ከአገር ውጭ የሚደረጉ ጉዞዎችንና የትምህርት ክፍያ ማረጋገጫ ዋስትናዎችን መስጠት እንደጀመረ የገለፀው ኢትዮ ለይፍ ኤንድ ጀነራል ኢንሹራንስ አክሲዮን ማህበር፤ ይህም አገልግሎቱን የተሟላ ለማድረግ እንደሚያስችለው የድርጅቱ ኃላፊዎች ከትናንት በስቲያ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አስታወቁ፡፡
በአገሪቱ የኢንሹራንስ ገበያ ውስጥ አዳዲስ አሠራሮች ናቸው ከተባሉት ከእነዚህ የመድን ዋስትናዎች በተጨማሪ የህክምና፣ የዕድሜ ልክ፣ የኢንዶውመንት፣ የብድር ዕዳ ማስወገጃ፣ የእሳት ቃጠሎና የመብረቅ፣ የአበባ እርሻ፣ የሠራተኞች ጉዳት ካሳ፣ የምሕንድስና መድንና ሌሎች የዋስትና ዓይነቶችንም ለአገልግሎት ማቅረቡን አስታውቋል፡፡
በጥቅምት ወር 2001 ዓ.ም ከብሔራዊ ባንክ በተሰጠው ፍቃድ መሰረት ሥራ የጀመረው አክስዮን ማህበሩ፤ በአሁኑ ወቅት 58ሺ አክሲዮኖችን ለሽያጭ ማቅረቡንና የአገልግሎት አድማሱን በማስፋት ሚሊዮኖችን ለማገልገል ዝግጅቱን ማጠናቀቁን ገልጿል፡፡ በ
ቅርቡ በአዲስ አበባና በኦሮሚያ ክልል ሁለት ቅርንጫፎቹን በመክፈት የቅርንጫፍ ቢሮዎቹን ቁጥር ወደ 15 ከፍ ለማድረግ ማቀዱንም ኃላፊዎቹ ገልፀዋል፡፡

ኢህአዴግስ?)    በኳስ ድል ስናጣ ወደ ፕሮፓጋንዳ ገባን!

          የፖለቲካ ወጋችንን ሰሞኑን በEBC (በጥንቱ ኢቲቪ ማለቴ ነው!) የስፖርት ፕሮግራም ላይ በሰማሁት አስገራሚ ዜና ለምን አንጀምረውም፡፡ ዘገባው የጀመረው የማሊ እግር ኳስ ቡድን (አሰልጣኝ መሰሉኝ?) “በአዲስ አበባ ላይ ባዩት ለውጥ ተገረሙ” በሚል ነው፡፡ ተገርመው ብቻ ግን ዝም አላሉም፡፡ “የአፍሪካ አገራት ከአዲስ አበባ ብዙ መማር አለባቸው” እንዳሉም  የስፖርት ጋዜጠኛው ዘግቧል (ስንቱ ይሆን ከኛ የሚማረው?!)
ይኸውላችሁ ልማታዊ ጋዜጠኝነት ስኬት ስኬቱ ላይ (success stories) አተኩር እንደሚል ዘንግቼው አይደለም፡፡ ግን የስፖርት (ያውም የእግር ኳስ) ዜና ላይ “አዲስ አበባን አደነቁ!” ዓይነት ዘገባ ስላልጠበቅሁ ነው! በኋላ ግን ችግሩ ገባኝ፡፡ ኳሱ የሚደነቅ ካልሆነ የትኩረት አቅጣጫን መቀየር የግድ ነው፡፡ አያችሁ … በኳስ ጨዋታው ውጤት አልተገኘም፡፡  እናም የስፖርት ጋዜጠኛው ምን ይዘግብ? ቢያንስ የማሊ እንግዶችን እየዞረ “አዲስ አበባን እንዴት አገኛችኋት?” በማለት “ልማታዊ ዜና” ወይም “ለአገር ገፅ ግንባታ አስተዋፅኦ የሚያበረክት ዘገባ” ማቅረብ አለበት፡፡ (በኳሱ ድል ቢቀናን እኮ ፕሮፓጋንዳው ይቀር ነበር፡፡)
በነገራችሁ ላይ አዲስ አበባ ስትደነቅ ወይም ደግሞ ኢትዮጵያ በፈጣን ዕድገቷ (ባለደብል ዲጂቱን ማለቴ ነው!) ስትወደስና በአርአያነት ስትጠቀስ መስማት የማይወድ ኢትዮጵያዊ ዜግነቱን እጠራጠራለሁ፡፡ የEBC ዘገባ ግን ችግሩ ምን መሰላችሁ መረጃና ፕሮፓጋንዳ ይደበላልቃል፡፡ በዚያ ላይ ማሊዎቹ እውነት አድናቆት ብቻ ነው የሰነዘሩት የሚለውም ያጠያይቃል፡፡ እንዴ…መብራት፣ ውሃ፣ ኔትዎርክ በሌለበት “አዲስ አበባ መንግስተ ሰማያት ናት” ቢሉስ ማን ያምናቸዋል፡፡
አሁን እኮ ሁሉም መሰረተ ልማቶች ጠፍተው ኢህአዴግ ብቻውን የቀረ ነው የሚመስለው፡፡ (ፕሮፓጋንዳው ግን ቀጥሏል!) በነገራችሁ ላይ አንዳንዴ ኢህአዴግ ይሁነኝ ብሎ ፕሮፓጋንዳን መተው አለበት፡፡ (ከእነ አካቴው አልወጣኝም!) በቃ በወር… በሁለት ወር አንዴ ከፕሮፓጋንዳ የፀዳ ንፁህ መረጃ ለኛ የስልጣን ህልውናውን በድምፃችን የመወሰን ስልጣን ላለን ህዝቦች ሊሰጠን ይገባል፡፡ በእርግጥ ከፕሮፓጋንዳ ለሰከንድም ቢሆን መላቀቅ ይከብዳል (ከስልጣን የባሰ ሱስ እኮ ነው!!) ሆኖም ማገገሚያም ቢሆን (Rehabilitation Center!) ገብቶ ፕሮፓጋንዳን ከደሙ ውስጥ ጠራርጎ ማስወጣት ይኖርበታል፡፡
ዕውቁ ደራሲ አዳም ረታ በቅርቡ ባወጣውና ተወዳጅነትን ባተረፈበት “መረቅ” የተሰኘ ረዥም ልብወለዱ፤ ፕሮፓጋንዳን “ጥዝጠዛ” ይለዋል፡፡ (ኢህአዴግ ስንት ዓመት ጠዘጠዘን?)
በነገራችሁ ላይ ስለ ፕሮፓጋንዳ ለማውጋት የተነሳሁት በአዳም ረታ ልቦለድ ተነሽጬ በመሆኑ በእናንተ ስም አመሰግነዋለሁ፡፡ እንዴት ነሸጠህ… አትሉኝም? ደራሲው በልብወለዱ ውስጥ ስለ ፕሮፓጋንዳ የፃፈውን አብረን እንቃኝ፡፡
“…ከአብዮት በፊት በአዲስአባ አራዶች ተወዳጅ የሆኑት ሬስቶራንቶች የፈረንጅ ምግብ የሚሸጥባቸው ነበሩ፡፡ የአብዮት ማዕበል አገሪቷን ሲንጥ ከሁሉም አቅጣጫ በሚመጡ ፖለቲከኞች ተንቀውና ፀረ - ኢምፔሪያሊስት በተባለው አቁዋም ተደናግጠው፣ ፍርሃት አስበርግጐአቸው ጠፉ፡፡ በ71 ዓ.ም አካባቢ ቀውሱ መብረድ ሲጀምር፣ ይሄን የውጭ አገር የምግብ ስፍራ በባሕል ምግብ መሙላት የቀረው አማራጭ ነበር፡፡ ይሄን የለውጥ ጐዳና ብዙዎች ተከትለዋል፤ ግን እንደ እኔ ሰፋና ገፋ አላደረጉትም፡፡ (ይሄን የሚለው የአባቱን ሆቴል ወርሶ በማሻሻል የተሳካለት “እዝራ” የተባለ ገፀባህርይ ነው) የተከፈተውን ቦታ በተመሳሳይ ይዘት ሞሉት እንጂ የተለየ ጣዕም ይሁን ቄንጥ አልወለዱም፡፡ ከላይ እንደጠቀስኩት የዝልዝል ጥብሴ ነገር በራዕይ ፈሰሰልኝና ወደ እዛ በድፍረት አመራሁ፡፡ ግን ይሄ ፈጠራዬ ተወዳጅ እንዲሆን መደረግ የሚገባቸው ውስብስብ ነገሮች ነበሩ፡፡ ከነዚህ መሰራት ከሚገባቸው ነገሮች አንደኛውና መሰረታዊው ፕሮፓጋንዳ ነበረ፡፡ ዝልዝል ጥብስና ፕሮፓጋንዳ ወይም ቀለል ላድርገውና ጥብስና ማስታወቂያን ለመሆኑ ምን አገናኛቸው?” (ወደ አዳም ዝልዝል ጥብስና ፕሮፓጋንዳ ከአፍታ “ቆይታ” በኋላ እንመለስበታለን፡፡)
እኔ የምለው ግን … የመንግስት መ/ቤት ህዝብ ግንኙነቶች (ይቅርታ “ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር” ለማለት ነው!) ዋና ሥራቸው ምንድነው? መቼም ፕሮፖጋንዳ ወይም ካድሬነት ሊሆን አይችልም፡፡ ኢህአዴግ ከባባድ ስሞች አሽሯቸው ሥራቸውን ነጠቃቸው እንዴ? (ጥያቄ እኮ ነው!) በመ/ቤታቸው ተማራችሁ ትችት ነገር …  ነቀፋ ቢጤ … ለመሰንዘር ከሞከራችሁ ከኢትዮጵያ ፀረ - ሰላም ሃይሎች ጋር ሊመድቧችሁ ምንም አይቀራቸው፡፡ ብዙ ጊዜ “ልማታችንን ለማደናቀፍ…” ምናምም ማለት ይወዳሉ፡፡ (የተተቹትን ከማስተካከል ይኸኛው ይቀላላ!) ኢህአዴግ አውቆም ይሁን ሳያውቅ፣ በየዋህነትም ይሁን በብልጣብልጥነት ካድሬ ወይም አባል አድርጓቸው ከሆነ (አያደርገውም ባይ ነኝ!) ጉዳቱ ተመልሶ ለራሱ ነው፡፡ ለምን መሰላችሁ? ሁለት ካባ ለብሰው ያምታታሉዋ! የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር እንዳሉት፤ “ህጋዊነትንና ህገወጥነትን እያጣቀሱ ይጓዛሉ”
አሁንም ወደ “መረቅ” ልመልሳችሁ፡፡   
“ …የሰው ልጆች ፍላጐት በየጊዜው ይለዋወጣል፤ ይኼ እውነት ልዩ ምስክር መጥራት  የሚያሻው አይደለም፡፡ የፍላጐት መለዋወጥ ብቻ ሳይሆን ያ ፍላጐቱ የሚተከልባቸው ማህበራዊ፣ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ሁኔታዎች ይለዋወጣሉ፡፡ እነዚህን ሳይነጣጥሉ በድምር የመረዳት ኪነቱ ነው “መረዳት” የሚሆነው፡፡ ምግብ እንደ ማንኛውም ሰባዊ ድርጊት ባሕል ነው፡፡ በአዲስነቱ እንደ ማንኛውም ዕውቀትና ባሕል መጀመሪያ መፈልሰፍ፣ ቀጥሎ በብዙዎች መኖሩ መታወቅ፣ ቀጥሎ ልማድ መሆን መቻል አለበት፡፡ ይኼ ደሞ እንደ ሁኔታው በአጭር ጊዜ ወይ በረዥም ጊዜ ሊሆን የሚችል ነው፡፡ ሰብአዊ ባሕርይ ስለሆነ የዕድገት መንገዱን ከሌሎች ሰብአዊ ድርጊቶች በመቅዳት መምራትና መቆጣጠር ይቻላል፡፡ ቀደም ብዬ ያነሳሁት የፖለቲካዊ ነገር የሚመጣው እዚህ ላይ ነው፡፡
“…ወጣቶች ፖለቲካ ውስጥ ተንጋግተው የገቡበት ሁኔታ ባብዛኛው በእኔና በሳል በሆኑ ሰዎች ግምት (ወይም በገባቸው ሰዎች ግምት) በአገራችን የሰፈነው ጭቆና አስከፊ ሆኖ መላወሻና መንቀሳቀሻ ጠፍቶአቸው ሳይሆን በረቀቀ ፕሮፓጋንዳ ግፊት መሆኑ ነው፡፡ ፕሮፓጋንዳ አዲስ ፍጡር አይደለም፤ ድሮም ነበረ፡፡ ዛሬ የፈረሰውን የሰለሞናውያን ስርወ መንግስት እዚህ ያደረሰው የአንድ ሰው ፕሮፓጋንዳ እንደ ሆነ ያውቃሉ? ታምሪን የተባለ ነጋዴ ለሳባ ስለ ሰለሞን ጥበብ ነጋ ጠባ ይነግራታል፣ በዚህ ምክንያት ሰለሞንን በአይኗ ሳታየው ወደደችው፡፡ ክብረ ነገስት “ከፍቅሯም ብዛት የተነሳ ታለቅስ ነበር፣ ለመንግስቱም (ለሰለሞን መንግስት) ልትገዛ ፈጽማ ትሻ ነበር” ይላል፡፡ ደካማ ትሁን አትሁን ወይም የዞረባት ቁሌታም፣ እንርሳውና፣ መጀመሪያውኑ ወደ ኢየሩሳሌም ሄዳ አርግዛ እንድትመጣ ቀስቃሽ ምክንያት የሆናት የነጋዴው የታምሪን ጥዝጠዛ ነው፡፡ ጥዝጠዛ ቀላል ጉዳይ አይደለም፡፡ ይሄን ክብረነገስት ውስጥ ሳነብ እስቅና እገረም ነበር…”
ደራሲው የፕሮፓጋንዳን ታሪካዊ አመጣጥ ለማስረዳት ሁሉ ሞክሯል (የ“ቤቶች” ድራማዋ አዛሉ ትዝ አለችኝ!)
ስለ ፕሮፓጋንዳ መረጃ ስበረብር እጄ ከገቡት አባባሎች ውስጥ አንዱ እንዲህ ይላል፡- “ፕሮፓጋንዳ ሰዎችን አያታልልም፤ ራሳቸውን እንዲያታልሉ ብቻ ነው የሚያግዛቸው” እውነት እኮ ነው፡፡ በጃንሆይ ዘመን ህዝቡ ድንገት ተነስቶ “ፀሐዩ ንጉሳችን!” ማለት አልጀመረም፡፡ የፕሮፓጋንዳ ውጤት ነው፡፡ አሁን በኢህአዴግ ዘመንም ቢሆን ተመሳሳይ ነው፡፡ “ልማታዊ መንግስታችን” የሚለውን እንደ አዝማች በየንግግራቸው የሚዶሉ የበዙት በቅርቡ ነው፡፡ (ከብዙ ዓመት የፕሮፓጋንዳ ልፋት በኋላ የተገኘ ድል በሉት፡፡)
“… ፖለቲካ ከወዳጆቼ ቢለያየኝም ከርቀት ሆኜ ግን እጠይቃለሁ፡፡ “ለምን?” እላለሁ፡፡ “እንዴት ሊሆን ቻለ?” እላለሁ፡፡ እንግሊዘኛ የማይችል በግዕዝ የሚጠነቁል ደብተራ የመጠየቅ መብት የለውም ማን አለ? ለምሳሌ በቀለም ትምህርቷ ጐበዝ የነበረችው፣ “ሳይንቲስት ትሆናለች” ብሎ ተማሪና አስተማሪ ተስፋ የጣለባት ተባረኪ፣ (ከፍቅር ድርጅቴ ይበልጥብኛል ብላ ኢህአፓን የሙጥኝ ያለች ገፀ ባህርይ ናት!) ፖለቲከኛ መሆን ነበረባት? ቢያንስ ቢያንስ የዳሌዋን ስፋት ያየ፣ የቁመቷን መለሎነት ያየ፣ የጡቶቿን ዲብ ያየ፣ የእግሮቿን ጠብደልነት ያየ፣ ጠንካራ ልጆች የምትወልድ ሚስት ትሆን ነበር ብሎ መገመት ይችላል፡፡ ታዲያ ከጐበዝ ተማሪነቷና ሚስት ሆና ልትወልድለት ከሚገባት አላዛር እርቃ ፖለቲካ ውስጥ መሰንቀር ይገባት ነበር? እኔ እንደምገምተው አይመስለኝም፡፡ ግን ጥሩ የፕሮፓጋንዳ መሳሪያ ትሆናለች…”
ጆስ ዌዶን የተባለ ፀሐፊ ስለዜና የተናገረው EBCን አስታወሰኝ፡፡ “የዜና ዓላማ በእርግጥ የተከሰተውን መንገር አይደለም፡፡ ልትሰሙ የምትሹትን ወይም ልትሰሙት ትፈልጋላችሁ ተብሎ የሚታሰበው ነው የሚቀርብላችሁ” ይላል፡፡ በእርግጥ የሰለጠነው ዓለም የተስማማበት የዜና ብያኔ ይሄ አይደለም፡፡ ትክክለኛና እውነተኛ መረጃ ለህብረተሰቡ ማቅረብ ነው፡፡ በሶሻሊዝምና በልማታዊ ጋዜጠኝነት ግን ዜና ሳይቀር የፕሮፓጋንዳ ሰለባ ይሆናል፡፡ ዜና በሁለት ይከፈላል ልንል እንችላለን፡፡ የኒዮሊበራሎችና የኮሚኒስቶች!! በነገራችሁ ላይ ኢህአዴግ ባለበት ሁሉ ፕሮፓጋንዳ አለ፡፡ በኢቴቪ ብቻ አይደለም፡፡ በፓርላማ ሪፖርት ወይም በመንግስት መ/ቤት ስብሰባ አሊያም ግምገማ ወይም ደግሞ በባለስልጣናት መግለጫ ሳይቀር ፕሮፓጋንዳው በሽበሽ ነው፡፡ (መዝናና ቦታም አይጠፋም!)
“በመጀመሪያ ቃል ነበር” የሚለው ዓረፍተ ነገር በሃይማኖት የስብከት ወይም በዘመኑ አለማዊ አባባል የፕሮፓንዳ መጀመሪያ ነው፡፡ (ከዲቃላው ሚኒሊክ መወለድና ሰለሞናዊ ስርወ መንግስት ከመፈጠሩ በፊት የታምሪን ቃል ነበር እንድንል) የኪነት መዝሙር የሚባለው ሁሉ በድብቅ ሆነ በግልፅ የሚዘምረው ዓለማዊ ቅዳሴ ነው፡፡ እኔ ደጀሰላም ሄጄ የአምላክን ቃል በዜማ ሳጅብ የእሱ የፈጣሪዬ ካድሬ መሆኔ ነው እኮ፡፡ ታዲያ ከነበረው ብዙ እርቀናል?
“ደግሜ ልበለውና ምድር ላይ ያሉ የሐይማኖት ተቁዋሞች ሁሉ ሰመረ አልሰመረ የእግዜር ማስታወቂያና የስለላ ድርጅቶች ናቸው፡፡ የሰዎች መናዘዝና ንስሐ መግባት በቅርብ አገሪቷ ውስጥ ሲደረግ የነበረውን ማጋለጥና ንቃት አይመስልም? ነገሩን ነው የምለው፡፡ ከላይ እስከ ታች ያለው የፖለቲካ ድርጅቶች አሰራር መለኮትና ነገረ መለኮት የተዋቀሩበትን ስልት የያዘ አይመስልም? ይኼን ማመሳሰል ሳደርግ ግን ቅንጣት ያህል ሐጢያተኛነት አይሰማኝም፡፡”
በነገራችሁ ላይ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የሃይማኖት መሪዎች ቋንቋ ተለውጦብኛል፡፡ (የእግዜር ካድሬ ሳይሆን የመንግስት ካድሬ እየመሰሉ ነው!) ጆሴፍ ጐመልስ የተባለ ፀሐፊ ደግሞ ፕሮፓጋንዳን እንዲህ ይገልፀዋል፤ “በበቂ ድግግሞሽና የህዝብ ስነልቦናዊ ግንዛቤ፤ ስኩዌር (ካሬ) ክብ መሆኑን ማረጋገጥ የማይቻል አይደለም፡፡ ዝም ብለው እኮ ቃላት ናቸው፡፡ ቃላት ደግሞ ሃሳብ እስኪለብሱና እስኪለበጡ ድረስ እንደተፈለገው ሊቀረፁ ይችላሉ፡፡” ኸርበርት ኤም. ሼልተን የተባለ ፀሐፊ እንዲሁ ተንጋደው “የተማሩ ሰዎችን ከማቃናት ጨርሶ የፊደል ደጅ ያልደረሱትን ማስተማር ይቀላል” ብሏል፡፡
ይሄውላችሁ… ኢህአዴጐች በሉ ተቃዋሚዎች… በአጠቃላይ የጦቢያ ፖለቲከኞች ከራሳቸው ውጭ ሌላውን ለመስማት ፈቃደ - ልቦና ያጡት …እልም ያሉ ትዕቢተኞች ወይም ክፉዎች ስለሆኑ አይደለም፡፡ (አንዳንዶች ግን አይጠፉም!!) ድሮ የተማሩትን፣ የሚያውቁትን፣ የኖሩትን… አስወጥተው በአዲስ መተካት ሞት ስለሚሆንባቸው ነው፡፡
አንድ (በፈቃዱ) የኢህአዴግ ተሟጋች የሆነ ወዳጅ አለኝ (ወዳጅነታችንን በከፊል በካድሬነት ለውጦታል) እናላችሁ… አልፎ አልፎ ስንገናኝ እኔ በመብራትና በኔትዎርክ መቆራረጥና መጥፋት ተማርሬ፣ ብሽቀቴን ሳጋራው፤ እሱ ሆዬ… ኢህአዴግ በቲቪ የሚያሰለቸኝን ባለሁለት ዲጂት የኢኮኖሚ ዕድገት እንደ አዲስ እየጠቀሰ ይጠዘጥዘኛል፡፡ (የሚሰለቸኝ እኮ ዕድገቱ  አይደለም - ጥዝጠዛው ነው!) አብረን በአገሪቱ መዲና እየኖርን እንዴት ስለ መንገዱና ስለ ባቡር ሃዲዱ ዝርጋታ፣ ስለ ህንፃዎቹ እንደ አሸን መፍላት፣ ስለ ፋብሪካዎቹ መበራከት ወዘተ ሊሰብከኝ ይፈልጋል (ቱሪስት እኮ አልመስልም!) እናላችሁ ወዳጆቼ… በግሉ ተደራጅቶ የፕሮፓጋንዳ ክንፍ ያዋቀረ በጎ ፈቃደኛ ካድሬም አለላችሁ፡፡ (አይጣልባችሁ እኮ ነው!)  

Saturday, 22 November 2014 12:15

ፊታውራሪ እርጅና

ባለ ጋሻ ጀግሬው ሰልፍ የሚያምርለት፣
አጀቡ አስፈሪ ጦር የበዛለት፣
ሠራዊተ ብዙ ፊታውራሪ እርጅና፣
ረጋ ብሎ ይመጣል ሞት ያስከትልና፡፡
    ስሜት ሲደበዝዝ፣
አካል ሲቀዘቅዝ፣
ዕይታ ሲደክም፣
አእምሮ ሲያዘግም፣
አደብ ይገዛሉ ህዋሳት በመላ፣
ሰውነት ይበርዳል ላይሞቅም ላይፈላ፡፡
ሆድ ጠግቦ ላይበላ ጉረሮ እህል ላይውጥ፣
ጉልበት ላይሆንለት ጦርን ሮጣ ማምለጥ፣
ነገርን አስታውሶ ለመናገር ፈጥኖ፣
እንደ ቀድሞ አይሆንም ጠፍቷልና ተንኖ፡፡
ዕቅድና ዓላማ እርግፍ አርጐ ትቶ፣
በትዝታ መኖር ምሃት፣ ተስፋ ጠፍቶ፡፡
እንስት ተባዕትን፣ ተባዕት እንስትን፣
ላይፈቃቀዱ ያሰንፋል ስሜትን፡፡
ጣፋጩ መራር ነው የሞቀው ቀዝቃዛ፣
በስተርጅና ሁሉም ይሆናል ጐምዛዛ፡፡
        ተው እርጅና፣
        ብቻህን ና!
ይህ ሁሉ ሳያንስህ ስኳሩን፣ ግፊቱን፣
ሪሁን፣ ራስ ምታቱን፣ ውጋት፣ ቁርጥማቱን፣
ነጭናጫ መሆኑን መነዝነዝ ዕለቱን፣
በትንሽ ትልቁ ፈጥኖ መከፋቱን፣
አንጋግተህ ያመጣህ ጨካኝ ነህ እርጅና፣
በስንት ጣዕሙ ሞት ይገባው ምስጋና፡፡
ኧረ ተው እርጀና አንተ ጅራታም፣
ምነው ጓዝህ በዛ (ሆንክና/ሆንክብኝ?) ኮተታም!
    ተው እርጅና፣
    ብቻህን ና!
ጥሩ ስም የሰጠህ ንገረን ማነው?
እርጅና እያሉ የጠሩህ ምነው?
እስቲ ከሞት ጋራ ተነጋገሩና፣
ከነ ተከታይህ በአንድ ላይ ሁኑና፣
እናንት? ሁለታችሁ ስብሰባ ግቡና፣
ስምህን ለውጡ ተመካከሩና፡፡
ሌላ ስም ይውጣልህ ከሞት ያላነሰ፣
ሥራህ ቢበዛ እንጂ መች ከእሱ ቀነሰ?
እናም…. ይኸው ወቀስኩህ ላትሰማኝ ነገር፣
 (ከእለታት ቀን ቆጥረህ መከሰትህ ሳይቀር?)
በሥራ በስፖርቱ አካሌን አጥብቄ፣
እጠብቅሃለሁ (አልቀርም) ወድቄ፡፡
ጦሬን ይዤ መጣሁ ደረስሁ ብትለኝም፣
እኔ አለሁ፣ አንተም ና ሥጋት አይገባኝም፡፡
በል እንግዲህ እርጅና - በቸር ያገናኘን
እስከዚያው ድረስ፣
አንተም አርጅተህ ሙት
- ወደ ልጅነቴ እኔም ልመለስ፡፡
*    *    *
ከአምሳሉ ጌታሁን ደርሰህ
ኅዳር 2007 ዓ.ም

Published in ጥበብ

ኢትዮጵያን በኤችአይቪ ምርመራና የምክር አገልግሎት ጊነስ ቡክ ኦፍ ሪከርድ ላይ ለማስመዝገብ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ዩኤንኤድስ የተባለ ድርጅት አስታወቀ፡፡
በስምንት ሰዓት ጊዜ ውስጥ ለሁለት ሺህ ሰዎች ነፃ የኤችአይቪ ምርመራና ምክር አገልግሎት በመስጠት፣ አገሪቱን በጊነስ መዝገብ ላይ ለማስመዝገብ የሚደረገው ጥረት፣ በጋምቤላ ክልል ህዳር 21 ቀን 2007 ዓ.ም እንደሚከናወን አዘጋጆቹ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡
ከሁለት ዓመት በፊት በተመሳሳይ ሁኔታ የአለም ክብረወሰን ሆኖ በጊነስ መዝገብ ላይ የሰፈረው በአሜሪካና በአርጀንቲና ለ1380 ሰዎች የተሰጠው ነፃ የምርመራና የምክር አገልግሎት እንደሆነ ታውቋል፡፡ ጥረቱ ለአገሪቱ በጐ ገፅታ ከማላበስ ባሻገር በክልሉ በኤችአይቪ ዙሪያ ያለውን ግንዛቤ ለማሳደግ ያግዛል ተብሏል፡፡

Published in ዋናው ጤና

ነባሩን መላምት የሚያፈርስ የጥናት ውጤት ተገኝቷል

አበረታች መድኀኒቶች መጀመርያ የተሰሩት የደም ማነስ ችግር ያለባቸውን ሰዎች ለመርዳት ታስቦ ነበር፡፡ መድኀኒቱ የደም ማነስ ባለባቸው ሰዎች ላይ ያመጣው ለውጥ፣ ቀይ የደም ሴላቸውን ቁጥር በመጨመር የተሻለ አቅምና ብርታት ለማግኘት የሚፈልጉ ስፖርተኞችን ቀልብ ሳበ፡፡ በተለያዩ የስፖርት ዘርፎች የሚሳተፉ ስፖርተኞች ለበለጠ ውጤታማነት አበረታች መድኀኒቶችን መጠቀም ጀመሩ፡፡ መድኀኒቱ የቀይ የደም ሴሎችን ቁጥር በመጨመር፣ ደም ኦክሲጅን የመሸከም አቅሙን የሚያሳድግ ሲሆን ስፖርተኛው በተሻለ ኃይል ውድድሩን እንዲያጠናቅቅና ውጤታማ እንዲሆን ያደርገዋል፡፡
በርካታ ዓለም አቀፍ ዝናን የተቀዳጁ ስፖርተኞች፤ ከአበረታች መድሃኒቶች ጋር በተገናኘ የስኬት ማዕረጋቸውን ተነጥቀው ለሃፍረት መዳረጋቸው ይታወቃል፡፡ የምስራቅ አፍሪካ በተለይ የኢትዮጵያና ኬንያ አትሌቶች በመልክአ ምድሩ አቀማመጥ የተነሳ ከሌሎች አገራት አትሌቶች በተለየ ቀይ የደም ሴሎቻቸው መጠን ከፍ ያለ በመሆኑ አበረታች መድሃኒቶቹን ቢጠቀሙም ባይጠቀሙም በውጤታቸው ላይ ለውጥ አያመጣም የሚል መላምት ሲቀነቀን ቆይቷል፡፡ በቅርቡ በኬንያ በተካሄደ ጥናት ግን ይሄን መላምት የሚያፈርስ ውጤት ተገኝቷል፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፊዚዮሎጂ ትምህርት ክፍል መምህርና ተመራማሪ ዶክተር ድረስባቸው ኃይሌ በጥናቱ ላይ ከተሳተፉት ተመራማሪዎች አንዱ ናቸው ባለፉት ሦስትና አራት ዓመታት በአበረታች መድኃኒት ዙሪያ ጥናት አድርገዋል፡፡ ዶ/ር ድረስባቸው ኃይሌን  በጥናቱ ዙሪያ አጭር ቃለ ምልልስ አድርገንላቸዋል፡፡

አበረታች መድሃኒት ስንል ምን ማለታችን ነው?
የቀይ የደም ሴሎች ቁጥርን በመጨመር፣ ደም ኦክስጂን የመሸከም ብቃቱን የሚያሳድጉና ሃይል በመስጠት ውጤታማነትን /performance/ የሚጨምሩ መድሃኒቶች ናቸው፡፡ ከእነዚህም መካከል አንዱና አትሌቶች በስፋት የሚጠቀሙበት ራስፓንቲን (epo) የሚባለው አይነት ነው፡፡  መድኀኒቱ ቀይ የደም ሴሎች ቁጥራቸው እንዲጨምር ለማድረግ ይረዳል፡፡ ሌሎችም የተከለከሉና አንድን ሰው አበረታች መድኀኒቶችን ተጠቅሟል የሚያሰኙ ነገሮች አሉ፡፡ ለምሳሌ አንድ ሰው የራሱን ደም ወይንም ተመሳሳይነት ያለውን የሌላ ሰውን ደም ወስዶ ፍሪጅ ውስጥ በማስቀመጥ ለውድድር ሲቀርብ ቢወስደው፣ ይህም ሰውየውን አበረታች መድኀኒት ወስዷል ሊያሰኘው ይችላል፡፡
ሌሎችም የተከለከሉና ብርታትን ወይንም አቅምን የሚያሳድጉ አበረታች መድኀኒቶች አሉ፡፡ እነዚህን መድኀኒቶች መውሰድ ፈጽሞ የተከለከለ ሲሆን የተወዳዳሪውን ውጤት ከማሰረዝ ጀምሮ ከስፖርቱ ዓለም እስከ ማሰናበት ሊደርስ የሚችል እርምጃ የሚያስወስዱም ናቸው፡፡
ደምን በፍሪጅ ውስጥ አቆይቶ መውሰድ ስንል ምን ማለታችን ነው?
ደም ኦክስጅን የመሸከም ብቃቱን ከጨመረ ፐርፎርማንስ ይጨምራል ይህንንም በተለያየ መንገድ ማድረግ ይቻላል፡፡ ከነዚህ ውስጥ አንዱ ደምን በፍሪጅ አቆይቶ መውሰድ ነው፡፡ ይህም የሚሆነው ደም ከአትሌቱ ይቀዳና ፈሳሹ ይደፋል፡፡ ከታች የዘቀጠው (ቀይ የደም ሴል) ማለት ነው ፍሪጅ ውስጥ ይገባል፡፡   አትሌቱ ወደ ውድድር ከመግባቱ ከሁለትና ከሦስት ቀናት በፊት በመርፌ ይሰጠዋል፡፡ ይህም ከመድኃኒቱ ጋር ተመሳሳይ የሆነ ውጤት አለው፡፡ የቀይ የደም ሴሎች ቁጥር እንዲጨምሩ ያደርጋቸዋል ማለት ነው፡፡  
አንድን መድሃኒት የተከለከለ ነው የሚያሰኘውና ከአበረታች መድሃኒቶች ተርታ የሚያስመድበው ምንድን ነው?
ጥሩ ጥያቄ ነው፡፡ አንድ መድኀኒት በህግ በተከለከሉ መድኀኒቶች ዝርዝር ውስጥ ለመግባት ሶስት መስፈርቶችን ማሟላት ይኖርበታል፡፡ እነዚህም መድኀኒቱ ለአትሌቱ ጤና ጠንቅ መሆኑ በሳይንስ መረጋገጥ፣ ውጤታማነትን የሚጨምርና የስፖርት መንፈስን የሚቃረን መሆኑ (መርሁ፤ አንድ ሰው በተፈጥሮውና ባለው ነገር ብቻ መወዳደር አለበት የሚል ነው) ናቸው፡፡ መድኀኒቱ እነዚህን ሶስት መስፈርቶች ሲያሟላ ወይንም ሁለቱን አሟልቶ ሲገኝ አበረታች መድኀኒት ነው ልንል እንችላለን፡፡
መድሃኒቱ ለአትሌቶች/ለተጠቃሚው ጤና ጠንቅ ነው የሚባለው እንዴት ነው?
መድኀኒቱ ቀይ የደም ሴሎች ቁጥርን ይጨምራል፡፡ በዚህ ጊዜም ደም ይወፍራል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም መድኀኒቱ ብዙ ላብ እንዲወጣን ያደርጋል፡፡ ላብ ከሰውታችን በሚወጣበት ጊዜ ደግሞ  ደማችን የበለጠ እየወፈረና እየረጋ ይሄዳል፡፡ የወፈረ/የረጋው ደም በቀጫጭኖቹ ደም ማመላለሻ ቱቦዎች ውስጥ እንደ ልብ መመላለስ ያቅተዋል፡፡ ይህ ደግሞ አትሌቱን ለሞት ሊዳርገው ይችላል፡፡ አበረታች መድሃኒቶች በአንድ ወቅት የአለማቀፉ ኦሎምፒክ ኮሚቴ ትልቅ ፈተና ሆነው ነበር፡፡ ኮሚቴው አበረታች መድሃኒቶች እየወሰዱ ለህልፈት የሚዳረጉ አትሌቶችን ሁኔታ መቆጣጠር ሲያቅተው፣ እ.ኤ.አ ከ1990 ዓ.ም ጀምሮ World Anti doping Agency (EADA) የተባለው ድርጅት ተቋቁሞ፣ በአበረታች መድሃኒቶች ቁጥጥር ላይ እየሠራ ይገኛል፡፡
በዚህ ድርጅት ድጋፍ በቅርቡ በምሥራቅ አፍሪካ አትሌቶች ላይ አንድ ጥናት ተካሂዶ ነበር፡፡ እስቲ ስለ ጥናቱና የተገኘው ውጤት ይንገሩኝ?
የምሥራቅ አፍሪካ አገራት በተለይም የኢትዮጵያና የኬኒያ አትሌቶች መፍለቂያ ቦታዎች ከባህር ወለል 2500 ጫማ በላይ መካከለኛ ከፍታ ወይም High Attitude መግቢያ ላይ ናቸው፡፡ እነዚህ ሰዎች እዚህ አካባቢ በመኖራቸው ብቻ ቀይ የደም ሴላቸው መጠን ከፍ ያለ ነው፡፡ እናም አበረታች መድሃኒቶች በእነዚህ አትሌቶች ላይ ያለው ውጤታማነትን የመጨመር አቅም ከሌላ ቦታ (እንደ ስኮትላንድና ዩናይትድ ኪንግደም) ከሚመጡ አትሌቶች ጋር እኩል ሊሆን አይችልም ተብሎ ይታሰብ ነበር፡፡ ይሄ ሃሳብ ትክክል ይሁን አይሁን ለማረጋገጥ ነበር ጥናቱ የተደረገው፡፡ ጥናቱ በመጀመሪያ ሊካሄድ የታሰበው በኢትዮጵያውያን አትሌቶች ላይ ነበር፤ ሆኖም በተለያዩ ምክንያቶች ሳይሳካ ቀረና ከኬኒያ 20 አትሌቶች፣ ከስኮትላንድ እንዲሁ 20 አትሌቶች፤ በድምሩ 40 አትሌቶች የተሳተፉበት ጥናት ተካሄደ፡፡ ጥናቱ አስር ሳምንታት የፈጀ ነው፡፡
የኬንያ አትሌቶች ቀይ የደም ሴል መጠን ከስኮትላንዶቹ በተፈጥሮው ከፍ ያለ ነበር፡፡ መድሃኒቱን ከወሰዱ በኋላ ግን የሁለቱም አገራት አትሌቶች እኩል ሆኑ፡፡ ውጤታማነታቸው (ፐርፎርማንስ) በእኩል ደረጃ አደገ፡፡ ሁለቱም 3ሺህ ሜትሩን ይሮጡበት የነበረው ጊዜ በ6 በመቶ ተሻሻለ፡፡ መድሃኒቱን ካቆሙ ከ4 ሳምንታት በኋላ ምን እንደሚፈጠር ለማወቅ በድጋሚ ለካናቸው፡፡ ውጤቱ እንደሚያሳየው፤ የሁለቱም ውጤታማነት (ፐርፎርማንስ) ከመጀመሪያው በ3 ከመቶ ከፍ ብሏል፡፡ የጥናት ግኝታችንም፤ የኬኒያና የስኮትላንድ አትሌቶች በመድሀኒቱ እኩል ተጠቃሚ መሆናቸውን የሚያረጋግጥ ነው፡፡ ይህም ኢትዮጵያውያንና ኬኒያውያን አትሌቶች ከመድሃኒቶቹ አይጠቀሙም የሚለው ሃሳብ ተቀባይነት እንደሌለው ለመጀመሪያ ጊዜ ያረጋገጠ ነበር፡፡ ይህንኑ ውጤትም ባለፈው ዓመት በአሜሪካ Collage of Sport Medicine ስብሰባ ላይ ያቀረብነው ሲሆን የ”ኢንተርናሽናል ስኮላር” ሽልማት ተሸላሚ አድርጐናል፡፡      
ጥናቱ በኢትዮጵያውያን አትሌቶች ላይ ሊደረግ ከታሰበ በኋላ ወደ ኬንያውያን አትሌቶች እንዲሻገር የተደረገበት ምክንያት ምንድነው?
ብዙ ምክንያቶች ይኖራሉ፡፡ ጥቂቶቹን ለማየት ብንሞክር፣ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ከአበረታች መድሃኒቶች መጠቀም ጋር በተያያዘ ስማቸው አይነሳም፡፡ ነገር ግን በርካታ ኬንያውያን የአበረታች መድሃኒት ተጠቃሚዎች ናቸው፡፡ ከዚህ ሌላ ደግሞ ኬንያውያን አትሌቶች ለጥናትና ምርምሮች በጣም ተባባሪዎች ናቸው፡፡
ጥናቱ እነሱን ሊጠቅም እንደሚችል ካመኑ፣ ምንም ነገር ከማድረግ ወደ ኋላ አይሉም፡፡ ወደ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ስንመጣ፤ ጥናትና ምርምር እንዲደረግባቸው ፈቃደኛ በመሆን በኩል ብዙ ይቀራቸዋል፡፡
ይህ ግን ስህተት ነው፡፡ አትሌቶቻችን ቀደም ሲል የነበራቸውን የስኬት ደረጃ አስጠብቆ ለማቆየት ከተፈለገ፣ በጥናት የታገዘ ስልጠና ሊሰጣቸው ይገባል፡፡ ለዚህ ደግሞ የአትሌቶቹ ተባባሪነት ወሳኝነት አለው፡፡

Published in ዋናው ጤና
Saturday, 22 November 2014 12:12

ፊታውራሪ እርጅና

ባለ ጋሻ ጀግሬው ሰልፍ የሚያምርለት፣
አጀቡ አስፈሪ ጦር የበዛለት፣
ሠራዊተ ብዙ ፊታውራሪ እርጅና፣
ረጋ ብሎ ይመጣል ሞት ያስከትልና፡፡
    ስሜት ሲደበዝዝ፣
አካል ሲቀዘቅዝ፣
ዕይታ ሲደክም፣
አእምሮ ሲያዘግም፣
አደብ ይገዛሉ ህዋሳት በመላ፣
ሰውነት ይበርዳል ላይሞቅም ላይፈላ፡፡
ሆድ ጠግቦ ላይበላ ጉረሮ እህል ላይውጥ፣
ጉልበት ላይሆንለት ጦርን ሮጣ ማምለጥ፣
ነገርን አስታውሶ ለመናገር ፈጥኖ፣
እንደ ቀድሞ አይሆንም ጠፍቷልና ተንኖ፡፡
ዕቅድና ዓላማ እርግፍ አርጐ ትቶ፣
በትዝታ መኖር ምሃት፣ ተስፋ ጠፍቶ፡፡
እንስት ተባዕትን፣ ተባዕት እንስትን፣
ላይፈቃቀዱ ያሰንፋል ስሜትን፡፡
ጣፋጩ መራር ነው የሞቀው ቀዝቃዛ፣
በስተርጅና ሁሉም ይሆናል ጐምዛዛ፡፡
        ተው እርጅና፣
        ብቻህን ና!
ይህ ሁሉ ሳያንስህ ስኳሩን፣ ግፊቱን፣
ሪሁን፣ ራስ ምታቱን፣ ውጋት፣ ቁርጥማቱን፣
ነጭናጫ መሆኑን መነዝነዝ ዕለቱን፣
በትንሽ ትልቁ ፈጥኖ መከፋቱን፣
አንጋግተህ ያመጣህ ጨካኝ ነህ እርጅና፣
በስንት ጣዕሙ ሞት ይገባው ምስጋና፡፡
ኧረ ተው እርጀና አንተ ጅራታም፣
ምነው ጓዝህ በዛ (ሆንክና/ሆንክብኝ?) ኮተታም!
    ተው እርጅና፣
    ብቻህን ና!
ጥሩ ስም የሰጠህ ንገረን ማነው?
እርጅና እያሉ የጠሩህ ምነው?
እስቲ ከሞት ጋራ ተነጋገሩና፣
ከነ ተከታይህ በአንድ ላይ ሁኑና፣
እናንት? ሁለታችሁ ስብሰባ ግቡና፣
ስምህን ለውጡ ተመካከሩና፡፡
ሌላ ስም ይውጣልህ ከሞት ያላነሰ፣
ሥራህ ቢበዛ እንጂ መች ከእሱ ቀነሰ?
እናም…. ይኸው ወቀስኩህ ላትሰማኝ ነገር፣
 (ከእለታት ቀን ቆጥረህ መከሰትህ ሳይቀር?)
በሥራ በስፖርቱ አካሌን አጥብቄ፣
እጠብቅሃለሁ (አልቀርም) ወድቄ፡፡
ጦሬን ይዤ መጣሁ ደረስሁ ብትለኝም፣
እኔ አለሁ፣ አንተም ና ሥጋት አይገባኝም፡፡
በል እንግዲህ እርጅና - በቸር ያገናኘን
እስከዚያው ድረስ፣
አንተም አርጅተህ ሙት
- ወደ ልጅነቴ እኔም ልመለስ፡፡
*    *    *
ከአምሳሉ ጌታሁን ደርሰህ
ኅዳር 2007 ዓ.ም

Published in ጥበብ

አሀዱ ኣባይነህ የኪነ-ህንፃ ባለሙያ ነው፡፡ በሙያው ለአስራ ስምንት አመታት ሲሰራ ቆይቷል፡፡ በ90ዎቹ ዓመታት በዝቅተኛ ወጪ የዛፍ ላይ መኖሪያ ቤት ሰርቶ ነበር፡፡ በቅርቡ ደግሞ በአዲስ አበባ ከፈራረሱ ቤቶች ላይ ከተሰበሰቡ የተለያዩ ቁሳቁሶች እየሱስ በመባል በሚታወቀው አካባቢ እጅግ ውብ የሆነ ቤት ሰርቷል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ኤልሳቤት እቁባይ የኪነ-ህንፃ ባለሙያውን በሰራው ቤትና በአጠቃላይ በሙያው ዙሪያ አነጋግራዋለች፡፡


ከቤቶች ፍርስራሽ አዲስ ቤት የመገንባት ሃሳብ እንዴት መጣ?
ቤቱን የሰራሁለት ሰው ዶክተር ኤርሚያስ ሙሉጌታ ይባላል፡፡ ጥንታዊ ቁሶችን በጣም ይወዳል፡፡ እናም በከተማዋ ከሚፈርሱ ቤቶች ላይ መስኮቶች፣ በሮች፣ ሸክላዎች፣ የወለል ጣውላዎችና የደረጃ ድንጋዮችን ከገዛ በኋላ፣ በእነዚህ ቁሳቁሶች ቤት እፈልጋለሁ አለኝ፡፡
የሥራው ሂደት ምን ይመስላል?
የመጀመሪያው ስራ ቁሳቁሶችን መለየት ነበር፡፡ በብዛት ትላልቅ ቢሞች፣ በሮችና መስኮቶች ነበሩ፡፡ መስኮቶቹና በሮቹ ከተለያዩ ቦታዎች የተሰበሰቡ ናቸው፡፡ በመጀመሪያ እነሱን ወደ ንድፍ፣ ከዚያ ወደ ዲዛይን ለወጥኳቸው፡፡ የተሰበሰቡት በሮችና መስኮቶች ዲዛይኑ ላይ መለያ ተሰጥቷቸው ተቀመጡ፡፡ ቤቱን ዲዛይን አድርጌ ስጨርስ ደግሞ መስኮቶቹና በሮቹ በተሰጣቸው ስያሜ መሰረት እንዲገጠሙ ተደረጉ፡፡
የቁሳቁሶቹ አሰባሰብ እንዴት ነበር?
በየቦታው ቤት የሚያፈርሱ ሰዎች የዶክተር አድራሻ አላቸው፡፡ ቤት ሊያፈርሱ ሲሉ ደውለው እዚህ ቦታ ቤት ልናፈርስ ስለሆነ ናና የምትፈልገው ነገር ካለ ተመልከት ይሉታል፡፡ በነገራችን ላይ ይሄን ቤት ከሰራሁ በኋላ፣ በተመሳሳይ መልኩ ከፍራሽ ቤቶች በተሰበሰቡ ቁሳቁሶች ሌሎች ቤቶችንም ሰርቻለሁ፡፡
ከወጪ አንፃር እንዴት ነው?
ወጪው ጥሩ ነው፡፡ አዲስ ቁሳቁሶች ከመግዛት ይረክሳል፡፡ አንዳንዶቹ በሮች የተገዙት ስምንት መቶና ዘጠኝ መቶ ብር ነው፡፡ አዲሱ ይገዛ ቢባል ወደ 20 ሺ ብር የሚጠጋ ወጪ ይጠይቃል፡፡ ነገር ግን መስኮቶቹና በሮቹ ከተለያዩ ቤቶች ፍራሽ ላይ የተወሰዱ በመሆናቸው ቀለማቸው የተዘበራረቀ ነበር፡፡ ማፅዳቱና ወጥ የሆነ መልክ እንዲይዙ ማድረጉ ጊዜ ወስዷል፤ የተወሰነ ወጪም ጠይቋል፡፡ በሮቹና መስኮቶቹን ለማፅዳት በኦክሲጅን ቀለማቸው ተልጦ እንዲሸበሸብ ከተደረገ በኋላ፣ በብርጭቆ ወረቀት ታሽተው ቫርኒሽ ተቀብተው ነው ተመሳሳይ መልክ የያዙት፡፡ ሸክላዎቹም ሲመጡ ከሲሚንቶ ላይ ስለወጡ ነጭ ነበሩ፤ በብርጭቆ ወረቀት ታሽተውና ተቀብተው ነው ጥቅም ላይ የዋሉት፡፡ የተለያዩ አይነት ድንጋዮችንም ተጠቅመናል፡፡ ከአምቦና ከትግራይም አስመጥተናል፡፡
ከተለያዩ ቦታዎች የመጡ ቁሳቁሶች እንዴት ሊጣጣሙ ቻሉ?
 እዚህ ቤት ላይ ሸክላና ድንጋይ እንዲሁም ሸክላና እንጨት ተቀላቅለው ተሰርተዋል፡፡ መጣጣሙ የመጣው ሁሉም የተፈጥሮ ስለሆኑ ነው፡፡ እዚህ ቤት ላይ አልሙኒየም ብንከት አንድነቱ አይጠበቅም፡፡ እንጨትና ድንጋይ አብሮ ይሄዳል፡፡ ተፈጥሮም እንደዚያ ነው የቀላቀለቻቸው፡፡ ዛፍ አፈር ላይ ነው የሚበቅለው፤ ስለዚህ ሸክላና እንጨት ላይጣጣሙ አይችሉም፡፡ ውበት ግኡዝ ነገር አይደለም፡፡ የሃሳቦች ውሁድ ነው፡፡ አንድ የሚያምር የፅጌረዳ አበባ ሳይ ያማረበት ምክንያት ምንድን ነው ብዬ፣ የቀለም ውህደቱንና አወቃቀሩን እማርበታለሁ፡፡ ዛፍ ስናይም በጣም ያምረናል፡፡ ለምን ያምረናል ስንል ምናልባት ከተፈጠርን ጊዜ ጀምሮ ስናየው ስለኖርን ይሆናል፡፡ ዛፍ ውስጥ ግን የምንማራቸው የተፈጥሮ ህግጋት አሉ፡፡ የዛፍ ቅርንጫፍ የት ጋ እንደሚወጣ አናውቅም፤ ግርምት ነው፤ ስለዚህ ከዛፍ የግንድ አበቃቀል አግራሞት የሚፈጥሩ ክስተቶች ተምሬያለሁ፡፡ እዚህ ቤት ውስጥ ልክ እንደ ዛፍ ግንድ ግርምት የሚፈጥሩ ሊያደርጉ የሚችሉ ነገሮችን አስገብቻለሁ፡፡
ኪነ-ህንፃ ሳይንስ ነው አርት በሚል ስለሚደረገው ሙግት ምን ትላለህ?
ይሄ ፀሀይ ብርሀን ነው ሙቀት ብሎ እንደ መሟገት ነው፡፡ በጣም የተያያዙና የማይለያዩ ናቸው፡፡ ስለ አርት ስናወራ፣ አርቱ ያለ ሳይንሱ አይሆንም፡፡ ሳይንሱን ካየን ለአንድ ህንፃ ንፅህና አጠባበቅ የፍሳሽ ማስወገጃው በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ ውሀ ሪሳይክል ማድረግ ወይም ማጠራቀም በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ ብርሀን በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ እዚህ ቤት በማታ መብራቶቹ በርተው ብትመጪ አሁን ከምታይው ጋር በምንም አይገናኝም፣ በጣም የተለየ ነው፡፡ እኛ ሳይንስ የምንለው በአብዛኛው ከቴክኖሎጂ አንፃር ነው፡፡ ብርሀንን በቀለም  እንረዳዋለን፡፡ ይህ ቤት የጠዋት ብርሀን ሲያርፍበትና የማታ ብርሀን ሲያርፍበት ለቤቱ የሚሰጠውና የሚፈጥረው ቀለም በጣም የተለያየ ነው፡፡
አርቱን ካየን ደግሞ አሁን ለምሳሌ እዚህ ቤት ብዙ ቁሳቁሶችን ተጠቅመናል፡፡ እነዚህ ቁሳቁሶች ኮተት እንዳይመስሉ ግን ብዙ ለፍተናል፡፡ በይዘት፣ በመጠን፣ በቀለም ወዘተ… እንዲጣጣሙ በማድረግ ውበቱ እንዲጠበቅ እናደጋለን ይሄ ጥበብ ነው፡፡ እርስ በእርስ ሊስማሙ በሚችሉ ቁሳቁሶች መስራት ለአይን ሻካራ የሆኑ ነገሮች እንዳይኖሩ ያግዛል፡፡ መስኮት የቤት አይን ነው፤ ስለዚህ ነው እያንዳንዱ የዚህ ቤት መስኮት ሲከፈት አይን ጥሩ እይታ ያለው ነገር ላይ እንዲያርፍ የተደረገው፡፡
ከተለመደው የቤት አሰራር ሂደት በተለየ መንገድ ነው ቤቱን የሰራኸው፡፡ ምን ዓይነት ስሜት ፈጠረብህ?
እንደዚህ ቤት ነፃ ሆኜ የሰራሁት ስራ የለም፡፡ ከባለቤቱ ጋር እየተወያየንና እየተስማማን ነው የሰራነው፡፡ በጣም ነፃነት ስለነበረኝ እጅግ ደስ እያለኝ ነው የሰራሁት፡፡ ህንፃ ልክ እንደ ልጅ ነው፡፡ የኪነ-ህንፃ ባለሙያውና የሚያሰራው ሰው እንደ አባትና ልጅ ናቸው፡፡ ሁለቱ የማይስማሙ ከሆነ ልጁ ጥሩ አይሆንም፡፡ ተስማምተው በደንብ መስራት ከቻሉ ውጤቱ ጥሩ ይሆናል፡፡ ባለሙያው ቤቱን አምጦ የሚወልድ ቢሆንም ባለቤትም ቤቱ ምን ያህል ስፋት ይኖረዋል፣ በጀቱ ምን ያህል ነው  ወዘተ… የሚለውን ይወስናል፡፡ ጥሩ ስራ ስትሰሪ መተማመኑ ይመጣል፡፡ ከዚያ ደግሞ ነፃነት ይገኛል፡፡ ይህን ቤት ስሰራ አስቤ ያላደረግሁት፣ ነገር ግን ሌላ ስራ ላይ አደርገዋለሁ ብዬ ያሰብኩት ነገር አለ፡፡ ይኸውም ከዩኒቨርስቲዎች ጋር ተነጋግሬ፣  የኪነ ህንፃ ተማሪዎች ሳይት ላይ መጥተው ከቁፋሮ ጀምሮ ባሉ ስራዎች ላይ እንዲሳተፉ ማድረግ ነው፡፡
ለምንድነው ተማሪዎቹን ማሳተፍ የፈለግኸው?
ለምሳሌ የዚህ ቤት ስራ አራት አመት ነው የፈጀው፡፡ ከቁፋሮ ጀምሮ በዚህ ቤት ስራ ላይ የተሳተፈ ተማሪ፣ ትምህርቱን ጨርሶ ሲወጣ ነገሮችን የሚያይበት አይን የተለየ ይሆናል፡፡ አንድ የተሞላ ኮንክሪት ድሮዊንግ ላይ በቃ አንድ መስመር ነው፡፡ እዚያ አንድ መስመር ላይ ግን ብዙ ነገሮች አሉ፡፡ ብረት፣ ኮንክሪት፣ ኮንዲዩት፣ ፎርም ወርክ፣ የመብራት ኬብል፣ የመብራት መስመር፣ አሸዋ፣ሲሚንቶ፡ ጠጠር እንዲሁም ከዚያ በላይ ደግሞ ወዛደሩና ወዛደሯ አሉ፡፡ ከእነሱ መሀል ምሳ የበላ አለ፤ ያልበላ አለ፣ ከቤት ሰራተኝነት ወጥታ ይሄ ይሻላል ያለች አለች፣ ወደ ቀድሞ ብመለስ ይሻላል በሚል እያመነታች ያለች ትኖራለች፤ሁለቱም ያልተመቻት ደግሞ አለች፡፡ አንድ ተማሪ ይህንን ሁሉ አውቆ ከት/ቤት ሲወጣ ብዙ ነገሮችን ይዞ ይወጣል፡፡
ግቢው እጅግ ባማሩ አበቦችም የተሞላ ነው፡፡ ብዙ ጥረት እንደተደረገበት ያስታውቃል…
አዎ፤ በግቢው ውስጥ 300 የአበባ ዝርያዎች አሉ፡፡ ወደፊት የዕፅዋት አጥኚ (ቦታኒስት) መጥቶ ስለ ዝርያቸው የሚገልፅ ነገር እንዲሰራ ዶክተር እቅድ ይዟል፡፡

Published in ህብረተሰብ

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
አጐንብሶ መሄድ አላውቅ ብዬ እንደ ሰው
እቀና ብዬ ነው ቤቴ የፈረሰው፤
የሚሏት “ተረትና ምሳሌ” ነገር አለች፡፡ አሁን አሁን እንደምንም ብለው ቀና ያሉ ሰዎች ቤታቸው መፍረሱን ወይም እየፈረሰ መሆኑን እንሰማለን፡፡ ምን አይነት ጊዜ እንደሆነ አንድዬ ይወቀው እንጂ…የአንዱ ስኬት የሌላውን ዓይን የሚያቀላበት ዘመን ውስጥ ነን፡፡ መቼም “ቶክ ኦፍ ዘ ታውን” በሽ ነው፡፡ ታዲያላችሁ…መቼም መአቱ ያው “ፊክሽን” ምናምን ነገር ነው፡፡ ችግሩ ምን መሰላችሁ “ፊክሽኑ” ሁሉ አሪፍ በሆነ መንገድ ስለሚቀርብ እውነቱንና “ቁጩውን” መለየት አቅቶናል፡፡ (“ቁጩ” የሚለው ቃል አሁንም “ሰርኩሌሽን” ውስጥ ነው እንዴ!) ደህናውን ጊዜ ያምጣልንማ!
ስሙኝማ…ይቺን ነገር ከዚህ በፊት ሳናወራት አልቀረንም፡፡ እሱዬው እሷዬዋን…”ዛሬ ተገናኝተን እንጫወት…” ይላታል፡፡ እሷዬዋም…”ዛሬ አልችልም…” ትለዋለች፡፡ “እሺ እንግዲያው ነገስ?” ይላታል፡፡ እሷም “ነገም አልችልም” ትላለች፡፡ “እሺ የዛሬ ሳምንትስ?” ሲላት ምን ብትለው ጥሩ ነው… “የዛሬ ሳምንት ራሴን ያመኛል፡፡” አሪፍ አይደል!
እናማ…በተዘዋዋሪ መንገድ…አለ አይደል…”የዛሬ ሳምንት ራሴን ያመኛል…” ስንል የሚሰማን እያጣን ተቸግረናል፡፡
“ስማ፣ ስፈልግህ ነው ያገኘሁህ፡፡”
“ለምን ፈለከኝ?”
“አንድ ጉዳይ አለ፣ ሻይ እየጠጣን እናወራለን፡፡”
“ለምን አሁን አናወራም!”
“ሌላ ጊዜ ተደዋውለን እንገናኝና የምነግርህ ነገር አለ፡፡”
“ጠርጥር፣ ገንፎ ውስጥ አለ ስንጥር” ማለት ይሄኔ ነው፡፡ “ሰሞኑን እንኳን አይመቸኝም፡፡ ጊዜ ሲኖረኝ እኔ ራሴ እደውልልሀለሁ…” ትላላችሁ፡፡ በቃ እንዲህ ማለት እኮ…”የዛሬ ሳምንት ራሴን ያመኛል…” ማለት ነው፡፡ ብዙ ጊዜ ሰዎች አንድን ነገር ወዲያውኑ የሚነግሯችሁ ካልሆነ…በቃ የሆነ ነገር አለው ማለት ነው፡፡ በሚቀጥለው ጊዜ በድንገትም ቢሆን ስትገናኙ… “ስማ አንድ የሆነ ቢዝነስ ስላለ እንድንገባበት ፈልጌ ነው፡፡ ብታዋጣ አንድ ሰማንያ መቶ ሺህ ብር ብቻ ነው፡፡” (“ሰማንያና መቶ ሺህ ብር” እንዲህ “ዋዛ፣ ፈዛዛ” ሆና ቀረች!) ከዚህ በኋላ የእሱ ስልክ ሲሆን ወይ “ኔትወርክ አይሠራም…” ወይ “አፓራተሱ ብልሽት አለበት…”፡፡ ልክ ነዋ…ሄዶ የየመን ቱሪስት ያታል! መቼም “ቱሪስት” አያጡም ብዬ ነው፡፡
እናማ…በተዘዋዋሪ መንገድ…አለ አይደል…”የዛሬ ሳምንት ራሴን ያመኛል…” ስንል ልብ ይባልልንማ!
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ምን ግርም ይልሀል አትሉኝም… “የምንመለመልበት” ሰበቦች ብዛት! ትንፋሽ ስጡና!
ግራ ክንፍ ይሁን፣ ቀኝ ክንፍ ይሁን፣ እንደውም “ክንፍ” እንኳን ይኑረው የማታውቁት “ቦተሊከኛ” ይመጣና… “እውነት፣ እውነት እልሀለሁ ስርየት የምታገኘው የእኛ ቡድን አባል ስትሆን ነው…” አይነት ነገር ይላችኋል፡፡
የኃይማኖቱ ሰው፣ ወይም “የኃይማኖት ሰው ነኝ” የሚለው ደግሞ ይመጣና (ዘንድሮ ማን ከእንትኑ ስር “ጭራ እንዳለው” መለየት አቅቶን ተቸግረናል፣ ቂ…ቂ…ቂ…) ይመጣና… “በእኛ በኩል ካላለፍክ እንኳን መንግሥተ ሰማያት ልትገባ፣ በርቀትም አታየው…” አይነት ነገር ይላችኋል፡፡ (መንገድ ላይ ማለፊያ የምታሳጡን ሰዎች ተውንማ!)
እነሱ የመንግሥተ ሰማያትን ቁልፍ እስከ መሸጥና እስከ መለወጥ ድረስ የሚያስችል “ውል” አላቸው እንዴ! (አሀ… “ወዮልሽ! ሁልሽም ገሀነም ትወረውሪያታለሽ!” ምናምን ብሎ ነገር ምንድነው!)
“የዓለም ዘጠኝ” ሰው ነኝ” የሚለው ይመጣና… “ማታ፣ ማታ ከተማው እንዴት ነፍስ እንደሚያድስ አልነግርህም፣ ለምን ጆይን አታደርገንም! ጌታው ጊዜ ›ለህ ቸስ በልበት…” ይላችኋል፡፡
ደግሞላችሁ…“ጆብ ዲስክሪፕሺኑ” በደንብ ያልለየው ይመጣና… “ስማ እንዴት አይነት ቺኮች እንደማገናኝህ እኔ ነኝ የማውቀው፡፡ እመነኝ፣ ዕድሜህ በእጥፍ ነው የሚጨምረው…ይላችኋል፡፡ እናላችሁ …“መልማዮች”ና የመመልመያ ምክንያቶች በዙብንማ፡፡
ታዲያላችሁ…እነኚህ ምክንያቱን በግልጽ የማይነግሯችሁ ግን በ “ቅቤ ምላስ” የዓለም ባንክን ካዝና ፊታችሁ የሚዘረግፉላችሁ “መልማዮች” አሉላችሁ፡፡ “ስማ፣ አንድ የሆነ ሥራ አለ፣ በቃ የዕድሜ ልክህን ፈራንክ የምትዘጋበት ነው፡፡ እኔ ከሰዎቹ ጋር አገናኝሀለሁ…” ምናምን ይላችኋል፡፡
ይሄ ሁሉ ጊዜ ታዲያ …በተዘዋዋሪ መንገድም ቢሆን…አለ አይደል… “የዛሬ ሳምንት ራሴን ያመኛል…” ስንል የሚሰማን አጥተናል፡፡
እኔ የምለው…የሆነ ነገር ትዝ አለኝማ…ደረታችሁ ላይ “ጠጉር” ያላችሁ ሰዎች “ለትራስነት” ታከራያላችሁ እንዴ! አሀ…ግራ ገባና! በቀደም አንድ ሚኒባስ ውስጥ ሁለቱ እንትናዬዎች በእነሱ ቤት መንሾካሾካቸው ነው…ሲያወሩ አንደኛዋ ምን ትላለች… “የሚገርመኝ ደረቱ ሁሉ ፀጉር ነው…” ትላለች፡፡ ሌላኛዋ ደግሞ “እሱ ላይ ለጥ አልሻ!” አለቻትና አረፈችው፡፡ በደረት “ጠጉር”ም “ዲስክሪሚኔሽን” ምናምን ሊመጣብን ነው እንዴ! …ሌጣ ደረቶች ሆይ፣ “ያመለጣችሁን” እዩማ፡፡ እኔ የምለው…ቅንድቡ፣ ጢሙ ምኑ፣ ምናምኑ “አርቲፊሻል” ምናምን ሲሠራለት…ምነዋ አርቲፊሻል የደረት ፀጉር አልተሠራ! የደረት “ጠጉር” የምንመኘው ሁሉ ደረታችንን የአማዞን ጫካ አስመስለን “ኤክስሬይ ለማንሳት ስለሚያስቸግር ባርቤሪ ሄደህ ተከርክመህ ና…” ልንባል እንችላለን፡፡
ስሙኝማ…ችግሩ ምን መሰላችሁ…ለደረት የተመኘነው ፀጉር የት ቢበቅል ጥሩ ነው…አዕምሯችን ውስጥ! ቂ…ቂ…ቂ የሚኮሰኩሱ ነገሮች መናገር የምናበዛ ሰዎች ምክንያቱ የቃላት መረጣ ሳይሆን “የአእምሮ ጠጉር” ሊሆን ይችላል!
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…እነኚህ የዓለም “የሰማይ ስባሪ” የሚሏቸው መሪዎች እንደ “ህጣን” ያደርጋቸዋል እንዴ! አሀ…በቀደም አውስትራሊያ ውስጥ ፑቲን ላይ ያሳዩት የነበረው ነገር ሁሉ…አለ አይደል…የእንትን ሰፈር ልጆች ሊያናድዱት የፈለጉትን ሰው… “ጭራ እናስበቅለው፣” የሚሉት አይነት “አድማ” ይመስላል፡፡ ነገሩ ደስ አይልም፡፡
እናላችሁ…ሁሉም አይነት “መልማዮች” ሆይ… “የዛሬ ሳምንት ራሴን ያመኛል…” ስንል አድምጡንማ! ልጄ… “ሲመች የአማት ተዝካርም ይወጣል፣ ሳይመች የአባትም ይቀራል፣” ስንልስ! (ወይም ከዘመኑ ጋር ለመዘመን ..አርሴም፣ ማንቼም አንሆንም ስንልስ! “እናንተ የማታውቁት፣ እኔ የማውቀው የመንግሥተ ሰማያት መንገድ አለ…” ስንልስ!ደግሞላችሁ…ከጥቂት ጊዜያት በፊት አንድ ወዳጄ ያለኝን ስሙኝማ! አንድ በቅርብ የሚያውቀው ሰው ምን ይለዋል… “ስማ ከሆኑ ፈረንጆች ጋር የሚሠራ ሥራ አለ፡፡ እኔ አንድ የምተማመነው ጓደኛዬ አለ ብያቸዋለሁ…”፡፡ ሥራው ምን እንደሆነ ይጠይቀዋል፡፡ ሰውየውም “እሱን ወደፊት እነግርሀለሁ፣ ግን ከፍተኛ ምስጢር ነው፣” ይለዋል፡፡ ይሄ ወዳጄ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ የጓደኛውን ስልክ ማንሳት ትቷል፡፡ “የዛሬ ሳምንት ራሴን ያመኛል…” እያለው ነው፡፡ እኔ የምለው…የ “ፈረንጅ” ነገር ከተነሳ…ሀሳብ አለን፡፡ ለምንድነው የአውሮፓ ህብረት አባል ያልሆነው? ልክ ነዋ! ምድረ የአውሮፓ ከተማ ሁሉ እዚህቹ ሸገራችን ውስጥ የሬስቶራንትና የቡቲክ ሁሉ መጠሪያ ሆኖ የለም እንዴ! እኔ እንደውም፣ አይደለም ሌሎች የአፍሪካ አገሮች፣ የአውሮፓ ሀገሮች እንኳን የእኛን ያህል የጐረቤቶቻቸውን ከተሞች ስም የሚጠቀሙ አይመስለኝም፡፡
 አባል ባያደርጉን እንኳን የታዛቢነት ወንበር ይሰጠን፡፡ “የዛሬ ሳምንት ራሴን ያመኛል…” እንደማንላቸው ፈርሙ ካሉንም ግጥም አድርገን እንፈርማለን፡፡
ደህና ሰንብቱልንማ!  


Published in ባህል
Saturday, 22 November 2014 12:06

ልማት “እንበለ” ባህል…!

“ከመወለዳችን በፊትም ሆነ ከሞትን በኋላ የምናካሂዳቸው ነገሮች እንዲሁም የየእለት ተእለት እንቅስቃሴያችን ከንጋት እስከ ንጋት በሙሉ ባህላዊ ናቸው፡፡” ይሉናል እውቁ የፎክሎር (ባህል) ጥናት መምህርና ተመራማሪ ፈቃደ አዘዘ (ዶ/ር)፡፡ እውነቱ ይህ ከሆነ የሰው ልጅ በራሱ ባህልም ነው ብሎ መፈረጁ የሚገድ አይመስልም፡፡ ስለ ምን ቢሉ… ኑሮውም ሆነ አኗኗሩ በብዙም ቢሉ በጥቂቱ፣ ከረቂቅ እስከ ግዙፍ ባህል ነውና፡፡
የጽሑፌ ማጠንጠኛ ባህልና ልማት ያላቸው ትስስር ነው፡፡ በዚህም ባህልና እሴቶቹ ለልማት ያላቸውን ፋይዳ፤ እንዲሁም ለባህል ትኩረት ያልሰጠ ልማት (ልማት ያለ/እንበለ ባህል) ምን እንደሆነ በወፍ በረር ለማስቃኘት እሞክራለሁ፡፡ ማስረገጫዬም ልማት እንበለ ባህል፤ ጭንጫ መሬት ላይ ዘር ዘርቶ ምርትን እንደ መጠበቅ አጉል ተስፋ መሆኑን ማተት ነው፡፡  
የባህል ጥናት የአንድን ማህበረሰብ ሁለንተናዊ ማንነት ለማወቅ ቁልፍ መሳሪያ ነው፡፡ የአንድን ማህበረሰብ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ደረጃ በአስተማማኝ እና ዘላቂ በሆነ መልኩ ማሳደግ ከተፈለገ ቀድሞ የማህበረሰቡን ባህል ማጥናትና እሴቶቹንም መነሻ ማድረግ እንደሚገባ የፎክሎር/ባህል ጥናት ባለሙያዎች ይገልጻሉ፡፡ ማንኛውም ማህበረሰብ የእኔ የሚላቸው መንፈሳዊ እና ቁሳዊ እሴቶች አሉት፡፡ እነዚህ እሴቶች የማንነቱ መገለጫና የህልውናው ማዝለቂያ ናቸው፡፡ ለዚህም ነው ባህላዊ እሴቶቹን ማጥናት እና መረዳት ማህበረሰቡን ማወቅ ነው የሚባለው፡፡ ይህ አስተሳሰብ አሁን አሁን በበርካታ የጥናት መስኮች ከፍተኛ ተቀባይነትን እያገኘ መጥቶአል፡፡
ባህልና ልማት ያላቸውን ቁርኝት/ትስስር ከማውሳቴ በፊት የነገሩን ጭራ ለመያዝ ያግዘን ዘንድ ሁለቱን ፅንሰ ሀሳቦች (ባህልን እና ልማትን) የመስኩን ተመራማሪዎች ጥናቶች እማኝ አድርጌ ለመፍታት ልሞክር፡፡ ባህልን ላስቀድም፡፡ ራስወርቅ አድማሴ የተባሉ የዘርፉ ተመራማሪ “ባህልና ልማት፦ ምንነታቸውና ትስስራቸው” (2004) በተባለው ጥናታቸው ላይ ባህልን እንዲህ ይበይኑታል፡-
“ባህል አንድን ህብረተሰባዊ የወጎችን ስርዓትን (a system of social norms) እንደሚያመለክት፤ ይህም ህብረተሰባዊ የወጎች ስርዓት ሲወርድ ሲዋረዱ የመጡ ወጎችን፣ ልምዶችንና፣ እርሞችን፣ ልማዳዊ-ሕጎችን፣ ድንጋጌዎችንና ከነዚህ ጋር የተዛመዱ እምነቶችን፣ አመለካከቶችንና፣ ጠባዮችን ያቅፋል፡፡”
የባህል ባለቤት ህብረተሰብ፣ ዝቅ ሲልም ማህበረሰብ እንደሆነ የሚገልጹት ተመራማሪው፤ ሰዎች ባህልን በመማር እንጂ በደም እንደማይወርሱት፣ አንድ ህብረተሰብ አባላቱ በሙሉ የሚጋሩት አንድ ነጠላ ባህል ብቻ ወይም ብዙ ባህሎችን ሊያስተናግድ እንደሚችል፤ እንዲሁም ባህል በሂደት እንደሚለወጥና ፍጹም እንደነበረ ሆኖ እንደማይቀጥል/እንደማይኖር ይገልጻሉ፡፡
ይህ አስተሳሰብ በበርካታ የመስኩ ምሁራን ዘንድ ቅቡል ቢሆንም የባህልን ሂደት አስመልክቶ ግን የመስኩን ምሁራን ያቧደኑ ሁለት ርዕዮቶች አሉ፡፡ እነሱም “ባህልን አንዴና ለመጨረሻ ጊዜ እንደተፈጠረ ግግር የሚቆጥረው ስታቲክ (static) ርዕዮት” እና የዚህ ተቃራኒ የሆነው ባህልን እንደ “ተለዋዋጭ ወይም ታዳጊ (dynamic) ፍሰት” የሚመለከተው ርዕዮት ናቸው፡፡
የባህልን ምንነት እንዲህ በግርድፉ ከጨበጥን እሱን እያሰላሰልን ወደ ልማት እንለፍ፡፡ (አሁንም ዋቢዬ የራስወርቅ አድማሴ ጥናት ነው፡፡) ልማት የሚባለው “አንድ አይነት ህብረተሰባዊ ለውጥ ሲሆን፣ ማንኛውንም ህብረተሰባዊ ለውጥ ግን ልማት ነው ማለት አይደለም፡፡ ልማት አዎንታዊ፣ በጎ ወይም ጠቃሚ ህብረተሰባዊ ለውጥ ማለት ነው፡፡” መልካም፡፡ ወደ ቀደመ ነገሬ ልመለስ፡፡ ባህልና ልማት ምንና ምን ናቸው?
ባህል የአኗኗር ዘዴን፣ ስልትን፣ ሥርዓትን፣ ደንብን፣ ኑሮን ራሱን ከመግለጫ ጥበቡ ጋር ጠቅሎ ይይዛል፡፡ ልማትም የሰው ልጆችን ህይወት አዎንታዊ በሆነ መንገድ ለመለወጥ የሚደረግ እንቅስቃሴ ውጤት በመሆኑ ቁሳዊና መንፈሳዊ ባህልን መሰብሰብ፣ ማጥናትና መተንተን ለልማት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለው፡፡
ባህል በልማት ላይ የሚያሳድረውን ተፅዕኖና ለፖሊሲም ያለውን ተፈላጊነት በተመለከተ አሁንም ድረስ በመስኩ ምሁራን መካከል ልዩነቶች ቢኖሩም አብዛኞቹ የስነ ማህበረሰብ  ተመራማሪዎች በአንድ ነጥብ ይስማማሉ፡፡ ይኸውም በባህልና በልማት መካከል መደጋገፍ እንዳለና፤ በአንድ ማህበረሰብ ውስጥ የሚካሄድ “የልማት እንቅስቃሴም” የማህበረሰቡን ባህላዊ እሴቶችን እና ከእነዚህ የሚመነጨውን አስተሳሰቡን ማዕከል ማድረግ እንደሚገባው፡፡
በርዕሰ ጉዳዩ ላይ በመስኩ ምሁራን የተደረጉ ጥናቶችም ባህላዊ ጉዳዮች ለልማት ያላቸው ፋይዳ እጅጉን ወሳኝ መሆኑን የሚያስረግጡ ናቸው፡፡ አስተማማኝ ልማት እንዲኖር ከተፈለገም የህብረተሰቡን ባህልና ፍላጎት ግምት ውስጥ ማስገባት እንደሚገባና እቅዶችና ፖሊሲዎችም ለማህበረሰቡ ባህል ትኩረት መስጠትና እሱ ላይ መመስረት እንዳለባቸው ጥናቶቹ ይገልጻሉ፡፡ የዚህም ምክንያቱ ባህልና የባህሉ ባለቤት የሆነው ማህበረሰብ ያላቸው ቁርኝት የሥጋና አጥንትን ያህል የጠበቀ በመሆኑና የማህበረሰቡም አስተሳሰብና ፍላጎት ከባህሉ ውጪ ስለማይሆን ነው፡፡
ማህበረሰብና ባህል ሕይወት ያላቸው/የሚኖሩ፣ ያለ ማቋረጥ የሚታደሱና ራሳቸውንም እንደወቅቱ ተጨባጭ ሁኔታ የሚለዋውጡ ናቸው፡፡ ባህል እየተለወጠና እሴቶቹ እየተለወጡ በሄዱ ቁጥርም የሰዎች አስተሳሰብ ይለወጣል፡፡ አንድ ነገር ልብ እንበል፡፡ ባህልና እሴቶቹ ሲለወጡ የባህሉ ባለቤት የሆነው ማህበረሰብ አስተሳሰብም ይለወጣል፡፡
ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ አለም አቀፋዊ ፖሊሲ ቀራጮችና “እቅድ አርቃቂዎች” ህብረተሰባዊ ወጎች (Social norms) እና ሌሎች ባህላዊ እሴቶች በሰዎች አመለካከትና ምርጫ ላይ የሚያሳድሩትን ተፅእኖ በመገንዘብ ለባህላዊ ጉዳዮች እውቅና እየሰጡ መጥተዋል፡፡ ሀገሮችም ይህንን እውነት በከፍተኛ ደረጃ እየተቀበሉና እየተገበሩት ነው፡፡ በዚህም በብዙ ሀገሮች የባህል ጉዳይ በልማት ዙሪያ በሚካሄዱ ውይይቶች፣ እቅዶች እና ተግባራት ውስጥ ቦታ እየተሰጠው መጥቷል፡፡ የዚህም ምክንያቱ ከሁሉ አስቀድመን “ልናለማው” የምንፈልገውን ማህበረሰብ በቅጡ ማወቅ ስለሚገባን ነው፡፡
ይህንን ዘመናዊና አለም አቀፋዊ ስምምነት ይዘን ወደ ሀገራችን ፊታችንን ስንመልስ ግን የምንመለከተው ምናልባትም የዚህን ተቃራኒ ነው፡፡ በሀገራችን የሚደረጉ ልማታዊ እንቅስቃሴዎች ባህልንና እሴቶቹን ያገናዘቡ ናቸው ማለት ድፍረት ነው፡፡ ያገናዘቡ  ይመስለን ይሆናል እንጂ አላገናዘቡም፡፡ ቀደም ብዬ እንዳልኩት የአንድን ማህበረሰብ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ደረጃ በአስተማማኝና ዘላቂ በሆነ መልኩ ማሳደግ ከተፈለገ ቀድሞ የማህበረሰቡን ባህል ማጥናትና እሴቶቹንም መነሻ ማድረግ የሚገባ ቢሆንም እየሆነ ያለው ግን በተቃራኒው ይመስላል፡፡ ይህም የልማቱን ሂደት በጭንጫ መሬት ላይ ዘርን ዘርቶ ምርትን እንደመጠበቅ አጉል ተስፋ አድርጎታል፡፡
ለማህበረሰቡ እንዲተዳደርባቸው ብሎም እንዲገዛላቸው የሚቀረጹት ፖሊሲዎች፣ እንዲፈጽማቸውና “እንዲለማባቸው” የሚታቀዱት እቅዶች ወዘተ… የሀገሬውን ባህላዊ እሴቶችና ከነዚህ የሚመነጭ አስተሳሰቡ ላይ ከመመስረት ይልቅ የሌሎች ሀገሮች ህዝቦች ላይ ተመስርተው የተቀረጹ ፖሊሲዎችና ስልቶች ናቸው፡፡ እነዚህም ለማህበረሰቡ እጅጉን ባዕድና ከሚጠብቃቸውና ከሚገዛላቸው ባህላዊ እሴቶቹ ጋር በጥቂቱም ቢሆን የማይሰምሩ በመሆናቸው ነገሩ ሁሉ አጓጉል መወራከብ ሆኖአል፡፡
የሌሎች ሀገሮችን መልካም ነገሮች ማምጣት የለብንም የሚል እምነት የለኝም፡፡ የማይጠቅሙንንም ጭምር ሳይሆን የሚጠቅሙንን ብቻ ለይተን ማምጣት እንዳለብን አምናለሁ፡፡ ከዚህ አስቀድሞ ግን ያሉንን ጠንቅቆ ማወቅና የሌሉንን/የሚጎድሉንን መለየት ያስፈልጋል፡፡  የሌሉንንም ከሌሎች አምጥቶ እንደወረደ መተግበር ሳይሆን ከእኛ አውድ ጋር ማልመድና መግራት፣ በነገሩም ላይ የጠራ ግንዛቤን ማስጨበጥ ያስፈልጋል፡፡ ይህ እስካልሆነ ድረስ አሁንም እናልማለን፣ በከንቱ እንደክማለን እንጂ የምንፈልገውን አንጨብጥም፡፡ ለዚህም ነው በርካታ “ልማታዊ” እንቅስቃሴዎች ከፍተኛ መዋዕለ ንዋይ ፈሶባቸው ሳይሳኩ ባክነው የቀሩት፡፡
በበርካታ የሀገሪቱ ክፍሎች (በተለይም በአርሶ አደሩ አካባቢዎች) በርካታ “ልማታዊ” እንቅስቃሴዎችና ተግባራት ተደርገዋል፡፡ ሆኖም እንዳለመታደል ሆኖ እንቅስቃሴዎቹ  የማህበረሰቡን ባህልና እሴቶቹን ግምት ውስጥ ያላስገቡና እንደተቀዱ የተተገበሩ በመሆናቸው ውጤታቸው ከትርፍ ይልቅ ኪሳራ የጎላበት ሆኖአል፡፡ የዚህም ምክንያቱ አስቀድሞም ማህበረሰቡ ለነገሩ የነበረው አመለካከት ወይንም ግንዛቤ አዎንታዊ አለመሆኑ ነው፡፡ ባህልን ያላገናዘበ “ልማት” ውጤቱ ይህ ነው፡፡ ከንቱ ድካም!
የሰው ልጅ ከሊቅ እስከ ደቂቅ፣ ከግለሰብ እስከ ህዝብ ከሚያከብራቸውና እንዲከበሩለት ከሚፈልጋቸው ነገሮች መካከል ምናልባትም ዋነኛው ባህሉ ነው፡፡ በመሆኑም ከባህላዊ እሴቶቹ ውጪ የሆኑና ምናልባትም በባህሉ ውስጥ አሉታዊ ትርጉም ለሚሰጣቸው ነገሮች ያለው ምላሽ ከሚፈለገው በተቃራኒው ነው፡፡ ስለሆነም ሲጀመርም ማንነቱን ያልተረዱ ተግባራትን አይቀበልም፡፡ በአስገዳጅ ሁኔታዎችና ተፅዕኖዎች እንዲቀበል ብናደርገውም ከመቀበል ባለፈ ለውጤቱ ምንም አይነት እንቅስቃሴ ስለማያደርግ፣ የሚፈለገው ውጤት “ላም አለኝ በሰማይ” አለፍ ሲልም ጭንጫ መሬት ላይ ዘር ዘርቶ ምርትን እንደመጠበቅ አጉል ተስፋ ነው፡፡ ከንቱ ድካም!
መልካም ሰንበት!!

Published in ህብረተሰብ

ከዕለታት አንድ ቀን ከብዙ ዓመታት በፊት ሰዎች እንደ ዛሬ ሳይሰለጥኑ በፊት፤ በአንዲት ትንሽ ከተማ አንድ እንደ ተዓምር የሚቆጠር ነገር ተፈጸመ፡፡ አንድ ቀንድ ያለው ጉጉት በአቅራቢያው ከሚገኘው ጫካ መጥቶ ከአንድ ሰው ግቢ ከሚገኝ የእህልና የከብት መኖ፣ እንዲሁም ጥራጥሬ መጋዘን  ውስጥ ይገባል፡፡ ሲነጋ እንዳይወጣ፤ ሌሎች ዶሮዎች ያዩኝና ልዩ ዓይነት ወፍ መሆኔን ሲረዱ ይጮሃሉ፡፡ ስለዚህ ዝም ብዬ ልቀመጥ ብሎ ወሰነ፡፡
ጠዋት የግቢው አሽከር ለከብቶች መኖ ሊወስድ ሲመጣ ጉጉቱን ጣራው አግዳሚ ላይ ሆኖ አየውና ደንግጦ “ጭራቅ! ጭራቅ!” እያለ እየጮኸ ወደ ጌትየው ሄዶ ተናገረ፡፡ የቤቱ ጌታም “አይ አንተ!  አንተንኮ እንደ እጄ መዳፍ ነው የማውቅህ፡፡ በሰፊ ሜዳ ቁራና ጥንብ - አንሣ የማባረር ልብ አለህ! አንዲት ጫጩት አንድ ጠባብ ቦታ ሞታ ብታይ ግን ወደዚያ ለመቅረብ ትልቅ ዱላ ፍለጋ ትሄዳለህ፡፡ ይሄን ጭራቅ ያልከውን እኔ ራሴ ሄጄ አየዋለሁ፡፡  ውሸት ቢሆን ወዮልህ!”
ጌትዬው  ወደ መጋዘን ገብቶ ሲያይ በድንጋጤ ተስፈንጥሮ ወጣ፡፡ ሮጦ ወደ ጎረቤቶቹ ሄዶ “ጎበዝ ማለቃችን ነው፡፡ አንድ አደገኛ ፍጡር ግቢዬ ገብቷል! ወጥቶ ወደ ከተማ ከገባ ህዝብ ማለቁ ነው፡፡ እንረዳዳና እዚሁ እርምጃ እንውሰድበት!” አለ፡፡
ወሬው ወዲያው ከመንደር መንደር በረረ፡፡ ከመንገድ መንገድ ሮጠ፡፡ ሰዉ ከፊሉ  ገጀራ፣ ከፊሉ ቆንጨራ፣  ከፊሉ ጦር፣ አካፋም፣ ማጭድም እያየዘ ወደግቢው ይመጣ ጀመር፡፡ ሰራዊት እንጂ አንድ ቀንዳም - ጉጉት ሊገድል የመጣ አይመስልም፡፡ በመጨረሻ ጭራሽ የከተማው ከንቲባ በሌሎች ሹማምንት ታጅበው መጡ፡፡ በተማው ለጥንቃቄ በየገበያው ምሽግ አሰርተዋል፡፡ አንድ የጎበዝ አለቃ ወደጉጉቱ ሄዶ ነበር፡፡ ድምፁን ሲሰማ በርግጎ ተመለሰ፡፡ ሌሎች ሁለት ሰዎች ሞከሩ፡፡
 ጉጉቱ ዓይኑን እያጉረጠረጠ በፍርሃት የሚያወጣው ድምፅ መብረቅ የመታቸው ያህል አስደግንጧቸው ዘለው ወጡ፡፡ በመጨረሻ አንድ መንዲስ የሚያህል ሰው፣ ያገሩ ጦረኛ ነው የሚባል ጀግና፣ ከጉጉቱ ሊተናነቅ ወስኖ መጣ፡፡ ከዛም በፉከራ ቃና “አንድን ጭራቅ “ጉድ! ጉድ!” በማለትና ዐይን ዐይኑን በማየት ልታባርሩት አትችሉም፡፡ ሁልሺም ቡከን ነሽ፡፡ ይሄን ጭራቅ ቀንዱን ይዤ ከጣራው ማውረድ አለብኝ! አለ፡፡ ሁለቱም የመጋዘኑ በር ብርግድ ብሎ ተከፈተ፡፡ አሁን ጉጉቱ ከጣራው  አግዳሚ እንጨት ላይ ተቀምጦ ቁልጭ ብሎ ይታያል፡፡ ጀግናው መሰላል አምጡልኝ አለ፡፡ መጣለት፡፡ ሰው ከፊሉ “ደፋር!” “አምበሳ!” አለው፡፡ ከፊሉ ይፀልይለት ጀመር፡፡
ጀግናው ወደ ጉጉቱ እየቀረበ ሄደ፡፡ ጉጉቱ ሁኔታውን በመጠራጠር የህዝቡን ጩኸት በመስማትና ምንም መውጫ እንደሌለው በማሰብ፤ ክንፎቹን አርገበገበ፡፡ ኩምቢውን ከፈተ፡፡ መንቆሩን ለጦርነት ያዘጋጀ መሰለ፡፡ ኩ-ፍ-ኩ-ኩ-ህ!” እያለ በፍጥነት መጮህ ጀመረ፡፡ ሰው “በለው!” “ያዘው” “አሳየው!” እያለ ከሥር ይጮህ ጀመር፡፡
“አይ ያገሬ ሰው! እኔ ያለሁበት ቦታ ቆመሽ ቢሆን አዳሜ ትንፍሽ አትይም ነበር!”
ጥቂት እርከን ለመውጣት ሞከረና ጀግናው፤ መርበትበት፣ መራድ ጀመረ፡፡ ቀስ እያለ በደረጃው ወረደ፡፡ ሰውም “አውሬው በትንፋሹ መርዞት ነው እንጂ የእኛ ጀግና እንዲህ ያለ ሰው አልነበረም፡፡ ለመሆኑ እንዲህ ያለ አውሬ ፊት ቆመን ህይወታችንን ማጥፋት አለብን እንዴ?” እያለ መንሾካሾክ ጀመረ፡፡ “ከተማችንን እንዳያጠፋ ምንድንነው የምናደርገው ማለት ቀጠለ?”  በመጨረሻ ከንቲባው መፍትሄ አመጡ፡፡
“ከመዘጋጃ ቤቱ ወጪ ተደርጎ ለመጋዘኑ ባለቤት የገንዘብ ካሳ እንስጥ፡፡ ለእህሉም. ለጭዱም፣ ለነዶውም መግዣ ይካካስለትና መጋዘኑ ከነአደገኛው አውሬ ይቃጠል! አሁን ለኢኮኖሚ የምናስብበት ጊዜ አይደለም!” ብራቮ ተባለ! ተጨበጨበ!
መጋዘኑ በአራቱም አቅጣጫ እሳት ተለቀቀበት፡፡ ምስኪኑ ወፍ በነበልባል ተለብልቦ አሰቃቂ ሞት ሞተ!
*          *           *
ነገሩ “አይ መሬት ያለ ሰው!” ያልነውን ያስታውሰናል፡፡ ነገርን በቅጡ አለማየት አሳቻ ፍፃሜ ላይ ያደርሰናል፡፡ ስለሆነም ወፍ አይተን ጭራቅ አየን እንላለን፡፡ አገሬው መንገኛ ከሆነ እንግዲህ  ይህንኑ ጭራቅ ጭራና ቀንድ ጨምሮለት ያልሆነ  ስዕል ፈጥሮ መዐት ይፈጥራል፡፡ የሰማህ ላልሰማህ የተባለ ይመስል እንደአዋጅ - ቃል ወሬ ይለፍፋል፡፡ ከዚያ ያገሩ ሹማምንት ያገባናል በሚል በተሳሳተው ነገር ላይ መመሪያ ይጨምሩበታል፡፡ መፍትሄ የማይፈጥር፣ ችግር ብቻ የሚያወራ ህዝብ ያልታደለ ነው፡፡ ኑሮ እንጉርጉሮ እንዳይሆን ማሰብ ያሻል! በወሬ የሚኖር ሰው፣ ነገር ያባብሳል እንጂ አንድ የመፍትሔ ጠጠር አይጥልም፡፡ ጎበዙን በለው! በለው! ለማለት የተፈጠሩ ይመስል፤ “በቅሎ ግዙ ግዙ አንድ አምሌ ላያግዙ!” ይሆናል ግርግሩ፡፡ ራሳችን በፈጠርነው የተሳሳተ ምስል “አስፈሪ! አደገኛ! …” እያልን፤ እሱኑም ፈርተን፤ ሌላውንም አስፈርተን፣ እሳት እንለኩሳለን! ይሄው ነው የአገራችን ፖለቲካ ነገረ - ሥራ!
“ጥፋታችንን አናምን፣ ሀጢያታችንን አንቀበል
ሁሌ ዝግጁና ፈጣን፣ በሌላው ላይ ለመቸከል
ደባ ነው መንገዳችን ሰርክ
ለእምዬ የአብዬን እከክ፣ በጥበብ ቅብ ለመላከክ!”
እንዳለው ገጣሚው፣ ራሳችን የሰራነውን ጥፋት በፈረደበት የበታች ወይም ቀን የጣለው ላይ መላከክ ነው ስራችን፡፡ ጥንት በአንድ አገር ዕምነት. ፍየል የዋህ ናት ትባል ነበር፤ አሉ፡፡
በሥርየት ቀን ቄስ ፍየሏ ጭንቅላት ለይ እጁን አድርጎ፣ የህዝቡን ሀጢያት ይናዘዛል፡፡ ጥፋት ሁሉ ወደ የዋህ ፍየል ይሄዳል፡፡ ይተላለፋል፡፡ ከዚያ ፍየሏ ወደ በረሀ ትነዳለች፡፡ እዛው ትቀራለች፡፡ የሰዉን ኃጢያት ሁሉ ይዛለት ጠፋች ማለት ነው፡፡ እንግዲህ Scapegoat የሚለው የፈረንጆች ቃል ከዚህ ነው የመጣው” ሊባል ይችላል፡፡ በሌላ ላይ ማሳበብ፣ በሌሎች ላይ መጫን ነው የአበሻ ኑሮ ዘዴ፡፡ ማዖ የባህል አብዮቱ ከሽፎ ክፉኛ ሲወድቅበት ምንም ይቅርታ አልጠየቀም፡፡ ይልቁንም በከፍተኛው የፓርቲ አመራር አባል ላይ ላከከ፡፡ የግል ፀሐፊውንም እንኳ ከወንጀሉ ነፃ አላደረጋትም፡፡ የእኛን ጨምሮ በየትም አገር በዘመቻም፣ በፕሬስም፣ በማፍረስም፣ በመገንባትም አንዳንድ የዋህ ፍየል አይጠፋም፡፡ ያውም እንደ ሰበብ ተደርጎ ሲቆጠር የማያጉረመርም ፍየል! ሌላ ምሣሌ:- ጥንት ጃንሆይ ለፀሐፊ ትዕዛዙ በቃል መመሪያ ይሰጡ ነበር አሉ፡፡ ያ መመሪያ ወደ ሥራ ተመንዝሮ ውጤቱ ሰናይ ከሆነ ምስጋናው ለጃንሆይ ይሆናል፡፡ ያልተሳካ ከሆነ ግን እርግማኑ ከፀሐፊ ትዕዛዝ ራስ አይወርድም፡፡ ዓለም የሥርዓተ- መላከክ (escapegoatism) ዓለም ነው፡፡
በተግባርና በወሬ መካከል ያለው ገደል - አከል ርቀት ሳይገደብ ለውጥ ማምጣት ከባድ ነው፡፡ ወሬ - ናፈቅ ትውልድ አገር ይሸረሽራል! “ጦር ከፈታው ወሬ የፈታው” የሚለው የአበው አነጋገር ቧልት አይደለም፡፡ “ወሬ ሲበዛ ጥበብ ዋዛ” እንደማለት ነው፡፡ ወሬ ሲበዛ ያልተሰራው ተሰራ፣ ያላሸነፈው አሸነፈ፣ ያልቀናው ቀና ማለትን ይወልዳል፡፡ ከጊዜ ብዛት ሰው ያምናል፡፡ ከዚያ ውሸት ሁሉ ዕውነት ይመስላል፡፡ “ወሬ ሲበዛ ጭቃ ከግድግዳ ተፍረክርኮ ይወድቃል፡፡ ሙቀጫም  ለጭፈራ ይነሳል” የሚለው የወላይታ ተረት የሚነግረን ይሄንኑ ነው!

Published in ርዕሰ አንቀፅ
Page 6 of 19