በዓለም የሳቅ ንጉስ በላቸው ግርማ ባለቤትነት የሚመራው “ላፍተር ጀነሬት ቱ ኦል”፤ የስድስት ቀን የሳቅ ሽርሽር ወደ ሰሜን ኢትዮጵያ እንደሚያደርግ አስታወቀ፡፡ ከታህሳስ 15-20 በሚደረገው ጉዞ፣ ከአዲስ አበባ ተነስቶ መቀሌ፣አክሱም፣ላሊበላ፣ፅዮን ማርያም፣ጦሳ ተራራና ሌሎች የሰሜን ኢትዮጵያ ታሪካዊ ቦታዎች ይጎበኛሉ ተብሏል፡፡ የዘንድሮው “ኢትዮ የሳቅ ሽርሽር” ለሁለተኛ ጊዜ የሚካሄድ መሆኑን የጠቆመው የድርጅቱ መግለጫ፤ ሽርሽሩ “ሃገር በሃገር ልጅ ትልማ፣ትጎብኝ፣ስደት ይብቃ” በሚል መሪ ቃል የተዘጋጀ እንደሆነ ጠቁሟል፡፡

በገጣሚ ገነት ወንድሙ ተደርሶ ለንባብ የበቃው “ከውሽንፍር ኋላ” የተሰኘ የግጥም መድበል፤ ነገ ከቀኑ 11 ሰዓት ላይ በጣይቱ ሆቴል፣ ጃዝ አምባ ይመረቃል፡፡ በምረቃው ስነስርዓት ላይ ወጣትና አንጋፋ ገጣሚያን የግጥም ስራዎቻቸውን የሚያቀርቡ ሲሆን የጥበብ ወዳጆች በፕሮግራሙ ላይ እንዲታደሙ ተጋብዘዋል፡፡

የ 70 ወጣት ሰዓሊያንን ስራ ለተመልካች ይፋ ያደረገ የስዕል ኤግዚቢሽን ትላንት በ8 ሰዓት በጣይቱ ሆቴል ተከፈተ፡፡ “አርት ፌር” በሚል ርዕስ የተዘጋጀው አውደርዕይ፤ 500 የሚጠጉ ስዕሎችን ያካተተ ሲሆን  እስከ ነገ ማታ ድረስ ለተመልካች ክፍት ሆኖ እንደሚቆይ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ቀደም ሲል እንዲህ ዓይነት የስዕል ባዛር በተለያዩ ስፍራዎች የተዘጋጀ ቢሆንም በጣይቱ ሆቴል  ሲስተናገድ ግን የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው፡፡

Saturday, 14 December 2013 13:10

የማንዴላ ሌላኛው ገፅታ!

በአይሁዶች ሚሽናህ ውስጥ “በእድሜ ዘመኑ የሰዎችን ልብ ደስ ለሚያሰኝ መልካም ስራ የተጋ፣ እነሆ የሌሎችን ቀንበር የተሸከመ፣ ከእርሱም ታላላቆችና ታናናሾች ለሆኑ ለወንዶችም ለሴቶችም ጠዋት በሆነ ጊዜ እንደሚገኝ ብርሃን የሆነ፣ እርሱ በሞቱም እንኳ ቢሆን በአምላክና በሰዎች ዘንድ እጅግ ይከብራል፣ ወደ ላይም ከፍ ከፍ ይላል፡፡” የሚል ቃል ሰፍሮ ይገኛል፡፡ ይህ ቅዱስ ቃል በኔልሰን ማንዴላ ተፈጽሞ እነሆ በዘመናችን ለማየት በቅተናል፡፡
እንደ እውነቱ ከሆነ፣ መላ ደቡብ አፍሪካውያን ከፍ ባለ አክብሮትና ፍቅር “ማዲባ” እያሉ የሚጠሯቸው ኔልሰን ማንዴላ፤ በረጅሙ የትግል ህይወታቸው የፈፀሙት ስራ በመላእክት እንጂ በስጋ ለባሽ ሰው የሚፈፀም አይመስልም። የዘር መድልዎና የጭቆና አገዛዝ ቀንበር ተሸክመው፣ ወደር የሌለው ከፍተኛ መስዋዕትነት የከፈሉበት ያ ረጅሙና እጅግ አስቸጋሪው ጉዞአቸው ለዘመናት ሲገፋ ለኖረው ሰፊው ህዝባቸው፤ ከማለዳ ጀንበር በብዙ እጥፍ የደመቀ የነፃነትና የእኩልነት ብርሃን አብርቶላቸዋል፡፡
“የማይናወጥ ጽኑ እምነት ያለው ተራሮችን ማንቀሳቀስ ይችላል” ተብሎ በቅዱስ መጽሐፍ እንደተጠቀሰው፣ ለእኩልነትና ለአንድነት የነበራቸው መቼም የማይናወጥ ጽኑ እምነት፣ ቀናቶች ሁሉ እስኪያልቁ ድረስ ይገረሰስ የማይመስለው የአፓርታይድ የዘር መድልዎና የጭቆና አገዛዝ፣ እግራቸው ስር አይሆኑ ሆኖ እንዲፈረካከስ አድርጐታል፡፡
ከመላእክት እንጂ ከሰው ልጆች መቸም ቢሆን እንዲህ እንደዋዛ በማይገኘው እፁብ ድንቅ ርህራሄአቸውና ፍፁም ይቅር ባይነታቸው፣ ከዚህ በፊት የትም ታይቶና ተሰምቶ በማይታወቅ ሁኔታ፣ የህዝባቸውን የደቡብ አፍሪካውያንን ብቻ ሳይሆን ድፍን የአለማችንን ህዝብ ከሊቅ እስከ ደቂቅ፣ በከፍተኛ ፍቅርና አክብሮት መማረክ ችሏል፡፡ እነሆ በሞታቸውም ጊዜ ቢሆን በአምላካቸው ፊት በእጅጉ ተከብረው፣ በሰው ልጆች ዘንድም  አቻ በሌለው ከፍተኛ ፍቅርና ክብር እንደ ንስር ወደ ላይ፣ ወደ ሰማይ ከፍ፣ እጅግ ከፍ ብለዋል፡፡ ለዘጠና አምስት አመታት ያህል የዘለቀው የኔልሰን ማንዴላ ረጅም የትግል ህይወት፤ በችግርና በፈተና፣ በጽናትና በአይበገሬነት፣ በውድቀትና በድል ታሪኮች የተሞላ ነው ብሎ በቀላሉ መናገር ምናልባት የአንባቢን ንቃተ ህሊና አሳንሶ እንደመገመት ሊቆጠር ይችላል፡፡ ምክንያቱም የእሳቸው የህይወት ታሪክ እንደነዚህ ባሉ ታሪኮች የተሞላ መሆኑን ድፍን አለሙ በሚገባ ያውቀዋልና፡፡  
ኔልሰን ማንዴላ፤ በአፓርታይድ አገዛዝ የእድሜ ልክ እስራት ተበይኖባቸው ሮቢን ደሴት በሚገኘው ጥብቅ ወህኒ ቤት ውስጥ ለሀያ ሰባት አመታት በእስር የማቀቁት የቀለም ትምህርት አሊያም የሙያ ክህሎት ስልጠና በመውሰድ ሳይሆን የኖራ ማዕድን በመቆፈር ነበር፡፡ ይህም ለተለያዩ የእፎይታና የመተንፈሻ አካላት በሽታ በከፍተኛ ሁኔታ አጋልጧቸዋል፡፡ ከሀያ ሰባት አመታት አስከፊ የእስር ቅጣት በሁዋላ ተፈተው፣ የሮቢን ደሴት ወህኒ ቤትን ለቀው ሲወጡ፣ ሳምባቸው በኖራ ብናኝ ክፉኛ ተጎድቶ በከፍተኛ የመተንፈስ ችግር እየተሰቃዩ ነበር፡፡ ይህም ብቻ አልነበረም፡፡ እስር ቤት ከገቡ ከአስራ አራተኛው አመት ጀምሮ ህይወታቸው እስካለፈበት ቀን ድረስ የእንባ አመንጪ እጢያቸው በኖራና በአስቤስቶስ ብናኝ ሙሉ በሙሉ በመጎዳቱ፣  ስሜታቸውን እንባ አውጥተው በማልቀስ መግለጽ አይችሉም ነበር፡፡
የቀድሞው የኬጂቢ ኮሎኔል፣ የዛሬው የራሺያ ቆፍጣና ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን፤ ስለ ራግቢ ጨዋታ የፈለገውን ያህል ቢያወሯቸው ጨርሶ አይሞቃቸውም አይበርዳቸውም። የጂዶ ጨዋታን ነገር ካነሱላቸው ግን መላ ስሜታቸው የሚነቃውና ሰውነታቸውን የሚነዝራቸው ከመቅጽበት ነው።
የሩዋንዳው ፕሬዝዳንት ፖል ካጋሜም የቅርጫት ኳስ ጨዋታ ነፍሳቸው ነው፡፡ አደባባይ ወጥተው ሲጫወቱ አይታዩ እንጂ የእረፍት ጊዜአቸውን በአብዛኛው የሚያሳልፉት ከመኖሪያ ቤታቸው ግቢ ውስጥ ከልጃቸው ጋር ነጭ ላብ እስኪያልባቸው  ድረስ የቅርጫት ኳስ በማልፋት ነው፡፡ እርግጥ ነው ማዲባ እንደ ቭላድሚር ፑቲን ጂዶ ሲታገሉ ወይንም እንደ ፖል ካጋሜ በመኖሪያ ቤታቸው ግቢ ውስጥ ከልጆቻቸውና ከልጅ ልጆቻቸው ጋር የቅርጫት ኳስ ሲጫወቱ ታይተው አያውቁም፡፡ ልጫወት ቢሉም የማያወላዳው ጤናቸው፣ ከተጫጫናቸው እርጅና ጋር ተዳምሮ ይህን መሰሉን እድል እንዳልሰጣቸው ይታወቃል። ይሁን እንጂ ሀገራቸው የአፍሪካና የአለም የእግር ኳስ ዋንጫ እንዲሁም የራግቢ የአለም ዋንጫ ውድድሮችን እንድታዘጋጅ ያደረጉት ጉልህ አስተዋጽኦ፣ አዘጋጅ ከሆነች በኋላም የሀገራቸውን ብሔራዊ የእግር ኳስና የራግቢ ቡድን ማሊያ ለብሰው ውድድሩ በሚካሄድበት ስታዲየም በመገኘት የሰጡት የሞቀ ድጋፍ፣ ብዙዎች ማንዴላ የእግር ኳስና የራግቢ ስፖርት ቅልጥ ያለ ደጋፊ ናቸው ብለው እንዲገምቷቸው አድርጓል፡፡
እውነቱ ግን ይህ አይደለም፡፡ ኔልሰን ማንዴላ የእግር ኳስም ሆነ የራግቢ ጨዋታ አድናቂ አልነበሩም፡፡ እርሳቸው የሚወዱትና የሚያደንቁት የስፖርት አይነት ቦክስና የረዥም ርቀት የሩጫ ውድድሮችን ብቻ ነበር፡፡ ሀያ ሠባት አመታትን ባሳለፉበት የሮቢን ደሴት ወህኒ ቤት ውስጥ ኖራና አስቤስቶስ ለመቆፈር ዶማና አካፋቸውን ይዘው ከመውጣታቸው በፊት ዘወትር ጧት ጧት የቦክስ ልምምድ ያደርጉ ነበር፡፡
“ረዥሙ የነፃነት ጉዞ” በሚል ርዕስ ባሳተሙትና የህይወት ታሪካቸውን በተረኩበት መጽሀፍ ውስጥ የቦክስ ስፖርትን ሲገልፁ “የቦክስ ስፖርት ሳይንሱ እንጂ ድብድቡ አዝናንቶኝ አያውቅም፡፡ አንዱ ራሱን ለመከላከል እንዴት ሰውነቱን እንደሚያንቀሳቅስ፣ ሌላው ደግሞ ለማጥቃትና ለመከላከል እንዴት ያለ ስትራተጂ እንደሚጠቀም፣ አንዱ ሌላኛውን እንዴት እንደሚቀድመው ሳይ ግን በጣም እገረም ነበር” በማለት ጽፈዋል፡፡
ለኔልሰን ማንዴላ የቦክስ ስፖርት ከዚህ ያለፈ ሌላ ትርጉምም ነበረው፡፡ ይህንንም በመጽሃፋቸው እንዲህ በማለት ገልፀውታል:- “የቦክስ ስፖርት ነፃና ዲሞክራሲያዊ ነው፡፡ በቦክስ ሪንግ ውስጥ ማዕረግ፣ እድሜ፣ ቀለምና ሀብት ምንም ቦታ የላቸውም፡፡ ፖለቲከኛ ከሆንኩ በኋላ የምሬን ተቧቅሼ አላውቅም፡፡ ዋናው ፍላጐቴ ልምምዱ ላይ ብቻ ነበር፡፡ አድካሚው ልምምድ ጭንቀትና ውጥረትን ማስተንፈሻ ድንቅ መሳሪያ ሆኖልኝ ነበር፡፡ ከባድ የቦክስ ልምምድ ካደረግሁ በኋላ አዕምሮዬንም ሆነ አካሌን ቅልል ይለው ነበር”
ኔልሰን ማንዴላ ለቦክስ ስፖርት የነበራቸውን ስሜት በመጽሀፋቸው ላይ በይፋ ከመግለፃቸው በፊት ዋልተር ሲሲሉስን ከመሳሰሉት የቅርብ የትግልና የእስር ቤት ጓዶቻቸው በቀር የሚያውቅ ሰው እምብዛም አልነበረም። የአለም የቦክስ ሻምፒዮን የነበረው አሜሪካዊው ሹገር ሬይ ሊዎናርድ፣ የአለም ሻምፒዮንነት ክብር የተቀዳጀበትን ቀበቶ በስጦታ ያበረከተላቸውም ይህንን ታሪካቸውን ጨርሶ ሳያውቅ ነው፡፡ ሹገር ሬይ ሊዎናርድ ያበረከተላቸው ይሄው የሻምፒዮንነት ቀበቶ፣ ሶዌቶ በሚገኘው የኔልሰን ማንዴላ ቤተሰብ ሙዚየም ውስጥ ተቀምጦ በጐብኝዎች እየታየ ይገኛል፡፡  ዛሬ ኔልሰን ማንዴላ የሚለው ስም በአለማችን አራቱም ማዕዘናት እንደ ጉድ የናኘና በቢሊዮን በሚቆጠሩ የአለማችን ህዝቦች ዘንድ በሚገባ የታወቀ መሆኑን አሌ ብሎ መከራከር ጨርሶ የሚያዋጣ አይደለም፡፡ ከ1926 ዓ.ም በፊት ግን የማንዴላ ወላጆች ሮሊህላህላ ማንዴላ እንጂ ኔልሰን ማንዴላ የሚል ስም ያወጡለት ወይም በዚህ ስም የተመዘገበ ልጅ አልነበራቸውም፡፡ ለሁሉም ተማሪዎች የክርስቲያን ስም ማውጣት ይገባል በሚል ኔልሰን የሚለውን ስም ያወጣላቸው፣ የዘጠኝ አመት ብላቴናና የሜቶዲስት ቤተክርስቲያን የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪ ሆነው ያስተምራቸው የነበረ መምህራቸው ነበር፡፡
ኔልሰን ማንዴላ ሲገረዙ የወጣላቸው ስም ዳሊ ቡንጋ የሚል ሲሆን ትርጉሙም የባህላዊው የቡንጋ አመራር አካል መስራች ማለት ነው፡፡ በአብዛኛው ደቡብ አፍሪካውያን ዘንድ በአክብሮት የሚጠሩበት “ማዲባ” ደግሞ የሚለው የጐሳ መጠሪያ ስማቸው ነው፡፡
ለኔልሰን ማንዴላ በተዘጋጀው የመታሰቢያ ስነ ስርአት ላይ ንግግር ካደረጉት መሪዎች አንዱ የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ናቸው፡፡ እሳቸውም ኔልሰን ማንዴላ ለነፃነት ሲሉ የከፈሉትን መስዋዕትነት በማውሳት፣ አለም ከእሳቸው ህይወት ጠቃሚ ልምድ ሊቀስም ይገባል ብለዋል፡፡  እንደ እውነቱ ከሆነ እንደ ግለሰብ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ያደረጉት ንግግር እንከን የለሽ ነው፤ እንደ ሀገር ከታሰበ ግን በጣም ኮሚክ ነው። ለምን ቢባል የአፓይታይድን ስርአት ሲያራምድ ከነበረው የደቡብ አፍሪካ የነጮች መንግስት በበለጠ የኔልሰን ማንዴላን የነፃነት ትግል የተቃወመች፣ በመጨረሻም ኔልሰን ማንዴላ ኢትዮጵያ ውስጥ የተሰጣቸውን ወታደራዊ ስልጠና ጨርሰው ሀገራቸው እንደገቡ እግር በእግር ተከታትላ በቁጥጥር ስር እንዲውሉ፣ ከዚያም የእድሜ ልክ እስራት ተበይኖባቸው ለሀያ ሠባት አመታት በወህኒ ቤት እንዲማቅቁ ያስደረገችው አሜሪካ ስለነበረች ነው፡፡ ይህም አልበቃ ብሏት እስከ 2008 ዓ.ም ደረስ ኔልሰን ማንዴላንና ይመሩት የነበረውን የአፍሪካ ብሔራዊ ኮንግረስ በአሸባሪና በአሸባሪ ድርጅትነት መዝግባ ይዛቸው ነበር፡፡  
ኔልሰን ማንዴላ፤ ኮልፌ የፖሊስ ማሰልጠኛ ተቋም ውስጥ ለስድስት ወር የተሰጣቸውን ወታደራዊ ስልጠና አጠናቀው ሲመረቁ፣ ግርማዊ ቀዳማዊ ሀይለስላሴ ንጉሰ ነገስት ዘኢትዮጵያ ሽልማትም፣ ማስታወሻም የሚሆን አንድ ሽጉጥ ሰጥተዋቸው ነበር፡፡ ይህንን ሽጉጥ በቁጥጥር ስር ከመዋላቸው በፊት አንድ ሰዋራ ቦታ ላይ ቀብረውት ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ኔልሰን ማንዴላ ከእስር ከተፈቱ በኋላ ከቀበሩበት ፈልገው ማግኘት አልቻሉም፡፡ ሽጉጡን ፈልጐ ማግኘት ከቻለ ሁለት ሚሊዮን ዶላር እሰጣለሁ ቢሉም ህይወታቸው እስካለፈበት ዕለት ድረስ አገኘሁ ያለ የለም፡፡ 

Published in ከአለም ዙሪያ

“ሥራ ህይወት ያለው ነገር ነው፤ ካላከበርከው ያዝናል፤ ይታዘብሃል”
የፌዴሬሽን ም/ቤት በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ዋና ከተማ በጅግጅጋ በተከበረው 8ኛው የብሔር ብሔረሰቦች ቀን በዓል ላይ እንድንገኝ ባደረገልን ግብዣ መሠረት ባለፈው ሳምንት በደማቅ ሁኔታ የተጠናቀቀው በዓል ተሳታፊ ነበኩር፡፡ እግረ መንገዴን ዋና ከተማዋን ስቃኝ ለሥራ፣ ከፍተኛ ክብርና፣ የተለየ አመለካከት ያለው ወጣት ኢንቨስተር አገኘሁ፡፡
“እኛ አልተረዳነውም እንጂ፣ ሥራ ሕይወት ያለው ነገር ነው፡፡ ሥራን ንቀን እንዳልባሌ ነገር ስንቆጥረው ይታዘበናል፣ ይከፋል፣ ያዝናል፡፡ “የዘራኸውን ነው የምታጭደው” እንደሚባለው ሁሉ፣ ምላሹም መጥፎና የከፋ ይሆናል፡፡ ስናከብረው ደግሞ ይስቃል፣ ይደሰታል፣ … ሥራውን ያከበረ ሰው ካሰበው ይደርሳል፤ እኔ ሥራዬ  ጓደኛዬ ነው” ይላል ወጣቱ ኢንቨስተር አሚር ሙክታር አብዱራህማን፡፡
በጅግጅጋ ከተማ ተወልዶ ያደገው አሚር፤ የ33 ዓመት ወጣት ሲሆን እስከ 12ኛ ክፍል ተምሯል፡፡ ትምህርት ላይ ጐበዝ እንደነበር የሚናገረው አሚር፤ ጉርምስና ሲጀምረው ለትምህርት ብቻ የነበረውን ሐሳቡን ብዙ ነገሮች ይጋሩት ጀመር፡፡ ከትምህርት ቤት እየጠፋ (እየፎረፈ) መቅረት ሲያበዛ ውጤቱም እንደዚያው ማሽቆልቆል ጀመረ፡፡ ከዚያስ ምን አደረገ? ራሱ ያጫውተናል፡፡
ትምህርት እንደማይሆነኝ ሳውቅ፣ እዚያው ላይ ሙጭጭ ማለት አልፈለኩም፤ ፈጣን እርምጃ ወሰድኩና ኮምፒዩተር መማር ጀመርኩ። ትምህርቱን አብረውኝ፣ እንደሚማሩት ልጆች ሳይሆን ጧት ወጥቼ እስከ ምሽት 4፡00 ድረስ ኮምፒዩተር ላይ ስለምቆይ፣ ጥሩ እውቀት ቀሰምኩ። ምሳዬን የምበላው በ10 ሰዓት ነበር፡፡ በዚህ የተነሳ የኮምፒዩተር ቤቱ ባለቤት እንድረዳው በ500 ብር ቀጠረኝ፡፡ እኔም፣ በተፈጠረልኝ የሥራ ዕድል ደስ ብሎኝ መሥራት ቀጠልኩ፡፡ እዚያ፣ አንድ ዓመት ተኩል ያህል እንደሠራሁ፣ ከባለቤቱ ጋር ስላልተስማማን ለቅቄ ወጣሁና የራሴን ቢዝነስ ጀመርኩ፡፡
በወቅቱ የነበረኝ ገንዘብ 10ሺህ ብር ነበር፡፡ በዚያ ገንዘብ “አልአሚር ስቱዲዮ” የተባለ ሙዚቃ ቤት ከፍቼ መሥራት ጀመርኩ፡፡ በመቀጠል ደግሞ ከመንግሥት ሲኒማ ቤት ተከራይቼ “አልአሚር” የተባለ ፊልም ቤት ከፈትኩ፡፡ እነዚህ ሥራዎች መነሻ ሆኑኝ፡፡ ይህ የሆነው በ1994 ዓ.ም አካባቢ ነበር። ሙዚቃ ቤቱን ከፍቼ እያለሁ ጥሩ የኮምፒዩተር እውቀት ስለነበረኝ፣ በየክፍለ ሀገሩ እየተዘዋወርኩ ኮምፒዩተር እጠግን ነበር፡፡ ይህ ሥራ ስለጠቀመኝ፣ ለተለያዩ ቢሮዎችና መ/ቤቶች ኮምፒዩተርና መለዋወጫቸውን እንዲሁም የተለያዩ የቢሮ ቁሳቁስ ማቅረብ ያዝኩ፡፡ በዚህ ዓይነት ገንዘብ መምጣት ጀመረ፡፡
ይኼኔ “ኢንፎቴክ ኮምፒዩተር ሴንተር” የተባለ የኮምፒዩተር ማስተማሪያ ት/ቤት ከፈትኩ። ጅግጅጋ ውስጥ ከከፍተኛ ባለሥልጣን እስከ ዝቅተኛው የከተማዋ ነዋሪ ድረስ አብዛኛው ሕዝብ እኛ ጋ የተማረ ነው፡፡ በእንደዚህ ዓይነት ስሠራ ቆይቼ የሚበቃኝን ያህል ከሠራሁ በኋላ በዚሁ ሥራ መቀጠል የለብኝም ብዬ ሙዚቃና ፊልም ቤቱን ዘጋሁ፡፡
ሙዚቃ ቤቱን እንኳ መዝጋት ሳይሆን አራት ወይም አምስት ዓመት ከሠራሁበት በኋለ አብሮኝ ይሠራ የነበረው ልጅ ራሱን እንዲችልበት አስተላለፍኩለት፡፡ ለአምስት ዓመት ያህል ኮምፒዩተር ቤቱን እያስተማርንበትና ለተለያዩ መ/ቤቶችና ድርጅቶች የተለያዩ የኮምፒዩተር ዕቃዎች ሳቀርብ ከቆየሁ በኋላ ከአሁን በኋላ፣ ከፍ ያለ ነገር መሥራት አለብኝ ብዬ ስለወሰንኩ ኮምፒዩተር ቤቱን ዘጋሁ፣ዕቃ ማቅረቡንም ተውኩ፡፡
እዚህ ውሳኔ ላይ የደረስኩት በቀላሉ አይደለም። አንደኛ የክልሉ መ/ቤቶች ጥቂት ናቸው፡፡ ያላቸው ቋሚ ዕቃዎችም ቶሎ ቶሎ ስለማይበላሹ፣ በየጊዜው የመግዛት ዕድሉም አነስተኛ ነው፡፡ ሌላው ደግሞ የከተማዋን ብዙ ሕዝብ ስላስተማርን ለመማር የሚመጣው ሰው ቁጥር ትንሽ ስለሆነ፣ እነዚህን ሥራዎች አቁሜ ቀጣይነት ወዳለው ቢዝነስ መግባት አለብኝ በማለት ወስኜ ነው፡፡
ለመዝጋት መወሰን ብቻ ሳይሆን በቀጣይ መሰራት ያለበትን ነገር መለየትም ቀላል አልነበረም። “እዚህ አካባቢ፣ ወደ ገንዘብ ሊቀየር የሚችል ምን ዕድል (ፖቴንሻል) አለ?” በማለት ለሁለት ዓመት የከተማዋን የወተት ፍላጐትና አቅርቦት በጥልቀት አጠናሁ፡፡ የጥናቱም ውጤት በልማዳዊ መንገድ የታለበ፣ ንፅህናው ያልተጠበቀ ወተት ከየአቅጣጫው ወደ ከተማዋ እንደሚገባ፣ ይህ ወተት በዘመናዊ መንገድ ፓስቸራይዝድ ተደርጐና ታሽጐ ቢቀርብ ከከተማዋ ሕዝብ ፍላጐት የሚተርፍ፣ … መሆኑን አመለከተ፡፡ በዚሁ መሠረት ዘመናዊ የወተት ማቀነባበሪያ ፋብሪካ ለማቋቋም ወሰንኩ። ሌላው ክፍተት ደግሞ በከተማዋ ዲጂታል ፎቶግራፍ ማተሚያ መሳሪያ አልነበረም፡፡ ይህንን ክፍተት ለመሙላት በልጆቼ ስም “3 ኤስ” የተባለ ዲጂታል ስቱዲዮ ቤት ከ3 ዓመት በፊት አቋቋምን። ማተሚያው ዋጋውን የመለሰው በሰባት ወር ሲሆን፣ አሁንም በጥሩ ሁኔታ ገቢ እያስገባ ነው። ሥራ በጣም እወዳለሁ። አንድ ሥራ ላይ ተወስኖ መቀመጥ አልወድም፡፡ ስለዚህ ሥራ ጓደኛዬ ነው፡፡
ይህን የወተት ማቀነባበሪያ ፋብሪካ የተከልክበትን ቦታ የክልሉ መንግስት ነው የሰጠህ?
ጠይቄ ነበር፡፡ የክልሉ መንግሥት ምላሽ ዘገየብኝ፡፡ ቢዝነስ ፈጣን ውሳኔ ስለሚፈልግ 3ሺህ ካ.ሜ ቦታ ከግለሰብ ገዝቼ ወደ ሥራ ገባሁ። ከጀርባ ያለውን ቦታ ለመግዛት እየተነጋገርኩ ነው፤ መንግሥትም ለማስፋፊያ የሚሆን ቦታ እሰጣችኋለሁ ብሎ ቃል ገብቶልናል፡፡
ይህን ፋብሪካ ለማቋቋም ምን ያህል ካፒታል ወጥቷል?
እስካሁን ድረስ በአጠቃላይ 15 ሚሊዮን ብር ያህል ፈጅቷል፡፡ በፍጥነት ሥራ ካልጀመረ ደግሞ ይጨምራል፡፡
ለስንት ዜጐች የሥራ ዕድል ፈጥሯል?
እስካሁን 48 ሠራተኞች አሉን፡፡ ይህ ቁጥር በቅርቡ 58 ይደርሳል፡፡ በዕቅዳችን ግን 72 ሠራተኞች ይኖሩናል፡፡
ይህ ፋብሪካ ምን ይሠራል?  ፋይዳውስ ምን ያህል ነው?   
የዚህ ፋብሪካ መቋቋም ጥቅሙ ብዙ ነው፡፡ ወተት፣ ከገጠር እያመጡ የሚሸጡ ሴቶች መንገድ ላይ አይተህ ይሆናል፡፡ እነዚህ ሴቶች የመኪና አደጋ ሊያጋጥማቸው ይችላል፡፡ ፀሐዩ፣ አቧራው፣ …አለ፡፡ ወተቱ ደግሞ ሳይሸጥ ቀርቶ ሲመለስ ይበላሻል፡፡ ይህ ፋብሪካ ሥራ ሲጀምር፣ ቋሚ ገበያ ይፈጠርላቸዋል ማለት ነው፡፡ ምን ለማድረግ አቅደናል መሰለህ? አርብቶ አደሮቹ ወተት ለመሸጥ ከተማ አይመጡም። እዚያው በአካባቢያቸው ወተት የሚያስረክቡበት ጣቢያ ወይም ማዕከል እናቋቁማለን፡፡ እዚያ ሆነን ወተቱን እንገዛቸዋለን ወይም ያስረክባሉ፡፡
አርብቶ አደሩ፣ ወተቱን ከሸጠ በኋላ ገንዘቡን ቋጥሮ ወደ ቤቱ አይመለስም፤ ከተማ ሄዶ የሚያስፈልገውን ስኳር፣ ዱቄት፣ ሸቀጣ ሸቀጥ ይገዛበታል፡፡ እኛ አሁን ለማድረግ ያቀደነው ከተማ ሄደው የሚገዙትን ዕቃ፣ በአካባቢያቸው ሱቅ ከፍተን፣ ከተማ መሄድ ሳያስፈልጋቸው ወተቱን አስረክበው፣ እዚያው ከሱቁ የሚፈልጉትን ዕቃ ገዝተው እንዲመለሱ ነው፡፡ በዚህ ሁኔታ ከመኪና አደጋ፣ ከፀሐይና ከአቧራ፣ … ይድናሉ፡፡ እኛ ፍሪጅ ያላቸው መኪኖች ስላሉን ከየማዕከላቱ ወተቱን ሰብስበን ወደ ፋብሪካው አምጥተን ፕሮሰስ አድርገንና አሽገን እንሸጣለን፣ ኤክስፖርት እናደርጋለን፡፡
ወዴት ነው ኤክስፖርት የምታደርጉት?
ጅቡቲ፣ ሀርጌሳ፣ … አቅም ካላቸው ተቀባዮች ጋር ተስማምተን ጨርሰናል፡፡ አዲስ አበባ ሩዋንዳ ቦሌ ሚካኤል አካባቢ ላሉ ሶማሌዎችም የግመል ወተት እናቀርባለን፡፡ ድሬዳዋ እናከፋፍላለን፡፡ ሥራውን በአጭር ጊዜ ለማስፋት አቅደናል፡፡
መቼ ነው ሥራ የምትጀምሩት?
በአንድ ሳምንት ጊዜ ውስጥ እንጀምራለን፡፡ ለዚህ የብሔር ብሔረሰቦች በዓል እናደርሳለን ብለን ነበር፡፡ ነገር ግን አንዳንድ የማሸጊያ ቁሳቁሶች ስለልደረሱልን ነው የዘገየው፡፡
ያጋጠሙህ ችግሮች አሉ? እንዴትስ ፈታሃቸው?
በሥራ ዓለም ብዙ ችግሮች ያጋጥሙሃል። ችግሮችን የምታስብ ከሆነ እዚያው አካባቢ ነው የምትሽከረከረው፡፡ ከችግሮቹ ወዲያ ማዶ ያለውን ስኬት ካየህ፣ ያጋጠመህ ችግር ቀላል ሊሆን ይችላል። ችግሮችን አግዝፈን ካየህ፣ አንዳንዱ እስከነጭራሹ አስሮ ሊያስቀርህ ይችላል፡፡ እኔ እምፈልገው ነገር ላይ ላይ ለመድረስ እንጂ ችግር ላይ አላተኩርም፡፡
በአንድ ወቅት ያጋጠመኝን ችግር እንዴት እንደተወጣሁት ላጫውትህ፡፡ ለተለያዩ መ/ቤቶች የተለያዩ የቢሮ ዕቃዎች እናቀርብ ነበር፡፡ ለአንድ መ/ቤት ዕቃ አቅርበን ከ500 እስከ 600ሺህ ብር የሚደርስ ኪሳራ አጋጠመን፡፡ ገንዘብ፣ ነገ ሠርተህ ታገኛለህ፤ ስምና ክብርህ ከጠፋ ግን ለመመለስ በጣም አስቸጋሪ ነው፡፡ ያቀረብነው ዕቃ በመበላሸቱ፣ መ/ቤቱ እንዳጭበረበርነው ነበር የቆጠረው። ስሜንና ክብሬን ለመጠበቅ እነዚያን ሰዎች ለማሳመን፣ ከእነሱጋር እንደገና መሥራት ነበረብኝ። እስከ መታሰር የሚያደርስ ነገር ነበር፡፡
ነገሩ እንዲህ ነው፡፡ ከድርጅቱ ገንዘብ ተቀብለን ከውጪ ድርጅት የተፈለገውን ዕቃ አቀረብን። ዕቃው ሲታይ፣ ላኪው ድርጅት ይወቅ አይወቅ ባላረጋገጥም፣ ዕቃው የቴክኒክ ችግር ነበረበት፡፡ ድርጅቱን የላካችሁልን ዕቃ የተበላሸ ነው ብንል “እኛ የላክነው ደህና ነው፤ እስኪ ላኩትና እንየው” አሉ። ቅሬታውን ካቀረበው መ/ቤት ዕቃውን ተረክበን እንዳንመልስ ተጠቅሞበታል፤ ገንዘብ ከፍሎ ቢያዝም ዕቃው ችግር ስለነበረበት ሊገለገልበት አልቻለምና እንዳጭበረበርነው ነበር የቆጠረን፡፡ ስለዚህ ስምና ክብራችንን ለመጠበቅ ከስረንም ቢሆን ጥሩ ዕቃ አስመጥተን አስረከብናቸው፤ ስማችንን አደስን፡፡
ያንን ያደረኩበት ምክንያት መንገድ ላይ የሚያይህ ሁሉ “አጭበርባሪው ነው፤ ታስሮ ነበር…” እያለ ሲጠቋቆምብህ ጥሩ አይደለም፤ በጣም ያማል። ገንዘቡን ከስሬ ትክክለኛ ሰው መሆኔን አስመስክሬ፣ ከዚያ በኋላ ብዙ ሥራ አብረን ሠራን፡፡
ለእናቱ ብቸኛ የሆነው አሚር፣ የ2ኛ ደረጃ ተማሪ እያለ የተዋወቃትን ልጅ ነው ያገባው፡፡ ከጋብቻ በፊት የ7 ዓመት ትውውቅ ሲኖራቸው፣ ትዳር ከመሠረቱ 10 ዓመት አልፏቸዋል፡፡ የመጀመሪያ ልጃቸው 10ኛ ልደቷን ያከበረችው ከ15 ቀን በፊት ሲሆን፣ ሁለቱ ወንዶች የ7 እና የ4 ዓመት ሕፃናት ናቸው፡፡
አሚር ለመሥራት ያሰበውን ነገር ሁሉ ለባለቤቱ ያማክራታል፡፡ ሚስቴ ለእኔ ሁሉ ነገሬ ናት፤ እንማከራለን፡፡ እምወደውንና የምጠላውን ነገሮች እነግራታለሁ፡፡ አንድ ሰው የቱንም ያህል አዋቂና ብልህ ቢሆን፣ የሆነ ጉድለት አያጣም፡፡ የእኔንም ጉድለት ባለቤቴ ታይልኛለች፣ ታግዘኛለች። እያንዳንዱን ነገር ከማድረጌ በፊት እነግራታለሁ፣ እንወያያለን፡፡ ብልህና አስተዋይ ስለሆነች እኔ ያልታየኝን ታሳየኛለች፡፡
በትዳር ዓለም 25 ወይም 50 ዓመት የኖሩ ሰዎች “አንድም ቀን ተጋጭተን አናውቅም” የሚሉት ከእውነት የራቀ ስለሆነ እኔ አልቀበለውም፡፡ ባልና ሚስት የሆነ ሰው ብዙ ጊዜ ይጋጫል፡፡ እኔና ባለቤቴ ተጋጭተን ማንም ሰው ሳያውቅ ሳምንትና 15 ቀን ልንዘጋጋ እንችላለን፡፡ የምንታረቀውም ራሳችን ነን-ሰው ገብቶብን አያውቅም፡፡ ከባለቤቴ ጋር ትንሽ ስንጋጭ እረበሻለሁ፣ ሥራ መሥራት ሁሉ ያቅተኛል።
ከባለቤቴ ጋር ያለኝ አግባብ ይህን ያህል ነው። እሷም ታውቀዋለች፡፡ ጥፋቱ የእሷ ከሆነ ደውላ ይቅርታ ትጠይቀኛለች፡፡ የእኔ ከሆነ ደግሞ ረጋ ብላ ታስረዳኛለች፡፡ በዚህ አይነት ነው ተግባብተን እየኖርን ያለነው፡፡
አንድ የቢዝነስ ሰው ለሥራው ታማኝ መሆን አለበት፡፡ ሥራ’ኮ ሕይወት ያለው ነገር ነው፡፡ ሥራ ካላከበሩት ይታዘባል፣ያዝናል፡፡ ካከበሩት ደግሞ ይስቀል ይደሰታል፡፡ አንድ ሰው ውጤታማ መሆን እፈልጋለሁ ካለ ለሥራው ታማኝ መሆን አለበት። ለሥራህ ታማኝ ከሆንክ ችግር ቢያጋጥምህም ሥራውን አትተውም፡፡ ያንን ችግር አብረኸው ታሳልፋለህ፡፡ የሥራ ትንሽ ስለሌለው፣ በትክክልና በታማኝነት ማገልገል አለብህ፡፡ አንድ ሥራ ስታከናውን ብዙ መስዋዕትነት መክፈል ሊኖርብህ ይችላል፡፡ ከጓደኛ መለየት፣ ከቤተሰብ መራቅ፣ … አለ፡፡ ያን ሁሉ መስዋዕትነት ከከፈልክ ሥራው ዋጋህን ይከፍልሃል፡፡ ሥራን ከናቅኸው መልሶ ይንቅሃል፡፡ ይህንን መገንዘብ ይኖርብናል፡፡  
የወደፊት እቅድህ ምንድነው?
ጅግጅጋ ብዙ ጊዜ የምትታወቀው በአሉታዊ ነገሮች ነው፡፡ ወደፊት ይህንን አመለካከት የሚቀይር፣ ወጣቱን፣ አዛውንቱን፣ ሕፃናቱን፣…ሁሉንም ያማከለ፣ በኢትዮጵያ ውስጥ ካሉት መዝናኛዎች በብዙ መንገድ የተሻለ (በገንዘብ ሳይሆን በሚሰጠው አገልግሎት) መዝናኛ ማቋቋም እፈልጋለሁ፡፡ በዱባይ፣ በኬንያ፣ ያሉ መዝናኛዎችን አይቻለሁ፡፡ በሁሉም አገሮች ያሉትን መዝናኛዎች ጉድለት አይቸባቸዋለሁ፡፡ “ይኼ ይኼ ቢኖረው ጥሩ ነበር” እላለሁ፡፡ የክልሉ መንግሥት አላስረከበንም እንጂ 20ሺህ ካ.ሜ ቦታ ፈቅዶልናል፡፡ መሬቱን እንደተረከብን፣ በዚህ ዓመት በሌሎች አገሮችና በኢትዮጵያ ያሉ መዝናኛዎች ያላቸውንና “ይጐድሏቸዋል” ብዬ ያየኋቸውን አገልግሎቶች ያሟላ እጅግ ዘመናዊ መዝናኛ ግንባታ ለመጀመር ጥናትና ዲዛይኑ ተጠናቋል፡፡ አሁን የምንጠብቀው መሬቱን እስኪያስረክቡን ነው፡፡ ከአሁን በኋላ ትናንሽ ሥራዎች ሞክሬ ያየኋቸው ስለሆነ ወደዚያ አልመለስም፡፡ መንግሥት ትኩረት በሰጣቸው አምራች ኢንዱስትሪዎች መሳተፍ ነው ትኩረቴ፡፡ ጊዜው እስኪደርስ ይቆዩ እንጂ ሁለትና ሦስት ጥናታቸው የተጠናቀቀ ትላልቅ ፕሮጀክቶችም አሉ፡፡
“በዚህ አጋጣሚ እኔ እንድለወጥና ሰው እንድሆን የረዱኝን ሰዎች ማመስገን እፈልጋለሁ፡፡ ከእግዜር ቀጥሎ የመጀመርያዋ ተመስጋኝ ባለቤቴ ናት፡፡ ከእሷ ቀጥሎ አቶ አካሉ ቢረዳን በጣም ማመስገን እፈልጋለሁ፡፡ እኔ መኪና ያላቸው ብዙ ጓደኞች አሉኝ፡፡ ይህ የወተት ማቀነባበሪያ ፕሮጀክት ከተጀመረ አንድ ዓመት ሆኖታል፡፡ በዚህ ጊዜ ውስጥ አንድ ወይም ሁለት ጊዜ ነው መጥተው ያዩት፡፡ አቶ አካሉ ግን መኪና የለውም፤ ፋብሪካው እየተሠራ ያለው ከከተማው ርቆ ዳር ላይ ነው፡፡ ታዲያ ፀሐይ እየለበለው በትራንስፖርት መጥቶ ብዙ ጊዜ አበረታቶኛል፤ ምክር ለግሶኛል፡፡ “ለካስ የዚህ ዓይነት ቅን ሰውም አለ! ከእንግዲህ ሰው አንድ ነገር ሲሰራ እኔም እንደአካሉ አደርጋለሁ፤ ለሰው ቅን እሆናለሁ” በማለት ሐሳቤን እንድለውጥና ሰብዕናዬን እንድቀርጽ ስላደረገኝ አመሰግነዋለሁ፤ አከብረዋለሁ፡፡” በማለት ለአቶ አካሉ ቢረዳ ያለውን አድናቆት ገልጿል፡፡

አዲሱ የኢትዮጵያ ደራስያን ማህበር ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ነባሩን የሥራ አስፈፃሚ አባላት ባለፈው ሐሙስ በወይን ኢትዮጵያ የባህል ምግብ አዳራሽ በደማቅ ሥነ ሥርዓት ሸኘ፡፡
አንጋፋና ወጣት ደራስያን እንዲሁም የልዩ ልዩ ሙያ ማህበራት መሪዎች በተገኙበት  የተሰናባቹ ሥራ አስፈጻሚ አባላት ገጠመኞቻቸውን እያቀረቡ ታዳሚውን ከማዝናናታቸውም በላይ ለስምንት ዓመታት ማህበሩን ሲመሩ፣ የነበራቸው የእርስ በርስ መናበብ ሐላፊነታቸውን በአግባቡ እንዲወጡ ብርታት እንደሰጣቸው ተናግረዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት ማህበሩን በፕሬዚዳንትነት የሚመሩት ዶ/ር ሙሴ ያዕቆብ ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር እንደገለጹት፤ የግል ሥራቸውንና ማህበራዊ ጉዳዮቻቸውን በመተው ለማህበሩ ዕድገት ሲጥሩ ለነበሩት የቀድሞ መሪዎች ክብርና ሞገስ ሊቸራቸው ይገባል፣ አዲሱ አመራርም አርአያነታቸውን ተከትሎ በትጋትና በፍቅር በመሥራት ማህበሩን ወደተሻለ የዕድገት ደረጃ ከፍ ለማድረግ ይጥራል ብለዋል፡፡
ክቡር አቶ ሙሉጌታ ሰኢድ የኢፌዴሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ በበኩላቸው፤ ለተሰናባቾቹ ሥራ አስፈጻሚ አባላት ማህበሩ ያዘጋጀላቸውን የዋንጫና የአድናቆት ምስክር ወረቀት ከሰጡ በኋላ ባደረጉት ንግግር፣ ሌሎች የሙያ ማህበራት መሪዎችም ከኢትዮጵያ ደራስያን ማህበር ሊማሩ ይገባል፤ ሚኒስቴር መ/ቤታችንም ከኪነ ጥበብ ማህበራት ጋር ለመሥራት ከመቸውም ጊዜ በላይ ዝግጁ ነው ብለዋል፡፡
ቀደም ሲል ማህበሩን በፕሬዚዳንትነት ይመሩ የነበሩት አቶ ጌታቸው በለጠ ከመስከረም 25 ቀን 2006 ዓ.ም ጀምሮ ከሃላፊነታቸው ወርደው በዶ/ር ሙሴ ያዕቆብ ፕሬዚዳንትነት የሚመራ አዲስ ሥራ አስፈፃሚ መሰየሙ ይታወሳል፡፡

Published in ጥበብ
Saturday, 14 December 2013 13:06

ማንዴላንአትመልስም!

“የታሪክህ አፅም
ተቆፍሮ ቢወጣ፤
ቀን የጣላት፣ ዘውድ ናት
የደፋሃት ባርኔጣ
የማንነትህ ዙፋን ነው
በርጩማህንም ነፃ አውጣ፣
ሥርወ - ቤትህን አውጅ
ጐጆህ ሀገር ትውጣ
ሳትነግሥ እንዳትሞት
አንጋለህ ሳትቀጣ
ብድርህን ሳትመልስ
ወግረህ ሳትቆጣ”
…እያለ ከሚያዝህ
ከዚያ ውዥንብር መንፈስ፣
ቀልብያህ ሳትድን
ነፍስህ ሳትፈወስ፣
ማንዴላን አታንሳ
ትርጉም ለማልፈስፈስ፡፡
ከተጠናወተህ፤ ስም አይጠሬ ህመም
የትውልድ በሽታ፣
ከሚያስደረድርህ፤ ጠመንጃና መውዜር
በበገና ፈንታ፣
አረር ከሚያስጤስህ
ከከርቤ እያፋታ፣
ጐጆ ከሚያስመልክ
ሀገር እያስረታ፤
ታሞ ካሳመመህ
ከይሄ ርኩስ መንፈስ፣
ቀልብያለህ ሳትድን
ነፍስህ ሳትፈወስ
ሕዋ ያህል ቃልን
በጐጆ አፍ ማወደስ
የጀግናውን ገድል
ትቢያ ላይ መለወስ፡፡

ሳምሶን ጌታቸው ተ.ሥ  

Published in የግጥም ጥግ
Saturday, 14 December 2013 13:03

ረቂቅ

ተጨረማምተው የወደቁት ወረቀቶች ለከራማ የተበተኑ ፈንድሻ መስለዋል፡፡
ጅምር ጽሑፍ…፡፡
የተሰበረ እርሳስ…፡፡
በረባው ባልረባው ነገር የተጣበበ ጠረጴዛ…፡፡
ያለቀበት የሶፍት ካርቶን…፡፡
ሶስት ቀን ያስቆጠረ ያልታጠበ የቡና ስኒ…፡፡
ያልተከደነ ፔርሙዝ…፡፡
የምጥን ሽሮ ቀለም ያለው ግድግዳ ላይ አራት አመት ያለፈው ካላንደር “ኧረ የአስታዋሽ ያለህ” የሚል ይመስል ተንጠልጥሏል፡፡
እነዚህ … እነዛ … የታሰቡት … ያልታሰቡት … ሁሉም እንደ ሐሳቡ ተዘበራርቀው ተቀምጠዋል፡፡
ሐሳብ ሲያላምጥ የቆረጠመው እርሳስ የመፋቂያ ጫፍ ሊመስል ትንሽ ነው የቀረው፡፡ ኤርምያስ የአስር አመት ፍቅረኛውን ፋይል ሳይዘጋ ከእህቷ ጋር የጀመረው አዲስ ምዕራፍ ውጤት ምን እንደሚሆን ለማወቅ ጓጉቷል … ረቂቅ እማታውቀው ነገር ቢኖር … ያላወቀችው ብቻ ነው፡፡
የወትሮው ደንደና ልቡን ከተሰደደበት መልሶታል፣ በከፊል የራሱን ታሪክ እየመሠለው ቢቸገርም መጨረሻውን ለማግኘት የጀመረው ጉልበት ሆኖታል፡፡ አጠገቡ ያሉትን ሐሳብ የሚበታትኑ ምስቅልቅል ነገሮች በሙሉ ተነስቶ አፀዳ፡፡ ጥግ ከቲቪው ጀርባ … የተሸረፈው ማጨሻ ጢም ብሎ ከተሞላው ፍም ላይ እጣን በተን አደረገ… ከርቤ እና ወገርት ቀላቅሎ ማጨስ ያስደስተዋል። ቅዳሜና እሁድ ብቻ ነው በተለየችው ማጨሻው ነጭ እጣን የሚያጨሰው፡፡ ያኔ ስስ ካናቴራ በረጅም ሙታንታ፣ በሰፊ ሸበጥ፣ ለስላሳ ሙዚቃ ከፍቶ ሙሉ ቀን በረጅም መፋቂያ ጥርሱን እየሟጨ … በእጣኑ ሽታ ከሠማይ ቤት እረፍት አድርጎ ይመጣል፡፡
ከአልጋው ትይዩ ያለውን አስራ አራት ኢንች ቲቪ ተመለከተው … የተሸከመውን አቧሯ አይቶ ራሱን ነቀነቀ፡፡ የቲቪው ማስቀመጫ ወደ ኋላ ዘንበል ስላለ፣ ውኃልኩ እንዲቃና በውጭ ሀገር አፍ በተፃፈ መጽሐፍ ነበር ያስደገፈው፡፡ “ፐርፌክት ዴዝ” የሚለውን መፅሃፍ አንገቱን ዘመም አድርጐ ተመለከተ፡፡ ቆይቷል ካነበበው… ሴት ናት ፀሐፊዋ … በእጣ ፈንታ ላይ ያተኮረ መጽሐፍ ነው… አልሆንለት ያለ ደራሲ ሲዳክር በጉልህ ያሳያል … ቢሆንም የመጽሐፉ እጣ ፈንታ በራሱ ያሳዝናል… የቲቪ ድጋፍ፡፡
ወደ ቦታው ተመለሠ… ግራ እጁን ወደ ቴፑ ሰዶ ከፈተ … የሙሉ ቀን መለሠ ሥርቅርቅ ድምፅ አጀበው … “ቁመትሽ ሎጋ ነው የኔ አለም…”
ካቆመበት ለመቀጠል እርሳስና ወረቀቱን ጠመደ፤ የእጣኑ ጢስ ሲትጐለጐል ራቁቷን ጀርባዋን ሠጥታ፣ ለወንድ ራሷን የሸለመች ልጃገረድ ይመስላል… ሽቅብ የጢሱ ቅርፅ አጓጓኑ፡፡
“በዚህ ቅዝቃዜ … ለዚያውም ማንም በሌለበት ብቻችንን እዚህ መሆኑን ወደኸው ነው?”
“ተመልከተው እስቲ ሰማዩን … ከእግዚአብሔር የበለጠ ሰዓሊ አለ ብለህ ታስባለህ?”
“አዎ!”
“ማን?”
“አንቺ”
“ሒድ ሞዛዛ… የምሬን ነው እግዚአብሔር ኮፒ የማይደረግ ሰዓሊ ነው፡፡”
እጇን ሳበው … ጣቶቿ ከርዝመታቸው በተጨማሪ የጥፍሮቿ ውበት የሰጠ ነው፡፡”
ጥፍሮቿ ላይ የተጋደመው ሠማያዊ ቀለም የሆነ ያልታወቀ ነገር አመላካች ነው፡፡ አግድም ጥቁር ጥቁር መስመር አለበት፡፡ ኤርምያስ የረቂቅን አይበሉባ ገለበጠውና የውስጥ እጇን ሳማት…
“እንደዚህ አትሣመኝ አላልኩህም?”
“ብለሽኛል” መልሶ ሳማት፡፡
“እና ለምን ውስጤን ይበልጥ ትረብሸዋለህ?”
“መሣም የት ሃገር ነው የረብሻ ምልክት የሆነው…?”
“ሌባ መሆኔ ቀረ፡፡”
“እኔን ነው የሠረቅሽው… ምን ችግር አለው?”
“ውስጥ እጄን እና አንገቴ ስር ስትስመኝ የሆነ የማላውቀው መንፈስ መላው ሰውነቴ ላይ ሲርመሠመሥ ይታወቀኛል …”
“እህትሽም እንዲህ ትለኝ ነበር…” አንገቷን አቀረቀረች፡፡ ሌባነቷ ውስጧን ሲሟገታት፣ ሲተናነቃት ታቀረቅራለች… “ምነው የኔ ቆንጆ … አጠፋሁ?”
“ታናሽ እህቴ ስላንተ ባወራችኝ ቁጥር እየወደድኩህ … እየተራብኩህ መጣሁ…”
“ይኸው አገኘሽኝ እኮ”
“በስርቆት የተገኘ ማንኛውም ነገር አንገት ይሠብራል” አሁንም ውስጥ እጇን ሳማት
“ተው! እንደ ኤሌክትሪክ ይነዝረኛል እያልኩህ?”
“ከከንፈሬ ግድብ የሚመነጨው ስድስት ሺ ቮልት እኮ ነው” ሳቀላት፡፡
“ሒድ ሞዛዛ … ባዶ ሜዳ ላይ እንዲህ መለኮስ ያስወነጅላል…”
“በየት ሃገር ወንጀለኛ መቅጫ ህግ?”
“የእኛ ሃገሩ ነዋ!”
“የኛን ሃገር ተይው!”
“ለምን?”
“አሰርዘን ሌላ ማፃፍ እንችላለን!”
“ስማ አንዲትን ልጃገረድ ሳትፈቅድና ሳታስበው ልቧን አሸፍቶ ለጦርነት መቆስቆስ ሐጥያት ነው ይላል ህጉ!”
“የምድር ህግ ስለ ሐጢያት ቦታ የለውም”
“ሞዛዛ አትሟዘዝብኝ… የኔን ሐሳብ ማናናቅህ ነው…?” አሁንም ደግሞ ውስጥ እጇን ሳማት፡፡ በምላሱ በስሱ ዳበሳት… ለመከልከል ግን ጉልበቱ አልነበራትም፡፡
“እዚህ ሆቴል አልጋ ይዣለሁ…” ቀስ ብሎ ተመለከታት … ዝምታዋ እንደ ጨረቃዋ ውብ ነው … እንደጠራው ሰማይ ቅኔ ነው …ፀጥ ያለ ባህር ሲዘፍን ይመስላል… ከዋክብቶቹ ፊቷ ላይ የፈጠነቁት ብርሃን ጥይምናዋ ላይ እንደወርቅ መርገፍ ተነስንሰዋል፡፡
“አልሠማሽኝም?”
“እ…?” ፈገግ አለች… በጠረጴዛው ሥር እግሮቿን ጭኖቹ ላይ አድርጋ ነበር፡፡ እጇን መለሠላትና … ሁለቱንም እጆቹን ከጠረጴዛው ሥር ሠደዳቸው…
“የኔ ቆንጆ… አንድ አይነት ላባ ያለን ሰዎች ነን፤ ምናለበት አብረን ብንበር…?”
“የት?”
“ከልብሽ ሰፈር… ከፍቅርሽ ዋሻ … ከሠላምሽ ደጀ ሠላም…?” ሷቋ መጣ… ህሊናዋ ውስጥ ሥርቆሽ ለምን እንደሚጣፍጥ …አብዝቶ የተወራን ጥሩ ፍቅር ለምን ሰርቆ የራስ ለማድረግ እንደምንማስን አሠበች … እጆቹ እግሮቿን እየዳበሠ፣ እሳቱን ይበልጥ ለማቀጣጠል እያራገቡ ናቸው፤ በለስላሳ መዳሰስ፡፡
ከወንበሩ ጠጋ አለ፤ ወደ እሷ … ከወንበሯ ጠጋ አለች፤ ወደ እሱ … እጆቹ ግን እዛው እሣት እያቀጣጠሉ ነው፡፡ ሥር የሠደደው የጭኗ ሙቀት መላ ሠውነቷን በንዳድ ናጣት … በእነዛ በሚያማምሩ ጣቶቿ የጠረጴዛውን ጨርቅ ጭምድድ አድርጋ ያዘች… ከምትገልፀው በላይ ውስጧ ሲርመሠመሥ ተሠማት… ሰማዩ ዝቅ ብሎ የተገለጠውን የፍቅር መሶብ ለመክደን ተቃርቧል፡፡
የእጣኑ ሽታ ከሩቅ ደብር ተሠዶ እንደሚመጣ ጣዕሙ እየቀነሠ ነው፡፡ ደረጄ … ለአፍታም ካቀረቀረበት ቀና አላለም፡፡ በሁለቱ ፍቅር የቀና ይመሥል ሠውነቱ ግሏል፡፡
ረቂቅ … የጠጣችው ሁለት ብርጭቆ ወይን ከሥር ከሚቆሠቆሠው ፍም ጋር ተዳምሮ አግሏታል… ጭኖቿን ጭምቅ ስታደርግ አብራ እጆቹንም ከጭኖቿ ጋር አጣበቀችው … “አራግበው” ይመስላል ሁኔታዋ፤ አይኑ አይኗ ላይ የተፃፈውን “ፈጠን በል የምን መፍዘዝ ነው…” የሚል ጽሑፍ እያነበበ ነው፡፡
ሥራ አልፈቱም እጆቹ፡፡ ሁለቱም ወንበራቸውን ስበው ተጠጋግተዋል… ያስተዋለ ግን አልነበረም፣ ቀኝ እጁን ከፍም ዳርቻ አንሥቶ አቀፋት … አንገቷን ከፍም የተበጀ እጅ ሲያሞቃት ተሠማት…፡፡
ደረጄ … ጭኑ ስር ሙቀት ሲፈስበት ታወቀው… ተቁነጠነጠ… እነሱን ለማረቅ እርሱ መቀዝቀዝ እንዳለበት ዘነጋ … እርሳሱን ጠበቅ አድርጐ ያዘ፡፡
ረቂቅ … በትከሻው አልፎ የመጣውን ፍም የለበሠ ሥጋ ሳመችው… ግራ እጇን ከጠረጴዛው ሥር ወርውራ እጅ ለእጅ ተቆራኙ… ሁለቱም የቀራቸውን ቀይ ወይን እኩል ተጐንጭተው ተነሱ…፡፡ ጃኬቱን አለበሳት…፡፡ የሁለቱም የልብ ትርታ ሲዳምኛ ይደልቃሉ፡፡
ደረጄ … አሁንም ተገርሞና በሙቀቱ ተወብቆ የመጻፊያ እርሳሱን ጠበቅ አደረገ፤ የእጣኑ ሽታ ሙሉ በሙሉ ርቋል፣ የማጨሻው ፍም አምዷል፡፡ ረቂቅ … የእሱን እጅ ጥብቅ አድርጋ ይዛ እየተከተለችው ነው… እየተቻኮለ የተከራየውን በር ከፈተ… ረቂቅ … ወደ ኋላ ቀረት አለች… ዞሮ አያት… መሬት መሬት ተመለከተች… አይበሉባዋን ሳማት … እጇን ከእጁ አላቀቀች፡፡
ደረጄ … ጠበቅ አድርጐ ሲፅፍ እርሳሱ ተሠበረ… “ቲሽ!” አለ ተበሳጭቶ፤ የተሠበረውን በንዴት ግድግዳው ላይ አላተመው… ማጨሻው አጠገብ ኩርምት ብሎ ተቀመጠ፤ እርሳሱ፡፡

Published in ልብ-ወለድ

ሒልተን ማሰልጠኛ ስላለው ሠራተኞቹ በእንግዳ አያያዝ ተወዳዳሪ የላቸውም
ሰውነቴ የሚንቀሳቀስ አይመስልም፤ ግን በጣም ቀልጣፋ ነኝ
በሆቴል መስተንግዶና ደንበኞች አያያዙ በጣም ብዙ ይቀረናል

በአዲስ አበባ ሂልተን ሆቴል ለ25 ዓመታት ሰርቷል፡፡ አሁን በምግብ ዝግጅት ክፍል በሼፍነት እየሰራ ቢገኝም የጀመረው ግን በእቃ አጣቢነት እንደሆነ ይናገራል፡፡ ሰውነቱ ወፍራም ቢሆንም ማናቸውንም ስራዎች ከማከናወን እንዳላገደው የገለፀው የምግብ ዝግጅት ባለሙያው ታደሰ አራጋው፤ ውፍረትና ሼፍነት ምንም የሚያገናኛቸው ነገር እንደሌለ ያስረዳል -የራሱን ተመክሮ በመጥቀስ፡፡ በአገራችን ሆቴሎች በከፍተኛ ደረጃ እየተስፋፉ ቢሆንም የመስተንግዶ ችግር እንዳለና ሥልጠና ላይ አተኩሮ መስራት እንደሚያሻ ይናገራል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ ከሼፍ ታደሰ ጋር ያደረገችው ቃለምልልስ እንደሚከተለው ተጠናቅሯል፡፡

ትውልድህና እድገትህ የት ነው?
ትውልድና እድገቴ አዲስ አበባ ራስ ደስታ ሆስፒታል አካባቢ ነው፡፡
ስንት የልደት ሻማዎች አብርተህ አጠፋህ?
ዞሮ ዞሮ እድሜህ ስንት ነው ለማለት ነው አይደለም? በ1956 ነው የተወለድኩት፤ ሀምሳ አመቴ ነው፡፡
ሆቴል ከመግባትህ በፊት ስራህ ምን ነበር?
አንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቴን ኢትዮጵያ ትቅደም ት/ቤት ካጠናቀቅኩ በኋላ “ኦአይሲ” በሚባል ድርጅት በግንበኝነት ትምህርት ስልጠና ላይ ቆይቼ፣ ባሌ ክ/ሀገር መስሎ የሚባል ቦታ በስራ ላይ ከቆየሁ በኋላ፣ አዲስ አበባ ተመልሼ ነው የሆቴል ስራ የጀመርኩት፡፡
እንዴት ነው ወደ ሆቴል ስራ ልትገባ የቻልከው?
ባሌ ውስጥ ስኖር እናቴ ርቄያት ስለምኖር ትጨነቅ ነበር፡፡ በመሀል ልጠይቃት መጣሁ፡፡ በአጋጣሚ ሂልተን የሚሰራ ሰው አየኝ፡፡ እዚያ ሆነህ እናትህን ከምታስጨንቃት ሆቴል ውስጥ ሥራ ብሎ አስገባኝ፡፡
በመጀመሪያ በምን ስራ ላይ ነው የተሰማራኸው?
በመጀመሪያ እቃ አጠባ ነው የገባሁት - “ስቲዋርዲንግ” ይባላል፡፡ ብረት ድስት ማጠብ አለ … ምን የማይታጠብ ነገር አለ፡፡ በወቅቱ ውሀው እና የሚታጠብበት ኬሚካል እጄን እየቆራረጠው በጣም እማረር ነበር፡፡ እናቴ ግን እጄን ባዝሊን እየቀባችና እያባበለች ስራው ላይ እንድቆይና ርቄ ክፍለ ሀገር እንዳልሄድ ታደርግ ነበር፡፡ ስራ ያስገባኝም ሰው እንድበረታ ያደርገኝ ስለነበረ፣ ታግዬ አሁን የደረስኩበት ደረጃ ደርሻለሁ፡፡ በዚህ አጋጣሚ ሂልተን ያስገባኝን አዳነን አመሰግነዋለሁ፤ አሁን ያለው አሜሪካ ነው፡፡
በሂልተን ሆቴል ውስጥ ስንት አመት ሰራህ?
የ25 ዓመት የሆቴል ስራ ልምድ አለኝ፡፡
እንዴት ነው ወደ ምግብ ዝግጅት ሙያ የገባኸው?
እዚያ ቦታ ስትሰሪ ስልጠናው አለ፣ በማየት የምታዳብሪው አለ፡፡ እናም ከእቃ አጣቢነት ወጥቼ ዌይተር ሆኜ መስራት ጀመርኩ፡፡ አሁን ሱፐርቫይዘር ነኝ፡፡ በካፕቴይን ማዕረግ ላይ ነው ያለሁት፡፡ ታዲያ ካፕቴይን ስልሽ የሆቴሉን ነው፤ የአውሮፕላኑን እንዳይመስልሽ (ሳ…ቅ)
እስኪ ስለ ሼፍነትህ እና ስለ ሰውነት አቋምህ እናውራ፡፡ ውፍረትህ ከሼፍነትህ ጋር ይያያዛል?
ሼፍነት የተማርኩት እዛው ሆቴል ውስጥ ነው። ሆቴል ውስጥ መስራት ብዙ ነገር ያስተምራል፡፡ ዩኒቨርስቲ የማታገኚውን በርካታ ነገር ትማሪበታለሽ። እኔም ሼፍነትን የተማርኩት በማየትና በራሴ ጥረት ነው፡፡
ከሰውነት አቋም ጋር በተያያዘ ያነሳሁት ጥያቄ ነበር፡፡ ውፍረትህ ሼፍነትህን ተከትሎ የመጣ ይሆን? አብዛኞቹ ሼፎች በጣም ወፍራሞች ስለሆኑ ከምግብ መቅመስ ጋር የሚያያይዙት ወገኖች አሉ፡፡ አንተስ ምን ትላለህ?
ይሄ እንኳን እውነት ለመናገር የተሳሳተ አመለካከት ነው፡፡ እንዲያውም ሼፎች ብዙ ጊዜ ምግብ አይበሉም፡፡ አንደኛ የሚሰሩት ምግብ ሽታ ይዘጋቸዋል፡፡ ሁለተኛ ስራው አድካሚ እንደመሆኑ በጣም ቢዚ ይሆናሉ፡፡ ብዙ ጊዜ ሼፎችን ካስተዋልሽ ደረቅ ነገሮችን ሲበሉ ነው የምታያቸው፡፡ እንጀራ በጨው፣ ደረቅ ዳቦ ምናምን ነው የሚቀማምሱት። እንደሚባለው አስሩን ምግብ በመቅመስ አይደለም ውፍረቱ የሚመጣው፡፡
ያንተ ውፍረት መንስኤ ምን ይመስልሀል? ለመሆኑ ስንት ኪሎ ትመዝናለህ?
ወደ 98 ኪሎ ግራም ነኝ፡፡ ሰውነቴን ስታይው የሚንቀሳቀስ አይመስልም ግን በጣም ቀልጣፋ ነኝ። በተለይ ፊልድ ስወጣ ሰዎች እምነት የላቸውም። የምንቀሳቀስ አይመስላቸውም፡፡ እስከ አፋር እና መሰል ቦታዎች ከቱሪስቶች ጋር በመዘዋወር ምግብ አዘጋጃለሁ፡፡ ፈረንጆቹ በጣም ነው የሚገርማቸው። ኦሞ፣ ዳሽን እና የመሳሰሉት ቦታዎች ሁሉ ሄጄ ሰርቻለሁ፡፡ የእግር ጉዞውም ሆነ ማንኛውም ነገር አያቅተኝም፡፡ እኔ መወፈር የጀመርኩት ከ30 አመት በፊት ነው፡፡ እስከ 20 ዓመት እድሜዬ ቀጭን ነበርኩኝ፡፡ ይህ ማለት የሆቴል ስራ ከመጀመሬ ከአምስት አመት በፊት ማለት ነው፡፡ ሆቴልም ስራ ጀምሬ ቶሎ ሼፍ  አልሆንኩም፡፡ በአጠቃላይ ውፍረቴ ከሼፍነቴ ጋር ጨርሶ አይገናኝም፡፡ ብዙ ጊዜ ሰዎች ሲያዩኝ ግን ይጨንቃቸዋል፡፡
98 ኪሎ ያልከውን ግን… ተጭበርብሯል ባይ ነኝ…
እውነቱ ይሄው ነው፤ ሄደን አስመዝኝኝና እውነቱን እወቂ፡፡ ስታይ ግን 200 ኪሎ ነው የምመስለው ግን 98 ኪሎ ነኝ፤ መቶ ለመሙላት እየጣርኩ ነው (ሳቅ…)
ቀደም ሲል እንደገለፅከው በሆቴል ውስጥ ብዙ ትምህርትና ገጠመኞች አሉ፡፡ ከገጠመኞችህ ብታካፍለን… በተለይ ከውፍረትህ ጋር በተያያዘ …  
በርካታ ገጠመኞች ይኖራሉ፡፡ ለምሳሌ አንድ ጊዜ ምን ገጠመኝ መሰለሽ? ከአንድ ቱር ኦፕሬተር ጋር ወደ አፋር ዳሎል ዲፕሬሽን ለመሄድ ስንነጋገር፣ “እሱን ይዤ አልሄድም ይሞትብኛል” ብሎ ታቃወመ፡፡ እኔ እንደምችልና ውፍረቴን አይቶ ሊገድበኝ እንደማይገባ ተሟገትኩ፡፡ እሱም “አፋር በጣም ሙቀት ስላለው ይሞትብኛል አልፈልግም” አለ፡፡ እኔ እንደውም ብርድና ቅዝቃዜ ሲሆን ነው የማይስማማኝ፡፡ እግሬን ያመኛል፤ ያው ይህን ሁሉ ክብደት ስለሚሸከምም ሊሆን ይችላል፡፡ ከብዙ ክርክር በኋላ ሊወስደኝ ተስማማንና ሄድኩኝ፡፡ እዛ ከሄድን በኋላ በክርክሩ ተፀፅቷል፡፡ በጣም በጥሩ ሁኔታ ቱሪስቶቹን ሳገለግል ቆይቼ፣ ምንም ችግር ሳይፈጠር ለመመለስ ቻልን፡፡ እንዲህ አይነት በርካታ ገጠመኞች አሉ፡፡
ሌላ የጤንነት እክል አለብህ ወይስ ጤነነትህ የተሟላ ነው?
አያመኝም፡፡ ምንም ችግር የለብኝም ግን እንዳልኩሽ እግሬን አልፎ አልፎ ያመኛል፡፡ በተረፈ ጤነኛ ነኝ፤ እግዚአብሔር ይመስገን፡፡
አንዳንዴ በራስህ ውፍረት ላይ እንደምትቀልድ ሰምቻለሁ…  
አዎ እቀልዳለሁ፡፡ በራሴ መቀለድ ደስ ይለኛል፡፡ አንዳንዴ ስልክ ደውዬ ማን ልበል ሲሉኝ፤ “ዙሪያው ነኝ” እያልኩ አስቃቸዋለሁ፡፡ ሁለተኛ ደግሞ ሰዎች ሲያዩኝ በጣም ይደነግጣሉ፡፡ ክብደቴም ብቻ ሳይሆን የቁመቴ ማጠርም ጭምር የሚያስደነግጣቸው አሉ። እና ድንጋጤያቸውን ሳይ፣ ዘና እንዲሉ አንዳንድ ቀልዶችን በራሴ ላይ ጣል አደርጋለሁ፡፡
በልክህ የተዘጋጁ ልብሶች ታገኛለህ?
አላገኝም፤ አሰፍቼ ነው የምለብሰው፡፡  
ስንት ሜትር ይበቃሀል?
እሱ እንኳን ያው ነው፡፡  
ያው ነው ስትል ከሌላው ሰው እኩል ነው ለማለት ነው?
አዎ፡፡ ከሌላው ሰው ጋር እኩል ነው፤ ኮትም አንድ ተኩል፣ ሱሪም አንድ ሜትር ተኩል ነው የሚበቃኝ፡፡
ይሄማ እንዴት ሊሆን ይችላል?   
እሱን እንዴት እንደሆነ ባላውቅም ከሌላው ጋር እኩል ነው የምለብሰው፡፡ ሬዲ ሜድ (የተዘጋጀ ልብስ) አልፎ አልፎ ሸሚዝ ብቻ አገኛለሁ፤ ግን የውጭ እቃ አድናቂ ስላልሆንኩ የአገሬን ልብሶች እያሰፋሁ እለብሳለሁ፡፡ አሁን ያደረግሁት ኮፍያ ራሱ የቅዱስ ጊዮርጊስ ቢራ ኮፍያ ነው፤ ምርቱን ስለምወደው ነው ኮፍያውንም ያደረግሁት፡፡ በአጠቃላይ ልብሶቼና ጫማዎቼ የአገር ውስጥ ምርቶች ናቸው፤ ሁሉም ሰው የአገሩን ምርት ቢጠቀም ደስ ይለኛል፡፡  
አሁን ባለህ የሰውነት አቋም ትጨነቃለህ?
በፍፁም አልጨነቅም፤ ደስተኛ ነኝ። ምክንያቱም ምንም ከማድረግ አያግደኝም፡፡ እዝናናለሁ፤ እጫወታለሁ፤ እደንስበታለሁ፡፡ ብታይኝ ይገርምሻል፤ በጣም ጐበዝ ዳንሰኛ ነኝ፡፡
ብዙ ጊዜ ወዳጅ ዘመዶችህን ከእኔ ጋር ገበያ አትውጡ ትላለህ ይባላል፡፡ ለምንድነው?  
እውነት ነው፤ እኔ ገበያ ስሄድ 10 ብር የነበረው እቃ 20 ብር ይሆናል፡፡ በእጥፍ ይጨምሩብኛል፤ ውፍረቴን ሲያዩ፣ ወርቃማውን ባለ ጉልላት የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እመስላቸዋለሁ መሰለኝ…
ባለ ትዳር ነህ?
በአንድ ወቅት ባለ ትዳር ነበርኩኝ፤ አሁን ሚስቴን ፈትቼያለሁ
ከሰውነት አቋምህ ጋር በተያያዘ ነው ትዳርህን የፈታኸው?
በፍፁም! በተለያዩ አለመግባባቶች ነው የተፋታነው፡፡ ከውፍረቴ ጋር የሚገናኝ አይደለም፡፡
ልጆች ወልዳችኋል?
አልወለድንም
እስኪ ወደሼፍነት ሙያ እንመለስ፡፡ የአገራችንን ሼፎች ከሌላው አለም ሼፎች ጋር አወዳድር ብትባልስ?
አሁን አሁን የአገራችን ሼፎች በጣም በጣም ጐበዝ እየሆኑ ነው፣ በጣም አሪፍ አሪፍ ሼፎች አሉ፡፡ ይገርምሻል፤ ከውጭ ከሚመጡት ሁሉ ይበልጣሉ። እንደውም ከውጭ የሚመጡት የአገራችንን ያህል ችሎታ አላቸው ብዬ አላምንም፡፡ ያለ ችሎታ ሁሉ የሚመጡ አሉ፡፡ ብዙ ጊዜ ታዝቤያለሁ፡፡ ነጭ ስለሆኑ ብቻ ይችላሉ ተብለው ይመጣሉ፡፡ እዚህ ግን በጣም ጐበዝ ጐበዝ ሼፎችን ታገኛለሽ፡፡
በሆቴል ኢንዱስትሪው ስላለው የመስተንግዶና የእንግዳ አቀባበል ሙያ ምን ትላለህ?
ኢትዮጵያ ውስጥ የመስተንግዶ ሙያ ዳብሯል የሚል እምነት የለኝም፡፡ በተለይ ከአዲስ አበባ ራቅ እያልሽ በሄድሽ ቁጥር በጣም ችግር አለ፡፡ ሩቅ ሳንሄድ እዚህ ቁጭ ብለን እየተወያየን ባለንበት ካፌ ውስጥ ሻይ ከቀረበ በኋላ ስኳር የመጣው በስንት ልመናና ጩኸት ነው፤ እንደዚህ አይነት ስህተቶች አሉ፡፡ ይሄ የአስተናጋጆች ጥፋት አይደለም፡፡ የአሰሪዎቹ ነው፣ ስልጠና እንዲያገኙ አላደረጓቸውም፣ የደንበኛ አያያዝ ላይ ግንዛቤ የላቸውም፤ ስለዚህ ችግር አለ፡፡
ይህን ችግር ለመቅረፍ በየቦታው እየተዘዋወርክ ስልጠና እንደምትሰጥ አውቃለሁ፡፡ እኔም በአንድ ወቅት ያቤሎ ውስጥ ለሆቴል አስተናጋጆች ስልጠና ስትሰጥ አግኝቼሀለሁ …  
ትክክል! በተለያዩ ቦታዎች ከቱሪስቶች ጋር በሼፍነት እንደምሄደው ሁሉ ሰራተኞችን እንዳሰለጥንላቸው የተለያዩ ሆቴሎች ይጠሩኛል። ግን ይህን ስልጠና ለሰራተኞች እንድሰጥላቸው የሚጠሩኝ ጥቂቶች ናቸው፡፡ አብዛኞቹ ሆቴል ይከፍታሉ፤ የዕለት ገቢ መሰብሰብ እንጂ ደንበኛዬን እንዴት ልያዝ፣ ምን ያስፈልገዋል፣ ለአስተናጋጆቹ ምን አይነት ስልጠና ይሰጣቸው የሚለው አንገብጋቢ ጉዳይ ትዝ አይላቸውም፡፡ አንድ ተስተናጋጅ ለምሳሌ አራት ቢራ ለመጠጣት አስቦ፣ የአስተናጋጆቹን ሁኔታ በማየት አንድ ብቻ ጠጥቶ ይወጣል፡፡ አራት ሊጠጣ የመጣን ሰው በአያያዙ ማርኮት፤ ስምንት እንዲጠጣ ነው ማድረግ ያለበት፡፡ ያለበለዚያ ኪሳራ እንጂ ትርፍ መጠበቅ የዋህነት ነው፡፡
በዋናነት የአስተናጋጆች ችግር የባህሪ ነው ወይስ…
እኔ እንደምታዘበው በርካታ ችግሮች አሉ። ለምሳሌ የንፅህና ጉዳይ አለ፤ የፀጉር አያያዛቸው፣ የደንብ ልብስ አለባበሳቸው … በዚያው መጠን የባህሪና ስነ-ምግባር ችግሮችም አሉ፡፡ በተለይ አንዳንድ ትልቅ መስለው የሚታዩ ሆቴሎች ወደ ውስጥ ስትገቢ “ውስጡን ለቄስ” እንደሚባለው ናቸው፡፡ በደንቡ መሰረት የአንድ ሆቴል እይታ የሚጀምረው ገና ከጥበቃ ሰራተኛው ነው፡፡ ያማረ የደንብ ልብስ፣ የተስተካከለ አቋምና መሰል ነገሮችን አሟልቶ ስታይው ወደ ውስጥ ለመግባት ይጋብዛል። ከበር ይጀምራል ሁሉም ነገር፡፡ የጥበቃ ሰራተኛ ስለመስተንግዶ ስልጠና ማግኘት አለበት፡፡ ገና ለገና ዘበኛ ነው ተብሎ የመስተንግዶ ስልጠና ካላገኘ በር ላይ ያለው አቀባበል ደንበኛውን ወደ ኋላ ሊመልሰው አሊያም ተመልሶ እንዳይመጣ ሊያደርገው ይችላል። ይሄ ሁሉ ትኩረት ካላገኘ ቢዝነሱ ውሀ በላው ማለት ነው፡፡ ብዙ ዘበኞች እንግዳ ይገላምጣሉ፣ ፍተሻ ላይ ስርዓት የላቸውም፤ ይሄ ሁሉ ችግር አለ፡፡
አሁን አሁን ብዙ ባለሀብቶች ወደ ሆቴል ቢዝነስ እየገቡ ነው፡፡ ይህን እንዴት ታየዋለህ?
ትክክል ነው፤ አሁን ሆቴሎች እንደ አሸን እየፈሉ ነው፡፡ ነገር ግን የአገሪቱም እድገት በዚያው ልክ እየፈጠነ ስለሆነ ሆቴሎች አስፈላጊ ናቸው፡፡ እንደውም ዘርፉ ገና አልተሰራበትም ባይ ነኝ፡፡ ነገር ግን ሆቴል ሲከፈት ከሆቴሉ ጋር አብረው መታየት ያለባቸው ጉዳዮች አሉ፡፡ ቢዝነሱን ጠንቅቆ ማወቅ ያስፈልጋል፡፡ ከቢዝነስ ጋር በተያያዘ የሰማሁትንና ያሳቀኝን ቁም ነገር ያዘለ ቀልድ ልንገርሽ፡፡ ለስራ ወደ አንዱ ክልል የወጡ ሰዎች ያጋጠማቸው ነው። ሰውየው የሚያምር ፔኒሲዮን ሰርተዋል፡፡ እዚያ የሚያርፉ ሰዎች ጠዋት ቁርስ ሲፈልጉ ራቅ ወዳለ ቦታ (ከተማ) መሄድ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ታዲያ ይህን የተመለከተ ተስተናጋጅ ባለቤቱን “አባቴ ጥሩ የእንግዳ ማረፊያ ሰርተዋል፣ ምቹ አልጋ አለ፣ ነገር ግን እንግዳ ጠዋት እርቦት ነው የሚነሳው፡፡ ግቢው ሰፊ ነው፤ እዚህ ትንሽ ቤት ሰርተው ቁርስ ቢያቀርቡ ምን ይመስልዎታል?” ይላቸዋል፡፡ ጋቢያቸውን ደርበው ግቢ ውስጥ የሚንጐማለሉት የእንግዳ ማረፊያው ባለቤት ምን ቢሉ ጥሩ ነው? “ደሞ ያጋደምኩት አንሶኝ ከርሱን ልሙላው?” ብለው አረፉት፡፡ ይሄ ቀልድ ሊመስል ይችላል፤ ግን ቢዝነስ አለማወቅ ነው። ሰው አንድ ስራ ሲሰራ ወይም ሊሰራ ሲነሳ አብሮ ሊሰራቸው የሚገባውን ነገሮች ማወቅ አለበት፡፡
አሁን ክብደትህን ለመቀነስ አላሰብክም?
እንደውም ለመጨመር ጥረት እያደረግሁ ነው፡፡  
ምግብህን ራስህ ነህ የምታዘጋጀው?
በአብዛኛው ራሴ አዘጋጅቼ ነው የምመገበው፡፡ አልፎ አልፎ ሌሎች የሚያዘጋጁትንም እመገባለሁ፡፡
ምን አይነት ምግብ ታዘወትራለህ?
እንደማንኛውም ኢትዮጵያዊ ነው የምመገበው። የተለየ አመጋገብ የለኝም፤ ብቻ ጥሩ ተደርጐ መሰራት አለበት፡፡
ብዙ ጊዜ ሼፎች የሚስቶቻቸው የምግብ አሰራር አይጥማቸውም … በሚስቶቻቸው ላይ ጫና ይፈጥራሉ የሚባለው እውነት ነው?
ጫና መፍጠር አይደለም፤ እሷም ጥሩ ምግብ አብሳይ እንድትሆን ታሳያታለሽ፡፡ ይህን እንዲህ አድርጊው፣ ይህን ጨምሪበት ብለሽ ትመክሪያለሽ፤ ታስተምሪያለሽ እንጂ ጫናውን ምን አመጣው፡፡ እኔ አሁን ብዙ ሰው በሚያዘጋጀው ምግብ ደስተኛ አይደለሁም፡፡ ከመጠን በላይ ዘይት፣ ጨው፣ ቅመም… ይጨምራሉ፡፡ ይህ ለጤና ከፍተኛ ችግር ነው፡፡ የንፅህናው ጉዳይም እንደዛው ትንሽ ያስጨንቀኛል፡፡
የንፅህናው ጉድለት ጉዳይ ስትል?
ሩቅ ሳንሄድ የቀድሞ እናቶችን የበርበሬ አዘገጃጀት እንውሰድ፡፡ በርበሬ በፈረሱላ ተገዝቶ እንደመጣ ዛላውን ያጥባሉ፣ ይቀነጥሳሉ፣ በቅመም ይደልዛሉ፡፡ ሲፈጭ ጣዕሙ የሚጠገብ አይደለም፡፡ አሁን ያየሽ እንደሆነ ገና ከገበያ እንደመጣ በፀሀይ ይደርቃል፤ ከነዛላው ወፍጮ ቤት ይገባል፤ አልታጠበ በደንብ አልፀዳ፡፡ እናቶች ደልዘው ቀምመው በሚያስፈጩት በርበሬ እንጀራ ስትበይበት አያቃጥልም፤ ይጣፍጣል እንጂ፡፡ የአሁኑ በርበሬ እንኳን እንጀራ በደረቁ ልትበይበት ወጥ ውስጥ ገብቶ እንኳን እንዴት እንደሚፋጅ አስቢው፡፡ ይህ ሁሉ ደስ አይለኝም። እናም በአብዛኛው ንፅህናው ያስጨንቀኛል፡፡ ሆቴሎች ብዙ አልጠቀምም፤ ቤቴ ራሴ አዘጋጃለሁ፡፡
ሒልተን በጣም አንጋፋና ባለ አምስት ኮከብ ሆቴል ነው፡፡ አለም አቀፍ እንግዶች የሚያርፉበት ነው፡፡ አንተ እነማንን አግኝተህ ታውቃለህ?
እውነት ለመናገር ብዙ መሪዎችን አግኝቻለሁ። ከታቦ ኢምቤኪ ጋር ተግባብቼ አዋርቼአቸዋለሁ፡፡ ሌሎች በቴሌቪዥን ብቻ የሚያዩዋቸውን እኛ እዛ ስለምንሰራ ብቻ በቀላሉ አግኝተን እናዋራቸዋለን። እነሱም በቀላሉ ጓደኛ ያደርጉሻል፡፡ እና እከሌ እከሌ ለማለት ያዳግተኛል፡፡ ሂልተን ለሰራተኞቹ የራሱ የስልጠና ማዕከል ስላለው፣ ሰራተኞቹ በእንግዳ አያያዝ ተወዳዳሪ የላቸውም፡፡ ስለዚህ ሆቴሉ ከአመት አመት እንግዳ ቀንሶቦት አያውቅም፡፡ ብዙ አለም አቀፍ እንግዶች ይመጣሉ፡፡ ሆቴላችን ለስልጠና ከፍተኛ በጀት መድቦ የሰራተኞቹን አቅም ይገነባል፡፡
ላለፉት 25 አመታት ማለትም የእድሜህን ግማሽ በሆቴል ስራ ላይ አሳልፈሀል፡፡ ስልጠናም ትሰጣለህ፡ የራስህን ሆቴል ወይም ማሰልጠኛ ማዕከል ለመክፈት አልሞከርክም?
ብዙ ጥረቶች አድርጌ ነበር፡፡ በተለይ የስልጠና ማዕከል ለመክፈት ሀዋሳ ፕሮፖዛል አስገብቼም ነበር፡፡ ነገር ግን ብዙ እንቅፋቶች ገጠሙኝና ሳልከፍት ቀረሁ፡፡
አሁን ግን አንድ በመጠናቀቅ ላይ ያለ ነገር አለኝ፡፡ በተለይ ከአዲስ አበባ ውጭ ስትሄጂ የአስተናጋጆቹ የትምህርት ደረጃ አነስተኛ ነው። መስተንግዶ ተምረዋል ቢባል እንኳን ደረጃውን የጠበቀ ሳይሆን የለብ ለብ ነው፡፡ ስለዚህ እነዚህን አስተናጋጆች የሚያግዝ ስለ መስተንግዶ አጠቃላይ መረጃ የሚሰጥ መፅሀፍ ፅፌ ጨርሻለሁ፡፡ አሁን ለህትመቱ ስፖንሰሮችን እያፈላለግሁ ነው፡፡ መፅሀፉ ለአንባቢ ሲደርስ የዚህን አገር የመስተንግዶ ደረጃ እንደሚያሳድገው እምነት አለኝ፡፡ ምክንያቱም መስተንግዶ ላይ በጣም በጣም ይቀረናል፡፡

Published in ጥበብ

“አሪፍ ሃያሲ ፊት ለፊት እየሄደ መንገድን ያሳያል፣ ቀሽም ሃያሲ ኋላ ኋላ እየተከተለ ይገፋል”  አርቲስት ግሩም ኤርሚያስ
አብዛኞቹ የፊልም አድናቂዎች ከ‹‹ሄርሜላ›› ፊልም ጀምሮ ያውቁታል፡፡ በፊልም ትወና ሙያ ለ11 ዓመታት የሰራው አርቲስት ግሩም ኤርሚያስ፤ በየጊዜው በርካታ የፊልም ፅሁፎች ቢቀርቡለትም እስካሁን በዓመት ከአንድ በላይ ፊልም አልሰራም፡፡ መስራት ሳይፈልግ ቀርቶ አይደለም፡፡ የሚመጥነው እያጣ መሆኑን አርቲስቱ ይናገራል። ባለፈው ሳምንት በኢትዮጵያ ኢንተርናሽናል ፊልም ፌስቲቫል ‹‹የዓመቱ ምርጥ የወንድ የፊልም ተዋናይ›› በሚል የተሸለመው አርቲስቱ፤ የዛሬ ሶስት ዓመትም በተመሳሳይ ዘርፍ ተሸላሚ ነበር፡፡ የ‹‹ሜተድ አክቲንግ›› የትወና ዘይቤ ገፀ ባህርይው መስሎ ሳይሆን ሆኖ መጫወት እንደሚፈልግ ያስረዳል፡፡ ለዚህ ነው የሚተውነውን ገፀ ባህሪ ለማጥናት ሰፊ ጊዜ የሚወስደው፡፡ ዘንድሮ በተሸለመበት በ‹‹400 ፍቅር›› ፊልም ላይ ቦክሰኛውን ሆኖ ለመጫዎት ለስምንት ወር የቦክስ ስልጠና እንደወሰደ ይናገራል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አበባየሁ ገበያው ከግሩም ኤርሚያስ ጋር ባደረገችው ቆይቶ ስለ ህይወቱና ስለ ሙያው፣ ስለ ኢትዮጵያ የፊልም ኢንዱስትሪና ተያያዥ ጉዳዮች አነጋግራዋለች፡፡


በቅርቡ ሁለተኛ ልጅ አግኝተሃል፡፡ ባለፈው ሳምንት ደግሞ የኢትዮጵያ ኢንተርናሽናል ፊልም ፌስቲቫል “የዓመቱ ምርጥ የፊልም ተዋናይ” በሚል ተመርጠሃል፡፡ ሽልማት በሽልማት ሆነሃል ልበል…
አዎ.. ሁለቱም ሽልማቶች ናቸው፡፡ የመጀመሪያ ልጄ ወንድ ነው..አምስት አመቱ ነው፡፡ ሁለተኛ ልጄ ደግሞ ሴት ናት፡፡ ይህ የእግዚአብሄር ሽልማት ነው። አዲስዋ ልጄ ከተወለደች ሃምሳ አምስተኛ ቀንዋ ነው። ሌላው በ”የኢትዮጵያ ኢንተርናሽና ፊልም ፌስቲቫል” ሁለት ጊዜ ማለትም በአምስተኛውና በስምንተኛው ዙር ውድድር “ምርጥ የወንድ ፊልም ተዋናይ” ሆኜ ተመርጫለሁ፡፡ ይሔኛው ሽልማት ደግም ሰዎች ለሰራሁት ስራ እውቅና ሰጥተው አክብሮታቸውን ያሳዩበት ነው፡፡ ሁለቱም ለእኔ ብርቅ ናቸው፡፡
እስቲ አሸናፊ ስለሆንክባቸው ስራዎችህ ንገረኝ?
በአምስተኛው ዙር ‹‹ትዝታ›› እና ‹‹ይሉኝታ›› በተሰኙት ፊልሞች በእጩነት ቀርቤ ነው  በአንዱ የተሸለምኩት፡፡ ባለፈው ሳምንት በስምንተኛው ዙር ውድድር ደግሞ ‹‹400 ፍቅር›› በተባለው ፊልም “ምርጥ የዓመቱ የወንድ ፊልም ተዋናይ” ሆኜ ተሸልሜአለሁ፡፡
‹‹ትዝታ›› እና ‹‹ይሉኝታ›› ፊልሞች..ጭብጣቸው ምን ነበር?
ሁለቱም በተለያየ ዘውግ የተፃፉ የተለያየ ባህሪ ያላቸው ፊልሞች ናቸው፡፡ ‹‹ይሉኝታ››ን ካየነው ዳርክ ኮሜዲ ከሚባለው የፊልም ዘውግ የሚመደብ ነው፡፡ ‹‹ትዝታ›› ደግሞ ሙሉ በሙሉ ድራማ ነው። ሁለቱ ውስጥ የተለያዩና ፅንፍ ለፅንፍ ያሉ ገፀ ባህሪያት ናቸው ያሉት፡፡ ‹‹ይሉኝታ›› ላይ ያለው ዋና ገፀ ባህሪ ጥግ ድረስ ሄዶ ሰዎችን የመረዳት ባህሪ ያለው..ለእኔ ጂኒየስ የምለው ዓይነት ሰው ነው፡፡ በቅርብ የማውቀውን ሰው ነው አክት ያደረግሁት። ለእኔ እንደዚህ ዓይነት ሰዎች ለፍፁምነት እጅግ የቀረቡ ናቸው፡፡ በምድር ላይ ብዙ አይደሉም። ክርስቶስ እንዳደረገው፤ ሁሉነገራቸውን ለሰው የሰጡ ዓይነት ናቸው፡፡ ከውጭ ስናያቸው ሞኝ፣ የዋህ ሊመስሉ ይችላሉ፡፡ እንደዚህ ዓይነት ሰዎች በርከት ቢሉ አለማችን ትቀየራች ብዬ አስባለሁ፡፡
‹‹ትዝታ›› ፊልም እውነተኛ ታሪክ ነው፡፡ ዳሬክተሩ ሃብታሙ አሰፋ፤ የአባቱን እውነተኛ ታሪክ ነው የጻፈው፡፡ ያልኖርኩበትን የ60ዎቹን ወጣትነትና በእርጅና ውስጥ ያለ ህይወት ነው የዳሰስኩበት፡፡ የሚገርመው ሁለቱንም አልኖርኩበትም፡፡ ሁለቱም ጽንፍ ያላቸው ግን ወድጃቸው የተጫወትኳቸው ናቸው፡፡ ዘንድሮ በስምንተኛው ዙር ያሸለመኝ ደግሞ ‹‹400 ፍቅር›› ፊልም ነው፡፡ የሁለት መንታዎች ታሪክ ነው፡፡ በመጀመሪያ ‹‹ምን ዓይነት መንታዎች አሉ?›› የሚል ሰፊ ጥናት አደረግሁ፡፡ ብዙ ዓይነት የመንታ ዓይነቶች አሉ፡፡ በፊልሙ ላይ ያሉት ግን ‹‹ሚረር ኢሜጅ አይዴንቲካል ትዊንስ›› የሚባሉ የመንታ ዓይነቶች ናቸው፡፡ እንደዚህ ዓይነት መንታዎች ከሌሎች መንታዎች የሚለዩት፣ ራሳችንን በመስታወት በምናይ ጊዜ መስታወት ውስጥ ላለው ምስል ሁሉ ነገራችን ተቃራኒ ነው። ቀኛችን ግራ ነው፣ ግራችን ቀኝ ነው፡፡ እንደዚህ ዓይነት መንታዎችም መልካቸው አንድ ዓይነት ይሆናል እንጂ ሁሉ ነገራቸው የተለያየ ነው፡፡ ለምሳሌ አንደኛው ግራኝ ከሆነ፣ አንደኛው ቀኝ ይሆናል፡፡ ፍፁም የተለያዩ ናቸው፡፡ አንደኛው ቦክሰኛ ነው፣ አንደኛው ደግሞ ዲዛይነር ነው፡፡
በዚህ ፊልም ውስጥ ቦክሰኛውን ሆነህ ለመጫወት ቦክስ ተለማምደሃል?
ያውም ስምንት ወር ነዋ  የፈጋሁት! ከቦክሰኞች ጋር በመዋል..ሙሉ በሙሉ የቦክስ ልምምዱን ወስጄ ነው የወጣሁት፡፡ ቦክሱን ያስተማሩኝን አሰልጣኝ ከድር ከማልን እና ካሳዬ ከፋን በጣም አመሰግናለሁ። በስምንት ወር ውስጥ ፕሮፌሽናል ቦክሰኛ ነው ያደረጉኝ፡፡
አሁን መዘረር ነው በለኛ...
/ሳቅ/ የሚገጥመኝ ካለ ዝግጁ ነኝ። እና በፊልሙ ላይ የመንትዮችን ባህሪ ሳጠና፣ ከእናትና ከአባታቸው የወረሱት ጂን ምንድን ነው? ለምሳሌ አንደኛው ከእናቱ የድፍረትን ጂን ወስዷል። አንደኛው ደግሞ አባታቸው ፈሪ ስለነበረ የአባታቸውን ጂን ወስዷል። የዚህን ያህል ነው የካራክተሮችን ባህሪ ያጠናሁት። የዚህ ልፋት ዋጋ ነው በሰዎች ዘንድ ዋጋ አሰጥቶኝ ያሸለመኝ፡፡
ወደ ሙያው ከገባህ ጀምሮ ስንት ፊልሞች ሰራህ?
አስራ አንድ ፊልሞች ነው የሰራሁት፡፡ “መስዋዕት”፣ “ሄርሜላ”፣ “ልዕልት”፣ “ስርየት”፣ “የሞረያም ምድር”፣ “862”፣ “ትዝታ”፣ “ይሉኝታ”፣ “አማላዩ” እና “400 ፍቅር” ናቸው፤ ባለፉት አስራ አንድ ዓመታት የሰራኋቸው፡፡ ይሄ እንግዲህ በዓመት አንድ ፊልም ማለት ነው፡፡
ፊልሞች በበዙበት ወቅት እንዴት በዓመት አንድ ብቻ በመስራት ተወሰንክ?
ሁሉጊዜ የሚስበኝ የምሰራበት ፊልም ያለው ታሪክ ምንድን ነው የሚለው ነው፡፡ ለማህበረሰቡ በተወሰነ መልኩ መልዕክት ማስተላለፍ የሚችል ታሪክ ሲሆን ደስ ይለኛል፡፡ በሁለተኛ ደረጃ፣ የምጫወተው ካራክተር (ገፀባህሪ) ነው የሚመስጠኝ፡፡ የእኔ መስፈርት፣ እስከዛሬ ከተጫወትኳቸው ካራክተሮች በጭራሽ የማይመሳሰል መሆን አለበት የሚል ነው፡፡ ለምሳሌ ሰዎች ‹‹አማላዩ››ን ፊልም አይተው ‹‹አማላዩ›› ላይ ያለውን አይነት ካራክተር..ይዘቱም ቅርፁም ተመሳሳይ የሆነ የፊልም ታሪክ ይዘውልኝ ይመጣሉ.. ግን አልቀበልም፡፡ ምክንያቱም ያ በቃ ሞተ፤ ለእኔ ያ ሰው እንደተቀበረ ሰው ማለት ነው። አንድ ካራክተር ከሰራሁት በኋላ እንሰነባበታለን፡፡ ከዛ ደግሞ ያልሰራሁት፣ ያልዳሰስኩት፣ ያልነካሁት ገፀ ባህሪ መጫወት እፈልጋሁ፡፡ የተወሰነ ጊዜ እጠብቃለሁ፤ አሪፍ አሪፍ ነገር እስኪመጣልኝ፡፡ ለዛ መሰለኝ..
ለአምስት ዓመት በማረሚያ ቤት ታስረህ ነበር፡፡ እንዴት ነው ያሳለፍከው?
ብዙ መፃህፍትን “ቁርጥም አድርጌ የበላኋቸው” የዛን ጊዜ ነው፡፡ ልቦለድ፣ ፍልስፍና፣ ስለላ.. ብዙ ታሪኮችን አንብቤያለሁ፡፡ የማንዴላን “Long walk to Freedom”፣ “ፍቅር እስከ መቃብር” ወዘተ.. ትምህርቴን አቋርጬ ስለነበር፣ እንደ አዲስ ከዘጠነኛ ክፍል ጀምሬ እዚያው ተማርኩ፡፡ የቋንቋ ችሎታዬን በተወሰነ መልኩ ለማዳበርም ሞክሬያለሁ፡፡ ማረሚያ ቤት ለእኔ ዩኒቨርስቲ ነበር፣ ህይወትን “ግራጅዌት” አድርጌ እንደወጣሁ ነው የምቆጥረው፡፡ ራስን የመፈለግ ጉዞ ነበር የሆነልኝ፡፡
የሁለተኛ ደረጃ ትምህርትን በማረምያ ቤት ጨረስክ፡፡ ከዚያ በኋላስ አልቀጠልክም?
ከሆሊላንድ አርት አካዳሚ በትያትሪካል አርት ተመርቄአለሁ፤ ሁለት ዓመት ተምሬ፡፡
አንዳንድ ባለሙያዎች ‹‹ሜተድ አክቲንግ” እንደምትከል ይናገራሉ፡፡ እስቲ ስለእሱ አብራራልኝ…
እንደ ስታይል የሜተድ አክቲንግ ስታይል ተከታይ ነኝ፡፡ የሩሲያዊውን አክተርና ዳይሬክተር የስታኒላቭስኪን የሜተድ አክቲንግ መፅሃፍ አግኝቼ አንብቤዋለሁ፡፡ እሱን ከአነበብኩ በኋላ ነው የሜተድ አክቲንጉ ተከታይ መሆን የጀመርኩት፡፡ በዚህ ስታይል መሰረት፤ የምትጫወችውን ካራክተር መምሰል ሳይሆን መሆን አለብሽ፡፡ አንቺ ወደ ካራክተሩ እንድትሄጂ እንጂ ካራክተሩ ወደ አንቺ እንዲመጣ አይጠበቅም፡፡ ወደ አንቺ የሚመጣ ከሆነ “ታይፕ አክተር” ነው የምትሆኝው፡፡ ያ ከሆነ ደግሞ የምሰራቸው ፊልሞች ተመሳሳይ ይሆናሉ ማለት ነው፡፡ ካራክተሩ ወደ አንቺ እንዲመጣ በጋበዝሽው ቁጥር  ሌሎች ሰዎችን ነው የምትሆኝው፡፡ ሜተድ አክቲንግ የሚጠቅመው ካራክተሮችን እንዳትደግሚ በማድረግ ነው፡፡ እኔ ደግሞ የዚህ ውጤት ነኝ፡፡
የተለያዩ ባህሪያትን እያጠኑ ሆኖ መጫወት ትክክለኛው የራስህ ባህሪ ላይ ተጽዕኖ አያሳድርም?
እውነት ነው፤ በጣም ተፅዕኖ (ኢንፍሉዌንስ) አለው፡፡ አንዳንድ ጊዜ ዲፕሬሽን (መደበት) ሊያጋጥምሽ ይችላል፡፡ የተጫወትኩት ባህሪ ከደሜ ውስጥ ሙልጭ ብሎ እስኪወጣ ድረስ ይዞኝ ይጠፋል፡፡ ይሁነኝ ብለሽ አይደለም የሚመጣብሽ። በሰብኮንሸስ ማይንድ (ንቁ ባልሆነው የአዕምሮአችን ክፍል) ነው የሚሰራው። ብዙዎቻችን የምንኖረውም በሰብኮንሼስ ማይንዳችን ነው፡፡ ሰብኮንሸስ ማይንድ በነገርሽው መጠን፣ ያንን ነገር ቅርጽ አስይዞ ያስቀምጥና ይመነዝረዋል፡፡ ከዚያም አሳልፎ ለኮንሸስ ማይንድ (ለንቁው የአዕምሮአችን ክፍል) ይሰጣል፡፡ ‹‹400 ፍቅር››ን ስሰራ አነበብኩ፤ ሪሰርች አደረግሁ፡፡ ቦክስ ተማርኩ…ከቦክሰኞች ጋር ተገኘሁ..ራሴን ‹‹ቦክሰኛ ነኝ›› ብዬ አሳመንኩ፡፡ ቦክስ ቦክስ ስል ሳላውቀው…ሰውነቴም ሪአክት ማድረግ ጀመረ… ክብደት ጨመርኩ..ጡንቻዬ ይሳሳብ ጀመር፡፡ አሁን ደግሞ የሃሺሽ ሱስኛ (ድራግ አዲክትድ) የሆነ ገፀ ባህሪ ያለበትን የፍጹም አስፋውን ፊልም ለመስራት ጥናት ላይ ነኝ፡፡ ሪሰርች ጀምሬያለሁ፤ ሰውነቴ ሲከሳ ይታወቀኛል፡፡
እንዴት ነው በሱስ የተያዘ ሰው ባህሪን የምታጠናው?
/ሳቅ/…ድራግ አዲክትድ ወይም የሀሺሽ ሱስኛ ሰውን ባህሪ ነው የማጠናው፡፡ በተደጋጋሚ ጳውሎስ ሆስፒታል “ሪሃብሊቴሽን ሴንተር” እየተመላለስኩ ነው፡፡ የድራግ ሰብስታንሶች ያሉባቸው ሰዎች ከሱሳቸው የሚነፁበትን መንገድ ለምሳሌ ከመጠጥ፣ ሲጋራ፣ አልኮልና፣ አደንዛዥ ዕፅ... ለማጥናት ሰሞኑን ያለሁት ጳውሎስ ነው..ብዙ የተሰሩ ጥናቶችን ከኢንተርኔት እያወጣሁ አነባለሁ፡፡ በሽተኞች፣ ዶክተሮች፣ ሳይካትሪስቶች…አግኝቻለሁ፡፡ እነሱን ሳገኝ ሳላውቀው ምን እንደሆንኩ ታውቂያለሽ? በየቀኑ የማዘወትረው ስፖርት አስጠላኝ፡፡ ብታምኝም ባታምኝም የምግብ ፍላጐቴ ሁሉ እየተዘጋ መጣ፡፡ ኪሎዬም እየቀነሰ ነው፡፡ ለምን መሰለሽ? ከህመምተኞች ጋር ሳወራ፤ የምግብ ፍላጎት እንደሚያጡና ክብደታቸው እንደሚቀንስ ሰማሁ፤ አሁን ሰውነቴ በዛ ነገር ውስጥ እየገባ ነው ያለው፡፡
ከአምስት ወር በፊት ወታደር ገፀባህሪ ያለው ፊልም ለመስራት ለሶስት ወር የወታደር ካምፕ ውስጥ ልትገባ በዝግጅት ላይ እንደነበርክ ነግረኸኛል፡፡ ምን ደረሰ?
ገና ነው፤ በሆነ ምክንያት እንዲቆይ ተደርጓል። ነገር ግን ከአምስት ወር በፊት እንዳልሽው ወታደር ወታደር ሸትቼ ነበር፡፡ በዛን ወቅት የማያቸው ፊልሞች በጠቅላላ የጦርነት “ዋር ሙቪ” ነበሩ። ማንበብ የምፈልገው መፃህፍት ሁሉ ከውትድርና ጋር የተገናኙ ነበረ፡፡ ማየት የምፈልገው ወታደር ነው፡፡ ከሚሊተሪ ነክ ሰዎች ጋር መዋል ጀምሬ ነበር። እነሱን መስማት ማድመጥ ነበር ስራዬ፡፡ ለሶስት ወር ስልጠና ልንገባ ወደ አዋሽ አካባቢ ካምፕ ሁሉ ተዘጋጅቶልን ነበር፡፡ ይህን ማድረጌ ካራክተሩን በቀላሉ ማግኘት እንድችል ይረዳኛል፡፡ ጊዜው ሲደርስ እሱንም እሰራዋለሁ ብዬ አምናለሁ፡፡
ስታንቶች የሚያስፈለጉት ታዲያ መቼ ነው?
ለምሳሌ እኔ ሞተር ሳይክል መንዳት ባልችል ወይም መኪና ከኋላ የሚከተለው የ”ካር ቼዚንግ” ካራክተር ያለው ፊልም ልስራ ብል..ስታንቶች ያኔ ይመጣሉ፡፡ ስታንቶች ለአክተሩ በጣም ከባድ የሆኑ ልዩ ክህሎት የሚጠይቅበት ቦታ ላይ ነው የሚያስፈልጉት፡፡ ካልሆነ ራስሽ ብትሰሪው ይመረጣል፡፡ እኔ ራሴ ብሰራው እመርጣለሁ፡፡ ደስ የሚለውን…እስከ አሁን በስታንት የተሰራ የለም..ራሴ ስታንት ሆኜ ነው የምሰራው /ሳቅ/
እስከ አሁን ከሰራኋቸው ፊልሞች ምርጥ “ማስተርፒስ” የምትለው ፊልም የትኛው ነው?
ሁሉም በቂ ዝግጅትና ጊዜ ተወስዶባቸው..ወድጃቸው..በጥናትና በፍቅር.. ተለፈቶባቸው፣ በተለያየ መንፈስና ከአካባቢ የተሰሩ ናቸው፡፡
ፊልም የሙሉ ጊዜ ስራህ ይመስለኛል..
አዎ፡፡ ፊልም ብቻ ነው የምሰራው /ሳቅ/
የምትጠይቀው ክፍያ አይቀመስም ይባላል፡፡ ለአንድ ፊልም ስንት ትላለህ?
ክፍያ ላይ ደህና ነኝ፡፡ ከመቶ ሺ በላይ ነው። የዓመት ቀለብ ናት፤ እሷን እየቆረጠምኩ.. ሌላ የሚመጥነኝ ፊልም እስኪመጣ እጠብቃለሁ፡፡
ለፊልም ብለህ በምትለማመዳቸው አንዳንድ ነገሮች ለምሳሌ መጠጥ፣ ሲጋራ ሱስ ተይዘህ ለመላቀቅ የተቸገርክበት ሁኔታ የለም?
/ሳቅ/ ከጫቱም፣ ከሲጋራውም፣ ከድራጉም.. ባጠቃላይ ከየትኛውም ሱስ የለሁበትም፤ እግዚአብሄር ይመስገን፡፡ ሱስ ካልሽው ግን የስፖርት ሱስ አለብኝ..ስራ ከሌለኝ አብዛኛውን ጊዜዬን ጂም ነው የማሳልፈው፡፡ ምክንያቱም ትወና ለእኔ የማይንድ ስቴትና (አዕምሮአችን) የፊዚካል ባዲያችን (አካላችን) ሃርመናይዤሽን ነው ብዬ ነው የማስበው። የሁለቱም ጥምረት ነው፡፡ ሁለትም እኩል መገንባት (መታነፅ) አለባቸው፡፡ ሁለትን ቢውልድ አፕ የሚያደርግ ተዋናይ አሪፍ ተዋናይ ይሆናል ይባላል፡፡ በትርፍ ጊዜዬ መፅሃፍ አነባለሁ። ድሮ ፊክሽን ነበር፤ አሁን የህይወት ታሪኮች (ባዮግራፊ) ፍልስፍና፣ (ሳይኮሎጂ) መፃህፍትን አነባለሁ፡፡ የግጥም መፃሃፍትም እሞካክራለሁ፡፡
መፃፍ ላይስ እንዴት ነው?
አጫጭር ልቦለዶችን እፅፋለሁ.. እሞክራለሁ፡፡ በፍቅር ነው የምወደው፡፡
ወደፊት በመፅሃፍ መልክ ይወጣሉ?
አዎ አስባለሁ፡፡ የተወሰኑ አሉኝ.. በቅርቡ ይታተማል፡፡
የፊልም ስክሪፕት መፃፍና ዳይሬክት ማድረግስ?
“የፕሬዚደንቱ ምስጢሮች” የሚለውን አጭር ታሪክ ዳይሬክት አድርጊያለሁ፡፡ በ2000 ዓ.ም. አካባቢ የአጭር ልቦለዶችን የአረትኦት ስራ ሰርቻለሁ፡፡ ሁለት ፊልሞችን ፅፌያለሁ.. ‹‹ልዕልት” እና “የሞሪያም ምድር›› የእኔ ድርሰቶች ናቸው። አሁን ግን ሙሉ በሙሉ በትወና ስራ ውስጥ ተመሰጥኩ፡፡
በተለይ በእኛ አገር በፊልም ውስጥ ለመተወን የሚያስቸግሩ አንዳንድ ነገሮች አሉ፡፡ ለምሳሌ ከንፈር ለከንፈር መሳሳም አንተ ይሄን ትደፍራለህ?
እንደነዚህ አይነት ነገሮች በርግጥ ትንሽ ከባድ ናቸው፡፡ ከባህላችን ጋር አይሄዱም፡፡ እንደዚህ ዓይነት ነገሮችን አልሞክርም፡፡ ብዙ ነገር በካሜራ ይሸወዳል እንጂ ይከብዳል፡፡ የቆምኩበት መሬት ወይም ባህላዊ መሰረት (ግራውንድ) ማን ነው ብዬ ነው የማስበው። የቆምኩበት ግራውንድ አሜሪካኖች ናቸው… ኢትዮጵያውያኖች? የምሰራው በኢትዮጵያውያን ግራውንድ ነው፡፡ አበሾች ነን። እኔም የዚህ ማህበረሰብ ውጤት ነኝ፡፡ ያደግሁት ሁሉ ነገር ሽፍንፍን ባለበት ማህበረሰብ ውስጥ ነው። እንደ አርት ግን ትክክል ነው፤ መሰራት አለበት፡፡
ፖለቲካ ላይ እንዴት ነህ? ብዙ አርቲስቶች “ፖለቲካና ኤሌክትሪክ በሩቁ” የሚሉ ይመስላል፡፡ አንተስ?
ፖለቲካ ከባድ ነገር ነው ብዬ አስባለሁ፡፡ እኛ እንደምናስበው ዓይነት ጨዋታ ላይሆን ይችላል፡፡ ሁሉም ለሆነ ነገር ይፈጠራል፡፡ አርቲስት፣ እግር ኳስ ተጫዋች.. አንዳንዱ ደግሞ ለፖለቲካ ይፈጠራል። ለዛ የተፈጠሩ ሰዎችን አከብራለሁ፤ አደንቃለሁ። እንደሌላው ሞያ ማለት ነው፡፡ ብዙ ጊዜ እኛ አድናቆት የሚኖረን ለአርት ለተፈጠረ ሰው ሊሆን ይችላል፡፡ ለምንድን ነው ለፖለቲካ የተፈጠረን ሰው የማናደንቀው? አንዳንድ ሰዎች ለፖለቲካ ተፈጥረዋል ብዬ አስባለሁ፡፡ እንደዚህ ዓይነት ሰዎችን ከልቤ አደንቃለሁ፡፡
በአኗኗርህ ምን አይነት የህይወት ስታይል ትከተላለህ?
ቀለል ያሉ አለባበሶች ይማርኩኛል፡፡ ህይወቴ በራሱ ሲምፕሊ ሲቲ የተከተለ ነው፡፡ በግል ህይወቴ የተወሳሰበ ነገር የለኝም፡፡ በኑሮዬም.. በብዙ ነገር… ስለብስም ቀለል ማለት ይመቸኛል፡፡ ግን ራሴን ሳጠናው ደግሞ አንድ ካራክተር አግኝቼ በልምምድ ላይ ከሆንኩ የዛ ካራክተር ስታይል ሲንፀባረቅብኝ አስተውላለሁ፡፡ እስከ አሁን በዲዛይነር የመልበስ ባህላችን ገና ነው፤ የሚያለብሰኝ ካገኘሁ ግን አልጠላም፡፡
አንተ አሪፍ የምትላቸው አሉ? እንደተመልካች ባለሙያ ማለቴ ነው…
ተይ! ከጓደኞቼ ጋር ታጣይኛለሽ፡፡ ግን ካስገደድሽኝ ከአስር አይበልጡም፤ እስከ አሁን ከአየሁዋችው፡፡
የኢትዮጵያ ፊልሞች የእድገት ደረጃ እንዴት ታየዋለህ?
የኢትዮጵያን ፊልም ኢንዱስትሪ እንደዥዋዥዌ ነው የማየው፡፡ በጣም ወደፊት የተራመደ ፊልም ታያለሽ፡፡ በተራመደበት ፍጥነት ተመልሶ ደግሞ ወደ ኋላ ይሄዳል፡፡ ብዙ ጊዜ ከጓደኞቼ ጋር ሳወራ ይህንኑ ነው የምለው፡፡ የሆኑ ፊልሞች ይዘውት ይወጣሉ፤ የሆኑ ፊልሞች ወደላይ ይዘውት ይወርዳሉ፡፡
ፕሮፌሽናል የፊልም ሃያስያን አለመኖራቸው ለዚህ አስተዋፅኦ አድርጓል ትላለህ?
በጣም ቆንጆ ጥያቄ ጠየቅሽኝ፡፡ በርካታ ሃያሲያንን እንፈልጋለን፡፡ በነገራችን ላይ ሃያሲው  ከፊልም ባለሞያዎቹ የተሸለ እውቀት ያለው መሆን አለበት፡፡ እንጂ ዘለፋ ሂስ ሊሆን አይችልም፡፡ በዘለፋ ምንም ማስተማር አትችይም፡፡ ፖዘቲቭና ኔጌቲቭ ጎኑን የሚነግረን፣ ሞያዊ አስተያየት የሚሰጠን ነው የእውቀት ሰው፡፡ እንደዚህ አይነት ሃያሲያን ቢኖሩን ጥሩ ነበር፡፡ ማርክ ትዌይን ስለሃያሲ ያለው አንድ አባባል አለ፡- “ከፊት ከፊት እየሄደ ለደራሲው መንገድ የሚያሳይ ትክክለኛ ሃያሲ ነው” ይላል፡፡ ቀሽም ሃያሲ ከኋላ ከኋላ እየተከተለ ባለሙያውን የሚገፋው ነው። ለእኛ የሚያስፈልገን ከፊት ለፊት እየሄደ መንገዱን የሚጠርግልን ሃያሲ ነው እንጂ የሚገፋ ምን ያደርጋል። የፊልም ኢንዱስትሪው እንዲያድግ እንደዚህ ዓይነት ሰዎች የግድ ያስፈልጋሉ፡፡ ራሱ ሂስ ‹‹ሞያዊ አስተያየት›› ስለሆነ ማለት ነው፡፡
ምን አዲስ ስራዎች እንጠብቅ?
ሁለት ስራዎች አሉ፡፡ ከቶም ፊልም ፕሮዳክሽን ጋር የሰራሁት አንድ ፊልም አለ፡፡ ታሪኩ ስለ አንድ ሃብታም ወጣት ነው፡፡ የተለየ አይነት ባህሪ ያለው ነው.. ትወድታላችሁ፡፡ ሁለተኛው እኔና ሰለሞን ቦጋለ የሰራነው ‹‹የፀሃይ መውጫ ልጆች›› የተሰኘ ፊልም ሲሆን የቢንያም ወርቁ ድርሰት ነው፡፡ በዓይነቱም በይዘቱም ለየት ያለ ነው፡፡ ..ለመስራት በጥናት ላይ ነኝ ያልኩሽ የድራግ አዲክትድ ካራክተር ደግሞ የፍፁም አስፋው ፊልም ነው፡፡ ለጊዜው እነዚህ ናቸው፡፡
ሃሳብ የለህም?
በማውቀው ቋንቋና በለመድኩት ባህል ላይ ስሰራ ደስ ይለኛል፡፡ በትምህርት በኩል ግን በተለይ ከትወና ጋር በተገናኘ ስኮላርሽፖችን ለማግኘት ሁልጊዜ ራሴን ማሳደግ እፈልጋለሁ፡፡ ለራሴ ብቻ ሳይሆን በአገሬም የትወና ፍላጎትና ጥማት ያላቸውን ሰዎች ማስተማር እፈልጋለሁ፡፡ ለዚህ ነው ከዚህ በፊት ተዋናይ ለመሆን ለሚፈልጉ ሰዎች መፅሃፍ ተርጉሜ ያሳተምኩት፡፡
የመፅሃፉ ርዕስ ምንድን ነው?
‹‹መሰረታዊ የትወና መማሪያ›› የሚል መፅሃፍ ነው፡፡ ወደ ትወና በስፋት እየገባሁ በመጣሁ ጊዜ ሙያው ባህር እየሆነና ብዙ ልፋት የሚጠይቅ እየሆነ መጣብኝ.. ያኔ በመሃይም ዕውቀቴ ትወና የጀመርኩ አካባቢ ያወቅሁ መስሎኝ ነበር፡፡ እየሰራሁ በመጣሁ ቁጥር እየሰፋብኝ ነው የመጣው፡፡ ስፋቱን ለማጥበብ መማር አለብኝ፡፡ እድሉን ባገኝ ደስ ይለኛል፤ እስከዚያው በአጠገቤ ያሉትን መፅሃፍት እያነበብኩ እቆያለሁ፡፡
የውጭ ፊልሞችን ትመለከታለህ? የትኞቹን ዘውጐች ትመርጣለህ? የትኞቹን የሆሊውድ አክተሮችስ ታደንቃለህ?
የውጪ ፊልሞች በጣም አያለሁ፡፡ አንድ መፅሀፍ ላይ እንዳነበብኩት አንድ ሰው ፊልም ሰሪ ለመሆን ከፈለገ ፊልም ማየት ነው የሚያስፈልገው። የፊልም ሜከር ትምህርት ቤቱ ራሱ ፊልም ማየት ነው፡፡ የአሜሪካ ፊልሞች እጅግ ይመስጡኛል። የድራማ ዘውግ ፊልሞች አድናቂ ነኝ፡፡ ድራማ የሚያነጣጥረው ሪያሊስቲክ በሆኑ ነገሮች ላይ ነው፡፡ ንፅፅሩም በሁለት መሃል ያሉ እውነቶችን እንድትመርጪ ነው የሚያደርገው፡፡ ድራማ ለተዋናዩም፣ ለአዘጋጁም፣ ለፀሃፊውም ከባድ ነው ይባላል፡፡ ከሆሊውድ አክተሮች የማደንቀው… ከወጣቶቹ ኩባ ጉዲንግ፣ ኤድዋን አልበርተን፣ ማትዴመንን ሲሆን ከፊልም “ሮሚዬዝ ብሊዲንግ” አደንቃለሁ፡፡ ጋሪአልድ ማን የተጫወተበት… ከአውሮፓ ፊልሞች “ሲኒማ ፓራዲዞ” የተባለውን የጣሊያኖች ፊልም አደንቃለሁ። በነገራችን ላይ የአውሮፓ ፊልምም አያለሁ፡፡ ብዙዎቹ የእንግሊዝኛ ሰብታይትል ስላላቸው ቋንቋ ላይ ችግር የለም። የኢራን ፊልሞች በጣም ነው የምወዳቸው። የሚገራርሙ ናቸው፡፡ የአውሮፓ ፊልሞች ለጥበብ አዳኞች ነው የሚሰራው፡፡ ለእኔ አንደኛ ፊልሜ ግን “ሲኒማ ፓራዲዞ” ነው፡፡ በዚህ አጋጣሚ ለአንባቢያን ይህንን ፊልም እጋብዛለሁ፡፡ የፊልም ትምህርት በጣም እየተሰጠ ያለው በአሜሪካ ነው። አውሮፓዎችም አላቸው፡፡ ግን ብማር ብዬ የማስበው አውሮፓ እንግሊዝ አገር ነው፡፡ የእነሱ ፊልሞች በጣም ጠንካራ ናቸው፡፡ ለጥበብ አዳኞች የሚሰራ ነው፡፡ ስኬፒስት ኦዴንሶች አይደለም የሚበዙት፡፡ የሚሰሩት ፊልሞች “ጥበብ ..ለጥበብ ደንታ” የሚባሉ አይነት ናቸው። እነሱ ሲያሾፉ ምን ይላሉ? “ኮሜርሺያል የሆነ የአውሮፓ ፊልም ሆሊውድ ውስጥ ቢሄድ የጥበብ ፊልም ይሆናል” ይላሉ፡፡ እንደዚህ ነው አውሮፓውያን አሜሪካኖቹን የሚንቋቸው፡፡ የሆሊውድ ዳይሬክተሮች ራሳቸው ፊልም የአውሮፓውያንን ፊልም ነው የማያዩት፡፡
ትያትር ላይ ስትተውን አተታይም፡፡ ለምንድነው?
መድረክ ላይ ሰርቼ አላውቅም፡፡ ትያትር የማከብረው ሞያ ነው፤ ዘልዬ መግባት አልፈልግም። ምናልባት ወደ ትያትር ብመጣ እንኳን ስለቲያትር የተወሰኑ ነገሮች በደንብ አውቄ መሆን አለበት፡፡ ምክንያቱም የፊልም አክቲንግ እና የመድረክ አክቲንግ የተወሰነ ልዩነት አላቸው፡፡ ልዩነቱን አጥብቤ ነው ወደ ቲያትር መግባት የምፈልገው፡፡ ለአንድ የፊልም አክተር ከዘጠና ፐርሰንት በላይ ያለው የስሜት ጨዋታ አይን ውስጥ ነው፡፡ ወደ ትያትር ስትመጪ ግን ሰፊ ነው፡፡ ብዙ ሰው ነው ያለው፡፡ ለዛ ሁሉ ሰው ስሜትሽ እንዲጋባበት የምታደርጊው በአይንሽ አይደለም፤ የእጅ እንቅስቃሴዎችን፣ የፊት ገፅታዎችን ትጠቀሚያለሽ …የፊልም ትወና በካሜራ ክሎዝ አፕ እየታየ ነው ጨዋታው፡፡
ፊልም አክት አይደረግም ኑሮ ነው የሚኖረው። “ኖ ፌስ አክቲንግ” ይባላል፡፡ ፊትሽ ላይ አክት አያስፈልግም፡፡ አይን ውስጥ ነው ብዙ ስሜቶች የሚያልቁት፡፡ በጥቅሉ ግን እኔ ቅኝቴም፣ የተጠመቅሁበትም ፊልም ነው፡፡

Published in ጥበብ