ከአዲስ አበባ ከተማ የመልሶ ማልማት እንቅስቃሴ ጋር ተያይዞ የቅርስ ጥበቃ ጥያቄዎች ይነሳሉ፡፡ አንዳንድ ወገኖች የከተማዋ ቅርሶችና ታሪክ የልማቱ ሰለባ ሆነዋል በሚል ይተቻሉ፡፡ ለአንድ ከተማ የቅርስ ፋይዳ ምን ያህል ነው? በአሁኑ ወቅት ያለው የቅርስ አጠባበቅስ ምን ይመስላል? የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ኤልሳቤት ዕቁባይ፤ በቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለስልጣን የአለም አቀፍ ቅርሶች ምዝገባ የቡድን መሪና በአለም አቀፍ ቅርሶች አስተዳደር ዕቅድ ዝግጅቶች ከፍተኛ ባለሙያ የሆኑትን አቶ ኃይለመለኮት አግዘውን አነጋግራቸዋለች፡፡

አዲስ አበባ የቅርሶች ከተማ ናት ይባላል፡፡ እስቲ ያብራሩልኝ…
አዲስ አበባ ቅርሶች ያሏት ከተማ ናት፡፡ ስለ አዲስ አበባ ቅርሶች ስንናገር፣ በዘመን ከፍለን ብናየው፤ ለምሳሌ በአርኪኦሎጂ እንግሊዝ ኤምባሲ አካባቢ የሚገኘው የዋሻ ሚካኤል ተክለሃይማኖትን፤ በታሪክና በአርኪኦሎጂ ደግሞ የመናገሻ የደን ታሪክን መጥቀስ እንችላለን፡፡ በከተማዋ ውስጥ ከሚገኙት ቀደምት አብያተ ክርስቲያኖች የቀራኒዮ መድሃኒያለም ቤተክርስቲያንን ስንመለከት፣ በ1836 በንጉስ ሳህለ ስላሴ ዘመነ መንግስት የተሠራ ነው፡፡ የእንጦጦ ማርያም ቤተክርስቲያንና ኡራኤልን እንዲሁም ሌሎችንም ማንሳት እንችላለን፡፡ እነዚህ ከከተማዋ መቆርቆር ከ1879 በፊት የነበሩ ናቸው፤ ስለዚህ አዲስ አበባ ቅርስም ታሪክም ያላት ከተማ ነች፡፡
የአዲስ አበባ የቅርሶች ምዝገባ ምን ይመስላል?
የከተማዋ ከፍተኛ መሀንዲስ የነበሩት ዶክተር ወንድሙ የሚባሉ ባለሙያ በ1964 ዓ.ም በኢትዮጵያን ሄራልድ ጋዜጣ ላይ የ”አዲስ አበባ ቅርሶች ከየት እስከ የት” የሚል ጽሑፍ በእንግሊዝኛ አቅርበው ነበር፡፡ ሊሴ ገብረማርያም ት/ቤት ጋ የሚገኘውን የራስ ናደው ወሎ ቤት ወይም በተለምዶ “ዋይት ሃውስ” ተብሎ የሚጠራውን ቤት ፎቶ ጋዜጣው ይዞት ወጥቶ ነበር፡፡ ጥናቱን መሠረት በማድረግ የአዲስ አበባ ማዘጋጃ ቤት አንዳንድ ስራዎችን ሲሰራ ነበር፡፡ እሳቸው በወቅቱ በጋዜጣ ላይ የፃፉት ስጋታቸውን ነው፡፡ ስለ አዲስ አበባ ከተማ የቅርስ ስጋት መፃፍ የተጀመረው ከዚህን ጊዜ ጀምሮ ነው ማለት ነው፡፡ በ1979 ዓ.ም አዲስ አበባ መቶኛ አመቷን ስታከብር፣ ከተማዋ ሙዚየም ያስፈልጋታል በመባሉ፣ ኤግዚቢሽን ማዕከል አጠገብ የሚገኘው የራስ ብሩ ወልደገብርኤል መኖሪያ ቤት ታድሶ፣ የአዲስ አበባ ከተማ ተንቀሳቃሽ ቅርሶች የከተማዋን ታሪክ ሊተርኩ በሚችል መልኩ ፊንፊኔ፣ እድገት፣ አድዋ ወዘተ የተባሉ አዳራሾች እንዲቀመጡ ተደረገ፡፡ ቤቱ ቀደምት የኪነጥበብ ህንፃ የሚታይበት ነው፡፡
ከ1979 እስከ 1983 ዓ.ም የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ የሙዚየሙ የበላይ ጠባቂ ስለነበሩ፣ ሙዚየሙ በጀትና የቅርብ ክትትል ነበረው፡፡ በ1983 የመንግስት ለውጥ ሲመጣ በፌደራል የሚገኘው የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ሠራተኞች ዲሴንትራላይዝድ ሲሆኑ የቅርስ ሃላፊነት ሊኖራቸው የሚገቡ ሰዎች ለአዲስ አበባ ተመደቡ፡፡ መጀመሪያ የተዋቀረው የከተማዋ የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ቡድን ነው፡፡ የከተማዋን ታሪካዊ ቤቶች ለመጀመሪያ ጊዜ የአዲስ አበባ ወጣቶች ማህበርን በማስተባበርና ከተመደቡት ባለሙያዎች ውስጥ የተወሰኑት ቤቶቹን ቆጥረው ከተሰበሰበው መረጃ ውስጥ ወደ 130 የሚሆኑ ታሪካዊ ቤቶች የአዲስ አበባ ማስተርፕላን ክለሳ በተሰራበት ወቅት እንዲካተቱ ተደርጓል፡፡ ቤቶቹ በእድሜያቸው መርዘም ምክንያት ብቻ የተመዘገቡ ነበሩ፡፡ ነገር ግን የአዲስ አበባ ቅርሶች በአፄ ምኒሊክ ዘመን የተሠሩ ቤቶች ብቻ ናቸው ማለት አይደለም፡፡ በወቅቱ የተመዘገቡ ቦታዎችም ነበሩ፡፡ ለምሳሌ መስቀል አደባባይ፣ ጃንሜዳና እንጦጦ ተጠቃሽ ናቸው፡፡
እነዚህ ቦታዎች እንዴት ነው የተመረጡት?
ህዝብ በብዛት ወጥቶ የተለያዩ ክንዋኔዎችን የሚያደርግባቸው ስለሆኑ ነው፡፡ ወደ አስራ ሰባት የሚጠጉ የከተማዋ ሀውልቶችና አደባባዮችም ተመዝግበዋል፡፡ ቀደምት የሆኑ አብያተ ክርስቲያናትም ተመዝግበዋል፡፡
አዲስ አበባ ልትናገራቸው የምትችላቸው የራሷ የእድገት ደረጃዎች ያላት ከተማ ናት፡፡ ከ1879 እስከ 1928 ዓ.ም የምኒልክ ዘመን ኪነ ህንፃን እናያለን፡፡ ይሄ ዘመን በተለይ መጀመሪያ ላይ ወደ ቤተመንግስቱ የመጡትን የአርመኖችና ህንዶች ኪነጥበብ ህንፃ ያሳያል፡፡ ለምሳሌ የአርመኖቹን ብናይ፣ የአዲስ አበባ ወጣቶች እና ስፖርት ህንፃ አጠገብ የቦጐሲያን ቤት ይገኛል፡፡ ይህ ቤት እስከ አሁን ድረስ ውበቱ እንደተጠበቀ ያለ ቤት ነው፡፡ ጐጆ ቤት ነው፤ እዚያ ቤት ውስጥ ነው የአፄ ምኒልክ የሬሳ ሳጥን የተገጣጠመውና የተሠራው፡፡ አዲስ አበባ ከተማ ስትጀመር የነበረውን ገፅታ ያሳያል፡፡ እነ ሰባ ደረጃና እነ አርባ ደረጃን የምናይበት ነው፡፡ ቀደም ብዬ እንዳልኩት ከላይ በተጠቀሰው ጊዜ፤ የአርመኖች፣ የህንዶችና የግሪኮች አሻራ ያረፈባቸው ኪነ ህንፃዎች እናያለን፡፡
ከ1928 እስከ 1933 ዓ.ም ደግሞ ጣሊያኖች የራሳቸውን አሻራ ጥለው አልፈዋል፡፡ እነ ቤላ፣ ፖፓላሬ፣ ካዛንቺስ እንዲሁም የጣሊያን እስር ቤትና ፖሊስ ማዘዣ የነበረውን ራስ ሆቴልና ኢሚግሬሽን፣ የጣሊያን ዘመንን የሚያሳዩ ናቸው፡፡ ከጣሊያን መውጣት በኋላ ከ1933 እስከ 1966 ዓ.ም አዲስ አበባ ውስጥ የተለያዩ ህንፃዎች ተሠርተዋል፡፡ የአፍሪካ ህብረትን፣ ማዘጋጃ ቤቱን፣ ብሔራዊ ትያትር አካባቢ ያሉትን ህንፃዎች፡- መከላከያ ሚ/ር፣ ብሄራዊ ባንክን… መጥቀስ ይቻላል፡፡ እስከ አሁን ድረስ የከተማዋን ውበት የሚያደምቁ ህንፃዎች ናቸው፡፡ ከ1966 እስከ 1983 የደርግ ዘመን ማብቂያ ድረስ ደግሞ የራሺያና የቡልጋሪያ የኪነ-ህንፃ ባለሙያዎች ስራ የሆኑ ህንፃዎችን እናያለን፡፡ ለምሳሌ ሰሜን ኮሪያውያኖቹ የሠሩት ጥቁር አንበሳ ጋ ያለው ሀውልት፣ ከጀርባው ደግሞ የዩጐዝላቪያ ባለሙያዎች ያነፁትን የጥቁር አንበሳ ሆስፒታልን እናገኛለን፡፡ በቦሌ መስመር ላይ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት የሚኖሩበት አፓርታማዎች በራሺያዎች የተሠሩ ናቸው፡፡ ኢህአዴግ አገሪቷን ማስተዳደር ከጀመረ በኋላም አዲስ አበባ እጅግ በጣም ፈጣን የከተማ እድገት እያሳየች ነው፡፡
ከተማዋ በስፋትም ሆነ በነዋሪዋ ብዛት ከፍተኛ ለውጥ ያመጣችበት ጊዜ ነው፡፡ ከተማዋ እንደ ገርጂ፣ አያት፣ ላፍቶ፣ ገላን፣ አየር ጤና የተባሉ አዳዲስ ሰፈሮችን አካትታለች፡፡ መሀል ከተማዋ ውስጥ ከፍተኛ የግንባታ ስራ እየተሠራ ነው፡፡ እዚህ ላይ ትልቁ ጥያቄ፣ “አዲስ ስንሰራ መነሻችን የሆነውን እንዴት በማድረግ ነው?” የሚለው ነው፡፡ አዲስ የባቡር መስመር ዝርጋታ እየተካሄደ ነው፡፡ ነገር ግን የመጀመሪያው የባቡር ሀዲድ ታሪካዊነቱ ቦታ ተሠጥቶት ጥበቃ አልተደረገለትም፡፡ የከተማዋ ነዋሪ ሳይቀር አፈር እያለበሰ ቤት ሠርቶበታል፡፡ ኤርትራ ውስጥ ከአቆርዳት እስከ ምፅዋ ያለው የባቡር መስመር ለቱሪዝም ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያደረገ ነው፡፡ ልማቱ ሠለባ ያደረጋቸው ቅርሶች አሉ፡፡ የአልሜክ ስልጣኔን የሚያሳየውና ሜክሲኮ አደባባይ የነበረው የራስ ቅል የተነሳ ሲሆን ተመልሶ ይሠራል የሚል ቃል ተገብቷል፡፡
ከመልሶ ማልማቱ ጋር ተያይዘው የሚነሱ የቅርስ ጥበቃ ጉዳዮች በምን ሁኔታ ላይ ይገኛሉ?
ከተማዋ አማካሪ አላት ወይ? የሚያስብሉ ስህተቶች ተፈፅመዋል፡፡ ለምሳሌ የአራት ኪሎ ሀውልትን የሚሸፍን ድልድይ መስራት ተገቢ አልነበረም፡፡ መስቀል አደባባይ የተሠቀሉ ትልልቅ የማስታወቂያ ሠሌዳዎች የቦታውን ታሪካዊነት ጋርደውታል፡፡ አደባባዩን ባቡሩ ማቋረጡ በራሱ አካባቢውን ለውጦታል፡፡ በአጠቃላይ ስርአት ይመጣል፤ ስርአት ይሄዳል፡፡ ያለፈው የሚባለው ትውልድ ጥሎት የሄደው መቀመጥ አለበት፡፡ የአዲስ አበባን ልማት በተመለከተ ለመነጋገር ማነፃፀር ያስፈልጋል፡፡ የምናነፃጽረው የድሮውን አሳይተን ነው፡፡ ሠፈሮቹን፣ በየሠፈሩ ውስጥ የነበሩ መስተጋብሮችን፣ ማህበራዊ ግንኙነትንና ትስስሩን ማቆየት አለብን፡፡ ስልጣኔ ማለት ትስስሩን ማጥፋት አይደለም፡፡ የተለያየ ርዕዮተ አለም ያልበገራቸውን ትስስሮች መጠበቅ አለብን፡፡ የመጀመሪያው ሲኒማ ቤት ሰይጣን ቤት ይባላል፡፡ ለምን እንደዚያ እንደተባለ የአሁኑ ትውልድ ሊያውቀው በሚገባ መልኩ መተረክና እዛው ቤት ውስጥ መፃፍ አለባት፡፡ በአለም ላይ ሲኒማ ከተፈለሠፈ በኋላ በአጭር ጊዜ ውስጥ ቴክኖሎጂው ከደረሳቸው አገሮች አንዷ ኢትዮጵያ ናት፡፡
የፊልም ኢንዱስትሪውን ለማነፃፀር፣ ያንን ቤት መጠበቅ አለብን፡፡ አዲስ አበባ ከተመሠረተች 125 አመቷ ነው ብለን፣ አዳዲስ ህንፃዎችን ብቻ የምናሳይባት ሳይሆን ዕድገቷን ራሷ ማሳየት የምትችል መሆን አለበት፡፡
ቅርሶች በማን ነው የሚያዙት?
ቅርሱን አድሰን እናስተዳድራለን ለሚሉ ወገኖች ይሰጣል፡፡ በግል የተያዙ ታሪካዊ ቤቶች እኮ አሉ፡፡ ልዕልት ማርያም፤ የመሐመድ አሊን ቤት “አዲስ ውበት” በሚባል ድርጅታቸው እንዲያድሱ ተደርጓል፡፡ ሞዴል ሊያ ከበደ፤ የደጃዝማች አያሌው ብሩን ቤት አድሳ ይዛዋለች፡፡ የቀድሞው የአዲስ አበባ ማዘጋጃ ቤት የነበረው የቢትወደድ ሃይለጊዮርጊስ መኖርያ ቤት ለቅርስ ባለ አደራ ተላልፏል የሚባል ነገር አለ፡፡ ያ ቤት አሁን መታደስ አለበት፡፡
አቶ አሰፋ ተሰማ፤ የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባ የነበሩ ሰው ናቸው፡፡ በአንድ ወቅት ሲናገሩ፤ “ከተሜነት ወሳኝ ነው፤ የአዲስ አበባ አብዛኛው ነዋሪ ከገጠር የመጣ ነው፡፡ የከተሜ የአኗኗር ባህል ሊኖር ይገባል፡፡ ይህ ደግሞ አመራሩ ላይ መንፀባረቅ ይኖርበታል፡፡ አመራሩ ከተሜ መሆን አለበት፡፡ ከተሜነት የግድ ከተማ መወለድ አይደለም፡፡ ከተሜነት ከተማዋ ሊኖራት የሚገባውን ደረጃ ማየት መቻል ነው፡፡ ለምሳሌ ከደብረ ዘይት መንገድ ወደ አዲስ አበባ የሚገባ ሰው መሃል አዲስ አበባ ከተማ መግባቱን እንዲያይ ተብሎ ነው መንገዱ ገለጥ ያለው፡፡ የአንበሳ ህንፃ ዲዛይንም መንገዱን ተከትሎ እንዲሠራ ተደርጐ ነበር…” ብለው ነበር፡፡ በከተማ ዕቅድ የታወቁ ከንቲባዎች የነበሯት ከተማ ናት፤ ለንደንን ዲዛይን ያደረጉ ሰዎች በአዲስ አበባ ማስተርፕላን ላይ ተሳትፎ አድርገዋል፡፡ የእነዚህን ሰዎች ግብአት መጠቀም አለብን፡፡ የግድ ሰዎች ይህ ቦታ ታሪካዊ ነው” እያሉ መጮህ የለባቸውም፡፡ ከተማው ራሱ መናገር አለበት፡፡ መርካቶ አሁን በህንፃ እየተሞላ፣ የቀድሞውን ታሪካዊ እሴት እያጣ ነው፡፡ የግድ ማፍረስ አይጠበቅም እኮ፡፡ ከተማዋ ሠፍታለች፤ ቅርሶቿንና ታሪኳን በማይነኩ ቦታዎች መጠቀም ይቻላል፡፡ ፀሐይ ሪል እስቴትን ማየት ይቻላል፡፡ በአለም ላይ አሮጌና አዲሱ ከተማ ያሉባቸው ቦታዎች አሉ፡፡ ካይሮ ጥሩ ምሳሌ ትሆናለች፡፡ አዲስ አበባንም እንደዚያ መስራት ይቻላል፡፡ “ሠፈሮቹ ያለፈው ስርአት ገዢ መደብ ወይም የነፍጠኛ መቀመጫ ስለነበሩ…” እያለ የሚያስብ ካለ ጤነኛ አይደለም፡፡ ይህ አይነት አስተሳሰብ ያላቸው ከአመራር መወገድ አለባቸው፡፡ የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ቡድን ተቋቁሞ የቆየው እስከ 1995 ድረስ ነው፡፡ በ1995 መዋቅር ሲሰራ፣ የቅርስ አስተዳደር፣ ንግድና ኢንዱስትሪ ቢሮ ውስጥ ገብቶ ነበር፡፡ ብዙ ጥፋት የደረሰው ያን ጊዜ ነው፡፡
በአንተ ዕይታ ኢትዮጵያ ሆቴል አካባቢ ያሉት ህንፃዎች ከምን ይመደባሉ?
በኔ ዕይታ በአጠቃላይ ብሔራዊ ትያትርና አካባቢው ቅርስ ነው፤ ዘመን ተናጋሪ ህንፃዎች ናቸው፡፡ ብሔራዊ ትያትር ጋ ያለው አንበሳ የከተማዋ አርማ ነበር፡፡ በነገራችን ላይ ከንቲባ ዘውዴ በላይነህ ሀውልቱን ሲመርቁ፤ “ይህ አንበሳ አንበሳ ባይመስልም የወጣበት ወጪ ግን አንበሳ አድርጐታል” ማለታቸው ይነገራል፡፡ ሰዓሊ ደስታ ሃጐስም ለቱሪዝም “የ13 ወር ፀጋ”  የሚለውን ስትሰራ የአንበሳውን ፊት በመውሰድ አርማ አድርጋዋለች፡፡ ህንፃዎቹ ብቻ አይደሉም፤ ከፍል ውሃ እስከ ሜትሮሎጂ ጫፍ ያሉት ዛፎች ጭምር ቅርስ ናቸው፡፡ ኢትዮጵያ ሆቴል አጠገብ ምን አይነት ህንፃ ይሠራ ይሆን? ከባድ ነው፡፡ የህንፃው ርዝመትስ ከመከላከያ ሚ/ር አንፃር እንዴት ሊሆን ነው?
ቅርስ በዩኔስኮ ማስመዝገብ ፋሽን እየሆነ የመጣ ይመስላል፡፡ እስቲ ስለሱ ይንገሩኝ…
ብዙ ሰው ቅርሱ የሚጠበቀው ዩኔስኮ ስለመዘገበው ይመስለዋል፡፡ ሌላው ደግሞ ቅርስ ማስመዝገብን ክልሎች ፉክክር የያዙበት ይመስላል፡፡ “የትኛውን መስቀል ነው ያስመዘገባችሁት?” ብሎ የጠየቀ ሃላፊ አለ፡፡ የተመዘገበው አከባበሩ ነው፤ ዩኔስኮ ሃይማኖት አይመዘግብም፡፡ የሶፍኦመርና ድሬ ሼክ ሁሴንን ለማስመዝገብም ጥረት እየተደረገ ነው፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ በሺዎች የሚቆጠሩ ባህላዊ አመጋገቦች፣ ከእምነት ጋር የተያያዙ ባህሎች አሉ፡፡ ለነዚህ ሁሉ ዩኔስኮ መዝገቡን ከፍቶ ይጠብቃል ማለት አይደለም፡፡ እንደ ኦሎምፒክ ተወዳድሮ ነው የሚመዘገበው፡፡ ሚ/ር መ/ቤቱም ምዝገባውን በተመለከተ መመሪያዎችን እያወጣ ነው፡፡ ዩኔስኮ አንድን ቅርስ ሲመዘግብ ቅድመ ሁኔታዎች አሉት፡፡ ለምሳሌ ታንዛኒያ አንድ የሆነ ቦታን ቅርስ ብለው ካስመዘገቡ በኋላ፣ ቦታው ላይ ነዳጅ ተገኘ ተባለ፡፡ ነገር ግን ነዳጅ ማውጣት ተከልክለዋል፡፡
ቅርሶችን በዩኔስኮ ማስመዝገብ ምንድን ነው ጥቅሙ?
ቅርሱን ለመጠበቅ የተወሰኑ ዕገዛዎች ይደረጋል፡፡ እኛ አገር በአንዳንድ ቦታ ባህሉን ትተው ለቱሪዝሙ ከፍተኛ ትኩረት ይሰጣሉ፡፡ ለቱሪዝሙ ዋናው ነገር ባህሉ መሆኑን ይረሱታል፡፡
በቅርቡ ለመመዝገብ የደረሰ ቅርስ አለ?
አዎ፤ ደቡብ ክልል ውስጥ ብራይሌ/አንጐይታ በመባል የሚታወቅና በአሁኑ ወቅት ስምንት ሰዎች ብቻ የሚናገሩት ቋንቋ አለ፤ እሱን ለማስመዝገብ ጥያቄ አቅርበን፣ ማስተካከያዎች እንድናደርግ ወደኛ ተልኳል፡፡ የገዳ ስርአትንም ለማስመዝገብ በሂደት ላይ ነን፡፡  

Published in ህብረተሰብ
Saturday, 08 November 2014 11:11

‘የቻይና ሆድ…’

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ሰውየው… አለ አይደል…ፊቱ የሚያስፈራ…፣ “አጠገቡ ምግብ አይበላም…” የሚባል አይነት ነው፡፡ እናማ አንዱን እንዲህ ይለዋል…
“ለመሞት ተዘጋጅ፡፡”
“ለምን?”
“እኔን የሚመስል ሰው ካገኘሁ ከዚህ ዓለም አሰናብተዋለሁ ብዬ ለራሴ ቃል ገብቻለሁ፡፡”
“አንተን እመስላለሁ እንዴ?”
“ቁርጥ እኔን ነው የምትመስለው፡፡”
“እንግዳው ከዚች ዓለም አሰናብተኝ፡፡”
እንዲህ ከመባል ይሰውራችሁማ!
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ዘንድሮ ምነዋ የራሳችንን መልክና ቁመና የምንጠላ ሰዎች በዛንሳ!
ሰውየው ሞቅ ብሎት ቤቱ ይገባል፡ ግድግዳው አጠገብ ተጠግቶ አፍጦ ሲያይ ይቆያል፡፡ ከዛም ለሚስቱ… “ይሄ ግድግዳው ላይ ፎቶው የተሰቀለው አስጠሊታ ሰው ማነው?” ይላታል፡፡ ሚስትም…“ፎቶ አይደለም፡፡ በመስታወት የራስህን መልክ እያየህ ነው…” ብላው አረፈች፡፡ ሌላ ልጨምርላችሁ…ሰውየው ጓደኛው ላይ ‘ሙድ ለመያዝ’ …“አንድ ጊዜ ልክ እንዳንተ ችምችም ያለ ጢም ነበረኝ፣፡ እንዴት አስጠሊታ እንደመሰልኩ ሳይ ግን ሙሉ ለሙሉ ተላጨሁት፡፡”
ጓድኝየው ምን ብሎ ቢመልስለት ጥሩ ነው…“እኔም አንድ ጊዜ ያንተን የሚመስል ፊት ነበረኝ፣ ግን እንዴት አስጠሊታ እንደመሰልኩ ሳይ ጊዜ ፊቴን ለመሸፈን ጢሜን አሳደግሁት፣” ብሎት እርፍ፡፡
እናማ…‘ሙድ የሚያዝበትን’ ሰው መምረጥ አሪፍ ነው፡፡
ስሙኝማ… ዛሬ ከረባት ሆዱ ላይ ‘ጣል’ አድርጎ ሲንጎማለል እይታችሁት በማግስቱ ደግሞ ሆድ የሚባል ነገር ያጣችሁበት ሰው ገጥሟችሁ አያውቅም! ነገርዬው እንዴት መሰላችሁ…ሠርግ ላይ ወይም ሌላ ሰው ለሰው የሚተያይበት ስፍራ ሲሆን ከረባቷ ትደረግና ሆድ ላይ ደገፍ ትላለች፡፡ (“‘ቦርጭ’ ለከረባት ነው ይባል የለ! የምንታውቀው ሰው ሆድ በአጭር ጊዜ ተጠቅለሎ፣ ተጠቅለሎ ያያቸ አንዲትሴተ ምነ አለች አሉ መሳለችሁ…እኔ ሳውቀው እኮ አንድ ሆድ ብቻ የበረው ጊዜ ነው አለች አሉ፡፡)
ታዲያላችሁ…በማግስቱ ከረባት ማድረግ በማያስፈልግበት ጊዜ ሆዷም ከከረባቱ ጋር አብራ ‘ትወልቃለች’! ልክ ነዋ…ነገርዬው ምን መሰላችሁ… ሰዎች ጥብብ ያለች ካናቴራ ይለብሳሉ፡፡ ይሄኔ ሆድ እንደ አቅሚቲ ‘ትቆዘራለች’፡፡ በዚህ ጊዜ ‘ቦርጭ’ መሰለች አይደል! (አሁን፣ አሁን ደግሞ ከመጥበቧ የተነሳ ‘ደም ስር ልትዘጋ የምትችል’ የመሰለች ካናቴራ ለብሰው ‘ደረት የሚገለብጡ’ ጎረምሶች ገጥመዋችሁ አያውቅም!)
እናላችሁ…የዚች አይነት ስትፈለግ ብልጭ የምትል፣ ስትፈለግ ደግሞ ‘የምትሰወር’ ሆድ ምን ትባላለች መሰላችሁ… ‘የቻይና ሆድ’! አሪፍ አይደለች!
እናላቸሁ ዘንድሮ ብዙ ነገሮች ‘የቻይና ሆድ’ ሆነዋል፡፡ ዛሬ ያያችሁት መልካም የሚመስል ነገር በማግስቱ አይደገምም፡፡ አንድ ሰሞን እገራቸው እስኪቀጥን እየተሯርጡ የሚያገለግሏችሁ የሆነ ድርጅት ሠራተኞች በአራተኛው ቀን…የዲያብሎስ ዕቁብተኞች ሆነው ቁጭ ይሉላችኋል፡፡ መሯሯጡ ‘የቻይና ሆድ’ አይነት ነገር ነዋ!
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…የአንዳንድ ዘፈኖቻችን ስንኞች ይለወጡልን፡፡ ለምሳሌ…
አሁን የእኔ አሟሟት አሟሟት ነው ወይ
ጉች፣ ጉች ያለ ጡት አንድ ቀን ሳላይ፣
የሚለው ስንኝ ይለወጥልንማ፡፡ አሀ፣ ልክ ነዋ!…ዘንድሮ ጉች፣ ጉች ያለ ጡት ‘ከመርካቶ ይሸመታላ!’ “አየሀት ያቺን ሴትዮ፣ እንደ አሜሪካን ፓትርዮት ሚሳይል ነው እኮ የደገነቻቸው…” የሚባለላቸው ነገረዬዎች የእውነትም እንደ ሚሳይሎቹ ‘የተተክሉ’ ሊሆኑ ይችላሉ! እናማ… የዚህ አይነት ጉች፣ ጉቾች ምን ይባሉ መሰላችሁ…‘የቻይና ሆድ’!
ለምሳሌ… አለ አይደል… “እንደው ፈጣሪ ሙሉ ቀን እነሱን ሲያሰማምር የዋለ ነው እኮ የሚመስለው…” የሚባልላቸው የአንዷን እንትናዬ የዓይን ሽፋሎች ታያላችሁ፡፡ እናማ…የእኔ ቢጤ ሞኝ… አለ አይደል… “የዓይኖቿ ሽፋሎች ልቤን አርገብገበው…” ምናምን ብሎ አዝማሪ ቤት ስንኝ ሲያስቋጥር ያመሻል፡፡ ‘የቻይና ሆድ’ መሆናቸውን አላወቀማ!…ሽፋል ‘ከመርካቶ ይሸመታላ!’
“አቤት ዳሌና መቀመጫ! ዚታዎ ከእነሪሞርኪዮ ነው የሚስለው፡፡ ሰው እንዲህ ተስተካከሎ ይወለዳል!”  ወይንም… እንደ ሆሊዉድ አክተሮች በሁለት ጎኗ ትላልቅ የማካሮቭ ሽጉጦች የታጠቀች ነው እኮ የሚመስለው…!” ብሎ ነገር አይሠራም፡፡ ዚታዎ ከእነሪሞርኪዮ የሚባል ዳሌና ‘አክሰሰሪዎቹ’ (ቂ…ቂ…ቂ…) ‘ከመርካቶ ይሽመታሉዋ!’
እናላችሁ…የሆነ የውሀ ዋና ቦታ ወይም ‘እዛ ቦታ’ ጂንስ ምናምን ሆዬ ውልቅ ሲል “ዚታዎ ከእነሪሞርኪዮም” አብሮ ውልቅ! ‘የቻይና ሆድ’ ነዋ!
እንትና…እስቲ ፒያሳ ምናምን ብቅ በልና ‘ስማርት ፎን’ የሚባለው የእንትናዬዎች ቁመና ምን አይነቱ እንደሆነ ጠቁመኝማ፡፡ ‘ስማርት ፎን’ አሪፍ ስም ነዋ…
ስሙኝማ…እግረ መንገዴን የስማርት ፎን ምናምን ነገር ካነሳን አይቀር የሆነ ነገር ትዝ አለኝማ… በዘንድሮው ቴክኖሎጂ…ሞባይላችን ጠፍቶ እንኳን የምንናገረውን ነገር መስማት ይችላል የሚሉት እውነት ነው እንዴ! ማወቅ አለብና! ቴክኖሎጂው ሳይገባንስ!
ዘንድሮ እንደሁ…አለ አይደል…
ባልሽ ፊልድ ሊሄድ ስንቁ ሲሰናዳ
እኔ ጓሮ ሆኜ በሳቅ ለፈነዳ፣
አይነት ነገር ኋላ ቀር ሆኗላ! ዕድሜ ለሞባይል… “ሰውዬሽ ሲወጣ ምልክት አድርጊልኝ…” ማለት ይበቃላ! እናማ… በየቀኑ በሞባይል ስልክ መናገር የምንችላቸውና የማንችላቸው ነገሮች ተለይተው ማኑዋል ነገር ይዘጋጅልንማ! አለበለዛ… “ባልሽ ፊልድ ሊሄድ…” ምናምን ወደ ማለቱ እንመልሳለን፡፡
እናላችሁ…ምን ለማለት ፈለገ ነው  አይነት ነገር ነው፡፡ (ስሙኝማ…በቀደም በአንድ የኤፍ.ኤም. ሬድዮ ፕሮግራም ላይ ሥራ ሲለቅ “የመሥሪያ ቤቱን ዌብሳይት አስረክብ…” ስለተባለው ሰው ሰምተን ስንስቅ ከረምን ነው የምላችሁ፡፡ ስንቱን ጉድ ነው የምንሰማው!)
ሰውየው የ‘ገርል ፈሬንዱ’ን ፎቶ ለጓደኛው ያሳየዋል፡፡ እናማ…ጎራዳ የምንላት አይነት ነች፡፡ ታዲያላችሁ…ምን ይልላችኋል… “ገርሌን አየሀት፣ ልክ እኮ ከመንግሥተ ሰማያት ተወርውራ እቅፌ ውስጥ የወደቀች ነው የምትመስለው…” ይለዋል፡፡ ጓደኛ ሆዬ ምን ቢል ጥሩ ነው… “አዎ ፊቷ ቀድሞ መሬት ላይ ያረፈ ነው የሚመስለው፣፡” ከእንዲህ አይነት ጓደኛ ይሰውራችሁ፡፡
ሰውየው የ‘ገርል ፍሬንዱ’ን ፎቶ ለጓደኛው ያሳየዋል፡፡ እናማ…ጎራዳ የምንላት አይነት ነች፡፡ ታዲያላችሁ…ምን ይልላችኋል… “ገርሌን አየሀት፣ ልክ እኮ ከመንግሥተ ሰማያት ተወርውራ እቅፌ ውስጥ የወደቀች ነው የምትመስለስው…” ይለዋል፡፡ ጓደኛ ሆዬ ምን ቢል ጥሩ ነው… “አዎ ፊቷ ቀድሞ መሬት ላይ ያረፈ ነው የሚመስለው፣፡” ከእንዲህ አይነት ጓደኛ ይሰውራችሁ፡፡
እናላችሁ…ዘንድሮ ብዙ ነገር ብዙ ነገራችን ‘የቻይና ሆድ’ ሆኗል፡፡ ሰዉ ሁሉ እውነተኛ ራሱ ይሁን፣ የቻይና ሆድ ግራ የሚያጋባ ዘመን ላይ ደርሰናል፡፡  
አንድ ሰሞን ቢ.ፒ.አር. ምናምን የሚባል ነገር ተነሳና መሥሪያ ቤቶች… “ሀያ ቀን ይፈጅ የነበረውን በሀያ ደቂቃ ብቻ…” ምናምን እያሉ አገር ምድሩ “በሥራ ፍቅር” ትንፋሽ አጥሮት ነበር፡፡ ጥቂት ወራት እንዲህ ከሆነ በኋላ ነገሮች ወደነበሩበት ተመለሱ፡፡ መጀመሪያም ቢሆን ሩጫው ‘የቻይና ሆድ’ ነገር ነበራ!
ከ‘ቻይና ሆድ’ አስተሳሰብ የምንላቀቅበትን ጊዜ ያፍጥልንማ!
ደህና ሰንበቱልኝማ!

Published in ባህል

            የቀድሞ የ“ፍትህ” ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ፤ በተከሰሰበት የወንጀል ክስ ጥፋተኛ ተብሎ የ3 ዓመት እስርና የ10ሺህ ብር የገንዘብ መቀጮ እንዲቀጣ መወሰኑ የህግ ባለሙያዎችን ጨምሮ ብዙዎችን ያነጋገረ ርዕሰጉዳይ ሆኗል፡፡
ከሁለት ዓመት በፊት ጋዜጠኛ ተመስገን የ“ፍትህ” ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ሆኖ ሲሰራ፣ በጋዜጣው ላይ የሚወጡ ፅሁፎችን የመቆጣጠር ኃላፊነት እያለበት አመፅ ቀስቃሽ፣ የመንግስትን ስም የሚያጠፉና የህዝቡን ስሜት የሚያናውጡ ፅሁፎችን አትሞ በማውጣቱ ክስ እንደተመሰረተበት ይታወሳል፡፡
አቃቤ ህግ እነዚህን ክሶች ሲያቀርብ፣ በ1996 ዓ.ም የወጣውን የወንጀለኛ መቅጫ ህግ አንቀፆች መሰረት አድርጎ ሲሆን የወንጀል ህጉን 257(ሀ)ን በመተላለፍ፣ አመፅ ቀስቃሽ የሆኑ ፅሁፎችን በጋዜጣው እንዲታተሙ በማድረግ፣ የወንጀል ህግ 244ን በመተላለፍ የመንግስትን ስም የሚያጠፉና በሃሰት የሚወነጅሉ ፅሁፎችን እንዲታተሙ በማድረጉና የወንጀል ህጉን አንቀፅ 486 (ሀ)ን በመተላለፍ፣ የህዝብ ስሜትን የሚያናውጡ ፅሁፎች እንዲታተሙ ማድረጉን ጠቅሶ ነው፡፡
የ3 ዓመቱ እስራትና የ10ሺ ብር መቀጮውም እነዚህን አንቀፆች በተለይም የወንጀለኛ መቅጫ አንቀፅ 257ን (መንግስትን በአመፅ ለመጣል ግዙፍ ያልሆነ መሰናዳትን በተመለከተ የሚደነግግ ነው) መሰረት በማድረግ የተላለፈ ነው፡፡
በሌላ በኩል የመገናኛ ብዙኃንና የመረጃ ነፃነትን ለመደንገግ የወጣው አዋጅ ቁጥር 590/2002/፤ በመገናኛ ብዙሃን ሊፈፀሙ የሚችሉ የህግ ጥሰቶችን በየአንቀፆቹ ከዘረዘረ በኋላ “ቅጣት” ብሎ የገንዘብ መቀጮን ብቻ ያስቀምጣል፡፡ በእስራት ስለሚፈፀም ቅጣት አዋጁ ያስቀመጠው ድንጋጌ የለም፡፡
በአዋጁ ክፍል አምስት፤ “ህጋዊ እርምጃዎችን ስለመውሰድ” በሚለው ርዕስ ስር፣ በአንቀፅ 45 ስለ ቅጣት እንዲህ ሲል ይደነግጋል፡- “በዚህ አዋጅ የተደነገገውን የተላለፈ ማንኛውም ሰው ከብር 20 ሺ እስከ ብር 200 ሺ ባላነሰ መቀጮ ይቀጣል”፡፡
ሰሞኑን በጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ላይ በወንጀለኛ መቅጫ ህጉ መሰረት እስራትና ቅጣት መወሰኑን ተከትሎ የተለያዩ የህግ ባለሙያዎችና አስተያየት ሰጪዎች፤ “ጋዜጠኛው የገንዘብ መቀጮን ብቻ የሚደነግገው የፕሬስ አዋጁ እያለ በወንጀለኛ መቅጫ አንቀፆች መከሰሱ አግባብ አልነበረም” ብለዋል፡፡
እነዚህ ወገኖች፤ የመገናኛ ብዙሃንን የመረጃ ነፃነትን ለመደንገግ የወጣው አዋጅ አንቀፅ 49 ከአዋጁ ጋር ስለሚቃረኑ ህጎች እንዲሁም በአንቀፅ 50 ላይ ስለተሻሩ ህጎች የተጠቀሱትን አንቀፆች ዋቢ በማድረግ መከራከሪያቸውን ያቀርባሉ፡፡
በአዋጁ አንቀፅ 49 ላይ፤ “ከዚህ አዋጅ (በ2002 የወጣው የፕሬስ አዋጅ ማለቱ ነው) ጋር የሚቃረን ማንኛውም ህግ፣ ደንብ፣ መመሪያ፣ ትዕዛዝ ወይም የተለመደ አሰራር በዚህ አዋጅ በተመለከቱ ጉዳዮች ላይ ተፈፃሚ አይሆንም” ይላል፡፡
ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የህግ ት/ቤት መምህር፤ በ1996 ዓ.ም ተሻሽሎ የወጣው የወንጀለኛ መቅጫ ህግ አንዳንድ አንቀፆች እንደገና መታየት እንዳለባቸው ጠቁመው፤ በተለይም ተመስገን ላይ ለክስ መነሻ የሆኑት የወንጀለኛ መቅጫ አንቀፆች ከህገመንግስቱ አንቀፅ 29፣ ሃሳብን በነፃነት ከመግለጽ ጋር እንዲጣጣሙ ተደርገው መቀረፅ ነበረባቸው ይላሉ፡፡
“አንድ መንግስት በሚሰራቸው ስህተቶች በሚገባ ተብጠልጥሎ ካልተተቸ ዲሞክራሲያዊ የሚያስብለውን መሰረት ያጣል” የሚሉት አስተያየት ሰጪው፤ በህጎቹ ላይ አመፅ መቀስቀስ፣ የመንግስትን ስም ማጥፋትና አመኔታ ማሳጣት የሚሉት አንቀፆች ሃሳብን በነፃነት ከመግለፅ መብት አንፃር በጥንቃቄ መታየትና መታረም እንዳለባቸው ይገልፃሉ፡፡ “የፕሬስ አዋጅ ተብሎ በህግ መቀመጡን ራሱ እቃወማለሁ” ያሉት የህግ መምህሩ፤ “የፕሬስ አዋጁ ስለ መረጃ አጠያየቅና አሰጣጥ፣ ክልከላ ስለሚደረግባቸው እንዲሁም ከስም ማጥፋት ጋር የተያያዙ ጉዳዮች እንዴት ሊታዩ ይችላል ከሚለው ሃሳብ ውጪ አሁን ጋዜጠኛ ተመስገን ከተከሰሰባቸው ጉዳዮች ጋር ግንኙነት ያላቸው አንቀፆች በሚገባ የሉትም” ሲሉ አስረድተዋል፡፡ በዚህም የተነሳ ተመስገን በየትኛው ህግ አንቀፆች መጠየቅ ነበረበት በሚለው ላይ አስተያየት ለመስጠት እቸገራለሁ ብለዋል - መምህሩ፡፡
የህግ አማካሪና ጠበቃ ተማም አባቡልጋ በዚህ ጉዳይ ላይ መደናገር የተፈጠረው ለምን እንደሆነ ሲያስረዱ፤ “ከወንጀለኛ መቅጫ ህጉ በተጨማሪ የፀረ-ሽብር አዋጅና የፕሬስ አዋጅ በስራ ላይ እንዲውሉ በመደረጉ ነው” ይላሉ፡፡ አንድ አገር ውስጥ የተለያዩ የወንጀል ህጎች መኖራቸው ለግለሰብ ብቻ ሳይሆን ለህግ ባለሙያውም አደናጋሪ መሆኑን ጠቁመው፤ በሃገሪቱ አንድ የወንጀለኛ መቅጫ ህግ ብቻ መኖር ነበረበት ብለዋል፡፡ “አሁን አቃቤ ህግ፤ ጋዜጠኛን መክሰስ ሲፈልግ ሲያሻው በፀረ-ሽብር ህጉ አሊያም በወንጀል ህጉ፣ ደስ ካለውም በፕሬስ ህጉ ሊከስ እንዲችል ተመቻችቶለታል” ባይ ናቸው፡፡
መጀመሪያ የወንጀለኛ ህጉ፣ ቀጥሎ የፕሬስ አዋጁ እንደ መውጣቱና  የተፈጻሚነት ወሰንን የሚደነግግ እንደመሆኑ ፕሬስን የተመለከቱ ጉዳዮች ተፈፃሚ መሆን የሚገባቸው በ2002 በወጣው የፕሬስ አዋጁ ነው ያሉት ጠበቃው፤ የተመስገን ጉዳይም በዚህ መሰረት መታየት ነበረበት ብለዋል፡፡
የጋዜጠኛ ተመስገን ጠበቃ አቶ አምሃ መኮንን በበኩላቸው፤ ከሚዲያና ብሮድካስት ጋር የተያያዘ ወንጀል በሁለት መንገድ ነው የሚታየው ይላሉ፡፡ የሚዲያውን ተቋማት አሰራር ለመደንገግ የወጣውን አዋጅ በመጣስ የሚሰራ ጥፋትን ተከትሎ የሚጣል ቅጣት አለ የሚሉት አቶ አምሃ፤ ይህ መሰሉ በመገናኛ ብዙሃን የመረጃ ነፃነት አዋጅ የሚዳኝ እንደሚሆን ይገልፃሉ፡፡ በወንጀል  መቅጫ ህጉ ላይ የተደነገጉትን መጣስ ደግሞ ሌላኛው ወንጀል እንደሆነ ጠበቃው ያስረዳሉ፡፡
የወንጀል ህጉ በእርግጥም ሃሳብን በነጻነት ከመግለፅ ጋር የተያያዘ ጥያቄ ያስነሳል ያሉት አቶ አምሃ፤ ነገር ግን ጋዜጣን እንደ መሳርያ ተጠቅሞ በወንጀል ህጉ ላይ የተደነገጉትን መጣስ የሚታየው በወንጀል ህጉ ነው ይላሉ፡፡
“ተመስገን ከተከሰሰባቸው ሶስቱ አንቀፆች መካከል ጥፋተኛ ተብሎ ቅጣት የተጣለበት አንቀፅ 257፣ የሚዲያ ውጤቶችን በመጠቀም ህዝብን ለአመፅ መቀስቀስ ወንጀል ነው ሲል ቅጣቱንም አያይዞ ይደነግጋል፤ ይሄ ህገ መንግስታዊ ነው አይደለም የሚለው በራሱ የሚያነጋግር ነው” ያሉት ጠበቃው፤ የአመፅ መቀስቀስ የመሳሰሉትን የሚከለክለው አንቀፅ ያለው የወንጀል ህጉ ላይ ነው እንጂ የመገናኛ ብዙሃን አዋጁ ላይ አይደለም ብለዋል፡፡ የመንግስትን ስም ማጥፋትና በሃሰት መወንጀል የሚለውም በወንጀል ህጉ ላይ እንጂ በመገናኛ ብዙሃን አዋጁ ላይ እንደሌለ፤ የህግ ባለሙያው ያስረዳሉ፡፡
በጥቅሉ የመገናኛ ብዙሃን አዋጁ በራሱ በተቋሙ የሚጣሱ ደንቦችንና መመሪያዎችን የሚመለከት ነው ያሉት ባለሙያው፤ የተመስገን በወንጀል ህጉ መከሰሱ ብዙም አጠያያቂ አይሆንም ብለዋል፡፡
ተመሳሳይ ክሶችን ከሚያደራጁ አቃቢያን ህግ መካከል ስሜ አይጠቀስ ያሉ አንድ አቃቤ ህግ  በሰጡት አስተያየት፤ የተመስገን ጉዳይ እያከራከረ መሆኑን እንደተገነዘቡ ጠቅሰው የመገናኛ ብዙሃን ህጉ የወንጀል ህጎቹን አንቀፅ ያልሻራቸው በመሆኑ፣ በዚሁ አግባብ ክሱ እንደተደራጀና አቃቤ ህግን በወንጀል ከመክሰስ የሚያግደው የህግ ድንጋጌ እንደሌለ ገልጸዋል፡፡
የፕሬስ አዋጅ፣ የፀረ-ሽብር አዋጅ፣ የወንጀለኛ መቅጫ ህግ እና በህገ መንግስቱ አንቀፅ 29 ሃሳብን በነፃነት ስለመግለፅ የተደነገጉት አንቀፆች ዛሬም የህግ ባለሙያዎችን ሳይቀር ማከራከራቸውን ቀጥለዋል፡፡ 

በስድስት ወራት ከ40ሺ በላይ ኢትዮጵያውያን የመን ገብተዋል
አማፂዎች በጥቂት ወራት ዘመቻ ሰንዓን እና ኤደንን ወርረዋል


               የመን “ታሪከኛ” አገር ናት - በአንድ በኩል ለረዥም ዘመናት የዘለቀ የጥንታዊ ስልጣኔ ባለቤት፣... በሌላ በኩል ደግሞ፣ ለበርካታ አመታት አለምን “ግራ ያጋባች ጉደኛ” አገር! እስቲ አስቡት። ከሰሜን አቅጣጫ የጦርነት ዘመቻ ሲያካሂዱ የከረሙ አማፂዎች፣ የመንግስት መቀመጫ የሆነችውን ዋና ከተማ ተቆጣጥረዋል። መንግስት ደግሞ፤ “የአማፂው ቡድን ታጣቂዎች ከተማዋን ለቀው እንዲወጡና የወረሯቸውን ወታደራዊ ካምፖችንና የሚኒስቴር መስሪያ ቤቶችን ይልቀቁልኝ” እያለ አቤቱታ ያሰማል። ሚኒስትሮች ወደ ቢሮአቸው ሲገቡ በአማፂ ታጣቂዎች ይፈተሻሉ። አይገርምም?
“መንግስት አለ ወይም የለም፤ አማፂዎች አሸንፈዋል ወይም አላሸነፉም” ለማለት ያስቸግራል። እውነትም የመን፣ ግራ የምታጋባ አስገራሚ አገር ናት። ምናልባትም፣ “አገሬው ሰላም ነው ወይስ አይደለም”፤ “የሚሰደዱባት ወይም የሚሸሿት አገር ነች” ለማለት ቢቸገሩ ይሆናል ብዙ የኢትዮጵያ ወጣቶች ወደ የመን መጉረፋቸውን ያላቋረጡት። ለነገሩ፣ የኢትዮጵያ ወጣቶች ብቻ ሳይሆኑ የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ለባራክ ኦባማም ጭምር፤ የየመንን ጭራና ቀንድ ለመለየት ተስኗቸዋል። የኦባማ ነገር! የአገራቸውን ፖለቲካና ኢኮኖሚ ያመሰቃቀሉት ፕሬዚዳንት ኦባማ፤ በአለማቀፍ ጉዳዮች ደግሞ የአሜሪካ ማፈሪያ ሊሆኑ ምንም አልቀራቸውም ማለት ይቻላል። እንደሳቸው ሃሳብማ፤ አሜሪካ ሁሉንም አገራት እንደእኩያ ብትቆጥርና መሪ ለመሆን ባትሞክር፣ ምድራችን ከዳር እስከ ዳር ሰላምና ደስታ ይሰፍንባት ነበር።

አሜሪካ የሁሉም ጥፋት ተጠያቂ ሳትመስላቸው አትቀርም።
ነገር ግን፣ የኮንጎ የእርስ በርስ ጦርነት ላይ፣ አሜሪካ ጣልቃ ስላልገባች ሰላም አልሰፈነም። ከስድስት በላይ አገራት ጎራ ለይተው በማዝመት ጦርነቱ ተባብሶ 5 ሚሊዮን ያህል ሰዎች ለእልቂት የተዳርገዋል። ሙዓመር ጋዳፊ ከስልጣን ከተወገዱ በኋላ፣ በሊቢያ ግጭት ላይ አሜሪካ እጇን እንዳታስገባ ኦባማ ትዕዛዝ ከሰጡ በኋላስ ሰላም ሰፈነ? እንዲያውም ባሰበት። በርካታ አክራሪ ድርጅቶች፣ ከደርዘን በላይ የጎሳ ታጣቂ ቡድኖች፣ ወታደራዊ አምባገነንነት ለመመስረት የሚመኙ ብሔረተኞች የሚጫረሱባት አገር ሆናለች። በምርጫ የተዋቀረው ፓርላማ ከዋና ከተማዋ ተባርሮ፣ መኖሪያውና መሰብሰቢያውን፣ የኪራይ መርከብ ላይ አድርጎ ከርሟል - የግብፅ እና የአረብ ኤሜሬትስ በአየር ሃይል ድብደባ ጭምር ወታደራዊ ድጋፍ ቢሰጡትም፣ ፓርላማው አንዲት ደህና ከተማ ለመያዝ እንኳ አልቻለም።

ዘጋርዲያን እንደዘገበው ሱዳንና ኳታር ደግሞ በሌላ ጎራ አክራሪ ቡድኖችን በማስታጠቅ ጦርነቱን ያቀጣጥላሉ።
አሜሪካ ጣልቃ አትገባም ማለት፤ ሌሎች በርካታ አምባገነን መንግስታት ጣልቃ ይገባሉ እንደማለት ሆኗል። ኦባማ ግን፤ በየቦታው ግጭት እየተቀሰቀሰ፣ ከአገር አገር ሲስፋፋ፤ ከሩቁ ሆነው “ተስማሙ፤ ዋናው ነገር መቻቻል ነው” በማለት ሰላም የሚያሰፍኑ ይመስላቸዋል። የእስራኤልና የፍልስጥኤም፣ የሊቢያና የሶሪያ ወይም የኢራቅና የሴንትራል አፍሪካ ጥያቄ ሲቀርብላቸው፤ የዘወትር ምላሻቸው... “ሁሉም ቡድኖች ተቻችለውና ስልጣን መጋራት ነው መፍትሄው” የሚል ስብከት ነው። ለመሆኑ፤ እነዚያ የአሜሪካ ስኬት ጠንካራ መሰረት ለመሆን የበቁ፣ “የግለሰብ ነፃነት፣ የነፃ ገበያና የህግ የበላይነት መርሆች” የት ገቡ? ያለ መርህ በዘፈቀደ መቻቻልኮ አይቻልም። እስቲ አስቡት። የየራሳቸውን ንብረት ይዘው የመጡ ገበያተኞች፤ የንብረት ባለቤትነታቸውን የሚያከብሩ ከሆነ ነው፣ ለግብይት መደራደር የሚችሉት - “ቀንስ፤ ጨምር” በማለት ተቻችለው ምርት የሚለዋወጡት። የንብረት ባለቤትነትን የማያከብርና ለመዝረፍ የሚፈልግ ሰው ሲመጣባቸውስ? አሁንም “ተቻችለው” ይደራደራሉ? “ሩብ ያህል ብቻ ዝረፍ” “አይ፤ ሙሉውን እዘርፋለሁ”፤ “ግማሽ ዘርፌ፣ ግማሽ ልተውልህ” በሚል የጋራ መፍትሄ ይፍጠሩ? በትክክለኛ መርህ ላይ ያልተመሰረተ ድርድርና መቻቻል፤ የሚያዛልቅ መፍትሄ አያስገኝም፤ መቋጫ የሌለው ግጭትን እንጂ። በአጭሩ፤ የባራክ ኦባማ ቀሽም አስተሳሰብ፣ ከአለም እውነታ ጋር ተጋጭቶ ለመፍረክረክ ጊዜ አልፈጀበትም ማለት ይቻላል። ታዲያ፤ ሰሞኑን በተካሄደ ምርጫ የባራክ ኦባማ ፓርቲ፣ በሰፊ ልዩነት በሪፐብሊካን ፓርቲ መሸነፉ ይገርማል?
እንዲያም ሆኖ፤ ባራክ ኦባማ የተሳሳተ አስተሳሰባቸውን ከማስተካከል ይልቅ፤ “ስኬቶችንም አስመዝግቤያለሁ” በማለት መከራከርን ይመርጣሉ። ስኬት ብለው የሚጠቅሱት ማንን መሰላችሁ? የመንን! ከሊቢያና ከግብፅ ጀምሮ፣ ማሊና ሴንትራል አፍሪካን ጨምሮ፣ ኢራቅና ሶሪያ በግጭት ቢታመሱም፤ ኦባማ “የመን፣ ለሁሉም አርአያ ልትሆን የምትችል አገር ናት” በማለት አወጁ። በግንቦት ወር ማለት ነው።
እንዲያው ስታስቡት፣ የመን በአርአያነት የምትሞገስ አገር ናት? የመንግስትና የአክራሪዎች ፋታ በማይሰጥ የአፈና ዘመቻ አገሪቱን አጨልመዋል። ኢኮኖሚዋ በድጎማና በሙስና ተዳክሞ የወጣቶች ስራ አጥነት ተባብሷል። በሰሜን በኩል ኢራን የምትደግፋቸውና በጎሳ የተደራጁ የሺዓ አማፂዎች፤ በደቡብ በኩል በጎሳ የተደራጁ ተገንጣይ አማፂዎች፤ ከመሃል በሳውዲ አረቢያ እና በኳታር የሚደገፉ ተቀናቃኝ አክራሪ ድርጅቶች... ከእነዚህም በተጨማሪ በነውጠኛነቱ የገነነ አልቃይዳ ቅርንጫፍ... በየፊናቸው አገሪቱን ያተራምሳሉ። እህስ? ባለፈው ሚያዚያ ወር እንደታየው የአገሪቱ ጦር ሰራዊት በዘመቻ አንዲት ከተማ ያስለቅቃል፤ የአሜሪካ መንግስት ደግሞ በሰው አልባ የጦር አውሮፕን (ድሮን) አራት አምስት የአልቃይዳ አሸባሪዎችን ይገድላል። ይሄው ነው በኦባማ ያሞገሱትና በአርአያነት የሚጠቀስ የየመን ስኬት። በዚያው ግንቦት ወር፤ ወደ 7ሺ የሚጠጉ ኢትዮጵያውያን ወጣቶች፣ በእግር የሶማሊያና የጂቡቲ በረሃዎችን አቋርጠው፤ በተጨናነቁ ጀልባዎች ባህሩን ቀዝፈው የመን ገብተዋል። በሚያዚያ ወርም እንዲሁ 7ሺ ያህል የኢትዮጵያ ስደተኞች የመን ደርሰዋል - የሚሸሿት ሳትሆን የሚሰደዱባት ምርጥ አገር የሆነች ይመስል! በእርግጥ የብዙዎቹ ስደተኞች ተስፋ፣ በየመን በኩል ሳውዲ አረቢያ መግባት ነው።
በሰኔ ወር፣ በሰሜን የመን በኢራን የሚደገፉ የሺዓ እምነት አክራሪዎች፣ “ሁቲ” በሚል የጎሳ ስያሜ ተደራጅተው ፀረመንግስት አመፃቸውን አላቋረጡም። በደቡብም የተገንጣይ ድርጅት ታጣቂዎች አላረፉም። የአልቃይዳ አሸባሪዎች በየከተማውና በየመንገዱ  ቦምብ ከማፈንዳት አልቦዘኑም። በየገጡም ሆነ በየመንደሩ፣ ሰዎች መታገታቸውም የዘወትር ዜና መሆኑ አልቀረም። ነገር ግን፤ በዚያው ወር እንደገና 4500 ገደማ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ወደ የመን ፈልሰዋል።
ኦባማ፤ የየመንን አርአያነት ካበሰሩ በኋላ ሁለት ወር ሳይሞላቸው ነው፤ የአገሪቱ ትርምት የተባባሰው። በሰሜን በኩል የሚዋጉት የሁቲ ታጣቂዎች፣ ተከታታይ ዘመቻ በማካሄድ ሰፊ የአገሪቱን ግዛት የወረሩት በሐምሌ ወር ነው። የመንግስትን ጦር እንዲሁም ተቀናቃኝ የሱኒ አክራሪ ታጣቂዎችን እያሳደዱ፤ ከዋና ከተማዋ ከሰንዓ በ50 ኪ.ሜትር ርቀት ላይ የምትገኝ አርማን የተሰኘች ከተማን እስከመቆጣጠር ደርሰዋል። እንዲያም ሆኖ፣ በዚሁ በሐምሌ ወር፤ 5ሺ ገደማ ኢትዮጵያውያን ወጣቶች በስደት የመን ገብተዋል።
ከአራት አመት በፊት የመንግስት ጦር፣ በሳዑዲ አረቢያ የአየር ሃይል ድጋፍ አማፂዎቹን ለማንበርከክ ቢችልም፤ ሐምሌ ወር ላይ ያጣቸውን አካባቢዎች ለማስመለስ አልቻለም። በነሐሴም ብዙ ሞክሯል - አልተሳካለትም እንጂ። የሁቲ አማፂዎች ይባስኑ በሰንዓ ዙሪያ ከበባ እያጠበቁ የአገሪቱን መንግስት መላወሻ ማሳጣት ጀምረዋል። በየከተማውና በየመንገዱ የአልቃይዳ ፍንዳታዎች ሲጨመርበት አስቡት። በደቡብም፤ ተገንጣይ ታጣቂዎች ጉልበት እያገኙ፣ አገሪቱ እየተብረከረከች ነበር - በነሐሴ ወር። ቢሆንም፤ ከ8ሺ በላይ ኢትዮጵያውያን፤ በዚያው ወር የየመንን ድንበር አቋርጠው የስደት እንደተመዘጉ የዩኤን መረጃ ያሳያል።
የመን እንዲያ እየታመሰች በአርአያነት ስትጠቀስና ኢትዮጵያውያን ያለማቋረጥ ሲሰደዱባት ያየ ሰው፤ “ይህችስ ጉደኛ አገር ናት” ቢል ይገርማል? ካላመናችሁ፤ ባለፈው መስከረም ወር የተከሰተውን ታሪክ ተመልከቱ። በሺዓ እምነትና በጎሳ ተወላጅነት የተደራጁት አማፂዎች፣ ሰሜን የመንን በመውረር ለወር ያህል በሰንዓ ዙሪያ ከበባ ካካሄዱ በኋላ ነው፤ በመስከረም ሁለተኛው ሳምንት የከባድ መሳሪያ ድብደባ ማካሄድ የጀመሩት።
የድብደባው በሁለት ዋና ዋና ኢላማዎች ላይ ያነጣጠረ ነው - በአንድ የጦር ካምፕ እና በአንድ ዩኒቨርስቲ ላይ! በመገረም፣ “ዩኒቨርስቲ?” ብላችሁ ትጠይቁ ይሆናል። አዎ፤ ዩኒቨርስቲ! ግን፣ ሳይንስንና ቴክኖሎጂን የሚያስተምር አይደለም። እንደ ግብፁ ሙስሊም ብራዘርሁድ ጋር ዝምድና ባለው ፓርቲ የሚተዳደርና፣ በየመን “የሱኒ አክራሪነትን ለማስፋፋት” የሚያገለግል ዩኒቨርስቲ ነው።
ታዲያ፤ ሁቲዎች ዩኒቨርስቲውን የጠሉት፤ “አክራሪነት”ን ስለሚያስፋፋ አይደለም። የሺዓ ሳይሆን የሱኒ አክራሪ ስለሆነ እንጂ! ከአልቃይዳ ጋርም ፀባቸው ከዚህ የተለየ አይደለም። ባለፉት ሳምንታት፣ የሱኒ አክራሪ የሆነው አልቃይዳ አጥፍቶ ጠፊዎችን እያሰማራ ሲያፈነዳ የሰነበተው፣ በአሜሪካ ኤምባሲ ወይም በመንግስት ተቋማት ላይ ሳይሆን፤ በሁቲ የሺዓ ታጣቂዎች ላይ ነው። መስከረም መጨረሻ ላይ፣ የሺዓ ታጣቂዎች ላይ አልቃይዳ በፈፀመው የአጥፍቶ ጠፊ ፍንዳታ ከ60 ሰዎች በላይ ሞተዋል። የኢራንና የሳዑዲ አረብያ መንግስታት እርስበርስ እንደ ደመኛ ጠላት የሚተያዩትን ያህል፤ በየመንም የሺዓ እና የሱኒ አክራሪዎችም በጠላትነት ይጠፋፋሉ፤ ይገዳደላሉ። ለዚህም ነው፤ የሺዓ ታጣቂዎቹ የከባድ መሳሪያ ድብደባው በዩኒቨርስቲው ላይ ያነጣጠረው።
ሁለተኛው ኢላማ፤ በአገሪቱ “ወደርለሽ ነው” በሚባልለት ‘1ኛው ሜካናይዝድ ክፍለጦር ካምፕ” ላይ ያነጣጠረውስ ለምን ይሆን? ለምን ቢባል፤ በጄነራል አሊ አልአህማር የሚመራው ይሄው ክፍለጦር ነው፤ ለበርካታ አመታት በአማፂዎቹ ላይ ተከታታይ ዘመቻ ያካሄደው። የሁቲ አማፂዎች፣ ከምፑንና ዩኒቨርስቲውን ከደበደቡ በኋላ፤ ወደ ከተማዋ ለመግባት ጊዜ አልፈጀባቸውም። ሊመክታቸው የሚሞክር ተዋጊም አላጋጠማቸውም። የተኩሱ መዓት አይጣል ቢሆንም፤ ለውጊያ ሳይሆን እንደ ርችት ድል ለማብሰር ነው የተጠቀሙበት። የመንግስት ጦር ስንቁንና ትጥቁን ሁሉ ለአማፂዎቹ ትቶ ሲበተን፤ የከተማዋ ፖሊስ በየቤቱ ተከቷል። ሰንዓ በአማፂዎቹ ቁጥጥር ስር ዋለች።አስገራሚው ነገር፤ አማፂዎቹ የመንግስት መቀመጫ የሆነችውን ከተማ ቢቆጣጠሩም፤ የቀድሞው መንግስት አልፈረሰም። አሁንም አለ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከፕሬዚዳንት መንሱር ሃዲ ጋር ተጣልተው ስልጣናቸውን ከመልቀቃቸው በቀር፤ የወትሮው የመንግስት መዋቅር አልተለወጠም፤ የመንግስት ባለስልጣናት አልታሰሩም፤ ከስልጣንም አልተሻሩም። አማፂዎቹ ጥርሳቸውን የነከሱት፣ በሱኒ አክራሪ ቡድኖችና በአንድ ባለስልጣን ላይ ብቻ ነው - በሜካናይዝድ ክፍለጦር አዛዥ ጄነራል አልአህማር ላይ! በአማፂዎቹ የሚታደኑት ጄነራል፤ ካለፈው ወር ወዲህ የት እንደገቡ አይታወቅም። የአማፂዎቹ ንዴት ግን የበረደ አይመስልም። ሰንዓ የሚገኘው የክፍለጦሩ ካምፕ ፈርሶ መናፈሻ ይሆናል ብለዋል አማጺዎቹ። የአገሪቱ ፕሬዚዳንትና ሌሎች ባለስልጣናት ግን፤ (በርካታዎቹ ባለስልጣናት ወደ ቢሮ ሲገቡ ለጥበቃ በተሰማሩ አማፂዎች የሚፈተሹ ቢሆኑም) ይሄውና አሁንም ስልጣናቸውን እንደያዙ ነው - ከአማፂዎቹ ጋር የሰላም ስምምነት ስለተፈራረሙ።
ነገር ግን፤ መንግስት አለ ለማለትም ያስቸግራል። የዛሬ ወር ገደማ ፕሬዚዳንቱ አዲስ ጠቅላይ ሚኒስትር የሾሙ ጊዜ ምን እንደተፈጠረ ይታወቃል። የጠቅላይ ሚኒስትሩ የስልጣን ዘመን ለአንድ ቀን አልዘለቀም፤ በጥቂት ሰዓታት ውስጥ ነው የተሻሩት - አማፂዎቹ አልወደዷቸውማ። የመን ነገር ግራ አያጋባም? “መንግስት አለ ወይም የለም” ብሎ ለመናገር አስቸጋሪ የሆነባት አገር!
ተስፋ ያልቆረጡት ፕሬዚዳንት፤ ለአማፃ ቡድኑን ታጣቂዎች አቤቱታና ጥሪ ከማቅረብ ወደኋላ አላሉም። “እባካችሁ፤ በስምምነታችን መሰረት ዋና ከተማዋን ለቅቃችሁ ውጡልን፤ የመንግስት መስሪያቤቶችንና የጦር ካምፖችን አስረክቡን፤ የወሰዳችኋቸው ታንኮችንና የጦር መሳሪያዎችን መልሱልን” በማለት አቤቱታ ሲያቀርቡ፣ ወር አለፋቸው። የአማፂዎቹ ዘመቻ በአገሪቱ ሰሜናዊ ክፍልና በሰንዓ ከተማ ላይ ብቻ ተገድቦ አልቆመም። በቅርቡ ወደ ደበቡ አቅጣጫ በመግፋት፤ የወደብ ከተማ ኤደንን ተቆጣጥረዋል። ከመስከረም ወዲህ የመን እንዲህ ነች - ጭራና ቀንዷ የማይታወቅ የትርምስ አገር!
እንዲያም ሆኖ፤ በመስከረም ወር 9500 ገደማ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ወደ የመን ገብተዋል። በአጠቃላይ ባለፉት ስድስት ወራት ከ40ሺ የሚበልጡ ኢትዮጵያውያን ወደ የመን ተሰደዋል። ለምን? የየመን ትርምስ በግልፅ ስላላወቁ ሊሆን ይችላል። ቢያውቁ እንኳ ብዙ አያሳስባቸው ይሆናል - ወደ ሳዑዲ አረቢያ ለመሻገር እንጂ የመን ውስጥ ለመቆየት ስለማያስቡ። በዚያ ላይ፣ በህጋዊ ምዝገባ ወደ ሳዑዲ አረቢያና ወደ ሌሎች የአረብ አገራት ለመጓዝ የሚያስችል አሰራር ካለፈው አመት ጀምሮ በመንግስት “ጊዜያዊ እገዳ” ስለተዘጋ፤ አማራጭ በማጣትም ሊሆን ይችላል።

በ6 ወር ወደ የመን የተሰደዱ ኢትዮጵያውያን
ሚያዚያ 2006    6,865
ግንቦት 2006    6,820
ሰኔ 2006    4,468
ሐምሌ 2006    4,917
ነሐሴ 2006    8,150
መስከረም 2007    9,443
በስድስት ወር    40,663


አንዳንድ ታሪክ ጊዜው እጅግ ሲርቅ ተረት ይሆናል፡፡
በጥንት ዘመን አንድ ሮማዊ ጀግና ወታደር ነበር ይባላል፡፡ አያሌ ጦርነቶችን በአሸናፊነት ተወጥቷል፡፡ አብዛኛውን ህይወቱን በጦር ሜዳ ስላሳለፈ በአካል የሚያውቀው ሰው የለም፡፡ ዝናው ግን በሰፊው ይወራል፡፡
አንድ ጊዜ ታዲያ አጠቃላይ ምርጫ በሀገሪቱ ሲካሄድ ያ ጀግና ፖለቲካ ውስጥ መግባት አለብኝ ብሎ ወሰነ፡፡ ስለዚህም በምርጫው ለከፍተኛው የፓርላማ ቦታ ይወዳደር ጀመር፡፡ በዚያን ጊዜው የሮማውያን የምርጫ ባህል ጥሩ ዲስኩር (ንግግር) ማድረግ ግድ ነበር፡፡ ጀግናው ንግግሩን የጀመረው ለዓመታት ለሮማ ሲዋጋ በጥይት ብዙ ቦታ ቆስሎ ነበርና ገላው ላይ ጠባሳዎቹን በማሳየት ነበር፡፡ ህዝቡ ከንግግሩ ይልቅ ጠባሳዎቹን እያየ ዕንባ በዕንባ ተራጨ፡፡ የዚያ ጀግና በምርጫው አሸናፊነት ከሞላ ጐደል የተረጋገጠ መሰለ፡፡
ታዲያ የዋናው ምርጫ ቀን ያ ጀግና በመላው የፓርላማ አባላትና በመሳፍንቱና በመኳንንቱ ታጅቦ ወደ መድረኩ ብቅ አለ፡፡ ህዝቡ ግራ ተጋባ፡፡ “በእንዲህ ያለ የምርጫ ቀን ይሄ ሁሉ ጉራ ለምን አስፈለገ?” ይባባል ጀመር፡፡   ያ ጀግና ንግግር ሲያደርግ አጃቢዎችንና ሀብታሞችን የሚያወድስ፣ በትዕቢትና በጉራ የተሞላ፣ የጦር ሜዳ ድሎቹን እያሳቀለ ከኔ ወዲያ ጀግና ላሳር ነው ይል ጀመር፡፡ ተፎካካሪዎቹንም አንተና አንቺ እያለ ያዋርድ ገባ፡፡ ቀልድ አወራሁ ብሎ የሚናገራቸው ወጐች ራሳቸው የሰው ሞራል የሚነኩና ህዝቡን የሚያበሳጩ ሆኑ፡፡ “ለሮማም እስከዛሬ ታይቶ የማይታወቅ ልማትና ሀብት አመጣላታለሁ!” እያለ በከፍተኛ መወጣጠር መድረኩ ላይ ተንጐራደደ፡፡
ህዝቡም “ያ እንደዚያ ዝናው የተወራ የጦር ሜዳ ጀግና እንዲህ ያለ ቱሪናፋ ነው እንዴ?” አለ፡፡ ወሬው በአገሪቱ ሙሉ ወዲያው ተሰማ፡፡ “ይሄንንማ ፈፅሞ አንመርጥም፡፡ እንዳይመረጥም ላልሰማው ህዝብ መናገር አለብን”፤ አለ ህዝቡ፡፡ ጀግናው ድምፅ አጣ! ሳይመረጥ ቀረ፡፡ ወደ ጦር ሜዳው ተመለሰ፡፡ “ያልመረጠኝን ህዝብ አሳየዋለሁ፡፡ እበቀለዋለሁ!” ይል ጀመር፡፡
ከጥቂት ሳምንታት በኋላ ወደ ሮማ የእርዳታ እህል በመርከብ መጣ፡፡ ምክር ቤቱ በነፃ ይታደል አለ፡፡ ያ ጀግና “ይሄ እህል በነፃ መታደል የለበትም፡፡ እምቢ ካላችሁ ጦር ሜዳውን ትቼላችሁ እመለሳለሁ” እያለ ያስፈራራ ጀመር፡፡ ይሄን ወሬ ምክር ቤቱ ለህዝቡ ነገረ፡፡ ህዝቡ ተቆጣ፡፡ “ያ ጀግና እፊታችን ቀርቦ ያስረዳ” አለ፡፡ ጀግናው ደግሞ “ህዝብ ብሎ ነገር አላቅም፡፡ ዲሞክራሲም አልቀበልም፡፡ አልመጣም” አለ፡፡ ህዝብ አደባባይ ወጥቶ ጮኸ፡፡ ምክር ቤቱ ያን ጀግና የግዱን እንዲመጣ አደረገውና ሸንጐ መድረክ ላይ ቆሞ እንዲናገር ታዘዘ፡፡ ጀግናውም አሁንም በእልህና በትእቢት ሁሉንም መሳደቡን ቀጠለ፡፡ ህዝቡ በሆታ አስቆመው፡፡ ለፍርድ ይቅረብልን አለ፡፡ ምክር ቤቱ ምንም ምርጫ አልነበረውም፡፡ ለፍርድ አቀረበው፡፡ በዚያን ዘመን ወንጀለኛ ቀጣበት በነበረው፤ ከከፍተኛ ተራራ ወደ መሬት ይወርወር፤ የሚል ሀሳብ ቀረበ፡፡ ሆኖም አስተያየት ተደርጐ ቅጣቱ እድሜ ልክ ይሁንለት ተባለና ዘብጥያ ተወረወረ! ህዝቡ በሆታና በዕልልታ መንገዱን ሞላው፡፡
                                                           ***
ሰዎችን በንግግር እንማርካለን ብለን ብዙ በለፈለፍን ቁጥር ብዙ ከቁጥጥራችን የሚወጡ ነገሮች ይከሰታሉ፡፡ ጠንካራና ልባም ሰዎች ጥቂት ምርጥ ነገሮችን ብቻ በመናገር የሰውን ልብ ይነካሉ፡፡ ስለዚህ ከአንደበታችን በመቆጠብ፣ ትሁት በመሆን፣ ህዝብን ባለመናቅ፣ ለምንናገረው ነገር የቤት-ሥራችንን ጠንቅቀን በመስራትና ጉዳያችንን በማወቅ ነው ለውጥ ለማምጣት የምንችለው፡፡
ከሁሉም በላይ ተአብዮ አገርንና ህዝብን ይጐዳል፡፡ ከማንም በላይ ነኝ እና አምባገነንነት የተአብዮ (የእብሪት) ልጆች ናቸው፡፡ ንቀት፣ ሰው-ጤፉነት፣ ሁሉን አውቃለሁ ባይነት፣ ቆይ-አሳይሃለሁ - ባይነት፤ ብቆጣም እመታሻለሁ ብትቆጪም እመታሻለሁ ማለት፤ የማታ ማታ ከላይ የተጠቀሰውን የጦር-ሜዳ ጀግና ዕጣ-ፈንታ የሚያሰጠን መሆኑ አሌ አይባልም፡፡ ከበደ ሚካኤል፤
“ኩራትና ትእቢት፣ የሞሉት አናት
ሰይፍና ጐራዴ፣ የመቱት አንገት
አይገላገሉም እንዲህ በቀላሉ
እመሬት ላይ ወድቀው ሳይንከባለሉ”
የሚሉን ለዚህ ነው፡፡
ከልክ ያለፈ ውዳሴና ማሞካሸትም ከጥቅሙ ጉዳቱ ነው የሚያመዝነው፡፡ ተወዳሹ እስኪታዘበን ድረስ ብናሳቅለው ለማንም የማይበጅ ንግግር እንዳቀረብን ነው የሚቆጠረው፡፡
ፀጋዬ ገብረመድህን፤
“ጅላጅል ምላስ ብቻ ናት
ማሞካሸት የማይደክማት”
የሚለን ለዚህ ነው፡፡
እናስተውል፡፡ ብዙ እዩኝ እዩኝ ደብቁኝ ደብቁኝን እንደሚያስከትል አንርሳ፡፡ ብዙ በተናገርን ቁጥር አልባሌና ዝቅ የሚያደርጉንን ጥፋቶች ለመስራት በር እንከፍታለን፡፡ ታዋቂው ሳይንቲስትና የጥበብ ሰው ሊዮናርዶ ዳቬንቺ፤
“ኦይስተሮች (Oysters) ጨረቃ ሙሉ በሆነች ሰዓት አፋቸውን ሙሉ በሙሉ ይከፍታሉ፡፡ ይሄኔ ክራቦች (Crabs) የባህር አረምን ኦይስተሮቹ አፍ ውስጥ ይሰገሰጋሉ፡፡ አፋቸው መንቀሳቀስ ያቅተዋል፡፡ ከዚያ የክራቦቹ ምግብ ይሆናሉ፡፡ አፉን ያለልክ የሚከፍት የማንም ሰው ዕጣ-ፈንታ ይሄው ነው፡፡ የአድማጩ ሰለባ ይሆናል” ይለናል፡፡
ባልባለቀ አእምሮና ባልበሰለ አንደበት ስንቶችን ልናስቀይም እንደምንችል እናጢን፡፡ “እዛም ቤት እሳት አለ” የሚለውን ተረት ከልቦናችን አንለይ፡፡ ከቶውንም እኔ አውቃለሁን ስንፈክር ሌላውም ያውቃልን አንርሳ፡፡ ባደባንበት ሊደባብን እንደሚችል፣ ደባ ራሱን ስለት ድጉሱን መሆኑን፣ ሥራ ለሰሪው እሾክ ላጣሪው እንደሚሆን አንዘንጋ፡፡ የወላይታው ተረት - “የኛ ቤት ጠማማነት እኛን ይጨርሳል፤ አለ እንጨት” የሚለን ይሄንኑ ነው!










Published in ርዕሰ አንቀፅ
  •    የ7.3 ቢሊዮን ዩሮ ተጨዋቾች፤ ከ2.09 ቢሊዮን ዩሮ በላይ ወጭ ፤ እስከ 57.4 ሚሊዮን ዩሮ ሽልማት
  • 5 ክለቦች ታጭተዋል ፤ ሪያል ማድሪድ፣ ባየር ሙኒክ፣ ባርሴሎና፣ ቼልሲና ማን. ሲቲ
  • ፕሪሚዬር ሊግ ፤ ከቦንደስ ሊጋና ላሊጋ ይተናነቃል         
  • የ2014-15 የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ሰሞኑን በአራተኛ ዙር የምድብ ማጣሪያ ጨዋታዎች ቀጥሏል፡፡ በምድብ ማጣሪያው ቀሪ የሁለት ዙር ጨዋታዎች ቢኖሩም 5 ክለቦች ሪያል ማድሪድ፤ ቦርስያ ዶርቱመንድ፤ ፒኤስጂ፤ ባርሴሎና እና ፖርቶ ወደ ጥሎ ማለፍ መሸጋገራቸውን አረጋግጠዋል፡፡

አትሌቲኮ ማድሪድ፤ አያክስን ጨምሮ አምስት ክለቦች ከውድድሩ ተሰናብተዋል፡፡ የአውሮፓ እግር ኳስ በየውድድር ዘመኑ እስከ 30 ቢሊዮን ይንቀሳቀስበታል፡፡ በተለይ ደግሞ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ በትርፋማነቱ የሚስተካከለው የለም፡፡ በትራንስፈርማርኬት ድረገፅ የቀረበ መረጃ እንደሚያመለክተው የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ፤ በየውድድር ዘመኑ ከቅድመ ማጣሪያ አንስቶ እስከ ዋንጫ ጨዋታ እንዲሁም የውስጥ የሊግ ውድድሮችን ጨምሮ 853 ተጨዋቾችን የያዙ 155 ክለቦችን በማሳተፍ ይካሄዳል፡፡ በዝውውር ገበያው የዋጋ ግምታቸው እስከ 7.3 ቢሊዮን ዩሮ የሚተመኑ ተጨዋቾች በየክለቡ ተሰልፈው የሚፋለሙበት መድረክ ነው፡፡ ለዘንድሮው ሻምፒዮንስ ሊግ በአምስቱ የአውሮፓ ሊጎች የሚወዳደሩት ክለቦች ከፍተኛ ትኩረት መስጠታቸው የተረጋገጠው በተጨዋቾች የዝውውር ገበያው 2.09 ቢሊዮን ዩሮ በላይ ወጭ ማድረጋቸው ነው፡፡ ከተጠቀሰው የዝውውር ገበያ ወጭ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ 45 በመቶ ድርሻ ይዟል፡፡

25 በመቶውን የስፔን 10 በመቶውን የጀርመን ክለቦች አውጥተዋል፡፡ የጣሊያን እና የፈረንሳይ ሊጎች ዝቅተኛውን የወጭ ድርሻ አስመዝግበዋል፡፡ የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር በ2014 /15 የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግና ዩሮፓ ሊግ ውድድሮች ለሽልማትና ሌሎች ገቢዎች ድርሻ 1.34 ቢሊዮን ዩሮ መቅረቡን አስታውቋል፡፡ ካለፈው የውድድር ዘመን በ30 በመቶ ጭማሪ አለው፡፡ የእግር ኳስ ማህበሩ እንዳመለከተው ሌሎች የገቢ ድርሻዎችን ሳይጨምር 60ኛዋን ዋንጫ ለማንሳት የሚበቃው ክለብ እስከ 57.4 ሚሊዮን ዩሮ የሽልማት ገንዘብ ይከፈለዋል፡፡ በምድብ ማጣርያው ላይ የሚገኙት 32 ክለቦች ደግሞ ቢያንስ 8.6 ሚሊዮን ዩሮ የገቢ ድርሻ አላቸው፡፡ በእያንዳንዱ የምድብ ጨዋታ በሚመዘገብ ውጤት መሰረትም የሽልማት ገንዘብ ይከፈላል፡፡ ለድል 1 ሚሊዮን ዩሮ እና ለአቻ ውጤቶች ደግሞ 500ሺ ዩሮ ይታሰባል፡፡ የምድብ ማጣርያውን አልፈው ጥሎ ማለፍ የሚገቡ 16 ክለቦች 3.5 ሚሊዮን ዩሮ ገቢ ሲኖራቸው፤ የሩብ ፍፃሜ 8 ክለቦች እያንዳንዳቸው 3.9 ሚሊዮን ዩሮ፤ የግማሽ ፍፃሜ አራት ክለቦች እያንዳንዳቸው 4.9 ሚሊዮን ዩሮ ፤ በዋንጫ ጨዋታ ተሰልፎ ሁለተኛ ደረጃ የሚያገኘው ክለብ 6.5 ሚሊዮን ዩሮ እንዲሁም ዋንጫውን የሚያሸንፈው ክለብ 10.5 ሚሊዮን ዩሮ ከሽልማት ገንዘብ ብቻ ይከፈላቸዋል፡፡ ባለፈው የውድድር ዘመን በሻምፒዮንስ ሊግ ተሳታፊ ለነበሩ 32 ክለቦች የተከፋፈለውገቢ 904.6 ሚሊዮን ዩሮ ነበር፡፡ 57.4 ሚሊዮን ዩሮ በማግኘት 10ኛውን የሻምፒዮንስ ሊግ ያስመዘገበው ሪያል ማድሪድ መርቷል፡፡ በሩብ ፍፃሜ የተሰናበተው ፓሪስ ሴንትዥርመን በ54.4፤ ሁለተኛ ደረጃ አግኝቶ የጨረሰው አትሌቲኮ ማድሪድ በ50፤ ዘንድሮ የማይሳተፈው እና አምና በሩብ ፍፃሜ የተሰናበተው ማንችስትር ዩናይትድ በ44.8፤ ለግማሽ ፍፃሜ የደረሱት ባየር ሙኒክ በ44.6 እንዲሁም ቼልሲ በ43.4 ሚሊዮን ዩሮ የገቢ ድርሻ ተከታታይ ደረጃ ነበራቸው፡፡ ፕሪሚዬር ሊግ በጥሎ ማለፍ ከቦንደስ ሊጋና ላሊጋ ጋር ይተናነቃል በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ወደ ጥሎ ማለፉ የሚሸጋገሩበት ክለቦች ዘንድሮም ከ5ቱ ታላላቅ ሊጐች መገኘታቸው የማይቀር ይመስላል፡፡

17 ክለቦች በየሊጋቸው ያለፈው የውድድር ዘመን ሻምፒዮን ሆነው የሚሳተፉበት ውድድር ቢሆንም ማለት ነው፡፡ በአውሮፓ እግር ኳስ በገቢው ከፍተኛነት የሚታወቀው የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ፤ በተረጋጋአስተዳደርና አትራፊነቱ እንደተምሳሌት የሚቆጠረው የጀርመን ቦንደስ ሊጋ እንዲሁም በተወዳጅነት እና በክዋክብት ስብስቡ የደመቀው የስፔን ላሊጋ ለሻምፒዮንስ ሊግ ዋንጫ ቋሚ ተፎካካሪ ሊጎች ከሆኑ ከሁለት አስርት ዓመታት በላይ ተቆጥረዋል፡፡ በተለይ ከሻምፒዮንስ ሊጉ የዋንጫ ፉክክር ከራቁ ሶስት የውድድር ዘመናት ያለፋቸው የእንግሊዝ ክለቦች ጥሎ ማለፍ ብቻ ሳይሆን ግማሽ ፍፃሜ መድረሳቸው እየተጠበቀ ነው፡፡ ቼልሲ፤ ማንችስተር ሲቲ ፤ ሊቨርፑልና አርሰናል እንግ ለዋንጫ እንደሚያበቁ በየአቅጣጫው ሰፊ ትንታኔዎችን ተሰጥተዋል፡፡ ይሁንና ባለፉት ስምንት የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ግማሽ ፍፃሜ ተፋላሚዎች ሰባቱ የስፔንና የጀርመን ክለቦች መሆናቸው ከባድ ክፍተት ነው፡፡ ባለፈው የውድድር ዘመን የሻምፒዮንስ ሊግ የፍፃሜ ተፋላሚዎች ሁለቱም ከስፔን ነበሩ ፡፡ ባለፉት አራት የውድድር ዘመናት ደግሞ በግማሽ ፍፃሜ ሁለት የላሊጋው ክለቦች ቋሚ ተሰላፊዎች ሆነው አሳልፈዋል፡፡ በ2011 ባርሴሎና እንዲሁም በ2014 ሪያል ማድሪድ ዋንጫን መውሰዳቸውም የስፔኑ ላሊጋ ከቦንደስ ሊጋው በላቀ ግምት እንዲታይ ያደርገዋል፡፡ በሌላ በኩል የጀርመኑን ቦንደስ ሊጋ የሚወክለው ባየር ሙኒክ ባለፉት አራት የውድድር ዘመናት ለ3 ጊዜ ፍፃሜ መድረሱ እና በ2013 ዋንጫውን መውሰዱና ከፍተኛ ግምት አሰጥቶታል፡፡ ዘንድሮ ፍፃሜው በበርሊን ከተማ መዘጋጀቱ ደግሞ የአሸናፊነት ግምቱን ለጀርመኑ ክለብ ያበዛለታል፡፡ በአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር የስታትስቲክስ ሰነድ የአምስቱ ታላላቅ ሊጎች በሻምፒዮንስ ሊግ መድረክ ስላላቸው የውጤት የበላይነት በርካታ ማስረጃዎች አሉ፡፡

ከ1993 እስከ 2014 እኤአ በሻምፒዮንስ ሊጉ 27 የዋንጫ ጨዋታዎች ተካሂደው ዋንጫዎቹን 13 ክለቦች ሰብስበዋል፡፡ 7 ጊዜ የስፔን፤ 5 ጊዜ የጣሊያን፤ አራት ጊዜ የእንግሊዝ፤ 3 ጊዜ የጀርመን እንዲሁም አንዳንድ ጊዜ የፈረንሳይ፤ የሆላንድ እና የፖርቱጋል ክለቦች ዋንጫዎቹን ወስደዋል፡፡ አራቱን ዋንጫ በመውሰድ ከፍተኛ ውጤት ያስመዘገበው የስፔኑ ክለብ ሪያል ማድሪድ ነው፡፡ እያንዳንዳቸው እኩል ሶስት ጊዜ የሻምፒዮናነት ክብር ያገኙት ደግሞ የጣሊያኑ ኤሲ ሚላን እና የስፔኑ ባርሴሎና ናቸው፡፡ እኩል ሁለት ጊዜ ዋንጫውን በማንሳት የእንግሊዙ ክለብ ማንችስተር ዩናይትድ እና የጀርመኑ ባየር ሙኒክ ሲጠቀሱ፤ እያንዳንዳቸው አንድ ጊዜ ዋንጫ በማግኘት የተሳካላቸው ክለቦች የፈረንሳዩ ኦሎምፒክ ማርሴይ፤ የሆላንዱ አያክስ፤ የጣሊያኑ ጁቬንትስ፤ የጀርመኑ ቦርስያ ዶርትመንድ፤ የፖርቱጋሉ ኤፍሲ ፖርቶ፤ የእንግሊዙ ሊቨርፑል፤ የጣሊያኑ ኢንተርሚላንና የእንግሊዙ ቼልሲ ናቸው፡፡ ባለፉት 27 የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የውድድር ዘመናት ስፔን 22 ጊዜ በግማሽ ፍፃሜ በመወከል ትቀድማለች፡፡ 19 ጊዜ እንግሊዝ፤ 13 ጊዜ ጣሊያን፤ 12 ጊዜ ጀርመን እንዲሁም 6 ጊዜ ፈረንሳይ በክለቦቻቸው የግማሽ ፍፃሜ ውክልናን አግኝተዋል፡፡ ስፔን በ4 ክለቦች ለ11 ጊዜያት ለዋንጫ ጨዋታ በመቅረብ አሁንም ግንባር ቀደም ነች፡፡ ጣሊያን በ3 ክለቦች ለ11 ፤ እንግሊዝ በ4 ክለቦች ለ9፤ ጀርመን በሶስት ክለቦች ለ8 እንዲሁም ፈረንሳይ በ2 ክለቦች ለ2 ጊዜያት ለዋንጫ ተጫውተዋል፡፡ በሌላ በኩል ከ1955 እሰከ 2014 እኤአ በተደረጉት 59 የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ዋንጫ የውድድር ዘመኖች 14 ጊዜ የሻምዮናነት ክብሩን በመውሰድ የስፔን ክለቦች ይመራሉ፡፡

በክለቦቻቸው እያንዳንዳቸው 12 ዋንጫዎች ወሰዱት የእንግሊዝ እና ጣሊያን ናቸው፡፡ ሌሎች የሻምፒዮንስ ሊግ ዋንጫዎች 7 በጀርመን ፤ 6 በሆላንድ፤ 4 በፖርቱጋልክለቦች የተወሰዱ ሲሆን፤ እያንዳንዳቸው አንድ ጊዜ በክለቦቻቸው የአውሮፓን ክብር ያገኙ አራት አገራት ፈረንሳይ፤ሮማንያ፤ ስኮትላንድ እና ሰርቢያ ናቸው፡ 5ቱ የዋንጫ ተፎካካሪዎች የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ገና በምድብ ማጣርያ 4ኛ ዙር ጨዋታዎች ላይ ቢገኝም ለዋንጫው አሸናፊነት 5 ክለቦች እንደታጩ በተለያዩ ዘገባዎች እየተገለፀ ነው፡፡ ለዋንጫው ከታጩትዋናዎቹ ሪያል ማድሪድና ባርሴሎና ከስፔን ፤ባየር ሙኒክ ከጀርመን እንዲሁም ቼልሲና ማንችስተር ሲቲ ከእንግሊዝ ናቸው፡፡የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የፍፃሜ ጨዋታ በየዓመቱ በአማካይ እስከ 300 ሚሊዮን ተመልካች በመላው ዓለም የሚያገኝ ነው፡፡ ዘንድሮ ለ60ኛዋ ዋንጫ የሚደረገው ፍልሚያ ከ7 ወራት በኋላ በጀርመን ዋና ከተማ በርሊን ውስጥ በሚገኘው ኦሎምፒያ ስታድዮን ይስተናገዳል፡፡ ባለፈው የውድድር ዘመን 10ኛውን የሻምፒዮናነት ክብር በመቀዳጀት የተሳካለት የስፔኑ ክለብ ሪያል ማድሪድ በተለያዩ ትንተናዎች፤ ቅድመ ትንበያዎች እና ውርርዶች ዘንድሮም ለሻምፒዮንነት በመጠበቅ የላቀ ግምት ወስዷል፡፡ ስለሆነም ሪያል ማድሪድ ምናልባትም ለ11ኛ ጊዜ ዋንጫውን በማንሳት የውድድሩን የከፍተኛ ውጤት ክብረወሰን በማሻሻል አዲስ ታሪክ ሊሰራ እንደሚችል በብዛት ተገምቷል፡፡ ይሁንና ባለፉት 24 ዓመታት በተከታታይ ሁለት የውድድር ዘመናት በማሸነፍ የሻምፒዮንነት ክብሩን ሊያስጠብቅ የቻለ ክለብ ግን የለም፡፡ በሻምፒዮንስ ሊግ የቅርብ ታሪክ ዋንጫዋን በተከታታይ ሁለት የውድድር ዘመናት ለማሸነፍ የበቃ ክለብ በ1990 እኤአ ላይ የጣሊያኑ ኤሲ ሚላን ብቻ ነው፡፡ ከዚያን በኋላ በተካሄዱት 24 የሻምፒዮንስ ሊግ የውድድር ዘመናት በሻምፒዮንነት ክብሩ የቀጠለ አልነበረም፡፡ በውድድሩ የቅርብ ጊዜ ታሪክ በቀደመው ዓመት ዋንጫውን አሸንፈው የሻምፒዮናነት ክብራቸውን ለማስጠበቅ እስከ ፍፃሜ ደርሰው ያልሆነላቸው 4 ክለቦች ነበሩ፡፡ ኤሲ ሚላን፤ አያክስ፤ ጁቬንትስ እና ማንችስተር ዩናይትድ ናቸው፡፡ በዓለም የእግር ኳስ ስፖርት የሚንቀሳቀሱ እውቅ አቋማሪ ድርጅቶች ለዋንጫው ድል ከፍተኛ ግምት በመስጠት አነስተኛ የውርርድ ገንዘብ ያቀረቡት ለስፔኑ ክለብ ለሪያል ማድሪድ ነው፡፡ ባየር ሙኒክ፤ ባርሴሎና፤ ቼልሲ እና ማንችስተር ሲቲ እንደቅደምተከተላቸው በአቋማሪዎች በየደረጃው የውርርድ ሂሳብ ወጥቶላቸው ለሻምፒዮንነት ክብሩ ተጠብቀዋል፡፡

ለናሙና ያህል ቢስፖርትስ የተባለ አቋማሪ ድርጅት ያወጣውን የውርርድ ስሌት መጥቀስ ይቻላል፡፡ ቢስስፖርትስ 32 ክለቦች በሚፎካከሩበት የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የዋንጫ ፉክክር ሪያል ማድሪድ 19.03 በመቶ የአሸናፊነት ግምት እንደሚሰጠው አመልክቶ፤ ባየር ሙኒክ 16.69፤ ባርሴሎና 15.51 ፤ ቼልሲ 11.87 እንዲሁም ሲቲ 6.7 በመቶ የማሸነፍ እድል እንደሚኖራቸው በመጥቀስ የውርርድ ሂሳቡን አስታውቋል፡፡ በሌላ በኩል ታዋቂው የእግር ኳስ ዘጋቢ ድረ ገፅ ጎል የአንባቢዎቹን ድምፅ በመሰብሰብ በሰራው የሻምፒዮንነት ትንበያ ላይ ዋንጫው የባርሴሎና ሊሆን እንደሚችል ተገልጿል፡፡ እንደጎል ድረገፅ አንባቢዎች ግምት 60ኛው የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ዋንጫን ለማሸነፍ 25.6 በመቶ እድል በመያዝ ባርሴሎና ቀዳሚ ነው፡፡ ቼልሲ በ25.5፤ ሪያል ማድሪድ በ13.2 እንዲሁም ባየር ሙኒክ በ11 በመቶ ድምፅ አግኝተው በተከታታይ ደረጃ ለዋንጫው ግምት ተሰጥቷቸዋል፡፡ ከአሰልጣኞች መካከልም ለዋንጫው አሸናፊነትና ለታሪካዊ ስኬትም የተጠበቁ አሉ፡፡ ጆሴ ሞውሪንሆ ከፖርቶና ከኢንተር ሚላን በኋላ ከቼልሲ ጋር በሶስተኛ ክለብ ጋር ዋንጫ በማንሳት ታሪክ መስራታቸው ግምት ተሰጥቶታል፡፡ ለሪያል ማድሪዱ አንቸሎቲ እና ለባየር ሙኒኩ ፔፔ ጋርዲዮላ ተመሳሳይ ታሪኮች ይጠበቃሉ፡፡ ክለባቸው አርሰናል ዘንድሮ ለመጀመርያ ጊዜ ሻምፒዮንስ ሊግን ማሸነፍ እንደሚችል በይፋ የተናገሩት ደግሞ አርሴን ቬንገር ናቸው፡፡ ቬንገር 90 በመቶ የዋንጫ ግምቱ ለሪያል ማድሪድ፤ ባርሴሎናና ባየርሙኒክ ቢያጋድልም፣ በሻምፒዮንስ ሊግ ልምድ ያለው አርሰናልም ለመጀመርያ ጊዜ ሻምፒዮን ለመሆን ተስፋ የሚኖረው ዘንድሮ ነው ብለዋል ፡፡

ከተጨዋቾች ለዋንጫው ያለውን እድል በተመለከተ ከተናገሩት ዋንኛው ተጠቃሽ የባርሴሎናው ሊዮኔል ሜሲ ነው፡፡ የካታላኑ ክለብ ከ3 የውድድር ዘመናት መራቅ በኋላ የሻምፒዮንስ ሊግ ዋንጫ ሊወስድ የሚበቃው በሊውስ ስዋሬዝ ምክንያት እንደሚሆን ሊዮኔል ሜሲ ተናግሯል፡፡ የሮናልዶ የወርቅ ኳስ ሃትሪክ እና ትንቅንቁ በዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር (ፊፋ) እና በታዋቂው የፍራንስ ፉትቦል መፅሄት ትብብር ለሚከናወነው የ2014 የዓለም ኮከብ እግር ኳሰኞች ምርጫ የቀረቡ እጩዎች ከሁለት ሳምንት በፊት ታውቀዋል፡፡ መላው ዓለም በጉጉት በሚጠባበቀውና ዋናው ሽልማት የሆነው የወርቅ ኳስ ነው፡፡ 23 ተጨዋቾች የመጨረሻ ዕጩዎች ሆነው ቀርበውበታል፡፡ አሸናፊው ከዓለም ዋንጫ ወይንስ ከሻምፒዮንስ ሊግ ይገኛል የሚለው ጉዳይ እያነጋገረ ነው፡፡ የኮከብ ተጨዋች ምርጫው በስፖርታዊ ብቃትና ዲሲፕሊን ተለክቶ ይበረከታል፡፡ በድምጽ አሰጣጡ ላይ በታዋቂው ፍራንስ ፉትቦል መጽሔት አማካኝነት ከመላው ዓለም የተውጣጡ ጋዜጠኞች እንዲሁም በፊፋ ስር ደግሞ የዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር አባል የሆኑ አገራት የብሔራዊ ቡድን አሰልጣኞችና አምበሎች ይሳተፋሉ፡፡ ዘንድሮ ለወርቅ ኳስ ሽልማት ተፎካካሪ ከሆኑት 23 እጩዎች መካከል የስፔኑ ላሊጋ 10 ተጨዋቾች በማስመረጥ ይመራል፡፡

የጀርመን ቦንደስ ሊጋ 6 እንዲሁም የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ 5 ተጨዋቾች ከእጩዎቹ ተርታ በማካተት ተሳክቶላቸዋል፡፡ ለ2014 ወርቅ ኳስ ሽልማት ዋና ተፎካካሪዎች የሆኑት የሪያል ማድሪዱ ክርስትያኖ ሮናልዶና እና የባርሴሎናው ሊዮኔል ሜሲ መሆናቸው በተለምዶ ቢነገርም የዓለም ዋንጫን ያሸነፉት የጀርመን ተጨዋቾች ዋና ተቀናቃዐኞቻቸው ናቸው፡፡ ጀርመናዊያኑ ፊሊፕ ለሃም፣ ቶምስ ሙለር፣ ማኑዌል ኑዌር እና ማርዬ ጐትዜ ፊፋ ለራሱ ውድድሮች በሚሰጠው ግምት ከመጨረሻዎቹ 3 እጩዎች ተርታ የመግባትና የማሸነፍ ዕድል እንዳላቸው እየተገለፀ ነው፡፡ ከጀርመናውያኑ የዓለም ዋንጫ አሸናፊዎች ከባድ ፉክክር ባሻገር በ2014 የዓለም ኮከብ ተጨዋቾች ምርጫው ከፍተኛ የማሸነፍ ዕድል እንዳለው የሚነገርለት ፖርቱጋላዊው የሪያል ማድሪድ ተጨዋች ክርስትያኖ ሮናልዶ ነው፡፡ ሌላ የቅርብ ተፎካካሪው ሊዮኔል ሜሲ ነው፡፡

ክርስትያኖ ሮናልዶ በ2014 ብዙ ስኬቶች ነበሩት፡፡ በአውሮፓ ትልልቅ ሊጎች ኮከብ ግብ አግቢነት የወርቅ ጫማ ለሶስተኛ ጊዜ መሸለሙ ተጠቃሽ ነው፡፡ ባለፈው የውድድር ዘመን ከሪያል ማድሪድ ጋር 10ኛውን የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ዋንጫ ድል በማግኘቱ፣ በ17 ጐሎች የውድድሩ ኮከብ ግብ አግቢ ሆኖ መጨረሱ፣ በአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር ምርጫ የዓመቱ ኮከብ ተጨዋች ሆኖ መመረጡና ከሁለት ሳምንት በፊት የላሊጋው ኮከብ ሆኖ አራት ልዩ የክብር ሽልማቶችን ማግኘቱ ለወርቅ ኳሱ ሽልማት የሚባቀበትን ሁኔታ አስፍቶለታል፡፡ ሮናልዶ ምንም እንኳን በዓለም ዋንጫ ከአገሩ ብሔራዊ ቡድን ጋር ስኬታማ ባለመሆኑ በምርጫው በፊፋ አባል አገራት ሊያገኛቸው የሚችላቸውን ድጋፎች ቢያወርድበትም 2014 ከገባ በክለብ ደረጃ በ44 ጨዋታዎች 45 ጐሎች ማስመዝገቡ የውድድር ዘመኑ ምርጥ ተጨዋች ያደርገዋል፡፡ ብራዚል ባዘጋጀችው 20ኛው የዓለም ዋንጫ አገሩን አርጀንቲና ለፍፃሜ ያደረሰው እና የዓለም ዋንጫው ኮከብ ተጨዋች ሆኖ የተመረጠው አርጀንቲናዊው ሊዮኔል ሜሲ ምናልባትም ከሮናልዶ ጋር ብዙ ተፎካካሪ የሚሆንበት ስኬት የለውም፡፡ ይሁንና ሊዮኔል ሜሲ በሻምፒዮንስ ሊጉ የ4ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ክለቡ ባርሴሎና የሆላንዱን አያክስ 2ለ0 ሲያሸንፍ ሁለቱንም ጎሎች በማግባት በውድድሩ ታሪክ የምንግዜም ከፍተኛ ግብ አግቢነትን በ71 ጎሎች ከቀድሞው ስፔናዊ ራውል ጋር በመጋራት ከሮናልዶ የቀደመ ስኬት ማግኘቱ ትኩረት እየሳበለት መጥቷል፡፡ ራውል 71 ጎሎች ያስመዘገበው በ144 ጨዋታዎች ሲሆን ሜሲ በ90 ጨዋታዎች ክብረወሰኑን ተጋርቶታል፡፡ ሮናልዶ በ107 ጨዋታዎች 70 ጎሎች አስመዝግቧል፡፡

ሊዩኔል ሜሲ የወርቅ ኳስ ሽልማትን ለ4 ጊዜያት ያሸነፈ ሲሆን ክርስቲያኖ ሮናልዶ ያሸነፈው ደግሞ ሁለቴ ነው፡፡ በ2013 የዓለም ኮከብ ተጨዋች ምርጫ ላይ ኢትዮጵያውያን በነበራቸው ተሳትፎ የብሔራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝ የነበሩት ሰውነት ቢሻው ሮናልዶ፣ ኢንዬስታ እና ኔይማር በማለት ኮከባቸውን በደረጃ አከታትለው ሲመርጡ ፤ የብሔራዊ ቡድን አምበል የነበረው ደጉ ደበበ ዣቪ፤አንድሬ ፒርሎና ቶሞስ ሙለርን ብሎ ነበር፡፡ በጋዜጠኞች ዘርፍ ደግሞ ታዋቂው መንሱር አብዱልቀኒ ፍራንክ ሪበሪ፤ ክርስትያኖ ሮናልዶ እና ሽዋንስታይገር ብሎ ድምፅ ሰጥቶ ነበር፡፡ በነገራችን ላይ ሰሞኑን ፎርብስ ለዓለም ስፖርተኞች ለዓመቱ ከፍተኛ ገቢ ባወጣው ደረጃ ሮናልዶ በ64 ሚሊዮን ዩሮ ከእግር ኳስ ተጨዋቾች አንደኛ ከሁሉም ስፖርተኞች ሁለተኛ ደረጃ አለዐው፡፡ የሮናልዶ ገቢ 41.6 ሚሊዮን ዩሮው ከደሞዝ ሲሆን 22.4 ሚሊዮን ዩሮ ደግሞ ከተለያዩ የንግድ ውሊች እና የስፖንሰርሺፕ ክፍያዎች ያገኘው ነው፡፡ ሜሲ በ52፤ ዝላታን ኢብራሞቪች በ32.32፤ ጋሬዝ ቤል በ29.12፤ ፋልካኦ በ28.32 እንዲሁም ኔይማር በ26.88 ሚሊዮን ዩሮ ገቢያቸው ተከታታይ ደረጃ ወስደዋል፡፡ ፡

  • የማህበሩንና የቤት ገዢዎችን ችግር ለመፍታት ኮሚቴ ተቋቁሟል


             አክሰስ ሪል እስቴት አክሲዮን ማህበር ካለበት እዳ ይልቅ ሃብቱ እንደሚበልጥ ተገለፀ፡፡ የማህበሩንና የቤት ገዢዎችን ችግር ለመፍታት ከትልልቅ ሚኒስቴር መ/ቤቶችና ከባለ ድርሻ አካላት የተወጣጡ የአብይና የቴክኒክ ኮሚቴዎች ተዋቅረዋል፡፡ ከትላንት በስቲያ በንግድ ሚኒስቴር በተሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ፤ የተዋቀሩት ኮሚቴዎች የአክሰስ ሪል ስቴትንና የቤት ገዢዎቹን ችግር ከመፍታት ባሻገር በአገር አቀፍ ደረጃ እየተከሰተ ያለውን የሪል እስቴት ችግር ለመቅረፍ የአጭር፣ የመካከለኛና የረጅም ጊዜ እቅድ ነድፈው እየተንቀሳቀሱ መሆናቸውን በንግድ ሚኒስቴር ስር የተቋቋመው የቴክኒክ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ኑረዲን መሃመድ አስታውቀዋል፡፡
የኮሚቴው የአጭር ጊዜ እቅድ በአክሰስ ሪል ስቴት አክሲዮን ማህበርና በአገር ውስጥና በውጭ አገር የሚኖሩ ቤት ገዢዎችን ችግር በአንድ አመት ውስጥ እልባት መስጠት ሲሆን በረጅም ጊዜ እቅዱ በአገር አቀፍ ደረጃ በሪል እስቴት ዘርፍ፣ በመሬት አዋጅ ዙሪያ፣ በአክሲዮን ማህበራት ምስረታና አካሄድ ላይ ያሉ ችግሮች ዘላቂ መፍትሄ የሚያኙበትን እርምጃዎች አጥንቶ ለመንግሥት ፖሊሲ ውሳኔ ለማቅረብ ይንቀሳቀሳል ተብሏል፡፡
የአክሰስ ሪል እስቴት የቤት ገዢዎችን ችግር የሁሉንም መብት ባስከበረ መልኩ ለመፍታት የጠቅላይ ሚኒስትሩ ፅ/ቤት በከፍተኛ የመንግሥት አመራሮች የሚመራ አብይ ኮሚቴ ያዋቀረ ሲሆን ኮሚቴውን የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስቴር ሚኒስትር አቶ መኩሪያ ኃይሌ በሰብሳቢነት፣ የንግድ ሚኒስቴር ሚኒስትሩ ደግሞ በምክትል ሰብሳቢነት ይመሩታል ተብሏል፡፡ ለስራው አመቺነት የአክሰስ ሪል እስቴት የዳይሬክተሮች ቦርድ፣ የቤት ገዢዎች ተወካይ፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ፅ/ቤት፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የፍትህ ቢሮ፣ የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ ፅ/ቤት እና የፍትህ ሚኒስቴር የኮሚቴው አባላት በመሆን እየሰሩ እንደሆነ ተጠቁሟል፡፡
አብይና የቴክኒክ ኮሚቴዎቹ የተቋቋሙት በአሁኑ ሰዓት በአክሰስ ሪል እስቴትና በቤት ገዢዎች መካከል የተነሳው ቀውስ በተናጠልና በፍ/ቤት ብቻ የሚፈታ ሳይሆን ሁለገብ የመንግሥት ድጋፍ ስለሚያስፈልገው እንደሆነ የተገለፀ ሲሆን ችግሩ እልባት እስከሚያገኝም ሶስተኛ ወገኖች በትእግስት እንዲጠብቁ ማሳሰቢያ ተሰጥቷል፡፡
አክሰስ ሪል እስቴት ያሉትን የገንዘብና የአይነት ሃብቶች፣ በአክሰስ ሪል ስቴት ስም ያሉትን፣ በስሙ ያልተመዘገቡትንና ወደ አክሰስ ሪል እስቴት መግባት ያለባቸውን መሬቶች፣ የተገነቡና የተሸጡ ህንፃዎችን እንዲሁም የደረቅ ቼኮችን ሁኔታ የቴክኒክ ኮሚቴው እየመረመረና ወደ መፍትሄ እየመጣ መሆኑን አቶ ኑረዲን ገልፀው፤ አክሰስ ሪል እስቴት ራሱ ውል ሰጪና ተቀባይ ሆኖ የተፈራረመባቸው ሰነዶች፣ ደረቅ ቼኮችና ተያያዥ የተጭበረበሩ ጉዳዮች በመገኘታቸው በዶክመንትነት ተይዘው እየተመረመሩ እንደሆነና ጅቡቲ ወደብ ላይ የደረሱ የኮንስትራክሽን መሳሪያዎችና ብረታ ብረቶች እንዳሉ እንደተደረሰበትም ተገልጿል፡፡
በቀጣይ ደረቅ ቼኩ ምን ይደረግ? ገንዘባቸውን የሚፈልጉ ቤት ገዢዎች የትኛው የማህበሩ ንብረት ተሸጦ ይመለስላቸው? የማህበሩን ህልውና ለማስቀጠልና የቤት ገዢዎችን ጥያቄ በአመርቂ ሁኔታ ለመመለስ ምን ምን ስራዎች ይሰሩ? የሚለው ላይ የቴክኒክ ኮሚቴው በትጋት እየሰራ እንደሆነም ተጠቁሟል፡፡
በመሬት አዋጁ፣ በሊዝ አዋጁና በአክሲዮን ምስረታ አካሄድ ላይ የፖሊሲ አቅጣጫዎች ለማስቀመጥ ስራዎች እየተሰሩ ሲሆን በእነዚህ ዘርፎች የሚታዩ የተዝረከረኩ አሰራሮች እንዲስተካከሉ ይደረጋል ተብሏል፡፡
የአክሰስ ሪል እስቴት መስራችን በተመለከተም ለጉዳዩ እልባት ለመስጠት ከአብይ ኮሚቴው ጋር በመነጋገር በዲፕሎማሲያዊ ጥረትና በተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ እየተሰራ ሲሆን አክሰስ ሪል እስቴት ህልውናውን ለማስቀጠል የሚያስችሉ የገንዘብና ሌሎች አቅሞች እንዳሉት የቤቶች ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስቴርን ወክለው በመግለጫው ላይ የተገኙት የቴክኒክ ኮሚቴው ምክትል ሰብሳቢ አቶ ታደሰ ገ/ጊዮርጊስ ለጋዜጠኞች ተናግረዋል፡፡

Published in ዜና

ከ140ሺ በላይ የጋራ መኖሪያ ቤቶች ግንባታ አልተጠናቀቀም

በአዲስ አበባ መሚገነቡ የ20/80፣ 10/90 እና 40/60 እንዲሁም ከመኖሪያ ቤት ህብረት ሥራ ማህበራት ተመዝጋቢዎች በቁጠባ መልክ የተሰበሰበው ገንዘብ 4.1 ቢሊዮን ብር መድረሱ ተገለፀ፡፡
በሥራ ተቋራጮችና በአማካሪ ኩባንያዎች ብቃት ማነስ ሳቢያ ከ140ሺ በላይ የጋራ መኖሪያ ቤቶች ግንባታ አልተጠናቀቀም ተብሏል፡፡
የከተማ ልማት ቤቶችና ኮንስትራክሽን ሚኒስቴር ሚኒስትር አቶ መኩሪያ ኃይሌ ሰሞኑን ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባቀረቡት ዕቅድና የዕቅድ አፈፃፀም ሪፖርት ላይ እንደገለፁት፤ ለኮንዶሚኒየም ቤቶች ከተመዘገቡና ከመኖሪያ ቤት ህብረት ሥራ ማህበራት ምዝገባ 4.1 ቢሊዮን ብር ተሰብስቧል፡፡ “ይህም የቤት ልማቱን ዘላቂነት ያረጋገጠ ሆኗል” ብለዋል- ሚኒስትሩ፡፡ በከተማው በ2003 እና በ2004 ዓ.ም በ20/80 ፕሮግራም የተጀመሩ 71ሺ 127 ቤቶች ግንባታቸው ሙሉ በሙሉ እንዲጠናቀቅ የታቀደ ቢሆንም በዕቅዱ መሠረት ግንባታው አለመጠናቀቁን አቶ መኩሪያ ተናግረዋል፡፡ በ2006 ግንባታቸው እንዲጀመር ከታቀዱት 50ሺ ቤቶች ግንባታቸው የተጀመረው 13ሺ014 ብቻ እንደሆኑ ጠቁመው በ10/90 ቤቶች ልማት ፕሮግራም በመገንባት ላይ የሚገኙት ቤቶች 24ሺ 288 ሲሆኑ የእነዚህም የግንባታ አፈፃፀም 62.17 በመቶ ብቻ መሆኑን ሚኒስትሩ ገልፀዋል፡፡
 ለግንባታዎቹ መዘግየት ከጠቀሷቸው ምክንያቶች መካከል የሥራ ተቋራጮችና የአማካሪ ኩባንያዎች ብቃት ማነስ፣ የባለሙያዎች እጥረት፣ የመሠረተ ልማት አቅርቦት ችግር፣ የመሬት አቅርቦት እጥረትና የክትትልና ድጋፍ ውስንነት ዋንኞቹ እንደሆኑ አብራርተዋል፡፡ ዘንድሮ በ10/90 ቤቶች ፕሮግራም 10ሺ340 ቤቶች፣ በ20/80 ቁጠባ ቤቶች ፕሮግራም 60ሺ740 ቤቶች፣ በ40/60 ቤቶች ፕሮግራም ደግሞ 17ሺ870 ቤቶችና በማህበራት 4870 መኖሪያ ቤቶች ለመገንባት ዕቅድ መያዙንም አቶ መኩሪያ ለምክር ቤቱ ባቀረቡት ሪፖርት ላይ ገልፀዋል፡፡

Published in ዜና
  • የ24 ሰዓት ሰላማዊ ሰልፍና ህዝባዊ ውይይት ለማካሄድ ታቅዷል
  • እውነተኛ ምርጫ ካለ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ያሸንፋሉ ብለዋል


          ከሁለት ሳምንት በፊት በዘጠኝ ብሔር ተኮርና ህብረ - ብሄር ፓርቲዎች የተመሰረተው የፓርቲዎች ትብብር፤ የህዳር ወር የተግባር እንቅስቃሴውን ሰሞኑን ይፋ ተደርጓል፡፡ ስድስት ዋና ዋና እንቅስቃሴዎችን ለመከወን እቅድ ያወጣው የፓርቲዎቹ ትብብር፤ የ24 ሰዓት ሰላማዊ ሰልፍና በአዲስ አበባ ሶስት አማካይ ዞኖች የሚካሄዱ ህዝባዊ ውይይቶች እንደሚገኙበት አስታውቋል፡፡
የህዳር ወርና ቀጣይ የተግባር እንቅስቃሴዎች በዋናነት ትኩረት የሚያደርጉት በመጪው ግንቦት ወር በሚካሄደው አገራዊና ክልላዊ ምርጫ ላይ እንደሆነም የትብብሩ አመራሮች ገልፀዋል፡፡
ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ለ2007 ምርጫ ያዘጋጀውን የጊዜ ሰሌዳ ለማወያየት በሚል የፖለቲካ ፓርቲዎችን ስብሰባ መጥራቱን ያስታወሱት አመራሮቹ፤ ከዚህ ስብሰባ አስቀድሞ የዚህ ትብብር አባል ፓርቲዎችን ጨምሮ 12 ፓርቲዎች ጥቅምት 5 ቀን 2005 ለቦርዱ ያቀረቧቸው ጥያቄዎች አለመመለሳቸውን፣ ገዢው ፓርቲና አጋሮቹን ጨምሮ ሁሉም ህጋዊ ፓርቲዎች ተገናኝተው በምርጫና በመድብለ ፓርቲ ሥርዓት ግንባታ ላይ የሚወያዩበት የጋራ መድረክ እንዲዘጋጅ ቢጠይቁም ምላሽ እንዳላገኙ ጠቁመው ሁኔታው የፖለቲካ ምህዳሩ ጠቧል ሳይሆን ተዘግቷል ወደሚል ድምዳሜ የሚያደርስ ነው ብለዋል፡፡
 “የፖለቲካ ምህዳሩ የቱንም ያህል ቢዘጋም ግን ህዝቡ ተገቢ መብቶቹን እስኪቀዳጅ ድረስ የትግሉን አስፈላጊነት አምነንበት በጥንካሬ እንጓዛለን” ብለዋል - አመራሮቹ በሰጡት መግለጫ፡፡ በምርጫው መሳተፍ አለመሳተፋቸውን እስኪወስኑ ድረስ በቀሪዎቹ ወራት የምርጫው ሂደት ፍትሃዊና ተዓማኒ እንዲሆን የሚመለከታቸው አካላት ትኩረት እንዲሰጡት የተግባር እንቅስቃሴውን እንደሚቀጥል ያስታወቀው ትብብሩ፤ የህዳር ወር የተግባር እንቅስቃሴው ህዝቡ በየቤተ - እምነቱ የፀሎት ፕሮግራም እንዲያደርግ ጥሪ ማስተላለፍ፣ በምርጫ ዙሪያ የፓናል ውይይት ማድረግ፣ የአደባባይ ህዝባዊ ስብሰባዎችን ማካሄድ፣ ለመንግስታዊ ተቋማት (ለፍትህ ሚኒስቴር፣ ለኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለስልጣንና መሰል መ/ቤቶች) ደብዳቤ ማስገባት፣ የተቃውሞ ድምጽ ማሰማትና የህዝብን ተሳትፎ ማበረታታት እንዲሁም ድጋፍ ማሰባሰብ የሚሉትን እንደሚያካትት ገልጿል፡፡
“አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታና ቀደም ካሉት የምርጫ ሂደቶች ተሞክሮ በመነሳት ገዢው ፓርቲ በጉዳይ ፈፃሚው በምርጫ ቦርድ በኩል የሚሰራውን ቧልት እናውቃለን” ያሉት የትብብሩ ሰብሳቢ ኢ/ር ይልቃል፤ ይህንን ቧልት ራቁቱን በማስቀረት ለነፃ፣ ፍትሃዊ፣ ተአማኒና አሳታፊ ምርጫ ሜዳው እንዲስተካከል፣ በሰላማዊ ትግል አዎንታዊ ተፅዕኖ ለማሳረፍና ለዚህም አስፈላጊውን መስዋዕትነት ለመክፈል፤ ትብብሩ መወሰኑን አስታውቀዋል፡፡
እውነት የዚህች አገር የፖለቲካ ችግር በፀሎት ይፈታል ወይ? በሚል ከጋዜጠኞች ለቀረበው ጥያቄ ሰብሳቢው ኢ/ር ይልቃል ሲመልሱ፤ “እንደኛ ደረቅ ፖለቲከኞች ቢሆን ይህች አገር ጠፍታ ነበር፤ እስካሁንም በእምነታቸው በፀኑ አባቶችና እናቶች ፀሎት ነው የኖረችው፤ ፀሎት መፍትሔ እንደሚያመጣ እናምናለን፤ ምክንያቱም ኢትዮጵያ የእነ አቡነ ጴጥሮስ አገር ናት” ብለዋል፡፡
 የ24 ሰዓቱ ሰላማዊ ሰልፍ መቼና የት ይካሄዳል ለሚለውም ሰልፉ ህዳር 27 እና 28 እንደሚካሄድ፤ ነገር ግን ጃንሜዳ ይሁን መስቀል አደባባይ ገና እንዳልተወሰነ አመራሮቹ ተናግረዋል፡፡ ከእንቅስቃሴው የሚጠበቀው ውጤት ምን እንደሆነ የተጠየቁት አመራሮቹ፤ ተስፋ ያለው አማራጭ የፖለቲካ ሃይል ሆኖ በመቅረብ ትግሉን ማካሄድ እንደሆነና ህዝቡ የኢህአዴግን አምባገነንነት ጠንቅቆ ስለሚያውቅ አማራጭ የፖለቲካ ሃይል ካገኘ ቀስቃሽ ሳያስፈልገው ስልጣኑን የራሱ እንደሚያደርግ ገልፀዋል፡፡ “በምርጫ ትሳተፋላችሁ አትሳተፉም? እስከ ዛሬ ካደረጋችሁት ሰላማዊ ሰልፍስ ምን አተረፋችሁ?” በሚል ከአዲስ አድማስ ለቀረበው ጥያቄም፤ “እውነተኛ ምርጫ ካለ 99.6 በመቶ የሚያሸንፉት ተቃዋሚ ፓርቲዎች ናቸው” ያሉት ሰብሳቢው፤ “ነፃ፣ ፍትሃዊና ግልጽ የምርጫ ሂደት በሌለበት በምርጫ መሳተፍ ማለት የዚህችን አገር ችግር ማባባስ፣ ለኢ-ዴሞክራሲያዊነትና ለስርዓት አልበኝነት መተባበር እንዲሁም በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ መሳለቅ በመሆኑ አንሳተፍም“ ብለዋል፡፡
 ሆኖም አሁን ሙሉ በሙሉ አንሳተፍም ብለን አልደመደመንም፤ ምርጫው ፍትሃዊ፣ ምርጫ ቦርድም ገለልተኛ የሚሆኑበትን አማራጮች ለመፍጠር እንጥራለን ሲሉ ሰብሳቢው ገልፀዋል፡
“በንጉሱ፣ በደርግም ሆነ በኢህአዴግ ጊዜ ምርጫዎች ተካሂደዋል፤ ሆኖም ይህቺን አገር ከአገዛዝ ወደ ዴሞክራሲ ስርዓት አላሸጋገራትም” ያሉት የትብብሩ ም/ሰብሳቢ፤ ለዚህ ምክንያቱ በአንዱም ዘመን እውነተኛ ምርጫ ባለመካሄዱ ነው ብለዋል፡፡
ሌሎች ፓርቲዎችም ወደ ትብብሩ ተቀላቅለው ተፅዕኖ እንዲፈጥሩ ጥሪ ያስተላለፉት አመራሮቹ፤ በአገር ቤትም ሆነ በውጭ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንም ሁለንተናዊ ድጋፍ እንዲያደርጉ ጠይቀዋል፡፡

Published in ዜና

          ሰሞኑን የሽብር ክስ የቀረበባቸው የአንድነት፣ የአረና እና የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና የሌሎች ተከሳሾች ጠበቆች፤ የዋስትና ጥያቄያችንን በፅሁፍ እናቅርብ በማለታቸው ፍ/ቤቱ የዋስትና ጥያቄውን መርምሮ ብይን ለመስጠት በድጋሚ ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
ተከሳሾቹ ባለፈው ረቡዕ የዋስትና ጥያቄ አቅርበው ፍ/ቤቱ ጥያቄያቸውን መርምሮ ብይን ይሰጣል ተብሎ የተጠበቀ ቢሆንም ጠበቆቻቸው የዋስትና ጥያቄውን በፅሁፍ ለማቅረብ እንዲፈቀድላቸው ጠይቀዋል፡፡ ቀደም ሲል ለአራቱ የፓርቲ አመራር ተከሳሾች ጥብቅናዬን ለጊዜው አቁሜያለሁ በማለት መግለጫ የሰጡት ጠበቃ ተማም አባቡልጉ፤ በድጋሚ ወደ ጥብቅናቸው የተመለሱ ሲሆን በእለቱም “ደንበኞቼን አስመልክቶ የማቀርበው የዋስትና ጥያቄ በዝርዝርና በሰፊው ስለሆነ በፅሁፍ እንዳቀርብ ይፈቀድልኝ” ሲሉ ፍ/ቤቱን ጠይቀዋል፡፡ የሌሎች ተከሳሾች ጠበቆችም ተመሳሳይ ጥያቄ በማቅረባቸው፣ ፍ/ቤቱ የሚቀርበውን የዋስትና ጥያቄ መርምሮ ብይን ለመስጠት ለህዳር 2 ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
የተከሳሽ ጠበቆች በክስ መዝገቡ ላይ የማስረጃ ዝርዝር አልተያያዘም፤ የከሳሽ አቃቤ ህጐች ስምም አልተገለፀም በማለት ለፍ/ቤቱ ጥያቄ ያቀረቡ ሲሆን አቃቤ ሕግ የማስረጃ ዝርዝርን በተመለከተ በሰጠው ምላሽ፤ “አቃቤ ህግ መስጠት የሚችለው፤ የማስረጃ ዝርዝር ሳይሆን የማስረጃ መግለጫ ነው  የሰነድ ማስረጃዎችን የተመለከቱ መግለጫዎችንም በሬጅስትራር በኩል እንዲደርሳቸው አድርገናል” ብሏል፡፡
 የአቃቤ ሕግ ስም አልተጠቀሰም ለሚለውም፤ ክሱ የተመሰረተው በተቋም ደረጃ ስለሆነ፣ የከሳሾቹ ተቋም ስምና ማህተም ከተገለፀ በቂ ነው ሲል ምላሽ ሰጥቷል፡፡አራት የፓርቲ አባላትን ጨምሮ 10 ተጠርጣሪዎችን ባካተተው የክስ መዝገብ፣ 1ኛ ተከሳሽ ሆኖ የቀረበው በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የማስተርስ ተማሪ ዘላለም ወርቅአገኘሁ፤ ከ2000 ዓ.ም ጀምሮ የግንቦት 7 አመራር ከሆነው ተድላ ደስታ የተባለ ግለሰብ ጋር በስልክና በፌስቡክ በመገናኘት በኢትዮጵያ ውስጥ የመንግሥት ለውጥ እንዴት ይምጣ በሚለው ላይ ተነጋግሯል ተብሏል፡፡

ተከሳሹ በ2003 ዓ.ም የግንቦት 7 አባል እንደሆነ፣ ማንነቱ እንዳይታወቅ በተደጋጋሚ በሌላ ሰው ስም የጂሜይል አካውንት በመክፈት፣ ከተድላ ደስታ ጋር ሲመካከር እንደነበር የክስ መዝገቡ ያመለክታል፡፡ በ2004 ዓ.ም በአረቡ ሀገር የተነሳው አይነት አመፅ በኢትዮጵያ እንዲፈጠር ሁለቱ ግለሰቦች ሲመካከሩ ነበር ተብሏል፡፡ የግንቦት 7 አባላት የሚሆኑ ግለሰቦችንም እየመለመለ ወደ ኤርትራ እንዲልክ ተልዕኮ ተቀብሎ እንደነበር የጠቆመው የአቃቤ ሕግ የክስ ዝርዝር፤ በግንቦት 7 አመራሮች 10 ሺህ ብር ተልኮለት ብሄራዊ ትያትር ቤት አካባቢ ማንነቱ ካልተጠቀሰ ግለሰብ መቀበሉን አመልክቷል፡፡
በሀገሪቱ እንዲመጣ የሚፈለገው ለውጥ ስኬታማ የሚሆነው የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን በአመፅ ቢዘጋ መሆኑን እንደተመካከሩም በክስ መዝገቡ ተጠቅሷል፡፡
ህጋዊ ፓርቲን ሽፋን በማድረግ የግንቦት 7 አባል በመሆን ሲንቀሳቀስ ነበር የሚል ክስ የቀረበበት 2ኛ ተከሳሽ የአንድነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ ሀብታሙ አያሌው፤ የአማራ ህዝብ ስቃይ እንዲያበቃ አሁን ያለውን መንግሥት መቀየር ያስፈልጋል ሲል ለግንቦት 7 ድርጅት መግለጫ መስጠቱ በክሱ ላይ ተመልክቷል፡፡ዘመኑ ንጉሴ ከተባለ የግንቦት 7 አባል ጋርም በስልክ በመገናኘት አንድነት ፓርቲን ሽፋን በማድረግ፣ አብረው ለመስራት መመካከራቸው የተገለፀ ሲሆን በፓርቲው ሰላማዊ ሰልፎች ላይ በመገኘትም አመፅ እንዲነሳ መልዕክት ሲያስተላልፍ ነበር ተብሏል፡፡ 3ኛ ተከሳሽ የአንድነት ፓርቲ የድርጅት ጉዳይ ምክትል ኃላፊ ዳንኤል ሺበሺ፤ ህዝቡ መንግሥትን ለመለወጥ መዘጋጀቱን፣ የመንግሥት ስልጣን ለመረከብ ምደባ መደረጉንና ተኩስ መጀመሩን ለግንቦት 7 አመራር አባል ለፋሲል የኔአቢይ መልዕክት ማስተላለፉ በክሱ ተመልክቷል፡፡
ከግንቦት 7 ጋር በጥምረት ይንቀሳቀሰል ከተባለው ዲምፀት ድርጅት ጋር ግንኙነት እንደነበረው የተጠቀሰው ሌላው ተከሳሽ ደግሞ የአረና ፓርቲ አባል አብርሃ ደስታ ነው፡፡ ተከሳሹ ኤርትራ ውስጥ ከሚገኙ የግንቦት 7 አባላት ጋር በስልክ ይገናኝ እንደነበርና አባላት መልምሎ ወደ ኤርትራ ለመላክ እንደተስማማ እንዲሁም በሥልጣን ላይ ያለውን መንግሥት አስወግዶ ህዝባዊ መንግሥት ማቋቋም እንደሚገባ መመካከሩ በአቃቤ ህግ የክስ መዝገብ ላይ ተጠቁሟል፡፡ የሰማያዊ ፓርቲ ምክር ቤት ምክትል ሰብሳቢ አቶ የሸዋስ አሰፋም ከግንቦት 7 አባላት ጋር ግንኙነት እንደነበረው ተጠቅሷል፡፡ ቀሪዎቹ ተከሳሾች፣ የግንቦት 7 አባል በመሆንና የሚሰጣቸውን ተልእኮ በመቀበል፣ የድርጅቱን አላማ ለማስፈፀም ሲንቀሳቀሱ ነበር ይላል - የክስ መዝገቡ፡፡

Published in ዜና