጀበ ነበር፡፡ ይሄን የሰሙ የአፍሪካ ጋዜጠኞችና የሚዲያ መሪዎች አገራቸው እስከሚገቡ እንዴት እንደሚቸኩሉ አልታያችሁም? (ለመሳቅ እኮ ነው!) እንኳን እነሱ ኢህአዴግም ይሄኔ በመግለጫው ፍርስ ብሏል (አይነግረንም እንጂ!) እውነቴን እኮ ነው … መንግስት ራሱ “በአገራችን የፕሬስ ነፃነት ሙሉ በሙሉ ተከብሯል” ብሎ አያውቅም፡፡ (ከየት አመጡት ታዲያ?) በነገራችሁ ላይ … የአፍሪካ ሚዲያ መሪዎች ፎረም መክፈቻ ላይ ንግግር ያደረጉት ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ … መንግስታቸው፤ በኢትዮጵያ ሚዲያ ላይ ለውጥና ማሻሻያ እንደሚያደርግ ተናገሩ እንጂ “የፕሬስ ነፃነታችን እንከን የለሽ ነው!” ብለው አልተመፃደቁም፡፡ “ዲሞክራሲውም … ነፃ ፕሬሱም … የሰብአዊ መብት አያያዙም ወደፊት ከልማቱ ጋር እየተሻሻለ ይሄዳል” ነው - የኢህአዴግ አቋም፡፡ (“ከጳጳሱ በላይ አማኝ” አሉ!) የጋዜጠኞች ማህበራቱ ጉዳይ በዚሁ ቢያልቅ “ተመስገን” ነበር፡፡ ባለፈው ሳምንት ምሽት ደግሞ “የነፃ ጋዜጠኞች ማህበር” ፕሬዚዳንትና ጋዜጠኛ ሳምሶን ማሞ ይሄንኑ ጉዳይ ለኢትዮጵያ ህዝብ እንዲያብራሩ ተጋብዘው ነበር - በኢቴቪ፡፡

የሚገርመው ታዲያ የምሽቱ አጀንዳ “በኢትዮጵያ የታሰሩ ጋዜጠኞች አሉ የሉም” ወይም “የፕሬስ ነፃነት ተከብሯል አልተከበረም” የሚለው አልነበረም። የአገር ሉዓላዊነት ማስከበር፣ አንድነትና ነፃነትን ማስጠበቅ ወዘተ … ሆነና አረፈው (የአቋም መግለጫ በማውጣት “አርበኝነት” የለም እኮ!) የኢቴቪ ጋዜጠኛው (ጋባዡ ማለት ነው) ታደሰ ሚዛን፤ ለጋዜጠኞች ማህበሩ ፕሬዚዳንት አስገራሚ ጥያቄ አቀረበ (ሃሳቡን እንጂ ቃል በቃል አይደለም!) “በቀጣይ እንደ CPJ ያሉ የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ነን ባዮች ‘በኢትዮጵያ ጋዜጠኞች ታስረዋል፣ የፕሬስ ነፃነት ታፍኗል’ እያሉ የሚያወጡትን መግለጫ እንዴት መከላከል ይቻላል?” ፕሬዚዳንቱም አስገራሚ ምላሽ ሰጠ፡፡ “ፅናትና መስዋዕትነት ይጠይቃል” በማለት፡፡ የምን ፅናት ነው? የምንስ መስዋዕትነት? እውነቱን መናገር እኮ በቂ ነው - እንደ ኢህአዴግ፡፡ (እውነት አንፃራዊ መሆኗ እንዳይረሳ!) ሁለቱን ጋዜጠኞች ወይም የ “ነፃ ጋዜጠኞች” ተወካዮች በኢቴቪ የጋበዘው ጋዜጠኛ፤ አንድ ነገር ግን ሳይሸወድ አልቀረም፡፡ (“አውቆ በድፍረት ሳያውቅ በስህተት” ሊሆን ይችላል!) ምን መሰላችሁ? የጋዜጠኞች ማህበራት ያወጡትን መግለጫ፣ የአገርን አንድነት (ዳር ድንበር) እንደማስከበር ነው የቆጠረው፡፡

(በአቋም መግለጫ “አንድነት” ተከብሮ አያውቅም እኮ!) እናም … ማህበራቱ ወደፊትም ተመሳሳይ መግለጫ በማውጣት የአገሪቱን አንድነት ለማስጠበቅ ይጥሩ እንደሆነ ጠየቀ - ወደ ውይይቱ መጠናቀቂያ ላይ፡፡ (ወይ ፍሬን መበጠስ!) መልሱም “ፍሬን የበጠሰ” ስለሆነ ትቼዋለሁ፡፡ አንድ ጥያቄ አለኝ፡፡ ሦስቱ የጋዜጠኞች ማህበራት ዓላማ ምንድን ነው? (የጋዜጠኞችን መብት ማስከበር እንዳይሉኝ ብቻ!) “ኢህአዴግ ማረኝ” ማለት ይሄኔ ነው፡፡ (“የባሰ አለና አገርህን አትልቀቅ” አሉ!) እናንተ … እኔም ፖለቲካዊ ወጌን በአቋም መግለጫ ልቋጨው ዳድቶኝ ነበር፡፡ (አንድዬ እኮ ነው ያዳነኝ!) በሉ ሰሞኑን በቴክስት የደረሰኝን “ቧልት” ላካፍላችሁና ልሰናበት፡- “ዓለም አቀፍ የቤተሰብ ዕቅድ ጉባኤ ላይ የተሳተፈችና የቡራዩን የስነ ተዋልዶ ጤና ኤክስቴንሽን የጐበኘች አንዲት አሜሪካዊት፣ በተለይ ለኢቴቪ በሰጠችው ቃለ ምልልስ፤ ‘ምነው እኔም ኢትዮጵያ ውስጥ በወለድኩ’ ስትል አድናቆቷን ገለፀች” (ማንም ምንም ቢል የምዕተ ዓመቱ የልማት ግብ እንደሆነ መሳካቱ አይቀርም!!) ድል ለዋልያዎቹ!!

አንዳንድ ጊዜ፤ አብረውት ሊኖሩ ግድ የሚል ክፉ ዓመል ያለበትን ተቋም ወይም ግለሰብ ባሕርይውን ተረድቶ መቀበል መቻል ቢያንስ ቢያንስ በየዕለቱ ሲነጫነጩ ከመኖር ይታደግ ይሆናል፡፡ ነገር ግን፤ የዚያ ክፉ ዓመል ባለቤት ድርጊት ሕይወትን በቀጥታ የሚያጠፋ ሆኖ ሲገኝስ? አመሉ እስኪቃና በትንሹ ተራ እሰጥ-አገባ ውስጥ እየተዘፈቁ መበጣበጥ አይቀሬ ነው፡፡ አብረው አንድ ቤት ውስጥ የታሰሩት ሠው “ክፍሉን አቃጥለዋል” ብሎ ቢነሳ ዝም ማለት አይቻል ነገር! ባለፈው ማክሰኞ ጥቅምት 19 ቀን 2006 ዓ.ም ከምሽት ሁለት ሠዓት የኢቴቪ ዜና እወጃ ላይ አንድ ለተአማኒነቱና “የሚያውቁ ሠዎችስ ምን ይሉኝ ይሆን?” ብሎ ያልተጨነቀ ዜና ተላልፎ ነበር፡፡ ዜናው በጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሣለኝ ፊት አውራሪነት፣ በአርሲ ዞን ሁለት ወረዳዎች ውስጥ የተፈፀመ የእርሻ ልማት ጀብድን የሚመሰክር ነበር፡፡ ዜናው፤ የአካባቢው ነዋሪዎች መሬትን በማጠንፈፍና በመስመር በመዝራት ከዚህ ቀደም (በሀገራችን ይቅርና በምርታማው የኢቴቪ ማሣ ላይ እንኳ) ከተመዘገቡት ሁሉ እጅግ የላቀና ክብረወሰን የጨበጠ የምርት መጠን እንደሚጠበቅ የሚያትት ነበር፡፡

እንደዘገባውና ጠ/ሚኒስትሩም ደጋግመው ሲናገሩ እንደተደመጠው፤ በዞኗ ሁለት ወረዳዎች ይገኛል ካለ በኋላ፤ የሚጠበቀው የስንዴ ምርት መጠን ግን በሄክታር አንድ መቶ ሃያ ኩንታል ነው የሚል ነበር። ይሄንን የሁለት ሰዓቱን ዜና ብቻዬን ስላዳመጥኩትና ጆሮዬንም ማመን ስላቃተኝ፣ የድጋሚውን ዜና ከምሽቱ አራት ሠዓት ላይ ጠብቄ ከአንድ ሌላ እማኝ የሚሆን ሠው ጋር አብሬ አዳመጥኩት፡፡ ልክ ነው፡፡ በሄክታር አንድ መቶ ሃያ ኩንታል፤ በድጋሚ ስህተቱ ተደገመ፡፡ ወይ የቁጥርን ነገር አለማወቅ! መቼም ዜናውን፤ የለመድናቸው የኢቴቪ ጋዜጠኞችና አንድን የስንዴ ሰብል ዘለላ የፓፓዬ ዛፍ ለማሳከል የሚጥረው ካሜራቸው ሆነው፤ ዜናውን በምስል ብቻ አግዝፈውት ቢያልፉ ኖሮ እኛም ያው እንዳልሰማ ሆነን ማሳለፍ ባልከበደን ነበር፡፡

ችግሩ፤ የሀገሪቱ የመጨረሻው ከፍተኛ ባለሥልጣን በሥፍራው ተገኝተው፤ ይጠበቃል ስለተባለው የምርት መጠን የስህተቱ “አብሳሪ” ሆነው መሣተፋቸው ነው፡፡ ላለፉት አንድና ሁለት ዓመታት ያህል ስንዴ በሄክታር ስልሳ ኩንታል ተገኘ የሚለው ልፈፋ ለሙያው ቅርበት ባላቸው ሠዎች ዘንድ አልዋጥ ማለቱ አስገራሚነቱ ሳያበቃ፤ በሄክታር በአንድ ጊዜ መቶ ሃያ ኩንታል ማምረት ችለናል፤ ወደሚለው መሸጋገሩ ቅዠት ማብዛታችንን ይመሰክርብናል፡፡ በዓለም ዓቀፍ ደረጃ አማካዩ የስንዴ ምርት መጠን በሄክታር ሰላሳ ኩንታል አካባቢ መሆኑ የሚታወቅ ጉዳይ ነው፡፡ ከፍተኛ የስንዴ አምራች የሚባሉ ሀገራት ምርታቸው በሄክታር ከሃምሳና ስልሳ ኩንታሎች እንደማያልፍ መረጃው በየድረ-ገፁ ቢታሰስ ይገኛል። በተመሣሣይም፤ በኢትዮጵያ እንደ ባሌ ባሉ ለስንዴ ምርት እጅግ ተስማሚ የአየር ንብረትና የቦታ አቀማመጥ ባላቸው ሥፍራዎች እንኳ፤ (ያውም ዘመናዊ የእርሻ መንገዶችን በመጠቀም የሚገኘው) ከፍተኛው አማካይ የምርት መጠን፤ በሄክታር ስልሳ አምስት /35/ ኩንታል አካባቢ መሆኑ ይታወቃል፡፡ በዚሁ አካባቢ ያለው የምርት መጠን በገበሬ ማሳ ሲሆን መጠኑ ከጠቀስኩት አነስ ይልና፤ በአማካይ ከሃያ አምስት እስከ ሰላሳ ኩንታል በሄክታር ይሆናል።

ይኼ እውነታ ከጠ/ሚኒስትሩም ሆነ ከአማካሪ ባለሙያዎቻቸው የተሰወረ እንዳልሆነ እሙን ነው። ታዲያ ዋናው ጉዳይ ምንድነው? ጠ/ሚኒስትሩ ማስተላለፍ የፈለጉት ዋና መልዕክትና የዘገባውም ዋና ዓላማ፤ በትንሽ ማሳና በአነስተኛ ገበሬ የእርሻ ምርት ሊያድግ ያዳግተዋል፤ የሚሉ እውቀትን የተንተራሱ ተከራካሪዎችን አፍ ለማስያዝ የታለመ ነበር ዜናው፡፡ ከአንድ ወገን ጋር የተገባውን የ”እንችላለን” “የለም አትችሉም” ክርክር፤ በአፋዊ ሙግት ለመርታት ሲባል ብቻ፤ ፍፁም ከእውነታ ያፈነገጡ ውጤቶችን አስመዝግበናል ማለት… ያውም በሀገር መሪ ደረጃ ከትዝብትም በላይ ያሳዝናል፡፡

ጉዳዩ፤ የሀገሪቱን ሰዎች ከመጉዳቱና ከማሳዘኑ አልፎ፤ ለሌላ ታዛቢም አሳልፎ ይሰጣል፡፡ ምክንያቱም፤ መቼም አንድ የሀገር መሪ፣ በብሔራዊ የቴሌቪዥን ጣቢያ ያውም የመጀመሪያ ዜና ሆኖ ንግግራቸው ሲቀርብ፣ የዓለም ዓቀፍ ሠዎችም ምን ብለው ይሆን ብለው ትርጓሜውን በጉጉት መስማታቸው የማይቀር ነው፡፡ ታዲያ እንዲህ ያለ ከእውነታና ከሳይንሳዊ መስፈርቶች ያፈነገጠ ንግግር ሲሰሙ… በሌሎች ጉዳዮች ላይ የጠ/ሚኒስትሩ ተአማኒነት መጠራጠራቸው ይቀራል? ባላንጣን ለማብሸቅ እና ጓዳናችን ሁሉ በስኬት የተሞላ ነው ብሎ ንግግርን ለማሳመር ሲባል ብቻ በሀገራዊ እቅድና ውሳኔዎች ላይ ፍፁም አሉታዊ ተፅዕኖዎችን የሚያመጡ የሀሰት ውጤቶች ተመዘገቡ ማለት ብዙ መዘዝ አለው፡፡ ይኼው በየጊዜው በየወረዳዎች “ከዕቅድ በላይ እየተመረቱ ነው” የሚባለው የምርት መጠን መንግሥት ለሚያከናውናቸው እቅዶችና ውሳኔዎች በታሳቢነት መወሰዳቸው የማይቀር ነው፡፡ ለምሣሌ ትክክለኛው የምርት መጠን ታውቆ ቢሆን ኖሮ፤ ምናልባት፤ ሀገሪቱ ተጨማሪ የስንዴ ምርት በግዢም ሆነ በእርዳታ በወቅቱ ልታስገባ ይቻላት ነበር። ነገር ግን እንደተመረተ የታመነው ወይም እንዲታመን የተወሰነው መጠን ከሀገሪቱ ፍላጎት በላይ ነው የሚል ሊሆን ይችላል፡፡

ስለዚህ በመቀጠል የስንዴ ምርትን ወደ ውጭ ሀገራት ኤክስፖርት እናደርጋለን ተብሎ ይወሰናል፡፡ ከዚያም፤ በሀገሪቱ ከፍተኛ የምርት እጥረትና የዋጋ ንረት ሲከሰት፤ የተለያዩ ሰበቦች ከመንግሥት ወገን መደመጥ ይጀምራሉ፡፡ ሀብታም ገበሬዎች ምርታቸውን መሸጥ ስላልፈለጉ ወይም ስግብግብ ነጋዴዎች ምርቱን በመጋዘናቸው ስላከማቹ… ወይም ሚሊዬነር ገበሬዎች ስንዴን በተለያየ መልክ መመገብ ስለጀመሩ …. የማያልቅ ንዝንዝ፡፡ ጉዳቱ በዚህ ብቻ አያበቃም፡፡ በሀገራችን በተቋም ደረጃ ብዛትም ጥራትም ያለው የተማረና የሰለጠነ የሠው ሀይል ካላቸው መ/ቤቶች መካከል በግንባር ቀደምትነት ሊጠቀስ በሚችለው ግብርና ምርምር ተቋም ላይም አሉታዊ ተፅዕኖው ሊንፀባረቅ ይችላል። እንዴት? ቢባል፤ በየዓመቱ የአንድና ሁለት ኩንታል ለውጥ /ያውም/ ከተቻለ የምርት ዕድገት ለውጥ ማምጣት እጅግ ትልቅ ስኬት ሆኖ ሳለ፤ በፖለቲካዊ ውሳኔ በብዙ ልፋት የሚደረስበት የምርታማነት መጠን “ከመድረሻው ጣራ በላይ ተደርሷል” መባሉ ተነሳሽነታቸውን ያሽመደምደዋል። አሁን በገበሬ ማሳ ማግኘት የሚቻለውን ሰላሳ ኩንታል የማይሞላ ምርት፤ (በብዙ ምርምር ጥረት) ሠላሳ አምስት ኩንታል የሚያደርስ ውጤት በአንድ የግብርና ባለሙያ ቢገኝ፣ ምን ብሎ ሪፖርት ያደርጋል? ምክንያቱም፤ ገበሬው አንድ መቶ ሃያ ኩንታል የሚያመርትበት ደረጃ ቀደም ብሎ (በዜናው አማካኝነት) መድረሱን ሰምቷል፡፡

በዘመናዊ ግብርና ድርጅቶችና በመንግሥት ስር በሚገኙ እንደባሌ ግብርና መሥሪያ ቤቶች እንኳ ተመርቶ የማያውቅ ምርት (ለገበሬ ማሳ ያውም እርሻውም - ውቅያውም በበሬ፣ ምርት ስብሰባው በማጭድ፣ የግብዓት መጠኑ በበቂ ሳይሟላ!) የዓለምን የጊነስ ክብረወሰን የሚወዳደር ምርት አምርተናል ማለት፤ ጉዳዩን ለሚያውቅ ሠው ጥፋ ጥፋ የሚል ስሜት ያጭርበታል፡፡ በአመራረት የተሻለ ደረጃ የደረሱ ሀገራትን ተሞክሮ ወደ ሀገር ቤት አምጥቶ ለማስፋፋት ከመጣጣር ይልቅ የመጨረሻ ኋላ ቀር የአስተራረስ ዘዴን ይዞ መድረሻውን አልፈነዋል ማለት ምን ይሉት ፈሊጥ ይሆን?! በብዙ ሚሊዮን ብር ከውጭ ሀገራት የእርሻ መሣሪያዎችን እያስመጣ ዘመናዊ የእርሻ ድርጅቶችን የሚመራ ባለሀብት፣ እንዲህ በቀላሉ በበሬ እርሻ ከሶስትና ከአራት እጥፍ በላይ ምርት ተመርቶ ከተበለጠ ልፋቱ ሁሉ ከንቱ ነበር ማለት ነው፡፡ በየዓመቱ ምርትን አሳደግሁኝ በማለት ሥልጣንን ለማዳበርና የበላይ አለቃን ይሁንታ ለማግኘት ከየወረዳዎቹ የሚቀርቡ “የአድገናል - አምርተናል” የቁጥር ጨዋታዎች፣ በሀገር አቀፍ ደረጃ ቁጥር የማያውቁ ሕዝቦች እስክንመስል ድረስ በድፍረት እየተለፈፈ ይገኛል፡፡ የቀድሞ ምክትል ጠ/ሚኒስትርና ግብርናና ገጠር ልማት ሚኒስትር አቶ አዲሱ ለገሠ፤ ወደሥልጣን ማብቅያቸው ሰሞን… አንድ ያስተላለፉት ትዕዛዝ በዚሁ ጋዜጣ ተፅፎ ማንበቤን አስታውሳለሁ፡፡ ጉዳዩ ምን መሰላችሁ? በወቅቱ ከተለያዩ ወረዳዎች የቀረበላቸውን “ምርት በምርት ሆነናል” የሚል ሪፖርት ካዳመጡ በኋላ፤ በጣም ተቆጥተው አንዳንዶቹ ከፍተኛ መጋነን እንዳለባቸው ስለታወቃቸው ተስተካክለው ይመለሱ ማለታቸውን አንብቤአለሁ፡፡ ባልተለመደ መልኩ የተደመጠው የሚኒስትሩ ተግሳፅ አስገርሞኝም አስደምሞኝም ነበር፡፡ ምን ዋጋ አለው… የገፋበት የለም እንጂ?! ምንአልባት አቶ አዲሱ፤ ድርጅታቸው ከያዘው የ“አጋኖ አምርተናል” አባዜ በማፈንገጣቸው ሂሳቸውን ውጠው ይሆናል። ማን ያውቃል?!

“የአፍሪካ ውድቀት ሁሌም የግለሰቦች አምልኮ ነው”

ነሐሴ 15 ቀን 2004 ዓ.ም፣ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ህልፈተ ሕይወት የተሰማበት አስደንጋጭ ቀን ነበር፡፡ በአድናቂዎቻቸውም በተቺዎቻቸውም ኢትዮጵያዊያን ዘንድ ከፍተኛ የሀዘን ድባብ ተፈጥሮ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ አጥብቀው በሚነቅፏቸው ወይም እንደሚጠሏቸው በይፋ በሚናገሩ ዜጐች ዘንድ ሁሉ የተደበላለቀ ስሜት የፈጠረ ክስተት ነበር፡፡ ከሁሉም በላይ የአቶ መለስ የጤና ሁኔታን አስመልክቶ በየጊዜው ትኩስ መረጃ የማግኘት እድል የተነፈገው ህዝብ፣ ድንገት በተነገረው ህልፈታቸው ከመጠን በላይ መረበሹ ወይም በአስደንጋጭ መንፈስ ውስጥ መግባቱ ብዙ ላይገርም ይችል ይሆናል፡፡

ሀገራዊ መልክ ያለው የሚመስለው ቀዝቃዛ የመንፈስ ህብረት ግን ወደለየለት ተስፋ መቁረጥና የእርስበርስ ግጭት ሊያመራ ይችላል እስከሚል አስደንጋጭ ሁኔታ ድረስ፣ ከፍ ያለ ስጋት መፍጠሩን የሚያናፍሱ ዜጐች ነበሩ በማለት፣ ባለፈው ወር ገዢው ፓርቲ ኢህአዴግ በዋና ፀሐፊው በኩል በይፋ ሲወቅስም ተሰምቷል፡፡ እንደተባለው አቶ መለስ የዚች ሀገር እጣ ፈንታ ወሣኝ ብቸኛ አሳቢ፣ ተመራማሪ፣ ድህነትን ተረት አድራጊ መሪ፣ የልማታዊ ንድፈ ሃሳብ ቀማሪ፣ በተለይም ለገዢው ፓርቲ ኢህአዴግ የህልውናው ፈጣሪ ስለመሆናቸው በተለያዩ የመንግስት የመገናኛ ብዙሀን በየቀኑ እስከ ዶቃ ማሰሪያው ሲሞላ የነበረ ህዝብ፣ የሰውዬውን ህልፈት በድንገት ሲሰማ ባይደነብር፣ ተስፋ ባይቆርጥ ነበረ የሚገርመው፡፡

የህልውናው መሠረት የሆኑት ታላቅ መሪ ለዘላለሙ ሲለዩት፣በአስደንጋጭ የፍርሃት ቆፈን ባይቀፈደድ ነበር የሚደንቀው፡፡ ለሁሉም ሀገራዊ ችግሮቹ ብቸኛ መፍትሔ አፍላቂ የሆኑትን “መተኪያ የሌላቸው” ብልህ ሰው ድንገት ሲያጣቸው፣ መንፈሱ በሀዘን ባይሰበር ነበር የሚያሳዝነው፤ የአብዛኛው ህዝብ የመንፈስ ስብራት እውነተኛ መረጃ ከነበረ፡፡ ሁሉንም ነገር የሆኑትን መሪውን ያጣ አውራ የፖለቲካ ድርጅት ምን ቀርቶት፣ ምን ይዞ ነው ሀገር የሚመራው!? ብለው የሚጠይቁ ጥቂት አስተዋይ ዜጐች እንኳ ሊፈታተነኝ ይችላሉ ብሎ አለመጠርጠሩ ደግሞ፣ ሌላ ግርምት የሚፈጥር የሀገሪቱ መሪር ሀቅ ይመስለኛል፡፡ ቅጥ ያጣ ፕሮፖጋንዳ፣ ቅጥ ያጣ የዘመን መንፈስ ሊፈጥር እንደሚችል አስተውሎቱ ያነሰ ይመስለኛል፡፡ በለብለብ የፕሮፖጋንዳ እውቀት እንዲንሣፈፍ የሚፈለግ ዜጋ፣ በለብለብ ሆይ ሆይታ ሣይታወቅ ዚቅ ሊወርድ ይችላል፤ ያልተፈለገ የመዝቀጥ አደጋ ሊያጋጥመው ይችላል፡፡

የትውልድን ነፃ የማሰብ ፈቃድና አቅም የሚያኮስስ፣ የርዕዮተ ዓለም መሣከር ሁሉ የሚፈጥር ተግባር ነው ማለት ይቻላል፡፡ በትክክለኛ አስተሳሰብ ላይ በጥናት ያልተመሠረተ የፕሮፖጋንዳ ሥራ፣ ውጤቱ ክሽፈት እንደሆነ በብሔር ፖለቲካ ተወጥራ እስከመበተን የደረሰችው የስታሊንን የቀድሞ ሀገር ሶቭየት ህብረትን ብቻ ማስታወስ ይበቃል፡፡ በሌላ በኩል ኢህአዴግ የአቶ መለስን ሃሳብና ተግባር ያለመጠን እየለጠጠ፣ሰዋዊ ግብራቸውን ወደ መልአክነት ሲለውጠው፣ “ኢህአዴግ የመላዕክት ስብስብ አይደለም፤ ስህተት አይሰራም ማለት አልችልም” ያሉትን እንኳ ለአፍታ አስታውሶ፣ ከፕሮፓጋንዳው ሊታረም ቀርቶ ሊሽኮረመም አልፈለገም፡፡

ለዚህም ነው፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያምን ጨምሮ የተለያዩ የመንግሥትና የኢህአዴግ ወፍራም ባለሥልጣናት ሳይቀሩ፣ በተገኘው አጋጣሚ የአቶ መለስን ራዕይ አስፈፃሚ ስለመሆናቸው በተደጋጋሚ ሲናዘዙና ቃል ሲመዙ የሚታየው፡፡ በርግጥ፣ እንደ አቶ ስብሃት ነጋ ያሉት ነባር የህወሓት ታጋይ፣ “የኢህአዴግ እንጂ፣ የመለስ ራዕይ የሚባል የለም” በማለት የአሠላለፍ ለውጥ የሚያደርጉበት አጋጣሚ እንዳለ መዘንጋት አይቻልም፡፡ አቶ መለስ ለአፍታ ሕይወት ዘርተው እየሆነ ያለውን ቢያዩ ሊበሣጩ ሁሉ እንደሚችሉ የሚመሰክሩላቸው የቅርብ ወዳጆች ያሏቸው መሆኑ ይነገራል፡፡ ባለቤታቸው ወ/ሮ አዜብም “መለስ የታይታ ነገር አይወድም፤ ለህዝብ ያደረገውን እንዲነገር አይፈልግም፤ ህዝብ እንጂ ግለሰብ ታሪክ አይሰራም የሚል አቋም ያለው…ለህዝብ የተሰዋ ጀግና…” በማለት ግለሰባዊ አምልኮን እንደሚቃወሙ አሥረድተዋል፡፡

የሚገርመው ግን፣ የኢህአዴግም በሉ የመንግሥት ተጠሪዎች ከአቶ መለስ አቋም ጋር እልህ የተጋቡ ይመስል፣ ሁሉንም ድርጅታዊና መንግስታዊ ሥራዎች በአቶ መለስ ስም መጥራት ወይም የእርሳቸው መታሰቢያ ማድረግ ወይም እርሳቸው አቅድውት እንደነበር መመስከር አልያም የእርሳቸው ራዕይ እንደሆነ ማስነገሩን አሁንም ቀጥለውበታል። እንደተባለው ከአቋማቸው ጋር እልህ ካልተጋቡ በቀር፣ እንዴት በአንደበታቸው እንደተናገሩት፣ በኋላም በመጽሐፍ መልክ እንደታተመ የሚታወቀውን አቋማቸውን ተመልክተው፣ እንደ አቶ ስብሃት ነጋ የፕሮፖጋንዳ ሥልቱን መቀየር ተሣናቸው? ብሎ መጠየቅ ይቻላል፡፡ የመንግስትም በሉ የኢህአዴግ ፕሮፖጋንዳን የሚያሠራጩ፣ በአቶ መለስ ስም ምለው የሚያድሩ ካድሬዎች ባይሰሙትም ወይም ባያነቡትም፣ አቶ መለስ ግን፣ “የአፍሪካ ውድቀት ሁሌም የግለሰቦች አምልኮ ነው፡፡ ስሞቻቸውም ሁሌ በመ ፊደል ዘር የሚጀምር ይመስላል፡፡ በዚህ ረገድ ሞቡቱ እና መንግሥቱ ነበሩን፡፡ መለስን ከዚህ ዝርዝር ውስጥ ማስገባት አልፈልግም” ከማለት ያገዳቸው አልነበረም፤ ሊያግዷቸውም አይችሉም፡፡ ለነገሩ አርቆ የሚያስብ የመንግስትም በሉት የድርጅቱ ብልህ ካድሬ ካለ፣ የአፍሪካ ሀገራትን ሁሉ እያጠፋ እንዳለ በማስረጃ አስደግፈው የተቃወሙት “የግለሰብ አምልኮን አሸባሪነት” ለማጥናት ይነቃ ነበረ። የግለሰቦችን ራዕይ በእውቀትና በእውነት መዝኖ ለሀገር ጥቅም ማዋል የሚሻ የበሰለ የፖለቲካ ተንታኝ ካለ ደግሞ፣ “የአፍሪካ ውድቀት ሁሌም የግለሰቦች አምልኮ ነው” ያሉት ተጠየቂያዊ ሃሳብ፣ “የአቶ መለስ ራዕይ” ብሎ ሊያስተጋባው፣ ሊያስተነትነው ይችል ነበረ፡፡ ለነገሩ አሁንም ጊዜ አለ!

Page 11 of 19