መልካም ወሬ ከፈለጋችሁ አይታጣም። በቅርቡ “አይፎን 6” ሞባይሎችን፣ ሰሞኑን ደግሞ አዳዲስ የ“አይ-ፓድ” ምርቶቹን ለገበያ ያቀረበው አፕል ኩባንያ፤ እንደለመደው ዘንድሮም ሬከርድ ሰብሯል - በአመት 40 ቢሊዮን ዶላር ገደማ ትርፍ በማግኘት። አትራፊነቱ አይገርምም። የጥረት፣ የፈጠራ፣ የቢዝነስ ታታሪነቱ ውጤት ነው። “አይፎን 6”ን ለመግዛት ሲጠባበቁ የነበሩ የአፕል ደንበኞች፣ በሽሚያ ነው የተረባረቡበት። በምርቶቹ ጥራት ተወዳጅነትን አትርፏላ። እናም፣ በመጀመሪያዎቹ ሶስት ቀናት ብቻ ከ10 ሚሊዮን በላይ ሞባይሎችን በመሸጥ ሬከርድ ሰብሯል። አምና፣ የ“አይፎን 5” ምርቶቹን ለገበያ ያቀረበ ጊዜ፣ በሦስት ቀናት ዘጠኝ ሚሊዮን ሞባይሎችን በመሸጥ ያስመዘገበውን ሬከርድ ነው የሰበረው።

ለመሆኑ አፕል ኩባንያ እና አይፎን ለኛ ምናችን ነው ብሎ የሚጠይቅ አይጠፋም።  መቼም፤ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ፣ በግዢም ይሁን በዳያስፖራ ስጦታ የአይፎን ደንበኛ ለመሆን የቻሉ ኢትዮጵያውያንም፣ አዲሱን አይፎን ከእጃቸው ለማስገባት መጓጓታቸው አይቀርም። የተመኙት ይስመርላቸው። ይሄም ብቻ አይደለም። “የአፕል ስኬታማነትና የአይፎን ተወዳጅነት ምን ትርጉም አለው?” ለሚለው ጥያቄ፣ ሌላ ትልቅ መልስ አለው። “እንዲህ ነው ጀግንነት” ብለን ማድነቅና ማክበር... ከዚያም “ይዝለቅበት” ከሚል መልካም ምኞት ጋር በአርአያነቱ የራሳችንን መንፈስ ለስኬት ማነቃቃት እንችላለን። በእርግጥ፣ ትንሽ ራቅ ይላል፤ ኧረ እጅጉን የራቀ ቢመስለን አይገርምም። ደግነቱ እዚሁ በቅርባችን ኢትዮጵያ ውስጥ፣ መልካም የስኬት ወሬ ብንፈልግም አናጣም። ከተቋቋመ ሰባት አመት የማይበልጠው አንድ የአበባ እርሻ፣ በ200 ሚ. ዶላር እንደተሸጠ አልሰማችሁም? 4 ቢ. ብር ገደማ መሆኑ ነው። ቀላል ስኬት አይደለም።
የዚህ ተቃራኒ የኪሳራ አልያም የምስኪን ወሬ ከፈለጋችሁም ሞልቷል። “መንግስት፣ እንዳንሞት እንዳንድን አድርጎናል” በማለት ቅሬታቸውን ሲገልፁ የሰነበቱ ወጣቶችን ማየት ትችላላችሁ። በአዲስ አበባ በጥቃቅንና አነስተኛ ተቋማት ተደራጅተው፣ ከ“ኮብል ስቶን” ሥራ ወደ ብሎኬት አምራችነት እንዲሸጋገሩ የተደረጉ ወጣቶች ናቸው። ብሎኬት አምራቾቹ፣ አሁን ቅሬታ ያቀረቡት፣ አዲስ ነገር ስለተፈጠረ አይደለም። ከአምናና ካቻምና የተለየ ነገር እንዳልገጠማቸውማ፣ ለቅሬታ ከተጠቀሙበት አባባል መረዳት ይቻላል - “እንዳንሞት፣ እንዳንድን ሆነናል” ነው የሚሉት። ተሳክቶልን ሳናድግ ወይም ለይቶልን ሳንሞት እንደጠወለግን እድሜ እንቆጥራለን እንደማለት ይመስላል።
በእርግጥ፣ መንግስት ለወጣቶቹ ሲሚንቶ እንደሚያቀርብላቸውና፤ ከዚያም ያመረቱትን ብሎኬት እንደሚገዛቸው ስነግራችሁ፤ “ታዲያ፣ ምን ጎድሎባቸው ቅሬታ ያቀርባሉ? እንደነሱ የደላውስ የት ይገኛል?” ትሉ ይሆናል። መስሏችኋል! ትልቁ ችግራችንም እዚህ ላይ ነው። መንግስትና ቢዝነስ ሲገናኙ መጨረሻቸው እንደማያምር ሺ ጊዜ በተግባር ቢታይም፤ ብዙዎቻችን ይህን እውነታ ለመገንዘብ በጭራሽ ፈቃደኛ አይደለንም።
የመንግስት ጥገኛ በመሆን በቢሮክራቶች እግር ስር የወደቀ ቢዝነስ፣  በየትኛውም መስክ ቢሆን... በኤሌክትሪክ ስርጭትም ሆነ በስኳር ፋብሪካ፣ በዘይት ንግድም ሆነ በመስኖ ግድብ ግንባታ... አይዋጣለትም። ለስኳር እርሻና ምርት ታስቦ፤ ከአስር አመት በፊት የተጀመረውና በሁለት አመት ውስጥ ይጠናቀቃል የተባለለት የከሰም ግድብ ግንባታ፣ ከሰሞኑ 87% ላይ እንደደረሰ ዜና ስትሰሙ ምን ትላላችሁ? ምንም አይገርምም። በመንግስት የሚካሄዱት በርካታ የስኳር ፕሮጀክቶች፣ በአብዛኛው... (በአብዛኛው ሳይሆን ሁሉም ፕሮጀክቶች) ለአመታት እየተጓተቱ እድሜያቸውን እየቆጠሩ ነው። ከአስር አመት በፊት በአገሪቱ የሚገኙ የስኳር ፋብሪካዎች አመታዊ ምርት 3 ሚሊዮን ኩንታል ገደማ ነበር። መንግስት ይህንን የስኳር ምርትን በ7 እጥፍ አሳድጋለሁ ብሎ ነው በየአመቱ በቢሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ እየመደበ ለአስር አመታት የዘለቀው። ባለፉት አምስት አመታትማ፤ የገንዘቡ መጠን ጨምሯል - በየአመቱ ከ10 ቢሊዮን ብር በላይ ሲመደብ ቆይቷል። ነገር ግን፣ እስካሁን የሚቀመስ ውጤት ጠብ አላለም። እንደእቅዱ ቢሆንማ ኖሮ አምና፣ ቢያንስ ቢያንስ ከ12 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ስኳር መመረት ነበረበት። ግን የዛሬ አስር አመት ከነበረበት መጠን ፈቅ አላለም - 3 ሚሊዮን ኩንታል ገደማ ብቻ ነው የተመረተው። ምን ያህል ገንዘብ በሙስናና በብክነት እንደሚጠፋ አስቡት። የፌደራል ዋና ኦዲተር ሪፖርትን ማየት ትችላላችሁ። ትልቁ የተንዳሆ ስኳር ፕሮጀክት፣ በየአመቱ በርካታ ቢሊዮን ብር ቢመደብለትም፣ ወጪና ቀሪው በቅጡ እንደማይታወቅ የኦዲተሩ ሪፖርት ይገልፃል። ለምሳሌ፤ ለፕሮጀክቱ ተገዝቶ የሚመጣ ከፍተኛ መጠን ያለው ሲሚንቶና ብረት፣ ለምን ለምን ስራ እንደዋለ በዝርዝር አይታወቅም ብሏል - የኦዲተሩ ሪፖርት። ለሙስናና ለብክነት እንዴት እንደሚመች ይታያችኋል?   
በእርግጥ፣ የመንግስት የቢዝነስ እቅዶች የማይሳኩትና ውጤታማ የማይሆኑት፤ እንዲሁም በሙስናና በብክነት ከፍተኛ ሃብት የሚጠፋው፤ “በዚህኛው መንግስት ስንፍና ወይም በገዢው ፓርቲ ድክመት፣ በባለስልጣናቱ ዝርክርክነት ወይም ሙስና ነው” ማለቴ አይደለም። ሌላ መንግስት ቢቀየር፤ አማራጭ ፓርቲ ቢመጣ፣ የባለስልጣን ሹም ሽር ቢደረግ፤ ከዚህ የተለየ ውጤት አይገኝም። ከምር አስቡት። እቅዶች ቢሳኩና ውጤታማ ቢሆኑ፤ የመንግስት ባለስልጣናትና የመንግስት ሰራተኞች ምን ያተርፋሉ? ሃብት በብክነትና በሙስና ባይጠፋ ምን ይጠቀማሉ? ምንም! ከወትሮው የወር ደሞዝ የተለየ ገንዘብ ኪሳቸው አይገባም። ታዲያ ለምን ብለው ይጣጣራሉ? የግል ቢዝነስ ላይ ግን፤ ስኬታማና ትርፋማ ለመሆን የሚጣጣር ይኖራል፤ ጥቅም ያገኝበታላ። ለኩባንያዎች በኮንትራት የተሰጡ አብዛኞቹ የኤሌክትሪክ ማመንጫ ግድቦች፤ እንደስኳር ፕሮጀክቶች አለመጓተታቸውን በምሳሌነት መጥቀስ ይቻላል። በሌላ በኩል ደግሞ ተመልከቱት። እቅዶች ቢጓተቱና ቢሰናከሉስ፤ የመንግስት ባለስልጣናትና የመንግስት ሰራተኞች ምን ያጣሉ? ሃብት በብክነትና በሙስና ቢጠፋስ ምን ይጎድልባቸዋል? ምንም! የወር ደሞዛቸው እንደሆነ አይቀርባቸውም። ታዲያ ለምን ብለው ይጠነቀቃሉ? የግል ቢዝነስ ላይ ግን፤ ሃብት እንዳይባክንና እንዳይዘረፍ የሚጠነቀቅ ይኖራል - አለበለዚያ ይከስራላ! ጉዳዩ የዚህን ያህል ግልፅ ነው። የመንግስት የቢዝነስ ፕሮጀክቶች፣ የማይሳኩትና የሚባክኑት አለምክንያት አይደለም። መንግስት ቢቀየር፤ ፓርቲ ቢፈራረቅ፣ የባለስልጣን ሹም ሽር ስናደርግ ብንውል፤ የተለየ ውጤት አይገኝም። በቃ! መንግስት ቢዝነስ ውስጥ ሲገባ፣ ኪሳራና ውድቀት ተከትለው ይመጣሉ - በየትኛውም ዘመን፣ በየትኛውም አገር - በስልጣኔ ደህና በተራመዱት አገራትም ጭምር። የዛሬ አመት፣ በአሜሪካ የተከሰቱ ሁለት አጋጣሚዎችን ላስታውሳችሁ እችላለሁ።
የአሜሪካ መንግስት በጤና አገልግሎት ኢንሹራንስ ውስጥ ይበልጥ እጁን እንዲያስገባ በ2002 ዓ.ም የወጣው አዋጅ፣ ተግባራዊ መሆን የጀመረው የዛሬ አመት በዚህ ሳምንት ነው። እንደ አጋጣሚ፣ በስኬታማ ቢዝነስ ታላቅ ትርፍና ክብር የተጎናፀፈው አፕል ኩባንያም በዚሁ ወር፣ እንደዘንድሮው ሁሉ አዳዲስ የአይፎን ምርቶቹን ለገበያ ማቅረቡን አትርሱ። ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ፣ ሁለቱን ክስተቶች በማነፃፀር ምን እንደተናገሩ ከመግለፄ በፊት፣ በቅድሚያ የጤና ኢንሹራንስ አዋጁ ምን እንዳስከተለ ልጥቀስላችሁ። አዋጁ ከፀደቀ በኋላ የተጨመሩ ከደርዘን በላይ ማሻሻያዎችና ጊዜያዊ ደንቦች ሳይቆጠሩ፣ አዋጁ ብቻ ከ900 ገፅ በላይ ነው። ውስብስብነቱ የዚያኑ ያህል ስለሆነ፤ የአዋጁ ይዘት ዛሬ ድረስ ገና ሙሉ ለሙሉ ተተንትኖ አይታወቅም። ለምሳሌ፣ ከአራት አመት በፊት የወጣው አዋጅ፣ “ለውርጃ የመንግስትን ድጎማ ይፈቅዳል” የሚል ክርክር የተነሳው ባለፈው ወር ነው - እስከዛሬ ሳይታወቅ ስለቆየ። ዋና ዋናዎቹ ነጥቦች ግን ይታወቃሉ። አንደኛ ነገር፤ እንደ ድሮው፣ ሰዎች ከገንዘብ አቅማቸው ጋር የሚመጣጠን የጤና ኢንሹራንስ መግዛት አይችሉም። በኢንሹራንስ የሚሸፈኑት የጤና አገልግሎቶች በእያንዳንዱ ሰው ምርጫና አቅም ሳይሆን በመንግስት “ስታንዳርድ” እንዲወሰኑ ያደርጋል - አዋጁ። ይሄ ከብዙ ሰዎች አቅም በላይ ስለሚሆን፣ መንግስት ድጎማ እንደሚያደርግ አዋጁ ይደነግጋል።  ገንዘቡ ከየት ይመጣል? በርካታ የአውሮፓ አገራት ውስጥ እንደሚደረገው፣ መንግስት እየተበደረ ወጪውን ይሸፍናል - በእዳ ክምር የኢኮኖሚ ቀውስ እስኪፈጠር ድረስ።
ሁለተኛ ነገር፣ ለጤንነትህ የምታደርገው ጥንቃቄና የህክምናህ ወጪህ ምንም ይሁን ምን፣ ለኢንሹራንስ የምትከፍለው ወርሃዊ መዋጮ ከሌሎች ሰዎች ጋር ተመሳሳይ ነው። አዎ፤ በዚህ ምክንያት ብዙ ሰዎች ለጤንነታቸው መጠንቀቅን ቸል ይላሉ። ለህክምና ወጪ ደንታ ቢስ መሆናቸው አይቀርም። እዚህ ኢትዮጵያ ውስጥ በ16 ቦታዎች ተሞክሮ ውጤቱ ምን እንደሆነ ሰምታችሁ ይሆናል፤ አመት ሳይሞላው፣ የህክምና ወጪ በሶስት እጥፍ ጨምሯል። በአሜሪካም መጠኑ ይለያይ እንጂ፣ አቅጣጫው ተመሳሳይ ነው። በቃ፤ ለትንሽ ለትልቁ፣ በሲቲ ስካን ካልታየሁ ብሎ ከሃኪም ጋር የሚሟገት ይበዛል። ይህም ብቻ አይደለም። የራስ ፀጉር ለማስተከል የሚፈልግ ራሰ በራ፣ የአፍንጫውን ቅርፅ ለማስለወጥ የሚመኝ ወጣት፣ የጡቷን መጠን “ለማስተካከል” የምትፈልግ ወይዘሮ... ዝርዝሩ ማለቂያ የለውም።
ሰዎች ከኪሳቸው የማይወጣ ገንዘብ ለማባከን፣ እልፍ አይነት “የፈጠራ” ሃሳብ እንደሚመጣላቸው አትጠራጠሩ - ያኔ የህክምና ወጪ ሰማይ ይደርስና ሁሉም ነገር ይፈራርሳል። አዋጁ፣ ይህንን የወጪ ፍንዳታ ለመከላከል እልፍ ቁጥጥሮችን ይዘረዝራል። ለምሳሌ፤ ሰዎች እንደየፍላጎታቸው የመታከሚያ ተቋማትን እንዳይመርጡ መገደብ፣ አንድ የወጪ መቆጣጠሪያ ዘዴ ሆኗል። ሰዎች፣ ምን አይነት ህክምና ማግኘት እንዳለባቸው፣ ምን አይነት መድሃኒት መግዛት እንደሚችሉ በቢሮክራቶች እየተመረመረ እንዲወሰን የሚያደርግ አሰራር መፍጠርም ሌላ ወጪ መቀነሻ ቁጥጥር ነው። አዋጁ፣ በእጅጉ የተወሳሰበውና 900 ገፅ ያልበቃው አለምክንያት አይደለም። እያንዳንዱ ሰው፣ ከነቤተሰቡ የራሱን ጤንነትና ወጪ ሲቆጣጠር አንድ ነገር ነው። መንግስት የእያንዳንዱን ሰው ጤንነትና ወጪ ለመቆጣጠር ሲሞክር ደግሞ፣ ሌላ ነገር ነው - 900 ገፅ የማይበቃው የቁጥጥር ውጥንቅጥ ይፈጠራል።
ለማንኛውም፤ ለጤና ኢንሹራንስ መመዝገቢያ ዌብሳይት በመንግስት ተዘጋጅቶ፣ በታላቅ ሆይሆይታ የተመረቀው አምና በዚህ ሳምንት ነው። በእርግጥ፣ በ95 ሚሊዮን ዶላር ይዘጋጃል ተብሎ የተጀመረው ዌብ ሳይት፣ ከሶስት እጥፍ በላይ ገንዘብ ፈጅቷል (290 ሚሊዮን ዶላር ገደማ)። ምን ይሄ ብቻ! ዌብ ሳይቱ ተመርቆ ሲታይ፣ በደንብ አይሰራም። “ሲታይ”? ...ዌብሳይቱን ከፍቶ ማየት ራሱ አስቸጋሪ ሆኖ አረፈው። መንግስት የዌብሳይቱን ችግር አልካደም። glitch እንዳጋጠመው ገልጿል። እዚህ ግባ የማይባል ትንሽዬ ችግር እንደ ማለት ነው። የዌብሳይቱ ችግር ግን “ትንሽዬ” አልነበረም። ለመመዝገብ የሞከሩ ሰዎች በአብዛኛው አልተሳካላቸውም። በአብዛኛው ማለት... 99% ማለት ነው።

መንግስት “ትንሽዬ እክል” ብሎ እያድበሰበሰ መቀጠል አልቻለም። ዌብ ሳይቱ በአንድ ጊዜ ከሃምሳ እስከ ስልሳ ሰዎችን ለማስተናገድ እንደተሰራ የገለፁት የመንግስት ባለስልጣናት፣ 250ሺ የሚደርሱ ሰዎችን በአንድ ጊዜ ለማስተናገድ ስላልቻለ ተንቀራፍፏል በማለት ለማስረዳት ሞክረዋል። መንቀራፈፍ ብቻ አይደለም። በመሃል ፀጥ ይላል፤ ከአገልግሎት ውጭ ይሆናል። በዚያ ላይ እስከ 60ሺ ሰዎችን በአንዴ የማስተናገድ አቅም እንዲኖረው ተደርጎ የተሰራው ዌብሳይት፣ ገና ሁለት ሺ የማይሞሉ ሰዎች ሲጠቀሙበት ነው የሚንቀራፈፈው። በጣም የሚገርመው፤ የዌብሳይቱ ቀርፋፋነት የታወቀው በምረቃው እለት ዋዜማ በተደረገ ሙከራ ነው። ግን፣ በሆይሆይታ ተመርቆ ተከፈተ፤ ለዚያውም ሃያ ሰላሳ ሚሊዮን ዶላር በወጣበት የምረቃ ስነሥርዓትና ድግስ። የግል ቢዝነስ እንዲህ አይነቱን ደንታ ቢስነት በእውኑ ይቅርና በህልሙም አይሞክረውም - ከስሮ እንደሚያርፈው ያውቀዋላ። የመንግስት ሲሆን ግን ችግር የለውም - አይከስርም። ኪሳራ ይኖራል፤ ኪሳራው ግን የባለስልጣናትን ወይም የቢሮክራቶችን ኪስ አይጎዳም። ዜጎች በሚከፍሉት ታክስ ይሸፈናል። እያደር ሲታይ ለካ የዌብሳይቱ ችግር፣ በቁጥርና በአይነት ጥቂት አይደለም - ዘርዝሮ ለመጨረስ ይከብዳል። ይልቅስ በዚሁ የመንግስት ፕሮጀክት ቀውስ መሃል፣ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ምን ብለው እንደተናገሩ ታውቃላችሁ? ዌብሳይቱ ትንሽ እክል እንደገጠመው የጠቀሱት ባራክ ኦባማ፤ የ“አፕል” ዌብሳይትም ሰሞኑን እክል አጋጥሞት እንደነበር እናስታውሳለን በማለት ማነፃፀሪያ አቅርበዋል። የአይፎን አምራች የሆነው አፕል ኩባንያ ነው ማነፃፀሪያቸው። በእርግጥም፤ ያን ሰሞን የአፕል ዌብሳይት ለአንድ ቀን ያህል ተጨናንቆ ነበር። እንደ መንግስት ዌብሳይት ለወራት እየተበላሸ አልተንፏቀቀም፤ ለአንድ ቀን ግን ተጨናንቋል። መቼ? አምና አዳዲስ ምርቶቹን (አይፎን 5 የተሰኙ ሞባይሎችን) ለገበያ ያቀረበ እለት ነው። ግን፤ 99% በመቶ ያህል ደንበኞቹን ማስተናገድ ያቃተው የመንግስት ዌብሳይት፤ ገና ሁለት ሺ ደንበኞች ሲጠቀሙበት ነው የተብረከረከው። የአፕል ዌብሳይት የተጨናነቀው ግን፤ በአንድ ቀን ውስጥ ከ2 ሚሊዮን በላይ ደንበኞችን በማስተናገድ፣ የግዢ ትዕዛዛቸውን በአግባቡ መቀበል እየቻለ ነው። ዘንድሮ አይፎን 6ን ለገበያ ባቀረበበት የመጀመሪያው እለት ደግሞ፤ ከ4 ሚሊዮን በላይ ደንበኞችን በዌብሳይቱ በማስተናገድ ሽያጭ አካሂዷል። የኦባማ ዌብሳይትና የአፕል ዌብሳይት ንፅፅር የዚህን ያህል የተራራቀ ነው - በአሜሪካም ቢሆን። በየትኛውም አገርና በየትኛውም ጊዜ፣ የመንግስት ቢዝነስ ውድቀትና የግል ቢዝነስ ስኬት የዚህን ያህል የሰማይና የምድር ርቀት አለው።ብሎኬት የሚያመርቱ የጥቃቅንና አነስተኛ ተቋማት ወጣቶች፣ ለአዲስ አበባ ቲቪ ያቀረቡትን ቅሬታ መስማት ትችላላችሁ። ለምሳሌ አንዱ ችግር ምን መሰላችሁ? መንግስት መቼ ሲሚንቶ እንደሚሰጣቸውና መቼ ብሎኬት እንደሚገዛቸው አይታወቅም። ለምን ራሳቸው ሲሚንቶ ገዝተው አይሰሩም? አይችሉም።

ምክንያቱም፣ የሚያመርቱትን ብሎኬት በቅናሽ ዋጋ ለመንግስት የመሸጥ “ግዴታ” ስላለባቸው፣ ሲሚንቶ ከገበያ ገዝተው ቢሰሩ ይከስራሉ። በቅናሽ የመሸጥ ግዴታ... ማለት እንዴት? እንግዲህ፣ የቤቶች ግንባታ በአብዛኛው በመንግስት ቁጥጥር ውስጥ ስለሆነ፤ አብዛኛውን ብሎኬት የሚገዛው መንግስት ነው። ታዲያ፣ እንደሌላው ገበያተኛ አይደለም። “ሲሚንቶ በቅናሽ ዋጋ እያቀረብኩ፤ ብሎኬት በቅናሽ ዋጋ እገዛችኋለሁ” የሚል መመሪያ አውጥቶላቸዋል - ለአነስተኛና ጥቃቅን አምራቾች። እናም፤ ሲሚንቶ እስኪያቀርብላቸው ድረስ እጃቸውን አጣጥፈው ይጠብቃሉ። ለሁለት ለሦስት ቀን ስራ የሚበቃ ሲሚንቶ ሲሰጣቸው፤ እሷን ተጠቅመው እንደገና ለሳምንታት ያህል በየቢሮው ለባለስልጣናትና ቢሮክራቶች አቤቱታ ማቅረብ ይቀጥላሉ። ያመረቱትን ብሎኬት ለመንግስት ለማስረከብና ክፍያ ለመቀበልም፤ ውጣውረዱና ደጅ ጥናቱ ቀላል አይደለም። በእርግጥ ውሎ አድሮ፣ ሰንብቶና ከርሞ... ትንሽ ሲሚንቶና ክፍያ ያገኛሉ። ለውጥ የሌለው አዙሪት ነው። ታዲያ፤ “መንግስት፣ እንዳንሞት እንዳንድን አድርጎናል” ቢሉ ይገርማል?

           የኢፌዴሪ ፕሬዚደንት ክቡር ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ ለሕዝብ ተወካዮችና ለፌዴሬሽን ምክር ቤቶች የጋራ ስብሰባ ንግግር በማድረግ የዓመቱን የሕግ አወጣጥ መርሐ-ግብር (Legislative Program) ማሳወቃቸው ይታወሳል፡፡ የዘንድሮው የፕሬዚደንቱ ንግግር ለየት ያለ ሃሳብ የተካተተበት መሆኑን አስተውያለሁ፡፡ ክቡር ፕሬዚዳንቱ በኢህአዴግ የሃያ አራት ዓመት የአስተዳደር ዘመን ተገልፆ የማያውቅ ቃል መናገራቸውንም አድምጫለሁ፡፡ ላለፉት ሃያ አራት ዓመታት እንዳየነው፣ ኢህአዴግ በታሪኩ በርዕሰ ብሔር ደረጃ ቀርቶ በተራ ካድሬ ደረጃ ሕዝብን በይፋ ይቅርታ ጠይቆ አያውቅም፡፡ ዘንድሮ ግን የመብራት መቆራረጥን በተመለከተ በክቡር ፕሬዚዳንቱ ንግግር ውስጥ በማካተት በይፋ ይቅርታ ጠይቋል፡፡
ኢህአዴግ ይህንን ያደረገው “ካንጀት” ይሁን “ካንገት” ባይታወቅም፤ በማወቅም ይሁን ባለማወቅ አሊያም ከአቅም በላይ በሆነ ምክንያት ለተፈጸመ ስህተት ይቅርታ መጠየቅ የስልጡንነት ምልክት እንጂ፣ ሽንፈትንም ሆነ ድክመትንም የሚያሳይ አይደለም፡፡ መሳሳትም ሆነ ድክመት በኢህአዴግ የተጀመረ ይመስል ኢህአዴግ ይህንን ቃል ለዘመናት ለምን ሲፈራውና ሲሸሸው እንደኖረ ግን ከቶም ሊገባኝ ያልቻለ ጉዳይ ነው፡፡ እነሆ! ዘንድሮ ይህንን እንደ መርግ የከበደ ቃል ከሀገሪቱ የመጀመሪያው ሰው (ከርዕሰ ብሔሩ) አንደበት ሰምተናል፡፡ እናም ይህንኑ ቃል መነሻ በማድረግ ይህቺን ማስታወሻ ለክቡር ፕሬዚዳንቱ ይድረስ ማለትን ወደደሁ፡፡
ክቡር ፕሬዝደንት! የማይሳሳት የማይሰራ ብቻ ነው፡፡ እናም ባቀረቡት ጥያቄ መሰረት እኔና ቤተሰቤ መንግስትዎን (መንግስታችንን) በይፋ ይቅር ብለናል፡፡ ይቅር ያልነው ዴሞክራሲያዊና ልማታዊ መንግስታችንን ፈርተንና ተሸማቀን ሳይሆን፤ ይቅርታ መጠየቅ የጀመረው ዴሞክራሲያዊና ልማታዊ መንግስታችን ይቅርታ መጠየቅ የሚያሳፍር መስሎት “ተሸማቆ” ይቅርታ መጠየቅ እንዳያቆም በማሰብ ነው፡፡
ክቡር ፕሬዝደንት! የእርስዎን ፕሬዝዳንታዊ ንግግር ካዳመጥን በኋላ “እውነት የመብራት መቆራረጥ ብቻ ነው እንዴ ይቅርታ ሊጠየቅበት የሚገባው ጉዳይ?” የሚለውን ጥያቄ እኔና ቤተሰቤ አንስተን ተወያይተናል፡፡ ለቀረበው የይቅርታ ጥያቄ “ይቅር” ብንልም ይቅርታ ሊጠየቅበት የሚገባው ጉዳይ ግን “የመብራት መቆራረጥ” ብቻ አለመሆኑን በታላቅ አክብሮት ልንገልጽልዎ እንወዳለን፡፡ የእኛ ይቅርታ እርስዎ ለዜጎች እንደሚያደርጉት ይቅርታና ምህረት “ፍትህ ሚኒስቴር ይየው፣ መንግስት ያቅርበው፣ ምናምን…” ማለት ስለማያስፈልገው በኛ በኩል ይቅርታ ላልቀረበባቸውም ጉዳዮች ሁሉ ይቅር ብለናል፡፡ እያንዳንዱ ቤተሰብ የእኛን ፈለግ ተከትሎ ይቅር እንደሚልም ተስፋ እናደርጋለን፡፡
ክቡር ፕሬዝደንት! “ይቅርታ ሊጠየቅበት የሚገባው ጉዳይ የመብራት መቆራረጥ ብቻ አይደለም” የምንለው ከመሬት ተነስተን አይደለም፡፡ ይህንን ለማስረገጥ በርካታ አብነቶችን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ይሁን እንጂ፣ የእርስዎንም የዚህን ጋዜጣ አንባቢዎችንም ጊዜ ላለማባከን ከመብራት፣ ከውሃና ከትራንስፖርት ጋር የተያያዙ ጥቂት ማሳያዎችን ብቻ አነሳለሁ፡፡
እኔና ቤተሰቤ የምንኖረው በኦሮሚያ ክልል፣ ፊንፊኔ ዙሪያ ዞን፣ ለገዳዲ - ለገጣፎ ከተማ ነው፡፡ የለገዳዲ - ለገጣፎ ከተማ ከአዲስ አበባ (ፊንፊኔ) ጋር ያለው ቅርበት የዓይንና የአፍንጫን ያህል ነው፡፡ በሁለቱ ከተሞች መካከል ያለው ድንበር የጣሊያኗን ሮም እና የቫቲካን ሲቲን እስኪመስል ድረስ ተገጣጥመዋል፡፡ በዚህም ምክንያት በቤት ኪራይ የተማረሩ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ወደ ታዳጊዋ ለገጣፎ ተሻግረው መኖር ከጀመሩ ሰነባብተዋል፡፡ ለገጣፎ ብቻ ሳትሆን በአጠቃላይ በፊንፊኔ ዙሪያ ያሉ ከተሞች የአዲስ አበባን ችግር እያቃለሉ በመሆኑ፤ ቀደም ሲል የነበሩት የእነዚህ ከተሞች መሰረተ ልማቶች በበቂ ሁኔታ የሕዝቡን ፍላጎት መሸከም አልቻሉም፡፡ ከነዚህ የመሰረተ ልማት ችግሮች አንዱ መብራት ነው፡፡
ክቡር ፕሬዝደንት! እርስዎ በዓመታዊ ንግግርዎ የጠቀሱት “የመብራት መቆራረጥ”ን በተመለከተ ነው፡፡ የለገጣፎ-ለገዳዲ ከተማ ችግር ግን የመቆራረጥ ችግር ብቻ አደለም፡፡ ቀድሞ ነገር መብራት መቼ ገባልንና ነው የሚቆራረጠው ክቡር ፕሬዝደንት?! መቆራረጥ ብቻማ ቢሆን ያው እን’ዳገር እንሆን ነበር፡፡ ከአዲስ አበባም ከመብራት ኃይልም ጓሮ የምትገኘውና የአዲስ አበባን ችግር ባልጠና ጀርባዋ የተሸከመችው የለገጣፎ-ለገዳዲ ከተማ ሰማንያ በመቶ የሚሆነው ነዋሪዋ በቤቱ የመብራት ቆጣሪ አልገባለትም፡፡
ክቡር ፕሬዚደንት! የመብራት ጎርፍ በደጃፋችን አልፎ በሰሜንም በደቡብም ያሉ የገጠር ከተሞችን ብርሃን በብርሃን ሲያደርግ እዚሁ ፊንፊኔ ጓሮ ተቀምጠን ሰማይ ጠቀስ የመብራት ኃይል ምሰሶዎችን ተደግፈን እንቆዝማለን፡፡
በኩራዝም በፋኖስም፣ በሻማም በእንጨትም በደህና ከምንኖርበት ሁኔታ መብራት ኃይል “አለሁላችሁ” ብሎ እንድንጠቀም አደረገን፡፡ ከተማችን እየሰፋች ስትመጣ መብራት ኃይል “የእናቴ ቀሚስ አደናቀፈኝ” ማለት አበዛ፡፡ እዚህ ላይ ‘ታዲያ እንዴት ሆናችሁ ነው እየኖራችሁ ያላችሁት?’ የሚል ጥያቄ ይነሳ ይሆናል፡፡ በኔ የመሀይም ግምት ሰማንያ በመቶ የሚሆነው የለገዳዲ-ለገጣፎ ነዋሪ በአሁኑ ወቅት መብራት የሚያገኘው ቀደም ሲል መብራት ከገባላቸው ወንድሞችና እህቶች በቀጫጭን ገመዶች እየወሰደ ነው፡፡  
አንዴ በግንድ፣ ሌላ ጊዜ በስኒ፣ ቆየት ብሎ በቆጣሪ፣… መታጣት እየተመካኘ ለገዳዲ-ለገጣፎ መብራት አሮባታል፡፡ ክቡር ፕሬዝደንት! እግር ጥሎዎት ወደ ለገጣፎ ቢመጡ በቀጫጭን ሽቦዎች፣ በቀጫጭን አጣናዎች ሁለት ሦስት ኪሎ ሜትር አቆራርጠው የሚሄዱ የመብራት ገመዶችን፤ አሊያም ከወዲያ ወዲህ፣ ከወዲህ ወዲያ የተዳወሩ የመብራት ገመዶች የሸረሪት ድር መስለው ሊመለከቱ ይችላሉ፡፡
ይህ ብቻ አደለም፤ ሰሞኑን በመንደራችን ስዘዋወር ምን እንዳየሁ ያውቃሉ ክቡር ፕሬዝደንት!? መብራት በአንዲት መስመር ብቻ ከአንዱ ቤት ወደ ሌላው ሲወሰድ ነው ያየሁት፡፡ ነገሩ ገረመኝና “ሁለተኛው መስመር የት አለ?” በማለት ጠየቅሁ፡፡ “ና ጉድ ተመልከት!” አሉና እውነትም “ጉድ” አሳዩኝ፡፡ ጫፏ ወሃ በያዘች ኩባያ ውስጥ የተነከረች አንዲት የኤሌክትሪክ ገመድ አሳዩኝ፡፡ መቼስ ኤሌክትሪክ ብርሃን የሚሰጠው በፖዘቲቭ እና በኔጋቲቭ (በእሳትና በውሃ ይሉታል ባለሙያዎች) መስመሮች አይደል?... አዎ! እሳቱን ከጎረቤት ውሃውን ከቤት አቀናጅቶ መብራት ያገኛል የለገዳዲ-ለገጣፎ ሕዝብ፡፡ ነገሩ የጨነቀው እርጉዝ ያገባል እንዲሉ ነው፡፡ በጥንቃቄ ጉድለት ሊደርስ የሚችለውን አደጋ ግን አስቡት! - በተለይ ምንም በማያውቁት ሕፃናት ላይ…!
የመብራት ነገር ከተነሳ አይቀር አንድ ነገር ልጨምር፡፡ ክቡር ፕሬዝደንት! በለገጣፎ ከተማ አንዲት አምፑል የመንገድ መብራት የለም፡፡ በአካባቢያችን ያን ያህል የከፋ ወሮበላ ባያስቸግረንም እኛን ብቻ ሳይሆን እኛን አልፎ አዲስ አበቤውን እያስቸገረ ያለው የጅብ መንጋ ሕፃናት ልጆቻችንን ሸክፈን ገና በአስራ ሁለት ሰዓት ቤታችን እንድንከተት እያደረገን ነው፡፡ ከመሸ መንቀሳቀስ ችግር ነው፡፡ የአካባቢው አርሶ አደር ልጆች የማታ ትምህርት መማር አልቻሉም፡፡
በእርግጥ እነዚህ ችግሮች የአካባቢያችን መስተዳደር የሥራ በድርሻ መሆኑን እገነዘባለሁ፡፡ ክቡር ፕሬዝደንት! እነሱስ ቢሆኑ በበላይ አካል “እንዲህ አድርጉ” ቢባሉ ምን ይላቸዋል? እንዲያውም ፕሬዝዳንታዊ ቃል ከንጉሳዊ ቃል የሚለይ ስለሆነ ተሰሚነቱ የላቀ ነው፡፡
ክቡር ፕሬዝደንት! የከተማችን አመራር ከኮብል ስቶንና ከውሃ ወይም ከመብራት ለእኛ የትኛው መቅደም እንዳለበት እንኳ ስላልገባው፣ ውሃና መብራቱን ትቶ የኮብል ስቶን መንገድ ሲሰራና ሲመርቅ ይውላል፡፡
እግራችንን ጭቃ እንዳይነካው ከሚጨነቅ ለሆዳችን ቢጨነቅልን የተሻለ ነበር፡፡ አብስለን የምንመገብበት ውሃና መብራት ትኩረት እንዲያገኝ ቢያደርግልን ወግ ያለው ሥራ ነው፡፡ ጭቃውን በቦት ጫማ እንወጣዋለን፡፡ እናም የኮብልስቶን በጀት ለጊዜው ወደ መንገድ መብራት እንዲለወጥልን በእርስዎ አማካይነት እናመለክታለን - ክቡር ፕሬዝደንት!
ወደ ውሃ ጉዳይ እንለፍ፡፡ ከአዲስ አበባ ነዋሪ ግማሽ ያህሉ የውሃ ፍጆታውን የሚያገኘው በእኛው ቀበሌ ከሚመረተው ከለገዳዲ የውሃ ግድብ እንደሆነ መገመት የሚቻል ይመስለኛል፡፡ ውሃን በተመለከተ እስከ ሰማንያ በመቶ ለሚሆነው የለገዳዲ ለገጣፎ ነዋሪ ከሞላ ጎደል የውሃ ቆጣሪ ገብቶልናል፡፡ ፈጣሪም መንግስትም ይመስገን! ውሃ የምናገኘው ግን በአስራ አምስት ቀን አንድ ጊዜ ነው፡፡
 በእኛው በራሳችን መንደር መንጭቶ በበራችን እየተንፎለፎለ በሚወርደው ውሃ፣ ከእኛ ማዶ ያሉ ወገኖች እንደልባቸው እየተጠቀሙ፣ እኛ እንደ መብራት ሁሉ የበይ ተመልካች መሆናችን ሀዘናችንን መሪር ያደርገዋል፡፡
ከጀሪካን የዘለለ የውሃ መያዣ ለሌለን ምስኪኖች የውሃ ቆጣሪ አስገብቶ፣ ውሃን በአስራ አምስት ቀን አንድ ቀን መስጠት፣ ሥጋ ሰጥቶ ቢላ መንሳት አይሆንም ክቡር ፕሬዝደንት? እዚያው ውሃው ዳር ስለሆናችሁ፣ እንስራችሁን ይዛችሁ መቅዳት ትችላላችሁ በሚል ስሌት ይሆን ይህ ግፍ በእኛ ላይ የተጫነው? የውሃ ልማት መስሪያ ቤት፤ የውሃ መስመሩን ከዘረጋ በኋላ የውሃ እጥረት አጋጥሞት ከሆነ፣ እንደ እኛ ላለ የውሃ መያዣ ሮቶ መግዛት ለማይችል ህብረተሰብ ጥቂት የቦኖ ውሃ ማሰራጫዎችን በየአካባቢው ቢያቆምልን ምን አለበት? ክረምቱንስ ከቆርቆሮ ጣሪያ የሚገኘውን ውሃ ጭምር እያጠራቀምን ችግሩን አለፍነው፡፡ የበጋው ነገር ገና ከወዲሁ እያሳሰበን ስለሆነ ለመንግስታችን አቤት እንላለን፡፡
በመጨረሻ የማነሳው የትራንስፖርት ጉዳይ ነው፡፡ ክቡር ፕሬዝደንት! በሕገ-መንግስታችን አንቀጽ 49 ንዑስ አንቀጽ 5 መሰረት፤ እንደ ለገጣፎ ያሉ በፊንፊኔ ዙሪያ ያሉ ከተሞች ከአዲስ አበባ የሚያገኙት የአገልግሎት ድጋፍ እንደሚኖርና በህግ እንደሚደነገግ ተቀምጧል፡፡
 በዚሁ መሰረት፣ እዚሁ አጠገባችን አያት አደባባይ የደረሰው የአዲስ አበባ ከተማ ባቡር ወደ ለገጣፎ እንዲሻገርና እኛም ተጠቃሚ እንድንሆን መጠየቅ ቅንጦት ስለሚሆን፣ ለጊዜው እሱ ይቅርና ከአዲስ አበባ የሚነሱ የከተማ አውቶቡሶች ቁጥር ይጨምርልን፡፡
በተለምዶ “ሐይገር” የሚባሉት መካከለኛ አውቶቡሶች ይመደቡልን፡፡ የታክሲዎች አገልግሎት ተጠናክሮ ይቀጥልልን የሚለውም መልእክት ለአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን ይነገርልን፡፡  
በአጠቃላይ፤ የእኛ ነገር ከሌሎች አካባቢዎች ጋር ሲነጻጸር፣ “እናቱ የሞተችበት እና ገበያ የሄደችበት እኩል ያለቅሳል” እንዲሉ ነው ክቡር ፕሬዝደንት! እናም ለሁለቱ ምክር ቤቶች ባቀረቡት ንግግርዎ ላይ “የመብራት መቆራረጥን በተመለከተ መላውን ሕዝብ ይቅርታ እንጠይቃለን፤ በተለይ የለገዳዲ-ለገጣፎ ነዋሪዎችን…” የሚል ማሻሻያ ሞሽን እንዳላቀርብ (በነገራችን ላይ ሕዝብም ሞሽን የማቅረብ መብት እንዳለው የምክር ቤቱ ደንብ እድል ይሰጣል) አሁን ጊዜው አለፈ፡፡ ብቻ ችግራችን በዚህ መልኩ እንዲታይልን ለመንግስትዎ እናመለክታለን፡፡

የፖለቲካ ሳይንስ ምሁሩና የኢትዮጵያ ፌደራላዊ አንድነት መድረክ (መድረክ) ሊቀመንበር የሆኑት ዶ/ር መረራ ጉዲና፤ “በውጭ ያሉ ኢትዮጵያውያንን የፖለቲካ እንቅስቃሴ” በተመለከተ አሜሪካ ውስጥ ላለፉት ስድስት ወራት ጥናት ሲያደርጉ ቆይተው በቅርቡ ወደ አገራቸው ተመልሰዋል፡፡ በአሜሪካ ስለነበራቸው ቆይታ፣ ስለ ጥናታቸው፣ እንዲሁም በሃገሪቱ ወቅታዊ የፖለቲካ ጉዳዮች ዙሪያ ከአዲስ አድማስ ከፍተኛ ሪፖርተር አለማየሁ አንበሴ ጋር ያደረጉት ቃለ-ምልልስ እንዲህ ቀርቧል፡፡

ላለፉት ስድስት ወራት አሜሪካ ቆይተው ነው የመጡት፡፡ የጉዞዎ አላማ ምን ነበር?
“ናሽናል ኢንዶውመንት ፎር ዲሞክራሲ” በተባለ የአሜሪካ ተቋም ውስጥ ጥናት ሳደርግ ነው የቆየሁት፡፡ ዲሞክራሲ እና የኢትዮጵያ ዳያስፖራን በተመለከተ በተለይ በኢትዮጵያ ውስጥ በሚደረገው ዲሞክራሲያዊ ትግል ውስጥ ያላቸውን ሚና ማየት ነበር የጥናቱ ዓላማ፡፡ የአሜሪካ ዋና ከተማ ዲሲ ውስጥ የኢትዮጵያ ሁለተኛ ዋና ከተማ በሚመስል ደረጃ ነው ኢትዮጵያውያኖች ያሉት፡፡ እዚያ አካባቢ ፖለቲካው ያገባናል ብለው የሚንቀሳቀሱትን አግኝቻለሁ፡፡ እንደ ሲያትል፣ ሳንዲያጎ፣ ላስቬጋስ፣ ሳንፍራንሲስኮ፣ ሚኒሶታ፣ ዳላስ፣ ፊላደልፊያ በመሳሰሉት የአሜሪካ ከተሞች ተዛዙሬም ኢትዮጵያውያንን አነጋግሬያለሁ፡፡ በዚያውም ለፓርቲያችን ድጋፍ ለማሰባሰብ ሞክሬያለሁ፡፡ ከሞላ ጎደል በውጭ ያለው ዳያስፖራ በሀገሩ ፖለቲካ ላይ እንዴት ነው? የሚለውን ነው ያየሁት፡፡ በ“ኢሳት” እና በ“ቪኦኤ” እንዲሁም በ“ኦሮሞ ሚዲያ ኔትዎርክ” ላይ የኢትዮጵያን ፖለቲካ በተመለከተ በስፋት ቃለምልልሶችንና ክርክሮችን ለማድረግ ሞክሬያለሁ፡፡ መጨረሻ ላይም አሜሪካውያንና ኢትዮጵያውያን በተገኙበት መድረክ ላይ የጥናት ውጤቱን አቅርቤአለሁ፡፡
መሰረታዊ ችግሮቻችንን ለመፍታት ከኢትዮጵያ መንግስት፣ በውጭው ዓለም ከሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ከዓለም አቀፍ ማህበረሰብ ምን ይጠበቃል በሚሉት ሶስት መሰረታዊ ነገሮች ላይ ነው አስተያየት ለማቅረብ የሞከርኩት፡፡
በወቅቱ ፕሬዚዳንት ኦባማ፣ የአፍሪካ አምባገነን መሪዎችን ሰብስቦ ሲያነጋግር፣ እኔ ጥናት ያቀረብኩበት ዲሞክራቶች የሚመሩት ናሽናል ዲሞክራቲክ ኢንስቲቲዩት፣ እንዲሁም ዊልሰን ሴንተርና ፍሪደም ሴንተር የሚባሉ ተቋማት በጋራ የአፍሪካ ሲቪል ማህበረሰብ አባላትን ሰብስበው ነበር፡፡ በጣም ሰፊ ስብሰባ ነው፡፡ በመድረኩ ላይም ስለ አፍሪካ መሰረታዊ ችግሮች ማለትም ስለ ምርጫ፣ ስለ ፍትህ፣ ስለ ሰብአዊ መብት አከባበር… ሃሳቦች ተንፀባርቀው ውይይት ተደርጓል፡፡ በዚህ ስብሰባ ላይም በተናጋሪነት ተሳትፌያለሁ፡፡ እንግዲህ እነዚህን ስራዎች ስሰራ ነው የቆየሁት፡፡
በዳያስፖራው ላይ ባካሄዱት ጥናት ምን ውጤት አገኙ?
ምንም ጥያቄ የለውም፤ ከዳያስፖራው ጋር በሁለት ነገሮች ላይ መግባባት ያስፈልገናል፡፡ እንደሚታወቀው ያለ ዳያስፖራው ድጋፍ መንቀሳቀስ ይከብዳል፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ አሁን ባለው የፖለቲካ ምህዳር፣ ከሃገር ውስጥ የፋይናንስ ድጋፍ ማግኘት የሚቻልበት ደረጃ ላይ አይደለንም፡፡ የዳያስፖራው ድጋፍ ያስፈልገናል፡፡ ዳያስፖራው ግን ድጋፉን ሲሰጠን ውሃ ልኩን ካላወቀ፣ ሃገር ውስጥ የሚደረገው ትግል መልኩን ሊስት ይችላል፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ የሚደረገውን ሰላማዊና ህጋዊ ትግል፣ ዳያስፖራው በውጪ ደረጃና ሚዛን ካየው እንዲሁም እንደዚያ ተንቀሳቀሱ ካለ፣ አገር ውስጥ በዚያ ደረጃ መንቀሳቀስ ስለማይቻል፣ ብዙ ተስፋ የመቁረጥ ዝንባሌ ይከሰታል፡፡ ይሄንንም በጥናቴ ተመልክቻለሁ፡፡ ሌላው ደግሞ ዳያስፖራው በሚሰጠው ድጋፍ መጠን በሚፈልገው አቅጣጫ ግፋበት የማለት ዝንባሌ ይታያል፤ እሱም ያስቸግራል፡፡ ከሁሉም በላይ ግን አስቸጋሪው ዳያስፖራው በተለይ በብሄር የመከፋፈሉ ነገር ነው፡፡ በብሄር ብሄረሰቦች ጥያቄ ዙርያ ዳያስፖራው ሃገር ውስጥ ካለነው በበለጠ ተከፋፍሏል፡፡   ምን ዓይነት ዲሞክራሲያዊ ለውጥ መምጣት አለበት በሚለው ላይ ሀገር ውስጥ ያሉት ተቃዋሚዎችም ሆኑ ዳያስፖራው ስምምነት ላይ ካልደረሱ፣ ለዲሞክራሲ የሚደረገውን ትግል ወደፊት ለመግፋት ይቸግራል፡፡ በዳያስፖራው እና በሃገር ውስጥ ባለው ተቃዋሚ መካከል ኢትዮጵያ እንዴት ወደ ዲሞክራሲያዊ ስርአት ትሂድ በሚለው ላይ መግባባት መፍጠር ያሻል፡፡
ዳያስፖራው በፖለቲካ ብቻ ሳይሆን በሃይማኖትም ጭምር እስከ መከፋፈል ደርሷል በማለት የሚተቹ ወገኖች አሉ፡፡ እርስዎ በጥናትዎ ምን ታዘቡ?
ከሃይማኖት ይልቅ በፖለቲካው ውስጥ ያለው ክፍፍል፣ በተለይ በብሄረሰቦች ጥያቄ ዙርያ ሁለት ፅንፍ አለ፡፡ መሃል መንገድ ላይ የሚሰባሰቡ ኃይሎች ተፈጥረው፣ የኢትዮጵያን ዕጣ ፈንታ ሊወስን የሚችል ዲሞክራሲያዊ ትግልን መልክ ማስያዝ እስካልቻሉ ድረስ ያለማጋነን የሁለት ፅንፎች እስረኛ እንሆናለን፡፡ አንዱ ኢትዮጵያ የሚባል ነገር አልሰማም ይላል፤ ሌላው ደግሞ የኢትዮጵያዊነት ሰርተፍኬት ሰጪም ከልካይም እኛ ነን ባይ ነው፡፡ ያ ደግሞ አገር ውስጥም ይንፀባረቃል፡፡ እነዚህ ነገሮች መልክ እንዳይዙ ያደረጉት የገዥው ፓርቲ ቀጥታም ሆነ ስውር እጆች ናቸው፡፡ ኢትዮጵያ በሃገር ደረጃ ያለባት ፈተናም ይሄን የማለፍ እና ያለማለፍ ነው፡፡
ይሄ የዳያስፖራው ሁኔታ ሀገር ውስጥ ባሉ ተቃዋሚዎች ላይ የሚያሳድረው ተፅዕኖ ምንድን ነው?
በዚህ ምክንያት በአጠቃላይ ትግሉ ተጎድቷል፡፡ ክርር ወዳለው መስመር የመሰባሰብ ችግር አለ፡፡ አብዛኛው ሰውም በዚህ ሃይል ስር ነው፡፡ ይህ ደግሞ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ሃገር ውስጥ ባለው ትግል ላይ ተፅዕኖ አለው፡፡ ለዚህ ደግሞ ተጠያቂው ገዥው ፓርቲ ነው፡፡ የፖለቲካ ምህዳሩን ባጠበበ ቁጥር ወደዚህ መሰሉ እንቅስቃሴ ብዙዎች መግባታቸው አይቀርም፡፡ ብሄረሰቦች እየተቻቻሉ፣ የተሻለች ዲሞክራቲክ ኢትዮጵያን እንዳይፈጥሩ ያደረገው ገዥው ፓርቲ ነው፡፡ የገዥውን ፓርቲ አቅጣጫ መለወጥ ካልቻልን የትም አንደርስም፡፡ የፖለቲካ ምህዳሩን የማስተካከል ኃላፊነት በግድም ሆነ በውድ የገዥው ፓርቲ ነው፡፡ በዳያስፖራው አካባቢ ላለው የከረረ ፖለቲካ ምንጩ ምንድን ነው? የሚለውን መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡ ዋናው ምንጭ የፖለቲካ ምህዳሩ መጥበቡ፣ ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ የሚካሄድበት መድረክ መፈጠር ያለመቻሉ፣ ነፃ ሃሳብ የሚንሸራሸርበት ሚዲያ አለመኖሩ፣ በቀላል ቋንቋ ገዥው ፓርቲ “ስልጣን ወይም ሞት?” በሚለው አቋሙ መቀጠሉ ነው ይሄን የፈጠረው፡፡ ትግሉን ወደ ውጪ ያስወጣው እኮ ራሱ ገዥው ፓርቲ ነው፡፡ ጋዜጠኞችን፣ ፖለቲከኞችን የሚያሳድደውና ሰው ወደ ውጭ እንዲያይ የሚያደርገው ገዥው ፓርቲ ነው፡፡ አገር ውስጥ ያለው ነገር ቢስተካከል የኢትዮጵያ ፖለቲካን ትግል ይዞ አሜሪካ ወይም አውስትራሊያ አሊያም ሌላ ሃገር የሚሄድበት ምክንያት የለም፡፡ ይሄ አካሄድ ደግሞ ገዥውን ፓርቲም ቢሆን እየጠቀመው አይደለም፡፡ በዋናነት የኢትዮጵያ ፖለቲካ እንዲሰደድ ያደረገው ገዥው ፓርቲ ነው፡፡ ገዥው ፓርቲ የኢትዮጵያ ፖለቲካ እንዳይሰደድ ከፈለገ፣ እዚህ ያለውን የፖለቲካ ምህዳር መክፈትና ማስፋት አለበት፡፡
በአብዛኛው በዳያስፖራው አካባቢ የሚደረገው ትግል እየሰፋ የሚሄድበትና በዚያው መጠን ፖለቲካው የሚከርበት ምክንያት ምንድን ነው? የሚለውን ብዙ ሰው እየረሳ ነው፡፡ እዚህ ያለው የፖለቲካ ምህዳር ስለጠበበ፣ ስለማያሰራ፣ ወጣቶችን፣ ጋዜጠኞችን፣ ፖለቲከኞችን ስለሚያሳድድ ውጪ እየሄዱ እየተደራጁ፤ ውጪም ብቻ ሳይሆን ጫካም እየሄዱ እየተደራጁ፣ ባገኙት መንገድ ትግሉን መቀጠል ስለሚፈልጉ ነው፡፡
የዳያስፖራው ትግል ሃገር ውስጥ ባለው ስርአት ላይ ተጨባጭ ተፅዕኖ የመፍጠርና ለውጥ የማምጣት አቅም አለው ብለው ያስባሉ?
ኢትዮጵያ ውስጥ ከሚደረገው ትግል ካልራቀ ምንም ጥርጥር የለውም፤ ተጨባጭ የሆነ ለውጥ ማምጣት የሚችልበት እድል አለው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ የሚደረገውን ትግል በሃብት ሊረዳ ይችላል፡፡ በእውቀት፣ በዲፕሎማሲና በብዙ መንገድ ሊረዳ ይችላል፡፡ የኢትዮጵያ ባለስልጣናትም ጭምር አሁን የሚደረገውን የዳያስፖራውን ትግል እንደቀላል እያዩት አይደለም፡፡ ዳያስፖራው እኮ ምናልባትም የእነሱም የመጪው ጊዜ መኖሪያ ሊሆን ይችላል፡፡ ብዙ የኢትዮጵያ መንግስት ባለስልጣናት፣ ብዙ ወጪ እያወጡ ዳያስፖራ ውስጥ ኑሮአቸውን ለመመስረት እየሞከሩ ነው፡፡ የደርግ ባለስልጣናት ዛሬ ኑሮአቸው ዳያስፖራ ውስጥ ነው፡፡ ባለስልጣናት በሚሄዱበት ሃገር ምን እየገጠማቸው እንደሆነ እያየን ነው፡፡ እኛን በሃገራችን መኖር እንዳንችል አድርጋችሁ እናንተ እዚህ መቀመጥ አትችሉም እየተባሉ ነው፡፡ እነ ጁነዲን ሳዶ እኮ እየተደበቁ ነው የሚኖሩት፡፡ ሃገር ውስጥ ለሰሩት ወንጀል ምናልባት በህግ ልንጠየቅበት እንችላለን እያሉ ይጨነቃሉ፡፡ በሃገሪቱ ኢኮኖሚ ላይም የዳያስፖራው ሚና ቀላል አይደለም፡፡ በዓመት 4.5 ቢሊዮን ብር ወደ ሃገር ውስጥ ይልካሉ፡፡
በቅርቡ በአሜሪካ በሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ከባንዲራ ጋር በተያያዘ ስለተፈጠረው ሁኔታ ምን ይላሉ?
የባንዲራው ጉዳይ ውስጥ ብዙ መግባት አልፈልግም፡፡ ኢህአዴግም ቢሆን ከማንም በላይ የባንዲራ ጠባቂ ነኝ ሊል የሚችል ድርጅት አይደለም፡፡ በተለይ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ስለባንዲራ ምን ይሉ እንደነበር ይታወቃል፡፡ ኢህአዴግ ያን ያል  የባንዲራ አስከባሪ መሆን አይችልም፡፡ ዋናው ነገር ኤምባሲዎች አካባቢ እንደዚያ ያለ ነገር ገፍቶ ከቀጠለ በአጠቃላይ ጥሩ ምልክት አይደለም፡፡ የሃገሪቱ ያለመቻቻል ፖለቲካ እዚያ ድረስ ሄዶ ሁላችንንም በማያስከብር መልኩ እየተንፀባረቀ ነው፡፡ ስለዚህ የኢትዮጵያ መንግስት የፖለቲካ ምህዳርን በመዝጋትና በማፈን ብዙ ነገሮችን አደርጋለሁ የሚለውን ደጋግሞ ቢያስብበትና ጩኸቱንም ቢሆን እዚሁ ሃገር ቤት ብንጯጯህ ይሻላል፡፡
ዳያስፖራው በተቻለው ሁሉ አሜሪካ በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ተፅዕኖ እንድታሳርፍ ሲጥር መቆየቱ ይታወቃል፡፡ ከዚህ በተቃራኒው በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ከፕሬዚዳንት ኦባማ ጋር ያደረጉትን ውይይት ተከትሎ በሰጡት መግለጫ፤ “ወዳጅነታችን ተጠናክሯል፣ ውጤታማ ውይይትም አድርገናል” ብለዋል፡፡ በዚህ ዙሪያ የእርስዎ አስተያየት ምንድነው?
የአሜሪካ መንግስት ባለስልጣናት ፍቅራቸውና ሌላ ነገራቸው ብዙም አያሳስበኝም፡፡ እኔ የሚያሳስበኝ የቤት ስራችንን መስራትና አለመስራታችን ነው፡፡ እኔ ፖለቲካል ሣይንስ በተለይም የውጪ ፖሊሲ ላይ አስተምራለሁ፤ እናም “አሜሪካኖች ቋሚ ጥቅም እንጂ ቋሚ ፍቅር የላቸውም፡፡” ለምሣሌ የግብጽ መንግስት ገና መናጋት ሲጀምር “በስልጣን ላይ ያለው መንግስት ወዳጃችን ነው” እያሉ ሲቀባጥሩ ነበር፡፡ ኋላ ላይ ግን ኦባማ “ሠላማዊ ተቃዋሚን መግደል ወንጀል ነው” ብሎ ተናገረ፡፡ ከዚያ በኋላ ጨዋታው ተቀየረ፡፡ ስለዚህ ዋናው ነገር ኢትዮጵያውያን በጋራ ትግሉን ማጠናከራቸው ነው፡፡ ያ ከሆነ የአሜሪካ መንግስት ትግሉን የማይደግፍበት ምንም ምክንያት የለም፡፡ አሁን ሁለቱን መንግስታት ያወዳጀው የሽብር ጉዳይ ነው፡፡ ይሄ በግልጽ ይታወቃል፡፡ በፀረ-ሽብር ጨዋታ ውስጥ ተጠላልፈው ገብተው እያደረጉ ያለው ነገር ግልጽ ነው፡፡ ነገር ግን ዋናው እኔን የሚያስጨንቀኝ የኢትዮጵያ ተቃዋሚ ሃይሎች፣ የኢትዮጵያ የዲሞክራሲ ሃይሎችና የኢትዮጵያ ሕዝብ የራሱን የቤት ስራ እየሰራ ነው? ለራሱ መብት፣ ክብርና ነፃነት እየታገለ ነው ወይ? የሚለው ጉዳይ ነው፡፡
ካነሱት አይቀር አሁን ያለውን የተቃዋሚ ሃይሎች ፖለቲካ፣ የህዝቡን ፍላጐት እና የገዥው ፓርቲን ሁኔታ እንዴት ይገመግሙታል?
 ሁሉም ፓርቲ የአቅሙን ያህል እየሰራ ነው፡፡ የመከፋፈል ፖለቲካው ግን አሁንም ቀጥሏል፡፡ ብዙ ፓርቲዎች የ97ቱን የመሠለ እንቅስቃሴ መፍጠር አልቻሉም፡፡ ያን ጊዜ ቢያንስ ሁለት ስብስቦች መፍጠር ተችሎ ነበር፤ አሁን ግን ሙከራዎች ቢኖሩም ወደፊት የሚያስኬድ አይመስልም፤ ክፍፍሉ አሁንም አለ፡፡ ነገር ግን ነፃና ፍትሃዊ የሚባለው አይነት የምርጫ ስርአት ከተዘረጋ ምንም ጥርጥር የለውም፣ ኢህአዴግ በአንድ ወር እንቅስቃሴ ይሸነፋል፡፡ ይሄን በሰሞኑ የመምህራን ስልጠና ላይም ተናግሬዋለሁ፡፡ ኢህአዴግን ለማሸነፍ ቀላል ነው፡፡ ዋናው ጉዳይ ኢህአዴግ በአንድ በኩል ተቃዋሚዎች ተዳክመዋል ይላል፤ መቼም ሰይጣን አይደለም ተቃዋሚዎችን የሚያዳክመው፤ ኢህአዴግ ራሱ ነው፡፡ አሞሌና ዱላ ይዞ የሚዞረው ኢህአዴግ ነው፡፡ በአሞሌ ያልወደቀ በዱላ ይወድቃል፡፡ ኢህአዴግ አሞሌና ዱላ ይዞ መዞር ካቆመ፣ እሱን ማሸነፍ ትልቅ ነገር አይደለም፡፡ ይልቁንስ ከዚያ በኋላ ሃገር ለመምራት ተቻችሎ፣ ተግባብቶ የጋራ የፖለቲካ አጀንዳ ቀርፆ ለመንቀሳቀስ ይቻላል ወይ የሚለው ነው እኔን የሚያሳስበኝ፡፡
ኢህአዴግን ለማሸነፍ ያስቸግራል የሚል ግምት ግን የለኝም፡፡ ዋናው ኢህአዴግ የራሱን ዳኛ ይዞ ወደ ጨዋታ ሜዳ አለመግባቱ ነው፡፡ አሁን ዳኛም ተጫዋችም ነው፡፡ ሁልጊዜ ዳኛም ተጫዋችም ሆኜ እቀጥላለሁ ካለ ግን ምናልባትም እኛም ኢህአዴግም የማንፈልገው ነገር ኢትዮጵያ ውስጥ ሊፈጠር ይችላል፡፡
በአንድ በኩል ምርጫ ቦርድ ገለልተኛ አይደለም የሚል ትችት ከተቃዋሚዎች ሲሰነዘር ይደመጣል፡፡ እነዚያው ፓርቲዎች ግን ባላመኑበት ምርጫ ሲሳተፉ እንመለከታለን፡፡ ቦርዱ ገለልተኛ አይደለም ካሉ በኋላ በምርጫው መሳተፍ ተገቢ ነው ይላሉ?
ሁለት ነገር ነው ያለው፡፡ ተቃዋሚ ስንል ህዝብ ተቃዋሚ ናቸው ብሎ የሚያምንባቸውን ነው እንጂ ኢህአዴግ የሚቀልባቸውን ማለት አይደለም፡፡ እነዚህ ፓርቲዎች ይህ አይነቱ አዙሪት እንዲያበቃ በጋራ “አንሳተፍም” የሚል አቋም መያዝ አለባቸው፡፡ ብዙ ጊዜ እንዲህ ያለ ሃሳብ ማግኘት ያስቸግራል፡፡ አንዱ ትልቁ ችግር ይሄ ነው፡፡ ለምሣሌ በ2002 ምርጫ መድረክ አካባቢ የተሠባሰብነው ወደ ምርጫ ያለመግባት ሃሳብ ነበረን፤ ነገር ግን መኢአድ የስነምግባር ደንቡን በመፈረሙ፣ የተቃዋሚዎችን የጋራ አቋም ስላላገኘን፣ ጨዋታው ከሚበላሽብንና የፖለቲካ ትርፍ ቢገኝ ብለን ገባንበት እንጂ ውጤት ያመጣል ብለን አይደለም፡፡ የ97 ምርጫን ካየን፣ ህብረት በጨዋታው ሜዳ ላይ ተደራድሯል፡፡ የሚፈለገውን በአንድነት ገፍተን ባናገኝም የተወሰኑ ጥቃቅን ነገሮች ተሻሽለዋል፡፡
የሚዲያ አጠቃቀምን ማንሳት እንችላለን፡፡ በወቅቱ ኢህአዴግ የቆመበት መሬት እስኪከዳው ድረስ የገፋነው በሱ ነው፡፡ የ2002 ምርጫ ላይ ግን መግባቱ ጥቅም አልነበረውም፡፡ አሁንም የተቃዋሚዎች ሙሉ አቋምና ውሣኔ እስካልተገኘ ድረስ አንዱ ገብቶ ሌላው ሲቀር አስቸጋሪ ነው፡፡ አንዳንዴ መቀመጫም ባናገኝ የፖለቲካ ጥቅም ለማግኘት የምንገባበት አጋጣሚም አለ፡፡ ሌላው ሁለት ምርጫ ላይ ያልተሳተፈ ይሰረዛል የሚል ህግ አለ፤ ያንን በመፍራትም ይገባል፡፡
አሁንስ የ8 ወር እድሜ ለቀረው የ2007 ብሔራዊ ምርጫ የተቃዋሚዎች ዝግጅት ከኢህአዴግ አንፃር እንዴት ይታያል?
ተቃዋሚዎች ዝግጅት ይኖራቸዋል፤ ነገር ግን ዋናው ጉዳይ የፖለቲካ ምህዳሩ እስካልሰፋ የትም አይደረስም፡፡ የ2007 ምርጫን ከአሁኑ ገምግም ከተባልኩ፣ ምናልባት ኢህአዴግ የተወሰኑ የመቀመጫ ፍርፋሪዎችን ለተቃዋሚዎች ለቆ እንደገና አሸነፍኩ ሊል ይችላል፡፡ ያ ማሸነፍ ለኢትዮጵያም፣ ለኢህአዴግም ለሁሉም የሚጠቅም አይመስለኝም፡፡ ምንጊዜም ህዝብን ተስፋ አታሳጣ፤ ህዝብን ተስፋ ካስቆረጥከው ተስፋ የቆረጠ ስራ ውስጥ ሊገባ ይችላል፡፡ አሁንም ሃገር ውስጥም ሆነ ውጪ ብዙ ነገሮች ጤናማ አይደሉም፡፡
ቀደም ብለው እንደነገሩኝ፤ በአሜሪካ ቆይታዎ ኢሣት ቴሌቪዥን ላይ ሰፊ ቃለ ምልልስና አስተያየት ሰጥተዋል፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት ደግሞ ጣቢያውን የ“አሸባሪዎች” ልሣን ነው በማለት የፖለቲካ ድርጅቶች ከጣቢያው ጋር ያላቸውን ግንኙነት እንዲገቱ አስጠንቅቋል፡፡ ከዚህ አንፃር ጉዳዩ ስጋት ውስጥ አልከተትዎትም?
“ኢሣት” እንግዲህ የኢህአዴግ ወዳጅ ሃገር በሚባለው አሜሪካ በነፃ ተመዝግቦ የሚንቀሳቀስ ጣቢያ ነው፡፡ ድጋፍ ከማህበረሰቡ እያሰባሰበ ነው የሚሠራው፡፡ እዚያ ጣቢያ ላይ መረራ የራሱን አስተያየት ነው የሰጠው እንጂ የኢሣትን ፕሮፓጋንዳ አይደለም ያንፀበረቀው፡፡
በአጠቃላይ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ላይ ነው አስተያየቴን የሰጠሁት፡፡ ኢሣት ጠመንጃ የለውም፣ የትጥቅ ትግልም እያካሄደ አይደለም፡፡
 ስለዚህ እኔ እንደ ከባድ ነገር አላየውም፡፡ በነገራችን ላይ የኢህአዴግ ባለስልጣናትም አልፎ አልፎ አስተያየት ይሰጣሉ፡፡ የኢትዮጵያ ሬድዮና ቴሌቪዥንን ባያፍን እኮ “ኢሣት” ጋ የምሄድበት የተለየ ምክንያት የለኝም፡፡ የውጪ ሚዲያ ጋ እንዳንሄድ ከፈለገ፣ የሀገር ውስጡን ይስጠን፡፡ መረራ “ኢሣት”ን ባይጠቀም ሌሎች ብዙ ሺህ ምሁራን ይጠቀሙበታል፡፡ እንደሚታወቀው የኛ ፓርቲ የሽብር ፕሮጀክት የለውም፤ በሰላማዊና ህጋዊ መንገድ ነው የሚታገለው፡፡ “ኢሳት” ላይ የምናገረው ሃገር ውስጥ ባለው ቴሌቪዥን ጣቢያ እንድናገር እድል ቢሰጠኝ የምናገረውን ነው፡፡ እኔ ውጪም ሆነ ውስጥ ቋንቋዬ አንድ ነው፡፡

(ዘልኤ አይቤ ጋዬ - ዎሬ አይቤ ቁፌ) የወላይታ ተረት

ከላፎንቴን ታሪኮች አንዱ እንዲህ ይለናል፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን የሰማይ ቁጣ በእንስሳት ላይ እየመጣ ነው ስለተባለ የዱር እንስሳት ተሰብስበው ማ አጠፋ? ማ አጠፋ? በመባል ጥፋተኛውን አጋልጠው ለመስጠት አውጫጪኝ ይቀመጣሉ፡፡ እንስሳት ሁሉ ለረሀብ ተጋልጠው የእርስ በርስ ፍቅራቸው ሁሉ ሞቷል፡፡ ሁሉ ተኮራፍፏል፡፡ ተኩላ ከተኩላ እርግብ ከእርግብ እንኳ አይነጋገሩም! ከመጣው መዓት ለመዳን ሁላችሁም ሀሳብ ስጡ ተባለ፡-
አንበሳ ወንበሩን ያዘና በሊቀመንበርነት፡-     
“ወዳጆቼ ሆይ! የሰማይ ቁጣ ጥፋተኞች ላይ መውረዱ ደንብ ነው፤ አንቃወመውም፡፡ ነገር ግን ሁሉ ኃጢያት እኩል አይደለምና የበለጠና የከፋ ኃጢያት የሰራውን መለየት ይኖርብናል! ያ ጥፋተኛ ቅጣቱን ሲቀበል ለእኛ ስርየት፣ መዳኛ ይሆንልናል! ህሊናችንን ሳናጭበረብር ዕውነቱን እንናገር፡፡ እኔ በበኩሌ  ጥቂት ያስቀየሙኝን በጎች በልቻለሁ - አንዳንዴም እረኞቻቸውንም የቀመስኩበት ጊዜ ነበረ፡፡ ወድጄ አይደለም ስላስቀየሙኝ ነው፡፡ ይህ ጥፋት ነው ካላችሁ ሞት ይፈረድብኝ፡፡ ብቻ ዋናው ነገር ሌሎቻችሁም ኃጢያት ኃጢያታችሁን ተናዘዙ፡፡ ድርሻ ድርሻችሁን ውሰዱ፡፡ ከዚያ የከፋ ጥፋት የሰራውን እንለያለን፡፡ (It is only fair that all should do their best
to single out the guiltiest)”
ከዚያ ቀበሮ ተነሳና
“ንጉሥ ሆይ! ለእንደ ርሶ ያለ የተከበረ የዱር አራዊት ጌታ፤ በግ መብላት በጭራሽ ሀጢያት ሊሆን አይችልም፡፡ እነዚህን ባለጌና ልክስክስ በጎች መብላት ፈፅሞ ሊያስጠይቅ አይገባም፡፡ እረኞችም ቢሆኑ በእኛ ላይ ሲዶልቱ የሚኖሩ ናቸውና የእጃቸውን ነው ያገኙት” ብሎ ተቀመጠ፡፡ ጭብጨባው ቀጠለ፡፡
ቀጥሎ ማንም በነብር፣ በድብና በመሳሰሉት ክቡር እም ክቡራን ይቅርታ - የለሽ ወንጀል ላይ ምንም ሀሳብ ሳያነሳ ጭራሽ እንዲህ ያለ የተቀደሰ ተግባር የፈፀመ ከዚህ የለም፤ እየተባለ ውዳሴው ተዥጎደጎደ፡፡
በመጨረሻ አህያ ተነሳች፡-
“አንድ ቀን አንድ ሰፊ የሣር መስክ ሳቋርጥ ረሀብ አንጀቴን ቢመዠርጠኝ የምላሴን ያህል ቅንጣት ሳር ግጬ አልፌያለሁ፡፡ ያንን ሳር የመጋጥ መብት እንደሌለኝ በእርግጥ አውቃለሁ” አለች፡፡
ሁሉም እጃቸውን እያወጡ በአህያ ላይ የእርግማን መርግ ይጭኑባት፣ ይወርዱባት ጀመር፡፡ አንድ የተማረ፣ ብዙ ያነበበ የሚባል ተኩላም ተነስቶ፤
“ከዚህ በላይ በዓለም ላይ ኃጢያት ተሰርቶ አያውቅም፡፡ የኃጢያቶች ሁሉ ኃጢያት የሰው ሣር መጋጥ ነው! የሁላችንንም ኃጢያት ልትሸከም የሚገባት ይህቺ አህያ ናት! ቁጣውም እሷ ላይ መውረድ አለበት፡፡ የተንኮል ሁሉ ደራሲ እሷ ናት! ፎ! የሰው ሳር እንዴት ይጋጣል?! ስለዚህ ሞት ነው የሚገባት! ሆኖም አንድ ሀቅ ልጨምር ብሎ በግጥም ቀጠለ፡፡
“ሀብታም ሆንክ ደሀ፣
ክክቡር ነህ የተባልክ ወይ ከንቱ ቁጥር
ሁልህ ይደርስሃል የተራህ ሥፍር
ችሎት ይቀባሃል፣ ወይ ነጭ ወይ ጥቁር!”
                                              *         *         *
ፍሬድሪክ ኒች “ከመጥፎ ሥራ ጋር አብሮ ከመኖር ከመጥፎ ህሊና ጋር አብሮ መኖር ይከብዳል” ይላል፡፡ በሌላው ላይ በጅምላ ስምምነት፣ በመንገኝነት መፍረድ ትልቅ ኃጢያት ነው፡፡ ውሎ አድሮ እንቅልፍ መንሳቱ አይቀሬ ነው፡፡ ከህሊና ጋር በእፎይታ ማደር፣ ያለ አንዳች ወንጀለኝነት ስሜት አንገትን ቀና አድርቶ ለመሄድ መቻል ታላቅ ጸጋ ነው፡፡ የራስን አሳር የሚያህል የተቆለለ ወንጀል አድበስብሶ አንዲትን ቀጭን ሽፋን አጋኖ በሌላው ላይ መደፍደፍ አገር ገዳይ ነው! ህዝብ አሰቃይ ነው፡፡
“በክፉ ሰዓት የእናት ልጅ አይታመንም!” ይላል አበሻ ሲተርት፡፡ በክፉ ሰዓት የማ ባህሪ መቼ እንደሚቀየር አይታወቅም፡፡ በክፉ ሰዓት የትኛው ወዳጅ ተገልብጦ ጠላት እንደሚሆን አይታወቅም፡፡ ብዙ የፌሽታ ጊዜ ጓደኞች ጊዜ ከምበል ሲል አብረው ይከነበላሉ! ዕበላ - ባዮች፣ አቋም - የለሾች፣ አድር-ባዮች፣ አሥጊና አጥፊዎች ናቸው የሚባለው ለዚህ ነው፡፡ ስለሆነም ለህዝብም ለአገርም አይበጂም!
በጥንታዊት ቻይና የዌይ ግዛተ - መንግስት አንድ ለንጉሱ ታማኝ ሚሱ ሳይ የሚባል ባለሟል ነበር፡፡ የግዛቱ ህግ “የንጉሱን ሰረገላ በሚስጥር የነዳ ሰው እግሩ ቆረጣል” ይላል፡፡ ያ ታማኝ ሰው እናቱ ትታመምና ልትሞት ታጣጥራለች፡፡ ሊደርስላት የንጉሡን ሰረገላ ምንም አይሉኝም ብሎ እየነዳ ሄደ፡፡ ንጉሡ ይሄን ሲሰሙ “አይሱ ሳይ! እጅግ ኃላፊነት የሚሰማው ሰው ነው፡፡ ለእንቱ ሲል እግሮቹን እንደሚያጣ ረሳ!” አሉ፡፡ ታማኝ ሰዎች ታማኝነታቸው የት ድረስ መብት እንደሚሰጣቸው የረሱ‘ለት ራሳቸውን ያጣሉ ነው ትምርተ - ታሪኩ (Lesson/Moral of the story እንዲሉ ፈረንጆች፡፡)
የሀገራችን ፕሮጀክት ቀራጮች፣ ንድፈ - ሀሳብ አንጓቾች (theoreticians) አማካሪዎች፣ ስትራቴጂስቶች፣ ቀዳሽ ዳሳሾች በእርግጥ ከልባቸው ለህዝብና ለአገር ተቆርቁረው ነው ወይ ሥራውን የሚሰሩት ብሎ መፈተሸ የአባት ነው! ማ በተዘዋዋሪ ወገንተኛ ነው? ማ ልታይ ልታይ እያለ ከሙሰኞች ጋር የተሰለፈ ነው? ማ አፍአዊ፣ ማ ልባዊ ነው? ማ አጉራሽ አልባሽነትን እንደትራንስፎርሜሽን እያስቆጠረ ነው? ውስጣችንን እንፈትሽ፡፡ አንደበተ - ርቱዑን ከበቀቀኑ እንለይ፡፡
ፖለቲካችን፣ ኢኮኖሚያችን፣ ማህበራዊ ግንኙነታችን በአስመሳይ ሰዎች ሲታጠር ህይወታችን ጉድፍ የተሞላ፣ በደል የበዛው፣ ዕድገታችን ሀሳዊ፣ ፍቅራችን ነውር ያጎደፈው፣ ተስፋችን ጨለግላጋ፣ የጋራ ቤታችን የተራቆተ እንደሚሆን ገሀድ ነው፡፡ ምን እየዘራን ምን እያጨድን እንደሆነ በቅጡ ልብ እንበል፡፡ “ንግድ ምንድንነው? ትንባሆ፤ ትርፉ ምንድን ነው? - ሳል” የሚለውን የወላይትኛ ተረት አበክረን እናስምርበት!

Published in ርዕሰ አንቀፅ

የቡርኪናፋሶ ፕሬዚዳንት “ለምሳ ያሰቡንን ለቁርስ አደረግናቸው” ሰለባ ሆኑ!
ከ27 ዓመት የስልጣን ዘመን በኋላም ስልጣን አልጠገቡም!
 “የዜግነት ሰብአዊ ክብር ከመግፈፍ የበለጠ በጥባጭነት አለ?” - መረቅ

          ሰሞኑን በዚህችው ባልታደለችው አፍሪካችን (አለመታደል ነው ኋላቀርነት?) አንድ አሳዛኝ ክስተት ተፈጽሟል፡፡ የምስራች ዜና ባይሆንም ነገርዬውን እንደሰማችሁት እገምታለሁ (ዕድሜ ለቴክኖሎጂ!) እናላችሁ… ቡርኪናፋሶን ላለፉት 27 ዓመታት የገዙት የአገሪቱ ፕሬዚዳንት፤ በ2015 በሚካሄደው ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ለመሳተፍ የሚያስችላቸውን የህግ ማሻሻያዎች (መጨመር፣ መቀነስ፣ መሰረዝና መደለዝን ያካትታል) ለማድረግ ሞከሩ፡፡ ይሄም ነው የአሳዛኝ ክስተቱ መነሻ ሰበብ፡፡
ለነገሩ በፕሬዚዳንቱም አይፈረድም (ሱስ እኮ ነው!) አያችሁ…ሰውየው በ27 ዓመታት የቤተመንግስት ኑሮ የስልጣን ጥማቸው አልረካም (ድሮስ ሙጋቤን!) እናም… በአቋራጭ የስልጣን ጥማቸውን ለማርካት ጥረት አደረጉ (ብዙ እኮ አላጠፉም!) የአገሪቱን ህግ ለማሻሻል (በ “ህጋዊ መንገድ” ማለት ነው!) የቡርኪናፋሶ ህዝብ ግን ታክቶታል መሰለኝ… ሊታገሳቸው አልፈቀደም (ይሄኔ ብዙ ችሏቸዋል!) ፕሬዚዳንቱ እንደሃሳባቸው ቢሆን በቀጣይ ምርጫ ለመሳተፍ የሚያስችላቸውን የህግ አንቀፅ ባለፈው ሐሙስ በፓርላማ ያስፀድቁ ነበር፡፡ ግን ተቀደሙ፡፡ (ማን ነበር “ለምሳ ያሰቡንን ለቁርስ አደረግናቸው” ያለው?!)
ህዝቡ ሰሞኑን ለተጨማሪ ዓመታት በስልጣን ላይ የመቆየት ጥማታቸውን በመቃወም አደባባይ የወጣ ሲሆን ፓርላማውን በእሳት እንዳጋየ ተዘግቧል፡፡ (ይሄም ሌላ የኋላቀርነታችን ምልክት ነው) ሃይል …ዱላ…እሳት …ጥይት…ታንክ …መድፍ …ጥላቻ …ኢሰብአዊነት…ጭካኔ… ወዘተ ካልተደባለቁበት ተቃውሞን መግለጽ አንችልም፡፡ የአፍሪካ መንግስታትም ካላሰሩና ካልገደሉ የተቆጡ አይመስላቸውም (ሲቆጣ የሚገድል መንግስት ያለው አፍሪካ ውስጥ ነው!) አሁን በአገሪቱ የድንገተኛ ጊዜ አዋጅ የታወጀ ሲሆን በአፋጣኝ የሽግግር መንግስት ተቋቁሞ በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ እንዲካሄድ ተወስኗል፡፡ ህዝቡ ፕሬዚዳንቱ አሁኑኑ ከስልጣን እንዲወርዱ እየጠየቀ ሲሆን እሳቸው ግን አንድ ዓመትማ እገዛችኋለሁ እያሉ ነው፡፡ (“የቆጡን አወርድ ብላ የብብቷን ጣለች” ነው የሆኑት!) እኔ የምለው… እኛ አፍሪካውያን ከስልጣኔና ከዲሞክራሲ ጋር በቅጡ የምንተዋወቀው መቼ ይሆን? (እንደ ኢህአዴግ “ዲሞክራሲ ሂደት ነው” እንዳትሉኝ!) ለማንኛውም ለቡርኪናፋሶ “ሂደት” ምናምን የሌለው ሰላምና መረጋጋት ተመኝተን፣ ወደ ራሳችን ገበና እንዝለቅ (ዲሞክራሲን መጋት ወይም በክትባት መስጠት አይቻልም!)
እኔ የምላችሁ… የዝነኛውን ደራሲ የአዳም ረታን አዲስ ልቦለድ አነበባችሁ? “መረቅ” የተሰኘውን ባለ 600 ምናምን ገጽ ማለቴ ነው፡፡ እኔ መቼም እንደሱ ብዙ የሚያመርት (prolific) የጦቢያ ደራሲ አላውቅም፡፡ (ይችልበታል ነው የምላችሁ!) “መረቅን” ከቀደምት ሥራዎቹ የሚለየው ደግሞ ፖለቲካ ላይ የሚያተኩር መሆኑ ነው (የፖለቲካ መረቅ በሉት!) መጽሐፉ የ60ዎቹን የተማሪ አብዮት ተከትሎ እንደ አሸን የፈሉትን ታጋይ ፓርቲዎች ሚና ያስቃኛል - በገፀ ባህርያቱ በኩል፡፡ አልአዛር የተባለው ዋና ገፀ ባህርይ በደርግ መንግስት በፀረ አብዮተኛነት ተጠርጥሮ በታሰረ ወቅት፣ አንድ መቶ አለቃ የወታደር ካድሬ እውነቱን እንዲያወጣ እንዴት እንደሚያስፈራራው እንመልከት:-
“…አየህ አገሬ በጦር ቢመጡባት ትመልሳለች፡፡ ከልጆቻችን ጋር አብሮ ከበላ ከጠጣ ቦርቧሪ ጋር መታገል ግን ትንሽ አያስቸግርም? እኔ የዋህ አይደለሁም፡፡ እንዲህም አይነት አፍራሾች በአንተ አይነቱ ቀዳዳ ተጠቅመው ነው የሚመጡት፡፡ ኑጐች የሚመጡት ከሰሊጥ ተደባልቀው ነው፡፡ ያን ቀዳዳ መድፈን አለብኝ፡፡ አሁን እተውሃለሁ፡፡ አንዳንዴ ቂል መመታት አለበት፡፡ “አውቃለሁ” የሚል ቂል ከጠላት ያላነሰ አደገኛ ነው፡፡ ደደብነት ከቦንብ ሊብስ ይችላል፡፡ አስብበት፡፡ ካልተጠነቀቅህ እንደ ኑግ ትወቀጣለህ፡፡ ከዛ በኋላ ስህተቱ የእኔ አይደለም፡፡ ፋሺሽት ፋሺሽት ብትለኝ አይገባኝም፡፡ የሚገባቸው ቢኖሩ በአንተ አይነት ከብት የሚጠቀሙ ናቸው፡፡ ትክክለኛ ዜጋ ነህ? ወይስ ማንም አገር ቆራሽ የሚነዳው ከብት? “ከብት አይደለሁም” ካልክ ማረጋገጫ እፈልጋለሁ፡፡ ተግባባን? የአገር ሕልውና ላይ ዲሞክራሲ፣ ሰብአዊ መብት ቀባጢሶ አይሰራም… ማንም ከሕግ አያመልጥም፡፡ የአገሬ ሕልውና ነጋሪት ጋዜጣ ውስጥ አይደለም ያለው፡፡ ታሪክና ጥይት ውስጥ ነው፡፡ “ወታደር መሃይም ነው” አይደለም የምትሉት? የእናንተን ትምህርት አላየን፡፡ በፖለቲካል ሳይንስ ባችለር ዲግሪ አለኝ፡፡ ትከሻዬ ላይ የምታየው ምልክት የመቶ አለቃ ሊሆን ይችላል፡፡ ምሁር ለመሆን አትሞክርብኝ፡፡ አሁን ወረቀት ይመጣልሃል፡፡ እዚያ ወረቀት ላይ ሆቴል ተቀምጣችሁ ያወራችሁትን ትዝ የሚልህን አንድ ሳታስቀር ታሰፍራለህ፡፡ እኔ “ሰላማዊ አይደለህም” እላለሁ፡፡ አንተ “ነኝ” ትላለህ፡፡ ቀላል ነው፡፡ የምናመሳክረውን እናመሰናክራለን፡፡ እኔ ስላጋጠምኩህ እድለኛ ነህ፡፡ መተባበር ካላማረህ መንገድ መንገድ አለ፡፡ ከምትነግረንና ከምትፅፈው ኑግ ወይም ሰሊጥ መሆንህን ማወቅ አለብን፡፡ ይገባሃል የምልህ? ማርክሲዝም ስለ ሰሊጥ አያውቅም፡፡ አንድ ቦታ አሳየኝ ማርክሲስቶች ስለ ኢትዮጵያ የፃፉበትን ቦታ፡፡ ለእኔ ጋቢ የለበሰ አድሃሪ ሱፍ ከለበሰው ማርክስ የሚሻል አይመስለኝም፡፡ አንተ ማርክሲስት ሆንክ አልሆንክ ግድ የለኝም፡፡ ዕውነቱን እፈልጋለሁ፡፡ ተግባባን? መግባባት ማለት እኔ የማዝህን ማድረግ ማለት ነው፡፡ መግባባት ማለት እውነቷን ሳታስቀር መናገር ማለት ነው፡፡ ይሄን እዚህ ላይ ማፈንዳት እችላለሁ…”
ገባችሁ አይደለ… ምን እንደሚያፈነዳ? አፉፋ (ፊኛ) አይደለም$ ጥይት ነው፡፡ የወታደር መንግስት ወይም አምባገነን ገዢ ይሄው ነው፡፡ መጽሐፉን መቃኘት እንቀጥል፡፡ በነገራችሁ ላይ የአዳም ረታን “መረቅ” ፖለቲካዊ ልቦለድ ብየዋለሁ (ታሪካዊ ልቦለድ እንደሚባለው) አሁን ደግሞ የአላዛር አባት በፖለቲካ ውስጥ እጁ የሌለበት ልጃቸው ጉዳይ ሲያሳስባቸው የሚሉትን እንስማ፡፡ ተባረኪ የተባለች አብሮ አደግ ፍቅረኛው ግን ቀንደኛ ኮሙኒስት ናት - የኢህአፓን ካፓ የደረበች፡፡ የፖለቲካ ድርጅት  ፍቅር አስክሯት ፍቅረኛዋን አላዛርን የዘነጋች፡፡ አሁን ግን ወደ አላዛር አባት ምክር ልውሰዳችሁ፡፡ “…በሚያነዱት እሳት የተማረው ጥቂት ወጣት እንዲነድ ነው፡፡ ፖለቲከኛ ባትሆን እንኳ በወታደር አስጠምደው ሊያጠፉህ የሚፈልጉ መአት ናቸው፡፡ አገሪቷ አሁን ጥምዝዝ ያለ የወሬ በሽታ ውስጥ ናት፡፡ “ምሁሩ በመሰደድ ላይ ነው” ይላሉ፡፡ አገራችን ብዙ ምሁር የላትም - የሚንጋጋም፡፡ የፖለቲካውን አለም ያሽከረክራሉ የሚባሉትን አንዳንዶቹን አውቃለሁ፡፡ ማክረር ይወዳሉ፡፡ በግድ ቼ ጉቬራን እንሁን ብሎ ነገር፡፡ አገሪቷ ቬትናም ብትሆን ደስ ይላቸዋል፡፡ “ለምን?” ብትል ሆ ቺ ሚንን ለመሆን ይቀላቸዋል፡፡ ሌላው አለም ያሉ ግለሰቦች ጀግና የተባሉበትን ነገር ባያስፈልግም እዚህ ቢያደርጉ ደስ ይላቸዋል፡፡ በዚያ ብናደንቃቸው ይወዳሉ፡፡ ሺህ አይነት የአገርና የኢትዮጵያ ካባ ቢያለብሱት አንድ ነገር አውቃለሁ፤ ቂል አይደለሁም I am not a fool. አንተም እንድትሆን አልፈልግም፡፡ በግድ “እንጣላ” ብሎ ነገር ፍለጋ አለ? ኢትዮጵያ ጠላቶቿ ላይ እንኳን አክራሪ አይደለችም፡፡ ሃይማኖታችንና ቋንቋችን የተዳቀለ ነው፡፡ ይሄ ልዩ ሊበራሊዝም ነው፡፡ የትም አገር የለም፡፡ ምን ማለት ነው? ኢትዮጵያ ጠላቶቿ ላይ እንኳን አክራሪ አይደለችም፡፡ ሃይማኖታችንና ቋንቋችን የተዳቀለ ነው፡፡ ይሄ ልዩ ሊበራሊዝም ነው፡፡ የትም አገር የለም፡፡ ምን ማለት ነው? እንዲህ የሚያባላ ነገር የለም ማለት ነው፡፡ አንዳንድ አለባበስ አበላልን ምናምን የመሰለ ከባዕድ እንደሚቀዳ ልክ እንደ ጆሊ ጃኪዝም ምናምን በለው ፖለቲካውን…፡፡ መተማማት መጋደልና መሰዳደብ አኮሳተረው እንጂ ውስጡ ያው ነው፡፡ የፖለቲካ ጆሊ ጃኮች ናቸው፡፡ ወደ ፓስታ ሊለወጡ የሚለፉ ድፎ ዳቦዎች ናቸው፡፡ አሁን የማየውና የምሰማው ሁሉ ልክ አይደለም፡፡ አንድን ነገር ሳይመረምር በተራ ልዩነት ላይ ተመስርቶ ሺት የሚሰጥህ ገና ያላደገ ልጅ ነው፡፡ ያውም ሪታርድድ የሆነ፡፡ ልዩነትን በቋንቋ በማግነን በማይሆን ነገር ቶሎ ተገዳድሎ መስዋዕት በመፍጠር፣ የአላማ ነገር ተትቶ (ቀድሞም የለም) በነዚህ በፈጠሩአቸው ሰማዕታት ስም ለዘላለም እንድንቀያየም የሚፈልጉ ይመስላል… ስለዚህ ጊዜህን አታጥፋ፣ ለተባረኪ አትጨነቅ፡፡ ማታ ማታ እሷን ስትጠብቅ አይሃለሁ…  ፍቅር ከሁለት በኩል ሲመጣ ነው፡፡ በአንተነትህ ሳይሆን በፖለቲካ አቋምህ የምትወደድ ከሆነ እርሳው፡፡ የተለወጠችው እሷ ናት፡፡ ቆንጆ ባገሩ ሞልቷል፡፡ የሆነች ዘጠዘጥ ቂጣም፡፡ “ሶሪ ሺ ዳዝንት ሃቭ ክላስ” እኔ እንደውም ድሮ ከፀናፅል ጋር ነበር የጠረጠርኩህ፡፡ (እሷም ሌላ አብሮ አደጉ ናት!) ለማንኛውም በፍቀር መፍረድ አልችልም፡፡ ግን ለራስህ በቶሎ ስለ ላይፍህ መወሰን ካልቻልክ፣ ጣልቃ መግባት አለብኝ፡፡ ሁለተኛ በሃሳብ ባክነህ በመንገድ ላይ ብቻህን እያወራህ ስትሄድ ማየት አልፈልግም፡፡”
ይሄ ሁሉ የአባትየው ዲስኩር ለሌላ አይደለም፤ ልጃቸውን ከፖለቲካ እሳት ለማትረፍ ነው…እናም በሚያውቁት ባለስልጣን በኩል ለትምህርት ወደ ምስራቅ ጀርመን ሊልኩት እንዳሰቡ ይነግሩታል፡፡ ብቸኛ የመኖሩን ተስፋ ኢህአፓ የተባለ ድርጅት ስለነጠቀው ለመሄድ አላመነታም፡፡ ፍቅረኛው ተባረኪን ለኢህአፓ ያለ አደራ አስረክቦ ጀርመን ገባ (ሶሻሊዝምን ሽሽት ወደ ሶሻሊስት አገር!)
እስቲ አሁን ደሞ የአላዛርን ንፁህ ፍቅር በኢህአፓ የለወጠችው ተባረኪ የምትለውን እንስማት…ስለ ፖለቲካ፣ ስለ እነ ማርክስ፣ ስለ “ለጭቁኑ ህዝብ መታገል”፣ ስለ መስዋዕትነት ወዘተ…
”ፖለቲካ ለአገር ማሰብ ነው፡፡ ፖለቲካ መታደል ከተጨመረበት ለአገርና ውስጥዋ ለሚኖረው ለሕዝብ መልካም ለመስራት መጣር ነው፡፡ “ከራስ በላይ ነፋስ” በሚባለው ነገር አላምንም፡፡ ከራስ በላይ ቤተሰብ፣ ዘመድ፣ ሰፈር፣ ወረዳ፣ አውራጃ፣ ክፍለሀገርና አገር አሉ፡፡ የቻለበትም አህጉርና አለምን በልቦናው ይከታል፡፡ የአገራችን አንድ የሚታይ ማንም የሚያወራባት ፀባይዋ በደሃና በተራራ የተሞላች መሆኗ ነው፡፡ አንድ ሰው በአገሩ ደሃ መሆን የለበትም፡፡ ቢያንስ መሰረታዊ ፍላጐቶቹና መብቶቹ መጠበቅ አለባቸው፡፡ የድሆች መናጢነት የሚመጣው ሰነፍ ስለሆኑ አይደለም፡፡ የለፉበት ውጤት በጥቂት ማን አለብኝ ባዮች ስለሚዘረፍ ነው፡፡ እነዚህም ዘራፊዎች ዝርፊያቸውን ያለ ሃሳብ ለማካሄድ ማስፈራራትንና ራሳቸው ያወጡትን ሕግ ይጠቀማሉ፡፡ ድሆች ወይም ጭቁኖች መብታቸውን ለማስከበር የሚነሱት ከወደቁበት የደሃነት አዘቅጥ ለመውጣት እንጂ በሃብታሞቹ ቀንተው አይደለም፡፡ ወይም በረብሻ ሃራራ ስላደጉ አይደለም፡፡ የሰዎችን የዜግነት ሰብዓዊ ክብር ከመግፈፍ የበለጠ ሌላ በጥባጭነት አለ? እንደማንም ማሰቢያ አእምሮ እንዳለው ፍጡር የአካባቢዬ ሁኔታ ሲለወጥ መለወጥ አለብኝ፡፡ ይሄ ደንብ ነው፡፡ ስድሳ ሰባት አመተምህረት መጨረሻ ላይ ሚኒሊክ ትምህርት ቤት የማውቀው ልጅ፣ አንድ ጥናት ክበብ አስገብቶኝ፣ ማርክሲስት ፍልስፍና ስማር፣ የግል ህይወቴ ቅርፅ ብቻ ሳይሆን ማራኪ ትርጉም አገኘ፡፡ ማርክሲዝምን እንደ አላሌሆይ ወይ እንደ ሆያ ሆዬ የሚዘፍኑ ልጆች አጋጠሙኝ፡፡ ተፎካካሪ ነኝና ብዙ ጊዜ የፍልስፍና መሰረታዊያኑን በአጭር ጊዜ መረዳት አላቃተኝም፡፡ ከሁሉ የሳበኝ ዲያሌክቲካልና ሂስቶሪካል ማቴሪያሊዝም ነበር፡፡ እነዚህ ሁለቱን በመጠኑ ስረዳ በምኖርበት አለም ላይ ያሉ ተፈጥሮአዊም ሆኑ ማህበራዊ እውነታዎች በሚገርም መልክ ለግንዛቤዬ ተከፈቱ፡፡ በተወሰኑ ሕጐች ማለት በተቃርኖ ሕግ፣ በሻሪ ሻሪ ሕግ ወዘተ… የተወሳሰቡ ማሕበራዊ ጉዳዮች ሲተነተኑ አሰራራቸው ግልጽ ሆነልኝ፡፡ የሆነ ነገር በራልኝ፡፡ ብሩህነት ተሰማኝ…”
ለማሳያነት እኒህን ጠቀስኩ እንጂ “መረቅ” የያኔውን ፖለቲካ በስፋትና በጥልቀት ነው የሚዳስሰው፡፡ “የፖለቲካ ቅቅል” በሉት፡፡ ልቦለዱን ስታነቡ ዛሬም የኢትዮጵያ ፖለቲካ ብዙም አለመለወጡን ትረዳላችሁ፡፡ ምናልባት ልዩነቱ ከተማ ውስጥ የታጠቁ ሃይሎች አለመኖራቸው ብቻ ነው (ያኔ እኮ መዲናዋ የጦርነት አውድማ ነበረች!) ዛሬ ተኩስና መገዳደል ባይኖርም የፖለቲካ ባህሉ ግን ስልጡንነትን አልተቀዳጀም፡፡ ዛሬም እንደ ያኔው ሁሉም ፓርቲ “የእኔ ብቻ ነው ልክ” ማለቱን በርትቶበታል፡፡ ለአንድ አገር እንደሚሰሩ ፓርቲዎች ቁጭ ብሎ መነጋገርና መወያየት ዛሬም እርማችን ነው፡፡ ሰብዓዊ መብት፣ ዲሞክራሲ፣ የመድብለ ፓርቲ ሥርዓት፣ ሃሳብን በነፃነት የመግለጽና የፕሬስ ነፃነት ወዘተ… በቅጡ አልገቡንም፡፡  ሁሉ ነገር ሃሳዊ ይመስላል፡፡ የይስሙላ፡፡ ለአፍ ዓመል የሚወራ፡፡  ከህይወት የራቀ፡፡ ወረቀትን የሙጥኝ ያለ፡፡ የአዳም ረታን “መረቅ” አንብባችሁ የፖለቲካ ታሪካችንን በቅጡ እንድትገነዘቡ እየጋበዝኩ፣ እዚያው ልቦለድ ላይ ስለ ዲሞክራሲ ባነበብኳት አንድ ጥቅስ ልሰናበታችሁ:-
“ዲሞክራሲ ያለ ይመስልሃል? ዲሞክራሲ ጨረቃ ላይ ያለች፣ አመድ ላይ እየተንከባለለች ሊፒስቲክ የምትቀባ የዞረባት ቺክ ናት” (የያኔዋን የጦቢያ ዲሞክራሲ ማለቱ ነው!) የዛሬዋን የጦቢያ ዲሞክራሲ እንዲህ አሳምሮ የሚገልጽ የተባ ብዕር ያለው ደራሲ ያስፈልገናል፡፡ በነገራችሁ ላይ የጦቢያ ፖለቲከኞች “መረቅ”ን ማንበብ አለባቸው (አቋም መያዝ ግን አይፈቀድም!) መጽሐፉ የፖለቲካ ማኒፌስቶ ሳይሆን በውብ ቋንቋ የተኳለ ልቦለድ ነው!!

Page 19 of 19