“ቡና የለም እንጂ ቡናማ ቢኖር

ወይ አገር ወይ አገር፣ ወይ አገር ጎንደር”
      *        *      *
አገሯ ጉዋሳ መገራ
ምነው አልሰማ አለች ብጣራ ብጣራ
      *        *      *
እውነት ለመናገር አንዳንድ አገራችንን ክፍሎች የምናውቃቸው በግጥም ብቻ ነው፡፡ ሄደን ስናይ ከግጥሙና ከአገሩ የቱ እንደሚሰፋ እንለያለን፡፡ መጀመሪያ ጎንደር፡፡ ጐንደር ደርሼ የተመለስኩት በአውሮፕላን ነው፡፡ ያረፍኩት ላንድ ማርክ የሚባል ግፉፍ ሆቴል ነው፡፡ ባለቤቱ ይህን ዓይነት ትልቅ ሆቴል ምን ሲል ሰራው አሰኝቶኛል ግርማ ሞገሱ! ፋሲል መናፈሻ ምሣ በላን፡፡ ከላንድ ማርክ ከፎቁ ላይ ሆኜ ጐንደርን ዙሪያ - ገባውን የማየት (Panoramic view) ዕድል አግኝቻለሁ፡፡ የጋበዘኝ “ግጥም በመሶንቆ” የሚባል ፕሮግራም አዘጋጅ አካል ነወ፡፡ [ጉዋሳ የሄድኩት ደግሞ ከ “ኤን.ቲ.ኦ” ጋር ነው (ዝርዝሩን ወደ ኋላ አምጥቼ ዓላማና ሁነቱን እተርክላችኋለሁ ግጥም በመሰንቆ ታዋቂ ሰዎችን በመጋበዝ)] በየወሩ ይሄንኑ ይሠራል፡፡ ጌትነት እንየው፣ በረከት በላይነህ፣ ኤፍሬም ሥዩም… ከኔ በፊት መምጣታቸውን ሰምቻለሁ፡፡ የፓኤቲክ - ጃዝ አመራር አባላትም ሙሉአቸውን ሄደው ነበር አሉ፡፡ አገር ላገር ግትም መናበብ ትልቅ ጸጋ ነው! ጥናቱን ይስጠን!! ይህ ፕሮግራም ቀድሞ ሲጀመር በመሰንቆ ብቻ ጨዋታ ይኖርና ግጥም ይፈስስበታል፤ አሉኝ፡፡ አሁን አሁን ክራርም፤ ዘመናዊ ሙዚቃም ተጨምሮበታል፡፡ እኔ የሄድኩበትን ፕሮግራም ልዩና በዓይነቱ አዲስ የሚያደርገው፣ ከዚህ ቀደም ፕሮግራሙ የሚካሄደው አዳራሽ ውስጥ ሲሆን አሁን በእኔ ጊዜ ግን ደጅ በላንድ ማርክ የተንጣለለ መስክ ላይ መካሄዱ ነው፡፡ አየሩ ይጥማል፡፡ ሰዉ አምፊ - ቲያትራዊ (ግማሽ- ክበብ) በሆነ ድባብ ግጥም ብሏል፡፡ ግጥም ብሎ ግጥም ይጠብቃል! ግጥም በናፍቆት የጐንደር ባህል ውስጥ መሪ ቦታ አለው፡፡ ለንጉሥ የሚገጠመውን ያህል ለአዘቦቱ ሰው፣ ለዜጋው፣ ለአሽከሩም ይገጠማል፡፡
አንድ ትዝ ያለኝን ነገረ ላጫውታችሁ፡፡
መልኬ ብርሃኔ የተባለ ጐንደሬ ወዳጄ አንዴ ማዕከላዊ ምርመራ ድርጅት እሥር ቤት አብረን ሳለን፤ ስለ ጐንደር ምስኪን ገበሬ የተገጠመውን ነግሮኛል፡፡
ያ ምስኪን ገበሬ ስሙ ‘ና’ ስቲለው ነው፡፡ ና ስቲለው ማለት ፈጣሪ ና እስኪለው፤ አምላክ እስቲጠራው፣ ድረስ ይለፋል ለማለት ነው፡፡ ታዲያ የሱን ኑሮና ህይወት ለመግለጽ እንዲህ ብለው ገጥመዋል፡፡
“ሰኞ ማለስለስ ነው
ማክሰኞም ጐልጓሎ
ዕሮብ ዘር ዝሪ ነው፤
ሀሙስ አረም ማረም
ዐርብም አጨዳ ነው፤
ቅዳሜም ውቂያ ነው
እሁድ ጐተራ ነው፤
ና - እስቲለው ኮት ገዝቷል፣ መቼ ሊለብሰው ነው!”
ከእሁድ እስከ እሁድ ለኮት መልበሻ እንኳ ጊዜ አጥቶ ሲለፋ ይኖራል ነው ነገሩ፡፡ ጐንደር ያለጥርጥር የግጥም አገር ነው፡፡ የጀግና አገር ነውና ይዘፈንለታል፡፡ ይገጠምለታል፡፡
“መቅደላ አፋፉ ላይ ጩኸት በረከተ
የሴቱን አናውቅም፤ ወንድ አንድ ሰው ሞተ” የተባለው እዚያ ነው፡፡
ያለነገር ---“ ገዴ ዙራ ዙራ፣ በዕንቁላሏ ላይ
ጊዜ እሚጠብቅ ሰው፣ ጅል ሊባል ነው ወይ! … አልተባለለትም፡፡
ያለነገርም፤
“ሞኞች ናቸው፣ ዳኞች ሞኞች ናቸው - ዋስ ጥራ ይላሉ
ከነዋሱስ ቢሄድ፣ ማንን ይይዛሉ!”
ተብሎ አልተገጠመለትም፡፡
እንግዲህ እዚህ ጐንደር አገር ነው የህይወት ገጠመኜን ለወጣቱ ላካፍልና ግጥም ላነብ የተጋበዝኩት፡፡
እንደልምድ ማጋራት ያወራኋቸው እሥር ቤት ሆኜ ስለተረጐምኩት “ነገም ሌላ ቀን ነው” የተባለ መጽሐፍ ነው፡፡ የማርጋሬት ሚሼል ጐን ዊዝ ዘ ዊንድ (Gone with the Wind) ነው፡፡ እና አንዳንድ የእሥር ቤት ገጠመኞቼንም አወጋኋቸው፡፡ አንዳንድ መከራ መጽሐፍ እስከመፃፍ ያስችላል፡፡ ግን ዋናው ትዕግሥቱና ጥንካሬው ወሳኝ መሆኑ ነው፡፡ ጊዜውን ከተጠቀሙበትና ፅናቱ ካለ ሥራ የማያሠራ ሁኔታ የለም!! የሚለው የሁልጊዜ አፅንዖቴ ነው፡፡ እሱንም  ተናግሬአለሁ፡፡አብረውኝ የጐንደር ወጣቶች ግጥም አንብበዋል፡፡ ጉልበት ያላቸው ግጥሞች በድራማዊ አነባበብ ያቀረቡ ነበሩ፡፡ ወዝና ደርዝ ያላቸው ግጥሞች ፈጥረዋል፡፡ ወጣት ግጥሞች በወጣት ፍል - ብስለት ቀርበው ነበር ለማለት ይቻላል! ቀስ  እያሉ የሚበስሉ ግጥሞችም አሉባቸው፡፡ ከድራማዊ አቀራረብ ወደ አርምሞአዊ ጥሞናዊ አነባበብ ይሸጋገራሉ የሚል ተስፋ አለኝ፡፡ የሌሎችን የአነባበብ ስልት መቅዳት እንደሚተውም ተስፋ አለኝ፡፡ እኔ ከራሴ “ከጥቁር ነጭ ግራጫ ግጥሞች፣ ከስውር ስፌት ቁጥር አንድና ቁጥር ሁለት፣ እንዲሁም በቅርቡ ከሚታተመው ስውር ስፌት ቁጥር ሶስት መራርጬ ነው ያነበብኩላቸው፡፡
ጐንደር ሄዶ ባህል ቤት ሳይደርሱ መምጣት መቼም ነውር ነው አሉ፡፡ እዚያም ሄጃለሁ፡፡ የሴት አታሞኛ (አታሞ መቺ) ማየት ማርኮኛል፡፡ የጐንደር ጨዋታ ቤት በጀግንነት የተሞላ ነው፡፡ ግጥሞቹ የጀግንነት እንፋሎት የአሞቃቸው ናቸው፡፡ ከአገሬው ግጥሞች በድጋሚ የሰማሁት ቢሆንም የምወደውን አግኝቻለሁ፡- “ደገኛ በሬውን ይለዋል አውግቼው
አትምጣ ብለሺኝ መጣሁ እረስቼው፡፡”
ከአዘጋጆቹ አንዷ የገጠመችው ግጥም ለየት ማለቱም፣ ቅርፅ- ወጣ ይዘቱም ማርኮኛል፡-
“አይቼ ሰምቼ ሁሌም ዝም የምለው
አይቶ እሚናገረው፣ ዐይኔ ስላለ ነው፡፡
ቀን ጨለማ ሳይል፣ ብርሃን ሳይሰጋ
ተራራ ሸለቆ፣ ቆላ ሳይል ደጋ
ልበ - ቢሱ ልቤ፣ ሄዷል ቀን ፍለጋ!”
ባለኝ አጭር ጊዜ በወፍ በረር እይታ ከአርባ ዓመት በኋላ አይቻት ከህንፃ ብዛትና ከባጃጅ ብር-ሽር-ሽው ሌላ ብዙ ለውጥ ያላየሁባትን ጎንደርን ብዙ አስተያየት ከመስጠት ተቆጥቤያለሁ፡፡ አንዳንድ የምለው ግን አለኝ፡፡
(ይቀጥላል)

Published in ባህል

15 ቢ. ብር የፈጁትን የነፋስ ተርባይኖች፤ በ5 ቢ.ብር የውሃ ግድብ መተካት ይቻላል
ከ10 ቢ. ብር በላይ ሃብት በከንቱ ባከነ፤ እንደ ዘበት በነፋስ ተወሰደ ማለት ነው
በረሃብተኛ ድሃ አገር፣ ይሄ ሁሉ ብክነት እብደት ነው? ወንጀል ነው? ወይስ ምን?
ግን፤ ወይ ነገሬ አላልነውም፤ ወይ አብረን አጨብጭበናል፤ ወይ በዝምታ ፈቅደናል
የግድብ ግንባታን የሚቃወሙ የአካባቢ ጥበቃ ቡድኖች፣ መጫወቻቸው አድርገውናል
ጠ/ሚ መለስ ዜናዊ፤ የአካባቢ ጥበቃ ቡድኖችን፤ “የድህነት ጠበቃ” ብለዋቸው ነበር

አገር    አመት    የነፋስ ተርባይኖች አቅም (ሺሜዋ)    በአመት ያመነጩት ሃይል (ሺ ጊዋሃ)    የተርባይኖቹ ብቃት
ጀርመን    2005    31    50    18%
ፈረንሳይ    2005    7.6    15    22%
ፖላንድ    2005    2.5    5.6    25%
ብሪታኒያ    2005    8.7    19    25%
ስፔን    2005    23    49    24%
ጣሊያን    2005    8    13.6    19%
አሜሪካ    2001    4    6.7    19%

በውሃ ግድብ የኤሌክትሪክ ሃይል የሚያመነጩ ጣቢያዎች ብቃትስ?    ከ40 – 50%
መንግስት ባለፈው ወር የተፈራረመውን ውል ጨምሮ፣ በነፋስ ተርባይን ኤሌክትሪክ የሚያመነጩ ሶስት ጣቢያዎችን ለማቋቋም 770 ሚሊዮን ዶላር ገደማ ሃብት አፍስሷል። ቀላል ገንዘብ አይደለም። ከ15.4 ቢሊዮን ብር በላይ ነው። የሶስቱ ጣቢያዎች ኤሌክትሪክ የማመንጨት አቅም ተደማምሮ ስንት እንደሆነ ደግሞ ተመልከቱ - 325 ሜጋዋት ብቻ ነው። በቃ፡፡ እና …ለዚህ ነው ያ ሁሉ ገንዘብ እየፈሰሰ ያለው? በገንዘብ መጫወት ይሉሃል፣ ይሄ ነው።
ለንፅፅር ያህል የህዳሴ ግድብ፤ ከነፋስ ተርባይኖቹ ጋር የሚመጣጠን የማመንጨት “አቅም” ለመፍጠር ምን ያህል ገንዘብ እንደሚፈጅበት ማስላት እንችላለን። ከግልገል ጊቤ ጣቢያዎች ጋር፣ አልያም ከተከዜ ወይም ከጣና በለስ ግድቦች ጋርም ማነፃፀር ይቻላል። የግድቦቹ አማካይ የግንባታ ወጪ፣ ዝቅተኛ ነው፡፡ ለአንድ ሜጋዋት 1.2 ሚሊዮን ዶላር አይደርስም። በዚህ ሂሳብ፣ ባለ 325 ሜጋዋት ማመንጫ ግድብ ለመገንባት፣ ቢበዛ ቢበዛ በአማካይ 390 ሚሊዮን ዶላር ቢፈጅ ነው (ማለትም፣ ከስምንት ቢሊዮን ብር በታች)። ለነፋስ ተርባይ ሲሆን ግን፣ ከ15 ቢሊዮን ብር በላይ!
ታዲያ፤ በአነስተኛ ወጪ፣ ከውሃ ሃይል ኤሌክትሪክ የሚያመነጩ ግድቦችንና ጣቢያዎችን መገንባት እየተቻለ፣ ያ ሁሉ ገንዘብ ለምን በነፋስ ተርባይን ይባክናል? እንዴ! ከሰባት ቢሊዮን ብር የሚበልጥ ልዩነትኮ፣ በጣም በጣም ብዙ ነው። በየእለቱና በየሰዓቱ መብራት እየተቋረጠ ስራ የሚስተጓጎለው፣ ፋብሪካዎች የሚከስሩት፣ ጨለማ ውስጥ የምናድረው፤ የኤሌክትሪክ ማሰራጫና ማከፋፈያ ተቋማት በማርጀታቸውና በማነሳቸው ነው ተብሎ የለ! በከንቱ የሚባክነውን ገንዘብ፣ ለዚህ ለዚህ ማዋል ይቻል ነበር።
“መቼም፣ የበርካታ ቢሊዮን ብር ሃብት በከንቱ እንዲባክን አይደረግም፤ አንዳች አሳማኝ ምክንያት መኖር አለበት” የሚል ሃሳብ ይመጣላችሁ ይሆናል። ‘ሃሳብ’ ሳይሆን፣ ‘ምኞት’ ብትሉት ይሻላል - ለዚያውም የማይጨበጥ ምኞት። አንዳችም አሳማኝ ምክንያት የሚያቀርብላችሁ አታገኙም። በነፋስ ተርባይን አማካኝት የኤሌክትሪክ ሃይል ማመንጨት፣ በጣም ከፍተኛ ወጪ እንደሚፈጅ...፣ በይፋ የሚታወቅ፣ በቁጥር የተሰላ፣ ማንም ጤናማ ሰው ሊክደው የማይችል ሃቅ ነው።
አስገራሚው ነገር፣ የነፋስ ተርባይኖች ችግር፣ ብዙ ገንዘብ መፍጀታቸው ብቻ አይደለም። ለካ አንዳንዴ የአገራችን ሰዎች “የባሰ አታምጣ” የሚሉት ወደው አይደለም! በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንደሚባለው ነው። በብዙ ወጪ የተተከሉት የነፋስ ተርባይኖች፣ የታቀደላቸውን ያህል ውጤታማ አይደሉም። ኤሌክትሪክ የማመንጨት ብቃታቸው አነስተኛ ነው። የአቅማቸውን 30 በመቶ ያህል እንኳ ብቃት የላቸውም። በውሃ ግድብ አማካኝነት ኤሌክትሪክ የሚያመነጩ ጣቢያዎች ግን፣ የአቅማቸውን 48 በመቶ በሚደርስ የላቀ ብቃት ኤሌክትሪክ እንደሚያመነጩ የኢትዮጵያ የበርካታ አመታት መረጃ ያሳያል። ይህን ለማረጋገጥና የአምና መረጃዎችን ለማየት፤ ብሔራዊ ባንክ በየሶስት ወሩ የሚያወጣቸውን ሪፖርቶች ተመልከቱ። አልያም ከአስር አመታት በፊት የነበረውን መረጃ፣ ከኤሌክትሪክ ሃይል ኮርፖሬሽን ሪፖርቶች ታገኛላችሁ።  
በአጭሩ፣ የነፋስ ተርባይን ጣቢያዎችን እና የውሃ ግድብ ጣቢያዎችን ስናነፃፅር፣ የነፋስ ተርባይኖች ኪሳራና ብክነት እጥፍ ድርብ መሆኑን በማያጠራጥር መንገድ መገንዘብ እንችላለን። የውሃ ግድብ ጣቢያዎች፣ የግንባታ ወጪ በግማሽ ያህል ቅናሽ ነው። ኤሌክትሪክ የማመንጨት ብቃታቸው ደግሞ ከነፋስ ተርባይኖች በ70 በመቶ ያህል ይልቃል።
እንዲያውም፣ ወደ ፊት የነፋስ ተርባይኖቹ ብቃት ይባስ እየቀነሰ መሄዱ አይቀርም። ለምን በሉ። አንደኛ ነገር፣ የነፋስ ተርባይኖች እድሜ በጨመረ ቁጥር፣ ብቃታቸው እየወረደ ይሄዳል። ሁለተኛ ነገር፣ ለነፋስ ተርባይኖች እጅግ በጣም ተስማሚ የሆኑ ነፋስ የሚበዛባቸውና የሚዘወትርባቸው ቦታዎች ናቸው አሁን ጥቅም ላይ የዋሉት። ወደ ፊት ተመሳሳይ ቦታ ለማግኘት አስቸጋሪ ነው። እናም የነፋስ ተርባይኖች ብቃት ከ25 በመቶ በታች መውረድ አይቀርለትም።
የነፋስ ተርባይኖች ብቃት 30 በመቶ እንኳ መድረስ ያልቻለው በኢትዮጵያ ብቻ አይደለም። በሁሉም የአውሮፓ አገራትና በአሜሪካ ጭምር፣ ላለፉት በርካታ አመታት በተጨባጭ የተመዘገበ መረጃ ነው። የነፋስ ተርባይን አፍቃሪ ተቋማት ራሳቸው የሚያቀርቡትን መረጃ ብቻ ልጥቀስላችሁ። የነፋስ ተርባይኖችን ለማስፋፋት መንግስታት ተጨማሪ ድጎማ መስጠት ይኖርባቸዋል እያለ ዘመቻ የሚያካሂደው የጀርመን ተቋም HSH NORDBANK፤ ባለፈው መስከረም ወር Sector Study WIND ENERGY በሚል ርዕስ ካቀረበው አመታዊ ሪፖርት የተወሰዱ ጥቂት መረጃዎችን እነሆ።
ከአመት በፊት በ2005 ዓ.ም፤ ጀርመን ውስጥ የሚገኙ ባለ 31ሺ ሜጋዋት የነፋስ ተርባይን ጣቢያዎች፣ 50ሺ ጊዋሃ ሃይል አመንጭተዋል ይላል ሪፖርቱ። ይህም ማለት የተርባይኖቹ ብቃት 18% ገደማ እንደሆነ ያረጋግጣል። የአሜሪካም ተመሳሳይ ነው። በ2001 ወደ አራት ሺህ ሜጋዋት የሚጠጋ አቅም ያላቸው የነፋስ ተርባይኖች በ19% የብቃት ደረጃ 7ሺ ጊዋሃ የኤሌክትሪክ ሃይል እንዳመነጩ፣ የአሜሪካ የኢነርጂ መስሪያ ቤት ገልጿል - እየተገባደደ ባለው የፈረንጆች አመት ባወጣው ሪፖርት።
የብሪታኒያ ትንሽ ይሻላል። የ8.7ሺ ሜጋዋት አቅም ያላቸው የነፋስ ተርባይኖች፣ በአመት ውስጥ ያመነጩት የሃይል መጠን 19 ሺ ጊዋሃ ነው። (ማለትም ተርባይኖቹ የሚሰሩት በ25% ብቃት ነው)። ምን አለፋችሁ? በየትኛውም የአውሮፓ አገር፣ በየትኛውም ጊዜ፣ የነፋስ ተርባይኖች ብቃት 30% ደርሶ እንደማያውቅ፤ HSH NORDBANK ያወጣው ሪፖርት ያስረዳል። ከተርባይኖቹ እድሜ ጋርም፣ ብቃታቸው ወደ ሃያ በመቶ ይወርዳል።
ነፋስ ተርባይኖች ብቃት፣ በአንዳንዶቹ አገራት ከ20 በመቶ ሊበልጥ የቻለው አንዳች ተአምረኛ ዘዴ ስለፈጠሩ አይደለም። በመሬት ላይ ሳይሆን በባህር ላይ የተተከሉ ተርባይኖችን ስለሚጠቀሙ ነው ልዩነት የተፈጠረው። ምድር ላይ ከሚተከሉት ተርባይኖች ይልቅ የባህር ላይ ተርባይኖች፤ በጥቂቱም ቢሆን የላቀ ብቃት አላቸው። እንዲያም ሆኖ፤ ብዙም ለውጥ የለውም። አንደኛ፣ የባህር ላይ ተርባይኖች ያን ያህልም የሚያስመካ ልዩነት አያመጡም። ሁለተኛ ነገር፤ ባህር ለሌላቸው እንደ ኢትዮጵያ ለመሳሰሉ አገራት፤ ትርጉም የለውም። ምን ለማለት ፈልጌ ነው? ነጋ ጠባ የአካባቢ ጥበቃ ቡድኖችና አጨብጫቢዎች ከሚለፍፉት ስብከት በተቃራኒ፤ የነፋስ ተርባይኖች ብቃት ውሎ አድሮ በተጨባጭ 20% ገደማ እንደሚሆን ለመግለፅ ፈልጌ ነው።
በውሃ ግድብ አማካኝነት የኤሌክትሪክ ሃይል የሚያመነጩ ጣቢያዎች ግን፣ ከብዙ አመታት አገልግሎት በኋላም በአማካይ 48 በመቶ ገደማ መሆኑን ደግሞ አትርሱ። ለዚህ ማረጋገጫ፣ ከኤሌክትሪክ ኮርፖሬሽንና ከብሄራዊ ባንክ የ2006 ዓ.ም ሪፖርቶች በተጨማሪ፣ ሌላ መረጃ ትፈልጉ ይሆናል። Study on the Energy Sector in Ethiopia በሚል በጃፓን ኤምባሲ የተዘጋጀውን የጥናት ሰነድ መቃኘት ትችላላችሁ፡፡ እስከ 2000 ዓ.ም ድረስ በነበረው መረጃ መሰረት፣ የኤሌክትሪክ ሃይል የሚያመነጩ ግድቦች በድምር “ባለ 670 ሜጋዋት” እንደነበሩ በማስታወስ፤ በአማካይ በአመት 2.84 ጊዋሃ ሃይል ያመነጩ እንደነበር ጥናቱ ይገልፃል። (የግድቦቹ ብቃት ከ48% በላይ ነበር ማለት ነው።) የአምና መረጃዎችን ብንመለከትም፣ ተመሳሳይ ውጤት እናገኛለን።    
የነፋስ ተርባይን ጣቢያዎችና የውሃ ግድብ ጣቢያዎች፤ ኤሌክትሪክ የማመንጨት ብቃታቸው እንዲያ የሚራራቀው ያለምክንያት አይደለም። የመኪና ሞተርን እንደ ምሳሌ በመውሰድ ልዩነቱን ለማሳየት ልሞክር። ሞተሩ የአቅሙን ያህል ለመስራት ነዳጅ ያስፈልገው የለ? የነፋስ ተርባይኖች፣ መንቀሳቀሻ ነዳጃቸው “ነፋስ” ነው። ለውሃ ግድብ ጣቢያዎች ደግሞ፤ ነዳጃቸው ውሃ ነው። እንዲህ የየራሳቸው “ነዳጅ” ቢኖራቸውም፤ የነዳጅ አጠቃቀማቸው ግን ይለያል። የነፋስ ተርባይኖች ነዳጃቸውን (ነፋስን) መቆጣጠርና ማጠራቀም አይችሉም። የነዳጅ መቆጣጠሪያና ማርሽ እንደ ሌለው መኪና ቁጠሩት - ለአቀበቱም ለቁልቁለቱም፣ ሲቆምም ሲጓዝም ነዳጁን ይጠቀማል። ነዳጅ ሲቋረጥበት፣ ከማጠራቀሚያ አውጥቶ መጠቀም አይችልም። ነዳጅ ሲያልቅበት በጀሪካን እስኪመጣለት ድረስ መኪናውን አቁሞ እንደሚጠባበቅ ሾፌር ማለት ነው። የውሃ ግድቦች ግን፤ የነዳጃቸው (የውሃ) መጠንን እየተቆጣጠሩ መልቀቅ፤ ብዙ የኤሌክትሪክ ሃይል በማያስፈልግበት ወቅትም ውሃውን ይዘው ማቆየትና ማጠራቀም ይችላሉ። የውሃ ግድብ ጣቢያዎች፤ የኤሌክትሪክ ሃይል የማመንጨት ብቃታቸው ከፍተኛ የሚሆነው በዚህ ዋና ምክንያት ነው።እዚህ ላይ፤ አንድ ቀላል ጥያቄ ቢነሳ አይገርምም። የውሃ ግድብ ጣቢያዎች ብቃት በእጥፍ የሚበልጥ ከሆነ፤ ወጪያቸው ደግሞ በግማሽ ያህል ቅናሽ ከሆነ ለምንድነው የነፋስ ተርባይን ጣቢያዎችን ለመገንባት ሃብት የሚባክነው? ወጪያቸው እጥፍ ነው፤ ብቃታቸው ደግሞ በግማሽ የወረደ መሆኑ እየታወቀ!
በነፋስ ተርባይኖች ምትክ 325 ሜጋዋት የሚያመነጭ ግድብ ቢገነባ ኖሮ፣ ወጪው በ7.6 ቢሊዮን ብር ያነሰ ይሆን ነበር። ከዚህም በተጨማሪ፣ የግድብ ሃይል ማመንጫ ብቃት 48% ገደማ ስለሆነ፤ በየአመቱ 1300 ጊዋሃ ሃይል ማመንጨት በቻለ ነበር። የነፋስ ተርባይኖች ግን፤ ወጪያቸው በእጥፍ ቢበልጥም፤ በየአመቱ የሚመነጩት ሃይል 800 ጊዋሃ ገደማ ብቻ ነው።ልዩነቱ እጥፍ ድርብ ነው። የነፋስና የግድብ ማመንጫ ጣቢያዎቹ “ባለ 325 ሜጋዋት” የሚል ስያሜ ቢለጠፍባቸውም፤ ወጪያቸውና ብቃታቸው በጣም ይራራቃል። የነፋስ ተርባይን ጣቢያዎች፤ ወጪያቸው ከፍተኛ፣ ብቃታቸው ደግሞ ዝቅተኛ ነው። የውሃ ግድብ ጣቢያዎች ደግሞ ወጪያቸው ዝቅተኛ፣ ብቃታቸው ግን ከፍተኛ። እንዳያችሁት፣ “ባለ 325 ሜጋዋት” የተሰኙት የነፋስ ተርባይኖች በአመት 800 ሜዋሃ ገደማ ብቻ ነው ማመንጨት የሚችሉት። የዚህን ያህል የኤሌክትሪክ ሃይል ለማመንጨትማ፤ ባለ 190 ሜጋዋት የግድብ ማመንጫ ጣቢያ መገንባት በቂ ነው - ለዚያውም ወጪው 230 ሚሊዮን ዶላር አይሞላም - ከ5 ቢሊዮን ብር በታች መሆኑ ነው። እንግዲህ አስቡት፤ ይህችኑ የሃይል መጠን ለማመንጨት ነው ከ15 ቢሊዮን ዶላር በሚበልጥ ወጪ ለነፋስ ተርባይን ጣቢያዎች  እየፈሰሰ ያለው። በሌላ አነጋገር፤ ከ10 ቢሊዮን ብር በላይ ሀብት በከንቱ እንዲባክን ተደርጓል። እብደት፣ ወንጀል ወይስ ምን? የጊዜ ጉዳይ እንጂ፤ በዚህ ብክነት ላይ የተሳተፉና የተባበሩ ሃላፊዎች ውሎ አድኖ ተጠያቂ መሆናቸው አይቀርም፡፡ እስከዚያው ግን መብራት በየሰዓቱ እየተቋረጠብን እንቀጥላለን፡፡ ለነገሩ፤ አስር ቢሊዮን ብር በከንቱ ለነፋስ ሲበተን እያየን ዝምታን የመረጥን ሰዎችስ፤ መብራት ሲቋረጥብን ቢውል ቢያድር ይገርማል፡፡ የእጃችንን ነው ያገኘነው፡፡  

Published in ዜና

በ 6 ወራት 8 አዳዲስ አውሮፕላኖችን አስገባለሁ ብሏል

የኢትዮጵያ አየር መንገድ በምዕራብ አፍሪካ አገራት የተቀሰቀሰው የኢቦላ ቫይረስ በፈጠረው ስጋት ምክንያት የመንገደኞች ቁጥር በመቀነሱ፣ በወር ከ8 ሚ. ዶላር በላይ ገቢ እያጣ እንደሆነ ሮይተርስ ትናንት ዘገበ፡፡
የአየር መንገዱን ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ተወልደ ገብረ ማርያምን ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ኢቦላ ለአየር መንገዱ ከየትኛውም አለማቀፍ የኢኮኖሚ ቀውስ በበለጠ በእንቅስቃሴው ላይ ተጽዕኖ የሚፈጥር ተግዳሮት ሆኖበታል፡፡
ምንም እንኳን በአዲስ አበባ ከተማ የሚገኘው የአየር መንገዱ ዋነኛ ማዕከል፣ በኢቦላ ቫይረስ ከተጠቁት የምዕራብ አፍሪካ አገራት የረጅም ሰዓታት በረራ የሚወስድ ርቀት ላይ ቢገኝም፣ በሽታው በአየር መንገዱ ተጓዦች ቁጥር ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ መፍጠሩ አልቀረም ያሉት አቶ ተወልደ፤ ሁኔታው በመጪዎቹ ጥቂት ወራት ውስጥ እንደሚቀየርና የመንገደኞች ቁጥርም ወደነበረበት እንደሚመለስ ያላቸውን ተስፋ ገልጸዋል፡፡በአገራቱ የተቀሰቀሰው የኢቦላ ወረርሽኝ፣ በመላ አህጉሪቱ ከሚደረጉ በረራዎች በአብዛኞቹ ላይ ተጽዕኖ መፍጠሩንና በሽታው ለአፍሪካ አየር መንገዶች ዋነኛው ስጋት መሆኑንም ተናግረዋል፡፡
ኢቦላ ወደ አፍሪካ አገራት በሚጓዙ መንገደኞች ላይ ስጋት መፍጠሩን የጠቀሰው ዘገባው፤ በተለይም በእስያውያን  መንገደኞች ዘንድ ያለውን ፍላጎት እንዲቀንስ አድርጎታል፡፡ በዘርፉ የሚታዩ የገበያ ችግሮች እንዳሉ ሆነው፣ አየር መንገዱ የቀየሳቸውን የረጅም ጊዜ የዕድገት ዕቅዶች መተግበሩን እንደሚቀጥል ገልጸው፣ እስከ መጪው 2015 የመጀመሪያዎቹ ስድስት ወራት፣ 3 ቦይንግ 787-8 ድሪምላይነር አውሮፕላኖችን ጨምሮ 8 አዳዲስ አውሮፕላኖችን ገዝቶ በስራ ላይ እንደሚያሰማራ አስረድተዋል፡፡
በተያያዘ ዜና የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሁለት ቦይንግ 777 የጭነት አውሮፕላኖችን ለመግዛት የሚውል የ41.4 ሚሊዮን ዶላር ብድር አይኤንጂ ካፒታል ከተባለ አሜሪካ የፋይናንስ ተቋም ማግኘቱን ከትናንት በስቲያ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
የገንዘብ ብድሩ መገኘቱና አውሮፕላኖቹ መገዛታቸው፣ በአፍሪካ ትልቁ የጭነት አየር መንገድ ሆኖ የመዝለቅ ዕቅድ ለያዘው የኢትዮጵያ አየር መንገድ አቅምንና የአገልግሎት ጥራትን በማሳደግ ረገድ ትልቅ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክትም ተገልጿል፡፡

Published in ዜና

“እኔ ከአቶ አበባው በላይ ለመኢአድ ዋጋ ከፍያለሁ

በቅርቡ በተካሄደው የመላ ኢትዮጵያውያን አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ጠቅላላ ጉባኤ ላይ ለአራት ዓመት ታግደው የነበሩት አቶ ማሙሸት አማረ ወደ ፓርቲው ተመልሰው በፕሬዚዳንትነት ተመርጠዋል፡፡ በጠቅላላ ጉባኤው የተካሄደውን ድንገተኛውን ምርጫ ተከትሎም የቀድሞው ፕሬዚዳንት አቶ አበባው… “መፈንቅለ ሥልጣን” ተካሂዶብኛል ያሉ ሲሆን ሂደቱ ከፓርቲው ደንብ ውጪ ነው ሲሉም ተቃውመውታል፡፡ አዲሱ ፕሬዚዳንት አቶ ማሙሸት አማረስ ምን ይላሉ? የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ፤ አወዛጋቢውን ምርጫ ጨምሮ ለአራት ዓመት ስለታገዱበት ሁኔታ፣ ስለ እርቁ፣ ፓርቲው ስላለበት አቋምና ተያያዥ ጉዳዮች በተመለከተ አቶ ማሙሸትን በፅ/ቤታቸው አነጋግሯቸዋል፡፡


ከፓርቲው መተዳደሪያ ደንብ አንፃር በቅርቡ በተካሄደው ጠቅላላ ጉባኤ አዲስ ፕሬዚዳንት መመረጡ አግባብ ነው?
በመጀመሪያ ደረጃ የአቶ አበባውን ስልጣን ካየን፣ በህግ የመኢአድ ፕሬዚዳንት አይደሉም፡፡ ያልሆኑበት ምክንያት ሐምሌ 13 እና 14 ቀን 2005 ዓ.ም ተደረገ የተባለው ጠቅላላ ጉባኤ ኮረም አልተሟላም፡፡ ይህንንም መላው የጉባኤው ተሳታፊዎች በፊርማቸው አረጋግጠዋል፡፡ ከዚያም ምርጫ ቦርድ፤ “በምልአተ ጉባኤው ያልተመረጠ ፕሬዚዳንት ነው” ብሎ የአቶ አበባውን ፕሬዚዳንትነት ውድቅ አድርጓል፡፡ ህዳር 6 ቀን 2006 ዓ.ም ቦርዱ ለእነ አቶ አበባው ያለ ምልአተ ጉባኤ ምርጫ መካሄዱን በደብዳቤ አሳውቋቸዋል፡፡ እነሱ ግን “ምርጫ ቦርድ አያገባውም” ብለው በጋዜጦች ላይ ሲመላለሱበት ነበር፡፡
ከዚያም በኋላ ፓርቲው በህገ ወጥ መንገድ እየተጓዘ መሆኑን ጠቅሶ፣ ለ6 ጊዜ ያህል ደብዳቤ ፅፎላቸዋል፡፡ ሰኔ 26 ቀን 2006 ዓ.ም ደግሞ ቦርዱ ከማንም ፓርቲ ጋር ውህደትና፣ ጥምረት ማድረግም ሆነ በፓርቲው ማህተም መጠቀም እንደማይችሉ ጠቅሶ ደብዳቤ ፅፎላቸዋል፡፡ ሐምሌ 6 ቀን 2006 ዓ.ም ከአንድነት ፓርቲ ጋር ሊደረግ የነበረው የውህደት ስምምነት የቀረው በዚያ ምክንያት ነው፡፡
የምርጫ ቦርድን ትዕዛዝ ጥሰው እንዋሃዳለን ብለውም ነበር፤ ነገር ግን ቦርዱ ሐምሌ 29 ቀን 2006 ዓ.ም በፃፈው ደብዳቤ፤ “ይሄን ብታደርጉ በህግ እንጠይቃችኋለን” ብሎ ማስጠንቀቂያ ፅፎላቸዋል፡፡ ስለዚህ አቶ አበባው በቦርዱም ሆነ በፓርቲው ህገ ደንብ ስልጣን አልነበራቸውም፡፡
የአሁኑን ጠቅላላ ጉባኤ ጥሪ ያካሄዱት በ2003 ዓ.ም በተካሄደው ጠቅላላ ጉባኤ በሙሉ ድምፅ ተመርጠው የነበሩት ኢ/ር ኃይሉ ሻውል ናቸው፡፡ ይህ የተደረገበት ምክንያት ህጋዊ ሰውነት ያላቸው ፕሬዚዳንት እሳቸው ብቻ ስለነበሩ ነው፡፡ በ2003 ዓ.ም ሆነ በ2005ቱ ጠቅላላ ጉባኤ ላይ የነበሩት አባላት ተሟልተው መገኘታቸው ተረጋግጦ ነው የአሁኑ ጠቅላላ ጉባኤው የተደረገው፡፡ ይሄንንም ሁለት የምርጫ ቦርድ ታዛቢዎች ተገኝተው አረጋግጠዋል፡፡
እርስዎን ጨምሮ 14 ሰዎች ከ2003ቱ ጠቅላላ ጉባኤ በኋላ የታገዳችሁበት ምክንያት ምንድን ነው?
በወቅቱ የታገድነው በስህተት ነበር፡፡ በአቶ ያዕቆብ ለኬ የተቀዳሚ ም/ፕሬዚዳንትነት አመራረጥ ላይ ልዩነት በመፈጠሩ ነው፡፡ በወቅቱ በምክር ቤቱ ሳይቀርብና ውሳኔ ሳይሰጥበት አቶ ኃይሉ፤ “አቶ ያዕቆብን ተቀዳሚ ም/ፕሬዚዳንት አድርጌዋለሁ” አሉ፡፡ ይህንን ህገ ወጥ አካሄድ ነው በማለታችን፣ በተፈጠረ ችግር እኛን ከሰሱንና በፍ/ቤት እንድንታገድ ተደረገ፡፡ በፍ/ቤት ከታገድን በኋላ የዲሲፒሊን እርምጃ ተወስዶባችኋል የሚል የእግድ ደብዳቤ እንደገና መጣ፡፡ ይህንን የእግድ ደብዳቤ የተመለከተው ፍ/ቤቱ፤ “አንድ ሰው ሁለት ክስ ሊቀርብበት አይችልም” በማለት፣ የዲሲፒሊን እርምጃውን ውድቅ አደረገው፤ የቀረውን “ሁከት መፍጠር” የሚል ክስ “ሁከት የለም፤ ፓርቲው በመተዳደሪያ ደንቡ መሰረት እንዲተዳደርና ይህንንም ምርጫ ቦርድ እንዲያስወስን” ብሎ ፍ/ቤት ትዕዛዝ አስተላልፏል፡፡ ስለዚህ እኛ በዲሲፒሊንም ሆነ በፓርቲው ጠቅላላ ጉባኤ አልታገድንም፤ ይህም በፍ/ቤቱ ውሳኔ የተረጋገጠ ነው፡፡
ኢ/ር ኃይሉ “ፓርቲውን እንዳሻቸው የሚያሽከረክሩ አምባገነን ናቸው” በሚል ስትወቅሱ ነበር፡፡ አሁን እርቃችሁ በምን መሰረት ላይ የፀና ነው?
እኛ በመጀመሪያ ወደ እርቁ ስንመጣ ማዕከል ያደረግነው ድርጅታችንን ነው፡፡ ድርጅታችን አደጋ ላይ ነበር፡፡ አንደኛ ህጋዊ ሰውነት አልነበረውም፡፡ በየሁለት ዓመቱ መከናወን የነበረበት ጠቅላላ ጉባኤ ባለመካሄዱ ችግር ላይ ነበር፡፡ ሁለተኛው እርቃችን መሰረት ያደረገው መርህን ነው፡፡ መተዳደሪያ ደንባችን ምን ይላል? የሚለውን ቁጭ ብለን ነው የመረመርነው፡፡ አንድ ፕሬዚዳንት ሲመረጥ ምን ይላል? ፕሬዚዳንትን ጨምሮ ተቀዳሚ ም/ፕሬዚዳንት፣ ምክትሉና ፀሐፊው የሚመረጡት በጠቅላላ ጉባኤው ነው ይላል፡፡ ሌሎች የስራ አስፈፃሚዎችን ደግሞ ፕሬዚዳንቱ መርጦ ለላዕላይ ም/ቤቱ ያቀርባል፡፡ ላዕላይ ም/ቤቱ ለጠቅላላ ጉባኤው ያቀርብና ሹመቱ እንዲፀድቅለት ይጠይቃል ይላል፡፡ መተዳደሪያ ደንባችን ይሄን ይላል፡፡ ስለዚህ በወቅቱ የአቶ ያዕቆብ ልኬ አመራረጥ ስህተት ነበር፡፡ በኋላም ኢ/ር ኃይሉ ይሄን በሚገባ ተረድተውታል፡፡ እናምየኛ አካሄድ ልክ ነበር፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ተወያይተን ተስማምተን፣ ከኛም ሆነ ከእሳቸው ይልቅ ድርጅታችን እንደሚበልጥ ተማምነንበት በሙሉ ድምፅ እርቅ ተፈጸመ፡፡ እርቁ ደግሞ በእሳቸውና በኛ ብቻ አይደለም የተወሰነው፡፡ ከመላ ሃገሪቱ በመጡ የጉባኤው አባላት ነው፡፡ ከእሳቸው ጋር ከታረቅን በኋላ ሁለታችንም ወደ ጠቅላላ ጉባኤው ነው የመጣነው፡፡ ጉባኤው የፓርቲው የመጨረሻ አካል እንደመሆኑ፣ እርቁ መፈጸም አለበት ብሎ በአንድ ድምፅ ወስኗል፡፡
ኢ/ር ኃይሉ  ስህተታቸውን በሚገባ አምነው ተቀብለዋል ማለት ነው?
ያሳሳቷቸው ሰዎች ነበሩ፡፡ እሳቸው በወቅቱ ታመው ውጭ ሃገር ለህክምና ይመላለሱ ነበር፡፡ ያኔ አንዳንድ ሰዎች የሚሰጧቸው መረጃ የተሳሳተ ነበር፡፡ የተሳሳተ መረጃ መሆኑን ኋላ ላይ እሳቸውም አረጋግጠዋል፡፡ ለምሳሌ የፍ/ቤቱን ጉዳይ እኛ አሸንፈን እያለ፣ “ተሸንፈዋል” የሚል መረጃ ነበር የቀረበላቸው፡፡ እርቁ እስከሚፈፀም ድረስ ፍ/ቤቱ በኛ ላይ እንደወሰነ ነበረ የሚያውቁት፡፡ የፍ/ቤቱ ውሳኔ ሲነበብላቸው ግን በጣም ነው ያዘኑት፡፡ ምን ዓይነት ስህተት ውስጥ እንደከተቷቸውም ተረድተዋል፡፡ ስለዚህ እርቃችን በደምሳሳው የተካሄደ ሳይሆን ከአንድ ወር በበለጠ ሂደት ብጥር ተደርጎ የተስማማንበት ነበር፡፡
እናንተን ጨምሮ በርካቶች “መኢአድ ኢ/ር ኃይሉ በገንዘባቸው የሚያሽከረክሩት የግለሰብ አምባገነንነት የነገሰበት ፓርቲ ነው” በማለት ስትነቅፉ ነበር፡፡ አሁን የአቋም ለውጥ አድርጋችኋል ማለት ነው?
መኢአድ የህዝብ እንጂ የግለሰብ ድርጅት አይደለም የሚል እምነት አለኝ፡፡ ኢ/ር ኃይሉ ይሄን ድርጅት በሊቀመንበርነት ብዙ ዓመት መርተዋል፤ ምንም ጥርጥር የለውም፡፡ በገንዘባቸው ግን እንደፈለጉ አያሽከረክሩትም፡፡ እኛም እሳቸውም እኩል ድምፅ ነው ያለን፡፡  እንኳን አቶ ኃይሉ ቀርተው ማንም በገንዘብ፤ሊያሽከረክረው አይችልም፡፡ ለምን? መኢአድ ብዙዎች ዋጋ የከፈሉለት ድርጅት ነው፡፡ አቶ ኃይሉ ድርጅቱን በገንዘብ ሊረዱ ይችላሉ፤ ሌላውም ሊረዳ ይችላል፤ ያ ማለት ግን በገንዘብ ማሽከርከር አይደለም፡፡
አሁን ኢ/ር ኃይሉ አምባገነን አይደሉም ነው የምትሉት?
እሳቸው በወቅቱ ህመም ላይ ነበሩ፡፡ የሚነግሯቸውን ነው ይዘው የሚሄዱት፡፡ ስለዚህ ውሳኔዎች ሁሉ ትክክል አልነበሩም፡፡ አሁን ይሄን ተረድተዋል፡፡ አቶ ኃይሉ በአምባገነንነት የሚወስኑት ውሳኔ ስለሌለ እኮ ነው እኛ የተቃወምነው፡፡ ለዚህ ነበር “እርስዎም እኛም እኩል ድምፅ ነው ያለን” ያልነው፡፡ እሳቸውም በውይይት ያምናሉ፤ ግን ከፓርቲው ብዙ ጊዜ ሲርቁ የተነገራቸውን ነው ይዘው የሚሄዱት፡፡ ያኔ ያሳሳቷቸው ሰዎች አሁን በአጠገባቸው የሉም፡፡ ያ እውነት ስለነበረን ነው እንደዚያ ባለ ሂደት ውስጥ ያለፍነው፡፡
የፓርቲውን ገንዘብ አጥፍታችኋል የሚል ክስም ቀርቦባችሁ ነበር፡፡ እሱንስ በምን አግባብ ፈታችሁት?
ይሄ ጉዳይ በዚህኛው ጠቅላላ ጉባኤ ላይም ቀርቧል፡፡ በ2003 ዓ.ም በአይቤክስ ሆቴል ተካሂዶ በነበረው ጠቅላላ ጉባኤ ላይ የፋይናንስ አስተዳደር የነበሩት አቶ ማህተመ በኩረ፤ ስራ አስፈፃሚ ሆነው ስላልተመረጡና ስለጠፉ፣ ለአባላቱ አበል የሚከፍል ጠፍቶ ትልቅ ችግር ተፈጥሮ ነበር፡፡ ለሆቴሉ የሚከፈለውንና 30ሺህ ብር መጠባበቂያ ገንዘብ እኔና ዶ/ር ታዲዎስ ቦጋለ በፊርማችን፣ አቶ ያዕቆብ ልኬና አቶ ግርማ ነጋ ገንዘቡን በማውጣት፣ ክፍያው ሲፈፀም ገንዘቡ ስላልበቃ (የተጠየቀው የገንዘብ መጠን 256 ሺህ ብር ነው፤ ያወጣነው ግን 90 ሺ ብር ብቻ ነው) ሩቅ ላሉት እየጨመርን፣ ቅርብ ላሉት ደግሞ ከአበላቸው ላይ እየቀነስን፣ ዶ/ር በዛብህ ደምሴ ባሉበት ሰጥተናል፡፡ ይሄን ጉዳይ በአሁኑ ጠቅላላ ጉባኤ ላይም አረጋግጠናል፡፡ ሁለተኛ፤ በኦዲት ወቅት “ብዙ ገንዘብ መበላቱን አረጋግጠናል” ብለው ያወሩት ነገር አለ፤ በወቅቱ እኛ ከቢሮ እንዳንገባ ተደርገን፣ ዶ/ር ታዲዎስም በታሰሩበት ሰዓት ከፍ/ቤት ትዕዛዝ ውጭ የታሸጉ ቢሮዎችን ሰብረው ገብተው “ኦዲት አደረግን” ያሉት ነበር፤ ያ ተቀባይነት የለውም፡፡ ሌላው በመኢአድ ፅ/ቤት ውስጥ እነሱ ተበላ ያሉትን ያህል ብር ሊኖር አይችልም፡፡  በዚህኛው ጠቅላላ ጉባኤ ላይም ራሳቸው አቶ አበባው በጉባኤው ፊት ቆመው፣ “እነ አቶ ማሙሸትን በገንዘብ አምተናቸዋል፣ ስማቸውን አጥፍተናል ነገር ግን ባላደረጉት ነው የወነጀልናቸው፤ ባይሆን ኃይለኞች ናቸው” ብለዋል፡፡ ከዚያ በኋላ ነው ወደ ምርጫ የተገባው፡፡ ከምርጫው በኋላም እሳቸው ለጠቅላላ ጉባኤው ኃላፊነታቸውን መልቀቃቸውን የሚገልፅ ደብዳቤ ፅፈው የሄዱ ሲሆን ጠቅላላ ጉባኤውም ቆሞ አጨብጭቦ ነው የሸኛቸው፡፡
በፍ/ቤት የቀረበባችሁና አሸንፈናል ያላችሁት ክስ ምን ይዘት ነበረው?
የቀረቡብን ክሶች አምስት ናቸው፡፡ አንዱ ክስ ሁከት መፍጠር ነው የሚለው፤ ሁለተኛው የአቶ ኃይሉ ሻውልን መኪና መስበር፣ ሶስተኛው አሲድ መርጨት፣ አራተኛው ድብደባ ፈፅመዋል የሚል ሲሆን አምስተኛው በሃሰት ማህተም መጠቀም የሚሉ ናቸው፡፡ በሁከቱ ጉዳይም ሆነ አሲድ መርጨት በሚለው ፈፅሞ ማስረጃ ማቅረብ አልቻሉም፡፡ በተለይ አሲድ ረጩ በተባለው ጉዳይ አሲድ ተረጨበት የተባለው ግለሰብ ተመርምሮ፣ አሲድ እንዳልሆነ ተረጋገጠ፡፡ በዚህ የተከሰሱት ሰዎች ነፃ ወጡ፡፡ የአቶ ኃይሉን መኪና በተመለከተ ምስክር ጠፋ፡፡ ፍ/ቤቱም በሃሰት ነው የተከሰሱት ብሎ ክሱ ተዘጋ፡፡ ድብደባውን በተመለከተ ተደብድቧል የተባለው ዘበኛ ቀርቦ “አልተደበደብኩም፤ ክሰስ ስላሉኝ ነው የከሰስኩት” ብሎ ተናገረ፡፡ ፍ/ቤቱ በዚህ ክስም ነፃ ናችሁ አለ፡፡ ማህተም መጠቀም በሚለው ዶ/ር ታዲዎስና አቶ ግርማ ነጋ ተከሰሱ፡፡ የአራዳ ምድብ የመጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት፤ በአንድ ቀጠሮ ብቻ ዶ/ር ታዲዎስን 2 ዓመት ከ4 ወር፣ አቶ ግርማ ነጋን 1 ዓመት ከ8 ወር እንዲታሰሩ ፈረደባቸው፡፡ በይግባኝ ከፍተኛው ፍ/ቤት ከእያንዳንዳቸው እስር ላይ 6 ወር አነሳላቸው፡፡ ቀጥለንም ጉዳዩን ሰበር አደረስነው፤ ተከራካሪው እኔ ነበርኩ፤ አምስቱም ዳኞች የስር ፍ/ቤቶችን ውሳኔ ተችተው፣ ከክሱ ነፃ እንዲሆኑ አድርገዋል፡፡ ስለዚህ በአምስቱም ክሶች ነፃ ወጥተናል፡፡
ኢ/ር ኃይሉ በጠቅላላ ጉባኤው ላይ ተፅዕኖ ፈጥረው፣ እናንተን ከውጪ አምጥተው አስመርጠዋል የሚሉ  ወገኖች አሉ፡፡ ኢ/ር ኃይሉ በጠቅላላ ጉባኤው ላይ የነበራቸው ሚና ምንድን ነው? ያንንስ ሚና በምን አግባብ አገኙ?
እኛ ከውጪ የመጣን አይደለንም፣ ለዚህ ፓርቲ ከማንም በላይ መስዋዕትነት የከፈልን ሰዎች ነን፡፡ እግድ የተባለውም በፍ/ቤት ተሽሯል፡፡ ከፍ/ቤት በላይ ማንም ሊመጣ አይችልም፤ ይሄ ጠቅላላ ጉባኤ የተጠራበት ዋናው ምክንያት የኛን ጉዳይ ለማየት ነው፡፡ አቶ ኃይሉ በ2003 በተካሄደው ጠቅላላ ጉባኤ ላይ እኛ ራሳችን በሙሉ ድምፅ የመረጥናቸው ፕሬዚዳንታችን ናቸው፡፡ እኛ አካሄዱን ነው እንጂ የተቃወምነው ፕሬዚዳንት መሆናቸውን አንጠራጠርም፡፡ አሁን ያንን ሚናቸውንና ኃላፊነታቸው ነው የተወጡት፡፡ እስከ ጥቅምት 30 ቀን 2007 ዓ.ም የፓርቲው ህጋዊ ፕሬዚዳንት ኢ/ር ኃይሉ ነበሩ፡፡ የ2005ቱ ጠቅላላ ጉባኤ ህጋዊ ሰውነት ስለሌለው ማለት ነው፡፡ በዚህ ኃላፊነታቸው ይሄኛውን ጠቅላላ ጉባኤ ጠርተዋል፡፡ መድረኩን የመሩትም በፕሬዚዳንትነት ኃላፊነታቸው ነው፡፡ ምርጫው የተካሄደውም እሳቸውን የሚተካ ፕሬዚዳንት ለመምረጥ ነበር፡፡ ነገር ግን አቶ አበባው እንዲወዳደሩ ሲጠየቁ፣ አስቀድመው ደብዳቤ አዘጋጅተው ተራ አባል እሆናለሁ ብለው ከውድድሩ ጥለው ወጡ፡፡ ኢ/ር ኃይሉም ሆኑ እኛ አቶ አበባውን ከጉባኤው  ገፍተን አላስወጣንም፤ ውድድሩ ነፃ ነበር፡፡
አቶ አበባው መኢአድን ከአንድ ዓመት በላይ ሲመሩ ቆይተው “ፓርቲው በፕሬዚዳንትነት አያውቃቸውም” ስትሉ ምን ማለታችሁ ነው?
ምርጫ ቦርድ እስከ ጥቅምት 30 ቀን 2007 ዓ.ም በፕሬዚዳንትነት የሚያውቃቸው አቶ ኃይሉ ሻወልን ነው፡፡ አቶ አበባው ኮረም ባልሞላ ጉባኤ የተመረጡ ሰው ናቸው፡፡ የጥቅምት 30 ጠቅላላ ጉባኤ አብላጫው አያውቃቸውም፡፡ ስለዚህ እሳቸው የመኢአድ ህጋዊ ፕሬዚዳንት አልነበሩም ማለት ነው፡፡ ኢ/ር ኃይሉም ቢሆኑ የጀርባ ተልዕኮ  ይዘው የመጡ አይደሉም፡፡ በወቅቱ ስልጣናቸው ስለሚፈቅድላቸው ነው መድረኩን የመሩትም ሆነ ጉባኤውንም የጠሩት፡፡ ሃቁ ይሄ ነው፡፡
ኮረም አልሞላም ሲሉ …
ኮረም አልሞላም ሲባል መገኘት የነበረባቸው የጠቅላላ ጉባኤ አባላት በአብላጫ ቁጥር አልተገኙም ማለት ነው፡፡ ኢ/ር ኃይሉ የ2005 ጠቅላላ ጉባኤ በምርጫ ቦርድ ውድቅ መሆኑን እርቁ እስከሚፈፀምበትና የመኢአድና አንድነት ውህደት እስኪደናቀፍ ድረስ አያውቁም ነበር፡፡ የአቶ አበባው ካቢኔ ህጋዊ እንደሆነ ነበር የተነገራቸው፡፡ ሃቁን ተደብቀዋል፡፡ እኛ ያንን ነው አንጥረን ያወጣነው፡፡ አቶ ኃይሉም በዚህ መሰረት ነው ግዴታቸውን የተወጡት፡፡
ኢንጂነር ኃይሉ የፓርቲው የበላይ ጠባቂ ናቸው የሚለው ነገር እንዴት ነው?
እሱ በ2005 የተፈጠረ ነገር ነው፡፡ መኢአድ የበላይ ጠባቂ የሚባል ነገር የለውም፡፡ መተዳደሪያ ደንባችን ላይም የለም፡፡ ከየት እንደመጣም አናውቅም፡፡ አሁን ከሌሎች ሰዎች ጋር ሆነው የፓርቲው አማካሪ ሆነዋል፡፡ የበላይ ጠባቂ የሚለውን ግን አናውቀውም፡፡ መተዳደሪ ደንባችን ላይም ፓርቲው የበላይ ጠባቂ ይኖረዋል የሚል የለም፡፡ የምንተዳደረው ግንቦት 1 ቀን 2001 በተደረገው ጠቅላላ ጉባኤ ላይ በፀደቀው ደንባችን ነው፡፡
ወደ ጉባኤው ከፍተኛ ደጋፊ ይዛችሁ በመግባት ሁለት ዓመት በተራ አባልነት እንድትገመገሙ የተወሰነውን ውሳኔ በማፈን ነው ወደ ስልጣን የመጣችሁት የሚል ወቀሳም ቀርቦባችኋል …
ይሄ ቀልድም ይመስላል፡፡ እኛ ትልልቅ ሰዎች ነን፡፡ እርቅ ምን እንደሆነና የጠቅላላ ጉባኤ ውሳኔ ምን እንደሆነ እናውቃለን፡፡ ምንም ይሁን ምን የሚወሰንብንን ለመቀበል ተዘጋጅተን ነው የገባነው፡፡ በሌላ በኩል ቲፎዞ (ደጋፊ) ይዘው ገብተው ነው የሚባለው፣ አንደኛ በጉባኤው መገኘት የሚችሉት የጠቅላላ ጉባኤ አባላት ብቻ ናቸው፡፡ በውድድር ደግሞ ደጋፊ አብዝተህ እንዲመርጥህ ማድረግ አንዱ የዲሞክራሲ መርህ ነው፡፡ ግን እኛ አንድም ሰው እንዲመርጠን አልጠየቅንም፡፡ ነገር ግን እነሱ አራት ዓመት ሙሉ ሲሉ የቆዩትና እኛ ቀርበን ስናስረዳ እውነቱ ስለወጣ ነው ሚዛኑ የተለየው፡፡ እኛ ሁለቱንም ቀን ምንም ሳንናገር ቆይተን ነው በሶስተኛው ቀን እንድንናገር የተደረገው፡፡
አቶ አበባውም ያኔ ነው ስለኛ በገንዘብ አለመታማት የመሰከሩት፡፡ ህዝቡም አጨብጭቦ ነው እውነቱን የተቀበለው፡፡     
ቀጣዩ ምርጫ ሊካሄድ ስድስት ወር ብቻ በቀረበት ወቅት ፓርቲው በእንደዚህ ያለ ሁኔታ ውስጥ መሆኑ አሉታዊ ተፅዕኖ ያሳድራል የሚል ስጋት የላችሁም?
ውሳኔ የሚሰጠው ህዝብ ነው፡፡ ለምርጫም የምንቀሰቅሰው ህዝቡን እንጂ እነ አቶ አበባውን አይደለም፡፡ አሁን እነሱ እየሰጡት ያለው መግለጫ ምንም ጥርጥር የለውም ይቆማል፡፡ መኢአድ ለሁለትና ለሶስት አካል አይገዛም፡፡ ህጋዊ አካል ሊሆን የሚችለው አንድ ወገን ብቻ ነው፡፡ ቦርዱም ይሄንን የሚታገስበት ሁኔታ አይኖርም፡፡
 በዚህ ጠቅላላ ጉባኤ የመጀመሪያ ተደሳች ቦርዱ ነው የሚል እምነት አለን፡፡ ኢ/ር ኃይሉ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲጠሩ ያሳሰበውም ቦርዱ ነው፡፡ እሳቸው ባይጠሩ ኖሮ፣ እኛ ባሰባሰብነው የ300 ጠቅላላ ጉባኤ አባላት ፊርማ ጉባኤው ሊጠራ ይችል ነበር፡፡ በዚህ ምክንያት ቦርዱ የአሁኑን ጠቅላላ ጉባኤ ህጋዊ ሰውነት እንደሚያረጋግጥ እርግጠኛ ነኝ፡፡ ምርጫን በተመለከተ አሁንም በመላ ሀገሪቱ መዋቅራችን  ሰፊ ነው፡፡ ወደ ምርጫው ለመግባትም ሆነ ተወዳዳሪ ለመሆን በኛ አደረጃጀት የምንቸገርበት ነገር አይኖርም፡፡ ጊዜ ስላለንም ለዝግጅት ይበቃናል፡፡
ከአንድነት ጋር የተጀመረው ውህደት የሚቀጥል ይመስልዎታል?
እስካሁን ሰነዶች እጃችን አልገቡም፡፡ ከአንድነት በኩልም አላገኘንም፡፡ ፓርቲው በ9 ፓርቲዎች በተመሰረተ “ትብብር” ውስጥም አለበት ተብሏል፡፡ ስለሱም አናውቅም፤ ወደፊት ሰነዶች አይተን የምንወስንበት ይሆናል፡፡
መኢአድን የሚመሩት ከአንድ ብሄር የሚወከሉ፤ ባስ ሲልም እርስዎን ጨምሮ የሰሜን ሸዋ አካባቢ ሰዎች ብቻ ናቸው የሚል ቅሬታ ይሰማል፡፡ በዚህ ላይ ያለዎት አስተያየት ምንድን ነው?
በመጀመሪያ ደረጃ  የመኢአድ ፕሬዚዳንትነት አመራረጥ ሂደት፣ ዘርንና ቋንቋን መሰረት ያደረገ አይደለም፡፡ ዘርና ቋንቋን መሰረት ካደረግን በቀጥታ የዚህን መንግስት የፌደራሊዝም አወቃቀር ተከተልን ማለት ነው፡፡ ከዚህ ስርዓት የሚለየው የመልክአ ምድራዊ አቀማመጥ፣ የህዝብ አሰፋፈርና የኢኮኖሚ ፍሰትን መሰረት ያደረገ በመሆኑ ነው፡፡
ፕ/ር አስራት ወልደየስ የተመረጡት በችሎታቸው ነው፡፡ አቶ ኃይሉንም ከቀረቡት 23 ሰዎች ውስጥ በትምህርትና በአመራር ብቃት ተብሎ ህዝቡ በአንድ ድምፅ ነው የመረጣቸው እንጂ በሰሜን ሸዋነታቸው አይደለም፡፡ አቶ አበባው ለምሳሌ ከጎጃም የመጡ ናቸው፡፡ ጎጃሜነታቸውን መሰረት ያደረገ ምርጫ አልነበረም፡፡
አሁንም ተቀዳሚ ም/ፕሬዚዳንቱ የአሩሲ ሰው ናቸው፣ ም/ፕሬዚዳንቱ ከሳውላ ጎት ናቸው፡፡ እኔም በፕሬዚዳንትነት ስመረጥ በሰሜን ሸዋ ተወላጅነቴ አይደለም፡፡
መንደርን መሰረት አድርጎ የሚነሳ ዘረኝነት ከቀጠለ፣ ትልቋን ሃገራችንን እንረሳታለን፡፡ ይሄ ቋንቋን መሰረት ያደረገው ፌደራሊዝም ያመጣው ጣጣ ነው፡፡ እኔ ከአቶ አበባው በላይ ለዚህ ድርጅት ዋጋ ከፍዬበታለሁ፡፡ በዚህ በኩል ምንም ጥርጥር የለውም፡፡
አንዱ የፕሬዚዳንትነት መስፈርት፣ እጩው በድርጅቱ ውስጥ የከፈለው መስዋዕትነትና ቆይታ ነው፡፡ ምርጫው የሚካሄደው በዚያ መሰረት እንጂ በተወለድንበት አካባቢ አይደለም፡፡ መኢአድ የሁሉም ኢትዮጵያዊ ቤት ነው፡፡

በአምስት ወጣቶች ተደፍራ ህይወቷ ያለፈው ታዳጊ ሃና ላላንጎ ጉዳይ ከፍተኛ ቁጣን የቀሰቀሰ ሲሆን በተለያዩ የመገናኛ ብዙሀናትን

በአምስት ወጣቶች ተደፍራ ህይወቷ ያለፈው ታዳጊ ሃና ላላንጎ ጉዳይ ከፍተኛ ቁጣን የቀሰቀሰ ሲሆን በተለያዩ የመገናኛ ብዙሀናትን ማህበራዊ ድረገፆች ላይ ድርጊቱን የፈፀሙት ግለሰቦች ተይዘው የሀገሪቱ ህግ ያስቀመጠው ከፍተኛ ቅጣት በአፋጣኝ እንዲፈረድባቸው እየተጠየቀ ነው፡፡
በተለያዩ ማህበራዊ ድረገፆች፤ “ፍትህ ለሃና” የሚል ንቅናቄ የተጀመረ ሲሆን በተለይ ተጠርጣሪዎቹ ረቡዕ ህዳር 10 ቀን 2007 ዓ.ም ፍርድ ቤት ቀርበው “ድርጊቱን የፈፀምነው እኛ አይደለንም፣ ለፖሊስ ድርጊቱን ፈፅመናል ብለን ቃል የሰጠነው ተገደን ነው ፈፃሚዎችን እንጠቁም” ማለታቸውን ተከትሎ የፍትህ አካላት ለጉዳዩ ትኩረት እንዲሰጡ የሚጠይቁ ወገኖች ተበራክተዋል፡፡
በጉዳዩ ላይ አስተያየት የጠየቅናቸው የህግ አማካሪና ጠበቃ አቶ ጳውሎስ ተሰማ እንዳብራሩልን፤ በወንጀለኛ መቅጫ ህግ በአንቀፅ 620 ንኡስ ቁጥር 1 መሰረት፤ “በግብረስጋ ግንኙነት ነፃነት እና ንፅህና ላይ የሚፈፀም ወንጀሎች” ብሎ በአስገድዶ መድፈር ርእስ ስር “ማንም ሰው ሀይል በመጠቀም ወይም በብርቱ ብቻ የሚፈፀም ድርጊት ወይም ህሊናዋን እንድትስት በማድረግ ወይም በማናቸውም መንገድ እራሷን መከላከል እንዳትችል በማድረግ ከጋብቻ ውጪ አስገድዶ ከአንዲት ሴት ጋር ግብረ ስጋ ግንኙነት የፈፀመ እንደሆነ ከ5 ዓመት እስከ 15 ዓመት በሚደርስ ፅኑ እስራት ይቀጣል” የሚል ሲሆን በአንቀፅ 620 በንዑስ ቁጥር 2 ላይ እድሜዋ 18 ዓመት ባልሞላት ሴት ልጅ ላይ የአስገድዶ መድፈር በሚፈፀምበት ጊዜ የግል ተበዳይ በተከሳሹ ቁጥጥር ስር በምትገኝበት ወይም በሱ ጥገኛ በሆነች ጊዜ ቅጣቱ ከ5 ዓመት እስከ 20 ዓመት ድረስ ይሆናል፡፡
ታዳጊዋን ለስራ የተሰማሩ መስለው ሲንቀሳቀሱ በታክሲው ተሳፍራ በቁጥጥራቸው ስር እንድትሆን በማድረግ ወንጀሉን በህብረት የፈፀሙባት በመሆኑ ቅጣቱ ከ5 ዓመት እስከ 20 አመት ይደርሳል፡፡ አስገድዶ መድፈሩ በተበዳይ ላይ የሞት አደጋ ያስከተለ እንደሆነ ከላይ በጠቀስነው የወንጀለኛ መቅጫ ህግ፤ ቅጣቱ እድሜ ልክ እስራት ይሆናል፤” ያሉት ጠበቃው፤ “በታዳጊዋ ላይ የተፈፀመው ወንጀል ከአንድ በላይ በመሆን ጭካኔ በተሞላ ሁኔታ በቁጥጥራቸው ስር በምትገኘው ለአቅመ አዳም ያልደረሰች ልጅ ላይ በመሆኑ በዕድሜ ልክ እስራት ይቀጣሉ” ብለዋል፡፡ ተደራራቢ ቅጣቶች አቃቤ ህግ ከከፈተ ቅጣቱን ሊያከብደው ይችላል፤ ነገር ግን የአስገድዶ መድፈር ህግ ላይ ከእድሜ ልክ እስራት በላይ የተቀመጠ ነገር የለም ሲሉ አስተያታቸውን ሰጥተዋል፡፡
በሌላ በኩል የኢፌዲሪ ሴቶች ህፃናትና ወጣቶች ጉዳይ ሚኒስቴር በጉዳዩ ላይ በሰጡት መግለጫ፤ ድርጊቱን የፈፀሙትን ግለሰቦች ለፍርድ ለማቅረብ ጠንክሮ እንደሚሰራ አስታውቆ፤ በሰብአዊ ፍጡር ላይ ኢ-ሰብአዊ ጥፋት የሚፈፅሙ የሰው አራዊቶች ከህግ በላይ አይሆኑም ብሏል፡፡
አየር ጤና በሚገኘው ታይምስ ኢንተርናሽናል ትምህርተ ቤት የ10ኛ ክፍል ተማሪ የነበረችው የ17 ዓመት ታዳጊ ሀና ላላንጎ፤ አየር ጤና በተለምዶ ሳሚ ካፌ ተብሎ ከሚጠራው አካባቢ በሚኒባስ ተሳፍራ ወደ ጦር ኃይሎች መስመር በመሄድ ላይ እንዳለች በሚኒባሱ ውስጥ በነበሩ አምስት ወንዶች ታፍና ተወስዳ፣ በተፈፀመባት አስገድዶ መድፈር በደረሰባት ከፍተኛ ጉዳት በዘውዲቱ መታሰቢያ ሆስፒታል ህክምና በመከታተል ላይ ሳለች ህይወቷ ማለፉ የሚታወስ ሲሆን ድርጊቱን ፈፅመዋል የተባሉት ተጠርጣሪዎች ፍርድ ቤት ቀርበው ድርጊቱን አልፈፀምንም ብለው ክደዋል፡፡ ፍ/ቤትም ጉዳዩን ለህዳር 22 ቀን 2007 ዓ.ም ቀጥሯል፡፡

Published in ዜና

“የመንግስት ሚዲያዎች የአቅም ውስንነትና የህግና ሥነ-ምግባር ጥሰት ይታይባቸዋል” አፍራሽ ዘገባዎችን የሚያሰራጩ ህትመቶች ከድርጊታቸው እንዲታቀቡና እንዲታረሙ ጥረት ቢደረግም ለውጥ ሊመጣ አልቻለም ያለው የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለስልጣን፤ አሳታሚዎቹን ለህግ ለማቅረብ መረጃዎች ተጠናቅረው ለሚመለከታቸው አካላት እንደተላለፈ ገለፀ፡፡ ህትመቶቹ ከገንቢነት ይልቅ የአፍራሽነት ሚናን ይዘው የሚሰሩ ናቸው ብሏል ባለስልጣኑ፡፡
ብሮድካስት ባለስልጣን ባለፈው ሳምንት ለተወካዮች ምክር ቤት ባቀረበው ሪፖርት  እንደገለፀው፤ የግል ህትመት ሚዲያዎች ከአደረጃጀታቸው ጀምረው አብዛኛዎቹ በኃላፊነት መንፈስ እየሰሩ የንግድ ዓላማቸውን ለማሳካት ሳይሆን የፖለቲካ ዓላማና ፍላጎትን ያለሙ ናቸው፡፡ አብዛኛዎቹ ህትመቶች በአገሪቱ የልማትና የመልካም አስተዳደር እንቅስቃሴ ውስጥ ከገንቢነት ይልቅ የአፍራሽነት ሚናን የመጫወት አስተሳሰብ ይዘው እየሰሩም ይገኛሉ ተብሏል፡፡
 በባለስልጣኑ አመታዊ ሪፖርት ላይ ሚዛናዊ ዘገባዎችን በማቅረብ፣ ህብረተሰቡ በአገሪቱ ስለሚከናወኑት እንቅስቃሴዎች ትክክለኛ መረጃ እንዲያገኝ የበኩላቸውን ጥረት ያደርጋሉ ተብለው የተጠቀሱ ሚዲያዎች ሲኖሩ፣ አፍራሽ ዘገባዎችን የሚያሰራጩና የሚስተዋሉባቸውን ክፍተቶች ለማረም ፈቃደኝነት የሌላቸው የተባሉም በዝርዝር ተገልፀዋል፡፡ አፍራሽ ዘገባ የሚያሰራጩ ህትመቶች እንዲታረሙ ጥረት ቢደረግም የሚፈለገው ለውጥ እንዳልመጣ በሪፖርቱ ላይ ተጠቁሟል፡፡ ገንቢ ሚና የሚጫወቱት የህትመት ሚዲዎች በስርጭት ላይ ከመቆየት አኳያ የአከፋፋዮች ጫና እንዳለባቸው የጠቆመው ሪፖርቱ፤ አፍራሽ ዘገባ የሚያሰራጩት አብዛኞቹ በገበያ ውስጥ መቆየታቸው፣ የማይታወቅ የፋይናንስ ምንጭ እንዳላቸው የሚያመላክት በመሆኑ፣ የተጠናከረ የክትትልና የጥናት ሥራዎችን መስራት እንደሚያስፈልግ አመልክቷል፡፡
ባለስልጣኑ የመንግስት ብሮድካስት ሚዲያውን አስመልክቶ በሪፖርቱ ላይ እንደገለፀው፤ የመንግስት ብሮድካስት ሚዲያው ምንም እንኳን በብሮድካስት አዋጁ የተጣለበትን ኃላፊነትና በልማቱ በኩል የራሱን ሚና ለመወጣት ጥረት የሚያደርግ ቢሆንም በአቀራረቡና አጀንዳ ቀርፆ አስተሳሰብን በመገንባት ረገድ የአቅም ውስንነት እንዳለበትና አልፎ አልፎም የህግና የስነ ምግባር ጥሰቶች እንደሚስተዋልበት ተጠቁሟል፡፡
ሪፖርቱ የግል ብሮድካስት ሚዲያውን አስመልክቶ በሰጠው ማብራሪያ፤ በአመዛኙ የአየር ጊዜያቸውን ወሳኝ ባልሆኑ ጉዳዮች የሚያውሉና በልማቱ ውስጥ ማበርከት የሚገባቸውን አስተዋፅኦ ለማበርከት የአመለካከት ችግር ያለባቸው እንደሆኑ ጠቅሶ፤ የሙያ ክህሎት እጥረት እንደሚታይባቸውም ጠቁሟል፡፡ ባለስልጣኑ በተያዘው በጀት ዓመት አሉ የተባሉ ችግሮችን ለመቅረፍ የሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሰራም በሪፖርቱ ላይ አመልክቷል፡፡   

Published in ዜና
  • ሳያት በኢትዮጵያ ፊልም ታሪክ ከፍተኛ ተከፋይ ትሆናለች
  • ፊልሙን የሚቀርፀው የጀርመን የቴሌቪዥን ጣቢያ ነው

የታወቀ የጀርመን የፊልም ኩባንያ ከ20 ሚ. ብር በላይ በሆነ ወጪ “ዘ ኢትዮጵያን” የተሰኘ በኢትዮጵያ ላይ የሚያተኩር ፊልም ሊሰራ እንደሆነ የተገለፀ ሲሆን ዕውቋ ድምፃዊና ተዋናይት ሳያት ደምሴ ከታዋቂ የጀርመን ተዋናይ ጋር በፊልሙ ላይ በመሪነት ትተውናለች፡፡ ሳያት ደምሴ በኢትዮጵያ ፊልም ታሪክ ከፍተኛው ክፍያ እንደሚከፈላት የፊልሙ ዝግጅት አስተባባሪ ዮሐንስ ፈለቀ ለአዲስ አድማስ ገልጿል፡፡ በጀርመናዊው ደራሲ ሄንሪክ ሄዲንት የአጫጭር ልቦለዶች መድበል ውስጥ የተካተተው “The Ethiopian” የተሰኘው ታሪክ ወደ ፊልም እንደሚቀየር የታወቀ ሲሆን ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ በአገሪቱ ባህልና የአየር ፀባይ ተማርኮ እዚሁ በቀረ ጀርመናዊ እውነተኛ ታሪክ ላይ ያጠነጥናል ተብሏል፡፡
በፊልሙ ላይ ከሳያት ደምሴ በተጨማሪ አንጋፋዋ አርቲስት ሃና ተረፈና ሌሎች ኢትዮጵያውያን ተዋንያን እንዲሁም ሶስት ታዋቂ ጀርመናዊ ተዋንያን ይሳተፋሉ ተብሏል፡፡ “ሳያት ብቻ ሳትሆን ሌሎችም ኢትዮጵያውያን ተዋንያን ከፍተኛ ክፍያ ያገኛሉ” ብሏል - አስተባባሪው፡፡ የፊልሙ ዳይሬክተር ታዋቂው ጀርመናዊ ፈርዲናንድ ለኢራች ሲሆን ፊልሙን በመቅረፅ ዕውቁ የጀርመን ቴሌቪዥን ጣቢያ “ሙቪ ዘ አርት ኦፍ ኢንተርቴይንመንት”፣ በፕሮዱዩሰርነት ደግሞ “ኮንስትሬይን ፊልም ፕሮዳክሽን” እንደሚሳተፉ አስተባባሪው ገልጿል፡፡
ኢትዮጵያ የተሟላ መሰረተ ልማት (ኢንተርኔት፣ ደረጃውን የጠበቀ ሆቱል፣ የቀረፃ ቦታና ሌሎች) የሏትም በሚል ፊልሙ በኬንያ ሊሰራ እንደነበር የጠቆመው አስተባባሪው “እንዴት የኢትዮጵያ ታሪክ ላይ ያተኮረ ፊልም ኬኒያ ውስጥ ይሰራል” የሚል ከፍተኛ ሙግት ከተካሄደ በኋላ በኢትዮጵያ እንዲሰራ መወሰኑን ገልጿል፡፡ የፊልሙ ቀረፃ ከመጪው ሳምንት ጀምሮ በአዲስ አበባ፣ በድሬደዋና በሃረር እንደሚከናወን አስተባባሪው አክሎ ገልጿል፡፡   


Published in ዜና

የዋሽንግተን የጤና ዳይሬክተር ጆክሴል ጋርሺያ
የዋሽንግተን ዲሲ ከተማ የጤና ዲፓርትመንት ዳይሬክተር ጆክሴል ጋርሺያ በከተማዋ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ሌሎች አፍሪካውያን በኢቦላ ምክንያት እየተገለሉ እንደሆኑ ዘ ዋሽንግተን ታይምስ ዘገበ፡፡
ስለ ኢቦላ በቂ ግንዛቤ የሌላቸው የከተማዋ ነዋሪዎች፣ በተለይ በታክሲ ሾፌርነት በመስራት ላይ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንንና ሌሎች የአፍሪካ አገራት ዜጎችን እያገለሉ እንደሚገኙ የገለጹት ዳይሬክተሩ፤ አሽከርካሪዎቹ አፍሪካውያን እንደሆኑ ሲያረጋግጡ ቫይረሱን ያስተላልፉብናል በሚል ስጋት ከመኪና እንደሚወርዱ ተናግረዋል፡፡
የመገኛኛ ብዙሃን ሰራተኛ የሆነ አንድ ግለሰብ ኢትዮጵያውያንና ኤርትራውያን ወደ አሜሪካ ሲገቡ ለምን የኢቦላ ምርመራ አይደረግላቸውም የሚል ጥያቄ እንዳቀረበላቸው ያስታወሱት ዳይሬክተሩ፤ ከሁለቱ አገራት ዜጎች ጋር የእጅ ሰላምታ የማይለዋወጡ የከተማዋ ነዋሪዎች እንዳሉም ገልጸዋል፡፡
ዩኒቨርሳል ፒስ ፌዴሬሽን የተባለ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ባዘጋጀው ስብሰባ ላይ ተገኝተው ንግግር ያደረጉት ዳይሬክተሩ፤ የሌሎች የአፍሪካ አገራት ዜጎችም በዕለት ከዕለት እንቅስቃሴቸው በኢቦላ ሰበብ መገለል እንደሚደርስባቸው አስታውቀዋል፡፡
በዋሽንግተን ከሚኖሩ የሌሎች አገራት ዜጎች፣ ኢትዮጵያውያንና ኤርትራውያን ከፍተኛውን ቁጥር እንደሚይዙም ዘገባው ጨምሮ ገልጿል፡፡

Published in ዜና

በሽብር የተከሰሱት የአንድነት፣ የሰማያዊ፣ የአረና ፓርቲ አመራሮች እና ሌሎች ተከሳሾች፣ ያቀረቡት የዋስትና ጥያቄ ከትናንት በስቲያ በፍ/ቤት ውድቅ የተደረገ ሲሆን፤ አቃቤ ህግ የተጓደሉ ማስረጃዎችን አሟልቶ እንዲቀርብ ታዟል፡፡
ከወራት በፊት የታሰሩት ተከሳሾች፤ በዋስትና ከእስር እንዲለቀቁ ጥያቄያቸውን ፌደራል ከፍተኛ ፍ/ቤት የልደታ ምድብ 19ኛ ችሎት ማቅረባቸው የሚታወስ ሲሆን፤ የሁሉም ተከሳሾች ጥያቄ ተቀባይነት ሳያገኝ ቀርቷል፡፡ በአቃቤ ህግ ክስ ላይ የተጠቀሰው የወንጀል አንቀፅ የዋስትና መብትን የሚያስከለክል መሆኑን ፍ/ቤቱ ጠቅሶ፣ ሁሉም ተከሳሾች ጉዳያቸውን ማረሚያ ቤት ሆነው ይከታተሉ ሲል ብይን ሰጥቷል፡፡
በእለቱ ጠበቆች ከክሱ ጋር ተያይዘው አንዳንድ ማስረጃዎች ያልተሟሉ በመሆናቸው፣ ተሟልተው ከቀረቡልን በኋላ ነው የክስ መቃወሚያ ማቅረብ የምንችለው በማለታቸው ፍ/ቤቱ አቃቤ ህግ ለህዳር 17 ጎደሉ የተባሉትን የማስረጃ ዝርዝሮች አሟልቶ ያቅርብ ብሏል፡፡
የአንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ የነበሩት አቶ ሃብታሙ አያሌው፤ የፓርቲው የድርጅት ጉዳይ ምክትል ኃላፊ አቶ ዳንኤል ሺበሺ፣ የሰማያዊ ፓርቲ ምክር ቤት ምክትል ሰብሳቢ አቶ የሽዋስ አሰፋ እና የአረና ፓርቲ አመራር አቶ አብርሃ ደስታን ጨምሮ በአስር ሰዎች ላይ የሽብር ክስ የተመሰረተባቸው ጥቅምት 21 ቀን 2007 ዓ.ም ነው፡፡
አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የማስተርስ ተማሪ ዘላለም ወርቅአገኘሁን አንደኛ ተከሳሽ በማድረግ አቃቤ ህግ ያቀረበው መዝገብ፤ ተከሳሹ የግንቦት 7 አባል ነው ብሏል፡፡ ግንቦት 7 በመንግስት አሸባሪ ነው ተብሎ እንደተፈረጀ አቃቤ ህግ ጠቅሶ፣ ተከሳሹ ለግንቦት 7 ሰዎችን በመመልመል ወደ ኤርትራ ሄደው እንዲሰለጥኑ አድርጓል፤ ህገ መንግስታዊ ስርአቱንና ማህበራዊ ተቋማትን በሽብር ለማፈራረስ ተንቀሳቅሷል የሚል ክስ አቅርቧል፡፡ አራቱ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች ህጋዊ ፓርቲን እንደ ሽፋን ተጠቅመዋል በማለት አቃቤ ህግ ያቀረበው ክስ ደግሞ፤ ተከሳሾቹ ከግንቦት 7 አመራሮች ጋር በመገናኘትና በመመካከር የተለያዩ የሽብር ተልዕኮዎችን ተቀብለዋል የሚል ነው፡፡
በሌሎቹ ተከሳሾች ላይ የቀረበው ክስም የግንቦት 7 አባል በመሆን አላማውን ለማስፈፀም ተንቀሳቅሰዋል ይላል፡፡

Published in ዜና

            በ97 ዓ.ም እና የዛሬ አምስት አመት በተደረጉ ምርጫዎች ከመንግስት ጋር ክፉኛ የተወዛገበው የአውሮፓ ህብረት ታዛቢ ቡድን፤ ለዘንድሮው ምርጫ በታዛቢነት እንደማይጋበዝ የተገለፀ ሲሆን፤ ሰሞኑን የአውሮፓ አገራት ዲፕሎማቶች ምርጫውንና የፓርቲዎች እንቅስቃሴን በተመለከተ በየክልሉ እየተዘዋወሩ ማነጋገር ጀመሩ፡፡
በኢትዮጵያ ከፍተኛ እርዳታ በመስጠት የሚታወቀው የአውሮፓ ህብረት በምርጫ ታዛቢነት ባይጋበዝም፤ ከበርካታ ድሀ አገራት ጋር ባለው የትብብር ስምምነት መሰረት በፖለቲካ ጉዳዮች ዙሪያ ፓርቲዎችን ማወያየትና መረጃዎችን መሰብሰብ ይችላል ተብሏል፡፡
በተለያዩ ክልሎች በመዘዋወር የመንግስት ሃላፊዎችና የፓርቲ ተወካዮችን፣ ምሁራንና የሲቪል ማህበራት መሪዎችን ማነጋገር የጀመሩት የአውሮፕ ዲፕሎማቶች፤ በአዲስ አበባ ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝን እንዲሁም የታዋቂ ፓርቲ መሪዎችን በተናጠል አነጋግረዋል፡፡ ገዢው ፓርቲና ተቃዋሚዎች ለምርጫ እንዴት እየተዘጋጁ እንደሆነ፤ በየክልሉ ተቃዋሚዎች ቢሮ ለመክፈትና ለመንቀሳቀስ የሚያጋጥማቸው ችግር፣ የህግ አከባበርና የሰብአዊ መብት አጠባበቅ ጉዳዮች በዲፕሎማቶቹ ጉብኝት ላይ እየተነሱ እንደሆነ ታውቋል፡፡
የህብረቱ ዲፕሎማቶች፣ ወደ ኦሮሚያ ክልል ከተሞች ከሚያደርጉት የጥናት ጉብኝት ጋር በተያያዘ ከክልሉ ርዕስ መስተዳድር አቶ ሙክታር ከድርና በርካታ የኦህዴድ አመራሮች፤ ዶ/ር መረራ ጉዲናን ጨምሮ የኦፌኮ ተወካዮችን እንዲሁም የአንድነት አባላትን አነጋግረዋል፡፡
ከዚሁ ጐን ለጐን የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮች ከአውሮፓ ህብረት አምባሳደር ሸንታል ኸብረሻት ጋር እንዲተዋወቁ ተጋብዘው፣ የግንቦቱን  ምርጫ በተመለከተ አጭር ውይይት ማካሄዳቸውን ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡
የመኢአድ ፕሬዚዳንት አቶ ማሙሸት አማረ፤ ከአምባሳደሯ ጋር የትውውቅ ፕሮግራም ከተከናወነ በኋላ ምርጫው ህግንና ስርአትን ተከትሎ መካሄድ እንዳለበት መነጋገራቸውን ጠቅሰው፤ የአውሮፓ ህብረት በምርጫው ዙሪያ ከገዢው ፓርቲም ሆነ ከተቃዋሚዎች ጋር ተከታታይ ውይይት አደርጋለሁ ማለቱን ተናግረዋል፡፡
የመድረክ ሊቀመንበር ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ በበኩላቸው፤ ከአፍሪካ ህብረት የአፍሪካ ጉዳዮች ዳይሬክተር ጋር እንደተወያዩ ገልፀው፤ ነፃና ሚዛናዊ  ምርጫ የማካሄድና የመሳተፍ እድሉ ምን ያህል ነው? በሚለው ጉዳይ አጭር ውይይት አድርገናል ብለዋል፡፡ መድረክ በምርጫው ይሳተፍ እንደሆን ጥያቄ እንደቀረበላቸው ፕ/ር በየነ አስታውሰው፤ መድረክ ለምርጫው ሂደት ሲል ወደ ምርጫውና ሂደቱ ሊገባ ይችላል የሚል ምላሽ ሰጥተናል ብለዋል፡፡
ሰማያዊ ፓርቲን ጨምሮ ሌሎች ፓርቲዎችም ከህብረቱ ጋር በ2007 ዓ.ም ምርጫ ዙሪያ ውይይት ማድረጋቸውን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡
የአውሮፓ ህብረት በ1997 ዓ.ም እና በ2002 ዓ.ም ምርጫዎች ላይ በታዛቢነት ተጋብዞ ባወጣቸው ሪፖርቶች ከመንግስት ጋር መወዛገቡ የሚታወስ ሲሆን፤ በተለይ በ1997 ምርጫ የታዛቢ ቡድኑ መሪ የነበሩት አና ጎሜዝ ስለምርጫው ይፋ ባደረጉት ሪፖርት የአውሮፓ ህብረትና መንግስት ሆድና ጀርባ ሆነው ነበር፡፡

Published in ዜና
Page 7 of 19