አድዋ ላይ ከወደቁት ጀግኖች ኢትዮጵያውያን አንዱ የሆኑት ፊታውራሪ ገበየሁ፤ “ጠላትን ስሸሽ ከሞትኩኝ አስከሬኔን እዚያው ቅበሩ፤ ጠላትን ፊት ለፊት ተጋፍጬ ከሞትኩ ግን አስከሬኔን በሀገሬ ይቅበሩልኝ” ሲሉ አፄ ምኒልክን ቃል አስገብተዋቸው ነበር፡፡ የአድዋ ጦርነት ተጀመረ፡፡ ባልቻም እያዋጉ ጠላት ያለበት ድረስ በድፍረት ዘለቁ፡፡ ጠላት አናታቸውን በጥይት ሲነድል የፊት ጥርሳቸው ረግፎ በክብር ለአገራቸው ነፃነት ወደቁ፡፡ በሕይወት እያሉ-
“የአድዋ ሥላሴን ጠላት አረከሰው
ገበየሁ በሞቴ ግባና ቀድሰው” የተባለላቸው ገበየሁ፤ አድዋ ሥላሴ ተቀብረው ከቆዩ በኋላ አፅማቸው ወደ አምባላጌ ጊዮርጊስ ተወሰደ፡፡ በቃል ኪዳናቸው መሠረት ከሰባት ዓመት በኋላም አጽሙ በአገራቸው በአንጎለላ ኪዳነምሕረት አረፈ፡፡ አሁን የፊታውራሪ ገበየሁ አጽም፤ አቶ አብርሃም ደምሴ በተባሉ ግለሰብ በመስታወት ውስጥ እንዲቀመጥ ቢደረግም ጉስቁልቁል ብሎ ይታያል፡፡
ከቤተክርስትያኑ በአጭር ርቀት ደግሞ በባቄላና ስንዴ ማሳ መሃል፣ የአያትየው ሳሕለ ሥላሴ ቤተመንግስት ፍራሽ ይታያል፡፡ የፍራሹ ምድር ቤት ግን አሁንም አለ፤ ቢጎሳቆልም፡፡ አጠገቡ የብዙዎችን ቀልብ የሳበውና ሳሕለሥላሴ ጠጅ እያጠጡ አሳደጉት የተባለ መንታ የሾላ ዛፍም አለ። በአንጎለላ ኪዳነምሕረት ቤተክርስትያን ውስጥ ጥንታዊ የቤተክርስትያን መገልገያ ቁሳቁስ፣ የተለያዩ የድሮ አልባሳት፣ የብራና መጻሕፍትና የምኒልክ ዳግማዊ የወርቅ ዘውድ ተቀምጠዋል፡፡ በቦታው የምኒልክ ሐውልት ቆሞ ጤና ጣቢያ ቢቋቋምበትም ጃንሆይ ምኒልክ ተወለዱባት የተባለችው ቤት፣አሁን ሣር የበቀለባት የድንጋይ ቁልል ሆናለች፡፡ ቦታው የቤተመዘክር (ሙዚየም) ያለህ የሚል ይመስላል፡፡
ቅርሳቅርሶች በግለሰቦች ቤትና በቤተክርስትያኒቱ ዕቃ ቤት ውስጥ የሚገኙ ሲሆን የቅርስ ምዝገባ አልተካሄደባቸውም፡፡ ለምን ቅርሶቹ እንዳልተመዘገቡ የተጠየቁ አንድ የአካባቢው ቤተክርስትያን አስጎብኚ “ከተመዘገበ ይጠፋብናል” ብለዋል፡፡ ትኩረታችን እኒህ ስለሆኑ ነው እንጂ በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ሰሜን ሸዋ ዞን፣ በእያንዳንዱ ኪሎ ሜትር በርካታ ቅርሶች አሉ፡፡ ባሉበት መጠበቅ አሊያም በቤተመዘክር መቀመጥ ይገባቸዋል፡፡ በየቤተክርስትያኑ እና በየግለሰቡ ቤት መቀመጣቸው በቀላሉ ለብልሽትና ለመጥፋት ይዳርጋቸዋል፡፡
በመካከለኛው ዘመን የኢትዮጵያ ታሪክ፣ታዋቂ የሙስሊም ሥልጣኔ መገለጫ የሆነውና በሱልጣን ይተዳደር የነበረው ይፋት የሚገኘውም በዚሁ ዞን ሲሆን ታሪካዊ መስጊዶች የጠባቂ ያለህ እያሉ ነው። ጥበቃና እንክብካቤ ሲኖር እኮ ነው ጐብኒዎችን መማረክ የሚቻለው፡፡
ዞኑ ከ “ሐገሬ ሚዲያና ኮሙኒኬሽን” ጋር በመተባበር፣በአካባቢው ያሉ ታሪካዊ መስሕቦችንና ሰው ሰራሽ ቅርሶችን የሚያስተዋውቅ “የሰሜን ሸዋ ዞን የቱሪዝም ማውጫ” ያሳተመው ጎብኚዎችን ለመሳብ አስቦ ነው፡፡ በዞኑ የሚገኝ እያንዳንዱ ወረዳ ያለውን መስሕብ በማውጫው ላይ የማስተዋወቅ እድል ተሰጥቶታል፡፡ ባለፈው ቅዳሜ የቱሪዝም ማውጫው የባሕልና ቱሪዝም ሚኒስትር ዲኤታ አቶ ሙሉጌታ ሰኢድ በተገኙበት ሲመረቅ፤ ትኩረቱ የውጭ ሀገር ቱሪስቶች ላይ እንደሚሆን ተገልጿል፡፡ ችግሩ ግን የቱሪዝም ማውጫው የታተመው በአማርኛ ብቻ ነው፡፡ ማውጫው በባለቀም ፎቶግራፎች ደምቆ ደረጃውን በጠበቀ ወረቀት ቢታተምም አንዳንዶቹ ፎቶግራፎች መግለጫ (Caption) የላቸውም፡፡ በማውጫው ውስጥ ከተጠቀሱ በርካታ መስሕቦች መካከል በአራተኛው ክፍለ ዘመን የተሠራው ኦፍና አማኑኤል ቤተክርስቲያን፣ አስከሬን የማይበሰብስበት የመልከጼዴቅ ገዳም፣ የለበቃ ኢየሱስ ፍልውሃ፣ የኢትዮጵያ አርበኞች ማሕበር የተመሠረተባት ግራር፣ በነቢዩ መሐመድ ጊዜ እንደተገነባ የሚነገርለት ሸዋ ሮቢት አካባቢ የሚገኘው የጐዜ መስጊድ፣ “የወፍ ዋሻ” የተፈጥሮ ደን፣ የሣህለሥላሴ ቤተመንግስት ፍርስራሽ፣ “ስድስት” መስጊድ፣ አሸም አገር መስጊድ፣ መገዘዝ ተራራ፣ ሊቅ ማረፊያ፣ አንኮበር ቤተመንግስት፣ ልበሊት ኢየሱስ ገዳም፣ የልቼ ከተማ ፍርስራሽ፣ የደብረሲና ዋሻ እና ከፍልፍል አለት የተሰራው ደብረ ከርቤ ዳግማዊት ጐልጐታ ገዳም ይገኙበታል፡፡
ለአዲስ አበባ ቅርብ የሆነው ሰሜን ሸዋ፤ በርካታ መስህቦች ቢኖሩትም ከቱሪዝም እምብዛም አልተጠቀመም፡፡ በተለይ ደግሞ ከውጭ አገር ቱሪስቶች፡፡ “ቱሪዝምን ለነጮች ብቻ ካደረግን ዶላር ናፋቂ ሆነን መቅረታችን ነው” የሚለው ባላገሩ አስጐብኚ ድርጅት፤ በሀገር ውስጥ ቱሪስቶች ላይ በማተኮር እንደሚሰራ በቱሪዝም ማውጫ ምረቃው ላይ የድርጅቱ ሥራ አስኪያጅ ተናግረዋል፡፡
የዳግማዊ ምኒልክ፣ የአቡነ ተክለሃይማኖት፣ እግዚአብሔርን እና ሰይጣንን ለማስታረቅ የሞከረችው ቅድስት ክርስቶስ ሰምራ፣ የአማርኛ ፊደል ገበታ በስፋት በማሰራጨት የሚታወቁት ተስፋ ገብረሥላሴ ዘብሔረ ቡልጋ እና የሌሎችም ታዋቂ ኢትዮጵያውያን የትውልድ ስፍራ የሆነችው ሰሜን ሸዋ፤ በርካታ መስሕቦች ይኑሯት እንጂ በቂ በጀት እና በቱሪዝም መስክ የሰለጠነ በቂ ባለሙያ የላትም፡፡ በደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ ጥናት መሠረት፤ ከሁለት ሚሊዬን በላይ ሕዝብ ያላት ሰሜን ሸዋ፤ በቱሪዝም ከፍተኛ ትምህርታቸውን ያጠናቀቁ ሦስት ባለሙያዎች ብቻ ናቸው ያሏት፡፡
ሰሜን ሸዋ ቱሪስቶችን ለመሳብ የምትሻ ከሆነ ቤተመዘክሮች መሥራትና ቅርስ መሰብሰብ፣ ስርቆሽና ዘረፋን መከላከል፣ በባለሙያ መደርጀት፣ ሆቴሎችና መንገዶችን ማሟላት እንዲሁም በቂ መረጃ መስጠት እንደሚጠበቅባት በቱሪዝም ማውጫው ምርቃት ላይ የተገኙ አስተያየት ሰጪዎች ተናግረዋል፡፡

Published in ህብረተሰብ

ለምሑራኑ እና ለጸሐፊዎች በጭራሽ ሊገቡ ያልቻሉ የኢትዮጵያ ውርስና ቅርሶች አሉ ከተባለ የዘመን መቁጠሪያው አንዱ መሆን አለበት፡፡ በ1990ዎቹና ከ2000 ዓ.ም ወዲህ ብቻ አሥር የሚጠጉ ጽሑፎች በመጽሐፍና በድረ ገጽ ቀርበውበታል፡፡ ይህንኑ በቀጥታ የሚመለከቱ የምርምርና ጥናት ሥራዎች፣ ዓውደ ጥናቶችና ዓውደ ርዕይ ቀርበውበታል፡፡
የትኞቹም ግን ያላንዳች ጉድለት አያቀርቡትም። ምን ያህል በሚገባ እና በትክክል ገልፀውታል በማለት የሚሻለውን እንመርጥ ይሆናል እንጂ አንዳቸውም ያላንዳች እንከን ፈጽመውታል አንልም፡፡ (የዘመን መቁጠሪያው መምሕር የሆኑትን ያሬድ ፈንታ ያሳተሙትን አይመለከትም፡፡)
ብዙዎቹ እንደ ትልቅና ጠቃሚ ሥራ ከሚቆጥሩት የፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ መጽሐፍ ጀምሮ እስከ ፕሮፌሰር ኤፍሬም ይስሃቅ ጥናታዊ ወረቀት ድረስ ስለመቁጠሪያው ስያሜ፣ ማንነት፣ ስለዓይነቱ፣ ስለታሪኩ የሚገለፁትን ያለጥያቄ ምልክት አናልፋቸውም፡፡
ምናልባት ሻል አድርገው ያቀርቡታል በሚባሉትም አንዳንድ ችግሮች ይታዩባቸዋል:: ከቅርቦቹ የህሩይ ስሜን እና የአብርሃም ደሞዝን ሥራዎች አንዳንድ ነጥቦችን ሳንነቅስ አናነብም፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን በሚያቀርባቸው የጥናትና ምርምር ሥራዎች ላይ ንፋስ የማያስገባ መሆኑ ይታወቃል። ይህን መቁጠሪያ በተመለከተው ዓውደ ርእይ ግን ፀሐያዊነቱን የሚነግር ገለጻ ነበር የቀረበው፡፡ የመቁጠሪያው ምንጭም መጽሐፍ ቅዱስ እንደሆነ መግለጹ ሐሳበ ዘመኑ ከልደት በፊት ቢሄድ እስከ ሙሴ ዘመን ድረስ ብቻ ማድረጉን ልብ አላለውም። “ሕገ ሊቃውንት፣ ሕገ ሐዋርያት፣ ሕገ ካህናት፣ ሕገ ነብያት፣ ሕገ አበው…”
እያሉ “ሕግ አዳም፣ ሕገ መላእክትና ሕገ አምላክ” ብለው የሚገልጹት በመጽሐፍ ቅዱስ ዕድሜ ብቻ ከመወሰናቸው ጋር ይጣላል፡፡ በሌላ በኩል “የራሷ መቁጠሪያ ያላት” እያሉ የጁልያን፣ የአሌግዛንድርያን የሚሉ በራሪ ጽሑፎችንና ፀሐፊዎችን እንዲሁም ጋዜጠኞችንም አይተናል፡፡
አንዳንዱ ደግሞ በቅንነት፣ የጠቀምኩ መስሎት፣ ስለ ቀን መቁጠሪያው የተለየ ግንዛቤ የሚያስይዝ ጽሑፍ ያቀርባል፡፡ የዶክተር አበራ ሞላ የድረ ገጽ ጽሑፍ ከነዚህ መካከል ሊጠቀስ ይችላል፡፡ የዘመን መቁጠሪያውን የታሪክ ዘመን ያራቁት መስሏቸው ከጥንታዊው ግብጽ ጋር የሚመሳሰልበትን ለማሳየት ሞክረዋል፡፡አሁን ደግሞ (ይህን ለመጻፍ ምክንያት የሆነና) በጭራሽ ስለ ኢትዮጵያው ዘመን መቁጠሪያው ነው ለማለት የሚከብድ የምርምርና የጥናት ሥራ ቀርቧል፡፡ “ጳጉሜ ፮” የተባለ መጽሐፍ፡፡
መጽሐፉ፤ “የኢትዮጵያ ቀን መቁጠሪያ የማነው?” ይላል፡፡ ፋሲል ሰይፉ በተባሉ የኢኮኖሚክስ መምሕር የቀረበ ነው፡፡ መምሕሩ ስለቀን መቁጠሪያው ደገኛ ሐሳብን ይዘው ጥናትና ምርምር እንዳደረጉ አያጠያይቅም፡፡ ስለመጽሐፉ ይዘትም ሆነ አንዳንድ ዝርዝሮችን ማቅረብ ሳያስፈልግ፣ በአጠቃላይ የኢትዮጵያ ዘመን መቁጠሪያን፣ ከመቁጠሪያው (ክፍላተ ዘመን ወይም/እና አዕዋዳቱን ዕለት፣ ወርኅና አመት/ዓውደ ወርኅ እና ዓውደ አመትን) ሙሉ በሙሉ ፀሐያዊ እንደሆኑ አድርገው በመያዛቸው ብቻ በ፬ ክፍል/ምዕራፍ ከፍለው ምርምርና ጥናት በማድረግ ያቀረቡት በሙሉ ከንቱ ድካምን የደከሙበት ያህል ይሰማል፡፡ ይህም ሲገለጽ ኃዘንን ብቻ ሳይሆን ቁጭትንም ያመጣብን መሆኑን በማከል ይኾናል፡፡ “ያን ያህል በእጅጉ የለፉበትና አብዝተው የተጠበቡበት ምናለ ዘመን መቁጠሪያውን፣ በተለይም የአመት እና የወሩን አዕዋዳበት በሚገባ መጠን፣ ካልሆነም መሠረታዊ የሆኑትን በማወቅ፣ ያን ወደ መሰለው የምርምርና የጥናት ሥራ ባመሩ ኖሮ…የሚል ነው ቁጭቱ፡፡
በመምሕሩ ዘንድ የኢትዮጵያ ዘመን መቁጠሪያ በአጠቃላይ፣ በዕለታት የሚቆጠሩት አዕዋዳት፣ ዓውደ ወርህ እና ዓውደ አመቱ በተናጠል “ፀሐያዊ” እና “ፀሐያዊ” ብቻ ስለመሆን አለመሆናቸው በጭራሽ ብልጭ ያለ ነገር የለም፡፡ “አመት” እናም ወቅት የሚፈጠሩት ምድር በፀሐይ ዙሪያ በመዞሯ የተነሣ ነው፤ ዕለትም ምድር በራሷ ዛቢያ በመሾሯ የተነሣ ነው” የሚለውን “ሳይንሳዊ” አስተሳሰብ ማን ምን ብሎ ይጠይቃል? ያለቀለትና የታወቀ ጉዳይ ነው፤ ታዲያ የአንድን አመት ጊዜ ምድር በፀሐይቱ ዙሪያ ለመዞር የሚፈጅባት ጠቅላላ የጊዜ መጠን አድርጐ በመያዝ ምርምርና ጥናት ውስጥ አይገባም?...
እርሳቸውም አስቀድሞ ዘመን መቁጠሪያው የጠራ ፀሐያዊ (Purely Solar) መቁጠሪያ በማድረግ የአመትንና የየወራቱንም ርዝማኔዎች በማጥናት ጠለቅ ያለ ምርመራን በማድረግ ደክመዋል፡፡ ስለሐሳበ ዘመኑ የተጻፉ አንዳንድ መጻሕፍትንም በመመልከት ዋቤዎች ቢያደርጓቸውም ድንገት በሐሳባቸው እንዲህ ያለ ጥያቄን ሊያመጡባቸው የሚችሉባቸውን ጥቆማዎች ያላገኙም ይመስላሉ። ሌላው ቀርቶ ከተመለካከቷቸውም ቢሆን (የፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ፣ የኅሩይ ስሜን እና የአብርሃም ጤናው መጽሐፎች እንዲሁም የዶክተር አበራ ሞላን የድረገጽ ጽሑፍ) በሙሉ ቢመለከቷቸው ሳያሳውቋቸው እንደማይቀሩ የሚታሰቡባቸው አንዳንድ ሙያዊ ቃሎችን ከእንግሊዝኛው ራሳቸው እንደ አዲስ ሲተረጉሙና ሲጠቀሙ፣ ደሞም ያለውንና የሚታወቀውን የሐሳበ ዘመኑን ቃል ሌላ ውክልና ሰጥተው ስለሚገኙ ምናልባት እነዚህንም ቢሆን በደንብ አላዩአቸው ይሆን ያሰኛል፡፡
ለምሣሌ፣ “Equinox” የሚለውን በአማርኛ “እኩልታ”፣ “እኩሌ” ፤“Leap year” የሚለውን የ”እመርታ አመት” ሲሏቸው ይገኛሉ፡፡ “ኢኩዊናክስ” በሐሳብ ዘመኑ የማይታወቅ እና ፍቺም ያልተበጀለት አልነበረም፡፡ “ዕሪና፣ ዕሩይ” ተብሎ የሚታወቅ ነው።
“ሊፕ” ወይም “ሊፕ ይር” የሚባሉትም “ሠግር” እና “የሠግር አመት” ተብለው ይታወቃሉ። “ዘንድሮ ጳጉሜ ትሠግራለች” ሲሉም “አንድ ቀን ይጨመርባታል” ማለታቸው ነው፡፡ሌላ ውክልና ከሰጡዋቸው ቃሎች ደግሞ “ዓውደ ፀሐይ” የሚለውን እንጠቅሳለን፡፡ “የዓውደ ፀሐይ አመት” ሲሉ ይገኛሉ፡፡ “የፀሐይ ዓውደ አመት” ለማለት ይመስላል፡፡ “ዓውደ ፀሐይ” ግን በሐሳብ ዘመኑ ራሱን የቻለ አንድ ዓውድ ነው፤ የ28 ዓመት ርዝማኔ ያለው፤ በአመታት ከሚቆጠሩ 4 መሠረታውያን አዕዋዳት አንዱ ነው፡፡ ደግሞም የፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌን የተሳሳተ አገላለጽ ይዘው፤ “አመት በዕለታት ብቻ ሳይሆን በወራትም እንደሚለካ ማወቃችን” የሚለውን ተቀብለው ይጠቀሙበታል፡፡
የሐሳበ ዘመኑ ትምህርት ግን እንዲህ ይላል - “ሰባት አዕዋዳት አሉ፤ ከነዚህ ሦስቱ በዕለታት ይሰፈራሉ፣ ይቆጠራሉ፡፡ እነዚህም ዓውደ ዕለት፣ ዓውደ ወርሀና ዓውደ አመት፤ 4ቱ በአመት ይቆጠራሉ፤ እነዚህ ዓውደ አበቅቴ፣ ዓውደ ፀሐይ፣ ዓውደ ማህተም እና ዓውደ ቀመር” የዓውደ አመት አሐድም (Unit) ዕለት መሆኑን እናያለን፡፡ ሐሳበ ዘመኑ በአሐዶች እንኳ ልዩ ጥንቃቄ የሚያደርግ መሆኑን ጭምር እዚህ ላይ ጠቀስ አድርገን እንመለስ።
እንግዲህ ዓውደ ዓመት የሚባለው ሙሉ በሙሉ ፀሐያዊ እንደሆነ “ዓመት ማለት ምድር በፀሐይ ዙሪያ ለመዞር የሚፈጅባት 365 ከ1/4 ዕለት መሆኑ ይታወቃል” በማለት (ገጽ 4) መነሻቸው ላይ በገለጹት ዘግተውታል፡፡
የኢትዮጵያ ዘመን መቁጠሪያ ዓመት የተባለውን አንድ ዓውድ እንዲህ በተፈጥሮአዊ ዓውድ ርዝማኔ የሚፈታ ስለመሆኑ ቅንጣት ባለመጠራጠር ወይም ይህን ባይፈታም ከዚህ ውጭ የሚሆን ዓመት የለም በማለት ይሆናል፡፡ ይኼ ይቆየንና ለመሆኑ አንድ አመት 365 ¼ኛ ቀን የተባለውስ በየትኛው የፀሐይ አመት ነው? ምድር ለመዞር ይህን ያህል ቀን የሚፈጅባት ከፀሐይ አመቶች በአንደኛው ብቻ እንደሆነ፤ የፀሐይ አመቶችም ቢያንስ ሦስት ዓይነት እንደሆኑ ለምን አልተመለከቷቸውም?
በዘመን መቁጠሪያዎች ዘንድ (ፀሐያዊ በሚባሉት) የተያዙት የፀሐይ አመቶች እንኳ ሁለት ዓይነቶች ናቸው፡፡ ሐሩራዊ የፀሐይ አመት (Tropical Solar year) እና ፈለካዊ የፀሐይ አመት (Sideral Solar year) ይባላሉ፡፡ ዛሬ ላይ ሳይንስ እነዚህን ሁለቱንም ምድር በፀሐይ ዙሪያ ለመዞር የሚፈጅባትን ትክክለኛ ጊዜ እንዳልያዙ በመጠቆም፣ ሌላ ሦስተኛ የፀሐይ አመት አስተዋውቋል “አኖማሊስቲክ ሶላር ይር” የተባለ፡፡
በእርሳቸው 365 ከ1/4ኛ የተባለው የሐሩራዊው ፀሐይ አመትን ርዝማኔ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ይህን የያዙት ቀን መቁጠሪያዎች ደግሞ እነ ግሪጐሪያንና ጁሊያን የመሳሰሉት ናቸው፡፡
ሰዎች ይህ ሐሩራዊ የተባለውን የፀሐይ አመት፣ እያደር ጊዜውን እየዛባው መሄዱን ዓውቀው የተሻለ ፀሐያዊ አመትን የሚይዘበትን ፈልገው፣ ከሺ አመት በፊት “ፈለካዊ” ያልነውን “ሳይድራል ሶላር” አመትን በመያዝ ያንን አርመውት ይገኛሉ፡፡ ፐርሺያዎች ከስንትና ስንት አመት በፊት የተውትን፣ ዛሬ እነ ኢራን የያዙት (ጃለሊ) ፣ አፍጋኒስታንና አንዳንድ የሂንዱ ውላጅ ካላንዴሮች ሁሉ የጣሉትን ሐሩራዊ አመት በመያዝ ነው እንግዲህ “ሳይንሳዊ” ምርምር ውስጥ የገቡት፡፡ “እንዲያው በነገራችን ላይ” ለማለት እንጂ የኢትዮጵያ ሐሳበ ዘመንስ እንዲህ ያለ በተፈጥሮ እንቅስቃሴ ላይ ይህን ያህል የወደቀ ሐሳበዘመንም አይደለም፡፡ እንዲህ ያለ የዘመን ፍቺም የለውም፡፡
“ዘመን ማለት በጊዜ ውስጥ ያለ የተወሰነ ጊዜ ነው፣ ብሎ በማስተማር የሚነሳ ብቸኛው ቀሪ የዘመን መቁጠሪያ ነው፡፡ ይህም ማለት ዓመት ዓውደዓመት፣ ወር (ዓውደ ወርኅ) ቢባል ዕለት በልቁ፣ በኩለንታው፣ በመላው ጊዜ ውስጥ ያሉ የጊዜ ወሰኖች እንጂ፤ “ዓመት ማለት መሬት በፀሐይ ዙሪያ (ተቃራኒውንም ቢሆን)፣ ዕለት በራሷ ዛቢያ እያለ አጉል መጠበብ ውስጥ የሚገባ አይደለም፡፡ እንዲያውም አንጻራዊ ጊዜን/ዘመንን የያዘ፣ እንደነ አልበርት እና ስቴፈን ሆውኪንግ ያሉ የሳይንስ ጭንቅሎዎች በ20ኛው መቶ ክ/ዘመን ከልደት ወዲህ ሊደርሱበት የቻሉትን የጊዜ/ዘመን ፍቺ ከጥንት ጀምሮ ይዞ፣ ተግባራዊ ጥቅም ላይ በሚያውልበት አያያዝ አውርዶ ሲጠቀምበት የኖረ የዘመንና የዓለም ሐሳብ ነው፡፡
ወደ አዕዋዳቱ ስንገባም የኢትዮጵያ ዘመን መቁጠሪያ በዓለም ላይ ካሉት ከአርባ በላይ የሆኑ መጠቀሚያና ሌሎችን ካሌንደሮች (አዳዲስ እየተሰሩ፣ ይህ ይሻለናል እያሉ በየድረገጹ የሚወተውቱትን) ሁሉ በዓይነት ለመክፈል የሚጠቀሙባቸውን ፀሐያዊ፣ ጨረቃዊ፣ ጨረቃ ፀሐያዊ፣ ፀሐይ - ጨረቃዊ እና ጨረቃ ኮከባዊ፣ ወዘተ እያሉ ለመክፈል በሚሞክሩባቸው እንኳ አንድ መግቢያ ቤትን ሊያገኙለት የሚከብድ የቀን መቁጠሪያ ነው፡፡
አንድ ዓውድ እንዴት ሆኖ ነው የፀሐይ፣ የጨረቃ፣ የሚባለው?
ይህን መመለስ ስንችል፣ የኢትዮጵያውስ ብለን በመጠየቅ የዘመን መቁጠሪያው የየትኛው ሰማያዊ ብርሃን እንደሆነ ልናውቅ እንችላለን፡፡ ይህንን ለመበየን ሦስቱን ዋና ዋና ዘመኖች ወይም አዕዋዳት መመልከት ይበቃል፡፡ እነዚህም አመት (ዓውደ አመት)፣ ወርኅ (ዓውደ ወርኅ) እና ዕለት (ዓውደ ዕለት) ናቸው፡፡
የነዚህንም ርዝማኔ በምን ምልክት ምን ያህል እንደሚያደርገው፣ እያንዳንዱም ዓውድ በአደ ቁጥር በየትኛው ምልክትነት እንደሚቆጠር ወይም እንደሚለይ (በስም እየጠራም ቢኾን) መመልከት ይጠይቃል፡፡
በዚኹ መሠረት የኢትዮጵያ ዘመን መቁጠሪያ የፀሐይን፣ የጨረቃንና የከዋክብትን ምልክትነት የሚጠቀም ብቸኛው የምድሪቱ ዘመን መቁጠሪያ እንደኾነ ማግኘት ይቻላል፡፡ እነዚህንም በምን ያህል መጠን ነው የሚጠቀመው የሚለው ደግሞ ሌላው የኢትዮጵያው የዘመን መቁጠሪያ አጠቃቀም የሚያስነሳው ጥያቄ ይሆናል፡፡
ከላይ “ምልክት” እያልን ስንጠራ በከንቱ እንደ ፖለቲከኛ ቃል አፍ ላይ በወደቀው ቃል ለመሙላት ስንል አይደለም፡፡ የኢትዮጵያ ዘመን መቁጠሪያ፤ ምድር ከፀሐይ ወይም “ፀሐይ ከምድር” ጋር በሚያደርጉት ተፈጥሮአዊ ቅንየት ጊዜው ይፈጠራል የሚል ቢኾን ኖሮ የተቀሩትን መቁጠሪያዎች ባለቤቶች የሚያዩትን መከራ እና “የተሻለ” እየተባለ ዐሥሩን መቁጠሪያ ማሰብና መምጣት ጣጣ ውስጥ ባስገባ ነበረ፡፡
ምድር ፀሐይን ለመዞር የሚፈጅባት ጊዜ ሳይንስ በተጠበበ፣ ቴክኖሎጂ በተራቀቀ ቁጥር የተሻለ ልኬት ተደረገ እየተባለ የየዘመኑን፣ የዓውደ ዘመኑን እንደ ዓውደዓመት ያለውን ርዝማኔ ለማስተካከል የመቁጠሪያ ለውጥ ያውም ተጠናቅቀው ላይጠናቀቁት እያወጁ የነበረውን፣ በተለይ ያለፈውን የዘመን ቁጥር እስከማጣት ድረስ የተደረሰበትን መደነጋገርና መሳሳት በፈፀመ ነበር፡፡ ጁሊያን 365.25 ቀን አድርጐታል ተብሎ በግሪጐሪያን 365.2324 ተተካ፡፡
በዚሁ ርዝማኔ ዓውደ አመት ተላክቶ በዖደ ቁጥር ይቆጠር ሲባል፣ ወደኋላ ሄደው ሲቆጥሩ በ10 ቀን ልዩነት የተለያዩ የሼክስፒር እና የሰርቫንቴስ ሞት ዕለት በአንድ ቀን የዋሉ ኾነው ተቆጠሩ፤ (ዛሬ ዩኔስኮ “የመጻሕፍት ቀን” ብሎ የሚጠራው ቀን እነዚህ ሁለት የአውሮፓ ደራሲያን የሞቱበት ቀን ኾኖ በመገኘቱ የተወሰነው ነበር፡፡ ኹለቱ ቀን በአንድ ቀን አልነበሩም የሞቱት::
የእንግሊዙ ልዑል በሕፃንነቱ ዘውድ የተጻፈለት ቀን መቼ እንደሆነ በተሻሻለው መቁጠሪያ ሲቆጥሩት፣ ጭራሽ በእናቱ ማኅፀን ውስጥ ገብተው በልዩ ሥነሥርዓት ዘውድ እንደጻፉለት ተደርጐ የሚታሰብበት ቀን ላይ ዐረፈ፡፡
ያለፈውን በማሳየት ብቻ አይደለም ይህ ዓይነቱ አያያዝ የማያመጣው፣ አሁንም በአንድ ወቅት በተያዘ መረጃ የዓመቱ ርዝመት ይህን ያህል የተባለው ተይዞ በዚያ መሠረት ለመቁጠር ሲቀጥሉ ከአመታት በኋላ ክረምት ይገባል የተባለበት በልግ የሚሆንበት፣ በልግ ነው ሲባል በጋ ሆኖ የሚገኝበት ሆኖ ቁጭ እያለ መከራ ውስጥ መግባት፣ እንደገና ሌላ መለኪያ መቁጠሪያ መፈለግ፡፡
ጳጉሜ 6 “የቀን መቁጠሪያው የማነው?” የሚል ጥያቄንም እንደ ርዕስ ተጠቅሟል፡፡ የኛም ጥያቄ ነው፡፡ያን ያህል የተለፋበት የቀን መቁጠሪያ የማነው? የኢትዮጵያውያንን ቀን መቁጠሪያ እንደማይመለከት በግልጽና በቀጥታ ስንናገር ግን በሀዘን ብቻ ሳይሆን በቁጭትም ጭምር ነው፡፡ ግን ግን ለምንድነው ይሄ ቀን መቁጠሪያ እንዲህ በምሑራኑ ሳይቀር በሚገባ ላይታወቅ የቻለው? ስለርሱ ከተጻፉት ውስጥ አንዳችም ስህተት የሌላቸው ስንቶቹ ይሆኑ?

Published in ህብረተሰብ

ማረሚያ ቤት የተከሳሾችን ህገመንግስታዊ መብት እንዲያከብር ታዘዘ
የከባድ ሙስና ወንጀል ክስ ተመስርቶባቸው ጉዳያቸውን በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 15ኛ ወንጀል ችሎት በመከታተል ላይ የሚገኙት የገቢዎችና ጉምሩክ ተከሳሾች፤ ማረሚያ ቤቱ ከትዳር አጋር እና ከልጆቻችን በስተቀር በወዳጅ ዘመድ እንዲሁም በሃይማኖት አባቶች እንዳንጐበኝ ተከልክለናል ሲሉ ያመለከቱ ሲሆን የማረሚያ ቤቱ አስተዳደር በበኩሉ፤ ለደህንነታቸው ሲባል በሰጡን የጠያቂ ዝርዝር መሠረት እያስተናገድን ነው ብሏል፡፡
ተከሣሾቹ ባለፈው ማክሰኞ በራሳቸው እና በጠበቆቻቸው አማካኝነት ለፍ/ቤቱ ባቀረቡት አቤቱታ፤ የተወሰኑ የጠያቂ ቤተሰቦቻቸውን ዝርዝር እንዲያስመዘግቡ የተደረገ መሆኑን አመልክተው፣ በዝርዝሩ ውስጥ የተካተቱት ቤተሰቦቻቸውም ጭምር በአግባቡ እየተስተናገዱ አለመሆናቸውን አስረድተዋል፡፡
ስለ ጉዳዩ እንዲያስረዱ ችሎቱ እድል የሰጣቸው ተከሳሽ አቶ ማርክነህ አለማየሁ፤ ከወራት በፊት በቁጥጥር ስር ሲውሉ እና ምርመራ ሲደረግባቸው ቤተሰብ ጭምር እንዳይጠይቃቸው መደረጉን አስታውሰው፤ በወቅቱ ክልከላ የተደረገው ከምርመራ ስራ ጋር በተያያዘ እንደሆነ ግንዛቤ በመውሰድ አቤቱታ ከማቅረብ መቆጠባቸውን ተናግረዋል:: ምርመራው ከተጠናቀቀና ክስ ከተመሰረተብን በኋላም ክልከላው መቀጠሉ ግን አግባብ አይደለም ብለዋል:: በተለያዩ ወንጀሎች በተከሰሱትና በማረሚያ ቤቱ ሆነው ጉዳያቸውን በሚከታተሉት ላይ እንዲህ መሰሉ ገደብ አለመኖሩን ያመለከቱት አቶ ማርክነህ፤ በኛ ላይ ግን የጠያቂ ገደብ ተጥሎብናል ሲሉ አስረድተዋል::
የጠያቂ ቤተሰቦቻችሁን ውስን ስም ዝርዝር አስመዝግቡ በተባሉት መሰረት ማስመዝገባቸውን የሚገልጹት አቶ ማርክነህ፤ጠያቂ ቤተሰቦች በአግባቡ የማይስተናገዱ ከመሆኑም በላይ ስም ዝርዝራቸውን ያካተትናቸው የአንዳንዶቻችን ቤተሰቦች፣ በብዙ ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኙ በመሆናቸው ያለጠያቂ ቀርተናል ብለዋል:: ቀደም ሲል የማረሚያ ቤቱ ገደብ ጊዜያዊ ነው፤ ይስተካከላል ተብሎ እንደነበር በመጥቀስም እንደተባለው ለውጥ ባለመኖሩ፣ ፍ/ቤቱ በጉዳዩ ላይ ጠበቅ ያለ ትዕዛዝ ያስተላልፍልን ሲሉ አቶ ማርክነህ ጠይቀዋል::
በተመሳሳይ የኬኬ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ባለቤት የሆኑት የአቶ ከተማ ከበደ ጠበቃ ባቀረቡት አቤቱታ፤ በህጉ መሰረት አንድ ታሳሪ የሃይማኖት አባትን ጨምሮ በቤተሰቦቹና በወዳጅ ዘመዶቹ ያለገደብ የመጎብኘት መብት እንዳለው አመልክተው፣ ጥየቃ በሰዎች መልካም ፍቃደኝነት ላይ ተመስርቶ የሚከናወን እንጂ እገሌ ሊጠይቀኝ ይችላል ተብሎ የሚታሰብ አይደለም፤ ስለዚህ እነ እገሌ ናቸው የሚጠይቁኝ ተብሎ ስም ዝርዝራቸው ሊሰጥ አይገባም ሲሉ ተከራክረዋል:: ደንበኛቸው የደህንንት ስጋት አለብኝ አለማለታቸውንም ጠበቃው አክለው ለችሎቱ አስረድተዋል::
ከተከሳሾቹ ጠበቆች ለቀረበው አቤቱታ ምላሽ ለመስጠት ፍ/ቤት የቀረቡት የማረሚያ ቤት አስተዳደር ሃላፊ፤ ውስን ቤተሰቦች ብቻ እንዲጠይቁዋቸው የተደረገው ታራሚዎቹ እራሳቸው ደህንነታችን መጠበቅ አለበት በማለታቸው ነው ብለዋል:: ማረሚያ ቤቱ የታራሚዎችን ደህንነት መጠበቅ አለበት ያሉት ሃላፊው፤ ለዚህም ሲባል የጠያቂዎች ስም ዝርዝር አሰራርን መተግበር እንዳስፈለገ አስረድተዋል:: በጥየቃ ሥርዓቱ ላይ የሚፈጠሩ ቅሬታዎችን ለመፍታትም በየ15 ቀኑ ከጠያቂ ቤተሰቦች ጋር ውይይት እንደሚደረግ ጨምረው ገልጸዋል::
ችሎቱ በእለቱ በዋናነት አቶ መላኩ ፈንታ እና አቶ ገ/ዋህድ ወ/ጊዮርጊስ አንደኛና ሁለተኛ ተከሳሽ ሆነው የቀረቡባቸው ሶስት መዝገቦች ጉዳይ ተመልክቶ የተለያዩ ትዕዛዞችን አስተላልፏል::
ቀደም ሲል በዋለው ችሎት፤ አቃቤ ህግ የማስረጃ ዝርዝር ሰነዶችን ለተከሳሾች እንዲያቀርብ እንዲሁም በመዝገቦቹ በተከሳሽነት ተጠቅሰው ፍርድ ቤት ያልቀረቡ ግለሰቦች እንዲቀርቡ መታዘዙ ይታወሳል:: በዚህ መሰረት አቃቤ ህግ ሰነዶቹን አያይዞ ያቀረበ ሲሆን በሰነዶቹ ላይ ከአንዳንድ ጠበቆች ቅሬታ ቀርቧል:: ሰነዶቹ የተሟሉ አይደሉም ከሚለው ቅሬታ ባሻገር፣ ማስረጃዎቹ በደፈናው ተጠቃልለው የቀረቡ ናቸው፣ ለተከሳሹ ይህ ነው የተገኘብህ ማስረጃ ተብሎ የቀረበ ባለመኖሩም፣ ለመከራከር አመቺ አይደለም ብለዋል - ጠበቆቹ:: በጉዳዩ ላይ ፍ/ቤቱ በሰጠው ብይን፣ ችሎቱ አሁን ባለበት ደረጃ የማስረጃውን ዝርዝር ጉዳይ የማየት ስልጣን እንደሌለው ገልጿል::
ኮሚሽኑ በታዘዘው መሰረት፤ በሁለተኛው መዝገብ ስር ተከሳሽ ከሆኑት ግለሰቦች መካከል ፍርድ ቤት እስከቀረቡበት እለት በገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን የዋና ዳይሬክተሩ አማካሪ አቶ አመሃ አባይ፣ በባለስልጣኑ የሃገር ውስጥ ታክስ ክትትል ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ግርማ ታፈሰ፣ በባለስልጣኑ የዋና ዳይሬክተሩ ፅ/ቤት ሃላፊ አቶ ነብዩ ሳሙኤል፣ በባለስልጣኑ የህግ ማስከበር የስራ ሂደት አስተባባሪ አቶ ሙሉጌታ ባልቻ፣ በባለስልጣኑ የአዳማ ቅርንጫፍ የገቢ ሂሣቦች ቡድን አስተባባሪ ወ/ሮ ሃይማኖት አለሙ እንዲሁም በግል ሥራ የሚተዳደሩት አቶ ተስፋዬ ቤተ እና መተዳደሪያ ስራ እንደሌላቸው ያመለከቱት አቶ ደሜ አበራ በፍርድ ቤት መጥሪያ አቅርቧል:: በእለቱ ለቀረቡት ተከሳሾች በዚሁ መዝገብ የተከሰሱት ባለስልጣናት ባቋቋሙት ህገወጥ ኮሚቴ ውስጥ አባል በመሆን ከተለያዩ ኩባንያዎች ይፈለግ የነበረ ግብርና ታክስ በተገቢው መልኩ እንዳይሰበሰብ በማድረግ፤ የመንግሥትን ሥራ በማያመች አኳኋን መምራት የሙስና ወንጀል መከሰሳቸው ተመልክቷል::
በእለቱ ተከሳሾቹ ክሳቸውን ካደመጡ በኋላ ስለ ጠበቃ እና የዋስትና ጉዳይ ለጽ/ቤቱ ያመለከቱ ሲሆን አብዛኞቹ መከሰሳቸውን በሚዲያ ሰምተው በገዛ ፍቃዳቸው ወደ ኮሚሽኑ በመሄድ ስለጉዳዩ መጠየቃቸውን እንዲሁም ፍ/ቤት እስከቀረቡበት ሰአት ድረስ በገቢዎችና ጉምሩክ መስሪያ ቤት በስራ ገበታቸው ላይ መሆናቸውን ገልጸው፣ ከዚህ አንፃር እምነት ተጥሎባቸው በዋስ ይለቀቁ ዘንድ ፍ/ቤቱን ጠይቀዋል::
አቃቤ ህግ በበኩሉ፤ ሁሉም ተከሳሾች የተጠቀሰባቸው አንቀጽ ከ10 አመት በላይ የሚያስቀጣ በመሆኑ የዋስትና መብት ጥያቄውን እንደሚቃወም አመልክቷል:: ፍ/ቤቱም በዚህ መዝገብ በሰጠው ትዕዛዝ፤ የተከሳሾችን የዋስትና ጥያቄ ውድቅ በማድረግ ጉዳያቸውን በማረሚያ ቤት ሆነው እንዲከታተሉ አዝዟል:: ከተከሳሾቹ መካከል አቶ ግርማ ታፈሰ፤ ወደ ፍ/ቤት ሲመጡ የመንግስት መኪና ይዘው መምጣታቸውን በማመልከት፣ መኪናውን ለማስረከብ እንዲፈቀድላቸው የጠየቁ ሲሆን ፍ/ቤቱም ጉዳዩን የልደታ ፖሊስ ከተከሳሹ ጋር በመነጋገር እንዲያስፈጽም አሳስቧል:: በሌላ በኩል በእለቱ በ5ኛው መዝገብ ተከሰው በፍ/ቤት መጥሪያ የቀረቡትና ክሳቸው የተነበበላቸው አቶ አውግቸው ክብረት፣ የዋስ መብታቸው ተከብሮላቸው በ15 ሺህ ብር ዋስ እንዲለቀቁ ተደርጓል:: ረቡዕ ቀጥሎ በዋለው ችሎት፣ የቀሪ 3 መዝገቦች ማለትም ሶስት ሰዎች የተካተተበት በእነ ጌታሁን ቱጂ፣ አምስት ሰዎች የተከሰሱበት በእነ ዳዊት ኢትዮጵያ መዝገብ እንዲሁም በተናጥል ክስ የቀረበባቸውን የባለሃብቱ አቶ ምህረተአብ አብርሃ ጉዳይ ተመልክቷል::
በፍ/ቤቱ ትዕዛዝ መሰረት፣ በባለስልጣኑ የታክስና ኦዲት የሥራ ሂደት አስተባባሪ የነበሩት አቶ ቶሌራ ዳንጌ በቀረበላቸው ጥሪ ተገኝተው የቀረበባቸው ክስ በንባብ ተሰምቷል:: ተከሳሹ የቀረበባቸው ክስ በመዝገቡ 1ኛ ተጠሪ ከሆኑት ከአቶ ጌታሁን ቱጂ ጋር በመሆን አቶ አደም ሃሰን ሳዲቅ የተባለ አስመጪ ከሰኔ 2002 እስከ ሚያዚያ 2003ዓ.ም ድረስ 1780 ካርቶን የቲማቲም ስልስና 2180 ካርቶን ብስኩት ከቀረጥና ከታክስ ነፃ እንዲያስገባ በማድረግ፣ መንግስትን ከ423 ሺህ ብር በላይ አሳጥተዋል የሚል ነው::
በእነ ዳዊት ኢትዮጵያ መዝገብ ደግሞ በተመሳሳይ በዕለቱ ፍ/ቤት የቀረቡት አቶ ዘሱ ወ/ጊዮርጊስ የላጋር ጉምሩክ ኦፕሬሽን ክፍል ሃላፊ እና አቶ ኢዮብ ጌታቸው በባለስልጣኑ የላጋር ጉምሩከ የጉምሩክ መቆጣጠሪያ ዋና ሃላፊ፣ በመዝገቡ ከተከሰሱ ሌሎች ተከሳሾች ጋር በመሆን አዳሽ አብድራህማን የተባለች አስመጪ ያስመጣችው አልባሳት በፍተሻ ከተያዘ በኋላ ተወርሶ ለመንግስት ገቢ መደረግ ሲገባው፣ ህጋዊ ነው በማለት አሳልፈዋል፣ በዚህም በመንግስት ጥቅም ላይ ጉዳት አድርሰዋል የሚል ነው::
ተከሳሾቹ በእለቱ የተለያዩ ምክንያቶችን አቅርበው የዋስትና መብታቸው እንዲከበር የጠየቁ ቢሆንም የተከሰሱበት አንቀጽ ከ10 አመት በላይ ሊያስቀጣቸው ስለሚችል በፍ/ቤቱ ውድቅ ተደርጎባቸው፣ ጉዳያቸውን በማረሚያ ቤት ሆነው እንዲከታተሉ ታዟል:: በ3ኛ መዝገብ ከኩባንያቸው ምፋም ትሬዲንግ ጋር በጋራና በተናጥል ክስ የቀረበባቸው አቶ ምህረተአብ አብርሃ፣ ቀረጥ ባለመክፈል መንግስትን ከ3.5 ሚሊዮን ብር በላይ አሳጥተዋል የሚል ክስ የቀረበባቸው ሲሆን ክሱ የፀረ ሙስና ሳይሆን የጉምሩክና ገቢዎች ቢሆንም የኮሚሽኑ አቃቤ ህግ ውክልና ተሰጥቶት ነው ክሱን ያቀረብነው ብሏል:: በዚህ መዝገብ ላይ ብይን ለመስጠትም ፍ/ቤቱ ጉዳዩን ለጥቅምት 28 ቀጥሯል::
ፍ/ቤቱ ማክሰኞ እለት በተመለከታቸው አንደኛ፣ ሁለተኛ እና ሶስተኛ መዝገቦች ላይ የተለያዩ ትዕዛዞችን ያስተላለፈ ሲሆን ክስ ተመስርቶባቸው ያልቀረቡ ተከሳሾች በቀጣይ ቀጠሮ አፈላልጎ እንዲያቀርብ፣የተከሳሾች ህገመንግስታዊ መብት በተሟላ መልኩ እንዲከበር፣ማረሚያ ቤትም ይህን በተሟላ መልኩ እንዲያከብር እንዲሁም በመዝገብ ቁጥር 141354 ባስተላለፈው ትእዛዝ መተማመኛ ፈርመው ያልቀረቡ ታስረው እንዲቀርቡ፣ መጥሪያ ያልደረሳቸው ደርሷቸው እንዲቀርቡ፣ ጠበቃ ያላቀረቡ ከጠበቆቻቸው ጋር እንዲቀርቡ፣ በተመሳሳይ በመዝገብ ቁጥር ር141352 ያልቀረቡ ተከሳሾች በቀጣይ ቀጠሮ እንዲቀርቡ በማለት ሂደቱ የሚታይበትን አግባብ ለመወሰን ሶስቱንም መዝገቦች ለጥቅምት 25 ቀን 2006ዓ.ም ቀጥሯል::
በሌላ በኩል የእነ አቶ ጌታሁን ቱጂን መዝገብ ለጥቅምት 28 እንዲሁም የእነ ዳዊት ኢትዮጵያን መዝገብ ለህዳር 3 ቀጥሯል::

                  የመንግሥት ተቋማት አገልግሎት አሰጣጥን በተመለከተ ተደጋጋሚ የነዋሪዎች እሮሮዎችና አቤቱታዎች ሲስተጋቡ የቆዩ ሲሆን መንግስት የአገልግሎት አሰጣጡን ለማቀላጠፍ፣ የስነምግባር ጉድለቶችን ለማሻሻል የተለያዩ እርምጃዎች መውሰዱ ይታወቃል፡፡ ሆኖም ግን አሁንም ችግሮቹ እንዳልተፈቱ ብዙዎች ይናገራሉ፡፡ ባለፈው ሰሞን የማህበራዊ ጥናት መድረክ “የህዝብ አገልግሎት አሰጣጥ ስነምግባርና ተጠያቂነት” በሚል ርዕስ በግዮን ሆቴል ዎርክሾፕ አዘጋጅቶ ነበር፡፡ በዎርክሾፑ ላይም የቀድሞ ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽነርና አሁን በግል አማካሪነት የሚሰሩት አቶ አትክልት አሰፋ እና የቀድሞ ሲቪል ሰርቪስ ጀነራል ዳይሬክተርና አሁን በግል ስራ ላይ የተሰማሩት የህግ ባለሙያ አቶ መስፍን ታፈሰ እንዲሁም የማህበራዊ ጥናት መድረክ ስራ አስፈፃሚ ዳይሬክተር፣ ዶክተር ምህረት አየነው የቀረበውን ፅሁፍ የሚተች ዳሰሳ አቅርበዋል፡፡
ኢትዮጵያ አስራ አራት የመንግሥት አገልግሎት ማሻሻያ ፕሮግራም እንዳላትና ሁሉም ፕሮግራሞች አገር በቀል እንደሆኑ የገለፁት አቶ አትክልት አሰፋ፤ ዋናው ፕሮግራም የመንግስት አገልግሎት (ሲቪል ሰርቪስ) ማሻሻያ እንደሆነ አስረድተዋል። በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ ለውጥ ለማምጣት የሚያስችሉ ተቋማት መቋቋማቸውን፤ የተለያዩ የህግ ማእቀፎችም መዘጋጀታቸውን አቶ አትክልት ጠቁመዋል፡፡ ችግሮች ቢኖሩም ትልቅ ለውጥ መታየቱን የተናገሩት አቶ አትክልት፤ የሙስናውም ደረጃ በንፅፅር ሲታይ በዝቅተኛ ደረጃ ላይ መሆኑን ጠቁመው፤ በተለያዩ የአገልግሎት ዘርፎች የሚስተዋሉ የስነምግባር ጉድለቶች እና ግድፈቶችን ዘርዝረዋል፡፡
በመጀመሪያ የተዳሰሰው የትምህርት ዘርፍ ሲሆን በፈተና እና በውጤት አሰጣጥ ላይ የሚፈፀሙ ማጭበርበሮች፣ ጉቦ መቀበል፣ የሀሰት ትራንስክሪፕትና ሰርተፊኬት መስጠት፣ የመምህራንን እድገት እና ዝውውር ከጥቅም ጋር ማያያዝ፣ ሴት ተማሪዎችን ለወሲብ ማስገደድና የመምህራን ለግል ስራ ቅድሚያ መስጠት እንዲሁም በስራ ገበታ ላይ አለመገኘት የሥነምግባር ጉድለቶች ተብለው ተጠቅሰዋል፡፡ በጤና ዘርፍ ደግሞ ለኤክስሬይ እና ለቀዶ ጥገና አገልግሎቶች ጉቦ መጠየቅ፣ የሆስፒታል አልጋ በጉቦ ወይም በዝምድና እንዲሰጥ ማድረግ፣ ለታካሚዎች ተገቢውን እንክብካቤ ያለማድረግ፣ የባለሙያ የብቃት ማነስ፣ የመድሀኒት እና የአምቡላንስ አቅርቦት ያለመኖር፣ አላስፈላጊ ምርመራዎችን በማዘዝ ታካሚዎችን ላላአስፈላጊ ወጪ መዳረግ፣ ታካሚዎችን ወደ ግል ፋርማሲ እና ክሊኒኮች መላክ፣ ተቆጣጣሪን በጉቦ መደለል እና የማጭበርበር ድርጊት መፈፀም፣ መገልገያ ቁሳቁሶችን መስረቅ እና ፈንድ ያለ አግባብ መጠቀም እንደ ጉድለት ቀርበዋል፡፡
አቶ አትክልት፤ ፍርድ ቤቶች፣ አቃቤ ህጎችና ፖሊስ ዘንድ ይፈፀማሉ ያሏቸውን የስነምግባር ጉድለቶችም በዳሰሳቸው ዘርዝረዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል፡- ፍርድ ቤቶች እና አቃቤ ህጎች ውሳኔን ለማስቀረት ወይም ለመጀመር ጉቦ መጠየቅ ወይም መቀበል፣ የአቃቤ ህጎች ስልጣናቸውን በመጠቀም ክሶችን መግደል ወይም ነፍስ እንዲዘሩ ማድረግ፣ ክስን በአግባቡ ያለመያዝና በፍትህ አስተዳደሩ ላይ የሚታዩ መጓተቶች፣ የብቃት ማነስ እና ጉቦ በመቀበል ክስን ማቅለል… የሚሉት ይገኙባቸዋል። የፖሊሶችን የስነ ምግባር ጉድለቶች ሲጠቅሱም፤ እስረኞችን በአግባቡ ያለመያዝ፣ የትራፊክ ፖሊሶች ህገወጥ ሾፌሮችን በጉቦ ማሳለፍ እንዲሁም በፀጥታ ጥበቃ ላይ የተሰማሩ ፖሊሶች በጥፋት መጠየቅ ያለባቸውን በጥቅም በመደለል አለመጠየቅ፣ ማስረጃዎችን ለማድበስበስ ምስክሮችን እንዳይቀርቡ ማድረግ… የሚሉትን ዘርዝረዋል፡፡
በንግድና ኢንቨስትመንት ከሚስተዋሉ የስነምግባር ጉድለቶች ውስጥም ህገወጥ ፈቃድ መስጠት፤ በህገ ወጥ፣ ደረጃቸውን ባልጠበቁና ጥራታቸው በተጓደለ ምርቶች ላይ የሚደረግ ክትትልና ቁጥጥር የይስሙላ መሆን፣ የሸቀጦች እጥረት ላይ የሚደረግ ቁጥጥር ማነስ የተጋነነ የዋጋ ማሻቀብ እና የውድድር መንፈስን በሚቃረኑ እና ከእውነት በራቁ የሸቀጦች ማስታወቂያ ላይ የሚደረጉ ቁጥጥሮች ማነስ በጥናቱ ላይ ተጠቅሰዋል፡፡
ከመሬት ጋር በተያያዘ የሚፈፀሙ የስነምግባር ጉድለቶችን በተመለከተ ደግሞ በቤት ልማት ላይ የተሰማሩ ባለሀብቶችን በቦታ አሰጣጥ ላይ በእኩል አይን አለማየት፣ የተጭበረበሩ የመሬት ባለቤትነት ሰርተፊኬትና ሰነድ አዘጋጅቶ መስጠት የሚሉት በዋናነት የስነምግባር ጉድለቶች ተብለው ተቀምጠዋል፡፡
የመንግስት ቤቶችን አስመልክቶም፤ ቤት ያለጨረታ ማከራየት፣ በኪራይ አሰባሰብ ላይ የብቃት ማነስና መዘግየት፣ በህገወጥ መንገድ ቤት በያዙና በተከራይ አከራይ ጉዳይ ላይ የክትትል ማነስ፣ ከህግና ደንብ ውጭ መስራት፣ በኪራይ ተመን ላይ ወጥ ያለመሆን እና የተቀናጀ የመረጃ ዘዴ ያለመኖር… የተጠቀሱ ሲሆን፤ በአገልግሎት ዘርፍም የእቃ ግዢና አቅርቦት ችግር፣ ተደጋጋሚ የመብራት እና የውሀ መጥፋት፣ የዘገየ የስልክ ጥገና እና ቀርፋፋ የኢንተርኔት አገልግሎት ጉድለት ተብለው ተዘርዝረዋል፡፡
የኮንስትራክሽን ዘርፉም ከስነምግባር ጉድለቶች አላመለጠም - በአቶ አትክልት ዳሰሳ መሰረት፡፡ ግንባታዎችን ማጓተት፣ ጥራቱን ያልጠበቀ ግንባታ መቀበል፣ የዋጋ መዛባት፣ በኮንትራክተሮች እና በሱፐርቫይዘሮች መካከል የሚደረግ መመሳጠር፣ ላልቀረቡ እቃዎች ክፍያ መፈፀም፣ ብክነት፣ ስርቆት እና አግባብ ባልሆነ መንገድ ተጫራቾችን መለየት የሚሉ ይገኙበታል፡፡
የቤቶች ልማት ፕሮጀክት ላይ የሚታዩ የሥነምግባር ጉድለቶችን የዳሰሱት አቶ አትክልት፤ ህግን ባልተከተለ መንገድ ያለ እጣ ለነዋሪዎች ቤት መስጠት፣ ባልና ሚስትን የሁለት ቤቶች እድል ተጠቃሚ ማድረግ፣ የከተማዋ ነዋሪ ያልሆኑና ያልተመዘገቡ ሰዎችን ተጠቃሚ ማድረግ እና በርክክብ ላይ የሚታይ መዘግየትን ጠቅሰዋል፡፡ ለቀበሌ እና የወረዳ ተመራጮች
የሚሰጣቸው የቅድሚያ የቤት እድል፣ ብቃት የሌላቸውን ሰዎች ለስራ መመልመል፣ የነዋሪነት የቀበሌ መታወቂያና ሰርተፊኬት በጉቦ መስጠት፣ የገንዘብ ብክነት፣ በህገወጥ የቤቶች ግንባታ ላይ ወቅታዊ ቁጥጥር እና እርምጃ ያለመውሰድ እንዲሁም በስብሰባዎች መብዛት ሳቢያ የጊዜ አጠቃቀም ላይ የሚፈጠሩ ችግሮች ተዘርዝረዋል፡፡
ቀደም ሲል በብቃቱና በቅልጥፍናው የሚታወቀው ኢሚግሬሽን፤ በአሁኑ ወቅት ፓስፖርት ለመስጠት ረጅም ጊዜ እንደሚወስድበት የተጠቀሰ ሲሆን መንግስታዊ ባልሆኑ ድርጅቶችና በሲቪል ማህበራት ላይ ጠበቅ ያለ ቁጥጥር እንደማይደረግም አቶ አትክልት በጥናታቸው ገልፀዋል፡፡
በጥናቱ ላይ ትችት ያቀረቡት አቶ መስፍን በበኩላቸው፤ የስነምግባርና የአገልግሎት አሰጣጥ ማሻሻያ ፕሮግራሙ ዲዛይን ከጊዜ ጋር የመራመድ ሁኔታው ምን ይመስላል? ትግበራውስ ምን አይነት ቅደምተከተል የያዘ ነው? በማሻሻያ ፕሮግራሙ ላይ የሰው ሀይሉ ሚና ምን ይመስላል? ቢፒአር ምን ያህል ከፖለቲካ የፀዳ ነው? ውጤታማ ነው ሲባል ውጤቱ እንዴት ይለካል? የሚሉ ጥያቄ አዘል ትችቶችን ሰንዝረዋል፡፡
ዶክተር ምህረት ደግሞ ትኩረት ያደረጉት በጥናታዊ ፅሁፉ ጎልተው መውጣት አለባቸው ባሏቸው ነጥቦች ላይ ነው፡፡ በመንግስት አገልግሎት አሰጣጥ ስነምግባር እንዲሰፍንና ተጠያቂነት እንዲጎለብት በሙያው የዳበረ፣ ነፃና በችሎታው ብቻ የተመረጠ የመንግስት ሠራተኛ ወሳኝ ነው ብለዋል። “ሰራተኛው ከፓርቲ ወይም ከፖለቲካው ቁጥጥር ነፃ ሆኖ በሙያው የተካነና ለሀላፊነቱ ተጠያቂ ቢሆን አብይ መስፈርት ነው ብዬ አስባለሁ” ብለዋል፡፡ “የስነ ምግባር ወይም የአፈፃፀም ጉድለቱን በፓርቲ ጥላ ስር መደበቅ ያለበት አይመስለኝም፡፡ በሙያው ይፈረጃል፤ ይመለመላል፣ ያድጋል፣ ይደራጃል፡፡” ሲሉም አብራርተዋል፡፡
ነፃ የሆነና በሙያው የተካነ ጋዜጠኛና ሚዲያ መኖር ዋነኛ የፖሊሲ ጥያቄ እንደሆነም ዶ/ር ምህረት ተናግረዋል፡፡ ተንቀሳቅሶ ማንቀሳቀስ የሚችል ሲቪል ማህበረሰብ ያስፈልጋል፤ ይሄ ጎላ ብሎ መውጣት አለበት ያሉት ዶ/ሩ፤ ነፃና ጠንካራ የሙያ ማህበራት ያስፈልጋሉ ብለዋል፡፡ “ዎች ዶግ” ተቋማት ነፃ ሆነው በህግ መሰረት መጠናከር እንዳለባቸውም ገልፀዋል። “ማሻሻያው” ብዙ ነው፤ የአንዱ ጥቅምና ጉዳት ሳይታይ በላዩ ላይ መደረብ ጉዳት አለው” ብለዋል - ዶ/ር ምህረት ባቀረቡት ጥናት፡፡

Published in ህብረተሰብ

(የሟች ኢ/ር ጀሚል ባለቤት፤ ወ/ሮ ፋጡ የሱፍ)
“ለመጀመሪያ ጊዜ የባሌን መታመም በስልክ ነው የሰማሁት፡፡ ሌላ ጊዜ ወገቡን ያመው ስለነበር ያው ህመሙ ነበር የመሰለኝ። ተኝቷል ወደተባለበት አሚን ጀነራል ሆስፒታል በፍጥነት ስሄድ ያጋጠመኝ ሌላ ታሪክ ነው፡፡ ባለቤቴ ጭንቅላቱ ተጐድቷል፤ አንድ የቀረ የሰውነት ክፍል የለውም፡፡ ተደብድቧል፡፡ ራሱን ስቶ እየቃዠ ነበር ያገኘሁት (… ከፍተኛ ለቅሶ …) ነገሩን ሳጣራ በብዙ ሰዎች ተደብድቦ ከቡታጅራ ነው ወደ አሚን ጀነራል ሆስፒታል የመጣው”
ይሄን የተናገሩት ግንቦት 20 ቀን 2004 ዓ.ም የ“ሊቃ” በዓልን ለማክበር ወደ ጉራጌ ዞን መስቃን ወረዳ፣ ሚኬኤሎ ገበሬ ማህበር፣ መልካሜ መስጊድ፣ ከጓደኞቻቸው ጋር ሄደው፣ ባደረሰባቸው ድብደባ ህይወታቸው ያለፈው የኢ/ር ጀሚል ሀሰን ባለቤት ወይዘሮ ፋጡማ የሱፍ ናቸው፡፡ በጉራጌ ዞን በመስቃን ወረዳ በየወሩ የሚከበረውን “ሊቃ” የተሰኘ ሀይማኖታዊ በዓል ለማክበር ግንቦት 20 ቀን 2004 ዓ.ም ከአዲስ አበባ ሱማሌ ተራ ከሚገኘው መስጊድ ተነስተው ከ50 በላይ ሰዎች ወደ ስፍራው ተጉዘው ነበር፡፡ በእለቱ ሚኬኤሎ በተባለው አካባቢ መልካሜ መስጊድ ደርሰው ስርዓቱን ለመከታተል ገና እንደገቡ እጅግ በርካታ ዱላ የያዙ ሰዎች ከአዲስ አበባ የሄዱትን ሰዎች መደብደብ ጀመሩ። አገር ሰላም ብለው የሄዱት እንግዶች፤ በአካባቢው ሰው የዱላ ውርጅብኝ ሲወርድባቸው ያመለጠው አመለጠ፤ የተጐዳው ተጐዳ፤ ነገር ግን ኢ/ር ጀሚል ማምለጥ ባለመቻላቸው ዱላው ሁሉ ሰውነታቸው ላይ አረፈ። ጭንቅላታቸውም ላይ ድንጋይ ተጫነ፡፡ በሞትና በህይወት መሀል ሆነው ከአዲስ አበባ በተላከ አምቡላንስ አሚን ጀነራል ሆስፒታል ገቡ፡፡
ህይወታቸውን ለማትረፍ ዶክተሮችና ነርሶች አቅምና እውቀታቸውን እስከመጨረሻው አሟጠው ቢጠቀሙም የኢ/ር ጀሚል ህይወት ተስፋ ሰጪ አልነበረም፡፡ በአስቸኳይ ወደ ቱርክ ሄደው እንዲታከሙ የአሚን ጀነራል ሆስፒታል ዶክተሮች ትዕዛዝ አስተላለፉ። ጉዞ ወደ ቱርክ ሆነ፡፡ ቱርክ በደረሱ በሶስተኛው ቀን ኢ/ር ጀሚል ሀሰን ይህቺን አለም እስከወዲያኛው ተሰናበቱ። “በሰው አገር ደህና ሰውነት የሌለውን፣ በዱላ ባዘቶ የሆነውን የባሌን አስክሬን ይዤ ግራ ገባኝ፤ ልጆቼን አሰብኳቸው፤ ለልጆቼ አባታቸው ምን ማለት እንደሆነ የማውቀው እኔ ነኝ” ይላሉ፤ የአቶ ጀሚል ባለቤት ወ/ሮ ፋጡማ የሱፍ፡፡ “ልጄ ኪናን ጀማል በትምህርቱ ጐበዝ ነበረ፤ ኢትዮጵያን ወክሎ ቱርክ በመሄድ ተወዳድሮ አንደኛ በመውጣቱ ከኢስታምቡል ፓርላማ ሽልማት ተቀብሏል፤ አሁን ግን በአባቱ ሞት የተነሳ መማር አልቻለም” ብለዋል፤ ወ/ሮ ፋጡማ፡፡
የድርጊቱ መንስኤ
ወልቄጢ አካባቢ “ቃጥባሬ” የተሰኘ መስጊድ ይገኛል፡፡ መስጊዱ በኢ/ር ጀሚል ገዳይ ቅድመ አያት በሀጂ ኢሳ እንደተሰራ የአካባቢው ነዋሪዎች ያስረዳሉ፡፡ ሀጂ ኢሳ በአካባቢው እስልምናን ያስፋፉ አስተማሪና በአካባቢው ህዝብ ተቀባይነት ያላቸው ሼክ እንደነበሩ ነዋሪዎቹ ይመሰክራሉ፡፡ ሀጂ ኢሳ ካለፉም በኋላ ልጃቸው ሻለቃ ሱልጣን ሀላፊነቱን ተረክበው የእስልምናን እምነት በትክክለኛው መንገድ ሲያስተምሩ፣ የተጣላን ሲያስታርቁ፣ ለታመመ ሲፀልዩና ሲያድኑ የቆዩ የሀይማኖት አባት እንደነበሩ ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው የአካባቢው ሰዎች ይናራናሉ፡፡ እኚህ አባት በስልጤ፣ ጉራጌ፣ በሶዶ ወረዳ የተለያዩ መስጊዶችን በማሰራት እምነቱ በትክክለኛው መንገድ እንዲቀጥል የራሳቸውን አሻራ ጥለው ማለፋቸውን ነዋሪዎቹ ይመሰክራሉ፡፡
እንደ አካባቢው ነዋሪዎች ገለፃ፤ ሀይማኖቱ እየተበላሸና ሌላ መልክ እየያዘ የመጣው ከሻለቃ ሱልጣን ልጅ እና ከልጅ ልጃቸው በኋላ ነው፡፡ በተለይ የልጅ ልጃቸው አቶ ሰልማን ሰይድ ፋሪስ፤ ከቅድመ አያቶቻቸውና ከአያቶቻቸው የተረከቡትን የእምነት ስርዓት ወደ ጐን በመተው፣ “ከአላህ ይልቅ እኔን አምልኩ” በሚል ወደ ጥንቆላና ባዕድ አምልኮ ቀየሩት ይላሉ፤ ነዋሪዎቹ፡፡ ይህን ጉዳይ አጥብቀው ከሚቃወሙት ውስጥ ደግሞ የሰልማን ሰይድ ፋሪስ አጐት በድሩ ሱልጣን አንዱ እንደነበሩ ይነገራል፡፡ በድሩ ሱልጣን፤ የሰልማን ሰይድ ፋሪስ የአባታቸው ወንድም (አጐታቸው) ናቸው፡፡
“ይሄ ነገር አይሆንም፤ ሰው ሁሉ ማመን ያለበት በፈጣሪው በአላህ ነው፤ ወደ አላህ መንገድ መመለስ አለብህ እያልኩ ሰው ሁሉ እሱን እንዲያመልክ የሚያደርግበትን መንገድ እቃወም ነበር፤ በዚህ ነው ሊገድለኝ የነበረው” ይላሉ፤ ከሞት የተረፉት አጐቱ አቶ በድሩ ሱልጣን፡፡ መጀመሪያ ሊገደሉ እቅድ የተያዘባቸው አጐቱ አቶ በድሩ ሱልጣን እንደነበሩና ግንቦት 19 ቀን 2004 ዓ.ም እራሱን “የሀይማኖት መሪ” እያለ የሚጠራው አቶ ሰልማን ሰይድ ፋሪስ፤ ለታናሽ ወንድማቸው እና ለተከታዮቻቸው መመሪያ ሲያስተላልፉ ሰምቻለሁ ብለዋል - አንድ የአይን እማኝ፡፡
የቡታጅራና የአካባቢው ከፍተኛ ፍርድ ቤት ጉዳዩን ሲመረምር ከቆየ በኋላ ህዳር 7 ቀን 2005 ዓ.ም (ኢ/ር ጀሚል ሐሰን ከተገደሉ ከስድስት ወራት በኋላ) የግድያው ዋና መሪ፣ አዘጋጅና አዛዥ እንዲሁም የግድያው ቀድሞ ጀማሪዎች የሀይማኖት መሪ ናቸው በተባሉት:- ሰልማን ሰይድ ፋሪስ ሱልጣን፣ ወንድማቸው ነሲቡ ፋሪስ ሱልጣን፣ ወልዩ ቦንሰሞና ሁሴን አብደላ በተባሉት ተከሳሾች ላይ በሶስት ተደራራቢ ወንጀል ክስ ተመስርቶ እንደነበር የአቃቤ ህግ መዝገብ ያስረዳል፡፡ ክሱም ከባድ የነፍስ ግድያ፣ በከባድ የነፍስ ግድያ ሙከራ እና ታስቦ የሚፈፀም የንብረት ማውደም የሚል ሲሆን ተከሳሾቹ የፈፀሙት ወንጀል፤ (በሁለት ተደራራቢ ክሶች) ከእድሜ ልክ እስራት እስከ ሞት የሚደርስ ፍርድ የሚያሰጥ ቢሆንም በቅጣት ማቅለያ ከ20 እስከ 11 ዓመት እስር ተፈረደባቸው፡፡ ክስ የቀረበባቸው 22 ሰዎች ቢሆኑም ሁለቱ አቃቤ ህግ አላስመሰከረባቸውም በሚል በነፃ ሲሰናበቱ፣ 20ዎቹ እንደየጥፋታቸው መጠን እስር ተፈረደባቸው - ከ11-20 ዓመት፡፡
የቡታጅራና አካባቢው ነዋሪና አቃቤ ህግ ግን በፍርዱ ደስተኛ አልነበሩም፡፡ ጥፋተኞቹ ሞት እና እድሜ ልክ እስር ሊፈረድባቸው ሲገባ ፍ/ቤቱ የሰጠው ብያኔ አግባብ አይደለም ያለው አቃቤ ህግ፤ ለደቡብ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሆሳዕና ምድብ ችሎት ይግባኝ ጠየቀ፡፡
በቡታጅራና አካባቢው የህግ ባለሙያ የሆኑትና ስማቸው እንዲገለፅ ያልፈለጉ አንድ ግለሰብ ጉዳዩን በቅርበት እንደሚያውቁ ጠቁመው፤ ጥፋተኛ የተባሉት ግለሰቦች በፊናቸው ምድብ ችሎት ሆሳዕና እያለ፣ እነሱ ግን ሀዋሳ በመሄድ ለክልሉ ጠቅላይ ፍ/ቤት ይግባኝ ማለታቸው አግባብ አልነበረም ይላሉ፡፡ የሆነ ሆኖ የክልሉ ጠቅላይ ፍ/ቤት የጥፋተኞችን ፋይል ከፍቶ ጉዳያቸውን ካየ በኋላ፣ የቡታጅራና አካባቢው ጠ/ፍ/ቤት አቃቤ ህግ ሆሳዕና ምድብ ችሎት ይግባኝ ያለበትን መዝገብ አጣምሮ ለማየት የሟች ጉዳይ መዝገብም ወደ ሀዋሳ ተዛወረ፡፡ የጉዳዩ ሂደት መዝገብ እንደሚያሳየው፤ በክልሉ ጠቅላይ ፍ/ቤት ፕሬዚዳንት በአቶ ታረቀኝ አበራ አይዶ እና በሌሎች ዳኞች የታየው የሁለቱ ወገኖች ይግባኝ የሟችን መዝገብ በዝርዝር ሳይመለከት እንዲሁም ተከሳሾቹ ጥፋተኛ የተባሉበትን ከፍተኛ የነፍስ ግድያ ወንጀል ተራ አምባጓሮ ወደሚለው በመለወጥ፣ “ከአዲስ አበባ ሊቃችንን ሊያበላሹ ይመጣሉ፤ ዱላ (ሽመል) ይዛችሁ ደብድቧቸው፣ ይህን ያላደረገ ከእኔ ጋ እንደተጣላ ይቁጠረው” የሚል ትዕዛዝ በማስተላለፍ ግድያውን በቀጥታ መርቷል በሚል 14 ዓመት የተፈረደበትን ሰልማን ሰይድ ፋሪስ፤ አቃቤ ህግ ማክበጃ አላቀረበም በሚል በቅጣት ማቅለያ ወደ አምስት አመት፣ የግድያውን ሂደት ዱላ በማሳረፍ አስጀምሯል የተባለውና የሰልማን ሰይድ ፋሪስ ታናሽ ወንድም የሆነው ነሲቡ ፋሪስ ከ19 ዓመት ወደ ዘጠኝ አመት ሲቀነስላቸው፤ የሌሎቹም ከ13 እና ከ11 ዓመት ወደ አንድ አመት ከስምንት ወር በመቀነሱ በጠቅላይ ፍ/ቤቱ ውሳኔ፣ እጃቸው ከተያዘ ጀምሮ አመት ከስምንት ወር ያለፋቸው 14 ሰዎች በነፃ ሊለቀቁ ችለዋል። ይህም ውሳኔ በሟች ቤተሰብ ዘንድ ለቅሶና ዋይታን ፈጥሯል። በዚህ ጉዳይ ላይ ያነጋገርናቸውና ሂደቱን ሲከታተሉት እንደነበር የገለፁልን የህግ ባለሙያ፤ ጉዳዩን የስር የቡታጅራና አካባቢው ፍ/ቤት፤ ተንትኖ እንዳየው፤ ከ50 በላይ የሰነድና ከ50 በላይ የሰው ማስረጃ ቀርቦለት በትክክል መወሰኑን ይናገራሉ፡፡ ይህን ውሳኔ ጠቅላይ ፍ/ቤቱ በአንድ አንቀፅ መሻሩ ፍትህ መዛባቱን እንደሚያሳይ የህግ ባለሙያው ገልፀዋል፡፡
“አጠቃላይ የሂደቱ መዝገብ እጄ ላይ ስላለ በደንብ ተመልክቼዋለሁ” ያሉት የህግ ባለሙያው፤ የጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ውሳኔ የኢፌዲሪን የቅጣት አወሳሰን መመሪያ የጣሰ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ በሌላ በኩል ባለሙያው “ስህተት” ነው ያሉት 539 1(ሀ) ከፍተኛ የነፍስ ግድያ ወንጀል ወደ 540 ተራአምባጓሮ መቀየሩን ነው። ከተቀየረም የተቀየረበት አጥጋቢ ምክንያት መኖር ነበረበት፤ ነገር ግን “ይህን አልተቀበልኩም፣ ይሄ አያስኬድም” እያለ ጠ/ፍ/ቤት የወሰነው ውሳኔ መሰረታዊ የህግ ስህተት እንዳለበት በግልፅ ያሳያል ብለዋል፡፡
የሟች ባለቤት ወ/ሮ ፋጡማ የሱፍ በበኩላቸው፤ በጠ/ፍ/ቤቱ የተሰጠው ውሳኔ በእርሳቸውም ሆነ በልጆቻቸው ላይ ከፍተኛ ሀዘን እንደፈጠረባቸው ይናገራሉ፡፡ “አባቴን የገደለው ሰው አምስት አመት ከተፈረደበት እኔም እሱን ገድዬ አምስት አመት መታሰር አያቅተኝም” በሚል ልጄ ወደበቀለኝነት ሀሳብ ገብቷል ሲሉ “የፍትህ ያለህ” ብለዋል፡፡ “እኔም ሆንን ልጆቹ ኢትዮጵያዊያን ነን ልጆቼን የት ሄጄ ላሳድግ የልጄን ሀዘንና የበቀለኝነት ስሜት እንዴት ነው የማስወግደው?” በማለት ያለቅሳሉ፡፡
“ትክክለኛ ፍርድ አገኛለሁ ብዬ ከአዲስ አበባ ሀዋሳ 35 ጊዜ ተመላልሻለሁ፤ እዛም ደርሼ ለሌላ ጊዜ ተዛውሯል፣ ከሰዓት ነው እየተባልኩ ልጆቼንና ስራዬን ጥዬ ተንከራትቻለሁ” ያሉት ወ/ሮ ፋጡማ፤ በውሳኔው በጣም ማዘናቸውን ተናግረዋል፡፡ “የጠ/ፍ/ቤቱን ፕሬዚዳንት አነጋግሪ ተብዬ አቶ ታረቀኝን እያለቀስኩ ትክክለኛ ፍርድ እንዲሰጡኝ ጠይቄ ነበር” ያሉት ወ/ሮዋ፤ “ትክክለኛ ፍርድ ታገኛለሽ፤ መዝገቡ በእኔ እጅ ነው” ብለውኝ ስጠብቅ፣ ጭራሽ 14 ሰዎች በነፃ ሲለቀቁ፣ የነፍሰ ገዳዮቹ ቅጣት ወደ አምስትና ዘጠኝ አመት መቀነሱ አሳዝኖኛል ብለዋል፡፡
“ውሳኔው ከአድልዎ፣ ከአምቻ ጋብቻ የፀዳ ነው”
አቶ ታረቀኝ አበራ
በጉዳዩ ዙሪያ ሀዋሳ ቢሯቸው ተገኝተን ያነጋገርናቸው የደቡብ ክልል ጠቅላይ ፍ/ቤት ፕሬዚዳንት አቶ ታረቀኝ አበራ፤ “ጉዳዩን በደንብ አውቀዋለሁ፤ ውሳኔውም በትክክል ታይቶ ተፈትሾ የተወሰነ ከአድልዎ፣ ከአምቻ ጋብቻ የፀዳ ነው” ብለዋል፡፡ ሆሳዕና ምድብ ችሎት እያለ፣ አቃቤ ህግም በሆሳዕና ይግባኝ ብሎ ሳለ ጥፋተኞቹ ወደ ክልሉ ጠ/ፍ/ቤት መጥተው ይግባኝ ሲሉ ፋይል ተከፍቶ መስተናገድ ነበረባቸው ወይ? በሚል ላነሳነው ጥያቄ ሲመልሱ፣ “መንግስት በየአቅራቢያው ምድብ ችሎቶችን የከፈተው ሰዎች የጊዜ፣ የገንዘብና መሰል ብክነቶች ለመከላከል ነው” ያሉት ፕሬዚዳንቱ ሆኖም ለየት ያሉ ጉዳዮች ሲመጡ የክልሉ ጠቅላይ ፍ/ቤት ፋይል እንደሚከፍት ገልፀው፤ ይሄኛውን ጉዳይ ለየት የሚያደርገው ሀይማኖታዊ ይዘት ስላለው ነው ይላሉ፡፡ አንቀፁ ከ539 /ሀ/ (1) እንዴት ወደ 540 (ተራ አምባጓሮ) ወደሚለው ለምን ተቀየረ? በሚል ላቀረብነው ጥያቄም፤ “ጉዳዩ የተፈፀመው በሀይማኖት ቦታ ሆኖ በድንገት በተነሳ ግርግር እንጂ የታሰበበት እንዳልሆነ ፍ/ቤቱ አጣርቷል፤ በዚህም ውሳኔ ሰጥቷል” ይላሉ፡፡
ይሁን እንጂ የስር የቡታጅራ አካባቢ ከፍተኛ ፍርድ ቤት፤ ሰልማን ሰይድ ፋሪስ ተከታዮቹን በመልካሜ መስጊድ በ19/09/2004 ዓ.ም ሰብስቦ “ነገ-ከአዲስ አበባ የሚመጡ እንግዶች አሉ፤ የሊቃ ስርዓቱን ለማበላሸት ስለሆነ ጅሀድ (ጦርነት) እናውጅባቸዋለን፡፡ ሁላችሁም ዱላ ሽመል ይዛችሁ ቀጥቅጣችሁ ግደሉ” ስለማለቱ 50 የሰው፣ 50 የሰነድ ማስረጃ አቅርቦ የቅጣት ውሳኔ ማስተላለፉን መዝገቡ ያስረዳል፡፡ “አቶ ሰልማን ሰይድ ፋሪስ ከዚህ ቀደም ብዙ የግድያ ሙከራዎች አድርጓል” የሚሉት አንድ የቡታጅራ አካባቢ ነጋዴ ስለተፈጠረው ነገር በደንብ እንደሚያውቁና በቅድሚያም ድርጊቱን እንደሚያወግዙ በመግለፅ ነው አስተያየታቸውን የጀመሩት፡፡ ከዚህ በፊት ወንጀለኛው (ሰልማን ሰይድ ፋሪስ) በሀይማኖት ሽፋን ህብረተሰቡን ያለ አግባብ “የሀይማኖት መሪ ነኝ” በማለት ራሱን ሰይሞ ምንም የሀይማኖት ምልክት በሌለበት እየበዘበዘ እንደሚገኝ ይናገራሉ፡፡ “ሰውንም ወዳልተፈለገ እምነትና ጥንቆላ ከቶታል” የሚሉት ነጋዴው፤ ይህ ሰው ከአቶ ጀሚል በፊት በጠራራ ፀሀይ ሁለት ጊዜ ሌሎች ሰዎች ላይ ሽጉጥ መተኮሱን፣ በዚህም ክስ እንደተመሰከረበት ጠቁመው “የሀይማኖት መሪ ነው” በሚል በነፃ መለቀቁን ይናገራሉ። “የወረዳው ይህን ያህል ሽፋን መስጠት አሁን ወደ ነፍስ ግድያ አሸጋግሮታል” ብለዋል፡፡
ከዚህ በፊት የሊቃ ስርዓት በሰላም ነው በየወሩ ሲከበር የነበረው ያሉት እኚህ ግለሰብ፤ “ከአዲስ አበባ የሚመጡ ስርዓቱን የሚያበላሹ ሰዎች ስላሉ በሰላም እንዳይመለሱ በዱላ ደብድባችሁ ግደሉ” የሚል ትዕዛዝ ማስተላለፉንና በዓሉ በሚከበርበት ቀን እርሱ በበዓሉ ላይ አለመገኘቱን፣ ከዚያ በፊት ግን ከሊቃ ስርዓቱ ቀርቶ እንደማያውቅ መስክረዋል፡፡
“አሁንም ቢሆን ማረሚያ ቤት ሆኖ በየጊዜው በመኪና እየታጀበ ወደ ቤቱ ይሄዳል፣ ኦሮሚያ ክልል ላይ የእርሻ ማሳ አለው፤ እርሱን ሊያሰራ ይሄዳል” ያሉት ግለሰቡ፤ ይህ የሚደረግለት ሽፋን ለቀጣይ ነፍስ ግድያ ያበረታታዋል ብለዋል፡፡ “ድብደባውን እና ግድያውን ፈፅመው ሲመለሱ ሌላው ተባባሪ የዛሬው ግንቦት 20 የድል ቀን ነው በደንብ አክብረነዋል እባክሽ ቅቤ ቀቢኝ ብሎ ለዋርሳው ሲናገር በጆሮዬ ሰምቻለሁ” የሚሉት ግለሰቡ፤ “ይህ ሰው ታስሮ ነበር፤ በይግባኙ ሂደት ተለቆ ወጥቷል ግን ድጋሚ እየተፈለገ ነው፤ ለአካባቢው ስጋት ሆኗል” ብለዋል፡፡
“በአካባቢያችን አንድ አርሶ አደር በቀን 60 ብር እየተከፈለው በሚሰራበት ወቅት ብዙ አርሶ አደሮች በነፃ እርሱን ሲያገለግሉ ይውላሉ” በማለትም አክለዋል፡፡
“በድሩ ሱልጣን የተባለው አጐቱ ሌሎች እንግዶችን ከአዲስ አበባ ይዞ እንደሚመጣ ያውቅ ነበር፤ አቶ በድሩ የተማረ በመሆኑ አጥብቆ ይቃወመዋል፤ ህዝቡን የሚበዘብዝበትን መንገድ እንዳያጣ ነው አጐቱን ግደሉት ያለው” ብለዋል፡፡ ሆኖም የአላህ ፈቃድ ሆኖ አቶ በድሩ ተደብድቦ ሲተርፍ፣ ኢ/ር ጀሚል ለሞት በቃ ብለዋል፡፡
“ወንጀሉን ፈፃሚውም ሟቹም ቤተሰቤ ነው ያለው ሌላ የቡታጅራ ከተማ ወጣት ነዋሪ፤ አጐቱ በድሩ ሱልጣን የሊቃን ስርዓት ከማክበር ባሻገር ከቃጥባሬ እስከ ወልቂጤ ያለ 12 ኪ.ሜ ኮረኮንች መንገድ በአስፋልት ለመቀየር አስቦ፣ ሟችን ጨምሮ ወደ 60 የሚጠጉ ሰዎችን ከአዲስ አበባ ይዞ እንደሚመጣና መንገዱን በተመለከተም ከህዝቡ ጋር ምክክር ለማድረግ ቀጠሮ አስይዞ እንደነበር ወጣቱ ይናገራል፡፡ “እወጃውን በግንቦት 19 አውጆ፣ ለበዓሉ ቀረ፤ ከዛን በፊት ቀርቶ አያውቅም” የሚለው ወጣቱ እነዚህ ሰዎች አገር ሰላም ብለው ሁለት ሚኒባስና አንድ ቅጥቅጥ አይሱዙ ይዘው ግንቦት 20 ቀን 2004 በስፍራው መገኘታቸውን ገልጿል፡፡ “በዋና ገዳይነት ተፈርዶበት እስር ቤት የሚገኘውታናሽ ወንድሙ ነሲቡ ሱልጣን “የተባሉት ሰዎች መጥተዋል ተነሱ” በሚል ድብደባውን መጀመሩንና ከሞቱት ግለሰብ ውጭ 19 ሰዎች ላይ ከባድ የአካል ጉዳት መድረሱን ወጣቱ ገልጿል።
የገዳይ የቅርብ ዘመድ እንደሆኑ የነገሩን ሌላው አዛውንት የአካባቢው ነዋሪ፤ ወንጀለኛው በእናቱ በኩል ዘመዳቸው እንደሆነ ገልፀው፤ “አንድ ጊዜ ወፍጮ ቤትህ በደንብ እንዲሰራ፣ ንግድህ እንዲቃና ከሱዳን ያስመጣሁት አዋቂ ስላለ 30 ሺህ ብር ከፍለህ መድሀኒት ላሰራልህ ብሎኝ እምቢ ብየዋለሁ” ብለዋል፡፡ ወንጀለኛው ጥንቆላ ውስጥ መግባቱንና ህዝቡን እያንቀጠቀጠ ገንዘብ እንደሚቀበልም ነዋሪው ተናግረዋል፡፡
የቡታጅራና አካባቢው ነዋሪዎች በእስር ላይ ስለሚገኘው ፍርደኛ፤ ሲናገሩ “እስር ቤቱ ለእርሱ መዝናኛው ነው፤ ድንኳን ተጥሎለት አሁንም ከህዝቡ ገንዘብ እየሰበሰበ ነው፤ ከእስር ቤት እየወጣ በየጊዜው ወደ ቤቱ ይሄዳል፣ “ወራ” የተባለውን የራሱን ሀይማኖታዊ ስርዓት ከማረሚያ ቤት ወጥቶ እቤቱ ነው ያከበረው፤ እርሻውን 50 ኪ.ሎ ሜትር እየሄደ ያሰራል፤ በየጊዜው ከማረሚያ ቤቱ 18 ኪ.ሜትር ወደሚርቀው ቤቱ ይሄዳል፤ ከፍተኛ ሀዘንና ችግር ቢከሰት እንኳን ከማረሚያ ቤቱ ሰባት ኪሎ ሜትር ራዲየስ መራቅ በህጉ አይፈቀድም፤ ለዚህ ሰው ሽፋን የሚሰጥበት ሁኔታ ለአካባቢው ስጋት ነው” በማለት ተናግረዋል፡፡
“ከፖሊስ ጣቢያ በህገ-ወጥ መንገድ ነው ያመጣነው”
ኮማንደር ወንደሰን አበበ
የቡታጅራ ማረሚያ ተቋም ሀላፊ ኮማንደር አበበን በማረሚያ ተቋሙ ተገኝተን ስለጉዳዩ ጠይቀናቸው፤ “በ2004 በነፍስ ግድያ ወንጀል ተከሰው የመጨረሻ ውሳኔ ያገኙ ሰዎች አሉ” በማለት ነው ጥያቄያችንን መመለስ የጀመሩት፡፡ በነፍስ ግድያው ወደ ማረሚያ ቤት የመጡት 19 ሰዎች እንደነበሩ ጠቁመው 14ቱ በአመክሮ እንደተፈቱ ኮማንደሩ ገልፀዋል፡፡ በማረሚያ ቤቱ ውስጥ ካሉት መካከል አንዳንዶቹ እንደፈለጉት እየወጡ ይገባሉ የሚባለውን በተመለከተ ሲናገሩም፤ “የህግ ታራሚዎች ገና ወደ ማረሚያ ቤት እንደገቡ በርካታ ማህበራዊ ችግሮች እንዳሉባቸው ይናገራሉ” የሚሉት የተቋሙ ሀላፊ፣ ንብረታቸውን ሳይሰበስቡ ቤተሰባቸውን ሳያረጋጉ፣ ማረሚያ ቤት እንደሚገቡ ጠቅሰው፤ ከዚህ አንፃር ህጉ ፈቃድ ይሰጣቸዋል ይላሉ፡፡ “ይህ ማለት ግን በየቀኑ ይወጣሉ ማለት አይደለም” ያሉት ኮማንደሩ፤ “በርካታ ንብረት በትኜ ነው የመጣሁት” የሚል ማመልከቻ ካቀረቡ በኋላ ጉዳዩ ተጣርቶ አጃቢ ተመድቦላቸው ሄደው እንደሚመጡ፣ ይህን የሚፈቅድ ህግ እንዳለም አብራርተዋል፡፡ ከኢ/ር ጀሚል ግድያ ጋር በተያያዘ በተቋሙ በእርምት ላይ የሚገኙት ሰልማን ሰይድ የአያያዝ አግባብ ሲያስረዱም፤ ሰውየው የልብ ህመም ስላለባቸው በየሶስት ወሩ ለህክምና ወደ አዲስ አበባ እንደሚመላለሱ ገልፀው፣ ይህ የሀኪም ትዕዛዝ እና የጤና ጉዳይ ስለሆነ የግድ መሄድና መታከም እንዳለባቸው፤ ምንም ማድረግም እንደማይቻል ኮማንደሩ በአፅንኦት ተናግረዋል፡፡
“የሰልማን ሰይድ ፋሪስን ጉዳይ በተመለከተ ውጭ ይወጣሉ በሚል ተደጋጋሚ ጥያቄ ከተለያዩ አካላት ይቀርብልናል” ያሉት ኮማንደር ወንድወሰን፤ ይህንንም በትክክለኛው መንገድ እየመለሱ እንደሚገኙ፣ ጤንነታቸውን በተመለከተና የመኝታን ጉዳይም ጭምር ዶክተሮች በሰጡት መመሪያ መሰረት ለብቻቸው እንዲተኙ መደረጉን ያብራራሉ፡፡
ለሰልማን ሰይድ ከህጉ ውጭ የተለየ ነገር አልተፈቀደለትም ይላሉ የማረሚያ ቤቱ ሃላፊ፤ አንድ የህግ ታራሚ ወላጆቹና ቤተሰቦቹ ቢሞቱበት 6 ኪ.ሜ ራዲየስ ድረስ ሄዶ እንዲቀብር የማረሚያ ቤቱ አሰራር ይፈቅዳል ያሉት ኮማንደሩ፤ ቡታጅራ ሆስፒታል የተኛ የቅርብ ቤተሰብ (ዘመድ) ካለውም ጠይቆ እንዲመጣ ፈቃድ እንዲሰጥ ህጉ ያዛል ብለዋል፡፡ “እርግጥ ሰልማን ሰይድ ፋሪስ በአንድ ወቅት እህል መሰብሰብ አለብኝ፣ ገንዘብ ያለበትንም ለባለቤቴ ልንገር ብለውን ፈቅደንላቸው ሄደው መጥተዋል፤ ከዚህ የዘለለ ግን እንደ ውሀ ቀጂ የሚመላለሱበት ጉዳይና የተለየ እድል የሚሰጥበት የህግ አግባብ የለም” ሲሉ አስረድተዋል፡፡
ኦሮሚያ ክልል ሄደው ማሳ ያሰራሉ፣ “ወራ” የተባለውን የራሳቸውን የሀይማኖት በዓል በቤታቸው ያከብራሉ፤ በማረሚያ ቤቱ ውስጥ ዳስ ተጥሎ ገንዘብ ይሰበስባሉ በሚል በታራሚው ላይ የሰማነውን መረጃ የጠቀስንላቸው ኮማንደሩ ሲመልሱ፣ “ኦሮሚያ ድረስ የሚሄዱበት ምክንያት የለም፤ ምክንያቱም በነፍስ ግድያ የገቡ ሰው ናቸው በቀል ስለሚኖር በሰው ጉዳት ሊደርስባቸውም ጉዳት ሊያደርሱም ይችላሉ በሚል የማረሚያ ተቋሙ ከፍተኛ ጥንቃቄ ያደርጋል” ብለዋል፡፡
ሌላ ታራሚ፤ ገንዘቤን ልሰብስብ፤ ቤተሰቤን ላረጋጋ ቢል ይፈቀድለት እንደሆነ ጠይቀ ናቸውም፤ ድንገት ተይዞ ለገባ ታራሚ ህጉ ለአንድ ቀን ብቻ እንደሚፈቀድ ተናግረዋል፡፡
ዳስ ተጥሎላቸው ገንዘብ ይሰበስባሉ የሚለውን በተመለከተም፤ እኔ በማረሚያ ተቋሙ ስሰራ 11 ዓመቴ ነው፤ በዚህ አመት ውስጥ በቀን ብዙ ጠያቂ መጣ ከተባለ 10 ወይም 15 ሰው ነው” ያሉት ሃላፊው፤ እኚህ ሰው ወደማረሚያ ቤቱ ከመጡ በኋላ በቀን ከ100 እስከ 250 ሰው ወደማረሚያ ቤቱ መምጣት መጀመሩን ይናገራሉ፡፡ የታራሚ መጠየቂያም በጣም ጠባብ በመሆኑ የግድ ዳሱ መጣል ስለነበረበት በላስቲክ ዳስ ተሰርቶ እንዲጠየቁ መደረጉን ገልፀው፤ “ይህንን ያደረግነው የሌሎች ታራሚዎችን ጠያቂዎች እድል ላለመንፈግ ነው” ያሉት ኮማንደሩ፤ ሰውየው ገንዘብ ይሰብስቡ አይሰብስቡ ማረሚያ ተቋሙን አይመለከተውም ብለዋል፡፡ ጠያቂው ከጠየቀ በኋላ ገንዘብ ሰጥቷቸው እንደሚሄድ በመግለጽ። “ከዚህ በተረፈ ከሌሎች ታራሚዎች የተለየ እድልና ቅድሚያ ለእርሳቸው የምንሰጥበት ምክንያት የለም፤ ዳሱንም ቢሆን ተቋሙ ሳይሆን ራሳቸው ታራሚው ናቸው ያዘጋጁት፡፡” ብለዋል፡፡ (በነገራችን ላይ በሰማያዊ ላስቲክ የተጣለውን ዳስና የተነጠፈውን ጂባ ምንጣፍ በስፍራው ተመልክተናል፡፡)
“እንኳን የተለየ እድል ልንሰጣቸው ከፖሊስ ጣቢያም ያመጣናቸው በህገ ወጥ መንገድ ነው” ያሉት ኮማንደሩ፤ ግድያው ራሱ የተፈፀመው በሃይማኖቱ የተነሳ መሆኑን፣ ሟችም አደጋው የደረሰባቸው በሰው ማመን የለብንም በሚል መሆኑ እንደሚታወቅ ገልፀው፣ “ታራሚው ከአያቴ፤ ከአባቴ የወረስኩት ነው የሚለውን እምነት እንዲያራምድ እንዴት ወደቤቱ እንልከዋለን” ሲሉ ይጠይቃሉ፡፡ እንደውም ከታራሚው ጋር የተፈጠረ ግጭት እንደነበር የሚያስታውሱት ሃላፊው፤ በአንድ ወቅት በማረሚያ ተቋሙ ውስጥ ከብት ሲታረድ “ሼኩ ያረዱትን ሳይሆን እራሳችን ያረድነውን ነው የምንበላው” በሚል ከታራሚው ጋር በነፍስ ግድያው ተፈርዶባቸው የመጡት ችግር ፈጥረው እንደነበረና ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ቄራ እየታረደ ስጋ እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡
ታራሚው ከዚህ በፊት በሰዎች ላይ ሽጉጥ ስለመተኮሳቸው፣ ብዙ ጊዜ ስለመከሰሳቸውና በማረሚያና በፖሊስ ጣቢያ ሽፋን ይሰጣቸዋል ስለመባሉ ያውቁ እንደሆነ ጠይቀናቸው፤ ሰውየው ወደማረሚያ ቤቱ የገቡት ለመጀመሪያ ጊዜ እንደሆነ ጠቅሰው ቀደም ሲል፣ ፖሊስ ጣቢያ ገብተው ይሆናል እንጂ ማረሚያ ቤት አልመጡም ብለዋል፡፡ “እርግጥ እኛም ከፖሊሶች እኒህን ታራሚና ሌሎች 19 ሰዎችን በህገወጥ መንገድ ነው የተቀበልናቸው ያልኩሽም፤ ገና ሳይፈረድባቸው ፖሊስ ጣቢያ እያሉ ሰዎችን ማነሳሳትና መሰል ድርጊቶችን ይፈጽሙ ስለነበር፣ ነገሩ ወዳልተፈለገ አቅጣጫ እንዳይዞር በመፍራት ነው ፍርድ ከማግኘታቸው በፊት ያመጣናቸው” ብለዋል፡፡
ድሮ አሜሪካም ሆኜ እዚህም ከመጣሁ ጀምሮ ሰልማንና ወንድሞቹ የሚያራምዱት እምነት አይስማማኝም ነበረ “የግድያው መንስኤም ይሄው ይመስለኛል” የሚሉት አቶ በድሩ፣ የጀሚል ሞት ግን የእድሜ ልክ ሀዘን እንደሆነባቸው በሀዘን ገልፀዋል፡፡ ፍ/ቤቱ ነፍሰ ገዳዮቹንና ግብረአበሮቻቸውን በይግባኙ የቀነሰላቸው የእስራት ጊዜና 14 ሰው በነፃ የለቀቀበት መንገድ ለኢ/ር ጀሚል እና ለቤተሰቦቹ፤ ለእኛም ጭምር ሁለተኛ ሞት ነው ብለዋል፡፡
ምንም እንኳ የክልሉ ፍትህ ቢሮ ለሰበር ሰሚ ይግባኝ ቢጠይቅም ይግባኙ የዘገየ መሆኑን የሚናገሩት ወ/ሮ ፋጡማ፤ ወደ ሰበር ችሎት ጉዳዩ ከመጣ በኋላ 14ቱን ሰዎች ያስቀርባቸዋል በሚል ሰበር ችሎቱ ከአንዴም ሁለት ጊዜ ትዕዛዝ ቢሰጥም የተፈቱት 14 ሰዎች ግን ራሳቸውን በመሰወራቸው ሊገኙ እንዳልቻሉ ገልፀውልናል፡፡ ሰበር ሰሚ ችሎቱ ለሶስተኛ ጊዜ በአዲስ ዘመን ጋዜጣ ለጥቅምት 26 ቀን 2006 ሰዎቹ እንዲቀርቡ ያዘዘ ሲሆን በቀጠሮው ቀን ይቅረቡ አይቅረቡ የሚታወቅ ነገር የለም ብለዋል - የሟች ባለቤት ወ/ሮ ፋጡማ፡፡
የ58 አመት ጐልማሳ የነበሩት ኢ/ር ጀሚል ሃሰን፤ ኪናንጀሚልና ኢፕቲሀጅ የተባሉ ሁለት ልጆችን አፍርተዋል፡፡ ከዋሽንግተን ዩኒቨርሲቲ በቢዝነስ አድሚኒስትሬሽን ዲግሪያቸውን ያገኙ ሲሆን ከኮሜርስ በአካውንቲንግ ዲግሪ አግኝተዋል፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የአርክቴክቸር ትምህርት መማራቸውንም ባለቤታቸው ወ/ሮ ፋጡማ ተናግረዋል፡፡ ከረጅም ዓመት በፊት “ርብቃ” የተባለ መጽሐፍ የተረጐሙ ሲሆን መታሰቢያነቱንም ለገዳይ አያት ሻለቃ ሱልጣን እንዳደረጉ ከመጽሐፉ መረዳት ይቻላል፡፡ ስድስት ያልታተሙ የትርጉም ስራዎች እንዳሏቸውና በመጨረሻው የእድሜ ዘመናቸው አካባቢ “the three Cup of Tea” የተሰኘ መጽሐፍ ተርጉመው ለህትመት ሲያዘጋጁ እንደነበር ባለቤታቸው ተናግረዋል፡፡ “አፒክስ” የተሰኘ የጉዞ ወኪል ድርጅት የነበራቸው ኢ/ር ጀሚል፤ “ኦፕቲፋም” የተሰኘ የኔትወርክ ቢዝነሳቸውን በማናጀርነት ይመሩም እንደነበር ታውቋል፡፡
ኢ/ር ጀሚል ከመሞታቸው በፊት “ሁሉንም ሰው ይቅር ብያለሁ፤ ገዳዮቼንም ጭምር” የሚል ቃል መናገራቸውን፣ ተጨማሪ መልዕክት ለማስተላለፍ እስኪርቢቶ ጠይቀው መፃፍ እንደተሳናቸው ባለቤታቸው በእንባ ታጅበው ነግረውናል፡፡ “ይህን ጉዳይ አይቶ የኢትዮጵያ ህዝብ ይፍረደኝ፤ ልጆቼም እኔም ፍትህ እንሻለን” በማለት ሃሳባቸውን ቋጭተዋል፡፡

 

 

አንድ አዋቂና አስተዋይ የተባ ለመምህር ተከታዮቹን ይዞ ረዥም መንገድ ይሄድ ነበር ይባላል፡፡ በመንገዳቸው ላይ አንዲት የታሠረች ጥቁር ላም ይመለከታል፡፡ ከዚያም ወደ ተከታዮቹ ዞሮ፤
“የዚችን ጥቁር ላም ወተት መጠጣት ውጉዝ ነው!” አለ፡፡
ተከታዮቹ በአንክሮ አዳመጡት፡፡ መንገዳቸውን ቀጠሉ፡፡ ወደ አንድ መንደር ሲደርሱ፤ እኔ እዚህ አድሬ አረፍ ልበል፤ እናንተ ደግሞ ወደየመንደሮቻችሁ ተጠግታችሁ እደሩና ጠዋት ከዚሁ መንገድ እንቀጥላለን አላቸው”
ሁሉም ወደሚያድሩበት ሄዱ፡፡
በየደረሱበት ግን ለሰው ትምህርት ለመስጠት ሞከሩ፡-
“የጥቁር ላም ወተት ውጉዝ ነው እነዳትጠጡ” እያሉ አስተማሩ፡፡
ህዝቡም
“ይህንን ማን አለ?” ሲል ጠየቀ፡፡
“መምህራችን!” አሉት፡፡
ጥቁር ላም ያለው ሰው ሁሉ ከፊሉ አዘነ፡፡ ከፊሉ ግራ ተጋባ፡፡ ከፊሉ “መምህርን መጠየቅ አለብን፡፡ አንድ ደሀ ሰው ያለችው አንዲት ጥቁር ላም ብቻ ብትሆንስ? በምኑ ይኖራል?” ሲል አጉረመረመ፡፡
በነጋታው መምህሩ በመንደራቸው ሲያልፍ፣ “መምህር ሆይ የጥቁር ላም ወተት መጠጣት
ስለምን ተከለከለ፣ ስለምንስ ውጉዝ ነው አልክ?” ሲሉ ጠየቁት፡፡
መምህሩም፤
“ተከታዮቼ የጥቁር ላም ወተት መጠጣት የተወገዘ ነው” ብለዋችሁ ከሆነ ተሳስተዋል፡፡ እኔ ያልኩት ነገር የሚመለከተው፣ ትላንት መንገድ ላይ ያየናትን ጥቁር ላም ነው” አላቸው፡፡
ሰዎቹም “ያቺንስ ጥቁር ላም ምን የተለየ ነገር ብታይባት ነው? አሉና ደግመው ጠየቁት፡፡
“መልካም ጥያቄ ነው፡፡ ተከታዮቼም ይህን ጥያቄ ሊጠይቁኝ ይገባ ነበር፡፡ ያቺ ጥቁር ላም እበረት ውስጥ ታስራለች፡፡ ምንም ምግብ አይሰጥዋትም፡፡ ሆኖም ጠዋት ማታ ያልቧታል፡፡ ይሄ ተግባር ግፍ ነው፡፡ ወተቱም ከግፍ የተገኘ ወተት ይሆናል፡፡ ውጉዝ ነው ያልኩት ለዚህ ነው፡፡ የጥቁርዋ ላም ምሳሌነቱ በግፍ ለተገኘ ማናቸውም ገንዘብ ንብረትና ሀብት ሁሉ ነው!” ሲል አብራራላቸው፡፡
* * *
ነገርን በጅምላው መውሰድ ስህተት ላይ ይጥለናል፡፡ የዓለምን ተመራማሪዎች ሲያጣሉና ተከታዮችንም ሲያወዛግቡ የኖሩ አያሌ ጥያቄዎች ከትርጓሜ ስህተት የመጡ እንደሆኑ አንዘንጋ፡፡ በእኩይ መንገድ የተገኘ ማናቸውም ዓይነት ብልፅግና ያስጠይቃል ፡፡ ሊያስጠይቅ የሚችልን ማናቸውም ኢፍትሐዊ ነገር የፈፀመን አለቃም ሆነ ምንዝር፤ ባለሥልጣንም ሆነ ተከታይ ጉዳዩን አብራርቶ እንዲጠይቅ ማድረግ የተበዳይ መብት ነው፡፡ ላሚቱ ራሷም ተዟዙራ የምትበላው እንዳትፈልግ አስረን ስናበቃ ያልሰጠነውን ለመቀበል፣ ያልመገብነውን ለማለብ መፈለግ፣ የሚገኘውን ወተት የግፍ ንብረት እንደሚያደርገው ማስተዋል ዋና ጉዳይ ነው፡፡ የበታቾቻችን፣ ተከታዮቻችን፣ ካድሬዎቻችን በየደረጃው ለመርሆች፣ ለመመሪያዎችና ለራዕዮች የሚሰጡት ትርጓሜ የተሳሳተ ከሆነ፤ የሚሳሳተው ብሎም የሚጎዳው፣ አገር ሙሉ ሰው ነው፡፡ ስህተቱ እጅግ የከፋ የሚሆነው ደግሞ የሚሰጠውን መግለጫ ህዝብ አብራሩልኝ ሲል “እኔ ያልኩህን ብቻ ተቀበል” የምንል ከሆነ ነው፡፡ አንድም ያለዕውቀት አንድም በዕብሪት፣ ይህን ግትርነት ካሳየን አስከፊ ጥፋት ከመሆን አይዘልም፡፡ የመንግሥት ሠራተኛም ቢሆን የህዝብ አገልጋል እንጂ ገዢ ነኝ የሚል አስተሳሰብ ካለም አደገኛ ነው! አገርና ህዝብን መበደል ነው፡፡ ዋና ዋና መርሆቻችንና የፖለቲካ አቋሞቻችንን ከመመርመርና ቆም ብለን ከማየት ይልቅ በደመ-ነብስ መከተልና እንደቦይ ውሃ አብሮ መፍሰስ ከዚያም ይልቅ የበለጠ መጮህ፤ ቢያንስ የዋህነት ነው፡፡
አሌክሳንደር ፓፕ የተባለው ገጣሚ “በጭፍኑ መስማማት መዋሸት ነው” ይለናል /To blindly comply, is to lie/፡፡
በሀገራችን ተጠይቀው ያልተመለሱ፤ ተመልሰው ያላጠገቡ፤ ከናካቴው ያልተጠየቁ ወይም ለመጠየቅ የሚፈሩ፤ በርካታ የፖለቲካም፣ የኢኮኖሚም፣ የማህበራዊም፣ የባህልም ጥያቄዎች በልማድ ታጅለው ብዙ ጊዜ አልፏቸዋል፡፡ አንዳንዶቹ፤ ብንጠይቅ ማን ይመልስልናል በሚል ሰበብ፣ እንደተዳፈኑ የሚቀሩ ናቸው፡፡ አንዳንዶቹ ብንጠይቅ እንጠየቃለን በሚል ፍርሃት የሚዳፈኑ ናቸው፡፡ ጥቂቶቹ መጠየቅ እንዳለባቸው ሳናውቅ እንደቀለጡ የሚቀሩ ናቸው፡፡ አብዛኞቹ በምን ያገባኛልና በምን-ግዴ፣ ቸልታ የተሸፋፈኑ ናቸው፡፡ ዞሮ ዞሮ ሁሉም ጉዳት ሲያደርሱብን ማየታችን አልቀረም፡፡ በተናጠል የምናብጠለጥላቸውና የምንሸሙርባቸው፤ እንዲሁም በንቀት የምናንጓጥጥባቸው ግን፤ ሲደርሱብን እሪ የምንልባቸው፤ በርካታ የዕለት-ጉርስ የዓመት-ልብስ ተኮር አንገብጋቢ ጥያቄዎች እንደ ዐባይ ከዓመት ዓመት ይፈስሳሉ፡፡
“ከበሮ የተደለቀውን ያህል ይጮሃል” የሚለው ተረት፤ የመቺውን እንጂ የተመቺውን ድምፅ የማያስተጋባበት ሁኔታ ውስጥ ከሆነ ያለነው፣ የትርጓሜ ስህተት አለ ማለት ነው፡፡ ያ ደግሞ የጥቁሯን ላም ያህል አሳሳቢ ችግር ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ የበደሉንን ይቅር ማለት ብቻ ሳይሆን መጠየቅም መልካም ሥነ-ምግባር ነው! የከበሮ መቺውንም፣ የተመቺውን ከበሮም፣ ነገር ለማወቅ የጠያቂነት ባህል እናዳብር!!

Published in ርዕሰ አንቀፅ

አንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) በአባላቱና በደጋፊዎቹ ላይ የሚደርስባቸው ጥቃትና የሰብአዊ መብት ጥሰቶች ከጊዜ ወደ ጊዜ መባባሳቸውን ገለፀ፡፡
ከትላንት በስቲያ ፓርቲው በፅ/ቤቱ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ወቅት፤ ከ2003 አንስቶ በአባላቱና ደጋፊዎቹ ላይ የደረሱ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን በዝርዝር አቅርቧል፡፡ ፓርቲው “የሰብዓዊ መብት ጥሰት ሪፖርት” በሚል ባወጣው ሰነድ፤ ከተዘረዘሩ ጥቃቶች መካከል:- በድብደባ አካል ማጉደል፣ በህገወጥ መንገድ በቁጥጥር ስር ማዋል፣ ማሰቃየት፣ ማስፈራራትና መዛት እንዲሁም በማስገደድ መረጃ ከፓርቲያቸው እንዲያመጡ ማድረግ፣ የመኖሪያ ቦታን በህገወጥ መንገድ መበርበር፣ ይዞታና ንብረትን ያለ ካሳ ነጥቆ መውሰድ… የሚሉት ይገኙበታል፡፡
አቶ ደምሴ መንግሥቱና አቶ ገበየሁ ይርዳው የተባሉ የፓርቲው አመራሮች፤ በአባላትና ደጋፊዎች ላይ የሚደርሰው ጥቃት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ እንደመጣ ጠቁመው፣ ጥቃት የደረሰባቸው አራት አዛውንት አባላቶቻቸው ጉዳታቸውን በአካል በማሳየት በህገመንግስቱ እውቅና የተሰጣቸውን:- በህይወት የመኖር፣ የአካል ደህንነት እንዲሁም በህግ ፊት እኩል የመታየት ተብለው የተዘረዘሩት መብቶች መጣሳቸውን ገልፀዋል፡፡

Published in ዜና

ለቀጣይ ህክምና 60ሺህ ብር ተጠይቋል
ጋዜጠኞች ገንዘብ ለማሰባሰብ መክረዋል
ከተመሰረት ጥቂት ወራትን ያስቆጠረው የ “ኢትዮ-ምህዳር” ጋዜጣ ስራ አስኪያጅ ሚሊዮን ደግነው፣ ዋና አዘጋጅ ጌታቸው ወርቁ እና አዘጋጁ ኤፍሬም በየነ ማክሰኞ አመሻሽ ላይ ወደ ሀዋሳ የተጓዙት ለሽርሽር አልነበረም። በነጋታው ረቡዕ የፍ/ቤት ቀጠሮ ስለነበራቸው ነው፡፡
ከሁለት ሳምንት በፊት “ኢትዮ-ምህዳር”፤ ከሙስና ጋር በተያያዘ በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ዙሪያ በዘገበው ዜና ምክንያት፣ ዩኒቨርስቲው በጋዜጠኞች ላይ የ300ሺ ብር ክስ እንደመሰረተባቸው ይታወሳል። ጋዜጠኛ ኤፍሬም አብሯቸው የተጓዘው አንድም ዜናውን የሰራው እርሱ በመሆኑ፣ ተከራከሩ ቢባል ለፍ/ቤቱ በደንብ እንዲያስረዳ፣ ሁለትም የተከሳሽ ባልደረቦቹን የፍርድ ቤት ውሎ በአካል ተገኝቶ ለመዘገብ እንደነበር ዋና አዘጋጁ ጌታቸው ወርቁ ተናግሯል፡፡
“ማክሰኞ ማታ ራሱ ኤፍሬም አልጋ ፈላልጎ ያዘልን፤ ምክንያቱም የሀዋሳ ልጅ በመሆኑ ከተማዋን በደንብ ያውቃታል” ያለው ጋዜጠኛ ጌታቸው፤ ምሽቱም ሌሊቱም በጥሩ ሁኔታ እንዳለፈ ገልፆ፤ ረቡዕ ጠዋት 3 ሰዓት ላይ በቀጠሯቸው መሰረት ሲዳማ ዞን ከፍተኛ ፍ/ቤት መቅረባቸውን ይናገራል፡፡ ሆኖም በዘጠኝ ሰዓት ተመልሳችሁ ኑ ተባልን ይላል። “እኛ በፌደራል ደረጃ ተመዝግበን የምንሰራ በመሆናችን ጉዳያችንም በፌደራል ፍ/ቤቶች ይታይልን፤ እንደገና ዘጠኝ ሰዓት ለመምጣት አንችልም፤ ወደ አዲስ አበባ መመለስ አለብን” ብንልም የግድ ዘጠኝ ሰዓት እንድንመለስ ታዘዝን ብሏል ዋና አዘጋጁ፡፡
ከፍ/ቤት ወጥተው በእግራቸው ወደ መነሀሪያ ከተጓዙ በኋላ ሻይ የሚጠጡበት ቦታ ፈልገው አጭር የኤዲቶርያል ስብሰባ እንዳደረጉ የጠቆመው ጌታቸው፤ “በስብሰባችን የተነጋገርነው የጋዜጣው አብዛኛው አዘጋጆች እዚህ በመሆናችን እስከ ዘጠኝ ሰዓት ባለው ጊዜ ዞር ዞር ብለን ስራ እንስራ፤ ከተሳካልን ከከተማዋ ባለስልጣናት አንዱን የጋዜጣችን እንግዳ እናድርግ” በሚል ተስማማን ይላል ጌታቸው፡፡ ከዚያም የሀዋሳ ጋዜጠኛ ወደሆነ አንድ ጓደኛቸው ይደውላሉ፤ ማንን ብናናግር ይሻላል በሚል እንዲያማክራቸው፡፡ ጋዜጠኛ ጓደኛቸው ግን “ልጄ ታሞብኝ ፒያሳ አካባቢ መድሀኒት እየገዛሁ በመሆኑ፣ ባጃጅ ተሳፍራችሁ ፒያሳ ድረስ ከመጣችሁ እጠብቃችኋለሁ” ይላቸዋል፡፡ ዋና አዘጋጁና ስራ አስኪያጁ በቀጠሮው ሲስማሙ፣ ጋዜጠኛ ኤፍሬም ግን ደስተኛ እንዳልነበር ጌታቸው ተናግሯል፡፡ “ለምን እዚሁ አንጠብቀውም? የእኛ ወደ ፒያሳ መሄድ አልታየኝም” ብሎም ነበር፤ እንደ ጌታቸው ገለፃ፡፡
“ባክህ እንሂድ ጊዜ አናባክን ብየው፣ ፒያሳ ለመጫን ከተደረደሩት ባጃጆች ውስጥ በዥዋዥዌ መልክ ይንቀሳቀስ የነበረ ባጃጅ ላይ ቀድሜ ገባሁ ያለው ጌታቸው፤ ኤፍሬምም ደስ ሳይለው አብሮ ባጃጅ ውስጥ መግባቱን ይናገራል፡፡ “ባጃጁ በጣም ይበራል፤ ትንሽ እንደሄድን ኤፍሬም አሁንም “በቃ” እዚህ እንውረድና ማኪያቶ እየጠጣን እንጠብቀው” ቢልም ጆሮ አልሰጠነውም ነበር ብሏል ጌታቸው በፀፀት፡፡ እየበረረ የነበረው ባጃጅ የበለጠ ፍጥነቱን ሲጨምር “አንተ ቀስ በል! ቀስ በል! ሞተር መጣ፤” እያለው ሞተሩ የተሳፈሩበትን ባጃጅ በሀይል ገጨው፡፡
አደጋው የተከሰተው በግምት ወደ አምስት ሰዓት አካባቢ እንደሆነ ጌታቸው ተናግሯል፡፡
“ከዚያ በኋላ እኔ ራሴን እንደመሳት አድርጎኝ ስለነበር፣ ብዙም የሆነውን አላውቅም፤ ሰዎች ሊያነሱኝ ሲሞክሩ ግን አመናጭቃቸው ነበር” ሲል በወቅቱ የተፈጠረውን አሰቃቂ አደጋ ገልጿል፡፡ ሰዎች በሌላ ባጃጅ አሳፍረው አዳሬ ወደተባለ ሆስፒታል ሲወስዷቸው፣ አንድ እጁ መጎዳቱን ልብ እንዳለ የሚናገረው ጌታቸው፤ ስራ አስኪያጁ ሚሊዮን ደግሞ ደረቱ ላይ እንደተጐዳ አወቀ፤ የኤፍሬም ጉዳት ግን እጅግ ዘግናኝ ነበር ብሏል፡፡
“ኤፍሬም በደረሰበት አደጋ ከወገቡ በታች ሰውነቱን ማዘዝ አይችልም፤ የማጅራቱ ሰባተኛው አከርካሪ አጥንት ተሰብሯል” መባሉን ስሰማ ራሴን መቆጣጠር አቃተኝ” በማለት አስረድቷል፡፡
ከአዳሬ ሆስፒታል ወደ ሀዋሳ ሪፈራል ሆስፒታል ከተወሰዱ በኋላ ለጌታቸውና ለሚሊዮን የመጀመሪያ እርዳታ ሲደረግላቸው፣ በኤፍሬም መጎዳት የተደናገጡት የሀዋሳ ሪፈራል ሆስፒታል ዶክተሮች፤ ልጁ በአስቸኳይ አዲስ አበባ መሄድና ኮሪያ ሆስፒታል መግባት እንዳለበት ገልፀው፤ አንገቱ እንዳይነቃነቅ በጀሶ ካሰሩት በኋላ፣ በሆስፒታሉ አምቡላንስ ወደ አዲስ አበባ ኮሪያ ሆስፒታል ልከውታል፡፡
“አሁን ጥፋተኝነትና ፀፀት የሚሰማኝ የኤፍሬምን ስድስተኛ የስሜት ህዋስ መረዳትና ማንበብ ባለመቻሌ ነው” የሚለው ጌታቸው፤ “ከአንድም ሁለቴና ሶስቴ ወደ ፒያሳ የምናደርገውን ጉዞ ለመሰረዝና እኛን ለማሳመን ጥረት አድርጎ ነበር” ብሏል፡፡
ረቡዕ አመሻሽ ላይ ኮሪያ ሆስፒታል የገባው ጋዜጠኛ ኤፍሬም፤ ከወገቡ በታች ሰውነቱን ማዘዝም ሆነ ሽንቱን መቆጣጠር አይችልም ነበር፡፡ ከትላንት በስቲያ የቀዶ ህክም የተደረገለት ሲሆን፤ ከሌላ የሰውነቱ አካል አጥንት ተወስዶ አከርካሪው ላይ በተሰበረው አጥንት ምትክ ቢገባለትም ሰውነቱን የማዘዝም ሆነ ከዚህ በኋላ ቆሞ የመሄድ ተስፋ እንደሌለው ሀኪሞቹ ተናግረው የነበረ ቢሆንም እንደገና ሰፋ ያለ ቀዶ ህክምና ካደረገ በኋላ ከወገቡ በታችና እግሩ አካባቢ መስማት ጀምሯል፡፡ ለቀጣይ ህክምና 60ሺህ ብር መጠየቁንም ጋዜጠኛ ጌታቸው ገልጿል፡፡
ከፍተኛ ጉዳት የደረሰበትን ጋዜጠኛ ለማትረፍ ሆስፒታሉ እንዲያሲዙ የጠየቃቸውን ብር በአፋጣኝ ለማግኘት ፈተና እንደነበር የሚናገረው ጌታቸው፤ “ኢትዮ-ምህዳር” አዲስ ጋዜጣ በመሆኑና ብዙ ስላልተቋቋምን ተቸግሬ ነበር ብሏል - ጋዜጠኛ ጌታቸው ሀሙስ 11 ሰዓት ላይ ከበርካታ ጋዜጠኞች ጋር ባደረገው ውይይት፡፡ “ጋዜጠኞች ህይወታችን ለአደጋ የተጋለጠ ነው፤ ራሳችንን ከጥቃት ለመከላከል፣ በአደጋ ጊዜ ለመረዳዳትም ሆነ ለመሰል ጉዳዮች የሚያገናኘን አንድም መድረክ የለም” ሲል ለሙያ አጋሮቹ ንግግር ያደረገው ጋዜጠኛው፤ በሌሎቻችን ላይ አደጋ ላለማድረሱ ዋስትና ስለሌለን በቀጣይ ምን ብናደርግ ይሻላል ሲል ጠይቋል፡፡
በቅርቡ ከስደት የተመለሰውን ጋዜጠኛ ዳዊት ከበደን ጨምሮ በርካታ ጋዜጠኞች በስብሰባው ላይ የተገኙ ሲሆን ጋዜጠኛ ኤፍሬም በየነ ከጉዳቱ እንዲያገገም ለመመኘት የአንድ ደቂቃ የህሊና ፀሎት ተደርጓል፡፡ ስብሰባውን ያስተባበሩት የ “ነጋድራስ” ጋዜጣ ዋና ስራ አስኪያጅ የነበሩት አንጋፋው ጋዜጠኛ አያሌው አስረስ ናቸው፡፡
የ27 አመቱ ጋዜጠኛ ኤፍሬም፤ ከባህርዳር ዩኒቨርስቲ በ1999 ዓ.ም በጆርናሊዝምና ኮሙዩኒኬሽን ዲግሪውን ከያዘ በኋላ ሥራ የጀመረው በነጋድራስ ጋዜጣ ላይ ነበር፡፡ ከጋዜጠኛ ጌታቸው ንግግር በኋላ ጋዜጠኞች የተለያዩ አስተያየቶችን ሰንዝረዋል፡፡
“በአሁኑ ሰዓት ቅድሚያ ሰጥተን መረባረብ ያለብን ጋዜጠኛ ኤፍሬም ላይ ነው” ያሉት ጋዜጠኞቹ፤ ውጭ አገር ሄዶ መታከም ካለበት፣ባለበትም ሆኖ የሚታከምበትና የሚድንበት መንገድ ካለ ሁላችንም በየፊናችን ገንዘብ በማሰባሰብና ስፖንሰር በማፈላለግ መትጋት አለብን” በማለት ስምምነት ላይ ደርሰዋል፡፡
በአደጋው መጠነኛ ጉዳት የደረሰባቸው ጋዜጠኛ ጌታቸው ወርቁና ማሊዮን ደግነው በፍ/ቤቱ ቀጠሮ መሰረት ዘጠኝ ሰዓት ላይ የቀረቡ ሲሆን ፍ/ቤቱ፤ ያቀረቡትን አምስት የክስ መቃወሚያዎች ውድቅ በማድረግ ተከራከሩ በሚል ለህዳር 10 ቀን 2006 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
አደጋውን ያደረሱት የባጃጅና የሞተር ሳይክል ሹፌሮች ዘለው እንደወረዱና ተይዘው ፖሊስ ጣቢያ ገብተው እንደነበረ የአይን እማኞች ገልፀዋል፡፡ የአደጋውን መንስኤ ለማጣራት ጉዳዩን ወደያዙት የከተማዋ ትራፊክ ፖሊሶች ደጋግመን ብንደውልም ስልካቸውን ባለማንሳታቸው ምላሻቸውን ማካተት አልተቻለም፡፡

Published in ዜና

የበሽታውን ምንነት ለማወቅ ናሙና ተልኮ ምርመራ እየተደረገ ነው፡፡
የድሬዳዋ ከተማ በጉንፋን መልክ በሚከሰት የበሽታ ወረርሽኝ ሥጋት ላይ ነች፡፡ በዚህ ወር ብቻ በበሽታው የተያዙ 2ሺ ሰዎች ተመዝግበዋል፡፡
ከወባ ጋር ተመሣሣይነት አለው በተባለው በዚህ በሽታ የተያዙ ህሙማን፣ በድል ጮራ ሪፈራል ሆስፒታልና በተለያዩ የከተማዋ ክሊኒኮችና የጤና ተቋማት ምርመራና ህክምና እየተደረገላቸው መሆኑን ምንጮች ለአዲስ አድማስ ጠቁመዋል፡፡ በበሽታው ተይዘው ህይወታቸው ያለፈ ህሙማን እንዳሉ ምንጮች ቢጠቁሙም፤ የከተማው ጤና ቢሮ ለሞት የተዳረጉ ህሙማን መኖራቸውን አላውቅም ብሏል፡፡
የድሬዳዋ አስተዳደር ጤና ቢሮ ኃላፊ አቶ ካሣሁን ኃ/ጊዮርጊስን ስለ ጉዳዩ ጠይቀናቸው፤ ችግሩ ወረርሽኝ በሚባል ደርጃ ተከስቷል ለማለት እንደማይቻልና ገና ስለሁኔታው ማጣራት እየተካሄደ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ወቅቱ የወባ በሽታ የሚስፋፋበት ወቅት ከመሆኑ አንፃር በአካባቢው ጠበቅ ያለ ዝግጅትና ቁጥጥር እየተካሄደ መሆኑን የጠቆሙት አቶ ካሣሁን፤ በዚህ ሁኔታ ውስጥ ከወትሮው የተለየ ቁጥር ያላቸው ህሙማን መመዝገብ መቻላቸው ሁኔታውን ትኩረት እንድንሰጥበት አስገድዶናል ብለዋል፡፡
በዚህ ወር ብቻ 2ሺ ሰዎች መመዝገባቸውንም አቶ ካሣሁን ተናግረዋል፡፡ የበሽታውን ምንነትና የመተላለፊያ መንገዱን ለማወቅ ናሙናውን ወደ አዲስ አበባ የጤናና ሥነ-ምግብ ምርምር ኢንስቲቲዩት (ፓስተር) መላኩንና ውጤቱን በመጠባበቅ ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ የበሽታው ምንነት ባልታወቀበት ሁኔታ ግን ዝርዝር መረጃ ለመስጠት እንደሚቸገሩም አቶ ካሳሁን ጨምረው ገልፀዋል፡፡ ሁኔታውን አስመልክቶ የሚሰበሰቡ መረጃዎችን በየዕለቱ ወደ ፌደራል ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር እየላኩ መሆናውን እና የበሽታውን ምንነትና የመተላለፊያ መንገዱን በቀጣዩ ሳምንት መረጃው ተጠናቆ እንደደረሳቸው ይፋ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል፡፡
ከሸንሌና ሔረር ተነስቶ ወደ ከተማዋ ተዛምቷል የሚል ጥርጣሬ ባሳደረው በዚህ በሽታ የተያዙ ሰዎች ከፍተኛ የራስ ምታት፣ ማንቀጥቀጥና ነስር እንደሚታይባቸውና በአሁኑ ወቅት በከተማዋ የሚታየው ከፍተኛ ሙቀት ለችግሩ መፍጠር ምክንያት ሊሆን ይችላል የሚል ሥጋት እንዳላቸውም ምንጮቻችን ጠቁመዋል፡፡

Published in ዜና
Saturday, 02 November 2013 10:39

በጂጂጋ ፍተሻው ተጠናክሯል

ከቀኑ 10 ሰዓት በኋላ ባጃጆች አይሰሩም
ከምሽቱ አራት ሰዓት በኋላ ሰዓት እላፊ ታውጇል
በኢትዮጵያ ሶማሊያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ከባለፈው ረቡዕ ጀምሮ እስከ ህዳር 30 ድረስ የመንግስት መስሪያ ቤቶች መዘጋታቸውን ምንጮች ገለፁ፡፡ በከተማው የሚገኙ 2300 ያህል ባጃጆችም ከቀኑ አስር ሰዓት በኋላ ስራ እንዳይሰሩ መታገዳቸውን ምንጮች የገለፁ ሲሆን ከምሽቱ አራት ሰዓት በኋላም ሰዓት እላፊ ስለታወጀ በከተማው ነዋሪዎች ከአራት ሰዓት በኋላ እንደማይንቀሳቀሱ የአካባቢው ነዋሪዎች ገልፀዋል፡፡
“በምሰራበት የመንግስት መስሪያ ቤት ዋና የስራ ሂደት ባለቤት ነኝ” ያሉ አንድ ግለሰብ፤ የመንግስት ሰራተኛ ስራውን ትቶ በከተማው ካሉ ልዩ ሀይሎች ጋር በመሆን ሰዎችን ወደመፈተሽ ስራ መግባቱን ተናግረዋል። አንድ ሰው ከከተማው አንድ ቦታ ተነስቶ የሚፈልግበት እስኪደርስ ቢያንስ አምስትና ስድስት ጊዜ ሊፈተሽ ይችላል ያሉት እኒሁ የመንግስት ሠራተኛ፤ ለከተማው ፀጥታ ሲባል ፍተሻው ተገቢ ቢሆንም ለ40 ቀን የመንግስት ስራ ቆሞ ሰራተኛውን ፈታሽ ማድረግ ግን አግባብ እንዳልሆነና እንደሚቃወሙት ገልፀዋል።
በቅርቡ የሚከበረውን የብሔር ብሔረሰቦች በዓል በጅጅጋ ለማክበር የሚደረገውን ዝግጅት ተከትሎ አካባቢውን ለመጠበቅ በሚል ፍተሻው ቢጠናከርም የመንግስት ሰራተኞች ለ40 ቀን ስራ ትተው ለፍተሻ መሰማራታቸው አግባብ እንዳልሆነ ሌላው የከተማዋ ነዋሪ ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡
“የብሄር ብሄረሰቦች በዓል በልዩነታችን ውስጥ አንድነታችንን የምናይበት እና የምንከባበርበት እንጂ ዜጎች ስራ አቁመው ወዳልተፈለገ ስራ የሚሰማሩበትና የሚሰቃዩበት መሆን የለበትም” ሲሉ አማረዋል፤ ግለሰቡ፡፡ “አንድ ባጃጅ ለሹፌሩን እና ለባለቤቱ ቤተሰቦች ገቢ የሚያስገኝ በመሆኑ ከ10 ሰዓት በኋላ እንዳይሰሩ መከልከሉን እንቃወማለን” ያሉት ስማቸውን ያልገለፁ ሌላው የመንግስት ሰራተኛ፤ ጉዳዩን የፌዴራል መንግስት አውቆት እልባት እንዲያገኝና የክልሉ መንግስት ስህተቱን እንዲያርም አሳስበዋል፡፡
“እኔ የመንግስት ሰራተኛ ባለመሆኔ የመንግስት መስሪያ ቤት ስለመዘጋቱ የማውቀው የለም” ያሉት አንዲት የከተማዋ ነዋሪ፤ ባጃጆች ከአስር ሰዓት በኋላ ስራ እንደማይሰሩና ሰዓት እላፊ መታወጁን ግን እንደሚያውቁ ተናግረዋል፡፡ “በአጋጣሚ መታወቂያ ሳትይዢ ከቤት ከወጣሽ ታፍሰሽ ወደ እስር ቤት ትወሰጃለሽ” ያሉት ሌላው ነዋሪ፤ ያለፖሊስ ማዘዣ ቤቶች ሲፈተሹና ሲበረበሩ ያድራሉ፤ ለዚሁ ስራ ለአንድ ወር ሲሰለጥኑ የነበሩ ልዩ ሀይሎች ተሰማርተዋል ሲሉ ተናግረዋል፡፡
“ለ40 ቀናት የመንግስት መስሪያ ቤቶች መዘጋት እንዳለባቸው ሰብስበው የነገሩን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አብዲ መሀመድ ኡመር ናቸው” ያሉት አንድ የመንግስት ሰራተኛ፤ የብሄር ብሄረሰቦችን ቀን ማክበር የመንግስት ብቻ አለመሆኑን ከተስማማን በኋላ ሁላችሁም ወገባችሁን አስራችሁ ፍተሻ ቀጥሉ በሚል ስም ተመዝግቦና ቁጥጥር እየተደረገ የመንግስት ሰራተኛው በቡድን ተከፍሎ ፍተሻውን ተያይዞታል ብለዋል፡፡
የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ አብዲአዚዝ መሀመድ በበኩላቸው፤ መረጃው የተሳሳተ መሆኑን ገልፀው “እንዴት የመንግስት መስሪያ ቤት 40 ቀን ሙሉ ይዘጋል” ሲሉ ጠይቀዋል፡፡
የብሔር ብሔረሰቦችን በዓል አከባበር በተመለከተ፣ የመንግስት ሠራተኞች በትርፍ ሰዓታቸው ለሕዝቡ የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርት አገልግሎት ይሰጣሉ ካሉ በኋላ፤ “ፍተሻ አለ፣ ባጃጅ አይሰራም፣ ሰዓት እላፊ ታውጇል የሚባለው ከእውነት የራቀ ነው” ሲሉ አስተባብለዋል፡፡

Published in ዜና
Page 19 of 19