ሰባተኛ ክፍል እያለን እንዲህ ሆነ፡፡ አንድ አርብ የክፍል ቤስት ጓደኛዬ የሆነው ልጅ ደብተሬ ውስጥ ደብዳቤ እንዳስቀመጠና ቅዳሜንና እሁድን አስቤበት ሰኞ ምላሽ እንደሚጠብቅ ነገረኝ፡፡ ልጁ ባይጽፍልኝም እንደምንዋደድ ራሳችንም እናውቃለን፡፡ አብረን እናጠናለን፣ አብረን እንረብሻለን፣ አብረን እንጫወታለን፡፡
ክፍል ውስጥ የራሱ መቀመጫ ቢኖረውም አብዛኛውን ጊዜ የኔ ወንበር ላይ ነበር የሚገኘው፡፡ ቤቶቼ ያውቁታል፤ ይወዱታል፡፡ ከዚህ ያለፈ ምን ማድረግ እንደሚቻል አላውቅም፡፡ ብቻ ለደብዳቤው መልስ ይፈልጋል፡፡ በመርህ ደረጃ 12 ሳልጨርስ ጓደኛ ብሎ ነገር በጊዜው ለኔ ስህተት ነው፡፡ በዚህ ምክንያት መልሴ ሳይጠይቀኝ የታወቀ ቢሆንም የተጨነኩት ከዚህ በኋላ ምን አይነት ግንኙነት ሊኖረን ነው ብዬ ነበር፡፡ እንደፈራሁት መፈራራትና መተፋፈር ጀመርን፡፡ ቀስ እያልንም ተራራቅን፡፡
በዚህ መሃል ማን ቢቀበለኝ ጥሩ ነው….ይሄንን ሁኔታ ያየና የተከታተለ ሌላ የክፍል ልጅ ለአባቱ እንዲህ አላቸው “…ፌቨን ጐበዝ ተማሪ ትወዳለች፡፡
ወደፊት እሷን ማግባት ስለምፈልግ ካሁኑ በትምህርቴ መጐበዝ እፈልጋለሁ፡፡ ለዚህ ደግሞ እሷ የማጠናከሪያ ትምህርት የምትማርበት ቦታ አስመዘግበኝ፡፡”
ይሄን እንግዲህ አባቱ ለአባቴ “ልጅህ ልጄን ጐበዝ ልታደርግልኝ ነው” ብለው ነግረውት የሰማሁት ነው፡፡ እሱ ግን ለኔ ምንም አላለኝም ነበር፡፡ ልጅት ሆዬ ሁኔታውን መከታተል ጀመርኩ፡፡ በርግጥም ልጁ የክፍል ውስጥ ተሳትፎው ጨመረ፡፡ የቤት ስራዎችን ጠንቅቆ ይሰራ ጀመር፡፡ አባቱ የልጄ የወደፊት ሚስት ብለው ይሁን ወይ እንደ ባለውለታቸው ቆጥረውኝ ብቻ…ባገኙኝ ጊዜ ሁሉ ፍሽክ ፍሽክሽክ ብለው ሰላምታ ይሰጡኛል፡፡ ስመውም አይጠግቡኝም ነበር፡፡ ታዲያ እኔ በማየው ነገር እየገረመኝ፣ ዮሲንም እየወደድኩት፣ አባቱ እየተደሰቱ፣ ዮሲ ዓላማውን ለማሳካት መንገዱን እየጠበጠበ ባለበት ወቅት የኢትዮ - ኤርትራ ግጭት በመጀመሩ ተለያየን፡፡
ዮሲን አደንቀዋለሁ፡፡ ሚስት ሁኚኝ አላለኝም፤ ራሱን ለብቁ ባልነት ማዘጋጀት ግን ጀምሯል፡፡ እንዲህ አይነቱን ማን አይወድም? እኔ እወዳለሁ!
ዮሲ ከሄደ በኋላ ልቤን ያስደነገጠ ሳይገኝ አመት አለፈ፡፡
ኛ ክፍል ላይ እንደገና ተረታሁ፡፡ ልጁ እንደሚወደኝ ነገረኝ፤ እንደምወደው ነገርኩት፡፡  በጣም አስብለት ነበር፡፡ ትዝ ከሚሉኝና ተቃውሜውም የማላውቀው ነገር ደብተሬ ላይ እየተፈላሰፈ የሚጽፈው ነገር ነው፡፡ ሁለት ገጽ፣ ሶስት ገጽ ይጽፋል (ስለ ፍቅር፣ ስለ ይቅርታ፣ ስለ ጓደኝነት…) አልገነጥለውም፡፡ ግን ያንን ደብተሬን ለማንም አልሰጥም፡፡ ቲቸርም የደብተር ማርክ ሲሞሉ አስተውለውት አያውቁም፡፡ የ9ኛ ክፍል የCivic ደብተሬ፣ የሱን ጥራዝ ነጠቅ ሃሳቦች እንደያዘ ማን አወቀ? ከኔና ከራሱ በቀር፡፡
ዮሲ አሁን የት እንዳለ አላውቅም፡፡
ከዚህኛው ልጅ ጋር እንኳን ከብዙ አመት በኋላ ፌስቡክ ላይ ተገናኝተን አወራን፤ መለያየታችንን ኮነንን፡፡ የአንድ የቆንጅዬ ልጅ አባት ሆኖ አገኘሁት፡፡ እኔ፤ ሆዴዴዴዴን እስኪያመኝ ቀናሁ፡፡ ሚስቱ በጣም ፉንጋ ናት አይደል? “Say” አዎ በናታችሁ!
*   *   *
የመጀመሪያ ደብዳቤ የደረሰኝ 7ኛ ክፍል ሆኜ ነው፡፡ የፃፈልኝ ልጅ በጣም ቀጭን ሲሆን ስሙ ብርሃኑ ይባላል፤ ግን ሉሲ ብሬ የሚል ቅጽል ስም ነበረው፡፡ ዳር ዳሩን በአበባ ባጌጠ ወረቀት ላይ አስቂኝ ፅሁፍ ሰጠኝ “እንደ እንጀራ ለምትርቢኝ እንደ ውሀ ለምትጠሚኝ ውድ ፍቅሬ…” ይልና በመጠማትና በመራብ ዙሪያ ትንተና ይሰጣል፡፡ ከጓደኞቼ ጋር በመሆን ወር ሙሉ ሳቅንበት፡፡ እሱም ሰኔ 30 ጥርሴን እንደሚያስለቅመኝ ዝቶ ተለያየን (እኔ በጣም ወፍራም ስለነበርኩ ማች አናደርግም ብዬ ነው)
ሁለተኛ ደግሞ እዛው 7ኛ ክፍል ሁለተኛው አጋማሽ ላይ ነው የደረሰኝ፡፡ ልጁ ሰፈር፣ ትምህርት ቤት ያስቸገረ ነውጠኛ፤ በጉልበቱ የሚያምን አይነት ነበር፡፡ ደብዳቤው የተፃፈው እንደነገሩ ነው “እወድሻለሁ ስትወጪ ጠብቂኝ” ይላል፡፡ አላመነታሁም፤ ጠበቅሁት፡፡ ምን እንዳወራን ባላስታውስም ሰፈር ድረስ ሸኘኝ፡፡ የቤታችን በር ጋ ስደርስ “ጓደኛዬ ነሽ፤ ከዚህ በኋላ ከሌላ ሰው ጋር እንዳላይሽ” ኧረ ማስጠንቀቂያ! ቤት ደግሞ ጓደኛ መያዜ ከተሰማ እገደላለሁ “እኔ ጓደኛህ መሆን አልፈልግም” አልኩት፡፡ “አስቢበት” ብሎ ጥሎኝ ሄደ፡፡ ጓደኛዬን ሳማክራት፣ ቤተሰቦቼ ሳያውቁ ጓደኛ እንዳደርገው አስማማችኝ፡፡ በበነጋታው በር ላይ ጠብቆ “እእ..” አለኝ፤ ትንሽ አመንትቼ “እሺ” አልኩት፡፡ እናም በክብር ያቺን አመት ጨረስኩ፡፡ ሰኔ ሰላሳም ሳልመታ አለፈ ግን ማርያምን ምንም አላደረግንም፡፡
ተወዳጅ መኮንን
*   *   *
ስምንተኛ ክፍል ሆኜ ነው፡፡ የሰፈሬ ልጅ ደብዳቤ ፅፎ ላከልኝ፡፡ ደብዳቤውን ያመጣው ትንሽ ልጅ ነበር፡፡ በወቅቱ ለወንድ ልጅ ካለኝ ፍርሃት የተነሳ ደፋር ነበርኩ፡፡ ፍርሃት በጣም ደፋር ያደርጋል ያሉት ለካ ወደው አይደለም፡፡
የተላከው ልጅ ከቤት አስጠርቶኝ “ለእሷ ብቻ ስጥ” ተብሏል መሰለኝ፣ ደብቆ ሰጠኝ፡፡ ገለጥ አድርጌ ሳየው ገባኝ፡፡ የልብ ቅርፅ ተስሎበታል፡፡ በአረንጓዴና በቀይ እስክርቢቶ በሚያምር የእጅ ፅሁፍ ተጽፏል፡፡ (የልጁ እጅ ፅሁፍ ማማር እራሱ ግርም ይለኛል) የወረቀቱ አስተጣጠፍ እንኳን በጣም ልዩ ነበር፡፡
በአንዴ ከድንጋጤም ድፍረትም ከየት እንደመጣ እንጃ! (አትንኩኝ ነው ነገሩ) ወረቀቱን አጣጥፌ ብጭቅ ብጭቅ አደረግሁትና፤ (ውይ ክፋቴ)
“ሲርብህ ብላው ብላሃለች በለህ” ብዬ መልሼ ሰጠሁት፡፡
አቤት…ከዚያ ወዲያ አኔም ሳላናግረው፣ እሱም ቀና ብሎ ሳያየኝ፣ ከዚያ ሰፈር ወጣሁ፡፡ በጣም ትልልቆች ሆነን እንኳን አላናግረውም ነበር፡፡
ሁለተኛውና የመጨረሻው 9ኛ ክፍል ስማር በዕረፍት ሰአት ደብተሬ ውስጥ ያገኘሁት፣ ማንነቱንና ምንነቱን ያልገለፀ ሰው በሙንጭርጭር ጽሑፍ የፃፈልኝ ደብዳቤ ነው፡፡ “መነን ት/ቤት መታጠፊያው ላይ ጠብቂኝ” የሚል ቀጠሮ ሁሉ ነበረው፡፡ (ማን እንደሆነ ሳይታወቅ!) ወይ ጊዜ፤ እንዴት ይሮጣል!
ሮሚ
*   *   *
የደረጃ…የስፔሻል ክላስ ተማሪ…ማፍቀር መፈቀር የማይታሰቡ ነገሮች…መሸ ነጋ ደብተሬ ላይ የምቸከል…ስለ ፍቅር ሲወራ “እኔ አላማ አለኝ፤ እንዲህ አይነት ነገር አላደርግም” ምናምን የምል… አካባጅ ነበርኩ፡፡ ከመምህሮቼ ጋር ጥብቅ ግንኙነት ስላለኝ ተማሪዎችም ደፍረው አይቀርቡኝም፡፡ እና ደብዳቤ ምናምን አልተጻፈልኝም (አሁን ቆጨኝ!)
ሁሌም አመሻሽ ላይ ከእህቶቼ ጋር የሃይማኖት ትምህርት ለመከታተል ቤተክርስቲያን እንሄዳለን፡፡ ትምህርት አልቆ ማታ ወደ ቤት ስንመለስ፣ ከመድሃኒያለም እስከ ሃያ ሁለት ጫፍ ዎክ እናደርጋለን፡፡ (በዚያ መስመር ብዙ ሰው ዎክ ያደርጋል) አንዳንዴ የማንገዛውን ቡቲክ ገብተን እንጠይቃለን… ሃሃሃ…
እዚያ አካባቢ የቀበሌ መዝናኛ ፑል ቤት አለ፡፡ ሁሌ በር ላይ የሚቆሙ ፍንዳታዎች ነበሩ፡፡ አንደኛው ላይ አይኔ አረፈና ተከየፍኩበት፡፡ ታዲያ የማየው ከሩቁ ነው፡፡ ቁመናውን እንጂ ጠጋ ብዬ ፊቱን አይቼው አላውቅም፡፡ እሱም በጨለማ ነው፡፡ በመንገድ መብራት ድብዝዝ ብሎ ነበር የሚታየኝ፡፡ ቆንጅዬ፤ ጠይም እንደሆነ ያስታውቃል፡፡ ዛሬ ፊቱን ማየት አለብኝ ብዬ ከሩቅ አስቤ እሄድና ልክ መቶ ሜትር ሲቀኝ አንገቴን አቀረቅራለሁ፡፡ ድፍረቴ ኦና ይሆናል፡፡ መቼም አጠገቡ ቆሜ እንደማላወራው አውቀዋለሁ፡፡ በሩቁ ብቻዬን ነበር ያፈቀርኩት፡፡ ለእህቶቼም እንኳን አልነገርኩም፡፡ አንድ ቀን ብቻዬን ወደ ቤተክርስትያን ስሄድ ከኋላዬ ደረሰብኝ፡፡ ነፍሴ ተርበተበተች፡፡
“ሃይ… ሰላም ነው” አለኝ ስሜን ጠርቶ፡፡ ስሜን መጥራቱ ቢያስደስተኝም አንደበቴ ተለጉሞ ዝም አልኩት፡፡
“ከኋላ በጣም ታምሪያለሽ” አለ፤ ቀጠለና፡፡ አስቀያሚ ብሎ የሰደበኝ መሰለኝ፡፡ ተናደድኩበት፡፡
“እንትን ጋራጅን ታውቂዋለሽ? እዛ ነው ምሰራው” አለኝ
“እግር ኳስ ተጫዋችና ጋራጅ ሰራተኛ እወዳለሁ” አልኩት፡፡ በኋላ “ለምን አልኩት” ብዬ ፀፀተኝ፡፡
“እንትናንስ ታውቂዋለሽ?” (ባለጋራጁን ማለቱ ነው)
“እንጃ ብዙ አላውቀውም” አልኩት፡፡
“ስልክ ቁጥሯን ተቀበልልኝ ብሎ ነው”
“ይሄ ትልቁ ሰውዬ?” አልኩት ድንገት በመገረም፡፡
“ኧረ ትልቅ አይደለም፤ አንቺ ስለማታውቂው ነው፡፡ ስልክ ከሌላት እኔ እገዛላታለሁ ብሏል…” ለድለላ ስራ እንደመጣ ሲገባኝ ኩምሽሽ አልኩ፡፡ አግኝቼ ያጣሁት መሰለኝ፡፡
አጋጣሚ እየጠበቀ ያናግረኝ ጀመር፡፡ እኔም እሱን ለመሳብ ይረዱኛል ያልኳቸውን ፍልስፍናዎች አዘንብበት ጀመር፡፡ ስለ ሰውየው ትተን፣ ስለ ራሳችን ማውራት ጀመርን፡፡
“እነንትና እኮ ዱሩዬ ናቸው፤ ለምን ከነሱ ጋ ትቆማለህ?” እለዋለሁ፡፡ ቀስ እያለ ያስረዳኛል፡፡
“አስፓልቱ ሰው ይበዛበታል… ውስጥ ለውስጥ እንሂድ” እያልን ከህዝብ ተገንጥለን ለብቻችን መሄድ ጀመርን፡፡ ቀጥሎ አንገትና ወገብ ተቃቅፎ መሄድ መጣ፡፡
እያለ …እያለ…እያለ… ሃሃሃ… ይበቃችኋል፡፡
*   *   *
የመጀመሪያው የፍቅር ደብዳቤ የደረሰኝ 5ኛ ክፍል እያለሁ ነበር፡፡ ስሙን የማልጠቅሰው፤ በረባሽነቱና ተጫዋችነቱ በጣም የሚታወቅ የክፍሌ ልጅ ነበር፡፡ በጣምም ደፋርና ጆሊ ነገር ነበር፡፡ የክፍላችን ወንዶች በሙሉ ጓደኞቹ ነበሩ፡፡ ትምህርት ቤታችን ውስጥ እሱን የማያውቅ ተማሪ አልነበረም፡፡ እናቱም አስተማሪያችን ነበሩ (ለድፍረትና ረብሻው አግዞት ይሆናል)
የሆነ ሆኖ አንድ ቀን “የቤት ሥራ አልሰራሁምና ደብተርሽን አውሽኝ” ይለኝና ደብተሬን ሰጠሁት፡፡ እኔ ደግሞ አታምኑኝም ይሆናል እንጂ ያኔ በጣም አይናፋርና ዝምተኛ ነበርኩ፡፡ ደብተሬን ከትምህርት ስንለቀቅ ግቢው በር ላይ ጠብቆ መለሰልኝ፡፡ እቤት ደርሼ ደብተሬን ስገልጥ፣ ዳር ዳሩ ላይ በአበባና ቢራቢሮዎች ያጌጠ፣ ሽቶ ሽቶ የሚሸት ወረቀት አገኘሁኝ፡፡ ከልጁ የተፃፈልኝ የ“እወድሻለሁ” ደብዳቤ ነበር፡፡ የተፃፉትን እያንዳንዱን ቃላት አላስታውሳቸውም፡፡ አንብቤው ለእህቶቼዋ አስነበብኩት፤ ለጓደኛዬም፡፡
ጓደኛዬ፤ “ታዲያ ምን ብለሽ ልትመልሽለት ነው? እሽ እንዳትይው፣ ረባሽ ነው፤ ከፈለግሽው ግን ይሁን” አለችኝ፡፡ መመለስ እንደሚገባኝ እራሱ አልገባኝም ነበርና ዘጋሁት፡፡ ልጁ በሶስተኛ ወይ በአራተኛ ቀን የተቀመጥኩበት ዴስክ ጋ መጥቶ “ምነው ደብዳቤዬን ሳትመልሽልኝ?” ብሎ ሲጠይቀኝ “አልፈልግም፤ ይኸው ደብዳቤህ” ብዬ ሰጠሁት፡፡ “እምቢ አልሽ አይደል፣ ቆይ ብቻ ሰኔ 30 ላግኝሽ” ብሎ ፎከረብኝ፡፡ እንዳለውም ሰኔ 30 ከጓደኞቹ ጋር መንገድ ላይ ጠብቆ እየፎከረ ሊመታኝ ሲያስፈራራኝ፣ እህቶቼና ጓደኛዬ ደፈር ብለው፣ ተለማምጠውና አባብለው ከመደብደብ አስጥለውኝ ነበር እላችኋለሁ፡፡
ሜሪ ፈለቀ



Published in ጥበብ
Saturday, 22 November 2014 12:39

የፀሃፍት ጥግ

 ጥሩ ተራኪ ግሩም የማስታወስ ችሎታ ያለውና ሌሎች የላቸውም ብሎ ተስፋ የሚያደርግ ነው፡፡
አይርቪን ኤስ. ኮብ  (አሜሪካዊ ተረበኛና ጋዜጠኛ)
* በስኬት ሱስ ሙሉ በሙሉ ተይዣለሁ፡፡
ስቲንግ
(እንግሊዛዊ የሮክ አቀንቃኝና የዘፈን ግጥም ፀሐፊ)
* ከምሠራው ነገር ጀርባ ሁሉ የዓይን ጥቅሻ አለ፡፡
ማዶና (የፖፕ ሙዚቃ አቀንቃኝና የፊልም ተዋናይ)
* ግጥም የተመጠነ ንግግር እንደሆነው ሁሉ ዳንስም የተመተረ እርምጃ ነው፡፡
ፍራንሲስ ቤከን (እንግሊዛዊ ፈላስፋ፣ በሳል ፖለቲከኛና የህግ ባለሙያ)
* ሙዚቃ ማቀናበር ከመጪው ዘመን ጋር በፍቅር እንደመቅለጥ ነው፡፡
ሉካስ ፎስ  (ትውልደ ጀርመን፣ አሜሪካዊ  አቀበናባሪ፤  ኮንዳክተርና ፒያኖ ቀማሪ)
* ጎበዝ አቀናባሪ አይኮርጅም፤ ይመነትፋል እንጂ፡፡
አይጎር ስትራቪንስኩ
(ትውልደ ሩሲያ አሜሪካዊ አቀናባሪ)
* ሁሉም ሰው መማር ከመጀመሩ በፊት አርቲስት ነው፡፡ ሁሉም ሰው መማር ካቆመ በኋላ አርቲስት ይሆናል፡፡
ታባን ሎ ሎዮንግ (ሱዳናዊ ገጣሚና ደራሲ)
* እግዚአብሔር ምድርን ፈጠረ በሰባተኛው ቀን ግን እረፍት ላይ ሳለ፣ ድንገት ተነሳና እንዲህ አለ፡፡
ሁሉንም ነገር ፈጥሬ ረሳሁ ሁለት ነገሮች  የፒካሶን አይንና እጆች
ራፌል አልበርቲ  (ስፔናዊ ገጣሚ)
* ታላላቅ የሙዚቃ ቀማሪዎች ታላላቅ መንታፊዎች እንደነበሩም አንርሳ፡፡ ከማንም ከየትም ሳይሉ ዘርፈዋል፡፡
ሰፓብሎ ካሳልስ (ሙዚቃ ቀማሪ)
* እብደትን በጥቂቱ መሞከር ሰዓሊን
አይጎዳውም፡፡
አዩ ክዌይ አርማህ (ጋናዊ ፀሐፊና የትምህርት ሊቅ)
* የእኔ ስራ የማውቀውን መሳል አይደለም፤ የማየውን እንጂ፡፡
ጄ.ኤም.ደብሊው ተርነር (እንግሊዛዊ ሰዓሊ)

Published in የግጥም ጥግ

በቅርቡ ለገበያ የዋለው የዕውቁ ድምፃዊ አብነት አጎናፍር “አስታራቂ” የተሰኘ አልበም ከትላንት በስቲያ ዝነኛ አርቲስቶች፣ ተጋባዥ እንግዶች፣ የአርቲስቱ ወዳጆችና አድናቂዎች በተገኙበት ተመረቀ፡፡ የአብነት “አስታራቂ” ሦስተኛው አልበሙ ሲሆን 14 ዘፈኖች ተካተውበታል፡፡  

በደራሲ ደሞዝ ጐሽሜ ተፅፎ ለንባብ የበቃው “ሶስተኛው ኪዳን” ልብወለድ መፅሀፍ ትናንት ምሽት በብሔራዊ ቤተ መፃሕፍትና ቤተ መዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ ተመረቀ፡፡
ለመጀመሪያ ጊዜ በሐምሌ 2003 ዓ.ም የታተመው መጽሐፉ፤ ሁለተኛው እትም ባለፈው መስከረም የወጣ ሲሆን ጭብጡ በኢትዮጵያ መንፈሳዊ ስልጣኔ ላይ የሚያጠነጥን ነው ተብሏል፡፡
በምረቃ ሥነስርዓቱ ላይ የመጽሐፍ ዳሰሳና ውይይትም ተካሂዷል፡፡ የምርቃት ሥነስርዓቱን ያዘጋጀው ኢጋ ሚዲያ እና ኮሙኒኬሽን እንደሆነ ታውቋል፡፡

Saturday, 22 November 2014 12:33

ማህሌት

የሆነ ያልገባው ነገር አለ፡፡ ስለ ህይወቱ? … ስለ እናቱ? በተለይ ስለ አባቱ? … በጥቂቱ ደግሞ ስለ ትምህርቱ፡፡ እንደ ድሮው አይደለም እሱነቱ፡፡ “ኤሊየን” ስለመሆኑ እንደ ድሮው ከዚህ ስምንት አመት በፊት አያምንም፡፡ እንኳንስ… አፍ አውጥቶ መናገር፡፡
የአስራ አንደኛ ክፍል ትምህርት እንደሚወራለት ከባድ አይደለም፡፡ ትንሽ አስተማሪዎቹ የሚሉትን መስማት ብቻ ነው የሚጠበቅበት፡፡ ደብተር ይዞ አያውቅም፡፡ አስተማሪ ተብዬዎቹ የሚያወሩትን ሰምቶ ፈተና በተባለው ወረቀት ላይ ሲደግምላቸው ይደሰታሉ፡፡ ሲደሰቱ “አንደኛ” ወጥተሃል ይሉታል፡፡
ዘጠነኛ ክፍል እያለ እንደዚያ አስደስቷቸው ነበር፡፡ አመቱን ሙሉ እነሱ የሚሉትን እንደ “ፓሮት” ደገመላቸው፡፡ አመቱን ሙሉ፡- ማለትም ሁለት ሴሚስተር ያህል “አንደኛ” ነህ አሉት፡፡ “አንደኛ” እና “አንተ ነህ” አሉት፡፡ ስሙ እና እውነተኛ ማንነቱ የጠፋው ሲመስለው፤ አስረኛ ክፍል አስተማሪዎቹ የሚሉትን መድገም አቆመ፡፡ “አንተ አይደለህም” ቢሉትም  አልጣሉትም፡፡ “ወደቀ” ብለው አሾፉበት እንጂ ሰርተፍኬቱ ላይ “ወደቀ” ብለው አልፃፉበትም፡፡
ዘጠነኛ ክፍለ ፊት ወንበር መጀመሪያ መደዳ ነበር የሚቀመጠው፡፡ አስረኛ ክፍል መጨረሻ መደዳ ተቀምጦ “ሮበርት ሉድለምን” እያነበበ፣ በደረጃ መጨረሻ እየወጣ አመቱን ጨረሰ፡፡ መጨረሻ መደዳ የሚቀመጡት ፊት የሚቀመጡትን እንደ “ባንዳ” እንደሚቆጥሯቸው የተረዳው ከእነሱ መሀል ሲቀመጥ ነበር፡፡ ፊት ወንበር የሚቀመጡት ኋላ ያሉትን ምን ብለው እንደሚጠሯቸው ግን በመሀላቸው ሳለ አልነገራቸውም፡፡
ከኋለኛው መደዳ ረድፈኞች ወደ አስራ አንደኛ ክፍል ያለፉት የተወሰኑት ናቸው፡፡ ከተወሰኑት መሀል ማህሌት አንዷ ናት፡፡ በመጀመሪያው ሴሚስተር ከሮበርት ሉድለም መፅሐፍ ማህሌትን ወደ ማጥናት አደገ፡፡ የእሷን ትኩረት ለመሳብ ሲል መሆን አለበት… ኋላ መደዳ ተቀምጦ ፊት ተቀማጮቹ የሚታሙበትን ነገር ማድረግ ጀመረ፡፡ ማጥናት፤ በአጭር ቋንቋ አስተማሪው የሚያዘውን ሁሉ ማድረግ፡፡ የሚደግመውን መድገም፡፡ ተመልሶ ፓሮት ሆነ፡፡
አስተማሪዎች ይገርሙታል፡፡ እነሱ ያሉትን ሁሉ አንድ ሳያስቀር ኮፒ አድርጎ የሚገለብጠውን ልጅ የፈተና ወረቀት ሲያርሙ፣ የእስክሪብቷቸው የቀይ ቀለም ጭነት ራሱ ይለሰልሳል፡፡ የሚወዱትን ልጃቸውን ጭንቅላት የሚያሹ ነው የሚመስሉት፡፡ “መቶ ከመቶ”፣ “ስልሳ ከስልሳ”… “ኤክሰለንት”… በ“Very Good” እና በ“Excellent” መትረየስ ወረዱበት፡፡ “አንተ ነህ” አሉት፡፡
ከማህሌት ጋር ለመተዋወቅ ቀላል ነበር፡፡ ያው ምክኒያት አያስፈልግም፡፡ “እቺን ነገር አሳየኝ!” “ያቺን ነገር አሳየኝ?”…
ስሙ አስተማሪዎቹ እንደሚጠሩት “አንተ ነህ” ሳይሆን...፣ ሚልኪ እንደሆነ አስረግጦ ነገራት፡፡ የተለያየ ቦታ፣ የተለያዩ ሰዎች የሚያወጡለት ስም እንዳለ ግን ደበቃት፡፡ የዛሬ አስር ዓመት ገደማ በነበረበት ሰፈር “Ace” እያሉ እንደሚጠሩት፣ ጥሪውን ግን ሰፈር ሲቀይር እንደተለወጠ መናገር ዋጋ የለውም፡፡ አባቱ የሚጠራው ስምም አለ፡፡ መውደድ ሰጥቶ መቀበል ነው፡፡ አይን ስለ አይን፣ ጥርስ ስለ ጥርስ፡፡
አሁን ከማህሌት ጋር ሚልኪ በሚለው ስሙ ነው መቀራረብ የፈለገው፡፡ መታወቂያው ላይም ስም አለው፡፡ በሱም ስም ሰዎች ይጠሩታል፡፡ ሁሉንም ጥሪ አቤት ብሎ ይቀበላል፡፡ ከነብሱ አንደበት ራሱን የሚመራበትን ስም ግን በአፉ ለራሱ እንኳን ቢሆን ጮክ ብሎ አይደግምም፡፡ ጉልበቱ የት እንደሚገኝ እንደ መግለፅ ይመስለዋል፡፡ ሳምሶን ጉልበቱን ፀጉሩ ላይ አስቀምጦ፣ ፀጉሩ እንደ በግ ሲሸለት፣ በግ እንደመሰለው …. እሱም ስሙን ምላሱ ላይ አስቀምጦት፣ ምላስ ያላቸው ሁሉ በእሱ ጉልበት እጣ ፈንታቸውን እንዲሸከሙ አይፈቀድላቸውም፡፡
ከማህሌት ጋር ተግባባ፡፡ ከማህሌት ጋር ሲቀራረብ፣ ከራሱም ማንነት ጋር ሆነ፡፡ አስተማሪዎች ማን እንደሆነ እየደጋገሙ ከሚደሰኩሩለት ራቅ ያለ ሶስተኛ ማዕዘን ላይ የተቀመረ መሆኑ ለራሱ ይሰማዋል፡፡ ቢሰማውም ይሄንን ሶስተኛ ማንነቱን ወደደው፡፡ ከወትሮው የሦስት መአዘን አቋሙ ጋር የሚስማማ ነገር ስላለው፡፡
በፊት እናቱ ከአባቱ ጋር አንድ ላይ በሚኖሩበት ጊዜ፣ እሱ የእናቱንም ሆነ አባቱን ወይንም አባቱ እሱን እንደሚያየው ወይንም እናቱ እሱን በምታየው አንፃር ራሱን ተመልክቶ አያውቅም፡፡ ሁሌም ሶስት መአዘን ይይዛል፡፡
በዚያ የልጅነት ዘመን ጎረቤቱ ያሉት እዮብ እና ናትናኤል ምርጥ ጓደኞቹ ነበሩ፡፡ ሁለቱም እሱን እንደሚያዩት .. የራሱን እይታ አመቻችቶ አያውቅም፡፡ የእዮብ እና የናትናኤል አባት ኢንጂነሩ በጣም ያደንቁት ነበር፡፡ “Ace” የሚለውን ለእነሱ እይታ የሚሆን ስም አውጥተው እንዲፀድቅ አድርገዋል፡፡ እነሱ እሱን እንደሚያዩት እንጂ እሱ እነሱን መልሶ እንደሚያያቸው… በማየት እና በመታየት መሀል ትልቅ ክፍተት እንዳለ አይገነዘቡትም ነበር፡፡ እነሱ እሱን ለመካብ የሚሰጡትን ስም እንጂ እሱ እነሱን ለማድነቅ ያወጣላቸውን ስያሜ አያውቁትም፡፡ እነሱ በሚያዩበት አለም ሁሉንም ብያኔ ለመስጠት የሚያስችል ንግስና እንዳላቸው፣ እሱም በራሱ ዓለም ውስጥ ለሚታዩት ነገሮች ብያኔ የመስጫ ልዕልና መጎናፀፉ ይረሳቸዋል፡፡
ከማህሌት ጋር ሲሆን አፍቃሪ እና ተፈቃሪ … ከመምህሮቹ ጋር ሲሆን ተማሪና አስተማሪ … ከእናቱ ጋር ሲሆን በአንድ ጊዜ ልጅ እና ወላጅ መሆን እንደሚችል ማንም አይገነዘብለትም፡፡ አብዛኛው ሰው የሚታየው አሀዳዊ መንገድ ብቻ ነው፡፡ የራሱ መንገድ፡፡ የራሱ ፍላጎት መንገድ፡፡ ኤስ ግን ሶስት መንገድ በአንድ ጊዜ ይታየዋል፡፡
በማህሌት ላይ የሚያየው መንገድ የዚህን ባህርይ የተላበሰ ነው፡፡ አንደኛው መንገድ እሱ እሷን ለማፍቀር፣ ጓደኛ ለመሆን፣ አብሮ ለመሰንበት የሚያሳየው ፍላጎት የሱ ፈቃድ ነው፡፡ ሁለተኛው ማህሌት ከሱ የምትፈልገው፣ እንዲሆንላት የምትመኘው፣ የሷ እምነት፣ እሱን በመቆጣጠር የሚፈጠረው መንገድ ነው፡፡ ሶስተኛው ከሁሉም ውጭ የሆነው ነው፡፡ ሁሉንም መሆን እና አለመሆን በአንድ ላይ የሚችለው መንገድ ነው፡፡ ይህ መንገድ እንደ እውነተኛው ስሙ እውነተኛው “ህቡዕ” ምንነቱ አድርጐ ይቆጥረዋል፡፡
የማህሌት መንገድ እና የእሱ መንገድ፤ ከዚያ ሶስተኛው መንገድ፡፡ ማህሌትን እያስጠናት እሱ ደግሞ እሷን ያጠናት ጀመር፡፡ እሷም እያጠናች እንደምታጠናው ያውቃል፡፡ ሁለቱንም ጥናቶች ከውጭ ሆኖ ሶስተኛው መአዘኑ ላይ ይቆምና ይከታተላል፡፡ ሲከታተል አስተማሪዎቹን፣ ተማሪዎቹን እናቱን፣ ህይወቱን አንድ ላይ ጠቅልሎ ነው፡፡
የማህሌትን ውጤት ዝቅ ካለበት ከፍ ሲል እያየ፣ የራሱን ከፍ ካለበት እንዲወርድ ፈቀደ፡፡ የአስተማሪዎቹ እይታ ስለሱ ወይንም ስለሷ …  ስለ እሷና እሱ መርገብገቡ ከማይርገበገበው መአቀፋዊ ምዘናው ላይ ሆኖ እንደገና ይለካል፡፡
ከአስተማሪዎቹ መሀል አንደኛው… ግጭት ለመፍጠር ከመንጋው መምህርነት ወጥቶ ወደነሱ ግንኙነት ተጠጋ፡፡ አስተማሪው የባይሎጂ ትምህርት የሚሰጥ ብቻ ሳይሆን ለትምህርቱ ሰውየውም የተሰጠ መሆኑ በስፋት ይነገርለታል፡፡ የሚነገርለትን ያለ ይሉኝታ ከመናገርም ሰውየው ራሱ አይቦዝንም፡፡ ለትምህርቱ ባሳየው ተነሳሽነት ብዙ ሽልማቶችን ሰብስቧል፡፡ ባዮሎጂ ህይወትን የሚያጠና በመሆኑ፣ አስተማሪው ከህይወት አይነቶች መርጦ ቆንጆ ሴቶችን መመርመር ይወዳል፡፡ የወደደውን ይመረምራል፡፡ ማህሌት የቆንጆ ሴቶችን መስፈርት የምታሟላ “እስፒስመን” ናት፡፡
በተሰጠው ክፍለ ጊዜ በጥቁሩ ሰሌዳ ላይ የሚፅፈውን ፅፎ ወይንም የሚያብራራውን አብራርቶ … ትንፋሽ ለመውሰድ የሚያመራው ወደ ማህሌት አቅጣጫ ነው፡፡ ደብተሯን ያገላብጣል፡፡ ደብተሯን በእጁ፣ መልኳንና ተክለ ሰውነቷን በአይኑ፡፡ ስህተት ሊያገኝባት ይታትራል፡፡ የሚፈልገውን ባያገኝም በአለባበሷ ላይ እንደ አባት ይሆንና ተግሳፅ ይሰጣል፡፡ እንደ አባት የጀመረው ምክር እንደ አጎት ይመስልና እንደ መሸታ ቤት ተስተናጋጅ ሆኖ ይጨርሳል፡፡ በተለያየ ጊዜ ቢሮ ጠርቷት ከባዮሎጂ ጋር በጣም ስለሚገናኙ የፆታዊ ባህሪዎች በጥያቄ መልክ አቅርቦለታል፡፡ አቅርቦልኛል ብላዋለች ኤስን፡፡
ሰው ሰማም አልሰማም፣ ሰውየው ለልጅቱ አንዳች ጥላቻ አለው፡፡ ተንጠራርተው የሚደርሱበትን ነገር እንደሚጠሉ ሰዎች ይመስላል… ማህሌትን ሲያያት የሚያሳየው መንገሽገሽ፡፡
“ንፍጥ” የሚል ስድብ ወደሷ አቅጣጫ ይሰነዘራል፡፡ የባዮሎጂ ተራ አስከባሪ በመሆኑ፣ ለትምህርቱ አምልኮት ያላቸው የፈተናውን ወንዝ ለመሻገር ይስቁለታል፡፡ ኤስ በዚህ ሁሉ ውስጥ የተመልካች ስፍራውን ይዞ ይታዘባል፡፡ መታዘብ ባበዛ ቁጥር ለምን ወደ አንዳች አቅጣጫ እያደገ መሆኑ እንደሚሰማው ለራሱም ማስረዳት አይችልም፡፡
ከእለታት በአንዱ ቀን በሰሌዳው ላይ የተለቀለቀውን ጽሑፍ ተማሪዎቹ እንደ እርግብ በእስክሪብቶው መንቁራቸው እየለቀሙ ሳሉ… እህሉን ያፈሰሰላቸው መምህር ወደ ማህሌት መቀመጫ ሄዶ፣ እለታዊ ጉንተላውን አከናወነ፡፡ በመቀጠል ነጭ ጋውኑን አንዘርፍፎ ከእሷ አንድ ረድፍ በቀደመው ወንበር ላይ ተቀምጦ፣ አስተማሪው የራሱን ጽሑፍ በተማሪ አይን ከኋላ ሆኖ መገምገም ጀመረ፡፡
ኤስ እንደ ሌሎቹ የተፃፈለትን ሁሉ አይለቅምም፡፡ ከሮበርት ሉድለም ወደ ጄምስ ካለቬል ድርሰት አድጓል፡፡ “ሾ ጋንን” እያነበበ ነው፡፡ አስተማሪው ሲያነብ ያየዋል ግን አይተናኮለውም፡፡ “አንተ ነህ” የሚለው ማዕረጉ፣ የሌላው ተማሪ ግዴታ እንዳይመለከተው መንገድ ሰጥቶታል፡፡ ግን ይህ የባዮሎጂ መምህር ስህተት ቢያገኝበት ሊጥለው እንደሚፈልግም ያውቃል፡፡ ከመከባበር ይሁን… ከመገማገም የመጣ መፈራራት በመሃላቸው ሰፍኗል፡፡ ኤስ ከማህሌት ጐን መቀመጡ የአስተማሪው የቀድሞ ፍቅር ወደ “ቆይ ጠብቅ” ሲቀየርበት ይታወቀዋል፡፡
ኤስ እና ማህሌት ከተቀመጡበት መደዳ ፊለፊት የተዘረፈጠው የባዮሎጂ አዋቂ በፈዘዘበት አንድ ነገር ተከሰተ፡፡ ኤስ ልጅ በነበረበት ወቅት አንድ ነገር ከመከሰቱ ጥቂት ቅጽበት ቀደም ብሎ የሚከሰተውን ነገር ያውቀው ነበር፡፡ ለምሳሌ አስተማሪ በሰሌዳው ላይ የሚያሰፍረውን ጽሑፍ ጥቂት ቀደም ብሎ ሰፍሮ ይታየው ነበር፡፡ ግን ይህ ችሎታውን ሳያዳብረው፣ ከሰው ተወራርዶ ሳይረታበት፣ በራሱ ውስጥ እንደያዘው እድሜው ከፍ እያለ ሲመጣ ቀስ በቀስ ችሎታው ጠፋበት፡፡
ጠፍቶበት ቆይቶ ልክ በዛች ቅፅበት አስተማሪው ከፊለፊቱ የእነሱን ዴክስ ተደግፎ በተቀመጠበት፣ ያ የተዘነጋ ችሎታው ድንገት ተከሰተለት፡፡ ማህሌት ቀጥላ የምታከናውነው ተግባር ታየው፡፡ ታየው፤ ግን ነገሩን ከመከሰት ለማቆም ምንም እርምጃ አልወሰደም፡፡ ሶስተኛው መአዘን ላይ ያቆመው ዋነኛው ሚዛን፣ የተከሰተውን ተግባር መግታት ይችል የነበረውን የእሱን እጅ ከውስጥ ያዘበት፡፡ Kay sera sera
ማህሌት ከሰሌዳው ላይ መገልበጧን ድንገት አቆመች፡፡ በፈጣን ትልልቅ ፊደል ለአስተማሪው እንዳይሰማው አድርጋ፣ ከጀርባ በነጩ ጋውን ላይ “የሰው ንፍጥ” ብላ ፃፈች፡፡
*    *    *
የትምህርት ጊዜ አለቀ፡፡ ሰውየውም የእውቀት ማቀበያ መሳሪያዎቹን (ቾክ እና ዳስተር) አንከብክቦ ወደሚቀጥለው ክፍሉ አመራ፡፡
ተቀያሪው አስተማሪ አንድ እግሩ አጠር የሚል፣ ጮክ ባለ ድምጽ የአማርኛን ሰዋሰው የሚያስጨብጥ ሰው ነበር፡፡ አስጨብጦ ሲጨርስ ረዘም ካለው እግሩ አጠር ወዳለው ወርዶ እረፍት ይወስዳል፡፡ መናገር ሊጀምር ሲል እንደገና ከአጭሩ ወደ ረጅሙ ይወጣል፡፡ ሁሉም አስተማሪዎች ቅጽል ስም አላቸው፡፡ ቅጽል ስሞች በአብዛኛው የሚወጡት ፊት መደዳ ከሚቀመጡት ተማሪዎች አይደለም፡፡ ጭቆና ከላይ ወደ ታች እንደሚበረታው፣ ቅጽል ስም ደግሞ ከታች ወደ ላይ የሚስፈነጥር ፍላፃ ነው፡፡ ፍላፃው ግን በተወረወረበት አካል ጆሮ ውስጥ ብዙውን ጊዜ አይገባም፡፡ እኩል እግር የሌለውን አስተማሪ “ሲትሮይን” በሚል ስም ነው ኋለኞቹ የሚጠሩት፡፡
ሲትሮይን፤ ትምህርቱን አስተላልፎ ለማብቃት ሁለት የቁመት ማጠር እና የማስረዘም ያህል ጊዜ ሲቀሩት፣ የክፍሉ በር በእርግጫ በመሰለ ሀይል ተመትቶ ተከፈተ፡፡ የባዮሎጂው መምህር የሹራብ ሰደርያ እና ጉርድ ሸሚዝ እንጂ ነጩን ጋውን አልለበሰም፡፡
ነጩ ጋውን እንደ ኤግዚቢት በዩኒት ሊደሩ እጅ ተይዟል፡፡ ዩኒት ሊደሩ በጣም ረጅምና በጣም ጥቁር አስፈሪ ሰው ነው፡፡ እውቀት ባያንሰውም ችግርን በዱላ በማስከበር ተፈሪነትን ያተረፈ ሰው ነው፡፡ ከዱላ ላለፈ እንቢ ባይነት… (ለምሳሌ ሌባ) ሽጉጥ አውጥቶ ሲያባርር ያዩ ተማሪዎች፣ በዚያች ቅጽበት እዚያው ክፍል ውስጥ ነበሩ፡፡
ነጩ ጋውን በሰሌዳው አናት ላይ ግማሽ በተመታች ሚስማር ላይ ተሰቀለ፡፡ ዩኒት ሊደሩ ወደ ኤግዚቢቱ እጁን እየቀሰረ…
“ማን ይሄንን ጽሑፍ እንደፃፈ ሳታወጡ…ትምህርት በዚህ ክፍል አይቀጥልም፡፡ አሁን እዚሁ ይሄንን የፃፍክ ግለሰብ ራስህን ካጋለጥክ፣ ግለሰቡ ብቻህን ከዚህ ትምህርት ቤት ትወጣለህ፡፡ ካልሆነ ሁላችሁንም አንድ ላይ…”
ተጠበቀ፤ ማንም መናገር አልቻለም፡፡ ለወትሮው አይኑ ከማህሌት ላይ የማይነቀለው ባዮሎጂ መምህር ወደ ማህሌት አቅጣጫ ለቅጽበት እንኳን አልተመለከተም፡፡ ማህሌት በጠረጴዛው ስር የኤስን እጅ ጭምቅ አደረገችው “ጉዴ ፈላ” ማለቷ ይሁን ወይንም “ከዚህ አውጣኝ” ግልጽ አልሆነለትም፡፡
የተማሪው አፍ ነጭ ሆኗል፡፡ ትምህርት ማለት እውቀት ብቻ ሳይሆን የህልውናም ብቸኛ መንገድ ነው፡፡ ከትምህርት ቤት መባረር ማለት ከምድረ ገጽ መሰረዝም ማለት ነው፡፡ አይኖች በጥርጣሬ እርስ በራስ ተያዩ፡፡ ባዮሎጂ አስተማሪው ሌላ ክፍል እንዳልተፃፈበት ሲትሮይን ለሚባለው አስተማሪ ማስረጃ እየጠቀሰ ነው፡፡
“አታወጡም?” ለመጨረሻ ጊዜ ዩኒት ሊደሩ ጠየቀ፡፡ መልስ ጠፋ፡፡ የሰዉ ፊት ሁሉ የጦጣ መስሏል፡፡
“የሁላችሁም የአማርኛ ደብተር ሰብስቡ” አለ ዩኒት ሊደሩ፡፡ ኤስ የአማርኛ ደብተሩ እንደ መጽሐፍ ንባቡ ባይገፋለትም የራሱን ደብተር ከላይ፣ የማህሌትን ከስር አድርጐ አስረከበ፡፡ ማህሌት በጠረጴዛው ላይ ተደፍታ እያለቀሰች ነው፡፡ እያለቀሰች ስለነበረች፣ ሚልኪ በደብተሮቹ ላይ የሰራውን ነገር አልተመለከተችም፡፡
ክፍሉ ተዘግቶ እያንዳንዱ ደብተር በጋውኑ ላይ ከሰፈረው እጅ ጽሑፍ ጋር በጥንቃቄ እየተመሳከረ ተመረመረ፡፡ ዩኒት ሊደሩ፣ ባለ ጥቃቱ ባዮሎጂ አስተማሪ እና ሲትሮይን ለብዙ ፔሬዶች ተማሪው ባለበት ደብተሮቹን ሲያተራምሱ ቆዩ፡፡ በስተመጨረሻ አንድ ደብተር ነጥሮ ወጣ፡፡ ሦስቱም አስተማሪዎች ወንጀለኛው የዚያ እጅ ጽሑፍ ባለቤት መሆኑን መቶ ፐርሰንት ተስማሙበት፡፡ የተማሪው ስም ተነበበ፡፡
ኤስ ስሙ እስኪጠራ አልጠበቀም፡፡ ዝግጁ ሆኖ ነበር፡፡ “አቤት” ብሎ ተነሳ፡፡ የማህሌት ፊት ምን እንደሚመስል ለማየት መጓጓቱ ለእሱ ብቻ ነው የሚታወቀው፡፡ “ኤስ” በዩኒት ሊደሩ እየተገፈተረ ከክፍሉ ወጥቶ ሄደ፡፡
ከሄደ በኋላ ማንም አይቶት አያውቅም፡፡ አንድ አመት ተቀጥቶ ይመለሳል ብለው ጓደኞቹ ቢያስቡም ሳይሆን ቀረ፡፡ ማህሌት ሚስጥሯን ይዛ እንደተብሰለሰለች ትምህርቷን ጨረሰች፡፡ እንዲያውም ማለፊያ ውጤት አግኝታ የንግድ ስራ ትምህርት ቤት ተቀላቀለች፡፡


Published in ልብ-ወለድ

በደራሲና ዳሬክተር ሱራፌል ኪዳኔ ተፅፎ የተዘጋጀው “ወደ ሀገር ቤት” ተሰኘው ሮማንስ ኮሜዲ ፊልም በሀርመኒ ሆቴል ዛሬ ይመረቃል፡፡ ፊልሙ የ1 ሰዓት ከ 37 ደቂቃ ርዝማኔ ሲኖረው ከአሜሪካ ወደ ኢትዮጵያ ተሰደው በሚመጡ ሰራተኞች ላይ ያጠነጥናል ተብሏል፡፡ በአቤል ፊልም ፕሮዳክሽን በቀረበው በዚህ ፊልም ላይ እንግዳ ሰው ሀብቴ (ቴዲ)፣ ካሳሁን ፍሰሀ (ማንዴላ)፣ ማርታ አሰፋ፣ መኮንን ለአከ፣ አስቴር አለማየሁ እና ሌሎችም ተዋንያን እንደተሳተፉበት ታውቋል፡፡

*የ‘ፍቅር እስከመቃብር’ ጉዱ ካሣ ኮከቡ ምንድነው?
*የኔልሰን ማንዴላና የመለስ ዜናዊስ?

ቀዳሚ ቃል
የኢትዮጵያ ኮከብ ቁጥር 2 የሆነው ፍካሬ ኢትዮጵያ፣ የአብነት ሁለተኛ የታተመ ሥራው ነው። ከመጀመሪያው ጋር የሚያገናኘው ነገር ቢኖር ሁለቱም የአስትሮሎጂ መጻሕፍት መሆናቸው ብቻ ነው። ከዚያ በዘለለ፣ የተደገመ ሀሳብም ሆነ ይዘት የለም-ከስመጥሮች ዝርዝር ውጪ። በየኢትዮጵያ ኮከብ ቁጥር 1 ውስጥ የተካተቱት ስመጥሮች 500 ያህል ነበሩ፣ አሁን በፍካሬ ኢትዮጵያ ሌሎች ተጨማሪ 700 ስመጥሮች ተካተው፣ የስመጥሮች ዝርዝር ወደ 1,200 ከፍ እንዲል ተደርጓል። የኢትዮጵያ ኮከብ ቁጥር 1ን ማርታ በፍቃዱ የተባለች አንባቢ፣ በሰንደቅ ጋዜጣ ላይ “የአስትሮሎጂ መሰረታዊያን (Introduction to Astrology) ሊባል ይችላል” ያለችውን ገለጻ እኔም ብጠቀመው እወዳለሁ። ፍካሬ ኢትዮጵያን የበለጠ ለማጣጣምና ለመረዳት የኢትዮጵያ ኮከብ እንደ አብሪ ጥይት መንገድ ጠራጊ ሆኖ የሚያገልግል መጽሐፍ ነው።
በፍካሬ ኢትዮጵያ፣ አርኪ በሆነ መልኩ የባዮግራፊ ኮክቴል ታገኛላችሁ። እነዚህን ከመቶ ሃምሳ በላይ የባዮግራፊ ክምችቶች ስታነቡ፣ ነፍሳችሁ እጅግ ሀሴት እንደምታደርግ አልጠራጠርም። ስለ ሀዲስ ዓለማየሁ፣ ስለ እማሆይ ጽጌ ማርያም፣ ስለ መኮንን ሐብተወልድ፣ ስለ አዳም እና ሔዋን፣ ስለ መንግሥቱ ለማ፣ ስለ አጼ ምኒልክና ስለ ጣይቱ፣ ስለ አጼ ሐይለሥላሴና ስለ ኢያሱ፣ ስለ እነ አክሊሉ ሀብተወልድ እና ……. ስለ ሌሎች ኢትዮጵያዊያንና ኢትዮጵያዊ ያልሆኑ ስመጥር ሰዎች የሕይወት ታሪክ በጣፋጭ ቋንቋ ተሰናድቷል።
መጽሐፉ አራት ዐብይ ክፍሎችና እና 18 ምእራፎች ሲኖሩት፣ ከፊቱ አበርክቶ፣ ማውጫና፣ መቅድም አለው፣ ከኋላው ደግሞ ድኅረ ቃል፣ ዋቢ መጻሕፍት እና ምስጋናን ይዟል። እነዚህን አለፍ አለፍ እያልኩ አስተዋውቃለሁ።
ክፍል አንድ፡ የአሥራ ሁለቱ ነገደ ከዋክብት ፍካሬ
በክፍል አንድ የአሥራ ሁለቱ ዋና ዋና ኮከቦች ሰፋ ያለ ሐተታ በሁለት፣ በሁለት ክፍል ተዋቅሮ ቀርቧል። በመጀመሪያው ክፍል የየኮከቡ ንድፈ ሐሳባዊ ገለጻ በስፋትና በብቃት ተብራርቷል፤ በለጣቂው ክፍል ደግሞ ተጨማሪ ንድፈ ሐሳባዊ ማብራሪያዎች በምሳሌዎች ዳብረው ቀርበዋል።
ለምሳሌ ያህል፣ እስኪ ቶረስን እንይ። በመጀመሪያዎቹ አምሥት ገጾች፣ ስለ ቶረስ ባህርያት ከተብራራ በኋላ፣ በቀጣዮቹ 14 ገጾች ከላይ ለተጠቀሰው እንደ ማጠናከሪያና ማስፋፊያ፣ የህይወት ታሪክ አጻጻፍ ስልትን በተከተለ መልኩ የቶረስ ኮከብ ያላቸው ስመጥር ሰዎችና የቶረስ ኮከብ ባለቤት ከመሆናቸው የተነሳ ያሳዩት ባሕሪና የከወኗቸው ድርጊቶች ተተርከዋል። ከነዚህም ውስጥ የአጼ ኃይለሥላሴ አባት ራስ መኮንን፣ ካርል ማርክስ፣ ሌኒን፣ ስብሐት ገብረእግዚአብሔር፣ የኡራጋዩ ፕሬዚደንት ጆሴ ሙጂካ፣ የኤደን ገነት፣ ሶቅራጥስ፣ ናርሲሰስ፣ አዶኒስ፣ ሼክስፒር፣ ማኪያቬሊ፣ ፍሮይድ፣ ፒኬቲ እና ሌሎችም በርካታ ቶረሶች  የከወኗቸው አስደናቂ ተግባራት በሚጣፍጥ ቋንቋ በበቂ ሁኔታ ቀርቦላችኋል።  
ስለነዚህ ሰዎች ስታነቡ፣ ራሳችሁ ቶረስ የሆናችሁ እንደሆነ የራሳችሁን ገጽታ በሌላ ሰው ስብእና ውስጥ ታገኙታላችሁ፤ አልሆናችሁ እንደሆነ ደግሞ የምታውቋቸውን ሰዎች እያሰባችሁ አንድን ነገር ለምን እንዳደረጉት ትረዱዋቸዋላችሁ። ከዚህ ከቶረስ ክፍል፣ የአንዲት አንቀጽ ክፋይ ላቅምሳችሁ (ገጽ 49)፡-
ከሚያዚያ 27፣ 1928 እስከ 2004 የኖረው ስብሐት ገብረእግዚአብሔርም ከስመጥር ፈላስፋዎች ጐን የሚመደብ ነው። ስብሐት ለሲግመንድ ፍሮይድ፣ ለካርል ማርክስና ለሼክስፒር ልዩ ፍቅር እንዳለው እየደጋገመ ይናገር ነበር። የሦስቱም ኮከብ ቶረስ ነው። ዶስቶቭስኪና ካሙ ለተባሉት ደራሲያንና ደጎል ለተባለው መሪ ደግሞ ልዩ አድናቆት ነበረው። ሦስቱም ስኮርፒዮ ናቸው። ስኮርፒዮ የቶረስ ዋልታዊ ተቃርኖ ኮከብ ነው፤ ሁሉም ኮከቦች በተቃራኒ ኮከባቸው ባህሪና ተፈጥሮ ይደመማሉ።
የ12ቱ ኮከብ ሐተታ፤ ወጥ አካሔድ መከተሉ፣ መጽሐፉን ለአንባቢ በጣም ምቹና ቀላል ያደርገዋል። ሐተታው በአጠቃላይ 260 ገጾችን የያዘ ሲሆን እያንዳንዱ በአማካይ በ21 ገጾች ተብራርቷል ማለት ነው። እያንዳንዱ ክፍል በፈረንጅና በአበሻ ኦቆጣጠር ከመቼ እስከ መቼ ነው የሚውለው በሚል ይጀምራል፤ ለምሳሌ ሳጁታሪየስ (ከ23 ኖቬምበር - 21 ዲሴምበር ወይም ከህዳር 14 - ታህሳስ 12) እንደ ማለት ነው። እያንዳንዱን ኮከብ ይገልጻሉ ተብለው የታሰቡ ጥቅሶች ተመርጠው ቀርበዋል። ለምሳሌ ያህል ስለ ጂኦሎጂ ብቻ ብዙ ነገር ከማውቅ፣ ስለ ስነ ጽሁፍም፣ ስለ ፖለቲካም፣ ስለ ባህልም፣ ስለ ፊዚክስም፣ ስለ ሀይማኖትም፣ ስለ ስነ ፍጥረትም … ትንሽ ትንሽ ባውቅ የተሻለ ነው ብለው የሚያስቡትን ጄሚናዮች ይወክላል የተባለው ጥቅስ የሚከተለው ነው (ገጽ 55)፡ “ስለ አንድ ጉዳይ ሁሉን ከማወቅ፣ ስለ ሁሉም ጉዳዮች አንድ ነገር ማወቅ ይበልጣል።-ፓስካል”። የሚገርመው ነገር ፓስካል ራሱ ጄሚናይ መሆኑ ነው። ጄሚናዮች ይህ ይወክላችኋል? እኔን በደንብ ወክሎኛል። ከዚህ በመቀጠል ደግሞ፣ አሁንም ለእያንዳንዱ ሐተታ ኮከብ መግቢያ፣ ምንጫቸው ህዝባዊ የሆነ ሀገር በቀል ባለ ሁለት ስንኝ መንቶ ቃላዊ ግጥሞች ይገኛሉ። እነዚህም፣ እያንዳንዱን ኮከብ የበለጠ ለመግለጽ የዋሉ ናቸው። ለምሳሌ፣ ወግ አጥባቂዎቹን ካፕሪኮርኖች ለመግለጽ፣ጸሃፊው፣ “እንደምነህ ብለው - እንደምነሽ አለኝ፤ የግዚሀር ሰላምታ - ሊቀር ነው መሰለኝ።” የሚለውን ስነቃል ተጠቅሟል። ካፔዎች ምን ትላላችሁ?

ከእያንዳንዱ ሐተታ ኮከብ የገለፃዎቹ ማብቂያ ላይ ደግሞ፣ እንደ መውጫ፣ በፊደል ቅደም ተከተል ተራ  ከአንድ ሺ ሁለት መቶ በላይ የስመጥሮች ዝርዝር ቀርቧል። በዝርዝሩ ውስጥ በዋናነት የኢትዮጵያውያንና የውጭ ሀገር ስመጥሮች፣ የአገሮች፣ የከተሞችና የገፀባህርያት ስሞች ተካተዋል።  አሕጽሮተ ቃላት፤ መቅ= መጽሐፍ ቅዱስ፤ ልፊ= በልቦለድ እና በፊልም ውስጥ የሚታወቁ ገፀባህርያት፤ ፍእመ= ፍቅር እስከ መቃብር፤ ግአ= ግሪክ አፈታሪክ፤ ተ=በተረት ውስጥ የሚታወቁ ገፀባህርያት በማለትም ገለጻቸው ተካቷል። ለምሳሌ፣ ራሱ ስኮርፒዮ በሆነው ተቋም በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ በአንድ ወቅት የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት የነበሩት ዶክተር ዐቢይ ክፍሌና፣ ፕሮፌሰር አንድርያስ እሽቴ ሦስቱም በስመ ጥር ስኮርፒዮዎች ምድብ ውስጥ ቀርበዋል። የፍልስፍና መምህሩ ዶክተር ዳኛቸው አሰፋ፣ ትንቢት ተናጋሪው የወሎው ሼክ ሁሴን ጅብሪልና የሐረር ከተማ - ሦስቱም ከስመጥር ሳጁታሪየሶች ዝርዝር ውስጥ ተካተዋል። አንዳች መመሳል ይታያችኋል? እንዲህ እንዲህ እያላችሁ ከግለሰቦች አልፎ፣ ሀገራትና ተቋማት፣ ገጸባህርያትና ጋዜጦች መጽሔቶች ሁሉ ኮከብ እንዳላቸውና ኮከባቸው ምን እንደሆነ፣ በዚያም የተነሳ ምን ምን ባህሪ እንደሚያሳዩ በመጽሀፉ ውስጥ ተብራርቷል።
ክፍል ሁለት፡ የዐውደ ነገሥት፣ የባሕረ ሐሳብ እና የፍቅር እስከ መቃብር ፍካሬ
ክፍል ሁለት፣ ሦስት ፍካሬዎችን አካቷል፡ የዐውደ ነገሥት ፍካሬ የሚለው የመጀመሪያው ንዑስ ክፍል ሲሆን በ13 ገጾች ተብራርቷል። በውስጡም፣ በዐውደ ነገሥት አሰራር የአንድ ሰው ኮከብ እንዴት እንደሚወሰንና የሞክሼ ፊደላት ጉዳይ በስሌቱ ላይ ያላቸው ተጽእኖ፣ የፊደልና የልደት ቀን ኮከብ ይመሳሰላል ወይስ አይመሳሰልም? ወደ የትኛው ማድላት ይሻላል? የሚለው፣ ዐውደ ነገሥት 12ቱን ኮከቦች የገለፀባቸው አግባብነት፣ እንዲሁም ስለ ዐውደ ነገሥትና ሆራሪ አስትሮሎጂ እና ሌሎች መሰል ርእሰ ጉዳዮችን የያዙ ሀሳቦች ተብራርተዋል።
እንዲሁም፣ የባሕረ ሐሳብ ፍካሬም ለውይይት ቀርቧል። ባሕረ ሐሳብ ወይም የኢትዮጵያ የዘመን ቆጠራ ጥበብ፣ አለቃ ያሬድ ፈንታና ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ በየመጸሕፍቶቻቸው ያነሱት ሀሳብ ተፍታቶ ቀርቧል። በገጽ 287 ላይ፣ “ባሕረ ሐሳብ ድንቅ የዕውቀትና የጥበብ መስክ ነው፡፡ ተድበስብሶና ተዝረክርኮ የቀረ የሚመስለውን አገር በቀሉን የፍካሬ ከዋክብት ዕውቀታችንን ለማሰባሰብም ባሕረ ሐሳብ አንዱና ዋነኛው መንገድ ሊሆን ይችላል፡፡” ይላል ደራሲው።
የፍቅር እስከ መቃብር ፍካሬ በ52 ገጾች ተብራርቷል። ይህ ገጸ ባህርያትን በአስትሮሎጂ ማእቀፍ ውስጥ ማየት በስነጽሁፉ ዘርፍ ፈር ቀዳጅና ልዩ የሆነ አካሔድ ነው። ጸሃፊው በፍቅር አስከ መቃብር ውስጥ ካሉት ዋና ዋና ገጸ ባህርያት አንዱ የሆነውን የጉዱ ካሳን ዓመልና ባሕሪ በማጥናት ኮከቡ አኳሪየስ መሆኑን፣ በ2001 ዓ.ም የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የቋንቋዎች ጥናት ተቋም ባዘጋጀው 21ኛው የቋንቋዎች ጥናት ኮንፍረንስ ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ ማቅረቡን አውቃለሁ። ርእሱም፡-‘የዘመን፣ የአገር እና የገፀ ባሕሪ ትንተና በአስትሮሎጂ ማእቀፍ ውስጥʼ የሚል ነበር። የጉዱ ካሳ ኮከብ አኳሪየስ ለመሆኑ ከመጽሐፉ ውስጥ ዐበይት የሆኑትን የካሳ ዳምጤን ባሕርያት በማውጣት አሳይቷል፡፡ በወቅቱም የቋንቋ ምሁራኑ፣ ፈር ቀዳጅና አዲስ አቀራረብ ነው በማለት አድንቀውታል። ይህንን ምእራፍ ሳነብ፣ ምነው ሀዲስ ዓለማየሁ በኖሩና፣ የሚሉትን በሰማሁ ብዬ መመኘቴ አልቀረም። ጉዱ ካሳ አኳሪየስ ነው፣ በዛብህ ፓይሰስ ነው፣ ሰብለወንጌል ስኮርፒዮ ናት ወይም ካሳ ዳምጤ፣ ደለዊ ንፋስ፣ በዛብህ ሁት ውሃ፣ ሰብለወንጌል ደግሞ ዐቅራብ ውሃ ናቸው ሲባሉ፣ምን ይሉ ነበር?
አንባቢዎች፤ ይህንን የፍቅር እስከ መቃብርን ፍካሬ ካነበባችሁ በኋላ፣ ፍቅር እስከ መቃብርን እንደገና ማንበባችሁ አይቀሬ ነው። ምክንያቱም፣ የመጽሐፉ መግለጫ እነሆ በስነ ከዋክብት ሳይንስ ተሰናስሏልና ነው። ጸሃፊው፣ አልፎ ተርፎም ፍቅር እስከ መቃብርን ከታሪክ ጋር አመሳክሮ ተንትኖ፣ መጽሐፉ ፈጽሞ ልቦለድ አይደለም፣ እውነተኛ ታሪክ ነው ሊለን ይሞክራል። እስኪ አንብቡና ፍረዱ፡፡
በገጽ 293፣ “የፍቅር እስከ መቃብር ታሪክ ከዐፄ ቴዎድሮስ ዘመን አንስቶ እስከ ዐፄ ኃይለሥላሴ የመጨረሻዎቹ ዓመታት ድረስ የሚዘልቅ ነው የሚመስለው። ይኸ አተያይ ደራሲው ራሳቸው ካመላከቱት ዘመን ብዙም የሚዛነፍና የሚጣረስ አይመስለኝም።” በማለት እመት ውድነሽ የ19ኛው  ክፍለ  ዘመን  ኢትዮጵያን  ይወክላሉ ይለናል - ጸሃፊው።
የፍቅር እስከ መቃብር ታሪክ ቢጋር፣ የቦጋለ እና የውድነሽ ኮከብ፣ የቦጋለ እና የውድነሽ ገጸ ባህሪ ውክልና፣ የበዛብህ ኮከብ ትንታኔና በመጽሐፉ ውስጥ ያለው ውክልና፣ የሰብለወንጌል ኮከብ ትንታኔና በመጽሐፉ ውስጥ ያላት ውክልና፣ የሰብለወንጌልና የጉዱ ካሳ ኮከብ የስምምነት ደረጃ፣ የሰብለና የበዛብህ ኮከብ የስምምነት ደረጃ፣ የፊታውራሪ መሸሻ እና የአጼ ኃይለሥላሴ (ሁለቱም ሊዮዎች ናቸው) ተመሳስሎ፣ በተለምዶ የታህሳሱ ግርግር የሚባለው የ1953ቱ መፈንቅለ መንግሥትና በፍቅር እስከ መቃብር የተተረከው የባላገሮች ዓመጽ፣ ጉዱ ካሳ አቤቶ ኢያሱን ይወክላል የሚለው አመክንዮ (ሁለቱም አኳሪየስ ናቸው) እና ሌሎች በጣም አስደናቂ የሆኑ አስትሮሎጂካዊና ታሪካዊ ትንታኔዎች መጽሐፉን እንደገና እንድናነበው ያስገድደናል።
ክፍል ሦስት፡ የማንዴላ ኮከብ ፍካሬ እና የመለስ ኮከብ ፍካሬ
ይህ ክፍል አስትሮሎጂን በተግባር የምናይበት ነው። የኔልሰን ማንዴላን የሕይወት ታሪክ በሙሉም፣ በከፊልም፣ በጥቂቱም እንደሁኔታው የማናውቅ አንኖርም። ኔልሰን ማንዴላ ማነው ቢባል-ደቡብ አፍሪካዊ የነጻት ታጋይ ነው የማይል የለም። ስለዚህ፣ ማንዴላ፣ በደቡብ አፍሪካ፣ እ.ኤ.አ ጁላይ 18 ቀን 1918 ዓ.ም ከቀኑ 8 ሰዓት ከ54 ደቂቃ  ላይ መወለዱ ምን ተጽእኖ አሳድሮበታል? እንዲሁም፣ ሚያዝያ 30 ቀን 1947 ዓ.ም ዓድዋ ላይ የተወለዱት የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ በዚህ ቀንና ዓመተ ምህረት መወለዳቸው ለስብእናቸው ምን አስተዋጽኦ ነበረው? እነዚህ የሁለቱ ታላላቅ ሰዎች ትንታኔ ኮከብ፣ በስፋትና በጥልቀት ታይቷል።
ክፍል አራት፡ የዘፈን ምርጫ ለኮከቦች እና የኮከቦች ዝማሬ
እስኪ፣ ለእያንዳንዱ ኮከብ ከተመረጡት ዜማዎች መካከል፣ ለናሙና ያህል የተወሰኑትን እንይ፤
ለኤሪስ- የፍቅር ጦርነት አለ ብትሉኝ፤ የመጀመሪያዋ ዘማች እኔ ነኝ (ብዙነሽ በቀለ)፣ ለቶረስ- ያዋከቡት ነገር (ጥላሁን ገሠሠ፣ ለጄሚናይ- ድንገት ሳላስበው (ብዙነሽ በቀለ)።
ከኮከቦች ብልጭታ ናሙና፡ ካፔ ለእርጋታ፣ አኳሪየስ  ላፈርሳታ፣ ፓይሰስ  ለይሉኝታ።
ከኮከቦችና መርሀቸው ናሙና፡ ሊዮ አደርገዋለሁ  I will፣  ቪርጐ  እተነትናለሁ  I analyze፣ ሊብራ   አመዛዝናለሁ  I balance
ኮከቦችና ሚንስቴር መስሪያቤቶች፣ የኮከቦች ገደኛ ቁጥር፣ ኮከቦችና የህክምና ዘርፎች እንዲሁም፣ ኮከቦቹን ሊወክል የሚችል አንድ አንድ ቃል፣ በዜማዊ ቃና ተመርጦ ቀርቧል።
በድኅረ ቃል
አልበርት ፓይክ MORALS and DOGMA በተባለው መጽሐፉ ከዘገበውና ጆን ጃክሰን ደግሞ Ethiopia and the Origin of Civilization በሚለው ጽሑፉ ስለ ኢትዮጵያ የአስትሮሎጂ ጥበብ ጀማሪነት ያቀረቡት ማስረጃ፣ በጣም አስደናቂና ለካንስ እኛ የብዙ ነገር ጀማሪዎች ነን የምንባለው ያለ ነገር አይደለም ያስብላል።
በዚያው ያልገፋንበትና ዛሬ ከእኛ እኩል ከነበሩት ከነ ቻይና፣ ኮሪያ እና ጃፓን አንሰን ያለነው ለምንድነው? የአስትሮሎጂ እውቀት ጀማሪ መሆናችንና አሁን ደግሞ ስለ አስትሮሎጂ ከፈረንጆቹ ለማወቅ የምንተጋው ለምንድነው? ሀገር በቀል የሆነው እውቀት እንዴት ባህር ተሻግሮ ሊሄድ ቻለ? በአስትሮሎጂ ሳይንስ እውቀት ያደጉት አገሮች ተጠቅመዋል ወይ? እኛስ ምን ቀረብን ? እና የመሳሰሉትን ጥያቄዎች ያጭርብናል።
አስትሮሎጂካዊ የምስጋና አጻጻፍ ዘዴ
ከአሁን በፊት ለተለያየ አላማ ባነበብኳቸው የአማርኛም ሆነ የእንግሊዝኛ መጻሕፍት ውስጥ፣ ምስጋና በተለያየ መልክ ሲጻፍ አይቻለሁ። ሆኖም የፍካሬ ኢትዮጵያን ምስጋና የመሰለ እስካሆን አላየሁም። አንድ ዘና የሚያደርግ አንቀጽ ላሳያችሁ -ገጽ 402፡ለመጽሐፉ  ምርቃት  አክብረውኝ  የተገኙልኝን  ሁሉ ከልብ ማመስገን እወዳለሁ፡፡ በፍጥነት ለማስታወስ የቻልኳውን ስሞች ብቻ እጠቅሳለሁ፡፡
ፕሮፌሰር ባየ ይማም (ካፕሪኮርን)፣ ዶክተር ፈቃደ አዘዘ (ካንሰር)፣ ዶክተር ታከለ ታደሰ (ስኮርፒዮ)፣ አቶ ተስፋየ ገብረ ማርያም (ጄሚናይ)፣ ዶክተር ሙሉጌታ ሥዩም፣ እሸቱ ጥሩነህ (ፓይሰስ) ፣ አበረ አዳሙ (ስኮርፒዮ)፣ ታደለ ገድሌ (ቶረስ)፣ ሊቀ ሕሩያን ተግባሩ አዳነ (ካፕሪኮርን)፣ ጥበቡ በለጠ (ኤሪስ)፣ ምህረት (የሪፖርተርዋ)፣ ተስፋዬ መሰለ (ካፔ)፣ ዮሐንስ አስፋው (አኳሪየስ)፣ ጌታሁን መሰለ (ሳጅ)፣ ሞገስ ገብረማርም (ስኮርፒዮ)፣ አራጌ ይመር (ፓይሰስ)፣ ሙባረክ ኑሩ (ሳጅ)፣ ዳንኤል (ቶረስ) እና ባለቤቱ (ሳጅ) ፣ ፍስሐ ስሜ (ካፔ)፣ ማርሸት ጐሳዬ (ፓይሰስ)፣ አባይ ጐሳዬ (ካንሰር)፣ ሚሊዮን ገብረመድኅን (ካፔ)፣ ምኞቴ አሰፋ (ካፔ)፣ ትእግስት ደምሌ (ፓይሰስ)፣ ሐመልማል ጌታቸው (ቶረስ)፣ አደይ (ስኮርፒዮ)፣ ሙሉነሽ ሐይለሥላሴ (ካንሰር)፣ ዮርዳኖስ ሽፈራው (ኤሪስ)፣ ንጉሴ ፍስሐ (ቶረስ)፣ አሳምነው (ቪርጐ)፣ የሉሊት (አኳሪየስ) ባለቤት ጐበና (ቪርጐ)፣ መለሰ (ሊዮ)፣ ታደሰ ኃይሉ (ሊዮ)፣ አበበ (አኳሪየስ)፣ የሙሴ (ሳጅ) ህይወት (ቪርጐ)፣ ቤዛ ሙሉጌታ (ኤሪስ)፣ ዮናስ (ሊዮ)፣ ያሬድ እንደሻው፣ ሳምራዊት በቀለ (ካፔ)፣ ………።
አጠቃላይ የመጽሐፉ አወቃቀር ሲታይ፣ አማካይ አንባቢ በቀላሉ እንዲረዳው ታስቦ የተዘጋጀ ነው። ፍካሬ ኢትዮጵያ፣ በይዘቱ መለስተኛ ኢንሳይክሎፒዲያ ቢባል የማያንስበት፣ በመጠኑ አንጀት አርስ፣ በአጻጻፉ ደግሞ አካዳሚያዊ ደረጃውን የጠበቀ፣ በምሁራዊ ሃላፊነትና በብርቱ ጥንቃቄ የተዘጋጀ፣ ባዮግራፊክ የአጻጻፍ ስልትን የተከተለ ድንቅ መጽሐፍ ነው። እየተዝናናችሁ ብዙ ቁምነገር ታተርፉበታላችሁ።

Published in ጥበብ

ለመቄዶንያ 500ሺ ብር አበረከተ

በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ የክፍያ ካርድ ያስተዋወቀው ዳሽን ባንክ፤ አሁን ደግሞ የአሜሪካ ኤክስፕረስ ካርድ፣ የሞባይልና ኤጀንሲ (ውክልና) አገልግሎት በቅርብ እንደሚጀምር ተገለፀ፡፡
የአሜሪካ ኤክስፕረስ ካርድ ከፍተኛ ገንዘብ የሚያንቀሳቅሱ ሀብታሞች የሚጠቀሙበት “ፕሪስቲጂየስ ካርድ” ነው ያሉት  የዳሽን  ባንክ የፕሮሞሽን ዋና ክፍል ኃላፊ አቶ እስጢፋኖስ በፍቃዱ፤ ከውጭ የሚመጡ ሀብታሞች ካርዱን ስለሚጠቀሙ ለውጭ ምንዛሬ ዕድገት ከፍተኛ ሚና ይኖረዋል ብለዋል፡፡ በቪዛ ካርድ እንዳደረግነው ሁሉ፣ የአሜሪካን ኤክስፕረስ ብራንድ ያላቸውን ካርዶች አምርተን ከጥር ጀምሮ ለህዝቡ እናድላለን ያሉት ኃላፊው፣ ካርዱ በአሜሪካ የሚያስገኛቸውን ጥቅሞች እዚህም ያስገኛል ብለዋል፡፡
አንድ ሰው በአሜሪካ በኤክስፕረስ ካርዱ ፒዛ ገዝቶ በመብላቱ ብቻ 40  ዶላር ሊመለስለት ይችላል፡፡ እዚህም የካርዱን አገልግሎት በሚሰጡ ማዕከላት ለምሳሌ እንደ ካልዲስ ወይም ሌላ ካፌ ፒዛ በልቶ፣ ወተት ወይም ማኪያቶ ጠጥቶ ካርዱን ሲሰጣቸው 40 ብር ሊመልሱለት ወይም የመቶ ብር ዕቃ ገዝቶ 80 ብር ሊመለስለት እንደሚችል አስረድተዋል፡፡
ዳሽን ባንክ ከትንሽ እስከ ትልቅ የፕላቲንየም፣ የብርና የወርቅ ብራንድ ያላቸው አሜሪካን ኤክስፕረስ ካርዶች ያዘጋጀ ሲሆን እንደ ግለሰቡ ፍላጐት የ100ሺ፣ የ300 ሺና የ500 ሺና ብር ካርድ ሊዘጋጅለት እንደሚችል ታውቋል፡፡
ዳሽን ባንክ፣ በአገራችን ያልነበረ አዲስ የሞባይልና ኤጀንሲ (የውክልና) አገልግሎት በሚቀጥለው ታህሳስ ወር ለመጀመር ዝግጅት ማጠናቀቁን አስታውቋል፡፡ ሞባይልና  ኤጀንሲ ማለት፣ ዳሽን ባንክ ቅርንጫፍ በሌለው አካባቢ አገልግሎት የሚሰጥ በማህበረሰቡ የተወደደና የተመረጠ ወኪል ማለት እንደሆነ አቶ እስጢፋኖስ ገልፀዋል፡፡
ዳሽን ባንክ ቅርንጫፍ በሌለው ትንሽ ከተማ ማህበረሰቡ የሚወደውና የሚያምነው ነዳጅ ማደያ፣ ሱፐርማርኬት፣ ወይም ከሌላ ድርጅት ጋር ውክልና ይፈራረማል፡፡ ውሉ የተሰጠው ድርጅት የተወሰነ ገንዘብ (200ሺ፣ 300 ሺ፣… ብር) እንዲያሲዝ ይደረጋል፡፡ ከዚያም፣ አዲስ አበባ፣ ጎንደር፣ መቀሌ፣ ጂማ፣ ሐዋሳ፣ ድሬደዋ፣ …. ያለ የዳሽን ባንክ ደንበኛ፣ ሞባይልና ኤጀንሲ ወዳለበት ቀበሌ ገበሬ ማኅበር፣ መንደር ወይም ትንሽ ከተማ፣ … ለሚኖር ዘመድ ወይም የንግድ ባልደረባ፣ … እንዲሰጠው ገንዘብ ዳሽን ባንክ ያስገባል፡፡
ባንኩም፣ ለላኪው፣ ተቀባይ ገንዘቡን የሚቀበልበትን ሚስጢራዊ ቁጥር ወይም ኮድ ይሰጠዋል፡፡ ከዚያም ለሞባይልና ኤጀንሲው (ወኪሉ) ደውሎ፣ እንዲህ ዓይነት ኮድ ለሚያቀርብልህ ሰው ወይም ድርጅት፣ ይህን ያህል ብር ክፈለው የሚል መልእክት ያስተላልፍና ወኪሉ ካስቀመጠው ገንዘብ ላይ የከፈለው ገንዘብ እንዲቀነስ ይደረጋል፡፡ በመጨረሻም፣ ወኪሉ ለሰጠው አገልሎግት ባንኩ ኮሚሽን ይከፍለዋል በማለት አስረድተዋል፡፡
በሌላ በኩል የዳሽን ባንክ የዳይሬክተሮች ቦርድ መቄዶንያ የአረጋውያንና የአዕምሮ ሕሙማን መርጃ ማዕከልን “ብቸኛ የዓመቱ ምርጥ በጐ አድራጐት ድርጅት” በማለት የ500ሺ ብር የገንዘብ ድጋፍ ማድረጉን የማዕከሉ መሥራችና ሥራ አስኪያጅ አቶ ቢንያም በለጠ አስታወቁ፡፡
መቄዶንያ በአሁኑ ወቅት 715 አረጋውያንና የአዕምሮ ሕሙማንን በተለይም የአልጋ ቁራኛ የሆኑ፣ ለመመገብም ሆነ ለመፀዳዳት የሰው ድጋፍ የሚያስፈልጋቸውን ወገኖች ከወደቁበት ጐዳና በማንሳት፣ የምግብ፣ የልብስ፣ የሕክምና፣ የተሟላ ቤተሰባዊ ፍቅርና እንክብካቤ እያደረገ መሆኑን አቶ ቢንያም ጠቅሰው፤ ዳሽን ባንክ ለሦስት ዓመታት በተከታታይ የገንዘብ ድጋፍ ማድረጉን አስታውቀዋል፡፡
ባንኩ ባደረገላቸው ድጋፍም የብዙ ወገኖችን ሕይወት ማትረፋቸውን ገልፀው፤ ሌሎች ባንኮችና ድርጅቶች አርአያውን ተከትለው ድጋፍ እንዲያደርጉ ጠይቀዋል፡፡
በድርጅታችን የአንድ ሰው የቀን ወጪ 20 ብር ነው ያሉት ሥራ አስኪያጁ፤ የ715 ወገኖች የቀን ወጪ 14,300 ብር፣ የወር ወጪ 429ሺህ ብር፣ የዓመት ደግሞ 5 ሚ. 219 ሺ 500 ብር ይሆናል ብለዋል፡፡ ዳሽን ባንክ ዘንድሮ ለማዕከሉ ባደረገው ድጋፍ፤ ተጨማሪ 70 ሰዎችን ከጐዳና ማንሳታቸውን ጠቅሰው፤ በተረጂ ወገኖች ስም ምስጋና አቅርበዋል፡፡
በቅርቡም “ዓለም ገነት ቆርቆሮ ፋብሪካ” ለመቄዶንያ የአረጋውያንና የአዕምሮ ሕሙማን መርጃ ማዕከል 500ሺ ብር የሚገመት የዓይነት ድጋፍ ማድረጉ ይታወቃል፡፡

በትምህርታቸው ጥሩ ውጤት ያላቸውንና በአነስተኛ የኑሮ ደረጃ ውስጥ የሚገኙ 600 ሴቶችንና 200 ወንዶችን ተጠቃሚ የሚያደርግ ነፃ የትምህርት ዕድል ለመስጠት መዘጋጀቱን የአፍሪካ ሴቶች የትምህርት ፎረም (FAWE) አስታወቀ፡፡
ድርጅቱ ከማስተር ካርድ ፋውንዴሽን ጋር በመተባበር ያዘጋጀውና በመጪው ታህሳስ ወር በይፋ በሚጀመረው የትምህርት ድጋፍ፣ በተለያዩ የአገሪቱ ክልሎች የሚገኙና በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ውስጥ ሆነው በትምህርታቸው ጥሩ ውጤት ያስመዘገቡ ወጣቶችን ተጠቃሚ የሚያደርግ ነው፡፡ በአዲስ አበባ፣ አዳማ፣ ባህር ዳርና አዋሳ ከተሞች ውስጥ በሚገኙ 8 ትምህርት ቤቶች፣ ከዘጠነኛ እስከ 12ኛ ክፍል ባሉ ተማሪዎች ላይ ተግባራዊ የሚደረገው ይኸው የስኮላርሽፕ ድጋፍ፣ ተማሪዎቹ የዓለም አቀፍ ነፃ የትምህርት ዕድል እስከመስጠት ድረስ የሚዘልቅ መሆኑም ታውቋል፡፡

አዋሽ ኢንሹራንስ ኩባንያ በአገሪቱ ለመጀመሪያ ጊዜ ዓለም አቀፍ ደረጃ ያለው አዲስ የኢንሹራንስ ሶፍትዌር አሰርቶ ስራ ላይ ማዋሉን አስታወቀ፡፡ ኩባንያው በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የታገዘ ውጤማታና ቀልጣፋ አገልግሎት ለደንበኞቹ ለመስጠት፣ የተቀናጀ የጠቅላላ መድን የመረጃ ሥርዓት (General Insurance Information System - Glls) ሶፍትዌር ማሰራቱን የጠቀሱት የኩባንያው ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ፀጋዬ ከሚሴ፤ ሶፍትዌሩን የሰራው የህንዱ ኩባንያ ኢንፎዥን፣ አማካሪው ደግሞ አገር በቀሉ ናሽናል ኮንሰልቲንግ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ ዛሬ የደረስንበት ስኬት በሀገሪቷ የኢንሹራንስ ኢንዱስትሪ ውስጥ የተሟላ የቴክኖሎጂ መፍትሄ በመፍጠር ረገድ እንደ መልካም መነሻ ይታያል ያሉት ሥራ አስኪያጁ፤ በየክልሉ ያሉት ቅርንጫፎቻችን በሙሉ ይህንን አዲስ ሶፍትዌር ስለሚጠቀሙና የመረጃ ሥርዓቱ በኔትዎርክ የታገዘ በመሆኑ፣ የኩባንያው የሥራ አመራሮች የእያንዳንዱን ቅርንጫፍ ዝርዝር ሥራ በመከታተል ተገቢውን ድጋፍ በፍጥነት ይሰጣሉ ብለዋል፡፡ በመረጃ ሥርዓቱ አማካይነት ሪፖርቶችን በአጭር ጊዜ ውስጥ በማግኘት መረጃና ዕውቀት ላይ የተመሰረተ የማኔጅመንት ውሳኔ መስጠት እንደሚቻል ገልጸው፤ በውል ሰነዶች ውስጥ ያሉ መረጃዎች ሁሉ በሲስተሙ ውስጥ ስለተጠቃለሉ የሁሉም  ደንበኞች የውል፣ የካሣ፣ የጠለፋ ዋስትና፣ የገበያ ልማትና የፋይናንስ መረጃዎች በቀላሉ የሚናበቡ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡
በውላቸው መሰረት ሶፍትዌሩን የሰራውና አማካሪው በየጊዜው ማሻሻያ እንደሚያደርጉና ይሄም ለኩባንያው ራዕይ መሳካት ከፍተኛ ሚና እንደሚጫወት የገለፁት ሥራ አስኪያጁ፤ በዚህም “ግንባር ቀደምና ተመራጭ መድን ሰጪ መሆን” የሚለውን የኩባንያችንን ራዕይ እናሳካለን ብለዋል፡፡ ለሶፍትዌሩ 2.5 ሚሊዮን፣ ለሃርድዌሩ ደግሞ 3 ሚሊዮን ብር ወጪ መደረጉንም ገልጸዋል፡፡  

Page 5 of 19