Monday, 03 November 2014 08:11

የአዳም ረታ ሃሳቦች

ስለስኬታማ ደራሲነት

         ስኬታማ ደራሲ ላልከው አንፃራዊነት ለሚንከባከቡ፣ ከጥናትም ይሁን ከግል ስሜትና ፍላጎት ተነስተው ለሚፈርዱ ወይም ለሚያደሉ ቦታውን ብለቅ ይሻላል፡፡ ስኬታማ የሚለውን ቃል ሙሉ ፍቺ አይናአፋር የተጠየቅ ቅንፍ ውስጥ ልክተተው፡፡
ስኬታማነት ተነቃናቂ ኢላማ ነው፡፡ ማታ ላይ አጠናቅቄ በሰራሁት ድርሰት ረካሁ ብዬ ብተኛም፣ ሲነጋ ቅር የሚሉኝ ነገሮች ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ከአመታት በፊት በፃፍኩት ዛሬ ላልደሰት እችላለሁ፡፡ የስኬታማነት መለኪያዎች አስራ አስር ናቸው፡፡ ነገር ግን አንድ ሰው አገሩ ውስጥ መኖሩን ወይም አለመኖሩን የስነ-ፅሁፍ ስኬታማነት መገምገሚያ ማድረግ ምስፋርን/ስፍራን (place) ብቻ የብቃት መለኪያ ማድረግ ነው፡፡ ይሄ ነጠላ ብቆታ በአብዛኛው ከውጤቱ ወይም ከድርሰቱ ውጭ ያለ ነው፡፡ የተለያዩ የስፍራ መደቦች አሉ፡፡ የግል ስፍራ አለ (Personal space)፣ የቤትህ፣ የቀበሌህ ስፍራ፣ ወዘተ … አለ፡፡ በተጨማሪም ደራሲው በኢምንትነቱ የሙሉኩሌው ወይም የወተትማው መንገድ አባል ነው፡፡ ግንባሩ በሶላር ፍሌርስ ይግላል፣ በበጋ በሚመጣ ዝናብ የሚከረስስ ቆዳ አለው፡፡ በምድር የመግነጢስ መረብ ይረግባል፣ ይወጠራል፡፡
አንድ ደራሲ ዋናው መሳሪያው ምናቡ ነው፡፡ ግን ነባር ልዩ ቦታህ በነበርክ ጊዜ በስርነቀል ልምድ ውስጥ እንድታልፍ ደንብ መሰለኝ (ይሄ ልምድ ፖለቲካ ብቻ መሆን የለበትም፡፡ ብዙ ጊዜ አንድ የልምድ ዝርያ ላይ ብቻ በማተኮርና ለዛም የማይገባውን ክብደት ብቻ በመስጠት በልምድ የመብሰል መለኪያ ሊደረግ ይሞክራል፡፡ ይሄ አድልኦ ነው፡፡)
ትተኸው (በእርግጥ ትተኀዋል ወይ?) የሄድከው ህብረተሰብ ውስጡ ምን ይመስል እንደነበር በመጠኑም ቢሆን መረዳት አለብህ፡፡ የትኛው ክስተትና ዕውነታ ነው ውዝፍ? (constant) የትኛው ነው ተለዋዋጩ? የቱ ነው ፈዞ/ተለውጦ የሚጠብቅህ? አለዋወጡ የሚገዙት የግንጵሊት ንጥረ ነገሮቹ (elements of metamorphosis) ምንድናቸው? ወዘተ…
ብዙ ብሑት (innovators) የሚባሉ የባዕድ ደራሲዎች ትልልቅ ድርሰቶቻቸውን የፃፉት ከትውልድ አገራቸው ውጭ ሆነው ነው፡፡ እንደውም አንዳንዴ ስለ ራሳቸው አገር በጠለላቸው አገር ቋንቋም ይፅፋሉ፡፡ ወሳኙ ያሳለፍከው የልምድ ስፋትና ጥልቀት፣ ለዚያም ያለህ ግንዛቤና በንቁነት ወይም በኢ-ንቁነት የምታነሳቸው ንፅፅሮች ናቸው እንጂ አካላዊ ዕርቀትና ቅርበት መለኪያ አይደለም፡፡
በራስህ ከምትገነዘበው፣ ተገንዝበህ የምታሰላስለው፣ አሰላስለህ መደምደሚያ የምትወስድበት፣ አንድ ተራ የመሰለ ድርጊት/ገጠመኝ ሰዎችን በግል ብቻ ሳይሆን ስርአት ውስጥ ያላቸውን ባህርይ እንድትረዳ ሰፊም ይሁን ጠባብ መንገድ ይከፍትልሃል፡፡ በስደት ስኖር በእርግጥ አዲስ የረቀቀ የስነፅሁፍ መሰረተልማት (Infrastructure) ውስጥ እገባለሁ፡፡ እነዚያ መኖራቸውን ታያለህ ግን ለእኔ ስራ መመጠናቸውን ማመዛዘን አለብኝ፡፡ ንፅፅር ያልኩት ይሄንን ነው፡፡
ባዕድ አገር ሆኜ ኢትዮጵያ ውስጥ ስላለ የቄስ ትምህርት ቤት ዘመን ብፅፍ በግል ተዘክሮዬ ይዤው የመጣሁት የመረጃ ወይም የዕውነታ አንኳር አለ፡፡ ዝርዝሩ ምናብ ነው፡፡ ጥቂት የሚታወሱ ነጥቦች አንስተህ እነዚያን ሚዛን በመጠበቅ የማያያዝና ጊዜ - ዘላይ ጭብጥ የማስነከስ ነው፡፡ ከልጅነቴ አርባ አመታት እርቄአለሁ በሚል ስለ ልጅነት ልብወለድ የመፃፍ መብቴን አላነሳም፡፡ የተወለድኩት አዋሳ ነው፣ አዲስ አባ መጥቼ ለምን ስለ አዋሳ እፅፋለሁ? ብዬ በቦታ መሸጋሸግን ወሳኝ አላደርግም (በአገር ውስጥ ስደት)፡፡ ይሄን መሰረታዊ ነጥብ ሃያሲው ከሳተ የቀረበው ትችት ሳይሆን ስህተት ፍለጋ ነው፡፡ የልጅነታችን ቦታዎችና ጊዜዎች ኢትዮጵያ ውስጥ እንኩዋን ብንሆን ሁሉንም ትተናቸው ሄደናል፡፡ ሁሉም ደራሲ ላለፈው ዘመንም ይሁን ቦታ/ስፍራ በሆነ ደረጃና መልክ ባዕድ ነው፡፡ ቦታዎችም እንደ ሰው ይለወጣሉ፡፡ እንደ ደራሲው እንደ ራሱ እና እንደ ገፀባህርያት፡፡ ልበወለድ ዶክመንታሪ አይደለም፡፡

ስለግንዛቤውና አፃፃፉ
የተወሳሰቡ ልምዶች አሳልፌአለሁ፡፡ በእኔ የተፈጠሩ ወይም በሌሎች ተየሰጡኝ፡፡ (ምርቃትም ይሁን እርግማን) አስከፊም ይሁን ደስ የሚሉ፡፡ እነዚህን ልዘረዘርልህ አልችልም፡፡ ብዙም ናቸው፤ ጥቂትም ናቸው፡፡
በባህርዬ በደንብ አያለሁ፡፡ አድልዖ አላደርግም፡፡ ይሄ ሁኔታዎች በነፃነት ለእኔ እንዲከሰቱ ያደርጋል፡፡ በጣም የሚሞቅ ፀሐያማ ቀን ባልወድም ፀሐይ ውስጥ እቆማለሁ፣ አለመውደዴን አጠናለሁ፡፡ እሱንም አወጣና አወርደዋለሁ፡፡ የሆነ የዜን ዝንባሌ (zen attitude) እይዛለሁ፡፡ ያለ ይሉኝታ (ምን መሆኔ ነው? ሰዎች ምን ይሉኛል?) ሳልል ለማየው ህያው ወይም ጎፍ (physical) አለም ራሴን በመስጠት ነው፡፡
ቅን መሆን አለብህ፡፡ ይሄን ደሞ አስበህ አታመጣውም (የሚያደርጉትይኖራሉ፡፡) ጥንቁቅ አይደለሁም፡፡ ዕቅድ የለህም፡፡ መረጃዎችን ብቻቸውን ሳይ (መገንዘገብ) ከፍፁም ግንኙነት አርቃቸዋለሁ ማለትም አይደለም፡፡ ያኔውኑ በፍጥነት ሊከሰትባቸው የሚችሉ አውታሮችን አስባለሁ፣ ወይም በትካቴ ይመጣሉ፡፡ በቀለ የተባለ ረዥም ልጅ ስልክ እንጨት ሊያስታውሰኝ ይችላል፡፡ ስልክ እንጨቱን ሳይ በቀለ ትዝ ሊለኝ ይችላል፡፡ አልማዝን ሳይ ቄጤማ ትዝ ሊለኝ ይችላል፡፡ የትርሲትን ድምፅ ስሰማ ሚጥሚጣ፣ ቁሶቹን ሳይ ደሞ አልማዝና ትርሲት፡፡ ዝርው የመሰለው ነገር በተለዋጭና በንፅፅር ስርአት ውስጥ ይገባል፡፡ ነጠላነትና ውህድነት በአያዎነት ይተገበራሉ፡፡ የመገንዘብ አድልኦ (Cognitive bias) ብዙ ነገር የመፃፍ ግላዊ ነፃነትህን ሊጋፋ ይችላል፡፡ በእኛ አገር ያልተነገረለት ሳንሱር ይሄ ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ ወሳኝም ይሆናል፡፡
እነዚህ በእንግሊዘኛው ተሳፋሪነት (bandwagon effect) ፣ የጥማድ ህልዮ (group think) የጂም ባህርይ (herd behavior) ፣ ምናምን የሚባሉ ናቸው፡፡
ይሄ ወደ ስሜት ህዋስ አድልዖ (observational bias) ወይም የፅንሰ ሃሳብ አድልዖ (Conceptual bias) ይወስዳል፡፡ ብዙ ሰው ስለሚያደርገው ላድርገው ብዬ ማድረግ፣ ያለ ዝርዝር ብቆታ መርጬ ማየት፣ እኔ ነገሩ ገብቶኛል ብዬ ከመጀመሪያው የማየውን ነገርና የምሰማውን ወስኜ በራሴም ይሁን በሌሎች ትርጓሜ መጥኜ ማስቀመጥና የግል/የቡድን እሴቴን ወይም ሕልዮዬን የማየው/የምገነዘበው/ ጉዳይና ነገር ላይ በጫና ማሸጋገር ከእውነታው ስለሚያሸሹኝ አልጠለልባቸውም፡፡
ሁሉ ነገር ለደራሲ መረጃ ነው፡፡ መረጃ ስል በተጨባጭ የማየው (በራሴ የስሜት ህዋሶች)፣ ከሰው የምሰማው፣ የማነበው፣ በህልሜ የማየው፣ የምቃዠው ሊሆን ይችላል፡፡ ለእኔ ክብደትና መራሂነት ያለው የመጀመሪያው ነው፡፡ አንዳንድ የመረጃ አንኩዋሮች ጥቅጥቅ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ እሴታቸው ቸኩሎ ላይከሰት ይችላል፡፡ ዛሬ ያነጫነጨኝ ልምድ ነገ ሊያስቀኝ ይችላል፡፡ ትናንት አደገኛ ያልመሰለህ ልምድ ቆይቶ አደገኛነቱ ይከሰታል፡፡ ዛሬ አደገኛ የመሰለ ልምድ ነገ ምቹ ሊሆን ይችላል፡፡ የአንዳንዱ ተራ የመሰለ ተፅዕኖ ወደ ድንጋግ የለሽ (ዳርቻ የለሽ) መረጃ ሊፈነዳ ይችላል፡፡ የማደርገው ከፈነዳ በሁዋላ የተበታተኑ የኩነት ፍንጣሪዎችን ወይም ዛላዎችን በማያያዝ መስራት ነው፡፡ …

ቅርፅና ይዘትን በተመለከተ
ዘመናዊ ደራሲዎች በየትም አገር በተለያየ መልክ የአገራቸውን የጥንት ተረቶች ለድርሰቶቻቸው ቅርፅና ይዘት መስሪያ ተጠቅመውባቸዋል፡፡ ይሄ መሸጋገር (translation) ብዙ ጊዜ ግን ከትረካ ወደ ትረካ ነው፡፡ ከድርሳን ወደ ድርሳን ነው፡፡ ከተረት ወደ ተረት ነው፡፡
“ግራጫ ቃጭሎች” የተባለው የመጀመሪያ ልብወለድ እዚህ ይመጣል፡፡ ይሄ መጽሐፍ ዋናውን ታሪክ በሚያጅቡ ንዑስ ታሪኮች በህዳግ ማስታወሻዎች፣ በቁርጥራጭ መረጃዎች፣ በአንዳንድ  የቁዘማ ውጤቶች አጀብ የተሰራ ነው፡፡ ይሄ ቅርፅን ለማደን መጣር አይደለም፡፡ ሁልጊዜ በደቡላወዊ (dualistic) ስልት ስለምናስብ እንጂ፣ ቅርፅና ይዘት የተናጠል ቦታ የላቸውም፡፡ እዚያና እዚህ አይደሉም፡፡
አንድ ላይ የሚተገበሩ ናቸው፡፡ በፍልስፍናም ይሁን ሃይማኖቶቻችን በምድራሶቻቸው (hermeneutics) ሁልጊዜ ባለቤትና ተሳቢ (Subject – object) ክፍፍል ላይ ስለሚያተኩሩ ከዚያ የተበደርነው ይሆናል፡ እንጀራ ጠንካራ የልዋጭነት እሴት አለው (metaphorical value)፡፡ ለመፃፊያ ሞዴልነት ለመጠቀም ይመቻል፡፡
ሞዴል ሲደረግ ከእንጀራነት ይላቀቅና ንፁህ ጂኦሜትሪ ይሆናል፡ ብዙ ጊዜ ሞዴሎች ከሚያጠኑት ጉዳይ የበለጠ ወይም የሚስተካከል ውስብስብነት ይኖራቸውና ራሳቸው መልሰው ችግር ይሆናሉ፡፡ እንጀራ እንደ ሞዴል የቀላልነቱ ምክንያቶች እነዚህ ናቸው፡፡
1/እንጀራ የተሟላ አይነት ውክልና አለው፡፡ ይታያል (እንደ ስዕል)፣ ይነካል፣ ይቀመሳል፣ እናም ይበላል፡፡ የመጨረሻው ፀባዩ የተለየ ያደርገዋል፡፡ እንደ ብዙ ቁሳቁስ በሩቅ የሚታይ አይደለም፡፡ ከሳብጀክቱ (የሰው ልጅ) ጋር ይዋሃዳል (embodied)፡፡
2/ የትውስታም ሰሌዳ ነው፡፡ አርኪዮሎጂስቶች በጥንት ጊዜ የተሰራ ቁስ አግኝተው በመሳሪያቸው መርምረው የእነዚህን ቁሶች ምንነታቸውን ያነባሉ፡፡ ተፎካካሪ ወይም የሚጋጭ ትርጉም ቢሰጣቸውም መረጃ ይሆናሉ፡፡ አፄ ሰንደቅአላማ የፈጠረው ጤፍ ተፎካካሪዎች የሚሻሙበት ጽላት (Icon) ነው፡፡ እንጀራ በሆነ መልክ ወገናዊነትን ያመልጣል፡፡ ተፎካካሪዎች ሁለቱም ይሽቱታል፡፡ በልቶ የማያድር የለም፡፡ የድንጋይ ላይ ጽሑፎች ሲጠፉ፣ ሲቃጠሉ፣ ሲዘረፉ፣ ከቦታ ቦታ ተላልፈው ሲጠፉ፣ እንጀራን ማንም ሊያሸሸው ባለመቻሉ እዚህ ደርሷል፡፡ ብዙ ዘመን የኖረው ሰንደቅአላማ መቃብር ላይ መገኘቱ ረዥም ዕድሜ ከእሱ መዋሱ ምሳሌ ይሆን?
በአሁኑ ወቅት ለምሰራው ስራ መረጃ ስለምፈልግ ብዙ ጊዜ ኢንተርኔት ላይ ነበርኩ፡፡ የግጥም ባሕር፣ የመጣጥፍ ሃይቅ በዛ አለ፡፡ ፌስ ቡክ በመጠቀም ብቸኛ ደራሲ መሆኔን አንተ ነህ የነገርከኝ፡፡ “ፍሬንዶች” ለሚያቀርቡልኝ አንዳንድ ጥያቄዎች መልስ ለመስጠት ግን ብዙ ጊዜ አረፍዳለሁ፡፡ ከእኔ ይልቅ የአገራችንን ስነፅሁፍ ወደ መርበትብተ - ኤሌክትሮኒክ ያመጡት ወጣቶች ሊመሰገኑ ይገባል፡፡ የእነሱ የድርጊት ሕልውና ስለሚቀድም ልፋታቸው የገነነ ነው፡፡ ስለ ራሴም እንዳውቅ ገፋፍተውኛል፡፡ ልክ እንደ ጠንቋይ፣ ደራሲ ስለራሱ አያውቅም፡፡
ምናልባት ወጣቶቹ የበዙት ደራሲያን ማንሳት ይገባቸዋል የሚሏቸውን እስከ ዛሬ የተሳቱ ጉዳዮች ስላነሳሁ ይሆናል፤ ወይም ገና ወጣትነቴ አልከሰመምና (እስከ አሁን ድረስ ከምኑም ከምኑም እየተላተመ መጥቶ ከተረፈ፣ በተአብነት ይመዘገባል) እኔን የሚመዘምዘኝ ጉዳይ እነሱንም ይመዘምዝ ይሆናል፡፡ እነዚህ ግምቶቼ ናቸው፡፡ በግምት ደግሞ እርቀት አይኬድም፡፡

ስለአስገራሚ ገጠመኙ
በብዙ ነገር ተገርሜ የጨረስኩ ይመስለኛል፡፡ ድሮ የገረሙኝ ነገሮችን ዛሬ ሳስባቸው ለዛሬ አስገራሚ ሆነው አይታዩኝም፡፡ የሚያስቅ? ሎል (lol) ከመጣች ጀምሮ መንተክተክ ሳይቀንስ አልቀረም? (ለማሾፍ ይፈቀድልኛል?)  

Published in ጥበብ

የኢትዮጵያ የንግድ ዘርፍ ማህበራት ምክት ቤት ዘንድሮ ለሰባተኛ ጊዜ የሚያካሂደው “የኢትዮጵያን ይግዙ” ዓለም አቀፍ የንግድ ትርኢት ሊካሄድ ነው፡፡ የንግድ ትርኢቱ ከጥቅምት 27 እስከ ህዳር 3 ቀን 2007 ዓ.ም በኤግዚቢሽን ማዕከል እንደሚቆይም የኢትዮጵያ የንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ዋና ፀሐፊ አቶ የሻው ደበበ በሰጡት መግለጫ አስታውቀዋል፡፡
በንግድ ትርኢቱ 161 የአገር ውስጥና ከ34 በላይ የውጭ ኩባንያዎች እንደሚሳተፉም ዋና ፀሐፊው ጨምረው ገልፀዋል፡፡ በዚህ ዓለም አቀፍ የንግድ ትርዒት ላይ ጃፓን፣ ቱርክ፣ ሱዳን፣ ቻይና እና ሌሎች ከአስር አገሮች የተውጣጡ አምራችና አገልግሎት ሰጪ ኩባንያዎች የሚሳተፉ ሲሆን ዘንድሮ ተሳታፊ የውጭ ኩባንያዎች ከአምናው የ60 በመቶ ጭማሪ ማሳየታቸው ተገልጿል፡፡
በዘንድሮው ኢትዮ ቻምበር የንግድ ትርዒት በተለይ አዳዲስና ለግብርናና ኢንዱስትሪ ዘርፍ አጋዥና ጠቃሚ የፈጠራ ውጤቶችን የሰሩ 15 ያህል ወጣቶች ያለ ምንም ክፍያ ምርቶቻቸውን እንደሚያስተዋውቁና የገበያ እድል እንዲያኙ ሁኔታዎች ተመቻችተዋል ብለዋል፤ ዋና ፀሐፊው በመግለጫቸው፡፡
ኢትዮጵያዊያን የአገራቸው የምርት ሁኔታ ምን ደረጃ ላይ እንደደረሰ እንዲጐበኙና የጐበኚውን ቁጥር ለማብዛትም ሲባል የንግድ ትርዒቱ በነፃ እንዲጐበኝ መደረጉም የዘንድሮውን የኢትዮ ቻምበር የንግድ ትርዒት ለየት ያደርገዋል ተብሏል፡፡ምክር ቤቱ ከዚህ በተጨማሪ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ካልሆኑ ድርጅቶች፣ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲና ከዩኒቲ ዩኒቨርስቲ እንዲሁም ከሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት የተውጣጡ ተማሪዎችና ሰራተኞች ትርኢቱን እንዲጐበኙ ፕሮግራም መያዙም ተብራርቷል፡፡ ኤግዚቢሽኑ በም/ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የኢኮኖሚ ክላስተር አስተባባሪና የኢንፎርሜሽን ኮሚዩኒኬሽን ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በሆኑት በዶክተር ደብረፅዮን ገ/ማሪያም እንደሚከፈት ለማወቅ ተችሏል፡፡ በንግድ ትርዒቱ ላይ ለተሳተፉ ኩባንያዎች ህዳር 3 በሂልተን ሆቴል የሚካሄድ የአቻ ለአቻ ውይይት የተዘጋጀላቸው ሲሆን ትርኢቱን በጥሩ ሁኔታ ያቀረቡ ኩባንያዎች መርጠው ሽልማት ይበረከትላቸዋል ተብሏል፡፡
ህብረተሰቡ እየተዝናና ትርዒቱን እንዲጐበኝም የፋሽን ትርዒት፣ የሙዚቃ ድግስና ሌሎች አዝናኝ ዝግጅቶች እንደሚኖሩ የምክር ቤቱ ኃላፊዎች ገልፀዋል፡፡

         የዛሬው ጉዞዬን እጅግ ልዩ የሚያደርገው ከአዲስ አበባ ደብረዘይት ለመሄድ 4 ሰዓት ተኩል መፍጀቱ ነው፡፡
በተለይ አዲሱ፣ ፈጣኑ የአዲሳባ - ናዝሬት/አዳማ መንገድ ከተሠራ በኋላ ይሄን ማሰብ በአያሌው ያስደምማል፡፡ ይሄ ለምን ሆነ?
ከኢየሩሣሌም ህፃናትና ሕብረተሰብ ልማት ድርጅት ጋር ወደ ደብረዘይት ለመሄድ የተቃጠርነው ሲአርዲኤ ፊት ለፊት - ከመኪና ማሰልጠኛው ማዶ ነው፡፡ እኔ አንድ ሰዓት ደርሻለሁ፡፡
ለወትሮው ቀድመው የሚጠብቁኝ የድርጅቱ መኪናዎች ዛሬ አይታዩም፡፡ ደቂቃዎች ሲገፉ “ቀጠሮውን የሰጠችኝ የድርጅቱ ህዝብ ግንኙነት ልጅ ቦታ ወይም ሰዓት ተሳስቷት ይሆን?” አልኩኝ፡፡ ትንሽ ልታገስ ብዬ የመታገሻዬን አረፍ የምልበት ቦታ በዓይኔ ማትሬ አንድ ሻይ ቤት መሣይ ቤት ጐራ አልኩኝ - እዚያው መንገዱ ዳር፡፡ ፓስቲና ብስኩት (ጃፓን) አዘዝኩ፡፡ ቅርፁ ከኔ ዘመን ፓስቲና ብስኩት የተለየ ሆኗል፡፡ ዋጋውማ የትና የት፡፡ ያም ሆኖ ፓስቲና ብስኩት ሳይ የተነጠቀ ልጅነቴን ያስመለስኩ ስለሚመስለኝ አንዳች ያሸናፊነት ስሜት ይሰማኛል፡፡ በከፊል ዐይኔ ከአስፋልቱ ዳር የሚቆሙትን መኪኖች እየማተርኩ፣ በከፊል ዐይኔ ፓስቲ - ብስኩቴን እጠብቃለሁ፡፡ (“ፓስቲ - ብስኩት” ያልኩት ዛሬ ብስኩት ሲባል በተለይ ያሁኖቹ ልጆች የፋብሪካው ብስኩት እንዳይታያቸው ከመስጋት ነው) ብስኩቴን እየኮረሸምኩ በላስቲክ ውሃ እያማግሁ ቁርሴን በላሁ፡፡ አሁንም መኪናው እንዳልመጣ ሳውቅ ስጋት ገባኝ - አንዳንድ አደጋ አጋጥሞስ ቢሆን ብዬ፡፡
ስለዚህ ደወልኩ፡፡ የደወልኩት ሰው አጣርቶ እንደሚደውልልኝ ነገረኝ፡፡ ቆይታ፤ ከፕሮግራሙ ያገናኘችኝ ልጅ “የትራፊክ jam (ጭንቅንቅ) ስለሆነ ነው - ሦስት መኪናዎች በተለያየ አቅጣጫ ወጥተዋል - ቀድሞ የደረሰ ይወስድሃል” አለኝ፡፡ መጠበቄን ቀጠልኩ፡፡ ብዙ በዙሪያዬ ያለው ሰው መኪና መጠበቅ እንዳይሰለቸው ይመስለኛል ከፊሉ ሞባይል ይጠቀጥቃል፣ ከፊሉ የግል ወሬ ያወራል፣ ከፊሉ ሰርቪስ ጠባቂ ስለሆነ አሥር አሥሬ ሰዓቱን ያያል፡፡ አብዛኛው አውቶብስ ጠባቂ ግር ብሎ እጁን ወደ ትኬት ቆራጯ ይሰቅላል - አሁንም ግን የእኔ መኪና አልመጣም፡፡
“አንዳንድ ቀን አለ፣
አንዳንድ ቀን አለ፣
ኮረኮንች የበዛው ሊሾ እየመሰለ”
የሚለው ግጥሜ ውል አለኝ፡፡ በራስ ግጥም መትጋት ያጋጥማል አልፎ - አልፎ አንዳንድ ሰዓት ጐታታ ነው፡፡ የዛሬው ሰዓት ግን ሌላ ቃል ሊፈጠርለት ይገባል፡፡ “ቀኝ ኋላ ዙር የተባለ ሰዓት” ይመስለኛል፡፡
ከቀኝ ኋላ ዙር ኋላ የእኛ መኪና መጣ፡፡ ተደወለልኝ፡፡ እፎይ ብዬ ገባሁ፡፡ የማላውቃቸውን አብሮ - ተጓዦቼን ተዋወቅሁ፡፡ ሶስት ሴቶች ስድስት ወንዶች ሆንን፡፡ መንገዱ ተጀመረ፡፡ ጥቂት እንደሄድን የጭቃ ጅራፉ መጣ! - ለምን እንደሆነ በማናውቀው ምክንያት የመኪና ሰልፍና ጭንቅንቅ ተጀመረ፡፡ እኛ መኪና ውስጥ ያሉት የሥራ ኃላፊዎች የደብረዘይቱን የኢህማልድ ማዕከልን የሥራ እንቅስቃሴ በስልክ አመራር ሊሰጡ ይሞክራሉ፡፡ “መኪናዎቹ አይንቀሳቀሱም፡፡ በአራትም ከደረስን መልካም ነው” አለ አንደኛው፡፡ ከደብረዘይት የሚያናግረን ሰው “አቃቂ አካባቢ የመኪና አደጋ ደርሶ ነው - አንድ የኛ መኪናም በመከራ ነው እዚህ የደረሰው” አለ፡፡ አሁን ዳር - ዳሩ ገባን፡፡ እንግዲህ መንገድ የዘጋ መኪና/መኪኖች ቢኖሩ ነው፡፡ በተለምዶ በፈረንጆቹ አጠራር Bottle-neck (የጠርሙስ - አንገት ማነቆ) እንደሚባለው ቃሊቲ ክራውን ሆቴል አካባቢ የመኪናዎች “ስክ” ይመስላል፡፡ (“ስክ” ማለት እሥር ቤት ሆነን እግር - ከአንገት ተቃቅፈን የምንተኛበት የቦታ ቁጠባ ሥርዓት ነው፡፡ ድንገት ቃሉ ባርቆብኝ ነው!) ሁሉም ተጓዥ ለሁለት ሰዓት የታቀደውን ፕሮግራም ከአዕምሮው መደምሰስ ይዟል፡፡
አንደኛው - “ስድስትም ብንገባ ደግ ነው” ይላል፡፡
“ፕሮግራሙን ወደ ከሰዓት ሺፍት እናድርገው በለው” ይላል የሥራ ኃላፊው
ሌላው - ኋላ ወደቀረው መኪና ሲደውል “ገና ቦሌ ተቀርቅረናል” አለው ያኛው፡፡
“ሌላ መንገድ ነበርኮ በሲኤምሲ ተገብቶ በደብረዘይት አትክልት መሸጫ የሚያወጣ - ወደኋላ ተመልሰው - ይሂዱ” አለ አንዱ አብሮ ተጓዥ፡፡
ሌላው - “ካለ ጥሩ ነው፡፡ ግን ከቦሌው ሰልፍ እንዴት ወደኋላ ይወጣል?”
ለላዋ - “ንቅንቅ አይሉም”
ይሄ ሁሉ ሲወራ መኪናው አንድ ጋት ነው ፈቀቅ የሚለው፡፡  
አሁን ጭራሽ ከወዳኛው የመኪና አቅጣጫ እየዘለለ ወደኛ መስመር እየበረከተ የሚረባው መኪና እየጨመረ መጣ፡፡
ይሄኔ አንዱ ከእኛ ጋር ያለ - ኢኮኖሚስታዊ አስተያየት ሰነዘረ፡-
“የመስመሩን ሰልፍ ርዝመት ታዩታላችሁ፤ ጫፉ አይታይምኮ!...ይገርማችኋል - ይሄ ስንት ኪሣራ እንደሚያስከትል አስቡ - የነዳጅ - የፍሬሲዮን - የጊዜ - የሥራ ቦታ፤ በአስቸኳይ - ድረስ የተባለ - የሞራል - ስንት የኢኮኖሚ ነገር ባንድ መኪና መገልበጥ ደረሰ!”
ሌላው - “ዱሮም እኛ አገር ችግር የሚመጣው በአንድ ሰው ምክንያት ነው” አለ፡፡
ሌላው - “በአንድ ሰው መገልበጥ ማለትህ ነው?!” ሁሉም ሳቀ፡፡ መኪናዎቹ በሰልፍ ተኝተዋል፡፡
ጥቂት ተንቀሳቀስን፡፡ አሁን የተገለበጠ መኪና አየን፡- ሲኖ - ትራክ” - ቀይ - አሸዋ የጫነ፡፡ በእኛ መስመር አንድ መኪናውን ያነሳል የተባለ ክሬን (ሸበል) አለ፡፡ ስለዚህ ከደብረዘይት መምጫውም ወደዚየ መሄጃውም ተዘግቷል ማለት ነው፡፡ ግራ - የተጋባ ሁኔታ ነው፡፡ አንድ መኪና ጠቅላላ የተጓዥ መኪኖችን ሰንሰለት ከወዲህም ከወዲያም ዘግቶ ማስቆሙ ይገርማል፡፡ ባንድ መኪና ጦስ አዲሳባም፣ ቃሊቲም፣ አቃቂም፣ ደብዘረይትም ቆመዋል፡፡ ተኝተዋል፡፡ ግን ለውጥ እናመጣለን መቼም! አጋዥ መኪና ይምጣ ብንል በየት ይመጣል? በሂሊከፐ‹ተርም ቢሆን ዘግነን ማንሳት አለብን! አማራጭ መንገድ የለም፡፡
ወዲያው አስቂኝ ነገር አየን፡፡ መኪና አንሺው መኪና ቀጭን ሽቦ ገመድ ልኮ አሸዋ ጭኒ የተገለበጠውን ከባድ መኪና ሊያነሳው ሲፍጨረጨር ሰው በሳቅ ሞተ! የሆነ አንበጣ የወደቀ ዝሆን ሊያነሳ የሚንፈራፈር ነው የሚመስለው፡፡ ወይም ሣር እግጣለሁ ብላ የኋላ እግሯ ብድግ አለ የተባለችው ኮሳሳ በግ ታሪክ፡፡ በመጨረሻ አንበጣው ዝሆኑን ትቶ ራሱን ከመንገዱ አወጣ፡፡
ከዚህ ቀጥሎ እንግዲህ በተለቀቀው መንገድ መኪና ለመኪና እየተሻሸ፣ መስመር በሚስተውና ደንቃራ በሚሆነው፣ በስግብግቡ፣ በቁጠኛው ወዘተ ላይ እርስበርስ እየተነጫነጨ…በመከራ አዲሱ የናዝሬት ፈጣን መንገድ ማዞሪያ ደረስን፡፡ በዘመናዊው የናዝሬት መንገድ በአየር የመንሳፈፍ ያህል ፈሰስን፡፡
ደብረዘይት ስንደርስ 4 ሰዓት ተኩል እንደደረስን ልብ አልን፡፡ ወደ ደብረዘይት ከተጠመዘዝን በኋላ የተገለበጡ መኪኖች አየን፡፡ የሚያስደነግጥ አገለባብጥ አይተናል - ከማማተብ በስተቀር ምን ይደረጋል? አማትበን አለፍን! በእኔ አታድርሰው ነው -ያበሻ ፀሎት1
የድርጅቱ ሥራ አስኪያጅ ቀድመውናል፡፡ ቀድመውን ከደረሱ የየማህበራቱ አባላት አስተዋወቁን
“ይሄው ጠዋት የወጣን መከራ ስናይ ውለን መጣን” አሉ ለሰው፡፡ ለሸገሩ ልጅ ዘወር ብለው - ያ የምታየው ምግብ ቤት ነው - ማሰልጠኛ ክፍሎች - ሰፊ ጊቢ Guest house የእንግዳ ማረፊያም አለው እናስጐበኝሃለን”
ኮረምብታው አናት ላይ አንገቱን አስግጐ በግርማ ሞገስ የቆመውንና ቁልቁል ወደ ደብረ ዘይት ሐይቆች የሚያስተውለውን ይሄን እንግዳ መቀበያ መንገድ ላይ ስንወያይበት ነበር፡፡
“አሪፍ ቪው አለው” አልኩኝ እኔ፡፡
“ቪዥንም አለው” አለ የሥራ ኃላፊው፡፡
“ቪክትሪ ነዋ የቀረው!” አልኩኝ እኔ፡፡
“Three “V” s አለች እየሳቀች አንደኛዋ የሥራ ባልደረባ፡፡ (ተሳሳቅን)
እጃችንን ታጥበን ቁርስ ወዳለበት ሄድን፡፡ አሁን እንግዲህ ከዚህ ቀደም የተረኩላችሁን የአዋሳ፣ የድሬዳዋ፣ የደብረብርሃን የእየሩሣሌም ልማት ድርጅት ኃላፊዎች ማግኘት ጀመርኩኝ፡፡
የአዋሳው ኃላፊ ለመስቀል በኢቢስ ስለተላለፈው ፕሮግራም እና እኔን ግጥም ስለማየቱ አድናቆቱን እየነገረንና ለሥራ አስኪያጁ እያብራራለት ወደመሰብሰቢያው አዳራሽ አመራን፡፡ ከሥራ አስኪያጁ ጋር እንደተለመደው በአበሻ ቴራፒ “ጠፋህ - ጠፋህ” እየተባባልን ከንፈር እየመጠጥን አዳራሹ ደጃፍ ደረስን፡፡ እግረ - መንገዱን የናዝሬቱን ልጅ የደብረዘይቱን የጄክዶ ተጠሪ አግኝቼ ስለ ናዝሬት በቅንጫቢ አወራን፡፡
ቀጥሎ ወደ አዳራሽ ከመግባታችን በፊት የዛሬውን ፕሮግራም ዓላማ በአጭሩ ንገረኝ አልኩት፡፡ የዛሬው ፕሮግራም 3 ዓላማዎች አሉት
1ኛው የእየሩሳሌም ህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ድርጅት ከጃክዶ ሲዳና ከጃክዶ ኤልማ በተገኘ ድጋፍ የአቅም ግንባታ ፕሮግራም 40 ከሚሆኑ የማህበራት ምሥርት ድርጅቶች ጋራ የሚያደርገው ስምምነት፡፡
2ኛው/ ድርጅቶቹን ማስተዋወቅ እርስ በርስ የሚደጋገፉበትን ሁኔታ እንዲፈጥሩ
3ኛው/ የሚሠሩበትን ሁኔታ ግንዛቤ ማስጨበጥ!!
(ይቀጥላል)

Published in ህብረተሰብ

         ብሩክ ኢትዮጵያ በደቡብ ብሄር ብሄረሰቦችና ህዝቦች ክልል በሃላባ ልዩ ወረዳ በ1 ነጥብ 8 ሚሊዮን ብር ወጪ ያስገነባቸውን የሃላባ ቁሊቶ ከተማና አካባቢው የጋማ እንስሳት ደህንነት ጥበቃና ስልጠና ማዕከልና የጋማ እንስሳት ውሃ ማጠጫ ገንዳዎችን አስመረቀ፡፡
በርካታ የጋማ እንስሳት በሚስተናገዱበት በሃላባ ከተማ ዋና የገበያ ስፍራ ላይ የተገነባው ማዕከል፤ ከእንስሳት እንክብካቤ ጋር የተያያዘ ስልጠና ከመስጠት ባለፈ፣ እንስሳቱ ተገቢውን መኖና ውሃ እያገኙ በምቹ ሁኔታ የሚቆዩበት ሲሆን እንስሳቱን ከስርቆት በመከላከልና ከሚደርስባቸው ስቃይ በማዳን ረገድ ጠቀሜታው የጎላ እንደሆነ ተነግሯል፡፡
በልዩ ወረዳው ለሚገኙ የመንግስት ክሊኒኮችና የእንስሳት ህክምና መስጫ ማእከላት የአቅም ግንባታ ድጋፎችን የሚያደርገው ብሩክ ኢትዮጵያ የአካባቢውን የጋማ ከብቶች የጤና እንክብካቤ ለማሳደግ ከ1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ በቁሳቁስ፣ በመድሃኒትና በህክምና መሳሪያዎች ማሟላቱን የድርጅቱ ሃላፊ አቶ ጥበቡ ደበበ ተናግረዋል፡፡
ህክምናውን ለማሻሻል የእንስሳት ሀኪሞችንና የህብረተሰብ የእንስሳት ጤና ሰራተኞችን አቅም በስልጠና በዘላቂነት ከማጎልበትና ለህብረተሰቡ ግንዛቤ በማስጨበጥ የተሻሉ የጋማ ከብት አያያዝ ልማዶችን ከማዳበር ባሻገር፣ በልዩ ወረዳዋ በሚገኙ ክሊኒኮችና የጤና ኬላዎች አስተማማኝ የጋማ እንስሳት መድሃኒት አቅርቦት እንዲኖር ለማስቻል በ370 ሺህ ብር የመድሃኒትና የክትባት ተዘዋዋሪ በጀት አሰራር ቀይሶ እንደሚሰራም ገልጸዋል፡፡
በምረቃ ስነስርዓቱ ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የሃላባ ልዩ ወረዳ የመንግስት ተወካይ፤ አቶ መሐመድ ኑር ሳኒያ በወረዳው ያሉት ከ39 ሺህ በላይ የጋማ ከብቶች ለህብረተሰቡ ከፍተኛ አገልግሎት እየሰጡ እንደሚገኙ ጠቁመው፣ ይሄም ሆኖ ግን የጋማ እንስሳትን ጤንነትና ደህንነት ከማስጠበቅ አንጻር ችግሮች እንደነበሩ ገልጸዋል፡፡ “ብሩክ ኢትዮጵያ” በልዩ ወረዳው እያከናወናቸው የሚገኙ ስራዎች የአካባቢውን የጋማ ከብቶች ደህንነት ለማስጠበቅ ከፍተኛ እገዛ እንደሚያደርጉም ተናግረዋል፡፡
“ብሩክ ኢትዮጵያ” የተቀናጀ የጋማ ከብት ደህንነት ትብብር ፕሮግራም በደቡብ ብሄር ብሄረሰቦችና ህዝቦች ክልል ጉራጌ፣ ሃዲያ፣ ወላይታና ጋሞ ጎፋ ዞኖች እንዲሁም ከአማራ መልሶ ማቋቋምና ልማት ድርጅት ጋር በመተባበር በሰሜን ጎንደር ዞን ፕሮጀክቶችን ቀርጾ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል፡፡


Published in ህብረተሰብ

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ስሙኝማ…ሰውየው እንትናዬውን ‘ኢምፕሬስ’ ለማድረግ ምን ይላታል መሰላችሁ…  
“የኩላሊትና የጉበት ስፔሻሊስት ነኝ፡፡”
“ወይኔ ዕድሌ!  ግን እውነትህን ነው?”
“አዎ፣ በተለይ በኩላሊትና በጉበት ቀደዳ የሚደርስብኝ የለም፡፡”
እሷም የኩላሊትና የጉበት ስፔሻሊስት እንትና እንዳላት ታወራለች፡፡ በቃ… ምን አለፋችሁ… በጓደኞቿና በቤተሰብ አካባቢ ዓቢይ አጄንዳ ሆና ከረመች፡፡ ልክ ነዋ…እንዲህ በሰው ዘንድ የሚነገርላቸው በአሪፎቹ እንትናዬዎች ተጠልፈው… የተረፍነው ጋዜጠኞች፣ አርቲስቶች፣ አይነቶች ነና! ቂ…ቂ…ቂ… የምር ግን…ምን ይገርመኛል መሰላችሁ…እንዳለነው ጋዜጠኞችና አርቲስቶች ብዛት ሆሊዉድና እነ ‘ኒው ዮርክ ታይምስ’ና ‘ዋሺንግተን ፖስት’ እዚህ አለመቋቋማቸው ግርም አይላችሁም! ኒኦ ሊበራሎች እንዲህ ነክሰው ይያዙን! ቂ…ቂ…ቂ…
ታዲያላችሁ… አንድ ቀን አጅሪት ከጓደኞቿ ጋር ቁርጥ ልትበላ ልኳንዳ ስትገባ ማንን ብታይ ጥሩ ነው…የኩላሊትና የጉበት ስፔሻሊስት ወዳጇን! ለካስ ሰውየው ‘ስፔሻላይዝ’ ያደረገው ሉካንዳ ቤት ነው! አሀ… ከበሬው ኩላሊቱንና ጉበቱን ለይቶ ለማውጣትም ልዩ ሙያ ያስፈልጋላ!
እሷዬዋ እኮ ይሄኔ ለቤተሰቦቿ… “ከዘመዶቻችን ወይ የጉበት ካንሰር፣ ወይ የኩላሊት ኢንፌክሽን ያለበት ካለ አትጨነቁ፡፡ ለእኔ ንገሩኝ…” እያለች…ጉራ ነስንሳ ይሆናል!
ይቺን አሪፍ ታሪክ ስሙኝማ…ባልና ሚስቱ የገጠር ሰዎች ናቸው፡፡ እናላችሁ… ባል ቀኑን ሙሉ ከመሬት ጋር ሲታገል ነው የሚውለው፡፡ የሚያግዘው ሌላ ሰው ስለሌለ ሲወጣ ሲወርድ ማታ ቤቱ ሲገባ ‘ጨርቅ’ ሆኖ ነው የሚገባው፡፡ ሚስትም በበኩሏ ቤት ውስጥ ጉድ፣ ጉድ ማለቷ አልቀረም፡፡ ግን የባሏን ያህል አይደክማትም፡፡
እናማ… እራት ተበልቶ ወደ መኝታ ሲኬድ…አለ አይደል… ሁል ጊዜ ‘ነገርዬው’ አይቀርም፡፡ (እንደ ‘ዴዘርት’ በሉት! ቂ…ቂ…ቂ…) ኮሚኩ ነገር ምን መሰላችሁ…የአቅም ጉዳይ! እሱ ለራሱ ድክም ብሎታል… የእሷን ጉልበት እንዴት ይቻለው!
በማግስቱም እንዲሁ ይሆናል…በማግስቱም…በማግስቱም…፡፡ ሁልጊዜም ደግሞ ‘ግፊቱ’ የሚመጣው ከሚስት ነው፡፡ (ድሮ… “ወደህ ነው፣ በቀበሌ ተገደህ!” የሚሏት ነገር ነበረች፡፡) እናላችሁ… ምርር ይለዋል፡፡ ቢላት ቢሠራት ምንም ልትለወጥ አልቻለችም፡፡ በመጨረሻ ሽማግሌዎች ዘንድ ይሄዳሉ፡፡ ሲፈራ ሲቸርም ጉዳዩን (‘ከእነ ብጉሩ’) ይነግራቸዋል፡፡ ሽማግሌዎቹም ለሚስቱ ረጋ እንድትል ይመክሯታል፡፡ ‘ነገርዬው’ ውል ሲልባቸው አንዳቸው ለሌላኛው ምልክት እንዲሰጣጡ ይመክሯቸውና ይስማማሉ፡፡
ታዲያላችሁ… ሚስት ሆዬ ደግሞ በአንድ ሌሊት ደጋግሞ ‘ውል’ እያለባት መከራ ማብላቷን አልተወችውም፡፡ (እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…አንዳንድ እንትናዬዎች…‘ነገርዬውን’ ከደማችሁ የተዋሀደ ታስመስሉታላችሁ የሚባለው እውነት ነው እንዴ! ቢሆን ነው እንጂ!… አሀ… የ‘አፍ መፍቻ’ ቋንቋ አታስመስሉታ!)
ታዲያላችሁ…በመጨረሻ ድክም ሲለው እንደ ሶማሌ ተራ መኪና መቶ ትንንሽ ከመሆኑ በፊት ሳታየው ይጠፋል፡፡ ራቅ ባለ ስፍራ ወደሚገኘው የአጎቱ ቤት ሄዶ እዛው ይቀመጣል፡፡ ድካሙም እየቀለለው ሄደ፡፡
እናላችሁ… ጠዋት ወጥቶ መስኩን፣ ጋራውን ምናምኑን ሲያስተውል አንዲት ሴት ፍየል ወንዱን ፍየል ስታሳድደው ያያል፡፡ በማግስቱም እንዲሁ ታሳድደዋለች፡፡ ለብዙ ቀናት ሴቷ ፍየል ወንዱን እያሳደደች መከራውን ስታበላው ሲያይ ቆይቶ ምን ቢል ጥሩ ነው፣
“አንተ ፍየል፣ አጎት የለህም?”
እናላችሁ… “አንተ ፍየል፣ አጎት የለህም?” የሚያሰኙ ነገሮች ብዙ ናቸው፡፡ መቼም ምስኪኖች ላይ የማይበረታ የለም!
ይኸው ኑሮ ‘አጎት የሌለው ፍየል…’ እያደረገን ነው፡፡
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…በቃ እዚህ አገር ነገርዬው ሁሉ ዋጋው ሽቅብ ሲወጣ ጭጭ፣ ጭጭ ነው!
“ስድስትና ስምንት ብር ትሸጥ የነበረችው ቲማቲም በአቅሟ ሃያ ምናምን ብር ገባች…” — ጭጭ!
“መዳፍ ላይ ቁጭ ብላ እንኳን በደንብ የማትታይ ኪኒን ቢጤ ፉርኖ ብር ከሠላሳ…”— ጭጭ!    
“ሁለት ብር ከምናምን ትሸጥ የነበረች እንቁላል ሦስት ብር ከሠላሳ…”— ጭጭ!
እኔ የምለው…“ልክ አይደለም፡፡ ይሄ ግብይት ሳይሆን ቅልጥ ያለ ዘረፋ ነው!” የሚሉ የኤፍኤም ፕሮግራሞች እንኳን እንጣ! ቢያንስ፣ ቢያንስ የሆኑ ነገሮች ዋጋ ሲጨምሩ ማሳመኛ ምክንያት ቢነገረን እኮ አንድ ነገር ነበር!
እናላችሁ… ኑሮ ‘አጎት የሌለው ፍየል…’ እያደረገን ነው፡፡
የ‘ብር’ እና የ‘ወንበር’ ነገር ‘አጎት የሌለው ፍየል…’ እያደረገን ነው፡፡
ምን ግርም ይልሀል አትሉኝም… ሚጢጢ ስልጣን ቢጤ ሲሰጠን ደረትና ትከሻችን የሚሰፋው የምንወጋው መርፌ ነገር አለ እንዴ! “ሰላምተኛ፣ የዋህ፣ ቤተክርስትያን ሳሚ…” ምናምን እንባል የነበረን ሰዎች በአንድ ጊዜ ከሰው አልፈን፣ የምንረግጠውን መሬት እንኳን ከፍ ዝቅ አድርገን መገላመጥ እንጀምራለን፡፡ በትንሽ በትልቁ ስልጣናችንን ለማሳየት ሰዉን መከራ እናበላለን፡፡
ስሙኝማ… ከ‘ፍሬሽ’ ባለወንበር፣ ከ‘ፍሬሽ’ አፍቃሪ፣ ከ‘ፍሬሽ’ ‘ታዋቂ አርቲስት’፣ ከ‘ፍሬሽ’ ገጣሚ፣ ምናምን … ይሰውራችሁማ!
እናላችሁ…ቁጥራቸው ትንሽ የማይባል (‘መሸወጃ አነጋገር’ ልትሏት ትችላላችሁ…) ባለ ወንበሮች ‘አጎት የሌለው ፍየል…’ እያደረጉን ነው፡፡
ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…እግረ መንገዴን የሆነች ነገር ትዝ ብላኝ ነው፡፡ ያው ነጋ ጠባ…
“ስልጣኔያችን እየናረ ነው…”
“ኒው ዮርክ በቅናት ዓይኗ ቀልቷል…”
“ፓሪስ እኛን አይታ ተንገብግባለች…” ምናምን አይነት ቃና ያላቸው አባባሎች እየለመዱብን ነው፡፡ የምር ግን የባቡር ሃዲድ አሪፍ ነው፣ ግን… ‘የስልጣኔ ከፍተኛ መለኪያ’ ሲያስመስሉት አሪፍ አይደለም፡፡ አሀ…ባቡር ጦቢያችን ከገባ መቶ ምናምን ዓመት ገደማ ሆኖታላ!
ደግሞ…ባለብሮች ‘አጎት የሌለው ፍየል…’ እያደረጉን ነው፡፡
የብር ነገርማ ተዉት…መጀመሪያ ነገር ብሩ ሁሉ ‘‘ከየት እንደሚመጣ ግራ እየገባን ይኸው…አለ አይደል… እየተቁለጨለጭን አለን፡፡ እንደ ሰዋችን መዝናናት፣ እንደሚመዠረጠው ብርና ዶላር፣ እንደሚፈሰው ጎልድ ሌብል ምናምን… ግራ ቢገባን አይፈረድብንም፡፡
ታዲያላችሁ…ዋናው ነገር ባለብሮች (“አንዳንዶቹ…” “በርከት ያሉት…” ምናምን ማለት ይቻላል፡፡) እንዴት እንደሚሆኑ ስታዩ ታዝናላችሁ፡፡ ብር ስላለ ብቻ እኛንም ልክ እንደ ‘ግል ንብረታቸው’ የሚቆጥሩን ነው የሚመስለው፡፡
እናላችሁ…አገልግሎት መስጫ ስፍራዎች በሉት፣ መዝናኛ ስፍራዎች በሉት፣ በየአውራ ጎዳናው በሉት..አለ አይደል…ቅድሚያ እንድንሰጥ ይጠበቅብናል፡፡
ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…እነዚሀ የማታ ሰፈሮች አካባቢ… ‘ብር ተቆልሎ’ ነገር ሥራቸውን ያሳጣቸው ሰዎች ዶላሩን፣ ፓውንዱን፣ ዩሮውን እየመዘዙና እየከተቱ የሚያሳዩትን ባህሪ ስትሰሙ በጣም ታዝናላችሁ፡፡
አንዳንድ ጊዜ እኮ… “ጥጋብም፣ ረሀብም አይችሉም... የምንባለው ነገር…አለ አይደል ዝም ብሎ የተፈጠረ አይደለም ትላላችሁ፡፡
እናማ…ባለብሮች ‘አጎት የሌለው ፍየል…’ እያደረጉን ነው፡፡
ማንቼና አርሴ… ‘አጎት የሌለው ፍየል…’ እያደረጉን ነው፡፡ ቂ…ቂ…ቂ…
ብቻ…አለ አይደል…ዘንድሮ ብዙ ነገሮች ‘አጎት የሌለው ፍየል…’ እያደረጉን ስለሆነ የተሻለውን ነገር ያምጣልንማ!
ደህና ሰንብቱልኝማ!!    


Published in ባህል

ባለፉት 15 ዓመታት በዓለም የማራቶን ውድድሮች መድረክ  የምስራቅ አፍሪካ አገራት ከፍተኛ የበላይነት ሲያሳዩ ቆይተዋል፡፡ ከ5 ዓመታት ወዲህ ግን በተለይ የኬንያ ወንድ አትሌቶች ከኢትዮጵያውያኑ ከፍተኛ ብልጫ እያገኙ ናቸው፡፡ በአንፃሩ በማራቶን ከኬንያ አቻዎቻቸው በመፎካከር እየተሳካላቸው  የሚገኙት የኢትዮጵያ ሴት አትሌቶች ሆነዋል፡፡ የዓለም ማራቶን ሜጀር ሲሬዬስ አካል በሆኑ ትልልቅ ማራቶኖችና ሌሎች ውድድሮች እንዲሁም፤ በዓለም የማራቶን ፈጣን ሰዓቶች ደረጃ ሰንጠረዦች በአጠቃላይ ኬንያውያን በሁለቱም ፆታዎች  በውድድር ዘመኑ ከኢትዮጵያውያን የተሻለ ስኬት ነበራቸው፡፡ በተለይ በወንዶች ምድብ በማራቶን ውጤት የኬንያ አትሌቶች ከኢትዮጵያውያን ተቀናቃኞቻቸው ጋር ያላቸው ልዩነት እየሰፋ መጥቷል፡፡
በተያያዘ ነገ የኒውዮርክ ማራቶን በታሪኩ ለ44ኛ ጊዜ ሲደረግ በሁለቱም ፆታዎች ፉክክሩ በምስራቅ አፍሪካ አገራት አትሌቶች እንደሚወሰን ቢጠበቅም የተሻለውን ግምት ኬንያውያን ወስደዋል፡፡ የኒውዮርክ ማራቶን እስከ 51 ሺ ተሳታፊዎች ፤ እስከ 2 ሚሊዮን ተመልካቾች የሚያጅቡት ትልቅ ውድድር ነው፡፡ ከኢትዮጵያውያን ማራቶኒስቶች መካከል በኒውዮርክ ማራቶን በወንዶች ምድብ በ2010 እኤአ ላይ አሸናፊ የነበረው ገብሬ ገብረማርያም እና በሴቶች ምድብ ደግሞ ለሁለት ጊዜያት ያሸነፈችው ፍሬህይወት ዳዶ ይሳተፋሉ፡፡ በሌላ በኩል የ2013/14 የዓለም 6 ማራቶኖች ሜጀር ሲሪዬስ “ማራቶን ሊግ” የደረጃ ሰንጠረዥ በመሪነት አጠናቅው 1 ሚሊዮን ዶላር ሽልማትንየ ሚካፈሉት አትሌቶች በሁለቱም ፆታዎች ኬንያውያን ናቸው፡፡ የማራቶን ሊጉ ነገ በሚካሄደው የኒውዮርክ ማራቶን ሲያበቃ ሲሆን በተለይ በወንዶች ምድብ አሸናፊውን የሚለይ ነጥብ ሊመዘገብበት ይችላል፡፡ የዓለም ማራቶን ሪከርድ ዘንድሮ ያስመዘገበው ኬንያዊ ዴኒስ ኪሜቶ የማራቶን ሊጉን እየመራ ቢሆንም ፤ የማራቶን ሪከርዱ የተሰበረበት የተሰበረበት ዊልሰን ኪፕሳንግ በነገው የኒውዮርክ ማራቶንን ካሸነፈ የማራቶን ሊጉን በአንደኛነት በመጨረስ 500ሺ ዶላር የመሸለም እድል ይኖረዋል፡፡
ለነገሩ ከወር በፊት ከተካሄደው የቺካጎ ማራቶን በኋላ በ2013/14 የውድድር ዘመን የማራቶን ሊግ ፉክክር  በሁለቱም ፆታዎች ኬንያውያን ማሸነፋቸው የተረጋገጠ ይመስላል፡፡  በተለይ በሴቶች ምድብ የቺካጎ ማራቶንን ያሸነፈችው ኬንያዊቷ ሪታ ጄፕቶ በውድድር ዘመኑ የማራቶን ሊግ አሸናፊነቷን ያረጋገጠችው ከኒውዮርክ ማራቶን በፊት ነው፡፡  ኬንያዊቷ ሪታ ጄፕቶ በሴቶች ምድብ የማራቶን ሊጉን 100 ነጥብ በመምራቷ የ500ሺ ዶላር ሽልማት ትወስዳለች፡፡
በ2014 የዓለም ማራቶኖች በወንዶች ኬንያ፣ በሴቶች ኢትዮጵያ
በ2014 እኤአ ላይ ኢትዮጵያውያን ሴት አትሌቶች በርካታ የማራቶን ውድድሮችን አሸንፈዋል፡፡  ትልቁ ድል የተመዘገበው የዓመቱን ማራቶን ፈጣን ሰዓት ባስመዘገበችው እና የበርሊን ማራቶንንን ባሸነፈችው አትሌት ትርፌ ፀጋዬ ነው፡፡ የትርፌ ፀጋዬ የዓመቱ ፈጣን የማራቶን ሰዓት 2 ሰዓት ከ20 ደቂቃዎች ከ18 ሰከንዶች ሲሆን በበርሊን ማራቶን አሸናፊነቷ ያስመዘገበችው ነው፡፡ ይሁንና በለንደን ፤ በቺካጎ፤ በቦስተን እና በፓሪስ ማራቶኖች የኬንያ ሴት አትሌቶች የበላይነት ማሳየታቸው በማራቶን ሊጉ የደረጃ ሰንጠረዥ ከፍ አድርጓቸዋል፡፡ ኢትዮጵያውያኑ  ሴት አትሌቶች በማራቶን ሊጉ የደረጃ ሰንጠረዥ በየጣልቃው ኬንያውያንን ለመፎካከር የበቁት በማራቶን ሊግ ውድድሮች ባይሆንም በሌሎች በርካታ ማራቶኖች ከወንዶቹ ኢትዮጵያውያን በተሻለ ብዛት አሸፊና በመሆናቸው ነው፡፡  ኢትዮጵያውያኑ  ሴት አትሌቶች በበርሊን ማራቶን ተከታትለው መግባታቸው አንፀባራቂው ስኬተ ነው፡፡ በሌሎች በዓለም ዙርያ በተካሄዱ ውድድሮችም በተመሳሳይ ሁኔታ ብልጫ ለማሳየት አሸንፈዋል፡፡ ከእነሱም መካከል ማሬ ዲባባ የሻይናሜን ማራቶንን በቻይና፤ ትርፌ ፀጋዬ በየነ የቶኪዮ ማራቶንን በጃፓን ፤ ፍሬህይወት ዳዶ  የፕራግ ማራቶንን፤ ትእግስት ቱፋ የኦታዋ ማራቶንን በካናዳ ፤ ሙሉ ሰበቃ የዱባይ እና የዳጋኖ ማራቶኖችን በማከለኛው ምስራቅ እና በቻይና፤ አበበች አፈወርቅ የሂውስተን ማራቶንን በአሜሪካ፤ ማርታ ለማ  የሙምባይ ማራቶንን በህንድ፤ መስታወት ቱፋ የዶንግ ያንግ ማራቶንን በደቡብ ኮርያ እንዲሁም አማኔ ጎበና የሎስ አንጀለስ ማራቶንን በአሜሪካ ማሸነፋቸው ከሴት ማራቶኒስቶች አስደናቂ ስኬት የሚጠቀሱ ናቸው፡፡ ኢትዮጵያዊ ወንድ ማራቶኒስቶች በአንፃሩ በ2014 ብቻ ሳይሆን ባለፉት አምስት አመታት ውጤታቸው ከኬንያውያኑ በጣም አየራቀ እና እየወረደ መጥቷል፡፡ በዓመቱ ፈጣን ሰዓቶች ደረጃ ኢትዮጵያ ወንድ ማራቶኒስቶች በበላይነት በቅርብ ጊዜ የሚመለስ አይሆንም፡፡ እነዚህን ደረጃዎች የያዟቸው ኬንያውያን ናቸው፡፡ ከ6 የማራቶን ሊግ ውድድሮች አንዱንም ኢትዮጵያዊ አትሌት ሊያሸንፍ ያልቻለበት የውድድር ዘመንም ነበር፡፡
በኦል አትሌቲክስ ድረገፅ የ2014 ከፍተኛ ውጤት በማስላት በወጣ የደረጃ ሰንጠረዥ መሰረት በወንዶች ማራቶን አንደኛ ደረጃ የያዘችው በ3994 ነጥብ ኬንያ ናት፡፡ ኢትዮጵያ በ3901 ነጥብ፤ ጃፓን በ3618 ነጥብ ፖላንድ በ3523 ነጥብ እንዲሁም ኤርትራ በ3509 ነጥብ እስከ አምስት ያለውን ደረጃ አከታትለው ይወስዳሉ፡፡ በሴቶችም ኬንያ በ934 ነጥብ መሪ ናት፡፡ ኢትዮጵያ በ3910 ነጥብ ትከተላታለች፡፡ ጃፓን በ3629 አሜሪካ በ3576 እንዲሁም ጣሊያን በ3503 እስከ አምስት ያለውን ደረጃ ይወስዳሉ፡፡ በዚሁ ድረገፅ በቀረቡ አሃዛዊ መረጃዎች ለመንገዘብ የሚቻለው በዓመቱ ምርጥ የማራቶን ብቃት እና ፈጣን ሰዓት ሁለቱንም የመሪነት ስፍራዎች የተቆናጠጡት ኬንያውያን ናቸው፡፡ ሪታ ጄፔቶ እና ዴኒስ ኪሜቶ 1340 እና 1456 ነጥብ እንደየቅደም ተከተላቸው በማስመዝገብ ነው፡፡ በዚሁ ደረጃ በሴቶች ምድብ እስከ 20ኛ ባለው እርከን ኢትዮጵያውያን ቢያንስ ከስምንት በላይ ናቸው፡፡ በወንዶች ግን ያሉት ከ3 አይበልጡም፡፡
የኬንያ ወንድ አትሌቶች የበላይነት በርግጥም ከፓሪስ፤ ከበርሊን  እና ከቦስተን ማራቶኖች በኋላ ከወር በፊት በተደረገው የቺካጎ ማራቶንም በግልፅ ታይቷል፡፡  የቺካጎ ማራቶንን ያሸነፈው በረጅም ርቀት የትራክ ውድድሮች የቀነኒሳ ተፎካካሪ ሆኖ የቆየው ኬንያዊ ኤሊውድ ኪፕቾጌ ነበር፡፡ ኪፕቾጌ ወደ ማራቶን ፊቱን ካዞረ ወዲህ አራት ጊዜ ተወዳድሮ ለ3 ጊዜ በአንደኛነት መጨረሱ አስደንቋል፡፡ በቺካጎ ማራቶን ሲያሸንፍ ያስመዘገበው ሰዓት ደግሞ  2 ሰዓት ከ04 ደቂቃዎች ከ15 ሰከንዶች ነው፡፡ በሁለተኛ ደረጃ ሳሚ ኪርሞ በ2 ሰዓት 04 ከ18 እንዲሁም በሶስተኛ ደረጃ ዲክሰን ቺምቦ በ2 ሰዓት 04 25 በሆነ ጊዜ የጨረሱ ሌሎቹ የኬንያ አትሌቶች ናቸው፡፡ በወንዶች እስከ 10ኛ ባለው ደረጃ አንድ ኢትዮጵያዊ ብቻ ሲመዘገብ 7 ኬንያውያን ነበሩ፡፡ ያ ኢትዮጵያዊ ደግሞ ሁለተኛ የማራቶን ውድድር ለመሮጥ የበቃው አትሌት ቀነኒሳ በቀለ ነው፡፡ በቺካጎ ማራቶን ላይ ቀነኒሳ በ4ኛ ደረጃ ውድድሩን ያጠናቀቀ ሲሆን ሰዓቱ 2 ሰዓት ከ05 ደቂቃዎች ከ51 ሰከንዶች ነው፡፡ ቀነኒሳ በውድድሩ 2 ሰዓት ከ5 ደቂቃዎችን ርቀቱን ለመሸፈን በቻለበት ብቃት እንደረካ በወቅቱ ተናግሮ ነበር፡፡  የግሉን ፈጣን ሰዓት ለማስመዝገብ ከጅምሩ ማቀዱ አልቀረም ነበር፡፡ እንደውም ሌትስራን ድረገፅ እንደዘገበው ያቀደው ጊዜ  2 ሰዓት ከ3 ደቂቃዎች ከ13 ሰከንዶች ነው፡፡ በእርግጥ ከቀነኒሳ በፊት የነበሩት ታላቅ የረጅም ርቀት ሯጮች በመጀመርያ ሁለት የማራቶን ውድድራቸው ፖል ቴርጋት በ2 ሰዓት ከ08 ደቂቃዎች ሃይሌ ደግሞ 2 ሰዓት ከ06 ደቂቃዎች ነበር ያስመዘገቡት፡፡ እንደ ጆስ ሄርማንስ አስተያየት ቀነኒሳ በቀለ በቺካጎ ማራቶን በውድድሩ አይነት ለሁለተኛ ጊዜ የተሳተፈው ልምድ ለማዳበር እና ማራቶንን ለመማር ነው፡፡
የቺካጎ ማራቶን ከመካሄዱ በፊት ማራቶንን በ2 ሰዓት እና ከ2 ሰዓት በታች ይገባል ተብሎ የተጠየቀው አትሌት ቀነኒሳ በቀለ የሰው ልጅ ያን ያህል መፍጠን አይችልም በሚል መልስ ሰጥቷል፡፡‹‹ ምናልባት ወደፊት ማን ያውቃል ሳይንቲስቶች ልዩ የሰው ልጆች ካልፈጠሩ በቀር…›› ነው ያለው ቀነኒሳ፡፡ የአትሌቱ ማናጀር የሆኑት የ64 ዓመቱ ሆላንዳዊ ጆስ ሄርማንስ ግን በተቃራኒው በሰጡት አስተያየት‹‹ ቀስ በቀስ ማራቶንን ከ2 ሰዓት በታች እንደሚገባ አስባለሁ… ምናልባትም ከ20 ዓመታት በኋላ›› ብለዋል፡፡ ለጆስ ሄርማንስ ለዚህ ብቃት ዋና እጩ የተደረገው ራሱ አትሌት ቀነኒሳ በቀለ ነው፡፡ በማራቶን ስልጠናው እና ልምምዱ ላይ ስርነቀል መሻሻሎች እንደሚያስፈልጉ ጎን ለጎን አስረድተዋል፡፡‹‹ ብዙ ለውጦች ያስፈልጋሉ፡፡ በልምምድ፤ በህክምና ድጋፍ እና በጤንነት አጠባበቅ፤ በፊስዮቴራፒ ያሉትን ሁኔታዎች ማሻሻል ይገባል፡፡ በቀለ በጣም ተፈጥሯዊ ብቃት የታደለ አትሌት ነው፡፡ መልቲ ቫይታሚን ወስዶ እንኳን አያውቅም›› በማለት ጆስ ሄርማንስ በአትሌቱ ላይ ስላላቸው ተስፋ መናገራቸውን ሌትስራን ድረገፅ ዘግቦታል፡፡ አትሌት ቀነኒሳ በቀለ ለቺካጎ ማራቶን ባደረገው ዝግጅት ለውጦች ማድረጉ ግድ ነበር፡፡ የመጀመርያ ማራቶኑን በፓሪስ ከመሮጡ በፊት የሰራው ልምምድ ምንም እንኳን በውድድሩ በምንጊዜም የማራቶን ፈጣን ሰዓት 6ኛ ደረጃ አስመዝግቦ ቢያሸንፍም በወቅቱ 27ኛው ኪሎሜትር ላይ ለገጠመው የጉዳት ስሜት ምክንያቱ የልምምድ ስርዓቱ ነበር፡፡ ለፓሪስ ማራቶን ሲዘጋጅ በሳምንት ከ180 እስከ 200 ኪሎሜትሮችን ሮጦ ነበር፡፡ ለቺካጎ ማራቶን የተዘጋጀው ግን ከ160 እስከ 180 ኪሎሜትሮችን ነው፡፡የዓለም የማራቶን ሪከርድ በኬንያዊ አትሌት ሲሰበር የዘንድሮው ለሶስተኛ ጊዜ ሲሆን በዴኒስ ኪሜቶ የተያዘው 2 ሰዓት ከ02 ደቂቃዎች ከ57 ሰከንዶችን በሚቀጥሉት 15 ዓመታት በ177 ሰከንዶች በማሻሻል በሰው ልጅ ብቃት ማራቶንን 1 ሰዓት ከ59 ደቂቃዎች መግባት እንደሚቻል ሳይንቲስቶች ይገልፃሉ፡፡ ከምስራቅ አፍሪካ አትሌቶች ይህን በማሳካት ደግሞ ኬንያውያን ወንድ አትሌቶች ከኢትዮጵያውያን እጅግ በላቀ ሁኔታ ግምት አግኝተዋል፡፡
ቺካጎ ላይ በሴቶች ምድብ  ያሸነፈችው ኬንያዊቷ ሪታ ጄፒቶ ስትሆን ርቀቱን በ2 ሰዓት ከ24 ደቂቃዎች ከ35 ሰከንዶች በሆነ ጊዜ በመሸፈን ነበር፡፡ ይሁንና የኢትዮጵያ ሴት አትሌቶች በውድድር ዘመኑ እንዳሳዩት ስኬት በቺካጎም ዋና ተፎካካሪዎች ነበሩ፡፡ ቺካጎ ላይ ኢትዮጵያዊቷ ማሬ ዲባባ በ2 ሰዓት ከ25 ደቂቃዎች ከ37 ሰከንዶች በሆነ ጊዜ ርቀቱን በመሸፈን ሁለተኛ ደረጃን ስታገኝ፤ 3 የወጣችው የኬንያዋ ፍሎረንስ ኪፕላጋት ናት፡፡ በሴቶች ሌሎቹ ኢትዮጵያውያን በ2 ሰዓት ከ27 ደቂቃዎች ከ02 ሰከንዶች በሆነ ጊዜ ብርሃኔ ዲባባ አራተኛ እንዲሁም ገለቴ ቡርቃ በ2 ሰዓት ከ34 ደቂቃዎች ከ17 ሰከንዶች በሆነ ጊዜ ስምንተኛ መውጣታቸው ይጠቀሳል፡፡

በ8 የማራቶን ሊጎች በወንዶች ኬንያ  7 ኢትዮጵያ 1፤ በሴቶች ኬንያ 3 ኢትዮጵያ 1
ማራቶን ሊግ “ዎርልድ ማራቶን ሜጀር ሲሪዬስ”  በሚል ስያሜ ዘንድሮ የተካሄደው ለስምንተኛ ጊዜ ነው፡፡ በማራቶን ሊግ ላይ በስድስት ትልልቅ ማራቶኖች  በሚመዘገብ ውጤት መሰረት 1ኛ ሆኖ መጨረስ በሁለቱም ፆታዎች በነፍስ ወከፍ የ500ሺ  ዶላር ሽልማት ይገኝበታል፡፡ ማራቶን ሊጉ ዘንድሮ የተጀመረው   በቶኪዮ ማራቶን ሲሆን የመጨረሻው ውድድር ነገ በኒውዮርክ ማራቶን ይሆናል፡፡
የዘንድሮ ማራቶን ሊግ በኒውዮርክ ማራቶን ከመጠናቀቁ በፊት በተለይ በሴቶች ምድብ በአንደኛነት በመጨረስ 500ሺ ዶላር እንዳሸነፈች ያረጋገጠችው ኬንያዊቷ ሪታ ጂፔቶ ሆናለች፡፡ ሪታ ጄፕቶ በ2013 እኤአ የቺካጎ እና የቦስተን ማራቶኖችን ለማሸነፍ የበቃች ሲሆን በ2014 እኤአ ደግሞ መልሷ በሁለቱም ማራቶን ውድድሮች በተከታታይ ዓመት በማሸነፍ በማራቶን ሊጉ 100 ነጥብ አስመዝግባለች፡፡ በ213 በዓለም ሻምፒዮና 1ኛ፤ በለንደን ማራቶን ሁለተኛ እንዲሁም በ2014 በለንደን ማራቶን ያሸነፈችው ኤድና ኪፕላጋት በ65 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ አግኝታለች፡፡ በ2013 እኤአ ላይ በቦስተን ማራቶን 3ኛ ደረጃ የነበራት እና በ2014 እኤአ የቶኪዮ እና የበርሊን ማራቶኖችን ያሸነፈችው ትርፌ ፀጋዬ በ51 ነጥብ 3ኛ ደረጃ በማግኘት በውድድር ዘመኑ በማራቶን ሊግ በኢትዮጵያዊ የተመዘገበውን ከፍተኛ ውጤት አግኝታለች፡፡
በሌላ በኩል በማራቶን ሊጉ የወንዶች ምድብ በነጥብ ብልጫ በአንደኛነት በመጨረስ የ500ሺ ዶላር ተሸላሚ የሚሆን አትሌት የሚታወቀው ነገ  በሚደረገው የኒውዮርክ ማራቶን ሊሆን ይችላል፡፡ በዚህም የኬንያውያን አትሌቶች እድል የሰፋ ነው፡፡ ሊጉን በአንደኛነት የሚመራው ከሳምንታት በፊት በበርሊን ማራቶን አዲስ የዓለም ክብረወሰን በማስመዝገብ ያሸነፈው እና በ2013 እኤአ ላይ በቶኪዮ እና ቺካጎ ማራቶን ላይ ያሸነፈው ዴኒስ ኪሜቶ በ75 ነጥብ ነው፡፡ በ2ኛ ደረጃ በ65 ነጥብ ይከተል የነበረው በ2013 በዓለም ሻምፒዮና አራተኛ ደረጃ በለንደን ማራቶን አንደኛ እና በኒውዮርክ ማራቶን 2ኛ ደረጃ እንዲሁም በ2014 በለንደን 3ኛ በቺካጎ አራተኛ ደረጃ ያስመዘገበው ኢትዮጵያዊ ፀጋዬ ከበደ ነው፡፡ በማራቶን ሊጉ የዴኒስ ኬሚቶን ደረጃ በመቀናቀን ከኒውዮርክ ማራቶን ውጤት በኋላ ለማሸነፍ እድል የሚኖረው የቀድሞ የማራቶን ክብረወሰን ባለቤት ዊልሰን ኪፕሳንግ ብቻ ይሆናል፡፡
በማራቶን ሊጉ ለአትሌቶች እስከ አምስተኛ ደረጃ በሚመዘገብ ውጤት  ነጥብ የሚያስገኙ ዓለም አቀፍ 6 ማራቶኖች  በቶኪዮ፤ በቦስተን፤ በለንደን፤ በበርሊን፤ በቺካጎ እና በኒውዮርክ የሚካሄዱት ናቸው፡፡ የኦሎምፒክ እና የዓለም ሻምፒዮና የማራቶን ውድድሮችም በሚካሄዱባቸው የውድድር ዘመናትም ነጥብ ይገኝባቸዋል፡፡ አንድ የማራቶን ሊግ የውድድር ዘመን በ2 የውድድር ዓመታት ውስጥ የሚወሰን ሲሆን በእዚህ ጊዜ ውስጥ የሊጉ አካል የሆኑ ቢያንስ 12 ማራቶኖች አሉ፡፡ በእነዚህ ውድድሮች ቢበዛ በ4 ማራቶኖች በመሳተፍ ከፍተኛ ውጤት ያስመዘገቡ አትሌቶች በደረጃ ሰንጠረዡ በአንደኝነት በመጨረስ 500ሺ ዶላር በየፆታ መደቡ ለመሸለም  ሰፊ እድል ይኖራቸዋል፡፡ በማራቶን ሊግ  ውድድሮች ለአንደኛ ደረጃ 25 ነጥብ ፤ ለሁለተኛ ደረጃ 15 ነጥብ ፤ ለሶስተኛ ደረጃ 10 ነጥብ ፤ ለአራተኛ ደረጃ 5 ነጥብ  እንዲሁም ለአምስተኛ ደረጃ 1 ነጥብ ይሰጣል፡፡ ከ2006 በእኤአ ወዲህ  በተካሄዱት 7 የማራቶን ሊግ የውድድር ዘመናት ኬንያውያን በከፍተኛ ብልጫ ኢትዮጵያውያን እየራቁ መሄዳቸው ይስተዋላል፡፡ የዎርልድ ማራቶንስ ሜጀር ሲሪዬስ ወይንም የማራቶን ሊግ ከተጀመረ ወዲህ 129 ውድድሮች ተደርገው ማሸነፍ ከቻሉ 102 የአፍሪካ አትሌቶች 93 የምስራቅ አፍሪካ አትሌቶች ናቸው፡፡ የአንበሳው ድርሻ ደግሞ የኬንያውያን ነው፡፡ከቺካጎ ማራቶን በኋላ በዓለም የማራቶን ሊግ ውስጥ በሚካሄዱ 6 የማራቶን ውድድሮች ከ1989 እኤአ ወዲህ የምስራቅ አፍሪካ በተለይ  የኬንያ እና የኢትዮጵያ አትሌቶች  በወንዶች 72.6 በመቶ በሴቶች 90 በመቶ አሸናፊዎች ናቸው፡፡
ከ1990 ወዲህ በሁለቱም ፆታዎች በቶኪዮ ማራቶን ኬንያ 9 ኢትዮጵያ 1 ፤ በቦስተን ማራቶን ኬንያ 14 ኢትዮጵያ 4፤ በለንደን ማራቶን ኬንያ 12 ኢትዮጵያ 3 ፤ በበርሊን ማራቶን ኬንያ 13 ኢትዮጵያ 4 ፤ በቺካጎ ማራቶን ኬንያ 12 ኢትዮጵያ 2፤  እንዲሁም ከነገው ውድድር በፊት በኒውዮርክ ማራቶን ኬንያ 10 ኢትዮጵያ 2 አሸናፊዎች አስመዝግበዋል፡፡
ባለፉት ስምንት የማራቶን ሊግ የውድድር ዘመናት የደረጃ ሰንጠረዡን በአንደኛነት በመጨረስ  የተሳካላቸው በወንዶች 7 ጊዜ የኬንያ አንድ ጊ. የኢትዮጵያ እንዲሁም በሴቶች ሶስት ጊዜ የኬንያ፤ እያንዳንዳቸው ሁለት ጊዜ የጀርመን እና የራሽያ እንዲሁም አንድ ጊዜ የኢትዮጵያ አትሌቶች በነፍስ ወከፍ የ500ሺ ዶላር ሽልማት አግኝተዋል፡፡ የማራቶን ሊጉን በማሸነፍ የተሳካላቸው ሁለት የኢትዮጵያ አትሌቶች ናቸው፡፡ በወንዶች ምድብ ባለፈው ዓመት በ75 ነጥብ የሊጉን ፉክክር በአንደኛነት በመጨረስ ያሸነፈው ፀጋዬ ከበደ ፤ እንዲሁም በሴቶች በ2006 እና 2007 ላይ በመጀመርያው የማራቶን ሊግ በ80 ነጥብ ያሸነፈችው ጌጤ ዋሚ ናቸው፡፡

        ጤናዎ ተጓድሎ ህመም ሲሰማዎና ስቃይ ሲበዛብዎ፣ ለስቃይዎ እፎይታን፣ ለህመምዎ ፈውስን ፍለጋ የሆስፒታሎችንና የክሊኒኮችን በራፍ ማንኳኳትዎ አይቀሬ ነው፡፡
እነዚህ የበሽታ ፈውስን ሽተው የሚሄዱባቸውና ከሥቃይም እንደሚገላግልዎት ተስፋ ያደረጉባቸው ቦታዎች ከከፍተኛ የአካል ጉዳት እስከ ሞት ሊያደርሱ የሚችሉ ሆስፒታል ወለድ በሽታዎችን የሚሸምቱባቸው ስፍራዎች ጭምር እንደሆኑ ቢነገርዎ ምን ይሰማዎታል? ለመታከም ገብተው ተጨማሪ ህመም ይዘው የሚወጡባቸው የጤና ተቋማት ጉዳይ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ አሳሳቢ እየሆነ መጥቷል፡፡ በጉዳዩ ዙሪያ የተደረጉ ጥናቶችም ይህንኑ እውነታ የሚያረጋግጡ ናቸው፡፡ ችግሩ በአገራችን ብቻ የሚከሰት ሳይሆን በዓለም አቀፍ ደረጃ ለበርካታ ሰዎች ህመምና ሞት መንስኤ እንደሆነ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡
በቀላሉ ሊድኑ በሚችሉ ህመሞች ተይዘው ህክምና ለማግኘት ከገቡበት ሆስፒታል ሸምተዋቸው በሚመጡት የሆስፒታል ኢንፌክሽኖች (Nosocomial Infection) ሳቢያ ከባድ የአካል ጉዳትና ሞት የሚደርስባቸው ሰዎች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እያሻቀበ መጥቷል፡፡ የዓለም ጤና ድርጅት እ.ኤ.አ በ2010 ዓ.ም ይፋ ያደረገው ጥናት እንደሚያመለክተው፤ በተለያዩ ህመሞች ተይዘው ለመታከም ሆስፒታል ከገቡ ህሙማን መካከል አብዛኛዎቹ ሆስፒታል ውስጥ በያዛቸው ኢንፌክሽን ሳቢያ ታመዋል፡፡ ድርጅቱ በአፍሪካ ውስጥ አደረግሁት ያለውን ጥናት ጠቅሶ እንደገለፀውም፤ ወደ ጤና ተቋማት ለህክምና ከሚሄዱ ህሙማን መካከል ከ10 በመቶ በላይ የሚሆኑት ከሄዱበት ተቋም በሽታ ሸምተው ይመለሳሉ፡፡
በኢትዮጵያ ይህንን ጉዳይ አስመልክቶ በስፋት የተሰሩ ጥናቶች ባይኖሩም በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል (ክሮኒቫል፣ ጌዴቦ እና ሀብቴ ገብሬ) በተባሉ ምሁራን በ1997 ዓ.ም የተደረገና “Hospital Acquired Infections Among Surgical Patients in Tikur Anbessa Hospital” በሚል ርእስ የተሰራ ጥናት እንደሚጠቁመው፤ ጥናቱ ከተደረገባቸው 1006 ህሙማን መካከል 165 የሚሆኑት በሆስፒታል ወለድ በሽታዎች ተይዘው ተገኝተዋል፡፡ በዚሁ ሆስፒታል የተደረገ “The Bacteriology of Nosocomial Infections at Tikur Anbessa Teaching Hospital” የተሰኘና በ2006 ህሙማን ላይ የተደረገ ሌላ ጥናት በበኩሉ፤ ከህሙማኑ 13 በመቶ የሚሆኑት በሆስፒታል ወለድ ኢንፌክሽኖች ተጠቅተዋል፡፡ ከእነዚህ ተጠቂዎች መካከልም ከፍተኛውን ቁጥር የሚይዙት በሆስፒታሉ የማዋለጃ ክፍል ውስጥ የነበሩ ህሙማን እንደሆኑ ጥናቶቹ ይጠቁማሉ፡፡
ይህ አሀዝ በሆስፒታሎቹ በየጊዜው እያደገ ከሚመጣው የተገልጋይ ቁጥርና የበሽታ ዓይነቶች ብዛት ጋር ተያይዞ እየጨመረ ሊሄድ እንደሚችልም ጥናቶቹ ይገልፃሉ፡፡ በአገሪቱ የተለያዩ የጤና ተቋማት የሚገለገሉ ህሙማን በተመሳሳይ ሁኔታ በሆስፒታል ወለድ በሽታዎች ሊጠቁ እንደሚችሉ የሚጠቁመው ጥናቱ፤ ለችግሩ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያሻቀበ መሄድ ዋንኛ ምክንያቶች ናቸው ብሎ ከዘረዘሯቸው ጉዳዮች መካከል ሆስፒታሉ የሚያስተናግዳቸው ተገልጋዮች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መሄዱ፣ ባለሙያዎቹ የኢንፌክሽን ቁጥጥር መመሪያዎችንና ሆስፒታል ወለድ በሽታዎች መከላከያ መንገዶችን በአግባቡና በጥብቅ አለመከታተላቸው፣ ለኢንፌክሽኖች መከላከያ የሚሰጡ ፀረ ጀርም መድኀኒቶች ከተዋህስያኑ ጋር መላመዳቸውና የሰዎች በሽታን የመከላከል አቅም በተለያዩ ምክንያቶች እየተዳከመ መምጣት የሚሉት ይገኙበታል፡፡
ሆስፒታሎች (የጤና ተቋማት) በተለያዩ ተላላፊና ተላላፊ ባልሆኑ ህመሞች የተያዙ በርካታ ሰዎች በአንድ ላይ የሚገኙባቸው ስፍራዎች በመሆናቸው ከፍተኛ ጥንቃቄ እንደሚሹ የገለፁት የውስጥ ደዌ ስፔሻሊስቱ ዶክተር ቴዎድሮስ ታዬ፤ ከልዩ ልዩ ጎጂና በሽታ አስተላላፊ ተዋህስያን ጋር ወደ ጤና ተቋማት ለህክምና የሚመጡ ህሙማን አስፈላጊውና ተገቢው ጥንቃቄ ካልተደረገ በሽታውን ወደ ሌሎች ሰዎች ማስተላለፋቸውና ለሌሎች ጠንቅ መሆናቸው አይቀርም ብለዋል፡፡
ሆስፒታል ወለድ በሽታዎችን በሁለት ዋና ዋና ዓይነቶች ከፍለን ልናያቸው እንችላለን ያሉት ዶክተሩ፤ የመጀመሪያው ታማሚው ሰው በቀጥታ በሽታውን ወደ ጤናማዎቹ ሰዎች እንዲተላለፍ የሚያደርግበት መንገድ ሲሆን ይህም እንደ ቲቢ ያሉና በአየር ተላላፊ የሆኑ እንዳሁም፣ በንክኪና መሰል ሁኔታዎች ከታማሚው ሰው ወደ ጤነኛው በቀላሉ ሊተላለፉ የሚችሉ በሽታዎች ናቸው፡፡ ይህም ህሙማኑ በተጨናነቀ ሁኔታ በሚጋሯቸው የመኝታና የመፀዳጃ ክፍሎች፣ ንፅህናቸውን ባልጠበቁ አልጋዎች፣ ብርድልብሶችና አንሶላዎች እንዲሁም አልባሌ ስፍራ በሚጣሉ አገልግሎት ላይ የዋሉ መጠቀሚያዎች ሳቢያ በሽታው በቀላሉ ወደ ጤነኛው ሰው ሊተላለፍ ይችላል፡፡ የጤና ባለሙያዎች በሽታን ወደ ጤናማው ሰው የሚያስተላልፉበት መንገድም ችላ ሊባል የሚገባው ጉዳይ አይደለም፡፡ የጤና ባለሙያው አንድ ህመምተኛን ለማከም የተጠቀመበትን ጓንት ሳይቀይር ሌላ ታማሚን ለማየት (ለመመርመር) ሲነሳ የተለያዩ በሽታ አምጪ ቫይረሶችን ከአንዱ ወደ ሌላው ማስተላለፉ አይቀሬ ነው ሲሉም አክለዋል፡፡
ሌላውና በበርካታ የጤና ተቋማት ውስጥ እንደ ትልቅ ችግር ሆነው የሚታዩት ሆስፒታል ወለድ በሽታዎች በተለያዩ ምክንያቶች የሚፈጠሩ ኢንፌክሽኖች ናቸው፡፡ በአገራችን በአብዛኛው የሚታዩት የኢንፌክሽን አይነቶች አራት ሲሆኑ እነሱም - surgical wound infections urinary tract infections እና Dosokimital Nimonia የተባሉት ሲሆኑ ሴቶች በወሊድ ወቅት የሚገጥማቸው ኢንፌክሽንም ተጠቃሽ ነው፡፡ እነዚህን ዘርዘር አድርገን ለማየት እንሞክር፡-
surgical wound infections
በቀዶ ጥገና ወቅት ከውጪ በሚገቡ የተለያዩ ጀርሞችና ባክቴሪያዎች አማካኝነት ቀዶ ጥገናው የተካሄደበት የሰውነት ክፍልን በንፅህና ካለመያዝና ንፅህናው በአስተማማኝ ሁኔታ ባልተጠበቀበት ሁኔታ ቀዶ ጥገናውን በማድረግ ሂደት የሚከሰት ኢንፌክሽን ሲሆን ይህም በርካታ ታማሚዎችን የሚያጠቃ የጤና ችግር ነው፡፡
Urinary Tract Infections
(በሽንት መተላለፊያ ቱቦ ላይ የሚከሰቱ ኢንፌክሽኖች)
 ይህ አይነቱ ኢንፌክሽን፤ ህሙማን ቀዶ ጥገና ለማድረግ በሚዘጋጁበት ጊዜ ወይንም በሌሎች ህመሞች ሳቢያ ሰው ሰራሽ የሽንት ማውጫ ቱቦ እንዲገባላቸው በሚደረግ ወቅት የሚከሰት ችግር ነው፡፡ ይህ ዓይነቱ ችግርም ሆስፒታል ውስጥ ለህክምና ከሚገቡ ህሙማን መካከል ከግማሽ በላይ የሚሆኑትን የሚያጋጥም ችግር ሲሆን ችግሩ የሽንት ማውጫ ቱቦው (ካቴተሩ) ወደሰውነታቸው እንዲገባ በሚደረግበት ወቅት የሚፈጠር መሆኑን ዶ/ር ቴዎድሮስ ገልፀዋል፡፡ አብዛኛውን ጊዜ ህሙማኑ ወደ ሆስፒታል ገብተው ለቀዶ ህክምና ዝግጁ እንዲሆኑ ሲደረግ የሚገጠምላቸው ሰው ሰራሽ የሽንት ማውጫ ቱቦ ብቁ ባልሆኑ ሙያተኞች እንዲሰራ ይደርጋል፡፡
አንዳንድ ጊዜ በሆስፒታሎች ለስራ ልምምድ የሚገቡ ተማሪዎች ይህንን ዓይነቱን ስራ እንዲሰሩ ስለሚተውላቸው ታማሚው በሽንት መተላለፊያ ቱቦ ኢንፌክሽን በቀላሉ ሊጠቃ ይችላል፡፡
3. Dosokimial Nlimonia
ይሄ የመተንፈሻ አካል ኢንፌክሽን የምንለው ሲሆን በዚህ ዓይነቱ ኢንፌክሽን የሚጠቁ ሰዎች ሰው ሰራሽ የመተንፈሻ መሳሪያ የሚገጠምላቸው በሽተኞች ሲሆኑ መሳሪያውን በመግጠም ሂደት ውስጥ በሚፈጠሩ ችግሮች ምክንያት እንደሚከሰት ዶክተሩ ገልፀዋል፡፡
4ኛ. በሴቶች ላይ ከወሊድ በኋላ የሚከሰቱ ኢንፌክሽኖች (በቀዶ ጥገና በሚደረግ ወሊድና በስቲች)ይህ አይነቱ ኢንፌክሽን በአገራችን በስፋት የሚታይና በርካታ ቁጥር ያላቸውን ሴቶች ለከባድ ህመምና ለሞት የሚዳርግ ችግር ነው፡፡
 በሆስፒታል ውስጥ ለሚከሰቱ ሆስፒታል ወለድ በሽታዎች በአብዛኛው ተጋላጭ የሚሆኑት ህፃናትና በዕድሜ የገፉ ሰዎች እንደሆኑ የጠቆሙት ዶክተሩ፤ የጤና ተቋማቱ ተላላፊ በሽታ ያለባቸውን ሰዎች ለይተው የሚያክሙባቸው ቦታዎች አለመኖራቸው፣ በሆስፒታል ውስጥ የሚገኙ የመፀዳጃና የጋራ መጠቀሚያ ስፍራዎች ንፅህና፣ በሆስፒታሎች ውስጥ ውሃ በበቂ ሁኔታ አለመገኘት፣ በየመኝታ ክፍሎችና ህክምና መስጫ ቦታዎች ላይ አየር በበቂ ሁኔታ የሚዘዋወርበት ሁኔታ አለመኖር ለችግሩ መባባስ ዋንኛ ምክንያቶች ናቸው ብለዋል፡፡
ሆስፒታል ወለድ በሽታዎችና ኢንፌክሽኖችን ለመከላከል ከፍተኛ ጥንቃቄ መደረግ እንዳለበት የገለፁት ዶክተር ቴዎድሮስ፤ ችግሩ ከተከሰተ በኋላም ታማሚውን ለማዳን የሚደረገው ጥረት እምብዛም አርኪ እንዳልሆነ ተናግረዋል፡፡
ሆስፒታል ወለድ ኢንፌክሽኖችን በቀላሉ ለማስወገድ ይረዱ የነበሩ መድሃኒቶች ከበሽታው ጋር በመላመዳቸው ሳቢያ በሽታው ለመድሃኒቶቹ መሸነፉን አቁሞአል፡፡ በዚህ ምክንያትም ቀላል በሽታ ለመታከም መጥተው በሆስፒታል ወለድ ኢንፌክሽኖች በመጠቃት ህይወታቸውን የሚያጡ ታማሚዎች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ ሄዷል ብለዋል፡፡
ሰሞኑን በእስራኤል አገር የኩላሊት ንቀላ ተከላ ህክምና የተደረገለት ታዋቂው የዜማና ግጥም ደራሲ አበበ መለሰ የዚህ ችግር ተጠቂ እንደሆነ ታውቋል፡፡ አበበ በሆስፒታል ውስጥ የኩላሊት ንቅለ ተከላ ህክምና ከተደረገለት ከጥቂት ሰዓታት በኋላ ቤተሰቦቹ ደስታቸውን ለመግለፅ ሲሞክሩ በተፈጠረ ንክኪ ጤናውን ለአደጋ ሊጥል የሚችል ሁኔታ ተከስቶ ነበር ተብሏል፡፡ ጎበዝ “የቆጡን አወርድ ብላ የብብቷን ጣለች” እንዳይሆንብንና ልንታከም ሄደን ታመን እንዳንመጣ ጠንቀቅ እንበል፡፡
 

Published in ዋናው ጤና

     ቅዱስ ጊዮርጊስ ቢራ (ቢጂአይ) “በጥቅምት አንድ አጥንት” በሚል መሪ ቃል ዛሬና ነገ በኤግዚቢሽን ማዕከል የቢራና የባህላዊ ምግቦች ፌስቲቫል እንደሚካሄድ አስታወቀ፡፡ በፌስቲቫሉ ቢራ ይጠጣል፣ ጥሬ ሥጋ (ጮማ) ይቆረጣል፣ በታዋቂ አርቲስቶች የሙዚቃ ዝግጅት ይደምቃል ተብሏል፡፡
የፌስቲቫሉ ዓላማ ምን እንደሆነ የቢጂአይ ቢራ የአዲስ አበባ ሽያጭ ኃላፊ አቶ ኢሳያስ አባተ ሲያስረዱ፣ በተለያዩ አገራት የቢራ ፌስቲቫል የተለመደ መሆኑን ጠቅሰው፣ በጀርመን ሙኒክ ከተማ ለአንድ ሳምንት በሚካሄደው የቢራ ፌስቲቫል 6 ሚሊዮን ያህል ሰዎች እንደሚሳተፉ ገልጸዋል፡፡
የቢራ ፌስቲቫል በአገራችን አዲስ አይደለም ያሉት አቶ ኢሳያስ፤ ሂልተን ሆቴል የቢራ ፌስቲቫል ያካሂዳል፡፡ ተጠቃሚዎቹ ግን ከፍተኛ ገቢ ያላቸው ስለሆኑ ተደራሽነቱ ውሱን ነው፡፡ የእኛ ቢራ ተጠቃሚዎች (ደንበኞች) መካከለኛ ገቢ ያላቸው ስለሆኑ ይህን የቢራ ባህል ወደ ህብረተሰቡ በማውረድ ለማስለመድ እንፈልጋለን፡፡ ከአሁን በኋላ በየዓመቱ ይቀጥላል ብለዋል፡፡ በፌስቲቫሉ ጥሬ ስጋ ለምን ተካተተ? ብለን ጠይቀን፣ ጥሬ ስጋ ባህላዊ ምግባችን ነው፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቢራም ተወዳጅ መጠጥ ስለሆነ አብረው ቢቀርቡ ጥሩ ነው የሚል ውሳኔ ላይ ደረስን፣ በመዲናዋ ታዋቂና ስም ያላቸው 6 ተመራጭ ሥጋ ቤቶች፡- ጨርጨር፣ አሹ፣ ኬርሻዶ፣ መዝገበ፣ በእምነትና ዋአካን ሥጋ ቤቶች በፌስቲቫሉ በመሳተፍ፣ ጥራት ያለው ሥጋ በተመጣጣኝ ዋጋ ያቀርባሉ፡፡ ጥሬ ስጋ ለማይበላ ሰውም ጥብስ አለ ብለዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት የአንድ ኪሎ ስጋ ዋጋ 220 ብር ደርሷል ያሉት ኃላፊው፤ ብዙ ደንበኞቻችን መጥተው በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲጠቀሙ በማድረግ የስጋ ቤቶቹን ወጪ ስለምንደጉም፣ የአንዱን ኪሎ ስጋ ለወትሮው ከሚሸጡበት ዋጋ 40 በመቶ ቀንሰው በ130 ብር ያቀርባሉ ብለዋል፡፡
ፌስቲቫሉ፣ መግቢያ ቢኖረውም ብዙ ሕዝብ እንዲሳተፍ ስለፈለግን 20 ብር አድርገናል፡፡ በሁለቱን ቀን ዝግጅትም እስከ 20 ሺህ ህዝብ እንጠብቃለን ብለዋል፡፡
በፌስቲቫሉ የሚቀርበው ድራፍት፣ ቢራና ጥሬ ስጋ ብቻ እንዳልሆነ የጠቀሱት አቶ ኢሳያስ፤ ታዋቂዎቹ “ዛጎል” ና “ጊዜ” ባንዶችና ታዋቂ ዘፋኞች፡- እነ ዓለማየሁ እሸቴ፣ ማህሌት ገ/ጊዮርጊስ፣ ግርማ ተፈራ ካሳ፣ ተሾመ ወልዴና ሌሎችም ህዝቡን ያዝናናሉ፡፡ ለልጆች መጫወቻ ስላለ ሰው፣ ልጆቹንና ቤተሰቡን ይዞ በመምጣት፣ እየበላና እየጠጣ፣ በሙዚቃው እየተዝናና በሥራ የደከመ አካልና አዕምሮውን ዘና ያደርጋል በማለት አስረድተዋል፡፡    


      የኢትዮጵያ የግሉ ዘርፍ ሐኪሞች ሕክምና ማኅበር በ7ኛ ዓመታዊ ጉባኤው፣ በገጠርም ሆነ በከተማ የጤና ሽፋኑን መቶ በመቶ ለማድረስ ከመንግሥት ጋር ተቀናጅቶ መስራቱን እንደሚቀጥል አስታወቀ፡፡
መንግሥት ሁሉን አቀፍ የጤና ሽፋን ለመላው ኅብረተሰብ ለማዳረስ የጀመረውን የጤና መድን ዋስትና ፖሊሲ ተግባራዊ ለማድረግ “አቅም የሌለውን ወገን ያማከለ የጤና መድህን ስርዓትን ለመዘርጋት፣ አጠቃላይ የጤና ሽፋንን እናረጋግጣለን!!” የሚለውን የጉባኤያቸው መሪ ሐሳብ አድርገዋል፡፡
የግሉ የጤና ዘርፍ የአገሪቱን አጠቃላይ የጤና ሽፋን ለማሳደግ እየተጫወተ ያለው ሚና በግልጽ የሚታይና በመንግሥትም እውቅና ያገኘ ነው ያሉት የማኅበሩ ጠቅላላ ጉባኤ ሰብሳቢ ዶ/ር ብርሃኑ ተክሌ፤ ማህበረሰቡን ያማከለ የጤና መድን ስርዓት ለመዘርጋት የግሉ የጤና ዘርፍ ከመንግሥት የጤና ተቋማት ጋር በመቀናጀት ጥራቱን የጠበቀ፣ ተወዳዳሪ የሆነ፣ አቅም የሌለውን ወገን ያካተተና የሚደግፍ የጤና አገልግሎት ሊሰጥ እንደሚገባ በአጽንኦት መግለጽ እሻለሁ ብለዋል፡፡
በዚሁ ወቅት የግሉን የጤና ዘርፍ የማይናቅ ሚና እንዳለው የጠቆመው አንድ ጥናታዊ ጽሑፍ፤ በከተሞች 59 በመቶ፣ በገጠር ደግሞ 33 በመቶ ሕዝብ የሚታከመው በግል የጤና ዘርፍ እንደሆነ ጠቅሶ፣ የግሉ የጤና ዘርፍ ከአጠቃላይ ጠየና ሽፋን 34 በመቶ ድርሻ አለው ብሏል፡፡
የመንግሥት የመጨረሻ ግብ ለ500 ቤተሰቦች አንድ ሐኪም እንዲደርሳቸው ማድረግ ነው ያሉት ጥናታዊ ጽሑፍ አቅራቢው፣ ይህን ዕቅድ፣ ተግባራዊ ለማድረግ መንግሥት ባለፉት 5 ዓመታት ለጤና ተቋማት ግንባታ 43 ቢሊዮን ብር አውጥቷል፡፡ በሚቀጥለው 20 ዓመትም 1,200 ሆስፒታሎችና 12,000 ጤና ጣቢያዎች ለመክፈት ማቀዱ፣ ለግሉ የጤና ዘርፍ አመቺ ሁኔታ እየፈጠረ ነው ብለዋል፡፡
11,060 የጤና ተቋማት፣ 65,200 ክሊኒኮችና መድኃኒት ቤቶች፣ 343 መድኃኒት አስመጪዎችና አከፋፋዮች፣ 15 የመድኃኒት ፋብሪካዎች በግል የጤና ዘርፍ ባለቤትነት የሚንቀሳቀሱ ናቸው ያሉት አቅራቢው፤ በእነዚህ ተቋማት ውስጥ 34,000 የሕክምና ባለሙያዎችና 159 ሐኪሞች ተቀጥረው እንደሚሰሩ አብራርተዋል፡፡

Published in ዋናው ጤና
Monday, 03 November 2014 07:56

ኢቦላ በአሃዝ ሲገለፅ

የዓለም ጤና ድርጅት በቅርቡ ያወጣው ሪፖርት እንደሚያመለክተው፤ የኢቦላ በሽታ ስርጭት በአስደንጋጭ ሁኔታ እየጨመረ ነው፡፡ የድርጅቱ ሪፖርት ቀጣዮቹን መረጃዎች ይፋ አድርጓል፡፡
8.033       እስከ አሁን በኢቦላ ቫይረስ የተያዙ ሰዎች
3865     በኢቦላ በሽታ ምክንያት ህይወታቸውን ያጡ ሰዎች
233    በኢቦላ በሽታ ህይወታቸውን ያጡ የጤና ባለሙያዎች
400     በበሽታው የተያዙ የጤና ባለሙያዎች
21    በኢቦላ ቫይረስ የተጠቃ ሰው የበሽታውን ምልክቶች የሚያሳይባቸው ቀናት
        ***        
የየአገራቱ የጤና በጀት
በአሜሪካ የነፍስ ወከፍ አመታዊ የጤና በጀት     $ 8895
በላይቤሪያ     “    “    “    $ 65
በሴራሊዮን     “    “    “$ 96
በጊኒ        “    “    $ 32
በኢትዮጵያ     “    “    $ 18        
የዓለም ጤና ድርጅት ሌሎች መረጃዎች
በኤችአይቪ በየሳምንቱ - 4795 ሰዎች ይሞታሉ
በተቅማጥ    በየሳምንቱ -2828   ሰዎች ይሞታሉ
በኢቦላ     በየሳምንቱ -10ሺ ሰዎች ይሞታሉ ተብሎ ይታሰባል፡፡   

Published in ዋናው ጤና