• በሂደቱ ተሣታፊ እንሆናለን ብለዋል
  • የመወዳደሪያ ምልክት እየወሰዱ ነው

      ተቃዋሚ ፓርቲዎች በምርጫው ስለመወዳደራቸው እርግጠኛ ባይሆኑም  በሂደቱ ተሳታፊ እንደሚሆኑ እየገለፁ ነው፡፡
“ከዚህ ቀደም በተካሄዱ ብሔራዊ ምርጫዎች ከተቃዋሚ ፓርቲዎች ይነሱ የነበሩ ቅሬታዎች ያልተፈቱ ቢሆንም በ2007 ሀገር አቀፍ ምርጫ ሂደት ውስጥ እንሳተፋለን” ሲሉ አዲስ አድማስ ያነጋገራቸው የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች ገልፀዋል፡፡ ፓርቲዎቹ የመወዳደሪያ ምልክታቸውን ለምርጫ ቦርድ በማቅረብም ላይ ናቸው፡፡
አባላቱ ለምርጫው መወዳደሪያ ምልክት እንዲጠቁሙት በጽ/ቤቱ በር ላይ ማስታወቂያ የለጠፈው የሠማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት፤ ሠላማዊ ሠልፍና ህዝባዊ ስብሰባ ማድረግን ጨምሮ መሠረታዊ የሚባሉ የፖለቲካ ምህዳር መጥበብ ችግሮች ባለበት ስለምርጫ ጉዳይ ማውራት አስቸጋሪ መሆኑን ገልፀው ፓርቲያቸው በዚህ ሁኔታ ውስጥም ሆኖ የ2007 ሀገር አቀፍ ምርጫ ሂደት አካል ለመሆን እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

በምርጫው ማንኛውም እንቅስቃሴ ውስጥ እንሣተፋለን” ያሉት ሊቀመንበሩ፤ ይህ ማለት በሂደት በምርጫው አንወጣም ማለት አይደለም፤ እስከመጨረሻው በሂደቱ ተጉዘን የማያስኬድ መስሎ ከታየን ከምርጫው ራሳችንን ልናገልል እንችላለን ብለዋል፡፡ የመላው ኢትዮጵያውያን አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ፕሬዚዳንት አቶ ማሙሸት አማረ በበኩላቸው፤ በቀጣዩ ምርጫ ሊያሳትፋቸው የሚችለውን የመወዳደሪያ ምልክት ከቦርዱ እንደሚወስዱ አስታውቀው፤ በምርጫው ፍትሃዊነትና አሣታፊነት ላይ ከመንግስት እና ከምርጫ ቦርድ ጋር መምከር እንፈልጋለን ብለዋል፡፡

“አሁን ባለው ሁኔታ የቀጣዩን ምርጫ ባህሪ ከወዲሁ መገምገም አይቻልም” ያሉት አቶ ማሙሸት፤ ምርጫውን ማሸነፍ ይቻላል አይቻልም የሚለውም ከሂደቱ ተነስተን የምናየው ይሆናል ብለዋል፣ ፓርቲያቸው በምርጫው ሂደት እስከ መጨረሻው ሊሳተፍ እንደሚችል በመጠቆም፡፡ የመድረክ አመራር ዶ/ር መረራ ጉዲና በበኩላቸው፤ ፓርቲያቸው በምርጫው በሚደረጉ ዝግጅቶች ተሣታፊ እንደሚሆን እንጂ ተወዳዳሪ ሆኖ ለመቅረብ እንዳልወሰነ ተናግረዋል፡፡ ዶ/ር መረራ፤ ህብረተሰቡን ለምርጫው የማዘጋጀት፣ ምልክት መምረጥ የመሳሰሉትን ፓርቲያቸው እንደሚከውንና ምርጫው ከቅርጫነት ያለፈ ትርጉም ያለው እንዲሆን በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ውይይቶችንና ድርድሮችን ማድረግ እንደሚፈልግ አስታውቀዋል፡፡
 መድረክ በምርጫው ሂደት ተሣታፊ ሆነ ማለት ይወዳደራል ማለት እንዳልሆነ የጠቆሙት ዶ/ር መረራ መወዳደሩን የምንወስነው በመጨረሻው ሰአት ነው ብለዋል፡፡ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት አባል የሆነው የመላ ኢትዮጵያውያን ብሔራዊ ንቅናቄ (መኢብን) ሊቀመንበር አቶ መሳፍንት ሽፈራው በበኩላቸው፤ የፓርቲያቸው ብሔራዊ ምክር ቤት ወደምርጫው በመግባት ጉዳይ ገና ውሣኔ ያላሳለፈ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ሌላው የጋራ ምክር ቤቱ አባል የኢትዮጵያውያን ራዕይ ፓርቲ (ኢራፓ) በ2007 ዓ.ም ሀገራዊ ምርጫ በመርህ ደረጃ ሙሉ ለሙሉ ተሣታፊ እንደሚሆንና በምርጫውም ተወዳዳሪ ሆኖ እንደሚቀርብ ፕሬዚዳንቱ ለአዲስ አድማስ አረጋግጠዋል፡፡ ፓርቲያቸው በሠላማዊ ትግል በምርጫ አሸንፎ ሃገር መምራት ይቻላል የሚል ፖሊሲ እንዳለው የጠቀሱት አቶ ተሻለ ሰብሮ፤ በ2007 ምርጫ ተወዳዳሪ ሆኖ መቅረቡ ምርጫው ምቹ ነው ከሚል ድምዳሜ እንዳልሆነ አስረድተዋል፡
 አሁንም ከፍተኛ ለምርጫ እንቅፋት ናቸው ተብለው በፓርቲዎች የተጠቆሙ ችግሮች ውይይት አልተካሄደባቸውም፣ ቀና ምላሽም አልተሰጣቸውም ብለዋል፡፡
 በቦርዱ የሚሠጡ ስልጠናዎች እንዲሁ ስልጠና ተሰጥቷል የሚል ሪፖርት ለማቅረብ ካልሆነ በስተቀር በስልጠናው የሚነሱ ችግሮች መፍትሔ አልባ ናቸው ሲሉ አቶ ተሻለ አማረዋል፡፡ እንደመርህ ወደምርጫው ውድድር መግባትን እንቀጥላለን ያሉት ፕሬዚዳንቱ ፤ በወቅቱ የሚፈጠሩ ክስተቶች ፓርቲው በምርጫው ተወዳዳሪ ሆኖ የመዝለቁን ጉዳይ ይወስናሉ ብለዋል፡፡
“ዋናው ጉዳይ ምርጫውን እንዴት ተአማኒ ማድረግ ይቻላል” የሚለው ነው መነሳት ያለበት” የሚሉት አቶ ተሻለ ሠብሮ፤ “በርካታ ጥያቄዎች ባልተመለሱበት ተአማኒ ይሆናል ብሎ ከወዲሁ መናገር አይቻልም” ብለዋል፡፡ “የህሊና እስረኞች ይፈቱ” በሚል የማህበራዊ ሚዲያ ዘመቻ እያካሄደ ያለው አንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ፓርቲ በበኩሉ ብሔራዊ ምክር ቤቱ በምርጫው ፓርቲው ይሳተፍ ዘንድ መወሰኑን አስታውቋል፡፡
ፓርቲው ቀደም ብሎ ለጋዜጠኞች በሰጠው መግለጫ ወደ ምርጫው ተሣታፊነት መግባቱ በምርጫው መሳተፍ የሚያስችል ምቹ ሁኔታ መኖሩን እንደማሳይ ጠቁሞ የምርጫ ምህዳሩ በሚሰፋበት ሁኔታ ላይ አበክሮ እንደሚሰራ አስታውቋል፡፡
ምርጫ ቦርድ  ከህዳር 15 ቀን 2007 ዓ.ም ጀምሮ ፓርቲዎች የመወዳደሪያ ምልክታቸውን እየወሰዱ መሆኑን ጠቁሞ እስከ ረቡዕ ዕለት ብቻ 15 ተቃዋሚ ፓርቲዎች የመወዳደሪያ ምልክታቸውን መውሰዳቸውን የቦርዱ የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ደምሰው በንቲ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡    

Published in ዜና
Saturday, 29 November 2014 10:37

ፈተና ሲርቅ ይቀላል?


በዚች ጠባብ ዓለም
መቼም አያጋጥም የለም
    ያንድ ጓደኛዬን ወንድም፣ ለፈተና ላዘጋጀው
    እስቲ ማትሪክ ይቅናው ብዬ፣ ትምህርቱን በወግ ላስጠናው
    ለፍቼ  አንድ ዓመት ሙሉ፣ በል ይቅናህ? ብዬ ሸኝቼው
    ሞራል ባርኬ ሰጥቼው
    ያለኝን ዕውቀት ለግሼው፡፡
    አመስግኖኝ ሄደ ፈጥኖ፣ የጭንቁን ቀን ሊጋተረው!
    መቼም የየኑሮው ፍልሚያ፣ ግቡ ፈተናን ማለፍ ነው!
ዛሬ ጊዜው የእርም ቀን ነው
“ይቅናህ!” እንጂ ሰው ቃል የለው
ያውም ደጉ ቢገኝ እንጂ፣ ልቡ እንደኪሱ ባዶ ነው!
ፈተና መፈተን በቀር
ማለፍ ጠቦ እንደገነት በር
ስንቱ ደጁ ሲንፈራፈር
ይታያል በየክፍሉ ፈር፡፡
*      *     *
የማትሪክ ፈተና አለቀ … ያስጠናሁት ልጅ አልመጣም
አንድ ወር ሁለት ወር አለፈ …. አጅሬ ግን ዝር አላለም!
“የዛሬ ልጅ!” አልኩ አዝኜ … ቅስሜን ቢቀጨኝ ድርጊቱ፡፡
“አይ ወጣቱ!”
ከበደኝ ቀለለኝ ሳይል … ምስጋና እንኳ መሰሰቱ!
*      *     *
አንድ ሶስት ወር አለፈና
ስጓዝ ባንድ አውራ ጎዳና
ያን ያስጠናሁትን ወጣት
ፊት ለፊት ባገኘው ድንገት
ቀልቡ ከላዩ ረግፎ፣ ዐይኑ ሲፈጥጥ አየሁት
“ኧረ አይዞህ” “አይዞህ አይዞህ”፣ አልኩት በቅን ለማፅናናት
“ያለፈው አልፏል እንግዲህ፣ እንዳይለምድህ ለወደፊት
እንደው የሆነስ ሆነና፣ ፈተናውስ እንዴት ነበር?”
ብዬ አርግቤ ብጠይቀው፣
ተንፍሶ ቁና ቁና
ጥቂት አየር ወሰደና
“አሁን ቀለል እያለኝ መጥቷል!” ብሎ መለሰ ወጣቱ
ይሄ ነው ጊዜው ክፋቱ!
ፈተናውን ሸሸው እንጂ፣ አይቀርለትም ውጤቱ!
ለካስ እየራቁት ሲኬድ፣ ፈተና ይቀላልሳ  
ሲጨብጡት ሲቀርቡት ነው፣ ህይወት ጭንቁ መቶ - ታምሣ
ቸል ብለው ሲቀመጡ፣ እየረሳሱት ሲሄዱ
እጅግ ከባዱም ፈተና፣ ይደበዝዛል ጣር ጉዱ!
ክፉ - ጉድ ሲርቅ ይረግባል
እያደር ቀን ሲገፋ ግን፣ የጠፋ መስሎ ያጠፋል!
*      *     *
እንደዚህ ነው ፈተናችን፣
የዛሬው ቀሳፊ ዘመን!
የሰከነ ልብ ላለው፣ የሰከነ ኑሮ ላሻ
ለየቀኑ ክቡር ህይወት፣ ንፁህ ተስፋን መጠንሰሻ
ለሰው ቅን ማሰብ ነው ደጉ፣ አገር በውል መፈወሻ!
የየፈተናችን ሀቁ
መስራትና ወገን ማዳን፣ እውነት መናገር ነው ጭንቁ፤
ቀርቦ ማየት ነው ራቡ፣ ሰውን ማስታመም ነው ሰቁ!!
የወገናችን ጭንቅ ቀን፣ ምጡ ምንም ቢጎነጎን
አጥንተን ማለፍ ነው እንጂ፣ ፈተናን መሸሽ አይጠቅመን!
ዛሬ የሚቀስፈን ህመም፣ ያገር ህመም ሰቆቃችን
በተስፋ አቅም ይሸነፋል፣ በልባም ልጅ ብርሃን ቀን
ፈተናውን መጋተር ነው፣ ማጥቃትና መከላከል
ያኔ ነው የህመማችን፣ ፈተናው ቀለለ እሚባል!!
ባይቀናን ብንወድቅም እንኳ ዳግም መፈተን አለብን
ማጥናትና መጥናት እንጂ፣ የትም አንደርስም ተሰደን፡፡
(ከችግር ለማምለጥ ችግር ውስጥ ለሚገቡ ወገኖቼ)
ታህሣሥ 28 1995 ዓ.ም

Published in ጥበብ

     ብረት ወይም አይረን ለሰውነታችን ከሚያስፈልጉ ንጥረነገሮች መካከል አንዱና ዋነኛው ነው፡፡ በተመሳሳይ አንዲት ሴት ስታረግዝ ጤንነቷ የተሟላ እንዲሆን ከሚያስችሉ ንጥረ ነገሮች መካከል አንዱ አይረን ወይም ብረት ነው፡፡
በዛሬው ፅሁፋችን አንዲት ሴት በሰውነቷ ሊኖር የሚገባው የብረት መጠን፣ ለእናቲቱ እንዲሁም ለፅንሱ የሚኖረው ጠቀሜታ፣ በማነሱ ሊከሰቱ የሚችሉ የጤና እክሎች እንዲሁም ሊደረግ የሚገባውን ጥንቃቄ ከባለሙያ ያገኘነውን ምላሽ ጨምረን እንዲህ ልናስነብባችሁ ወደናል፡፡
ዶክተር ሊያ ታደሰ የማህንና ፅንስ ሕክምና እስፔሻሊስት ናቸው፡፡ በአጠቃላይ ብረት ለሰውነታችን የሚኖረውን ጠቀሜታ እንዲህ ሲሉ ይገልፁታል፡፡
“...አይረን ወይም ብረት ለሰውነታችን ህዋሶች በጣም ወሳኝ የሆነ ንጥረነገር ነው፡፡ በዋነኛነት በቀይ የደም ሴሎች ላይ ሄሞግሎቢን የሚባል ኦክስጅን በሰውነታችን ውስጥ እንዲመላለስ የሚያደርግ ህዋስ አለ፡፡ ይህ ህዋስ ኦክስጅንን የሚያመላልሰው አይረን ወይም ብረት በተሰኘው ንጥረ ነገር አማካኝነት ነው፡፡ ስለዚህ በሰውነታችን ላይ በቂ የሆነ ኦክስጅን እንዲኖር የሚያደርገው ይህ ንጥረነገር ነው ማለት ነው፡፡ በተጨማሪም ሴላችን ውስጥ ማይቶኮንድሪያ የሚባል ኢነርጂ ሴል ወይም power house አለ እዛም ውስጥ ደግሞ ወሳኝ የሆነ ስራ አለው ስለዚህ ባጠቃላይ ብረት ለሰውነታችን ወሳኝ የሆነ ንጥረ ነገር ነው፡፡”
ከላይ የተገፀለው አይረን ወይም ብረት በማንኛውም ሰው ላይ የሚኖረው ጠቀሜታ ሲሆን አንዲት ነብሰጡር ሴት በእርግዝና ወቅት የብረት ንጥረነገር በበቂ ሁኔታ በሰውነቷ ውስጥ መኖሩ ለእናቲቱ ብሎም ለፅንሱ የሚኖረው የተለየ ጠቀሜታ እንዳለ ዶክተር ሊያ ይልፃሉ፡፡
“...በእርግዝና ወቅት የሰውነታችን የአይረን ፍላጎት ይጨምራል፡፡ ይህም የራሱ የሆነ ምክንያት አለው በአንደኛ ደረጃ ፅንሱ በምያድግበት ግዜና እርግዝናው እየገፋ በሚሄድበት ወቅት ከሰውነታችን የሚጠቀመው የአይረን መጠን አለ፡፡ አንደኛው ምክንያት እሱ ነው ሁለተኛው ደግሞ በእርግዝና ግዜ የሰውነታችን የደም መጠን ይጨምራል፡፡ ከዛ ውስጥ የተወሰነውን የሚይዙት የደም ሴሎች ሲሆኑ ፕላዝማ የምንለው የደም ሴል የሌለው የደም ክፍሉም ይጨምራል ነገርግን የሚጨምረው በእኩል መጠን እይደለም ይህም ማለት የደም ሴሉቹ ከደም መጠኑ እኩል አይጨምሩም ስለዚህ dilute የመሆን እድላቸው ከፍተኛ ነው፡፡ በተጨማሪ ደግሞ ፅንሱና የእንግዴልጁ ተጨማሪ አይረን ስለሚፈልጉ እነዚህ ነገሮች የሰውነታችን የአይረን ፍላጎት እንዲጨምር ያደርጉታል፡፡”
ይህ ንጥረነገር በሰውነታችን ያለው መጠን አንሶ ሲገኝ አኒሚያ ወይም በተለምዶ የደም ማነስ የምንለውን ችግር ሊያስከትል ይችላል ነግር ግን እንደ ባለ ሙያዋ አገላለፅ ሁሉም የደም ማነስ ችግሮች የሚከሰቱት ከብረት እጥረት የተነሳ ነው ለማለት አይቻልም፡፡
“...በሰውነታችን ያለው የአይረን ማነስ ደም ማነስ የምንለውን ችግር ያስከትላል ነገርግን ደም ማነስ ሁልግዜም በአይረን እጥረት የሚከሰት ነው ማለት አይቻልም በሌሎች የተለያዩ ምክንያቶች ደም ማነስ ሊከሰት ይችላል፡፡ ግን ብዙውን ግዜ በተለይ በእርግዝና ወቅት አብዛኛው የደም ማነስ ምክንያት  በተለይ ደግሞ እንደኛ አይነት ታዳጊ በሆኑ ሀገሮች ላይ የተለመደው ከአይረን እጥረት የሚመጣው የደም ማነስ ነው፡፡”
ደም ማነስ መኖሩ በምን ይታወቃል ለሚለው ጥያቄ ዶ/ር ሊያ ሲመልሱ...
“...ደም ማነስ መኖሩን ለማወቅ የተለያዩ ምርመራዎቸ ያስፈልጋሉ፡፡ ለምሳሌም የደም ምርመራ ለምሻሌ ምኄሞግሎቢን መፀን ምጵበ ውስጥ የአይረን መጠን የመሳሰሉትና የአይነ ምድር  ምርመራ በማድረግ ማወቅ ይቻላል፡፡”     
በፈረንጆቹ 2005 በሀገራችን የተደረገ አንድ ጥናት እንደሚያሳየው ከሶስት ሴቶች መካከል አንዷ በአይረን እጥረት ምክንያት ለሚከሰት የደም ማነስ ተጋላጭ ነች፡፡ ለመሆኑ የሄሞገግሎቢን ምርመራ ውጤት አተረገጓጎም ምን ይመስላል?
“...እርጉዝ ላልሆነች ሴት normal የሚባለው ከአስራ ሁለት በላይ ነው፡፡ በእርግዝና ወቅት ደግሞ ወደ አስራ አንድ ዝቅ ይላል፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ቀይ የደም ሲል እንደገለፅኩት በእርግዝና ወቅት ከደማችን መጠን መጨመር ጋር ተያይዞ የደም ማነስ ስለሚኖር ነው፡፡ ስለዚህ በሰውነታችን ያለው የአይረን መጠን ከአስራ ሁለት እስከ ስምንት ግራም (ፐር ዴሲሊትር) ከሆነ መጠነኛ የደም ማነስ አለ ማለት ነው፡፡ ከስምንት እስከ ስድስት ከሆነ ደግሞ የደም ማነሱ መካከለኛ ሊባል ይችላል፡፡ ነገርግን ከስድስት በታች ከሆነ የደም ማነሱ እጅግ ከፍተኛ ስለሚሆን ደም መሰጠት የሚያስፈልግበት ሁኔታ ሊፈጠር ይችላል፡፡”
በደማችን ውስጥ ያለው የሄሞግሎቢን መጠን መቀነስ ለደም ማነስ አንዱ ማሳያ ሊሆን ይችላል፡፡ ይህም በሰውነታችን ውስጥ ያለው የአይረን ንጥረነገር ዝቅተኛ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ የሚከሰት ነው፡፡ በዚህም የተነሳ የተለያዩ የጤና ችግሮች ሊከሰቱ እንደሚችሉ ዶክተር ሊያ ይገልፃሉ፡፡
“...እናትየው ላይ ሊከሰቱ የሚችሉት ችግሮች እንደ አጠቃላይ የደም ማነሱ መጠን ይለያል ለምሳሌ የደም ማነሱ መጠነኛ ከሆነ  እንደ የልብ ምት መጨመር፣ መድከም እንዲሁም ማዞር የመሳሰሉት ችግሮች ይኖራሉ፡፡ የደም ማነሱ ከፍተኛ ከሆነ ግን የሰውነት ማበጥ ከዛም አልፎ የልብ ድካም ሊያስከትል ይችላል፡፡ ይህ እንግዲህ በእርግዝናው ወቅት ያለው ነው፡፡ ነገር ግን ከባዱ ችግር የሚመጣው በወሊድ ወቅት ነው፡፡ ማንኛዋም ሴት በወሊድ ወቅት ከፍተኛ የሆነ የደም መፍሰስ ሊያጋጥማት ይችላል ነገር የደም ማነስ ያላት ሴት ይህንን መቋቋም አትችልም ይህ ደግሞ እስከ ሞት ሊያደርሳት ይችላል፡፡ እንደሚታወቀው በወሊድ ግዜ የሚኖር የደም መፍሰስ አንዱና ትልቁ የእናቶች ሞት ምክንያት ነው፡፡ ፅንሱን በሚመለከት ደግሞ ፅንሱ ክብደቱ አነተኛና እድገቱም ዘገምተኛ እንዲሆን ወይም በበቂ ሁኔታ እንዳያድግ ሊያደርግ ይችላል አንዳንዴ ደግሞ ካለቀኑ ምጥ እንዲጀምርም ሊያደርግ ይችላል ከዛ ውጪ ልጁ ሲወለድም የደም ማነስ ያለበት ሆኖ ሊወለድ ይችላል፡፡”  
አንዲት እርጉዝ ሴት ይህን መሰል ችግሮች እንዳያጋጥማት በምን መንገድ ልትከላከል ትችላለች? ብለን ላነሳንላቸው ጥያቄ ተከታዩን ሰፋ ያለ ሞያዊ ማብራሪያ ሰጥተውናል፡-
“...የመጀመሪያዎቹ ሶስት ወራት ብዙ የብረት መጠን ላያስፈልጋት ይችላል ነገርግን  ከዛ በኋላ በተለይ እርግዝና እየገፋ ሲመጣ በፊት ከሚያስፈልጋት ስምንት ወይም ዘጠኝ እጥፍ  በላይ ሊያስፈልግ ይችላል፡፡ በዚህም ምክንያት ማንኛዋም እርጉዝ ሴት ከምግብና ከምግብ በተጨማሪ ደግሞ icon supplement እንድትወስድ የሚመከረው ለዚህ ነው ምክንያቱም ከምግብ  የምታገኘው አይረን በእርግዝና ወቅት ያለውን የሰውነት ፍላጎት አያሟላም፡፡ ስለዚህ ከምግብ በተጨማሪ  ሌሎች እንደ ፎሊክ አሲድ ያሉ ንጥረ ነገሮች አብረው መሰጠት አለባቸው፡፡ ፎሊክ አሲድም በፅንሱ ጤንነት ላይ እንዲሁም አኒሚያ ወይም ደም ማነስን በመከላከሉ እረገድ የሚያመጣው ተፅእኖ ስላለ ማንኛዋም እርጉዝ ሴት በእርግዝናዋ ወቅት በለተይ ከሶስት ወር በኋላ ባለው ግዜ ውስጥ አይረንና ፎሊክ አሲድ እንድትወስድ ይመከራል፡፡”
ይህ እንዳለ ሆኖ በህክምና ከሚሰጠው የአይረን ንጥረ ነገር በተጨማሪ አንዲት እርጉዝ ሴት አመጋገቧን እና በሰውነቷ ያለውን የአይረን መጠን በማስተካከል የእራሷን ብሎም የፅንሱን ጤንነት መጠበቅ ትችላለችም ብለዋል ዶክተር ሊያ፡-
“...ማንኛዋም እርጉዝ እናት ወደ ህክምና ተቋም ስትመጣ በቅድሚያ በደሟ ውስጥ ያለው የሂሞግሎቢን መጠን ተለክቶ መጠኑ አነስተኛ ከሆነ icon supplement እንድትወስድ ይደረጋል፡፡ በአመጋገብ በኩል ደግሞ ከእንስሳት ተዋፅኦ የሚገኘውን ..ጉበት፣ኩላሊት፣ቀይ ስጋና እንቁላል.. የመሳሰሉት ወይም ደግሞ ከአትክልትና ፍራፍሬ በአይረን የበለፀጉ ምግቦችን በመመገብ በሰውነታችን ያለውን የአይረን መጠን መጨመር ይቻላል፡፡”
ከእዚህ በተቃራኒ ደግሞ በሰውነታችን ያለውን የአይረን መጠን እንዲቀንስ የሚያደርጉ እንደ ቡና፣ሻይ የመሳሰሉትን መቀነስ በሰውነታችን የሚኖረው የአይረን መጠን ተመጣጣኝ እንዲሆን እንደሚያደርግ ዶክተር ሊያ ይገልፃሉ፡፡
በመጨረሻም ዶክተር ሊያ በእርግዝና ወቅት ከአይረን እጥረት ጋር ተያይዞ የሚከሰተውን የደም ማነስ በሚመለከት መደረግ አለበት ያሉትን ሀሳብ የፅሁፋችን ማጠቃለያ አድርገነዋል፡፡
“...ከላይ...ከደም ማነስና ከአይረን ጋር የተያያዙት ጉዳዮች በደንብ ተነስተዋል፡፡ ነገርግን አስቀድሜ ፎሊክ አሲድ ብዬ የጠቀስኩትም ንጥረ ነገር ልክ እንደ አይረን ሁሉ ከደም ማነስ ጋር በተያያዘ በሰውነታችን የሚኖረው ጠቀሜታ እጅግ ከፍተኛ በመሆኑ ተመሳሳይ ትኩረት ልንሰጠው ይገባል፡፡ ይህ ንጥረ ነገር ልክ እንደ አይረን ሁሉ ከሶስት ወር በኋላ መውሰድ ይቻላል፡፡ ፎሊክ አሲድ እርግዝና ከመከሰቱ አስቀደሞ ፅንሱ ጤንነት ላይ ትልቅ ተጽእኖ  አለው፡፡ ስለዚህ አንዲት እናት ቢቻል እርግዝና ከመፈጠሩ በፊት ብትወስድ... ይህም ሳይሆን ከቀረ በእርግዝና ወቅት እስከ ሶስት ወር ባለው ግዜ ውስጥ ብትወስድ እጅግ ጠቃሚ ነው፡፡”

Published in ላንተና ላንቺ

          14ኛው የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ነገ 40ሺ ተወዳዳሪዎችን በማሳተፍ ይካሄዳል፡፡ የ10 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫውን ከማካሄዱ በፊት ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ሰሞኑን ውድድሩን ያጀቡ የተለያዩ ዝግጅቶች ነበሩት፡፡ የመጀመርያው ባለፈው ረቡዕ በኤግዚብሽን ማእከል የተከፈተው የስፖርት ኤክስፖ ነው፡፡ በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን በአፍሪካ ለመጀመርያ ጊዜ የዓለም የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር ስራ አስኪያጅ ኮሚቴ ስብሰባም ተስተናግዷል፡፡ የዓለም የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር የስራ አስኪያጅ ኮሚቴ ስብሰባ ትናንት እና ከትናንት በስቲያ በቀነኒሳ ሆቴል ተካሂዷል፡፡ መስተንግዶውን ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ከታዋቂው የአትሌቲክስ ስፖርት ፎቶግራፈር ዢሮ ሚሹዙኪ፤ ከቀነኒሳ በቀለ እና ከአትሌቲክስ ፌደሬሽን ጋር በመተባበር አከናውነዋል፡፡ በስብሰባው ላይ ለመገኘት ወደ ኢትዮጵያ የመጡት  ከ10 የተለያዩ አገራት የተውጣጡ 29 የስፖርት ባለሙያዎች ናቸው፡፡ ከመካከላቸው ከኦስትሪያ ፤ከዩክሬን፤ ከሮማንያ ፤ከፈረንሳይ፤ ከደቡብ ኮርያ፤ ከጃፓን፤ ከእንግሊዝ ከጣሊያን ከኬንያ እና ሌሎች የዓለም ክፍሎች የመጡ ባለሙያዎች ይገኙበታል፡፡

ባለፈው ረቡእ በቀነኒሳ በቀለ ሆቴል በተዘጋጀላቸው የእራት ግብዣ ላይ የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ መስራች እና ሊቀመንበር ኃይሌ ገብረስላሴ ባሰማው ንግግር አትሌቲክስ ስፖርት ኢትዮጵያን ለዓለም ለማስተዋወቅ ሁነኛ አማራጭ እንደሆነ ትተዘባላችሁ ሲል ተናግሯል፡፡ በዚሁ የእራት ግብዣ ላይ የኢትዮጵያ የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር ለእንግዶቹ የአገር ልብስ ስጦታ ያቀረበ ሲሆን የአትሌቲክስ ፌደሬሽን ተወካዮች በበኩላቸው ኢትዮጵያ በስፖርቱ የ65 ዓመታት ታሪክ ማሳለፏን ጠቅሰው የታላላቅ አትሌቶች መገኛ በሆነች አገር ለምታዘጋጅቱ ትልቅ ውድድራችሁ እናመሰግናለን በማለት ለታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ድጋፍ ሰጥተዋል፡፡
14ኛው የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ዛሬ በጃንሜዳ አካባቢ እስከ 4ሺ ህፃናትን በማሳተፍ በሚካሄደው ከ500 ሜትር እስከ 2000 ሜትር ውድድር ነው፡፡ ነገ ጠዋት በጃንሜዳ አካባቢ ውድድሩን የሚያስጀምሩት የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ የተከበሩ አባዱላ ገመዳ ሲሆኑ የእለቱ የክብር እንግዶች እንግሊዛዊው የትራያትሎን አትሌት አሊስተር ብራውንና ኬንያዊቷ ማራቶኒስት ኤድና ኪፕላጋት አብረዋቸው ይኖራሉ፡፡ በዋናው የአትሌቶች ውድድር 40 ክለቦችን የወከሉ ከ600 በላይ አትሌቶች የሚፎካከሩ ሲሆን ፤ ለአንደኛ 40ሺ ለሁለተኛ 25 ሺ እንዲሁም ለሶስተኛ 12ሺ 500 ብር በሁለቱምፆታዎች በሽልማት ይበረከታል፡፡  ከ15 አገራት የመጡ 300 ስፖርተኞች ከ40ሺው ስፖርተኛ መካከል ሲገኙበት የ13 አገራት አምባሳደራት በኢትዮጵያን ኤርላይንስ አዋርድ ለማሸነፍ ይሽቀዳደማሉ፡፡ትናንት በሂልተን ሆቴል በተሰጠው መግለጫ ላይ  በ10 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫው በጋራ እየሮጥን በጋራ እንደሰት በማለት መልዕክት ያስተላለፈው ኃይሌ ገብረስላሴ፤ የውድድሩ እድገት ገና ይቀጥላል ብሏል፡፡ የክብር እንግዶች ከሆኑት አንዷ ኬንያዊቷ ኤድና ኪፕላጋት ኃይሌን ከ16 ዓመቷ ጀምራ እንደምታውቀው ገልፃ በምታደንቀው አትሌት የተዘጋጀ ውድድርን ለማስጀመር መጋበዟ ታላቅ ክብር ነው ብላለች፡፡ ኤድና ኪፕላጋት ከ12 በላይ ማራቶኖችን ያሸነፈች አትሌት ስትሆን  በሀለት የዓለም ሻምፒዮናዎች በማራቶን አከታትላ በማሸነፍ ሁለት የወር ሜዳልያዎች የተጎናፀፈች እና ዘንድሮ የለንደን ማራቶንን ለማሸነፍ የበቃች ናት፡፡ በሌላ በኩል ሌላው የክብር እንግዳ በለንደን ኦሎምፒክ በትራይትሎን ስፖርት የወርቅ ሜዳልያ ያገኘው አሊስተር ብራውንሊ በውድድሩ ለመሳተፍ መጓጓቱን ይናገራል፡፡ ትራያተሎን 500 ሜትር በዋና፤ 40 ኪሎሜትር በብስክሌት ግልቢያ እንዲሁም 10 ኪሎሜትር የጎዳና ላይ ሩጫን በማካተት የሚካሄድ ስፖርት ነው፡፡ ለታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያን በአጋርነት ሲደግፉ ከቆዩት አንዱ የሆነው የእንግሊዙ ኖቫ ኢንተርናሽናል ዲያሬክተር ዴቪድ ሊንግተን ውድድሩ ባለው ማራኪ ድባብ ከዓለማችን ምርጡ ነው ካሉ በኋላ የውድድር ተቋማቸው በመላው እንግሊዝ ካካሄዳቸው ውድድሮች አሸናፊዎቹን ይዞ በመምጣት ዘንድሮ ተሳትፎ እንደሚያደርግ ገልጿል፡፡ ኖቫ ኢንተርናሽናል አስከ 1 ሚሊዮን ተሳታፊዎች ያገኙ ውድድሮችን በማዘጋጀት በመላው ብሪታኒያ የሚንቀሳቀስ ነው፡፡ በሌላ በኩልየኢትዮጵያ ቱሪዝም ኦርጋናይዜሽን ዲያሬክተር አቶ ሰለሞን ታደሰ የሩጫ ውድድሩ የቱሪዝም እንቅስቃሴን የሚያቀላጥፍ ብለው ሲያደንቁ፤ የውድድሩ ስፖንሰር የሆነው የኢትዮጵዩ ንግድ ባንክ ሃላፊ አቶ ኤፍሬም መኩርያ የኢትዮጵያ ትልቁ ባንክ የአፍሪካን ታላቅ ውድድር ስፖንሰር በማድረጉ ደስተኛ ነው ብለዋል፡፡

Saturday, 22 November 2014 12:51

ስለ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ

የ10 ኪሎሜትር የጎዳና ላይ ሩጫው 10ሺ ተወዳዳሪዎች በማሳተፍ የተጀመረ ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ተሳታፊው ወደ 18ሺ፤ 25 ሺ፤ 35 ሺ ፤ 38ሺ  እያደገ ቀጥሎ ዘንድሮ 40ሺ ደርሷል፡፡
አዲስ አበባ ከባህር ጠለል በላይ በ800 ጫማ መገኘቷ የሩጫ ውድድርን ያከብደዋል፡፡  የአልቲትዩድ ከፍተኛነት አስቸጋሪ ነው፡፡ ለጥሩ ሰዓት አይመችም፡፡ በሌላ በኩል የኢትዮጵያ ትልልቅ አትሌቶች በውድድሩ ቋሚ ተሰላፊ መሆናቸው ከሌሎች አገራት ተፎካካሪ እንዳይመጣ ምክንያት ሆኗል፡፡
 በውድድሩ ላይ የሚገኙ እውቅ የዓለም አትሌቲክስ ማናጀሮች ከ10 በላይ ይሆናሉ፡፡ የኢትዮጵያን አትሌቶች ከለመመልመል የሚጠቀሙበት መድረክ ለመሆን በቅቷል፡፡ የተለያዩ ዓለም አቀፍ ውድድሮችም ግምት ይሰጡታል፡፡ በውድድሩ ጥሩ ደረጃ ያገኘ አትሌት ዓለም አቀፍ ውድድር የማግኘት እድሉ ሰፊ ነው፡፡
በአሁኑ ወቅት በዓለማችን መሮጥ አለባቸው ከተባሉ 10 የጎዳና ላይ ሩጫ ውድድሮች  አንዱ ነው፡፡ በታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ የ10 ኪሜ ውድድር አንድ ቀለም ማልያ በሚለብሱ ተሳታፊዎቹ የአፍሪካ አስደናቂው የአትሌቲክስ መድረክ ለመሆን በቅቷል፡፡ ውድድሩ በየጊዜው ታላላቅ የክብር እንግዶችን ከውጭ እና ከአገርውስጥ በማሳተፍም ስኬታማ  ሆኖ ቆይቷል፡፡  ፖል ቴርጋት፤ ገብሬላዛቦ፤ ካሮሊና ክሉፍት፤ ዴቭ ሞርክሩፍት፤ፓውላ ራድክሊፍ በክብር እንግድነት ውድድሩን ካስጀመሩ የዓለማችን ምርጥ ታላላቅ አትሌቶች ይጠቀሳሉ፡፡
ከአጋር ስፖንሰሮችና ከባለድርሻ አካላትም ጋር አርዓያ በሆነ መንገድ በመስራት የሚጠቀስ ሆኗል፡፡ እንደቶታል፤ ቶዮታ፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድ እና የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አብይ ስፖንሰር ሆነውለታል፡፡ በተለያዩ ቁሳቁሶች አቅርቦት፤ በመስተንግዶ እና ሌሎች ተግባራትን በአጋርነት የሚሰሩት ከ50 በላይ ድርጅቶች ናቸው፡፡
በየዓመቱ ከዋናው የ10 ኪሎሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ ጋር በዓመት ከ10 በላይ ውድድሮች እስከ 60ሺ ስፖርተኞች ይሳተፋሉ፡፡ ውድድሮችን የሚያዘጋጁ፤ የሚያስተናግዱና የሚያስተባብሩ ሰራተኞች ከ200 በላይ ናቸው፡፡
ከውድድሩ አያይዞ በሚያነግባቸው መርሆችም ተሳክቶለታል፡፡ በገቢ ማሰባሰብ እንቅስቃሴም ባለፉት አምስት አመታት ከ4.5 ሚሊዮን ብር በላይ በመሰብሰብ ለ15 ግብረሰናይ ድርጅቶች በማከፋፈል ተመስግኗል፡፡
በዋናው የአትሌቶችውድድር የመጀመርያው አሸናፊ ኃይሌ ገብረስላሴ ነበር፡፡ ከዚያም በኋላ በረጅም ርቀት ዓለምን መቆጣጠር የቻሉት የኢትዮጵያ አትሌቶች በውድድሩ ተሳታፊ ሆነዋል፡፡  ገብሬ ገብረማርያም፤ ስለሺ ስህን፤ ፀጋዬ ከበደ፤ ብርሃኔ አደሬ፤ ወርቅነሽኪዳኔ፤ ጥሩነሽዲባባ አሸናፊዎች ነበሩ፡፡
የ10 ኪሎሜትር የጎዳና ላይ ሩጫው ሪከርዶች በወንዶች በድሪባ መርጋ በ28 ደቂቃዎች ከ18.86 ሰከንዶች 6ኛው እንዲሁም በሴቶች ደግሞ በ11ኛው በአበበች አፈወርቅ በ32 ደቂቃዎች ከ59 ሰከንዶች የተመዘገቡ ናቸው፡፡

ጣሊያናዊው ጂያኔ ሜርሎ የዓለም የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር (AIPS) የወቅቱ ፕሬዝዳንት ናቸው፡፡ በታዋቂው የጣሊያን የስፖርት ሚዲያ ላ ጋዜታ ዴሎ ስፖርት ላይ በተለይ የአትሌቲክስ ስፖርት ዘጋቢ ሆነው ሲሰሩ 10 ኦሎምፒኮችን በቀጥታ በመዘገብ ከፍተኛ ልምድ ያካበቱ ባለሙያ ናቸው፡፡ ከስፖርት አድማስ የሚከተለውን አጭር ቃለምልልስ አድርገዋል፡፡
በኢትዮጵያ መሰብሰባችሁ  ምን ጥቅም አለው?
በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን በአፍሪካ የመጀመርያው ስብሰባችን ማድረጋችን ወደፊት ብዙ እድሎችን ይፈጥራል፡፡ እያገኘን ያለው መልካም መስተንግዶ ደግሞ ወደፊትም ሌሎች ዓለም አቀፍ ስብሰባዎች እና ዝግጅቶችን ለማካሄድ የሚያነሳሳን ይሆናል፡፡ ከምናገኘው ልምድ ተነስተን ብዙ ተግባራት የምናከናውን ይመስለኛል፡፡ እኔ ወደ ኢትዮጵያ ስመጣ ለ3ኛ ጊዜ ቢሆንም ሌሎቹ የዓለም የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር ስራ አስኪያጅ ኮሚቴ አባላት ግን የመጀመርያቸው ነው፡፡ በቆይታቸው የሚኖራቸውን ልምድ በመንተራስ ብዙ የጉብኝት እድሎችን ለኢትዮጵያ የሚፈጠሩ ይመስለኛል፡፡ ኢትዮጵያ በአትሌቲክስ ስፖርት ታላላቅ አትሌቶችን በማፍራት በመላው ዓለም ገንናለች፡፡  ይህ ስኬት  ደግሞ በዓለም ስፖርት ጋዜጠኞች ትኩረት ውስጥ አስገብቷታል፡፡ በአትሌቶቻችሁ ስኬት ነው  ወደ ኢትዮጵያ ብሎም ወደ አፍሪካ ለመጀመርያ ጊዜ በመምጣት የዓለም አቀፍ ማህበራችንን የስራ አስኪያጅ ኮሚቴ ስብሰባ ለማድረግ የበቃነው፡፡ ኃይሌና ቀነኒሳ እንዲሁም ሌሎች የኢትዮጵያ አትሌቶች ምስጋና ይገባቸዋል፡፡ ወደ ኢትዮጵያ ደጋግመን እንመጣለን፡፡
ስብሰባችሁ የሚያተኩርባቸው አጀንዳዎች ምንድናቸው ?
ዓለም አቀፉ ማህበራችን ከተመሰረተ 90ኛ ዓመቱን ዘንድሮ ያስቆጥራል፡፡ በስብሰባችን ይህን እናስባለን፡፡ በዋናነት የያዝናቸው አጀንዳዎች ግን በስፖርት ሚዲያው አሰራር ላይ ያተኩራሉ፡፡ በዓለም አቀፍ ደረጃ እየተፈጠሩ ያሉ መሰናክሎች እና ችግሮችን በዝርዝር በመመልከት የመፍትሄ ሃሳቦችን እያቀረብን ውይይት እናደርጋለን፡፡ የስፖርት ሚዲያዎች በነፃነት መስራት የሚችሉባቸውን ሁኔታዎች እንዳስሳለን፡፡ በመረጃ ምንጮቻቸው የስፖርት ሚዲያዎች ማድረግ የሚገባቸውን ከለላ  የሚያጠናክሩባቸውን አቋሞች ለመቅረፅ እናስባለን፡፡ በሌላ በኩል አዲስ በጀመርነው እና ተተኪ የስፖርት ሚዲያ ትውልዶችን ለመፍጠር ያግዘናል ያልነው የወጣት ስፖርት ጋዜጠኞች የማስተር ስልጠና ፕሮግራም አወቃቀር ዙርያ ያሉ ጅምር ተግባራትን እንገመግማለን፡፡
የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ውድድርን ማህበራችሁ እንዴት ይመለከተዋል?
ካለኝ ልምድ በመነሳት የምናገረው ውድድሩ ዓለም አቀፍ ደረጃ እንዳለው ነው፡፡ የአትሌቲክስ ስፖርት ባህል በሁሉም ኢትዮጵያዊ የእለት እለት ህይወት እንዲቆራኝ ያደረገ ነው፡፡ የሙያ ባልደረቦቼ ከስብሰባው ጎን ለጎን የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ውድድርን ለመከታተል እቅድ አላቸው፡፡ ውድድሩን በጥልቀት ገምግመው ወደየአገሮቻቸው ሲመለሱ በርካታ የዘገባ ሽፋን ይሰጡታል፡፡ ይህ ደግሞ የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያን ዝና እያሳደገ ይቀጥላል፡፡ በውድድሩ አገሪቱ እያገኘች ያለው ትኩረት ሌላው ስኬት ይመስለኛል፡፡
ስለ አበበ ቢቂላ ሲናገሩ ሰምቻለሁ፤  ከኢትዮጵያ አትሌቶች ጋር እንዴት ተዋወቁ?
በ1960 እኤአ ላይ በሮም ኦሎምፒክ ላይ ገና 13 ዓመቴ ብቻ ነበር፡፡ አበበ ቢቂላ የማራቶን ውድድር ሲያሸንፍ ተመለከትኩ፡፡ በጣም ለህይወቴ አስፈላጊውን መነቃቃት ነበር ያገኘሁት፡፡በአትሌቲክስ ስፖርተኛነት ቆርጬ የተነሳሁበት ታሪክም ሆነ፡፡  አፍሪካዊያን ሯጮች በዓለም የስፖርት መድረክ ያን ያህል ጥንካሬ አልነበራቸውም፡፡ በአበበ ቢቂላ ብቃት ግን ብዙ ተነሳሱ፡፡ እኔ በዚህ ታላቅ ኢትዮጵያዊ አትሌት  ተማርኬ  ከስፖርቱ ጋር በፍቅር ወደቅኩ፡፡ ጀግንነቱም በተተኪ የኢትዮጵያ አትሌቶች ሲደጋገም ለማየት ስታደል ደግሞ ተደሰትኩ፡፡ ከአበበ ቢቂላ በኋላ ምሩፅ ይፍጠር እና መሃመድ ከድርንም ለማወቅ ችያለሁ፡፡ በ80ዎቹ በሚላኖ ከተማ ውስጥ ከሃምሳ ሺ በላይ ስፖርተኞችን የሚያሳትፍ ውድድር ላይ ተሳትፈው ስለነበር ነው፡፡ ከእነሱ በኋላ እኔም ወደ ስፖርት ጋዜጠኝነቱ ስገባ እነ ኃይሌን ተዋወቅኩ፡፡ ከዚያም ቀነኒሳንም ጥሩነሽንም በደንብ የማውቃቸው እና የምከታተላቸው  ሆኜ አሳልፍያለሁ፡፡
ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ለምስራቅ አፍሪካ አትሌቶች በረጅም ርቀት የአትሌቲክስ ውድድሮች መወዳደርያዎች ጠፍተዋል፡፡ በውጤታማነት ከሌሎች የዓለም አገራት ልቀው መሄዳቸው ምክንያት ይመስለኛል፡፡ ይሁንና በውድድሮች መመናመን የሚቆረቆር አለመኖሩ ሁኔታውን አባብሶታል፡፡ የዓለም ስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር ይህ ሁኔታ አሳስቦት ለምን አልተከራከረም?
 የዓለም ስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር በዚሁ የረጅም ርቀት የአትከሌቲክስ ውድድሮች መመናመን ዙርያ አስተያየት ለመስጠት ቢችልም ተፅእኖ በማሳደር ምንም አይነት ነገር ማስቀየር ግን  አይችልም፡፡ ይህን ሁኔታ ማረም ማስተካከል የሚችሉት አትሌቲክሱን የሚያስተዳድሩ አለማቀፍ ተቋማት ብቻ ናቸው፡፡ ዋናው ችግር እንደሚመስለኝ የምስራቅ አፍሪካ አትሌቶች ከጥራት ይልቅ በብዛት ተሳትፏቸው የዓለምን ውድድሮች ማጨናነቅ መጀመራቸው ነው፡፡ ዛሬ ከዚሁ የአፍሪካ ክፍል እንደ ኃይሌ፤ ቀነኒሳ፤ ፖል ቴርጋት ልዩ የስፖርት ስብዓና ያላቸው ስፖርተኞች የሉም፡፡ ብዛት ብቻ ነው ያለው፡፡ ለምሳሌ በ10ሺ ሜትር ውድድር ድሮ አንድ ሁለት ኢትዮጵያዊ እና ኬንያዊ ቢኖሩ ነበር፡፡ ሌሎች አገራትም በተመጣጣኝ ኮታ  ከአውሮፓ፤ ከኤስያ፤ ከአሜሪካና ሌሎች የዓለም ክፍሎች ይወከሉ ነበር፡፡ ዛሬ ግን አስራምናምን ኬንያዊ እና ኢትዮጵያዊ በየውድድሩ መስፈርቱን አሟልቶ እየገባ የሌሎች አለም ክፍሎችን ፍላጎት እያመነመነው መጣ፡፡ ውድድር አዘጋጆችም ከእነስፖንሰሮቻቸው በዚህ ደስተኛ አይደሉም፡፡ ዓለም አቀፍ ሚዲያውም ስለ ሁለቱ የምስራቅ አፍሪካ አገራት አትሌቶች በመዘገብ ተሰላችቷል፡፡ እነዚህ ሁኔታዎች ለውድድሮች መጥፋት መንስኤ ይመስለኛል፡፡
ከኢትዮጵያ አትሌቶች ብቃት እና ስብዕና  ምን ያስደንቅዎታል?
በጣም ደስ የሚሉኝ እነዚህ ስፖርተኞች ከደሃ አገር ወጥተው በዓለም አቀፍ የውድድር መድረክ የሚገኑበት ጀግንነታቸው ነው፡፡ በተለያዩ ዓለም አቀፍ ውድድሮች በአትሌቶቹ መካከል በተለይ በፊት የምታዘባቸው የቡድን ስራዎች እና አንድነታቸው ይማርከኛል፡፡ በኢትዮጵያ የአትሌቲክስ ስፖርት ከህዝቦች ጋር ባህል ጋር የተሳሰረበት ሁኔታም ያስደንቀኛል፡፡
በኢትዮጵያ ላሉ የስፖርት ጋዜጠኞች ምን ምክር ይሰጣሉ?
ወደ ዓለም አቀፍ መድረክ የሚያወጣቸውን የትምህርትዐ የቋንቋ እና የልምድ ብቃት ያሳድጉ ነው የምለው፡፡ በተለይ በእንግሊዘኛ ቋንቋ ያላቸውን ችሎታ ማሳደግ አለባቸው፡፡ ለታላላቅ አትሌቶች የመረጃ ምንጭ መሆን ያለባቸው የራሳቸው አገር ሚዲያዎች እንጂ የሌላ አገር ተቋማት መሆን የለባቸውም፡፡ በአገር ውስጥ ያሉ የስፖርት እንቅስቃሴዎችን በተለይ ኢትዮጵያ የምትታወቅበትን የአትሌቲክስ ስፖርት በተለያየ ሁኔታ ለመላው ዓለም የሚያሰራጩበትን አሰራር ማሳደግ ይጠበቅባቸዋል፡፡ በዓለም አቀፍ ውድድሮች ላይ የሚያገኙትን እድል ተጠቅመው በመስራትም ከሌሎች አገራት ባለሙያዎች ጋር ወቅቱን በጠበቀ መረጃ እና ተፅእኖ ፈጣሪነት እንዲሰሩ እመክራለሁ፡፡




  • ዓምና  በተፈጸሙ 10 ሺህ ያህል ጥቃቶች፣ ከ18 ሺህ በላይ ሰዎች ሞተዋል
  • 6ሺህ 362 ሰዎች የሞቱባት ኢራቅ ቀዳሚነቱን ይዛለች

        በአለማችን የሚፈጸሙ የሽብር ጥቃቶች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ በመምጣት አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱንና ባለፈው የፈረንጆች አመት ብቻ ከ18 ሺህ በላይ የተለያዩ አገራት ዜጎች ለህልፈት መዳረጋቸውን ስካይ ኒውስ ዘገበ፡፡
የአለማቀፉን የሽብርተኝነት አመልካች ጥናት ሪፖርት ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ እ.ኤ.አ በ2013 ብቻ በአለማችን የተለያዩ ክፍሎች 10ሺህ ያህል የሽብር ጥቃቶች የተፈጸሙ ሲሆን፣ በጥቃቶቹ የሞቱ ሰዎች ቁጥር ከአንድ አመት በፊት ከነበረው  በእጥፍ ያህል መጨመሩንም ጠቁሟል፡፡በአመቱ በሽብር ጥቃቶች በርካታ ዜጎች የሞቱባት ቀዳሚ የዓለማችን አገር ኢራቅ ስትሆን፣ በአገሪቱ 6ሺህ 362 ያህል ሰዎች ከሽብር ጥቃቶች ጋር በተያያዘ ለሞት ተዳርገዋል፡፡
ችግሩ በከፍተኛ ሁኔታ የተስፋፋበቸው ሌሎች የአለማችን አገራት አፍጋኒስታን፣ ፓኪስታን፣ ሶሪያና ናይጀሪያ ሲሆኑ፣ አይኤስ፣ አልቃይዳ፣ ታሊባንና ቦኮሃራም ደግሞ በአገራቱ አብዛኞቹን ጥቃቶች የፈጸሙ ቡድኖች ናቸው ተብሏል፡፡ የሽብርተኝነት እንቅስቃሴዎች በሚታዩባቸው 162 የአለማችን አገራት ላይ የሰራውን አለማቀፍ የሽብርተኝነት አመልካች ጥናት ለሁለተኛ ጊዜ ይፋ ያደረገው፣ ኢንስቲቲዩት ፎር ኢኮኖሚክስ ኤንድ ፒስ የተባለ አለማቀፍ ተቋም ነው፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

* የግዳጅ ጋብቻ፣ ከሚገባው በላይ ማሰራት፣ ህገወጥ የሰዎች ዝውውር፣ ህጻናትን ጦር ሜዳ ማሰለፍ---
* በህንድ 14.3 ሚሊዮን ሰዎች የዘመናዊ ባርነት ሰለባዎች ናቸው
በአሁኑ ወቅት በአለማችን የተለያዩ አገራት 36 ሚሊዮን ያህል ሰዎች ዘመናዊ የባርነት ህይወት እየገፉ እንደሚገኙ ዎክ ፍሪ ፋውንዴሽን የተባለ ተቀማጭነቱን በአውስትራሊያ ያደረገ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ተቋም ሪፖርት ጠቅሶ ዘ ጋርዲያን ዘገበ፡፡
ተቋሙ ለሁለተኛ ጊዜ ሰሞኑን ይፋ ያደረገው አመታዊ የባርነት መጠን አመልካች ሪፖርት እንደሚለው፣ በአለማችን የዘመናዊ ባርነት ሰለቦች ቁጥር ከአምናው በ23 በመቶ ጭማሪ አሳይቷል፡፡
ጥናቱ ከተደረገባቸው 167 አገራት ቀዳሚውን ስፍራ የምትይዘው ህንድ ስትሆን፣ በአገሪቱ 14.3 ሚሊዮን ዜጎች የባርነት ኑሮን በመግፋት ላይ ይገኛሉ፡፡
ቻይና በ3.24 ሚሊዮን፣ ፓኪስታን በ2 ሚሊዮን፣ ኡዝቤኪስታን በ1.2፣ ሩስያ በ1 ሚሊዮን፤ ከሁለተኛ እስከ አምስተኛ ያሉትን ደረጃዎች ይዘዋል፡፡ ከአጠቃላይ ህዝባቸው ብዙ በባርነት ውስጥ የሚኖሩ ዜጎች ያሉባቸው አገራትን በተመለከተ ሪፖርቱ እንዳለው፣ ሞሪታንያ በ4 በመቶ፣ ኡዝቤኪስታን በ3.9 በመቶ፣ ሃይቲ በ2.3 በመቶ፣ ኳታር በ1.3 በመቶ እና ህንድ በ1.1 በመቶ ከአንድ እስከ አምስት ያሉትን ደረጃዎች ይዘዋል፡፡ዘመናዊ ባርነት በሁሉም አገራት ውስጥ እንዳለ የተቋሙ መስራችና ሊቀመንበር አንድሪው ፎሬስት መግለጻቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ ዘመናዊ ባርነትን ለማጥፋት ትኩረት ሰጥቶ በመስራት ረገድ፣ አውስትራሊያ፣ ኦስትሪያ፣ ጆርጂያ፣ አየርላንድ፣ ኔዘርላንድ፣ ኖርዌይ፣ ስዊድን፣ ስዊዘርላንድ፣ እንግሊዝና አሜሪካ ቀዳሚነቱን እንደሚይዙ ገልጧል፡፡ እንደ ሪፖርቱ አገላለጽ፤ የሚገባቸውን ክፍያ ሳያገኙ ከሚገባቸው በላይ የስራ ጫና ያለባቸውና የተለያዩ ጥቃቶች የሚደርሱባቸው ህጻናት፣ ሴቶችና በተለያዩ የዕድሜ ክልሎች የሚገኙ ሰዎች፣ ከዘመናዊ ባርነት ሰለባዎች  ይመደባሉ፡፡ ሰዎች ነጻነታቸውን ተጠቅመው የፈለጉትን እንዳይሰሩ በመጨቆን፣ የገቢ ማስገኛ አድርጎ መጠቀም፣ የባርነት አንዱ ትርጓሜ ነው ያለው ሪፖርቱ፤ የግዳጅ ጋብቻ፣ ከሚገባው በላይ ማሰራት፣ ህገወጥ የሰዎች ዝውውር፣ ህጻናትን ወደ ጦር ሜዳ ማሰለፍና የመሳሰሉት የባርነት ተግባራት በስፋት እየተፈጸሙ እንደሚገኙ አመልክቷል፡፡


Published in ከአለም ዙሪያ

“ፒካሶ የሚባለው ዋና የጥፋት ዲያቆን ነው፡፡ ከስዕል ጥበብ ውስጥ ምክንያታዊነትን ሙሉ ለሙሉ አውጥቶ አብስትራክት አርት ፈጠርኩ አለ፡፡ ደግሞም ፈጥሯል፡፡ በድህረ-ዘመናዊነት ማፍረስ መፍጠር በመሆኑ ማለት ነው፡፡ ባለ ሦስት አውታሩን ስዕል ወደ ሁለት አውታር፣ ሲሻው ደግሞ አውታር አልባ አድርጐ አቀረበ፡፡”


ስለ ምን ላውራ? ስለ ምንም ነገር ባወራ ከዘመኑ መንፈስ ውጭ አይሆንም አይደል? አንድ ወዳጄ ዘመኑ “ድህረ ዘመናዊነት” (Post modernism) ነው ብሎኛል፤ እኔም አምኜዋለሁ፡፡ አምኜም ለአማኝ አውርቼ አሳምኛለሁ፡፡ እንግዲህ ይህ የሀሳብ ወዳጅ እንደነገረኝ ከሆነ፣ መጀመሪያ የአዳም እና የሄዋንን ታሪክ ከስር መሰረቱ ማወቅ ያስፈልጋል፡፡ የአዳም እና የሄዋን ታሪክ በጣም አጭር ነው፡፡ አንድ መስመር ነው እንዲያውም፡፡ ሄዋን አንገት ናት፤ አዳም ደግሞ እራስ ነው፡፡ ይሄ አጭር ታሪክ ጥንታዊ ነው፡፡ ጥንታዊ እና ሃይማኖታዊ፡፡
ዘመናዊው የሰው ልጅ ታሪክም እንደ ጥንታዊው በጣም አጭር ነው፡፡ ጥንታዊው አዳም እራስ፣ ሄዋን አንገት ነበረች ብያለሁ፡፡ ዘመናዊው ላይ ምንም አዲስ ነገር አልተከሰተም፡፡ ጥንታዊው አዳም ዘመናዊ ሲሆን ጭንቅላቱን መጠቀም ጀመረ፡፡ ጭንቅላቱን መጠቀም ሲጀምር ልቡን መጠቀም ያቆማል፡፡ ልቡን መጠቀም ሲጀምር ደግሞ ተገላቢጦሽ፡፡ የዘመናዊነት አስተሳሰብ በአዳም ጭንቅላት መስራት እና አለመስራት ሁልጊዜ ብቅ የሚል እና ተመልሶ እልም የሚል ነገር ነው፡፡ ልክ እንደ ሀገራችን የመብራት አቅርቦት ብዬ መመሰል አይጠበቅብኝም፡፡ በግሪኮቹ ዘመን ጭንቅላቱን መጠቀም ጀምሮ ነበር ይባላል አዳም፡፡ በኋላ የክርስትና አብዮት ሲቀጣጠል ጭንቅላቱ ተመልሶ ጠፋበት፡፡ ጠፍቶበት ቆይቶ ወደ አስራ ስድስተኛው ክፍለ ዘመን አካባቢ መልሶ መብራት መጣለት፡፡ ጭንቅላቱን እና እጁን አጣምሮ ሳይንስን አዋለደ፡፡ ማሽን ሰራ፣ በጭንቅላቱ ውስጥ ብቻ የማይቀር መብራት በጐጆው አበራ፡፡ ፋብሪካው፣ መድሃኒቱ፣ መንገዱ፣ ባቡሩ…የዚህ ፈጠራው ማስታወሻ ናቸው፡፡
ይሄ ከላይ የጻፍኩት ሁሉ ወዳጄ ያወራልኝን መሆኑ አይዘንጋ!
ድህረ - ዘመናዊነትስ? አልኩት፡፡
ድህረ - ዘመናዊነት ልብንም ሆነ ጭንቅላትን በአንድ ላይ ለማጣት የሚያደርገው ሙከራ ነው አለኝ፡፡ ምሳሌ እንዲሰጠኝ ጠየቅሁት፡፡
ምሳሌውን ከፈላስፎቹ ነው የጀመረልኝ…ሳይንስ በተወለደበት ግርግም ውስጥ ሰበአ ሰገሎቹ ስጦታ ይዘው ለሰው ልጅ መጡ፡፡ ይዘው የመጡት እጅ መንሻ ግን ከርቤ፣ ወርቅ እና እጣን አልነበረም፤ አለኝ፡፡
የሰበአ ሰገሎቹ ስም ሰረን ኪርከርጋርድ፣ ማርቲን ሀይደርጋር እና ፍሬድሪክ ኒቼ ናቸው፡፡ ይዘው የመጡት ስጦታ…ሳይንስ ወይም የልጅነት ልምሻን የሚከላከል ክትባት አልነበረም፡፡ አቀጭጮ የሚገድለውን መጽሐፍ ነው ያበረከቱለት፡፡ ሳይንስ ቀጭጮም አልሞተም፤በልጅነት ልምሻ ተጠቅቶ በዱላ እየተደገፈ በህይወት መኖረ ቀጠለ፡፡
ከሳይንስ ጋር የጓደኛዬ ትረካም ቀጥሏል፡፡
ሳይንስ የሚኖረው ምክንያታዊነት እስካለ ድረስ ነው፡፡ ምክንያታዊነት በጭንቅላት ነው የሚሰራው፡፡ ምክንያታዊነት በሃይማኖት ወይንም በልብ ወይንም በስሜት አይሰራም፡፡ ድህረ - ዘመናዊነት በማይሰራው እንዲሰራ፣ በሚሰራው እንዳይሰራ የማድረጊያ ፍልስፍና ነው፡፡ አንገትን ጭንቅላት፣ ጭንቅላትን አንገት ሲደረጉ ነው ወይ የማይሰራው እንዲሰራ የሚሆነው፡፡ አልኩት፡፡ እኔ የሴቶችን ከጓዳ ወደ መስክ መውጣት ለማለት ፈልጌ ነው፡፡
ሴት እና ወንድ ሁለቱም ጭንቅላት፣ ሁለቱም አንገት አላቸው፤ልዩነታቸው በአንገት እና በጭንቅላት ሊመሰል አይችልም፡፡ ሴቶች የወንዶችን የቀድሞ ሃላፊነት መጋራታቸው እንዲያውም ምክንያታዊ-- ሳይንሳዊ ነው፡፡ እኔ የምልህ ሌላ ነው፡፡ እኔ የምልህ በደንብ እንዲገባህ ወደ ጥበባቱ ብናተኩር ይሻላል፡፡
ቅድም የጠቀስኳቸው ሰብዓ ሰገሎች፣ ፈላስፎች ወይንም ጠንቋዮች ምክንያታዊነትን የሚያጣጥል ፍልስፍና በምክንያታዊ መሳይ አቀራረብ፣በተወለደው ልጅ ደም ውስጥ ረጭተው ዞር አሉ፡፡ የተረጨው መርዝ መስራት የጀመረው…እንደ ሁልጊዜውም መጀመሪያ በተጨባጭ የታየው ጥበበኞቹ ላይ ነው፡፡ የመጀመሪያዎቹ የድህረ-ዘመናዊነት ምረዛ ሰለባዎች፣ በሃያኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያ ላይ ነው ወደ አለም መድረክ የመጡት፡፡ ስማቸውን ታውቃቸዋለህ? እነ ፒካሶ፣ እነ ገርትሩድ እስታይን፣ እነ ጄምስ ጆይስ…ምናምን ናቸው፡፡ ይዘን መጣን የሚሉት የጥበብ ዘይቤ…ኪውቢዝም፣ ዳይዝም…ስትሪም ኦፍ ኮንሸስነስ…ጂኒ ቁልቋል…ጂኒ ጃንካ… ፒካሶ የሚባለው ዋና የጥፋት ዲያቆን ነው፡፡ ከስዕል ጥበብ ውስጥ ምክንያታዊነትን ሙሉ ለሙሉ አውጥቶ አብስትራክት አርት ፈጠርኩ አለ፡፡ ደግሞም ፈጥሯል፡፡ በድህረ-ዘመናዊነት ማፍረስ መፍጠር በመሆኑ ማለት ነው፡፡ ባለ ሦስት አውታሩን ስዕል ወደ ሁለት አውታር፣ ሲሻው ደግሞ አውታር አልባ አድርጐ አቀረበ፡፡
ለስነጽሑፉ ደግሞ ጄምስ ጆይስ አለልህ፡፡ የሰውን የውስጥ የሃሳብ አፈሳሰስ አሳያለሁ ብሎ በእውን ህልም የሚያዩ ገፀ ባህሪዎች ቀረፀ፡፡ መጽሐፉን እስካሁን በቅጡ የሚረዱት ጥቂት ሰዎች ናቸው፡፡ በኋላ የመጨረሻ ስራውን አወጣ፡፡ Finnigans wake ይባላል፡፡ በዓለም ላይ የመጨረሻው ከባድ የልብ ወለድ ድርሰት መሆኑ ይነገርለታል፡፡ ከባድ የተባለው ከደራሲው በስተቀር ለማንም በግልፅ ስለማይገባ ነው፡፡ የራሱን አዲስ ቃላት እየፈጠረ፣ አንድ አረፍተ ነገር የሚያክሉ ቃላትን ያለ ክፍተት አንድ ላይ እያጠባበቀ … መግለፅ ሳይሆን መደበቅን ለአንባቢ አበረከተ፡፡ … ይኸው አበርክቶቱ የድርሰት ቁንጮ መሆኑ ይሰበካል … የድርሰትን ምክኒያታዊነት ሙሉ በሙሉ ኢ - ምክኒያታዊ ማድረግ ነው ግቡ፡፡ ግቡ ተሳክቶለታል፡፡
 ቅድም ልብን በጭንቅላት ስለ መቀየር አንስቼብሀለሁ፡፡ ድህረ ዘመናዊነት ልብም ጭንቅላትም አይደለም፡፡ ሁለቱንም አፈራርሶ፣ ከፍርስራሹ ከሁለቱም ውጭ የሆነ ነገር መፍጠር ነው፡፡ ልብን እምነት፣ ጭንቅላትን እውነታ ልንላቸው እንችላለን፡፡ ድህረ-ዘመናዊነት ጭንቅላትን እና ልብን እንደ መሳሪያ ተጠቅሞ .. መሳሪያውን መልሶ ለማፍረስ የሚደረግ የትዕቢት እንቅስቃሴ ነው … አለኝ እና ከንዴቱ መለስ አለ፡፡ እናም ቀጠለ፡፡
ወደ ሀገራችን ስትመጣም ጥበቡ በዚሁ ደዌ የተመታ ነው፡፡ ግን ደዌው ምክንያታዊነትን አይገድለውም፡፡ ምክንያቱም አበሻ ምክንያታዊነት በጭንቅላቱ ውስጥ ወይንም በልቡ ውስጥ የሚገኝ ባለመሆኑ ነው፡፡  የአበሻ ምክንያታዊነት የሚገኘው በባህሉ ውስጥ ነው፡፡ ባህል ደግሞ መቼ እንደተሰቀለ የማይታወቅ  ርቆ ያለ ማስጠንቀቂያ ነው፡፡ ማስጠንቀቂያው የፈለገ ርቆ ቢሰቀልም … ግልፅ ሆኖ ባይነበብም… መስራቱ ግን አይቀርም፡፡ ማስጠንቀቂያውን “የአበሻ ጨዋነት” ብለን ብንጠራው የራቀ ስያሜ አይመስለኝም፡፡ ማስጠንቀቂያው ከላይ “የአበሻ ጨዋነት” … ዝቅ ሲል ደግሞ በደቃቅ ፅሁፍ “የአበሻ ነብራዊ ዥንጉርጉርነት” ነው፡፡
ዥንጉርጉርነቱን በምሳሌ ላሳይህ፡-
በአንድ ቀለሙ ድህነትን የሚያከብር ህዝብ ነው… በሌላ በኩል ባለፀጋነትንም ይመኛል፡፡ በአንድ በኩል ክርስቲያን ነው-- በሌላ በኩል አዶ ከብሬ አለበት፡፡ ክታብ እና መስቀሉን አቻችሎ የሚኖር ህዝብ ነው፡፡ ሰም እና ወርቅ አለው፡፡ በጨዋነት ሰምና ወርቁን እየደበቀ እና እየገለፀ አንድ ላይ ያስተናግዳል፡፡ ቋንቋው  ራሱ የሰም እና የወርቅን ባህርይ በውስጡ ያቀፈ ነው፡፡ ስለዚህ የአበሻ ምክንያታዊነት የፈረንጆቹን አይደለም፡፡ የአበሻ ሃይማኖት የአውሮፓዊያኖቹን አይመስልም፡፡ ከውጭ መስሎ ቢገኝ እንኳን ከውስጥ ግን እነሱን አይደለም፡፡ አበሻ የራሱ አንገት እና የራሱ ጭንቅላት ባለቤት ነው፡፡ በአንገቱ አዟዙሮ ቢያይም በጭንቅላቱ አዟዙሮ ቢያስብም … ከዥንጉርጉርነቱ እና ከጨዋነቱ አያፈነግጥም፡፡
እና ምን እያልከኝ ነው? አልኩት፡፡
አበሻ ዘንድ ሞደርኒዝምም ሆነ ፖስት ሞደርኒዝም አይገባም፡፡ ሳይንስን በግርግሙ ስላላዋለደ … ሳይንስን አይነጠቅም፡፡ ድሮውኑ ያልነበረ ነገር አይጠፋም፡፡ ሳይንስን ያዋለዱት ሳይንስን ሲያከብሩ አብሮ ያከብራል፡፡ የሳይንስን ምክንያታዊነት ሲያዋርዱ ያዋርዳል፤ ግን የሚያዋርደው እነሱን ለማገዝ እንጂ ራሱን ለማርከስ አይደለም፡፡ የሚያከብረውም ሆነ የሚያደንቀው በሰም ደረጃ ያለውን ነው፡፡ ወርቁን ግን አያስነካም፡፡ አበሻ ዥንጉርጉርነት እና ጨዋነት ባህሉ ነው፡፡ ሳይንስም ሃይማኖትም ለሱ እነዚህ ናቸው፡፡
ስለዚህ … ሰለሞን ደሬሳ ቅርፃዊነት ብሎ ሲነሳ .. ወይንም አንቶኔ ኢንስታሌሽን አርት ብሎ ብቅ ሲል … ከራሱ ጥፋት ወይንም ልማት ጋር ምንም ግንኙነት እንደሌላቸው … በደመነብሱም ቢሆን አውቆ ነው፡፡
የአበሻ ጨዋነት እና ዥንጉርጉርነት በድህረ-ዘመናዊነት አይነካም፡፡ አበሻ ሞደርን ከመሆኑ አስቀድሞ post modern ሊሆን ይችላል፡፡ አለም የያዘውን ፋሽን ይይዛል፡፡ ስለ ማንነት ቀውስ ሲነሳ፣ የቀውሱን መገለጫዎች ተላብሶ ወየው! ይላል፡፡ የጨዋነቱ አካል ነው ይኼም፡፡
አበሻ እንደ ፒካሶ ሙሉ ለሙሉ ሊያምፅ አይችልም፡፡ ምክንያታዊነት ላይ ለማመፅ መጀመሪያ ሳይንሳዊ ማንነት ያስፈልጋል፡፡ ሳይንሳዊ ማንነት ያላቸው፣ ሳይንሳዊ ፈጠራዎች ሲልኩለት ይቀበላል፡፡ ሳይንሳዊ ማንነትን ለማጥፋት የሚቀሰቅሱትንም ይተባበራል፡፡ ዘመናዊ ልብወለድን እና ዘመናዊ ትያትርን ይመለከታል፡፡ እነሱ በሰሩት መልክ ይሰራል፡፡ ባፈረሱት መንገድ ያፈርሳል፡፡ ወርቁን ግን አያስነካም፡፡ ዘመናዊ ልብወለዱን እያጻፈ፣ ባህላዊውን ተረቱን በዥንጉርጉር ልቡ የወርቅ ማህደር ውስጥ ይዞ ይቀጥላል፡፡ ባህላዊው ተረትና ምሳሌ በዘመናዊነት ውስጥ አልተፈጠረም፡፡ በድህረ-ዘመናዊነት ውስጥም አይለወጥም፡፡ ባህላዊው አበሻ ከፍልስፍና ውስጥ የተፈጠረም አይደለም፡፡ የፈረንጆቹ ምክንያታዊነት በጥቂት ፈላስፎች የተፈጠረ ነው፡፡ በመሆኑም በጥቂት ኢ-ምክኒያታዊ ፈላስፎች ተመልሶ ሊናድ ይችላል፡
ከአበሻ ጨዋነት ጋር የሚጋጭ ፍልስፍና ይዞ የሚመጣ ወዮለት፡፡ በአበሻ ዥንጉርጉርነት ጉራማይሌ ባህሉ ውስጥ የሚጋጨው ፍልስፍና፣ ከነብሩ ዥንጉርጉሮች መሀል አንዱ ይሆናል፡፡ የአበሻ ጨዋነት አንድ ኢላማ ስላልሆነ አንድ ተኳሽ አይመታውም፡፡ በነብር ቆዳ ላይ ያሉትን ነጠብጣቦች በአንድ ተኩስ መምታት አይቻልም፡፡ የነብሩ ህልውና ያለው በነጠብጣቦቹ ላይ ነው፡፡
ስለዚህ---አንተ ምክንያታዊነትን ነው የምትደግፈው ወይንስ ፖስት ሞደርኒዝምን? ቁርጡን ጠየቅሁት፡፡ የምደግፈው አበሻነቴን ነው፡፡ በአበሻነቴ ውስጥ ሁለቱም የሉም፡፡ ግን እንደ ፋሽን ፖስት ሞደርኒዝም ወደ እብደት ያጋደለ ሲመስለኝ ወደ ምክንያታዊነት እመለሳለሁ፡፡ ምክንያታዊነት አላፈናፍን ብሎ ችክ ሲልብኝ ደግሞ ወደ ሀይደርጋር ወይንም ወደ ኤግዚዝቴንሻሊዝም እመለሳለሁ፡፡ ኤግዚዝቴንሻሊዝም ራሱ ፖስት ሞደርኒዝም የገራው ኮሚኒዝም መሆኑን አትዘንጋ---፡፡ ብሎ ንግግሩን ቋጨልኝ፡፡ ግን የነገረኝ ሁሉ ራሴ መስማት የምፈልገውን በመሆኑ፣ ከሱ ወርጄ ንግግሩን የራሴ አደረግኋቸው፡፡  

Published in ጥበብ

አርቲስት ፈለቀ፤ ሳልፈልግ ቴአትሩን እንዳቋርጥ ተደርጌአለሁ አለ

“Desperate to Fight” የተሰኘውና በደራሲ መዓዛ ወርቁ “ከሠላምታ ጋር” በሚል ወደ አማርኛ የተተረጎመው ቴአትር፤ ለተወሰነ ጊዜ ከተቋረጠ በኋላ የፊታችን ሰኞ በጣይቱ ሆቴል ጃዝ አምባ አዳራሽ እንደገና መታየት እንደሚጀምር ፕሮዱዩሰሩ አቶ ዘካሪያስ ካሱ ለአዲስ አድማስ ገለጹ፡፡  ቴአትሩ ለአምስት ወራት በጃዝ አምባ አዳራሽ፣ በዓለም ሲኒማና በኤድናሞል ሲኒማ ለተመልካች ሲቀርብ እንደነበር የጠቆሙት ፕሮዱዩሰሩ፤አንድ ተዋናይ ስራ በማቋረጡ ከመስከረም 26 ቀን 2007 ጀምሮ መታየት አቁሞ እንደነበር አስታውሰዋል፡፡ አሁን ግን አዲስ ተዋናይ እንደቀየሩና ለተመልካች መቅረብ እንደሚጀምር ተናግረዋል፡፡
ከመጀመሪያ አንስቶ በተውኔቱ ላይ ሶስት ገፀ-ባህርያትን ወክሎ ሲጫወት የቆየው አርቲስት ፈለቀ የማር ውሃ አበበ በበኩሉ፤ ቴአትሩን ሳልፈልግ እንዳቋርጥ ያደረገኝ የማኔጅመንቱ ችግር ነው ብሏል፡፡
“ከሠላምታ ጋር” የተሰኘው ቴአትር በፈጠራ ጽሁፍ፣ በአቀራረብና በሚቀርብበት ቦታ ተወዳጅነትን አትርፎ እንደነበር የገለጹት ፕሮዱዩሰሩ፤በተዋንያን ምክንያት ትርኢቶች የሚቋረጡበትን አካሄድ የሚያሻሽል አሰራር እንደሚተገብሩ ጠቁመዋል፡፡
“በሌላው ዓለም በቴአትር ስራ ተጠባባቂ ተዋናይ (under study) አዘጋጅቶ ማቆየት የተለመደ ነው፤በእኛ አገር ይህ አሰራር ባለመለመዱ ብዙ ትርኢቶች እየተቋረጡ ተመልካቾችን እያሳዘኑ ነው፤ይሄ ሁኔታ ማብቃት አለበት” ብለዋል - የቴአትሩ አዘጋጆቹ ሰሞኑን ባወጡት መግለጫ፡፡ ከሰኞ ጀምሮ አርቲስት አለማየሁ ታደሰን በአርቲስት ፈለቀ የማርውሃ አበበ ቦታ ተክተው እንደሚያሰሩ የጠቆመው መግለጫው፤ ተጠባባቂ ተዋንያንን የማዘጋጀቱ ስራ በአርቲስት ኤልሳቤት መላኩ፣ በቴአትሩ ላይ በሚሳተፉ ዳንሰኞችና በሌሎችም ተዋንያን ላይ ተግባራዊ እንደሚሆን አመልክቷል፡፡
“እንዲህ መደረጉ ቴአትር በፍፁም መቋረጥ የለበትም (The show must go on) የሚለውን መርህ ያስከብራል” ያሉት ፕሮዲዩሰር ዘካሪያስ ካሱ፤ “አሰራሩ ከጊዜ፣ ከጉልበት፣ ከገንዘብና መሰል ወጪዎች አንፃር ከባድ ቢሆንም በቴአትር መቋረጥ ላይ ያለውን ችግር ለመቅረፍ አማራጭ የሌለው መፍትሄ ነው” ብለዋል፡፡
 አርቲስት ፈለቀ የማርውሃ አበበ በበኩሉ፤ “ቴአትሩን ሳልፈልግ እንዳቋርጥ ያደረገኝ የማኔጅመንቱ ከአቅም በላይ የሆነ ችግር ነው” ብሏል፡፡ ቴአትር በፍፁም መቋረጥ የለበትም “The show must go on” የሚለውን መርህ ከማንም የበለጠ እንደማከብር፣ የእናቴን አስከሬን አስቀምጬ መድረክ ላይ መተወኔና የቀለበቴን ስነስርዓት ቴአትር ሰርቼ ስጨርስ እዚያው መድረክ ላይ መፈፀሜ  ምስክር ናቸው ብሏል፡፡
“ይሄን መርህ ለማክበር፣ ለሙያዬ ያለኝን ክብር ለመግለፅ እንዲሁም እኔን ሊመለከት የመጣውን ሰው ማክበሬንና ማፍቀሬን ለማሳየት፣ ማኔጅመንቱ ለሁለት ወር ያለ ክፍያ ሲያሰራኝ፣ ከኪሴ ወጪ እያወጣሁ፣ በነፃ ሳገለግል ቆይቻለሁ” ያለው አርቲስቱ፤ “ከቀረኝ ክፍያ ላይ ግማሹን የከፈሉኝ እንኳን ከ15 ቀን በፊት ነው፤ አሁንም ቀሪ ክፍያ አለኝ” ብሏል፡፡
“ማኔጅመንቱ የራሱን  ችግር ሳይቀርፍ በተለያዩ ሚዲያዎች ላይ እኔ ፈልጌ ስራውን እንዳቋረጥኩ ተደርጎ በተናፈሰው አሉባልታ በጣም አዝኛለሁ” ያለው አርቲስት ፈለቀ፤ “የቴአትር አፍቃሪያን ለስራዬ ፍቅርና ክብር እንዳለኝና ሀዘኔንም ደስታዬንም በመድረክ ላይ የማሳልፍ መሆኑን አውቆ እውነታውን እንዲረዳ እፈልጋለሁ” ብሏል፡፡ የስራ ውሉ እንዳልተቋረጠም አርቲስቱ አክሎ ገልጿል፡፡
የቴአትሩ ፕሮዱዩሰር አቶ ዘካሪያስ ካሱ፤ ከአርቲስት ፈለቀ ጋር የተፈጠረውን አለመግባባት በተመለከተ ጠይቀናቸው፤ “እኛ ከሁለት ወር በፊት በተፈፀመ ጉዳይ ላይ ጊዜ ማባከን ትተን አዲስ ስራ ጀምረናል፤ ቴአትሩን የፊታችን ሰኞ በአዲስ መልክ ለመጀመር ሩጫ ላይ ስለሆንን ምንም ዓይነት ምላሽ ለመስጠት ዝግጁ አይደለሁም” ብለዋል፡፡  


Published in ጥበብ
Page 4 of 19