በታሪካዊው የመርካቶ ዘጋቢ ፊልም ታሪካዊ ስህተቶች ተካትተዋል

የአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ባህልና ቱሪዝም ጽሕፈት ቤት ያሰራው ዘጋቢ ፊልም “መርካቶና አዲስ ከተማ” የሚል ርዕስ አለው፡፡ የ1 ሰዓት ከ20 ደቂቃ እርዝማኔ ያለው ዘጋቢ ፊልሙ፤ በ“እመቤት መልቲሚዲያ ፕሮዳክሽን” የተዘጋጀ ሲሆን አርቲስት እመቤት ወልደገብርኤል ናት  የምትተርከው፡፡
በዲቪዲ የቀረበው ዘጋቢ ፊልም ለሁለት ዓላማዎች የተዘጋጀ ነው፡፡ ባለፈው ዓመት መርካቶ የተመሠረተችበትን  75ኛ ዓመት ኢዮቤልዩ በዓል ለማክበር፣ የተለያዩ አካላት ልዩ ልዩ እቅዶችን ሲነድፉ ቢቆዩም እቅዶቹ ሳይተገበሩ ቀርተዋል፡፡ ዘጋቢ ፊልሙ የተዘጋጀበት አንዱ ዓላማም ለበዓሉ ማድመቂያ  ነበር፡፡
ሁለተኛው ዓላማ ደግሞ በልማት ሳቢያ እየጠፋ ያለውን የመርካቶ የግብይት ሥርዓት፣ እንቅስቃሴና ታሪካዊ ቅርሶች በምስል ቀርፆ ለቀጣይ ትውልድ ለማስተላለፍ ነው፡፡ ይሄኛው ዓላማ በእርግጥም ተሳክቷል፡፡ ዘጋቢ ፊልሙ ተሰርቶ በዲቪዲ ወጥቷል። ነገር ግን በፊልሙ ላይ ስለቅርስ ዋጋ የተሰጡት ምስክርነቶችና ማብራሪያዎች እርስ በርሳቸው የሚቃረኑ ናቸው፡፡
በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም ባልደረባ ረዳት ፕሮፌሰር አህመድ ዘካሪያ በሰጡት ምስክርነት፤ “ገበያን በቅርስነት የምንይዝበት ምክንያት የሰው ልጅ እንቅስቃሴ ያለበት ቦታ ስለሆነ ነው፡፡ ገበያ ለብዙ ነገር ምክንያት ነው፡፡ ዕቃ፣ ሀሳብ፣ ፍቅር፣ ቴክኖሎጂና የእውቀት ልውውጥ ይካሄድበታል፡፡ ገበያ ሕብረተሰብን ነው የሚያቅፈው፡፡ ሕንፃ የተወሰኑ ግለሰቦችን ነው የሚይዘው፡፡ ገበያ ስንል ግን ሁሉንም ጠቅልሎ የሚያቅፍ ነው፡፡”  
መርካቶ በሁሉም የኢትዮጵያ ግዛት ያሉት ነጋዴዎች የሚመጡባት የንግድ ቦታ ናት ያሉት ረዳት ፕሮፌሰር አህመድ ዘካሪያ፤ ወደ መርካቶ እየገባ የሚወጣው ሕዝብ እንደ አገር ውስጥ ቱሪስት ታይቶ የገበያው ዕድገትና ልማትም ይህንን ግምት ውስጥ ያስገባ እንዲሆን በዘጋቢ ፊልሙ ላይ አሳስበዋል። በአዲስ መልክ የምትለማው መርካቶ የመናፈሻ ቦታዎች እንዲኖሯትና ንጽሕናዋ እንዲጠበቅም አደራ ብለዋል - ምሁሩ፡፡  
“የውጭ አገር ቱሪስት አዲስ አበባ ሲመጣ መርካቶን ሳይጎበኝ አይሄድም” የሚሉት ደግሞ በክፍለ ከተማው ባህልና ቱሪዝም ጽሕፈት ቤት፣ የቱሪስትና ልማት ቅርስ አስተዳደር የስራ ሂደት መረጃ ኦፊሰር ወ/ሮ ዙፋን ፍቅሬ ናቸው፡፡ ቅርሶች ያለፈውን ትውልድ የጥበብ አሻራ ለመጪው ትውልድ የሚያስተላልፉ ናቸው የሚሉት ወ/ሮ ዙፋን፤ እነዚህን ቅርሶች የመጠበቅ ኃላፊነት የሁሉም ሕብረተሰብ ክፍል ግዴታ ነው ብለዋል፡፡
ቱሪስቶችን የሚስበው ታሪክና ቅርስ ነው ያሉት የስራ ሂደት መሪዋ፤ “የውጭና የአገር ውስጡን ቱሪስት ብቻ ሳይሆን በመርካቶ ለሚገለገለው ሕብረተሰብም ገበያዋ ምቹ እንድትሆንለት ቴክኖሎጂ-ተኮር  አሰራር መዘርጋት አለበት” ሲሉ በአፅንኦት ተናግረዋል፡፡
በዘጋቢ ፊልሙ ላይ  የክፍለ ከተማው ባህልና ቱሪዝም ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አበራ ኃ/ማርያምም አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡ መርካቶ የአገራችን ትልቋ ገበያ በመሆኗ ምክንያት የቱሪስቶችን ቀልብ ትስባለች ያሉት የቢሮ ኃላፊው፤ እንዲህ ዓይነት ቅርሶችን ጠብቆ ማቆየት በብዙ አገሮች የተለመደ መሆኑን ፊሊፒንስን በምሳሌነት በመጥቀስ ያስረዳሉ። “በፊሊፒንስ ማኒላ በሚባል ቦታ እንዲሁም በአንትራሞስ አካባቢ ታሪካዊ የሆኑ የግንባታ ስራዎች ስለሚገኙ፤ ያንን ቅርስ ከልለው በማቆየት በዙሪያው አዲስ የሰፈራ መንደር ለመስራት ሞክረዋል” ብለዋል፡፡
በዕድገት እንቅስቃሴ ውስጥ ጥንታዊ ነገሮችና አስተሳሰቦች እርስ በእርስ የሚቃረኑበት ሁኔታ አለ የሚሉት አቶ አበራ ኃ/ማርያም፤ “ዕድገትን መግታት አይቻልም፤ መርካቶ ትልቅ ገበያ እንደመሆኗ ትልቅ አገልግሎት መስጠት አለባት፡፡ የነጋዴውም የተገበያዩም ቁጥር ከፍተኛ ከመሆኑ አንፃር ገበያዋ መለወጥና ማደግ አለባት፡፡ አሁን ጥያቄው ታሪካዊቷን መርካቶ እንዴት አድርገን ነው በቅርስነት ለትውልድ የምናስተላልፈው?” ሲሉ ይጠይቁና ራሳቸው አስገራሚ መልስ ይሰጣሉ፡፡
አዲስ አበባ  ከጣሊያን ወረራ በፊት፣ በጣሊያን ወረራ ወቅትና ከወረራው በኋላ በሦስት ዘመን ሊከፋፈል የሚችል ታሪክ አላት ያሉት አቶ አበራ፤ መርካቶም በዚህ ውስጥ ስላለፈች ሦስቱን ዘመን የሚያሳዩ ቅርሶችን መርጦ በማስቀረት ሌላውን ፎቶግራፍ በማንሳት፣ ቪዲዮ በመቅረጽ ዶክመንት አድርጎ ልማቱ መፋጠን እንዳለበት ያሳስባሉ - ዘጋቢ ፊልሙ የተዘጋጀበት አንዱ ምክንያት ይኸው መሆኑን በመግለፅ፡፡
በዘጋቢ ፊልሙ ላይ መርካቶ ውስጥ እየጠፉ ያሉ ነገሮች እየተበራከቱ መምጣታቸውን የሚጠቁሙ  መረጃዎችና ምስክርነቶች ቀርበዋል፡፡ “ዱቄት ተራ” ሥሙን ብቻ ይዞ እንደቀረ፣ ምዕራብ ሆቴል አካባቢ የሚገኘው “ጌሾ ተራ” በመጥፋት ሂደት ላይ እንደሆነ፣ በቅርስነት ተመዝግቦ የነበረው ሲኒማ ራስ ፈርሶ አዲስ ሕንፃ ሊገነባበት እንደታቀደ፣ ከ “ቄጠማ ተራዎች” አንዱ ሙሉ ለሙሉ እንደጠፋ፣ በቆጮ ንግድ ሁለት ፀጉር አብቅያለሁ ያሉት ወይዘሮ በልማቱ ምክንያት እንዳይፈናቀሉ ያቀረቡት ተማጥኖ … የመርካቶ ታሪካዊ ቅርስነትና የቱሪስት መስህብነት እያከተመ መምጣቱን ጠቋሚዎች ናቸው፡፡
መርካቶ ምን ትመስል እንደነበር ለመጪው ትውልድ ታሪክ ለማስቀመጥ በተዘጋጀው ዘጋቢ ፊልም ውስጥ ጥቂት የማይባሉ ታሪካዊ ስህተቶች ተካትተዋል፡፡ በንጉሡ ዘመን መርካቶን በአዲስ መልክ ለማልማት ሁለቱ አዳራሾች (የመሀል ገበያ ሕንፃዎች) ፈር-ቀዳጅ የግንባታ ሥራዎች ናቸው መባሉ፤ በፍራሽ ተራ የሚገኘው የሐጂ አህመድ ሳላህ ሻይ ቤት ለመርካቶ የመጀመሪያው ነው የሚል አዲስ ታሪክ መፈጠሩ፤ በቅርስነት ተመዝግቦ የነበረውና ለባቡር መስመር ዝርጋታው ሲባል የፈረሰው የቁጭራ ባንክ የነበረበት መክሊት ሆቴል ሕንፃን ያሰሩት ፊታውራሪ ሀብተጊዮርጊስ ዲነግዴ ናቸው የሚሉና ሌሎችም ከስህተቶቹ መካከል ተጠቃሽ ናቸው፡፡
ለእንዲህ ዓይነት ስህተቶች መፈጠር ዋናው ምክንያት የሚመስለኝ ደግሞ የቀድሞው ዘመን ጥረቶችና ሥራዎች ከአሁኑ ጋር እንዲያያዙ ባለመደረጋቸው ነው፤እንጂማ ባለፉት 20 ዓመታት መርካቶን በቅርስነት እንዴት መጠበቅ እንደሚቻል፣ ለውጥና ዕድገቷ በምን መልኩ መመራት እንዳለበት በተለያዩ ባለ ድርሻ አካላት በጣም ብዙ ሙከራዎች ተደርገው ነበር፡፡
በ1985 ዓ.ም ተለጣፊ ሱቆች ከመርካቶ የተነሱበት አብይ ምክንያትም ገበያዋን የማልሚያ ጥርጊያ መንገድ ለማመቻቸት ነበር፡፡ ዛሬ በጨረታ መሬት ለመውሰድ ተጋፊው የበዛበት የሊዝ ፖሊሲ፣ ለመጀመሪያ ጊዜ በ1986 ዓ.ም ሲወጣ ያለ ጨረታ መሬት በመውሰድ በዕድሉ እንድትጠቀም ግብዣ የቀረበው ለመርካቶ ነበር፡፡ ዘጠነኛው ማስተር ፕላን በ1995 ዓ.ም ሲፀድቅ መርካቶ ውስጥ መፍረስ ያለባቸውና የሌለባቸው ቤቶች ተለይተው ቀጣይ መልኳ ምን መምሰል እንዳለበት የሚያሳይ ሞዴል ተሰርቶላት ነበር፡፡
በ1998 ዓ.ም አዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር፣ አዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ፣ ጂቲዜድና የንግዱ ሕብረተሰብን የሚወክሉ አካላት ያሉበት የመርካቶ ማሌኒየም ግብረ ኃይል ተዋቅሮ የነበረ ሲሆን ካከናወናቸው ተግባራት መካከልም “Merkato Guide Book” በሚል ያሳተመው መፅሃፍ ተጠቃሽ ነው፡፡ ባለ አደራው ከንቲባ በነበሩበት ጊዜም መርካቶን ማዕከል ያደረጉ ሥራዎች ተሰርተዋል፡፡ ዛሬም እየተሰራ ነው፡፡
የቀደመው ዘመን ሥራ ከአሁኑ ጋር እየተያያዘ፣ እየጎመራ፣ እየበሰለ ባለመምጣቱ ግን መርካቶን በልዩ የቅርስ ቦታነት መጠበቅ የማይቻልበት ዘመን ላይ ደርሰናል፡፡
መርካቶ የሚታዩና የሚዳሰሱ ብቻ ሳይሆን የማይታዩና የማይዳሰሱ ብዙ እሴቶች ባለቤት ነበረች፡፡ የመርካቶ ብቻ ሊባል የሚችል ገጽታና ባህልም ነበራት፡፡ በብድር፣ በእቁብ፣ በዕድር … የተሰናሰሉ  ማህበራዊ መስተጋብሮች ጎልተው የሚታዩባት የገበያ ሥፍራም ነበረች፡፡
“መርካቶና አዲስ ከተማ” በሚለው ዘጋቢ ፊልም ላይ እንደተገለፀው፤ የመርካቶ ታሪክ በበራሪ ወረቀት፣ በመጽሔትና በተንቀሳቃሽ ምስል ተቀርፆ የሚቀመጥ ሲሆን አዲሷ መርካቶ በኒውዮርክ፣ ሕንድ፣ ብራዚል፣ ቻይና፣ ዱባይ እና በመሳሰሉት አገራት እንዳሉት የገበያ ስፍራዎች ሆና ትለማለች። ይሄንንም ለማሳካት  መንግሥት፣አዲስ አበባ ከተማ አስተዳደርና ክፍለ ከተማ እየተጉ እንደሆነ ተጠቁሟል፡፡ አሁንም ግልፅ ያልሆነልኝ ግን በዘጋቢ ፊልሙ ላይ ስለ ቅርስና ዕድገት የተሰጡት እርስ በእርስ የሚጋጩ መረጃዎች  ናቸው፡፡ 

“የተሳፋሪው ፍላጎት የሆነ መሬት ላይ ማረፍ ብቻ  ነበር”
በሃዋሳ ከተማ በተለምዶ ኬሮ ሰፈር እየተባለ በሚጠራው አካባቢ ተወልዶ ያደገው ወጣት ምህረቱ ገብሬ፣ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርቱን በቀድሞው ሀዋሳ ኮምቦኒ የመጀመርያ ደረጃ ት/ቤት ነው የተከታተለው። የሁለተኛ ደረጃ ማጠናቀቂያና የመሰናዶ ትምህርቱንም በቅዱስ ዳንኤል ኮምቦኒ የሁለተኛ ደረጃና የመሰናዶ ት/ቤት አጠናቋል። ከሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ በ2001 ዓ.ም በሲቪል ምህንድስና የመጀመሪያ ዲግሪውን ካገኘ በኋላም፤ እስከ 2004 ዓ.ም ድረስ በዩኒቨርሲቲው ውስጥ በመምህርነት አገልግሏል፡፡ በመቀጠልም ነጻ የትምህርት ዕድል በማግኘት፣ ወደ ጣሊያን አምርቶ የሁለተኛ ዲግሪ ትምህርቱን በመከታተል ላይ ይገኛል፡፡
በቅርቡ ለእረፍት ወደ አገሩ የመጣውና በሃዋሳ ቆይቶ ወደ ጣሊያን ለመመለስ አውሮፕላን የተሳፈረው ምህረቱ፣ ባለፈው ሰኞ በረዳት አብራሪው ተጠልፎ ጄኔቭ እንዲያርፍ በተደረገው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ቦይንግ 767 አውሮፕላን ውስጥ ከነበሩት 200 ገደማ ተሳፋሪዎች ውስጥ አንዱ ነበር፡፡ በአሁኑ ወቅት በጣሊያን የሚገኘው ምህረቱ፣ የጠለፋውን አጋጣሚ በተመለከተ ጋዜጠኛ አንተነህ  ይግዛው በኢ-ሜይል ለላከለት ጥያቄዎች የሰጠውን ምላሽ  እንደሚከተለው አጠናቅረን አቅርበነዋል፡፡  

የጉዞው አጀማመር ምን ይመስል ነበር?
አርፍዶ ወደ አውሮፕላን ጣቢያ መምጣት የሚያደርሰውን ጣጣ ስለማውቀው፣ አውሮፕላኑ ከሚነሳበት 50 ደቂቃ ያህል ቀድሜ ነበር የተገኘሁት፡፡ ከምሽቱ አራት ሰዓት አካባቢ ማለት ነው፡፡ ያው ጉዞው ሲጀመር እንደሌላው ጊዜ ሁሉ ስርአቱን የጠበቀና ሰላማዊ ነበር።  አውሮፕላኑ ከበራራ ሰዓቱ ሰባት ደቂቃ ያህል ዘግይቶ ነበር የተነሳው።
አውሮፕላኑ ውስጥ አቀማመጥህ እንዴት ነበር? የት አካባቢ ነው የተቀመጥከው?
የመቀመጫዬ ቁጥር 27F ነበር። የተሳፈርንበት ቦይንግ 767 በርዝመቱ ትይዩ 7 የመቀመጫ መደዳዎች አሉት። ሁለት ሁለት መደዳዎች በሁለቱም ጥጎች እና ሶስት መደዳዎች መሃል ላይ። እኔ የተቀመጥኩት ከመሃል ሶስቱ መደዳዎች የመሃለኛዋ ወንበር ላይ ነበር። ከበስተግራዬ ያለችው ወንበር ላይ የተቀመጡት ሪካርዶ የተባሉ የ85 አመት የዕድሜ ባለጸጋ ጣሊያናዊ ነበሩ፡፡ በቀኜ በኩል እንዲሁ በግምት በስድሳዎቹ ዕድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ ሌላ ጣሊያናዊ ተቀምጠው ነበር፡፡ ተዋውቀን ነበር፣ አሁን ግን ዘንግቼዋለሁ። ኢትዮጵያን ተዟዙረው እንደጎበኟት እያጫወቱኝ ነው ጉዞውን የጀመርነው፡፡
ጉዞውስ  እንዴት ነበር?
እንደማስታውሰው ጉዞው ሲጀመር ሰላማዊ ነበር። ከፓይለቱ ጋርም ግንኙነት (ኮሙኒኬሽን)  ነበረን፡፡ እኔ ድካም ስለተሰማኝ ወዲያው አሸለብኩ፡፡ በረራው ከተጀመረ በግምት ከ1 ሰዓት በኋላ የሱዳን አየር ክልል ውስጥ ይሆናል ብዬ እገምታለሁ. . . መብራት ሲበራ ከእንቅልፌ ነቃሁ፡፡ የምግብ ሰዓት መድረሱ ገብቶኛል። ወደ ፊት አሻግሬ ሳይ ሆስተሶቹ እያስተናገዱ ከእኔ ፊት 4ኛ ይሁን 5ኛ ረድፍ ደርሰዋል። ሁሉም ተዘገጃጅቶ እየተጠባበቀ ነበር። በዚህ መሃል የፕሌኑ ፍጥነት ሲጨምር ይታወቀኛል፡፡ ከፍታዉም ሲጨምር በጆሮዬ ላይ በሚሰማኝ ስሜት አስተዋልኩ። በተሳፋሪዎች ፊት ላይ የመረበሽ ስሜት ሲፈጠር አየሁ። እኛ  ኢኮኖሚ ክላስ ስለነበርን ከፊት ምን እየተካሄደ እንደነበር አላየንም። በኋላ ስሰማ ከፊት የነበሩትም የቢዝነስ ክላስ ተሳፋሪዎች ምንም መረጃ አልነበራቸውም፡፡
ከዚያም በድምጽ ማጉያው የሆነ ድምጽ ተሰማ፡፡ የረዳት አብራሪው ድምጽ ነበር።
“ተሳፋሪዎች ከ 12 ደቂቃዎች በኋላ ሚላን እናርፋለን” አለ ረዳት አብራሪው፡፡ ጥቂት ቆይቶም፣ “ስለተፈጠሩ አንዳንድ መጉላላቶች ይቅርታ እንጠይቃለን” ሲል አከለ-በእንግሊዝኛና በአማርኛ ቋንቋ። የረዳት አብራሪውን ንግግር ተከትሎ የተወሰኑ ተሳፋሪዎች ማጉረምረም ጀመሩ፡፡ አንዳንዶችም ጮክ ብለው ሲያወሩ ይሰሙ ነበር፡፡ ከኔ በስተግራ በኩል ሶስት አራት መደዳዎችን አልፎ ከፊቴ ተቀምጦ የነበረ አንድ ወፍራም ሰው፣ በጣሊያንኛ ቆጣ ብሎ እየጮኸ ተናገረ - “መጀመሪያ ሚላን ሳይሆን ሮም ነው ማረፍ ያለብን ፣ ወደ ሮም ውሰዱን!” በማለት። ሌሎችም የሰውየውን ሃሳብ ደገፉ፡፡ ምክንያቱም አብዛኛው ተሳፋሪ ወደ ሮም ነበር የሚጓዘው። ረዳት አብራሪው ሚላን ላይ እንደምናርፍ መናገሩ ብዙዎችን አበሳጭቶ ነበር፡፡  
እውነቱን ለመናገር፣ እኔ ግን ሚላን እንደምናርፍ ስሰማ ደስ ብሎኝ ነበር፡፡ ምክንያቱም እኔ ሚላን ወራጅ ነኝ፡፡ ረዳት አብራሪው የነገረን አስራ ሁለቱ ደቂቃዎች እየተገባደዱ መሆናቸው ሲገባኝ፣ ከአውሮፕላኑ ለመውረድ መዘገጃጀትና ጓዜን መሸካከፍ ሁሉ ጀመርኩ። ሆኖም  አስራ ሁለቱ ደቂቃዎች አልፈውም አውሮፕላኑ አላረፈም፡፡ ካሁን አሁን ሚላን አውሮፕላን ማረፊያ ደረስን እያልን ስንጠባበቅ፣ ሌላ አስራ ሁለት ደቂቃዎች አለፉ፡፡ አሁንም ሌላ አስራ ሁለት ደቂቃዎች---
ተሳፋሪው ሁሉ ግራ በመጋባት ሰዓቱን ደጋግሞ መመልከትና እርስ በርስ በጥርጣሬ መተያየት ጀመረ። ከአስራ ሁለት ደቂቃዎች በኋላ ሚላን ላይ ያርፋል የተባለው አውሮፕላን፣ ከአንድ ሰዓት ተኩል በላይ በአየር ላይ ቆየ፡፡ የሚገርመው ያን ያህል ጊዜ አየር ላይ መቆየቱ ብቻ አይደለም፡፡ አበራረሩ የተለየ ነበር፡፡ አንዴ ፍጥነቱን ጨምሮ ይከንፋል፣ ከዚያ ደግሞ ፍጥነቱን ይቀንስና ተረጋግቶ ይበራል፡፡ እንደገና ይፈጥናል፣ እንደገና ይረጋጋል፡፡ ግራ ገብቶን እያለን፣ ከመቅጽበት አውሮፕላኑ ማረፊያው ላይ ደርሶ ማኮብኮብ ጀመረ፡፡ ያንን ያህል ግዙፍ አውሮፕላን፣ በዚያች ጠባብ ቦታ ላይ ያለችግር ማሳረፍ መቻሉ፣ የረዳት አብራሪውን ብቃት ያሳያል፡፡ ለማንኛውም አውሮፕላኑ በሰላም አረፈና እኛም እፎይ አልን፡፡
አውሮፕላኑ ካረፈ በኋላ የተሳፋሪዎች ስሜት ምን ይመስል ነበር?
የሚገርመው ነገር፣ አውሮፕላኑ እንዳረፈ በተሳፋሪው ፊት ላይ ከታየው ደስታና እፎይታ በተጨማሪ፣ ተሳፋሪው ለረዳት አብራሪው የሰጠው አድናቆት ነበር፡፡ አብዛኛው ተሳፋሪ ስለረዳት አብራሪው ችሎታ ነበር ተደንቆ የሚያወራው፡፡ በከፍተኛ የአድናቆት ስሜት ተውጠው፣ ለረዳት አብራሪው ያላቸውን አድናቆት በጭብጨባና በፉጨት የገለፁም ነበሩ፡፡ እኔም በደመነፍስ ሳጨበጭብ ነበር፡፡ ሚላን ምድር ላይ በሰላም እንዲያሳርፈኝ ለፈጣሪዬ ያደረስኩትን ጸሎት የማውቀው እኔ ነኝ፡፡
ሚላን እንዳረፋችሁ ነበር የምታውቁት ማለት ነው?
የሚገርመው እኮ እሱ ነው!... አውሮፕላኑ መሬት ከነካ በኋላ ሁሉ፣ ተሳፋሪው በሙሉ ጣሊያን ሚላን እንዳረፈ ነበር የሚያውቀው፡፡ ሚላን እንደምናርፍ ነው ረዳት አብራሪው የነገረን፡፡ ትኬት ከፍለን የተሳፈርነውም ወደ ጣሊያን እንጂ ወደ ስዊዘርላንድ ለመሄድ አልነበረም። በዚህ ቅጽበት ጄኔቭ የምትባል ከተማ በምን ተአምር እንሄዳለን ብለን እናስብ?
ጄኔቭ መሆናችሁን ያወቃችሁት እንዴት ነው?
አውሮፕላኑ በሰላም ካረፈ በኋላ ተሳፋሪው ከጭንቀቱ ተገላግሎ መረጋጋት ጀመረ፡፡ አንዳንዶች ሞባይል ስልኮቻቸውን አውጥተው መነካካት ያዙ። በሞባይላቸው የኢንተርኔት መስመር በመጠቀም ጎግል ማፕ የተሰኘውን የአገራትና የከተሞች ካርታ የሚያሳይ ድረገጽ፣ ጂ ፒ ኤስ ከሚባለው አቅጣጫ ጠቋሚ ቴክኖሎጂ ጋር አያይዘው ሲመለከቱ፣ ፊታቸው ላይ ድንገተኛ መደናገር ሲፈጠር አየሁ፡፡ አንዱ ተሳፋሪ ሞባይሉ ላይ ያየውን መረጃ በመጠራጠር፣ የሌላኛውን ሞባይል ማየት ጀመረ፡፡ “የት ነው ያለነው?” ለሚለው ጥያቄ እርግጠኛ የሆነ መልስ የሚሰጥ ጠፋ፡፡ ግማሹ “ ኦስትሪያ ነን!” ሲል፣ ገሚሱ “የለም ፈረንሳይ ነን!” ብሎ ይመልሳል፡፡ አንዳንዱ “ጀርመን ውስጥ ነው የምንገኘው!” ይላል፡፡ ሌላው “ስዊዘርላንድ ጄኔቭ ነው ያረፍነው!” እያለ ይናገራል፡፡ ጭንቀትና ውጥረት የፈጠረው መደናገር ሊሆን እንደሚችል ያሰብኩት በኋላ ነው፡፡
 ጄኔቭ ማረፋችሁንና አውሮፕላኑ መጠለፉን ያወቃችሁት እንዴት ነበር?
እያንዳንዱ ተሳፋሪ አውሮፕላኑ ያረፈበትን አገርና ከተማ በተመለከተ የየራሱን መላምት እየሰነዘረ ግራ ተጋብቶ ጥቂት ደቂቃዎች አለፉ፡፡ በዚህ መሃል ነው፣ ድንገት የአውሮፕላኑን ዋና አብራሪ ድምጽ የሰማነው። በረራው ከተጀመረ አንስቶ የዋና አብራሪውን ድምጽ ስንሰማ ለመጀመሪያ ጊዜያችን ነበር፡፡ ዋና አብራሪው በጣሊያንኛ ቋንቋ ነበር የሚያወሩት፡፡ በጣሊያን ቆይታዬ የቀሰምኳት ቋንቋ ብዙም የምታወላዳ አልነበረችምና፣ ደቂቃዎችን ከፈጀው የአብራሪው ንግግር የተወሰነችዋን ተረድቼ፣ ቀሪውን ከጎኔ ከተቀመጡት ጣሊያናውያን ጠይቄ ለመረዳት ሞከርኩ፡፡
አብራሪው  ወደመጸዳጃ ቤት ሲወጡ ረዳት አብራሪው በር እንደዘጋባቸው፤ አውሮፕላኑን ለሰዓታት ሲያበር የቆየው ረዳት አብራሪው እንደነበር፤ አውሮፕላኑ ያረፈው ጄኔቭ መሆኑን፤ በተፈጠረው ነገር ማዘናቸውን መግለጻቸውን እንዲሁም እያንዳንዱ ተሳፋሪ የስዊዘርላንድ ፖሊሶች ለሚያደርጉት ምርመራ ተገቢውን ትብብር እንዲያደርግ ጥሪ ማስተላለፋቸውን ነገሩኝ፡፡ ተሳፋሪው ስለ ጠለፋው ያወቀው በዚህ ጊዜ ነው፡፡
ተጠልፋችሁ ያላሰባችሁት ቦታ እንዳረፋችሁ ስታውቁ ምን ተሰማችሁ?
እውነቱን ለመናገር በወቅቱ የሁሉም ተሳፋሪ ጸሎትና ምኞት በረራው በሰላም መጠናቀቁና አውሮፕላኑ አደጋ ሳያጋጥመው ማረፉ ብቻ ነበር፡፡ የተሳፋሪው ፍላጎት የትም ይሁን የት፣ ብቻ የሆነ መሬት ላይ ማረፍና ከጭንቀት መገላገል ነበር፡፡ አስበው እስኪ… ከአብራሪውም ሆነ ከሆስተሶቹ ጋር ምንም አይነት ግንኙነት በሌለበት አደናጋሪ ሁኔታ ውስጥ ነው ለሰዓታት የበረርነው፡፡ ከዚያ ደግሞ… ሮም የማረፍ ዕቅዱ ተሰርዞ፣ ከ12 ደቂቃዎች በኋላ ሚላን እንደምናርፍ ድንገት ተነገረን፡፡ ይሁን ብለን ተቀብለን፣ አስራ ሁለቱን ደቂቃ በጉጉት ስንጠባበቅ ደግሞ፣ ለተጨማሪ አንድ ሰዓት ተኩል ያህል ጊዜ በረራው ቀጠለ፡፡ በዚያ ላይ በረራው ጤነኛ አልነበረም፡፡ አንዴ የሚፈጥን፣ ሌላ ጊዜ ደግሞ የሚረጋጋ ምቾት የማይሰጥ በረራ ነበር፡፡
በዚህ ሁኔታ ውስጥ ያለ ተሳፋሪ፣ የትም ቢሆን ማረፍን እንጂ፣ማረፊያ ቦታውን አይመርጥም፡፡ እኔም ሆንኩ ሌሎች ተሳፋሪዎች ጉዳዩን ያወቅነው፣ ጠለፋው ከተጠናቀቀና አውሮፕላኑ ጄኔቭ ውስጥ በሰላም ካረፈ በኋላ ዋና አብራሪው ሲነግሩን በመሆኑ እምብዛም አልተደናገጥንም፡፡  
ከአውሮፕላኑ ስትወርዱ የነበረው ሁኔታ ምን ይመስላል?
አውሮፕላኑ ጄኔቭ ካረፈ በኋላ በግምት ለአንድ ሰአት ያህል በሩ ሳይከፈት ቆሞ ቆየ፡፡ ዋና አብራሪው ሁሉንም ነገር በግልጽ ከነገሩን በኋላ፣ ከእግር ጣታቸው እስከ ራስ ጸጉራቸው የብረት ጭንብል የለበሱ ሰዎች፣ በሩን በርግደው በፍጥነት ወደ ውስጥ ገቡ። አገባባቸውና መላ ሁኔታቸው አክሽን ፊልም የሚሰሩ ነበር የሚመስሉት፡፡ ሁኔታው እጅግ ያስጨንቅ ነበር፡፡ በመካከል አንደኛው ፖሊስ በእጁ በያዛት አነስተኛ የድምጽ ማጉያ ፈረንሳይኛ በሚመስል እንግሊዝኛ መናገር ጀመረ።
“ዚስ ኢዝ ኤ ፖሊስ ኦፔሬሾን። ዶንት ሙቭ!... ፑት ዩር ሃንድስ ኦን ዩር ሄድ!... ዶንት ሜክ ሙቪ ባይ ሞባይል (በሞባይል አትቅረጹ ማለቱ ነው)” ሲል ቀጭን ትዕዛዝ አስተላለፈ፡፡ ሁሉም እጆቹን አናቱ ላይ ጭኖ ድምጹንም አጥፍቶ አቀረቀረ፡፡ ተሳፋሪው በፖሊሶቹ መሪነት አንድ በአንድ ከአውሮፕላኑ እየወረደ፣ ሁለት ሁለት ጊዜ ተበርብሮ ተፈተሸ፡፡
ፍተሻው እንደተጠናቀቀም በትላልቅ ሽንጣም አውቶብሶች እየጫኑ ወደ ተርሚናሉ ወሰዱን፡፡ ተርሚናሉ ላይ ስንደርስ የሚገርም አቀባበል ተደረገልን፡፡ የምንበላው ቁርስና ሻይ ቡና እንዲሁም ለብርዱ ብርድልብስ ተዘጋጅቶ ጠበቀን፡፡ የህክምና ባለሙያዎችና የስነልቦና ባለሙያዎች እርዳታ ሊሰጡን እየተጠባበቁ ነበር፡፡ አስገራሚ አቀባበል ነው የተደረገልን።
ኢትዮጵያውያንስ አላገኛችሁም?
ተርሚናሉ ዉስጥ ገብተን ትንሽ እንደቆየን አንድ ኢትዮጵያዊ ወደ እኛ ሲመጣ ተመለከትን፡፡ ለጊዜው ስሙ ትዝ አይለኝም። ከኢትዮጵያ ኤምባሲ እንደመጣ ነገረንና ስለሁኔታው ጠየቀን። “አይዟችሁ!... ደርሰንላችኋል!...” የሚል መንፈስ ያለው ማበረታቻ ሰጠን፡፡ ከዚያም የግል ሞባይሉን ከኪሱ አውጥቶ አገር ቤት ያሉ ቤተሰቦቻችን ጋ ደውለን ደህንነታችንን እንድናረጋግጥ ራሱ እየደወለ ያገናኘን ጀመር፡፡   
በዚህ ጊዜ ነው፣ በስዊዘርላንድ የኢትዮጵያ አምባሳደር የመጡት፡፡ በአውሮፕላኑ ውስጥ የነበርን ኢትዮጵያውያንን አነጋግረው አረጋጉን፡፡ በስተመጨረሻም ከተርሚናሉ እንዲወጡ ስለታዘዙ የማስታወሻ ፎቶግራፍ አብረውን ተነሱና ጉዳያችንን በቅርብ እንደሚከታተሉ ነግረውን አበረታቱንና ሄዱ፡፡ ሌሎች ሁለት የኤምባሲው ባልደረቦችም፣የሚፈቀድላቸው ቦታዎች ላይ ሁሉ እየተገኙ ድጋፍ በማድረግ እስከመጨረሻው አብረዉን ነበሩ።
በእለቱ ስለተከሰተው ሁኔታ ምን ትላለህ?
እናቴ እንደነገረችኝ፣ በህፃንነቴ የወራት ዕድሜ ላይ እያለሁ፣ የሆነ ቀን ከታላቅ ወንድሜ መላኩ ገብሬ ጋር ከጎማ ላስቲክ የተሰራ አልጋ ላይ ተኝቼ ነበር። ቡና ስታፈላ ምንጊዜም ዕጣን ማጨስ እማትዘነጋው እናታችን፣ ያጨሰችዉን እጣን እኛ የተኛንበት አልጋ አጠገብ አስቀምጣው ኖሮ፣ እሷ ጎረቤት ደርሳ ስትመለስ ቤቱ በጭስ ተሸፍኖ ጨልሞ ጠበቃት። ጩኸቷን ለቀቀችው። ጩኸት ሰምቶ የመጣ ጎረቤት ነው አሉ ፈልጎ አግኝቶኝ በመስኮት ወደ ውጭ የወረወረኝ። ምህረቱ የተባልኩትም በዚያ ምክንያት ነው። እንዳጋጣሚ እሳቱ ቀድሞ የተያያዘው ወንድሜ በተኛበት በኩል ስለነበር እሱን ማትረፍ አልተቻለም።
የፈጣሪ ምህረት ዛሬም አልተለየኝም፡፡ በአውሮፕላኑ ላይ ሊደርስ ከሚችለው አሰቃቂ አደጋ አትርፎኛል። እንደትላንትናው ሁሉ ነገዬም በፈጣሪ እጅ እንደሆነች አምናለሁ። እርሱ ይሁን ያለው ሁሉ መልካም ነው። ቸርነቱ አይለየኝና ፍቃዱ ሆኖ ለነገ ካበቃኝ ለልጆቼ የምነግረው ተጨማሪ ታሪክ አግኝቻለሁ።
ደህና ነኝ እንኳን ብላት የማታምነኝ እናቴ ብርሃነማርያም ኪአን፣ እጮኛዬ ዮዲት ቦርሳሞን፣ ወንድሞቼን፣ ብቸኛዋን እህቴን፣ አክስቶቼን ከነቤተሰቦቻቸው፣ ጓደኞቼን፣ስለደህንነቴ የሚጨነቁልኝን ሁሉ ደህና መሆኔን ንገርልኝ። ከሁሉ አስቀድሞ ስለሆነውም ስለሚሆነዉም ክብር ሁሉ የእርሱ ነውና ፈጣሪ የሚገባዉን ክብር እና ምስጋና ይውሰድ።

Published in ህብረተሰብ
Saturday, 22 February 2014 13:01

እውን ወንዶች ያርጣሉ?

ከ50-60 ዓመት ዕድሜ ክልል ውስጥ ያሉ ወንዶች የማረጥ እጣ ፋንታ ሊገጥማቸው ይችላል
በ40ኛው ዓመት እድሜ ማጠናቀቂያ ላይ የወሲብ ፍላጎት ማጣት፣ የስሜት መዋዠቅና ድብርት ይከሰታል

ሴቶች በህይወት ዘመናቸው በአብዛኛው አጥብቀው ከሚፈሯቸውና ከሚሸሿቸው ጉዳዮች አንዱ ማረጥ ነው፡፡ ይህን ተፈጥሮአዊ ሂደት ተከትሎ የሚከሰቱ አካላዊና ስነ-ልቦናዊ ለውጦችን መቀበልና እንደአመጣጣቸው ማስተናገዱም የብዙ ሴቶች ፈተና ነው፡፡ አብዛኛውን ጊዜ ከ45-49 ዓመት ዕድሜ ክልል ውስጥ ያሉ ሴቶች ትውልድ ለመቀጠል (ለመውለድ) የሚያስችላቸውን የዘር እንቁላል ማምረት ሙሉ በሙሉ እንደሚያቆሙ ቀደም ያሉ ሳይንሳዊ መረጃዎች ቢጠቁሙም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እየወጡ ያሉ ሳይንሳዊ መረጃዎች ይህንን የማረጫ ዕድሜ ወደታች አውርደውት ከ35 ዓመት ዕድሜ ክልል በላይ ያሉ ሴቶች በማንኛውም ጊዜ እንደሚያርጡ ይጠቁማሉ፡፡
በእንግሊዛውያን ተመራማሪዎች የተደረገና ባለፈው ጥር ወር ይፋ የሆነ አንድ ጥናት በበኩሉ፤ ከ50-60 ዓመት ዕድሜ ክልል ውስጥ ያሉ ወንዶችም ይኸው የማረጥ እጣ ፈንታ ሊገጥማቸው እንደሚችል ጠቁሞ፤ ከ70ኛ ዓመት እድሜያቸው መጠናቀቂያ በኋላ በሰውነታቸው ውስጥ የሚኖረው የቴስቶስትሮን መጠን በግማሽ እንደሚቀንስ አመልክቷል፡፡
አርባኛው የዕድሜ ክልል መጠናቀቂያ የአብዛኛው ወንዶች ወሲባዊ ስሜት መቀዛቀዣ ጊዜ መሆኑን የጠቀሰው መረጃው፤ በዚህ ዕድሜ ክልል ብልት እንደቀድሞው ፈጥኖ ለመንቃትና ለመቆም እንደሚቸገርም ጠቅሷል፡፡ በሴቶች ስነተዋልዶአዊ አካላት ላይ ተፈጥሮአዊ ለውጥ የሚያስከትለው ኤስትሮጂን ሆርሞን የሚፈጥረውን ዓይነት ለውጥ ቴስቶስትሮን የተባለው ሆርሞን በወንዶች ላይ እንደሚፈጥር ያመለከተው ይኸው መረጃ፤ ሆርሞኑ ወንዶች ዘር ለመተካት የሚያስችላቸውን በቂ ስፐርም ከማምረት እንደሚያግዳቸውና የብልት መልፈስፈስ እንደሚያስከትል ጠቁሟል፡፡
ቴስቶስትሮን የተባለው ሆርሞን፤ ወንዶች በጉርምስና ዕድሜያቸው (ለአቅመ አዳም ሲደርሱ) የወንድነት መለያ የሆኑ ለውጦች ለምሣሌ የጢም ማብቀል፣ የድምፅ መጎርነን፣ የጡንቻ መዳበር እንዲፈጠርና በብብትና በስነ ተዋልዶ አካላት ዙሪያ ፀጉር እንዲበቅል ለማድረግ የሚያስችል ነው። ከዚህ በተጨማሪ ሆርሞኑ ወንዶች በጉርምስና ጊዜያቸው የወሲብ ፍላጎት እንዲኖራቸው፣ የብልት መነሳሳት እንዲፈጠርና በግብረስጋ ግንኙነት ወቅት ስሜት ያለውና የተሳካ ወሲብ እንዲፈፅሙ ለማድረግ ያስችላቸዋል፡፡ ይህ ሆርሞን ወንዱ በሚገኝበት የዕድሜ ደረጃ መሠረት መጠኑ እንደሚወሰን የገለፀው መረጃው፤ ዕድሜ እየገፋ በሄደ ቁጥር በወንዶች ሰውነት ውስጥ የሚመረተው የቴስቶስትሮን መጠን እንደሚቀንስ ጠቁሞ በ70ዎቹ ዕድሜ ዘመን በግማሽ ሊቀንስ እንደሚችል ጠቁሟል፡፡ በዚህ ወቅትም ወንዶች የብልት መልፈስፈስ፣ ድብርት፣ የስሜት መዋዠቅ፣ የወሲብ ፍላጎት ማጣት፣ ወሲብ የማድረግ ብቃት ማነስ፣ ብልት እንደቆመ ረዘም ላለ ጊዜ መቆየት አለመቻል፣ ዘር ሲረጭ ግፊቱ ጠንካራ አለመሆን፣ ዘርን ሲረጩ አለማወቅ፣ የዘር ፍሬዎች መሰብሰብና ከረጢታቸውም ከወትሮው ማነስ ሊያጋጥማቸው ይችላል፡፡ ይህ ሁኔታ የሚከሰተው በአንድ ጊዜ ሳይሆን ቀስ በቀስ እንደሆነና የወንዶች የወሲብ አካል ከወሲብ ግንኙነት በራቀና ወሲብ መፈፀም ባቆመ ቁጥር የደም ስሮቹ በመጨራመትና የዘር ማቀፊያዎቹም በመውደቅ ለመውለድ (ዘር ለመተካት) ያለውን ዕድል በእጅጉ እንደሚቀንሱት መረጃው አመልክቷል፡፡
የስነ-ወሲብና የስነ-ልቦና ባለሙያው ዶክተር አስናቀ ይሄይስ ይህንኑ ጉዳይ አስመልክተው ሲናገሩ፤ ወንዶች በተፈጥሮአቸው ጤናማ የሆነ የወሲብ ፍላጎትና ለወሲባዊ ግንኙነት ብቁ የሆነ አካላዊ ተፈጥሮ እንዲኖራቸው የሚያደርገው ቴስቶስትሮን የተባለው ሆርሞን፤ በአብዛኛው በወንዶች የጉርምስና ወቅት ተፈጥሮ የወንዶቹ ወንድነት መለያ እንዲኖራቸው ለማድረግ ያስችላል፡፡ ወንዶች በጉርምስና መጀመሪያ ዕድሜያቸው ላይ ድምፃቸው እንዲጎረንን፣ ጡንቻዎቻቸው እንዲዳብሩና ከሴቶች የተለየ አካላዊ ቅርፅ እንዲኖራቸው የሚያደርገውም ይኸው ሆርሞን ነው፡፡ ሆርሞኑ በጉርምስና የዕድሜ ዘመን በመጠን በርከት ብሎ የሚመረት ሲሆን ወንዱ በፈለገው ጊዜና ሁኔታ የወሲብ ፍላጎቱ እንዲነሳሳ፣ ብልቱ እንደልቡ እንዲቆምና በግንኙነት ወቅት ጠንከር ያለ ግፊት ያለው የዘር ርጭት እንዲኖረው ለማድረግ ያስችላል፡፡ ዕድሜ እየገፋ በሄደ ቁጥር ግን ሰውነታችን ይህን ሆርሞን የሚያመርትበት መጠን ቀስ በቀስ እየቀነሰ ይሄዳል። ይህም በወንዶች ወሲባዊ ህይወት ላይ ለውጥ እንዲከሰት ያደርጋል፡፡ ለውጡ ቀስ እያለ የሚከሰት እንጂ እንደሴቶቹ በአንድ ጊዜ የሚፈጠር ባለመሆኑ የወንዶች ዘር የመተካት (የመውለድ) ብቃት ማነስ እምብዛም ጎልቶ እንዲታይ አላደረገውም፡፡ ይሁን እንጂ ወንዶች የ50 ዓመት ዕድሜያቸውን ከዘለሉ በኋላ የወሲብ ፍላጎታቸውም ሆነ አፈፃፀማቸው እንደቀድሞው ሊሆን አይችልም፡፡ ይህ ደግሞ በመውለድ ብቃታቸው ላይ የራሱ የሆነ ከፍተኛ አስተዋፅኦ አለው፡፡
በተለይ ወንዱ ጤናማ ካልሆነና ሌላ ተጨማሪ ችግሮች እንደ ደም ግፊት፣ ስኳር፣ የሣንባ በሽታና መሰል የጤና ችግሮች ካሉበት ልጅ የማግኘት ዕድሉ የመነመነ ነው ብለዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት አብዛኛዎቹ ወንዶች የወሲብ ፍላጎት ማጣት ወይም የብልት መልፈስፈስ አሊያም እንደልብ አልቆም ማለት ሲያጋጥማቸው ቪያግራን የመሳሰሉ መድሃኒቶችን መጠቀም እንደሚያዘወትሩ የጠቀሱት ባለሙያው፤ እነዚህ ነገሮች ለችግሩ መፍትሔ ከመስጠት ይልቅ ችግሩን እንደሚያባብሱትና ሰዎችን የመድሃኒት ሱሰኛ በማድረግ፣ ለከፋ የጤና እክል እንደሚዳርጋቸው ገልፀዋል፡፡ ይህ ዓይነቱ ችግር የገጠማቸው ሰዎች ወደ ህክምና ባለሙያዎች በመሄድ ችግራቸውን ቢያማክሩ፣ መፍትሔ ሊያገኙ እንደሚችሉና ከዕድሜ ጋር ተያይዞ የሚከሰተውን ችግር ለማከም እንደሚቻልም ጠቁመዋል፡፡  

Published in ዋናው ጤና
Saturday, 22 February 2014 13:00

የቀልድ - ጥግ

ትንሽ     ስለ ቀልድ

ቀልድ መቼና እንዴት መጠቀም አለብን ብሎ መጠየቅ ያባት ነው፡፡ ቀልድ በመደበኛም ሆነ በኢመደበኛ ንግግር ውስጥ መሠረታዊ ግብዓት ሆኖ ያገለግላል፡፡ ቀልድ ቅመም ነው፡፡ ወጥ በቅመም እንደሚጣፍጥ ሁሉ በጥንቃቄ መመረጥ፣ መመጠንና በትክክለኛው ሰዓት መጨመር ይኖርበታል፡፡ ቀልድ በትክክል ከተመጠነና ከተጨመረ በብርቱ ጥንቃቄ በበቃ ባለሙያ የተነገረውን ዲስኩር እንኳ የበለጠ አመርቂና ለታዳሚው እጅግ የሚጥም ያደርገዋል፡፡
ጆርጅ ጄሰል የተባለ ፀሐፊ፣ “ጥሩ ንግግር ልክ እንደጥሩ ካልሢ፣ ካልሢው በተሰራበት ጨርቅ ዓይነት ይወሰናል” ይላል፡፡ (የቻይናን አቃጣይ ካልሲዎች ልብ ይሏል) የቀልድ ጥግ የሚለው የአምድ-ሩብ፤ ታላላቅ ሰዎች፣ ነጋዴዎች፣ ወጣቶች፣ የጥበብ ሰዎች፤ በንግግር፣ በውይይት፣ በስብሰባ መግቢያና ሌሎች የዕለት ተዕለት የንግግር እንቅስቃሴዎቻቸው ውስጥ፤ ትኩስ የቀልድ ምንጭ እንዲሆን የታሰበና የተዘጋጀ ነው። ቀልዶቹ በዘርፍ የተከፋፈሉ ስለሆነ በአጫጭር ጭውውቶች፣ ገጠመኞች፣ ተረቦች፣ ውጋውጎች /witticisms/፣ የነገር አዋቂዎች አባባሎች፣ ተረቶችና የአንዳንድ ሀሳቦች ትርጓሜዎች ወዘተ እየተመረጠ የሚቀርብበት ነው፡፡
በመሰረቱ ቀልድ መጠቀም ያለብን አንድን መልዕክት ፅኑ ነጥብ ለማጠንከር ስንሻ ወይም የተደበረና የተኮሳተረን ታዳሚ ላላ ለማድረግ ስናስብ፤ አሊያም የከረረና የመረረ ስሜቱን በተለየ አቅጣጫ ለመቃኘት ስንፈልግ ነው፡፡
ቀልድ ሌላውን ሰው ወይም ታዳሚ ለማጥቃት የምንጠቀምበት መሆን የለበትም፡፡ ስለዚህ ከመጠቀማችን በፊት የታዳሚው ምላሽ ምን ይሆናል? ታዳሚው  ምን ይሰማዋል? ብሎ ማሰብ መልካም ነው፡፡ ለማረጋገጥ በራሳችን የቅርብ ሰው ላይ ሞክረን የሚያስከፋው መሆኑን ማጤን ይገባል፡፡
ቀልድ ለዛ የሚኖረው በቦታው ሲቀርብ፣ በሰዓቱ ስንገለገልበት ነው፡፡ ቀልድ በኮስታራ ንግግር ውስጥ ጣልቃ አስገብተን ከምንጠቀምበት ሰዎች ጀምሮ፤ ለመዝናኛ እንደማሺንገን የሚተኩሱ፣ እንደተልባ የሚንጣጡ ኮሜዲያኖች እስከሚጠቀሙበት ድረስ፤ የተለያየ የመገልገያ መንገድ አለው፡፡ ሆኖም ብዙዎች በዚህ ጉዳይ ላይ የተመራመሩ ፀሐፍት ቀልዶች አንድ ላይ እንደጥይት ዝናር ከሚደረደሩ ከቁምነገር ንግግሮች መካከል ጣልቃ ቢገቡ እንደለዘዘ ቆሎ ጥርስ ከማስቸገር ይድናሉ ይላሉ፡፡
እኛም ይህንን መንፈስ በማጠንከር የተወሰኑ ቀልዶችን ብቻ በየጊዜው እናቀርብላችኋለን፡፡
የቀልዶቹ ዘርፎች ለምሳሌ አንድ ሳምንት በሰካራሞችና በአካል ዙሪያ፣ በሌላ ሳምንት በዶክተሮችና በሕክምና ዙሪያ፣ ቀጥሎ በባንክና በባንከሮች ዙሪያ፣ ከዚያ በነጋዴዎችና በንግድ ዙሪያ እንቀጥላለን፡፡ እናንተም ያጋጠማችሁን የሰማችኋቸውን ብትልኩልን ደስ ይለናል፡፡ ሣምንት እንጀምርላችኋለን፡፡

Published in የግጥም ጥግ

ከ38 ዓመት በኋላ ከመቃብር የወጣው አስከሬን ትርዒት

የፊዚክስ ባለሙያው የዶ/ር ሙሉጌታ በቀለ አባት የፊታውራሪ በቀለ ኦገቶ አስከሬን እንዴት ተገኘ? ዝርዝሩ ብዙ ነው፤ ጉዳዩ ግን ተዓምር ተባለ!

ወደ አርሲ አሰላ - ሳጉሬ መንገድ የጀመርነው ቅዳሜ የካቲት 8 ቀን 2006 ዓ.ም ከንጋቱ ለአንድ ሩብ ጉዳይ ነው፡፡
ከናዝሬት .. ወደ ሶደሬ አቅጣጫ … መልካሰዲ ስንደርስ ወደ ቀኝ ዞረን ዴራ፣ ኢቲያን አልፈን በብቅል ፋብሪካ አድርገን አሰላ ገባን፡፡ ከዚያ ወዲያ እንግዲህ ከ 23 ኪ.ሜ በኋላ ሳጉሬ ወረዳ ልንሄድ ነው፡፡
ወደ ሳጉሬ ከመሄዳችን በፊት ወደ አሰላ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን መሄድ ዋንኛው የመርሀ-ግብሩ መነሻ ነው፡፡ ለምን? ታሪኩ እዚህ ጋ ይጀምራላ፡፡
38 ዓመት የፈጀው አስከሬን ለምን ይሄን ያህል ጊዜ ፈጀ? ሂደቱ ምን ይመስላል? ከመጨረሻው ትርዒት ጀምረን ወደ ኋላ 38 ዓመት እንጓዛለን፡፡
ከአሰላ ሚካኤል ቤተ ክርስሪያን አስከሬኑን ይዘን ወደ ሳጉሬ ሥላሴ ቤተክርስቲያን ወደ ፊታውራሪ በቀለ ኦጋቶ ትውልድ አገር እየተመምን ነው። ከ100 በላይ መኪና እንደሰንሰለት ተቀጣጥሎ ነው የሚሳበው፡፡ አስከሬኑ በፒካፑ መኪና ነው የተጫነው፡፡
የሳጉሬ ፖሊሶች በተጠንቀቅ መሆናቸው አያጠራጥርም፡፡ በፒካፓቸው አጀቡን እየተቆጣጠሩ ፊት ኋላ ይላሉ፡፡ በአብዛኛው መሪዎቹ እነሱ ናቸው!
ገና ወደ ሳጉሬ ወረዳ መዳረሻ ስንደርስ፤ ከመቶ በላይ ፈረሰኞች ተቀበሉን፡፡ ግማሹ “ጌታዬ! ጌታዬ!” ይላል፡፡ ግማሹ “አምሣ ቢወለድ አምሳ ነው ጉዱ
አምላክ ካበጀው ይበቃል አንዱ!” ይላል፡፡
ሌላው ያቅራራል፡፡ ሌላው ይፎክራል፡፡ ጉድ ነው የሚታየው! ዛሬ ትኩስ ሬሳ የሚቀብር እንጂ የ38 ዓመት አፅም ስብርባሪ ተሰብስቦ፣ እንደ ሙሉ አስክሬን ታስቦ፤ ሊቀብር የመጣ አይመስልም!
አንድ የዘመነ ብሉይ-(ክላሲካል) ፊልም የማይ ነው የመሰለኝ፡፡ የፈረስ ግልቢያ ጥበብና የስሜታዊ ንዝረታቸው ህያውነት እጅግ አድርጎ አስደምሞኛል።
ወደ ከተማው ስንዘልቅ እንደገና የፈረሰኛው ቁጥር ጎላ፡፡ ህዝቡ በነቂስ ወጥቶ ግራና ቀኝ ይጠብቀናል። በቀበሌ ጥሩምባ፣ በመንግሥት ትዕዛዝ ማስጠንቀቂያ ተሰጥቶት እንጂ የሟቹ ሀዘን ከ38 ዓመት በኋላ ልቡን ነክቶት ነው ለማለት ይቸግራል! ሽለላ፣ ለቅሶ፣ ፉከራ… ድብልቅልቁ ወጥቷል፡፡
ከ38 ዓመት በኋላ የተገኘው አስከሬን ታሪክ፤ ዛሬ ነብስ ዘርቶ እየተነሳ ነው፡፡ የፊታውራሪ በቀለ ኦገቶና የሌሎች የ16 አፅሞች ሰብስብ የቀብር ቀን! በደርግ መንግስት በግፍ ተገድለው የትም የተጣሉ 17 ሰዎች ታሪክ ትንሣዔ! በሺዎች የሚቆጠር ህዝብ ያጀበው የፊታውራሪ በቀለ ኦገቶ አፅም ወደ መጨረሻ ቦታቸው ሲጓዝ ማየት በእውነት ተዓምር ነው! ለዐይን ማረፊያ የሌለበት ህዝብ ብዛት ለጉድ ይታያል፡፡
የካሜራ ባለሙያዎች እየበረሩ በመኪና ቁመት እየማተሩ ይቀርፃሉ፡፡
ወደ መቃብሩ ቦታ የሚተመውን ጉንዳን ህዝብ፣ ቁጥሩንም ሆነ ነገደ- ጉንዳን ጉዞውን መተለም አይቻልም።
አፋፉ ላይ፣ ትልቅ የብረት ወንፊት ሳጥን የመሰለው የመቃብር ቤት በጉልህ ይታያል፡፡
ወጣቶች ባካባቢው ባለው ዛፍ አናት ተንጠላጥለው ስነ-ስርዓቱ ቁልጭ ብሎ እንዲታያቸው ዐይናቸውን ቁልቁል ወደ መድረኩ ሰክተዋል፡፡
የሚገርመው ከምልዓተ-ለቀስተኛው የሚበዛው፣ በወንድም በሴትም፤ ሙስሊሙ ነው፡፡ እኔ በሆዴ በአግራሞት፤ “ሰውዬው ሙስሊም ናቸው እንዴ? እላለሁኝ፡፡ እኔ እስከማውቀው ድረስ ፊታውራሪ ክርስቲያን ናቸው! ምንድነው ጉዱ? ሙስሊም ሴቶች ወደቀብር እንደማይሄዱም አውቃለሁ፡፡ እንዴት እንዲህ እንደ አንድ ደግ መሪ የህዝብ አጀብ ደመቀላቸው?
ሥላሴ ቤተክርስቲያን አፋፍ ላይ ትልቅ መካነ-መቃብር ይታያል ብያለሁ፡፡ ግዙፍ ነው በጣም። ከመካከል የሀውልቱ ግድግዳ ላይ የፊታውራሪ በቀለ ኦጋቶ ፎቶ ይታያል፣ ከግርጌውም የህይወት ታሪካቸው ይነበባል፡፡
የፕሮግራም መሪው የህይወት ታሪካቸውን ያብራራው በተለይ ዶክተር ሙሉጌታ በቀለን አስከሬኑ እንዲገኝ ስላረጉት ጥረት በማመስገን ነበር።   
ፊታውራሪ በቀለ ኦገቶ ከአባታቸው ከግራዝማች ኦገቶ ጉቱና ከእናታቸው ከወይዘሮ ሻሹ ገልቹ በ1907 ዓ.ም በጢጆ አካባቢ በአሽበቃ ተወለዱ። ዕድሜአቸው ለትምህርት ሲደርስ መድረሳ ትምህርት ቤት ገብተው ቁርአን አክትመዋል። ከዚያም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እምነት ተቀብለው ለትምህርት ካላቸው ፍቅር የተነሳ ማንበብና መፃፍ ተምረዋል፡፡ ፊታውራሪ በቀለ ኦገቶ ባላቸው ትጋትና ሥራ ወዳድነት ተመርጠው በ1936 ዓ.ም ገና በወጣትነት ዕድሜአቸው ማለትም በ19 አመታቸው የመንግስት ሥራ በምስለኔነት በባብሌ ሜዳ ምክትል ወረዳ አስተዳዳሪነት ሥራ ጀምረዋል። እስከ 1939 ዓ.ም በምስለኔነት የሳጉሬ ምክትል ወረዳን አስተዳድረዋል፡፡
ከ1942 እስከ 1966 በአሰላ፣ አዳሚ ቱሉ፣ ጢዮ፣ በጭላሎ እና በጢቾ ከምስለኔነት እስከ አውራጃ ገዢነት ተሹመው አገልግለዋል! ከአቡነ ሉቃስና ከህዝቡ ጋር በመተባበር በ1959 ዓ.ም በከታር ወንዝ ሆፊ በሚባለው ቦታ የብረት ድልድይ አሰርተዋል። ከአሰላ እስከ በቆጂ ያለውን የመንገድ ሥራ ዋና አስተባባሪ ነበሩ፡፡ ከሳጉሬ ጢቾ በቦራ ለኩ በኩል የሚያልፈውን መንገድ ከደጃዝማች አባይ ካሳ በወቅቱ (የጢቾ አውራጃ ገዥ የነበሩ) ጋር ተባብረው አሰርተዋል፡፡
ፊታውራሪ በቀለ ኦገቶ በሸሬ ወረዳና በአዳሚ ቱሉ ወረዳ በሰሩባቸው ጊዜያት የአካባቢው ሕዝብ የሴቶች አለባበስ እንዲለወጥ አድርገዋል፡፡ ከዚህ ቀደም ሴቶች እንደካባ የሚደርቡት ከከብቶች ቆዳ የተሰራና ቅቤ የተነከረ ኦምባ የሚባል ልብስ ነበር። ፊታውራሪ በቀለ ኦገቶ ይህንን ልማድ በጨርቅ አቡጀዲ እንዲለወጥና እንዲቀየር ጥረት አድርገዋል።
ፊታውራሪ በቀለ ኦገቶ ምንም ዓይነት የሃይማኖት ልዩነት ሳያደርጉ የአርሲ ሕዝብ ዘመናዊ ትምህርት እንዲማር በማድረግ ቀዳሚ ናቸው፡፡ ፊታውራሪ በቀለ ኦገቶ ዘመናዊ ትምህርት ምንም ዓይነት ክፍፍልና ልዩነት ሳይደረግ ለሕዝብ እንዲደረስና የተሳሳተ አመለካከቱን ሕዝቡ ቀስ በቀስ እንዲለውጥ ከግል ገንዘባቸው የቁርዓን አስተማሪ ቀጥረው በፈረቃ እንዲሰጥ አድርገዋል፡፡
ትምህርት ቤት ሲያሰሩ ከሚታወሱባቸው አባባሎች እንጨት ራሳቸው ይሸከሙ እንደነበረና፤ ይተዉ ሲባሉ “እኔ እንጨት ልሸከም፤ ተውሉኝ፣ አንተ ግን ልጅህን ለትምህርት ስጠኝ” ማለታቸው ነው፡፡
ፊታውራሪ በቀለ ኦገቶ በሃይማኖት መካከል ልዩነት የማያደርጉ ታላቅ ሰው ነበሩ፡፡ በሳጉሬ ከተማ ከግል መሬታቸው በመስጠት መስጊድ አሰርተዋል። እንዲሁም በሳጉሬ ከተማ የስላሴ ቤተክርስቲያንን አሰርተዋል፡፡”
አሃ! የዚህ ሁሉ ሙስሊምና ክርስቲያን ውህደት ምክንያት ለካ ይሄ ነው፤ አልኩ! ፊታውራሪ በቀለ፤ መስከረም 24 ቀን 1968 ዓ.ም. በግፈኛው የደርግ መንግሥት፣ የፍየል ወጠጤ ተዘፍኖባቸው፣ ከ16 ዘመዶቻቸውና ወዳጆቻቸው ጋር ተገድለዋል!! አስከሬናቸው በእንጨትና በጣውላ ርብራብ፣ ሬሳቸው ከነሙሉ ልብሳቸው በሚሥማር ተመቶ ተሰድሮ፤ ህዝብ እንዲያይ፣ ቀኑን ሙሉ በአደባባይ እንዲቆም ተደርጓል! (ይቀጥላል)

Published in ባህል

ፈጠራ ብቻ ሳይሆን ኩረጃም የማይችል ትውልድ!

ጽሑፌን የሚያነብቡ ሰዎች “የተሳሳተ ማጠቃለያ ሰጥተሃል፤ በርካታ የፈጠራ ባለሙያዎች በአገራችን የሉም ወይ?” የሚል ጠንካራ ጥያቄ ሊያነሱልኝ ይችላሉ፤ ጥያቄያቸው ደግሞ ተገቢ ነው፡፡ ግን “ትውልድ” ስል ራሴን ጨምሬ እየወቀስሁ መሆኑም ግምት ውስጥ ሊገባልኝ ይገባል፡፡ እንዲያውም ኃይሉ ገብረ ዮሐንስ (ገሞራው) በ1966 “በረከተ መርገም” በሚል ርዕስ ካሳተመው ረጅም ግጥሙ ውስጥ የሚከተሉትን ስንኞች ብቻ ብጠቅስ አቋሜን ይገልጹልኛል ብዬ አምናለሁ፡፡
“… በእሱነቱ ግምት፣ በተዛባ መንፈስ መሰሌን መርገሜ ኃጥእ ነው ቢያሰኘኝ፣
ራሴው በራሴ የእኔው ገሃነም ነኝ”
ስለሆነም በትውልዴ ውስጥ ፈጠራና ጥሩ ነገር ካለ የእኔ ድርሻ ጥቂትም ቢሆን ቦታ ይኖረዋል፤ ትውልዴ ከሰነፈና አገሬ ከጠቅላላ ችጋር ካልወጣች ከተወቃሾች ታሪክ ውስጥ ተገቢው ድርሻ ይኖረኛል ብዬ አምናለሁ፡፡ ለዚህም ነው ተገቢ በሆነ ድፍረት ትውልዴን በጅምላ ልወቅሰው የተነሳሁት፤ በነገራችን ላይ “ትውልድ” ስል መንግሥትንም ይጨምራል፡፡ በኩረጃ በተደነቁ የዘመናችን ፖለቲከኞች የሚመራ የትውልዱ ዋናው ቁንጮስ እሱ አይደለም?
የወቀሳዬ ዋና ፍሬ ነገር ኩረጃ ነው፡፡ መንግሥት በ“አንድ ለእናቱ” ቴሌቪዥኑና ሬዲዮ ጣቢያው የ10ኛ እና የ12ኛ ክፍል ፈተና ጊዜ በቀረበ ቁጥር “ኩረጃ ወንጀል ነው፤ ሲኮርጅ የተገኘ ተማሪ ፈተናው ዋጋ ቢስ ይሆናል፤ አስኮራጁም ተመሳሳይ ዕጣ ይደርሰዋል” እያለ እስኪሰለቸን ድረስ ይነግረናል፡፡ ለትምህርት ጥራት ጠንክሮ እንደሚሰራም በየጊዜው ይምል ይገዘታል፡፡
በመገናኛ ብዙኃኑ አማካይነት የኩረጃን አደገኛነት እየሰበከ፣ራሱ ግን ያውም ከፍተኛ ዶላር እየመነዘረ ቱባ ባለሥልጣናቱን በየሀገሩ ለኩረጃ ይልካል፡፡ ባለሥልጣናቱ የተላኩበትን የኩረጃ ተልዕኮ በአግባቡ ስለማይወጡም ድካማቸው ሁሉ ከንቱ ይሆናል፤ ዶላሩም አለት ላይ የተዘራ ዘር ሆኖ ይቀራል፡፡ ማስረጃ ልጥቀስ፡-
ለዘመናት ሥር ሰድዶ የኖረውን የሲቪል ሰርቪስ አደረጃጀትና አገልግሎት አሰጣጥ ዘመናዊ ለማድረግ አስቦ በ1993/94 አካባቢ ባለስልጣናቱን ወደተለያዩ አገሮች ልኮ ነበር፡፡ በየሀገሩ ተጉዞው የነበሩት ባለሥልጣናትና አጃቢዎቻቸው (ጥቃቅን ባለሥልጣናት) በተሰጣቸው ዶላር የሆኑትን ሆነው ከተመለሱ በኋላ “በሲቪል ሰርቪሱ ውስጥ የነበረው ችግር ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ዕልባት ሊያገኝ ነው” ተብሎ ሌት ከቀን ተሰበከ፤ ቁጥሩ የማይገመት መዋዕለ ንዋይ እየወጣም በአውደ ጥናት፣ ሲምፖዚየምና ሴሚናር ስም በየሆቴሉ ተበተነ፡፡ በፕሮፓጋንዳ የማለለው ህዝብ “ተአምር ሊፈጠር ነው” ብሎ ሲጠብቅ በወቅቱ የአቅም ግንባታ ሚኒስትር የነበሩትና ጥሩም ይሁን መጥፎ እንደልባቸው በመናገር የሚታወቁት አቶ ተፈራ ዋልዋ ድንገት በቴሌቪዥን መስኮት ብቅ አሉና “የሲቪል ሰርቪስ ማሻሻያ ፕሮግራሙ ጨንግፏል” አሉ፡፡
እርግጥም ያ ብዙ የተደከመበት፤ በወረቀት፣ በቀለም፣ በውሎ አበል፣ በጽሑፍ አቅራቢነት፣ በአዳራሽ ኪራይ እና በመሳሰሉት የትየለሌ ገንዘብ የባከነበት መርሐ ግብር፣ ጠብ የሚል ቁም ነገር ሳይታይበት የውሃ ሽታ ሆኖ ቀረ፡፡ መንግሥት ከዚህ ቢማር መልካም ነበር፤ ግን ሌላ ስም አወጣና ሌላ ጉዞ ወደ አሜሪካ፣ አውሮፓና ኤሽያ ጀመረ። ዘመቻውንም “ዘመቻ ቢፒአር” ብሎ ጠራው፡፡ አሜሪካዊው የምጣኔ ሃብትና የመዋቅራዊ ችግሮች ዘዴ ቀያሽ እንደሆኑ የሚነገርላቸው ሐመርና ሌሎች የሰሯቸው መጻሕፍት እየተባዙም በየመንግሥት ተቋማቱ ተበተኑ፤ እንደ ማርክሲስት ሌኒኒስት ካድሬዎች በርካታ ጮሌዎች በየመድረኩ ብዙ ለፈለፉ፡፡
በዚህም “አሁን ገና ለውጥ መጣች” ተባለ፤ ግን ለውጡ የመጀመሪያው (በአቶ ተፈራ አባባል የጨነገፈው) “የሲቪል ሰርቪስ ማሻሻያ ፕሮግራም” ሲባል ሁለተኛው “ቢፒአር (መሠረታዊ የአሠራር ሂደት ለውጥ)” መባሉ ብቻ ነው፡፡ እርግጥ ነው ቢፒአር ነባሩን የተቋማትና መምሪያዎችን እንዲሁም ዋና ክፍሎችን ስም አጥፍቶ በሥራ ሂደት መሪ፣ዳይሬክቶሬት፣ ዳይሬክተር፣ ወሳኝ የሥራ ሂደት ባለቤት፤ ኤጀንሲ፣ ኮሚሽን፣ ወዘተ--- አይነት ግራ አጋቢ ስሞችን አትርፏል፡፡ “መልከ ጥፉን በስም ይደግፉ” እንደማለት ነው፡፡ ወይም የሀገራችን ፖሊስ ባለ ማዕረጐች ኢትዮጵያዊ በሆነውና ህዝቡ በለመደው የማዕረግ ሥም መጠራታቸው ቀርቶ “ሳጅን፣ ዋና ሳጅን፣ ኢንስፔክተር፣ ወዘተ” የሚል የተውሶ የማዕረግ ስም ከእንግሊዝ እንደመጣላቸው  ማለት ነው፡፡ እውነት ለመናገር ሲጠሩት ደስ የሚለው “ሻለቃ፣ መቶ አለቃ፣ ሃምሳ አለቃ፣ አስር አለቃ፣ ወዘተ ሲባል ነው ወይስ ግራ በሚያጋባው “ኮንስታብል” አይነት መጠራት? ኮንስታብል መታወቂያ ላይ ሲጻፍ “ኮ/ል” ተብሎ ስለሆነ ብዙ ሰው “ኮሎኔል” እያለ ለመጥራት መገደዱን ከፖሊስ አካባቢ የሚወጡ ወጐች ያስረዱናል፤ “ኮንስታብል” ማለት’ኮ “ተራ ወታደር” ማለት ነው፡፡ ታዲያ ለምን ስም እንኮርጃለን? በኩረጃስ ለምን እንደናገራለን?
የመንግሥት ኩረጃ በቢፒአር አላቆመም፤ በለውጡ የተገኙ ውጤቶችን ሲነግረን “የሰነዶች ማረጋገጫና የውልና ማስረጃ ጽ/ቤት” እንዲሁም “የኢምግሬሽንና የዜግነት ጉዳይ ዋና መምሪያ ቀልጣፋ አገልግሎት በመስጠት አርአያ ለመሆን በቁ” ተብሎ ተጨበጨበላቸው፤ ግን እውነታው በግልባጩ ሆነና አረፈው፡፡ በተለይ የኢምግሬሽንና የዜግነት ጉዳይ ዋና መምሪያ ወደ ተለያዩ አገሮች ለመሰደድ ገና ከንጋቱ 11 ሰዓት ጀምሮ በሚኮለኮሉ ዜጐቻችን ተከብቦ መዋልና አገልግሎቱን ለማግኘት እስከ አምስት ወራት የሚደርስ ቀጠሮ ለመስጠት ተገደደ፡፡ ግን ይህንን ችግር የሰው ኃይልና ተጨማሪ ቢሮዎችን በጊዜያዊነትም ቢሆን በመክፈት ማቃለል ይቻል ነበር፡፡
መንግስት ህግ ሲያወጣም እየኮረጀ ነው፣ “የመረጃ ነፃነት ህጉ እና የፀረ-ሽብር ህጉ አያሰሩም አፋኝ ናቸው” ሲባል፣ብዙዎቹ አንቀፆች እገሌ ከተባለው ሥልጡን አገር ቃል በቃል የተቀዳ ነው ይላል - ደረቱን ነፍቶ፡፡   ጥያቄው ግን “ለምን ኩረጃውን ትተህ በኢትዮጵያዊ ህግ አትመራም?” የሚል ነው፡፡ አሁን ደግሞ መንግሥት ፊቱን ወደ ጃፓን አዞረና “የችግሮች ሁሉ መፍቻ ጠንካራው ዘዴ የአንድ ለአምስት አደረጃጀት ብቻ ነው” ብሎ ለተግባራዊነቱ ደፋ ቀና እያለ ነው፡፡ “ቢኤስሲ” የሚባል የአሰራር ዘዴ ሥራ ላይ ማዋል ከጀመረም ቆየ፤ ግን ውጤቱ ሁሉ ጉቦኛነት እና በሙስና የተዘፈቁ በርካታ ደቀመዛሙርትን ከመፈልፈል በቀር ጠብ ያለ ነገር የለም፡፡ ምክንያቱም ዘዴዎቹ ሁሉ በኩረጃ የተገኙ ናቸዋ! የሃገራችንን ዘርፈ ብዙ ችግሮች ለመፍታት መፍትሔው ኩረጃ ሳይሆን ኢትዮጵያዊውን የአስተዳደር ዘይቤ በአግባቡ አጥንቶ መተግበር ነው፡፡ እንዲያ አድርገው ሲያበቁ የጐደለ ሲኖር ከውጭ መበደር የአባት ነው፡፡ አለዚያ ግን ከንቱ መዋተት ነው፡፡
ኩረጃን ከመንግሥት የኮረጁት ኮራጆች በየቦታው ሞልተዋል፡፡ ማንነታቸው አሳፍሯቸው ወይም የሰለጠኑ እየመሰላቸው የልጆቻቸውን ስም፣ የንግድ እና የቤት እንስሶቻቸውን ስም ሳይቀር በባዕዳን ስሞች እየተኩ ናቸው፡፡ ከሁሉም በላይ አደገኛው ኩረጃ የሚስተዋለው በኪነ-ጥበቡ መስክ ነው፡፡ አንዱ ድምፃዊ የሌላውን ይኮርጃል እንጂ አይፈጥርም፤ የፈጠራ ስራ ባለመኖሩም ጆሮአችን ውስጥ የሚገባ ዘፈን መስማት እየናፈቀን ነው፡፡
በእነ ጥላሁን ገሠሠ፣ አለማየሁ ቦረቦር፣ መሐሙድ አህመድ፣ ዓለማየሁ እሸቴ፣ ሂሩት በቀለ፣ አበበ ተሰማ፣ ብዙነሽ በቀለ፣ ሙሉቀን መለሰ፣ ወዘተ--- ዘመን የነበሩ ዘፈኖች ሁሉ በጊዜያቸው ብቻ ሳይሆን ዛሬም በፍቅር ይደመጣሉ፡፡ ምክንያቱም ጥርት ያሉ፣ ኢትዮጵያዊ የፈጠራ ሥራዎች ናቸዋ! የሚገርመው ደግሞ የዚያ ሁሉ ፈጠራ ባለሙያዎች የነበሩት በትምህርት እምብዛም ያልገፉ፣ ወይም ስማቸውን እንኳን መጻፍ የማይችሉ ነበሩ፡፡ ለምሳሌ አለማየሁ ቦረቦር ሲፈርም እንኳ በጣቱ ዱካ እንጂ የፊደሉን እጅና እግር መለየት እንደማይችል ከታሪኩ አንብቤያለሁ፤ ግን ዘፋኝ ብቻ ሳይሆን ድንቅ የዜማና የግጥም ደራሲም ነበር “በላይ በላይ፣ ዓባይ ማዶን፣ ያችውና መጣች፣ መስታወቴን፣ አንችና አንችዋ፣ ተው እረስ ገበሬ …” በራሱ ዜማና ግጥም የተጫወታቸው ናቸው፡፡ አበበ ተሰማም በዚያ በማይሰለች ድምፁ ካቀነቀናቸው በርካታ ዘፈኖቹ ውስጥ አብዛኛው ግጥምና ዜማ የራሱ ነበር፡፡
ዛሬ እንደ አበበ ተሰማ፣ እንደ ዓለማየሁ ቦረቦርና እንደ ጥላሁን ተንሰፍስፈን የምናዳምጠው ዘፈን ያጣነው ኩረጃ ላይ በማተኮራችን ነው፡፡ መንግሥት የራሱ ኮራጅነት አንሶ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የኩረጃ “ጥበብ” የሚስተናገድበት መድረክ ከፍቷል። መድረኩ “የባላገሩ አይዶል” የሚባለው ነው፡፡ ቀደም ሲልም “ኢትዮጵያን አይዶል” የሚባል የኩረጃ መርሃግብር ነበር፡፡ ልብ አድርጉ! ስሙ ራሱ የኩረጃ ነው “አሜሪካን አይዶል” ከሚባለውና ከሌሎች አገሮች የተኮረጀ፡፡
“የባላገር አይዶል” ገንዘብ እየተከፈለው የሚያወዳድረው ግልገል ኮራጆችን ነው፤ ነገ የተዋጣላቸው ኮራጆች ሆነው አገርን እንዲያስጠሩ በማሰብ የሚካሄድ መርሃ ግብር፡፡ ምን አለ ይህንን ሃሳብ በፈጠራ ስራዎች ላይ ቢያደርጉትና ከዚያ ሁሉ መንጋ ኮራጅ መሃል በጣት የሚቆጠሩ ወጣቶች በራሳቸው የፈጠራ ስራ ሲወደሱ ብናይ? ዳሩ የውድድሩ ዓላማና ግብ ፈጠራን ማበረታታት ሳይሆን ገንዘብና ሌላ ነው፡፡
ይህን እውን ለማድረግ ከፈረንጅ መኮረጅ አያስፈልግም፤ አገራችን ውስጥ ያሉ ነባር የጥበብ ተቋማትን ለምሳሌ ቅኔ ቤትን መጎብኘት ብቻ በቂ ነው፡፡ አንድ የቅኔ ተማሪ ወይም ዘራፊ አንድ ቦታ የተቀኘውን የራሱን ቅኔ ሌላ ቦታ መልስ መቀኘት አይችልም፡፡ ከእነ ምሳሌው “የቅኔ ቋንጣ የለውም” ነው የሚባል፡፡ ይህ የሚያገለግለው ታዲያ በየቀኑ ቅኔ እንዲቆጥር፣ በየጊዜው እንዲመራመር ነው። ይህ ዘዴም የቅኔ ጥበብ በአገራችን እንዲያብብ አድርጎታል፡፡ ታዲያ ጥበብን እንጂ ኩረጃን ለምን እናበረታታለን?
በአገራችን ዜማው ብቻ ሳይሆን ትክክልም ይሁን አይሁን አለባበስም ይኮረጃል፤ የማንም የባህል ልብስ ያልሆነ ጥብቆ አንድ ዘፋኝ ለብሶ ከታየ ምድረ ኮራጅ “ለምን?” ብሎ ሳይጠይቅ በነጋታው ለብሶት ብቅ ይላል፡፡ ልብስ ብቻ ሳይሆን አነጋገርም ይኮረጃል፤ የፖለቲካ መሪዎች “… ያለበት ሁኔታ ነው ያለው” ሲሉ የሰሙ ጋዜጠኞች ሁሉ ይህንኑ እየደጋገሙ ያሰለቹናል፡፡ መንግሥት ሆይ! ካልሆነ ኩረጃን በሥርዓት የሚመራ የኩረጃ “ኤጀንሲ” አቋቁምልን!


Published in ህብረተሰብ

“ቱሪዝም አሁንም ገና ጨቅላ ነው”
የአገሪቱን ቱሪዝም ምቅር ቤት የሚመሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ናቸው
አስጐብኚ ምንም ነገር አላውቅም ማለት የለበትም
ባለፈው የጥምቀት በዓል ሰሞን በጎንደር ከተከናወኑት ጉዳዮች አንዱ የጎንደር እህት ከተማ በሆነችው የፈረንሳይዋ ቬንሰን ከተማ ሁለገብ እድሳት ተደርጎለት የተጠናቀቀውን የ“ራስ ግንብ”ን ማስመረቅ ነበር፡፡
ግንቡ ራስ ሚካኤል ስሁልን ጨምሮ በርካታ የጎንደር ነገስታት ራሶች መኖርያ ስለነበር ነው፡፡ “ራስ ግንብ” የተባለው፡፡
የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፣ ለ20 ዓመታት የፋሲል አብያተ-መንግስትን በማስጎብኘት እውቅናና አድናቆትን ካተረፉት
የቱሪዝም ከፍተኛ ኤክስፐርት አቶ ጌትነት ይግዛው ንጉሴ ጋር በጐንደር የቱሪዝም እንቅስቃሴ፣ በታሪካዊ ቅርሶች እድሳት፣
በአስጎብኝነት ህይወታቸው፣ እንዲሁም
በቱሪዝም ኢንዱስትሪና ተያያዥ
ጉዳዮች ዙርያ
ቃለምልልስ አድርጋለች፡፡  

ወደ ፌደራል ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ከመምጣትዎ በፊት የአፄ ፋሲል አብያተ መንግስትን ለ20 ዓመታት እንዳስጎበኙ ሰምቻለሁ፡፡ እስቲ ስለዚህ ጉዳይ ያጫውቱኝ …
ዌል! ይሄ ረጅም ጊዜ ነው፡፡ ለ 21 ዓመታት የቱሪስት ጋይድ ነበርኩ፤ የጎንደር አካባቢ ሲኒየር ጋይድ ሆኜ ሰርቻለሁ፡፡ ከዛ በኋላ የጎንደር ዓለም አቀፍ ቅርስ አስተዳደር (የአብያተ መንግስታት አስተዳደር) ማናጀር ሆንኩኝ፡፡ የዩኔስኮም ተጠሪ (ፎካል ፐርሰን) ሆኜ ሰርቻለሁ፡፡ የጎንደር ቅርሶች በዓለም አቀፍ ደረጃ የተመዘገቡ በመሆናቸው፣ አሁን እኔ ስራዬን ወደ ፌደራል ባህልና ቱሪዝም በመቀየር የዛሬ አንድ ዓመት ከአምስት ወር አካባቢ ጀምሮ የቱሪዝም ከፍተኛ ኤክስፐርት ሆኜ እየሰራሁ ነው፡፡
ጎንደርን ለመጎብኘት እጅግ በርካታ ቱሪስቶች ይመጣሉ፤ አንዱ ሲሄድ ሌላው እየተተካ በቀን ለብዙ ጎብኚዎች ገለፃ ማድረግ ይኖርብዎታል፡፡ አድካሚነቱ ምን ያህል ነበር?
የማስጎብኘት ሥራ የዲፕሎማሲ ስራ እንደመሆኑ የአገርን ታሪክ፣ የአገርና ህዝብን ባህል፣ የአገርን ኢኮኖሚና ፖለቲካ እያገናዘቡ፣ ህዝብንና አገርን ማዕከል በማድረግ ገለፃ የሚደረግበት ነው፡፡ እንዳልሽው የተለያየ ዓይነት ቱሪስት ነው የሚመጣው፤ ከአገር ውስጥም ከውጭም ማለቴ ነው፡፡ እጅግ በርካት የሆኑ ሰዎችን አግኝቻለሁ። ለምሳሌ የአገር መሪዎች፣ በርካታ የጥናትና ምርምር ስራ የሚሰሩ ባለሙያዎች፣ ለመዝናናትና አዲስ ተመክሮ ለመቅሰም የሚጓዙና መሰል ሰዎችን አግኝቻለሁ፡፡ ምክንያቱም ሁለት አስርት ዓመታት ቀላል አይደሉም፡፡ እንደውም ዝም ብዬ ሳስበው የያኔው ስራዬ አሁን ካለሁበት ስራ አንፃር ሲታይ እጅግ ውስብስብ ነበር፡፡ ምክንያቱም በቱሪዝም ህግ መሰረት አንድ አስጎብኚ “አላውቅም” አይልም፡፡ ስለዚህ የምትጠየቂውን ሁሉ መመለስ ይጠበቅብሻል፡፡ ስትመልሺ ታዲያ ታሪክሽን እንዳታዛቢ ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ አለብሽ፡፡ ምክንያቱም አሁን በዓለማችን ውስጥ ከፍተኛ የታሪክ ሽሚያ አለ፡፡ ሃይማኖትን፣ ዘርንና ቀለምን ሳታይ ለሁሉም እኩል መስተንግዶ መስጠት ግዴታሽ ነዉ። ከዚህ አንፃር ሳየው በጣም የተወሳሰበና አድካሚ ነበር፤ ሆኖም ኃላፊነቴን በአግባቡ ተወጥቻለሁ ብዬ አምናለሁ፡፡
የትምህርት ዝግጅትዎ ከቱሪዝም ሙያ ጋር የተያያዘ ነው?
የትምህርት ዝግጅቴ ከቱሪዝምና ከቅርስ አስተዳደር የወጣ አይደለም፡፡ ከሰርተፍኬት ጀምሮ እስከ ማስተርስ ዲግሪ የሰራሁት ከቱሪዝምና ከቅርስ አስተዳደር እስከ ሄሪቴጅ ማኔጅመንት ድረስ ነው። ለምሳሌ ማስተርሴን የሰራሁት በቱሪዝምና ሄሪቴጅ ማኔጅመንት፣ የመጀመሪያ ዲግሪዬ በቱሪዝም ማኔጅመንት፣ ዲፕሎማዬ በእንግሊዝ አገር ከሚገኝ ካምብሪጅ ኮሌጅ በቱሪዝም እና ትራቭል ኤጀንት ማኔጅመንት ሲሆን ሰርተፍኬቴን ያገኘሁት ደግሞ በአገራችን በቱሪዝም ዘርፍ ፈር ቀዳጅ ከሆነው CTTI ቱሪስት ጋይድ በተባለ ዘርፍ ነው፡፡ እንደምታይው ከቱሪዝም አልወጣሁም ማለት ይቻላል፡፡
አንዳንድ ጎብኚዎች በተለይም ከአውሮፓ እና ከሌሎች አህጉራት የሚመጡት የግንቦቹን አሰራር ረቂቅነት ሲመለከቱ እጃችን አለበት በማለት እንደሚሟገቱ ሰምቻለሁ፡፡ እነዚህን ዓይነት ፈታኝ ጥያቄዎች እንዴት ነበር የሚጋፈጧቸው?  
የዓለም ስልጣኔ መጀመሪያ የአፍሪካ አህጉር እንደሆነ በማስረዳት እጀምራለሁ፡፡ ምክንያቱም አገራችን የሰው ዘር መገኛ ሆና በዓለም ከታወቀችበት ጊዜ ጀምሮ እስካሁን በሌላ ዓለም ቀደምት የሰው ዘር ቅሪት አልተገኘም፡፡ ስልጣኔ የሚነሳው ደግሞ ከሰው ልጅ መሆኑ ግልፅ ነው፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ሰው የኑሮ ጫናዎቹን ለማቃለል ደፋ ቀና ሲልና ለችግሮቹ መፍትሄ ሲፈልግ ነው ስልጣኔ እና ፈጠራ አብሮ የሚመጣው፡፡ የመጀመሪያው መልሴ ከላይ የገለፅኩት ነው፡፡ አውሮፓውያን የስልጣኔ ምንጭ አውሮፓ ናት ካሉ፣ ያ በእነሱ መልክ ነው የሚሆነው። አሜሪካኖችም እንዲያ ሲሉ በእነሱ መልክና እሳቤ ነው፡፡ ለምን ካልሽኝ … የዛሬ 400 ዓመት የተመሰረተች አገር፣ ከሶስት ሺህ ዓመት በላይ ታሪክ ካላት አገር ጋር እኩል መሆን አትችልም፡፡ የሰው ልጅ እስካለ የኪነ-ህንፃም ሆነ ሌላም ስልጣኔ ይኖራል፡፡ ይህን ሳስረዳቸው የዚያ ጥበብና ስልጣኔ ባለቤት እንደሆንን ያምናሉ፤ የመንፈስ ቅናት አድሮባቸው ካልካዱ በስተቀር ማለቴ ነው፡፡
ከኪነ-ህንፃ ጋር በተያያዘ በተለይ የውጭ ጎብኚዎች ምን ይላሉ? እንዴት ነው ስሜታቸው? ይገርምሻል! አግራሞታቸው ሰፊ ነው፡፡ ጥቁር ህዝብ ቤተ-መንግስት ውስጥ የሚኖርባት የአፍሪካ አገር መሆኗ ይገርማቸዋል፡፡ በእነሱ እምነት ቤተ-መንግስት ውስጥ የሚኖረው አውሮፓዊ ብቻ ነው፤ የታላቋ ብሪታኒያ ነገስታቶች፣ የፈረንሳይ ነገስታቶች ብቻ ይመስሏቸዋል፡፡ ይታይሽ … ከ16ኛው ክ/ዘመን መጀመሪያ አንስቶ እስከ 17ኛው ክ/ዘመን፣ በጎንደርና አካባቢዋ ከፍተኛ ቤተ-መንግስታት ተሰርተው ነበር፤ ስልጣኔውም ነበር፡፡ እንደሚታየው ግንባታው ከኖራ ጋር ተቀላቅሎ ዝም ብሎ የተሰራ ሳይሆን የኪነ-ህንፃ ልዩነቱን ጠብቆ በጥልቅ ፈጠራ የተገነባ ነው እና የኪነ-ህንፃ ጥበብ ያረፈባቸው፣ ገላጭ የሆኑ ህብረ-ህንፃዎች ናቸው፡፡ ይህን በአግራሞትና በመደመም ነው የሚመለከቱት፡፡ ከዚህ አንፃር የሚያነሱት ዘርፈ ብዙ ጥያቄዎች ማባሪያ የላቸውም፡፡
ከ400 ዓመት በላይ እድሜ ያላቸው የፋሲል አብያተ መንግስታት ግንባታዎችን ከአሁኑ ዘመን የኪነ-ጥበብ ህንፃ ጋር ማነፃፀር ይቻላል? እርስዎ ያነፃፅሩ ቢባሉ እንዴት ይገልፁታል?
እንግዲህ ውርስ ሊኖር ይችላል፤ የእውቀትና የቴክኖሎጂ ውርስ ማለቴ ነው፡፡ ነገር ግን ሙሉ በሙሉ ውርስ ይኖራል ብሎ መናገር ይከብዳል፡፡ የጎንደርን ኪነ-ህንፃዎች አንቺ ቅድም እንደገለፅሽው የውጭ ዜጎች ናቸው የገነቡት ይላሉ፤ እኔ በፍፁም በዚህ አልስማማም፡፡ የኪነ-ህንፃ ጥበብ ልክ እንደ ሙዚቃ የአለም ቋንቋ ነው፡፡ አንዲት አገር የራሷ ወጥ የሆነ የኪነ-ጥበብ ህንፃ የላትም፡፡ በምን ምክንያት ካልሽ … በእኛ በሰዎች ምክንያት፡፡ ሰው የተለያየ የህይወት ውህደት አለው፤ ይዘዋወራል፡፡ ሲዘዋወር አካባቢውን ይመስላል፤ ከአካባቢው የሚወስደውም ጥበብ ይኖራል፡፡
ያ ሰው ከሄደበት አካባቢ የወረሰውን ጥበብ፣ ሌላ ቀን የራሱ አድርጎ ይተረጉመዋል፤ ነገር ግን የነበረበት አካባቢ ተፅዕኖ ያርፍበታል፡፡ በዚህ የተነሳ ኪነ-ህንፃ የዓለም ቋንቋ ነው ይሉታል፡፡ እዚህ አካባቢ የፖርቹጋል፣ የህንድ፣ የአርመንና የሞሪሽየስ ዜጎች ነበሩ፡፡ በእርግጥ ከጎንደር በፊት የተሰሩ የአክሱም፣ የላሊበላና የየሀ ህንፃዎች አሉ፡፡ ሰዎች እስካሉ ድረስ እንኳን ጥበብ ዘርም ይቀያየራሉ፤ ከዚህ አንፃር የጎንደር ኪነ-ህንፃዎች የእነዚህ አገር ሰዎች ተፅዕኖዎች አለበት ይባላል፡፡
ከስድስቱ የፋሲል አብያተ መንግስታት አንዱ፣ በህንዳዊ የኪነ-ህንፃ ባለሙያ እንደተሰራ ይነገራል። እውነት ነው?
እርግጥ አብዱልከሪም የሚባል ህንዳዊ የኪነ-ህንፃ ባለሙያ በአፄ ፋሲለደስ ዘመን ነበር፡፡ እንደሚታወቀው አፄ ፋሲል አባታቸው አፄ ሱስንዮስ የካቶሊክን እምነት ለማስፋፋት ጥረት ያደርጉ ስለነበር በ1622 (ቅድመ ክርስቶስ ልደት) በርካታ ህዝብ አልቋል፡፡ አፄ ፋሲል ይህን አልተቀበሉም ነበር፡፡ የንግስና ዙፋኑን ሲይዙ 7 ሺህ ገደማ የካቶሊክ ሚሽነሪዎችን ከኢትዮጵያ አስወጥተዋል፡፡ የዛን ጊዜ ታዲያ ኢትዮጵያ ቢያንስ ለ200 ዓመት በሯን ለአውሮፓውያን  ዘግታ ነበር፤ ይህ “የጨለማ ዘመን” እያሉ የሚጠሩት ነው፡፡ ስለዚህ አብዱልከሪም የተባለው ህንዳዊ ሰውዬ ምንም እንኳ ሙስሊም ቢሆንም በኪነ-ህንፃ ጥበብ የተካነ ስለነበር፤ ከአባ ገ/እግዚያብሔር ጋር በመሆን የንጉስ አፄ ፋሲልን ቤተ መንግስት እንዲሰራ ተደርጓል፡፡ በዚህ ምክንያት የህንዶች ኪነ-ህንፃ ተፅዕኖ አለበት፡፡
እስቲ ወደ እርስዎ የአስጎብኚነት ጊዜ እንመለስ። ዝነኛ አስጎብኚ እንደነበሩና እንደነ ሲኤንኤን፣ ቢቢሲ እና መሰል ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች ዘጋቢ ፊልም ለመስራት ሲመጡ፣ በሰከንድ 120 ዶላር ለእርሶ እየከፈሉ በሙያዎ ያገለግሏቸው እንደነበር ሰምቻለሁ፡፡ እውነት ነው? እስቲ ያጫውቱኝ…
ይህ እንግዲህ በፈረንጆቹ 1991 ዓ.ም አካባቢ ነው፡፡ ያኔ “ፍሮም ፖል ቱ ፖል” የተሰኘ ፊልም ተሰርቶ ነበር፡፡ የዛን ጊዜ አብሬ ሰርቻለሁ፤ ክፍያው በሰከንድ ሳይሆን በሰዓት ነበር፡፡ በሰዓት 150 ዶላር! ለእኛ አገር ትልቅ ይመስላል እንጂ ለእነሱ በጣም ዝቅተኛ ክፍያ ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች ገና ከለንደን ከመነሳታቸው ከአንድ ወር በፊት ነው አፈላልገው ያገኙኝ፡፡ ከዚያም ያንን ፊልም ሰርተናል፡፡ ከቢቢሲ በኋላ ከሌሎችም የፊልም ቡድኖች ጋር ብዙ ስራዎችን ሰርተናል፡፡ ለምሳሌ ከጀርመንና ከጣሊያን፣ የፊልም ቡድኖች ጋር ሰርቻለሁ፡፡ ከፍተኛ የህይወት ልምድም አግኝቼበታለሁ፡፡
በጎንደር ከተማ የመንግስት ሰራተኛ ሆነው መኪና የነበረዎት ብቸኛው ሰው እንደነበሩም ሰምቻለሁ …
(ሳ…ቅ!) በአንዳንድ አጋጣሚ በግልሽ ቢዝነስ ስትሰሪ ገንዘብ ታገኛለሽ፡፡ ስለዚህ መኪና መግዛት ቻልኩ፡፡ የዛን ጊዜ መኪና እንደአሁኑ ውድ አልነበረም፤ እኔ በገዛሁበት ወቅት 50ሺ ነበር ዋጋው። የዛሬ 12 ዓመት አካባቢ ማለት ነው፡፡ እርግጥ ያኔ ብሩ በደንብ ዋጋ ነበረው፡፡ ስለዚህ በዚያን ወቅት መኪና መግዛት ያን ያህል የሚያስደንቅ ነገር አልነበረም፡፡
የበፊቷ መኪና ተቀየረች ወይስ…
አልተቀየረችም ራሷ ናት፤ አዲስ አበባ ነው አሁን ያለችው፡፡
ስለ አገራችን ቱሪዝም ስታስብ የሚቆጭህ ነገር ምንድን ነው?
አሁን የሚቆጨኝ ነገር የለም! እኔ ቱሪዝምን በአስተሳሰብ ደረጃ ተረድቼ ስሰራ በነበረበት ወቅት ብዙ ሰው ገና አልተረዳውም ነበር፡፡ ቱሪዝምን የምቾት፣ የቅንጦትና የመዝናናት አድርገው የሚያዩት ወገኖች ነበሩ፡፡ ቱሪዝም ግን እንደዛ አይደለም፡፡ ቱሪዝም የስራ እድል ፈጣሪ ነው፤ ዳቦ ነው፤ ሰላም ነው፤ ሁሉም ነገር ማለት ነው፡፡ አገርሽ ውስጥ ያለውን የባህልና የታሪክ ቦታዎች የምትሸጭበትና የስራ እድል የሚፈጥር ኢንዱስትሪም ነው፡፡ ከዚህ አንፃር ሲታይ የዚያን ጊዜ ሰዎች ቱሪዝምን የተረዱበት አስተሳሰብ ትክክል አልነበረም፡፡ እናም ሰው መቼ በትክክል እንደሚገባው፣ ገብቶትም መቼ ወደ ቢዝነስ እንደሚቀይረውና ተጠቃሚ የሚሆንበትን ቀን እናፍቅ ነበር፡፡ በአሁኑ ሰዓት ግን ሁሉም ሰው ስለቱሪዝም ያወራል፡፡ ስለ ገፅታ ግንባታው፣ ስለ ስራ ፈጣሪነቱና ስለተያያዥ ጉዳዮች ሰው ሲናገር ስሰማ በጣም እደሰታለሁ፤
ምክንያቱም ማንም ሳይረዳሽ ብቻሽን ስለቱሪዝም የምታወሪበት ጊዜ አልፎ አሁን አጋር ስታገኚና ሰው ሲገባው በጣም ያስደስትሻል፡፡
በወሬ ብቻ ነው ወይስ በተግባርም ነው?
አገሪቱ በዚህ ቅኝት ውስጥ እየገባች ነው ብሎ መናገር ይቻላል፡፡ ምክንያቱም ወደ ኢንዱስትሪው እንሸጋገራለን የሚል እቅድ ላይ ነው ያለነው፡፡ ወደ ኢንዱስትሪ ዘመን ሲገባ የበለጠ የሚያይለው የአገልግሎቱ ዘርፍ ነው፡፡ አሁን አገራችን ወደዚያ እየሄደች ነው፡፡ የቱሪስቱ ፍሰት እየጨመረ ነው። የበላይ አመራሮችና ውሳኔ ሰጪ አካላትም ስለቱሪዝም እያቀነቀኑ ነው፡፡ የትራንስፎርሜሽን ኤጀንሲ ተቋቁሟል፡፡ ከዚያ ባሻገር የአገሪቱን የቱሪዝም ምክር ቤት የሚመሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ናቸው፡፡ ይህን ስታይ አገሪቱ ወደ ቅኝቱ ገብታለች ማለት እችላለሁ፡፡ እና ቁጭት የለኝም፤ እንዲያውም በጣም ደስታ ነኝ፡፡
ጎንደር ባሏት ታሪካዊ መስህቦች የሚገባትን ያህል ተጠቅማለች ይላሉ?
እዚህ ላይ ነው ወሬ የምናቆመው! ከተማዋ ያላትን ሀብት በአግባቡ አልምታ፣ የህብረተሰቡን ግንዛቤ አሁን ካለው የበለጠ አስፍታ፣ ህዝቡን ቀጥተኛ ተጠቃሚ አድርጋ የማስኬድ ስራ ገና ይቀራታል፡፡ ቱሪዝም ኢትዮጵያ ውስጥ የ30 እና የ40 ዓመት እድሜ ነው ያለው፡፡ ቅርስ አጠባበቅም እንደዚሁ! ምክንያቱም ቱሪዝም ካልሽ የምትሸጪው ቅርስ ስለሆነ፡፡ ኢትዮጵያ እኮ ከ80 በላይ ብሄር ብሄረሰቦች፣ ከ35ሺህ በላይ ገዳማትና ቤተክርስቲያናት፣ ከ25 በላይ ከፍታቸው ከ4ሺህ ሜ በላይ የሆኑ ተራሮች፣ በምስራቅ አፍሪካ ትልቁ የስምጥ ሸለቆ ስክራች መነሻና ሌሎች አገሮችን የሚያቋርጥ ስምጥ ሸለቆ እንዲሁም አሁንም በአይን የሚታይና አክቲቭ የሆነ እሳተ ጎመራ ያላት ናት። ይህም ሆኖ ቱሪዝም አሁንም በአገራችን ጨቅላ ነው፡፡ ይህንን ወደ ጥቅም ለመለወጥ እኔም፣ አንቺም ሌላውም በየሞያው የቤት ስራ አለበት፡፡ አለቀ፡፡
አሁን ቆመን የምንነጋገርበት ቦታ በእነ ፋሲለደስ ዘመን ራሶችና ተመሳሳይ ስልጣን የነበራቸው ሰዎች የሚኖሩበት “ራስ ግንብ” ነው፡፡ ዛሬ እዚህ ቦታ የተገናኘነውም የጎንደር እህት ከተማ በሆነችው የፈረንሳይ ቬንሰን ከተማ እድሳት ተደርጎለት የምርቃት ስነ-ስርዓቱ በመሆኑ ነው፡፡ በእድሳቱ የተነሳ “ራስ ግንብ” ብቻ ሳይሆን ሌሎችም አብያተ መንግስታት ምንነታቸውን እና የቀድሞ መስህብነታቸውን ያጣሉ የሚል ስጋት አለ፡፡ ይህ እንዳይሆን ምን ምን ቅድመ ጥንቃቄዎች ይደረጋሉ?
አሪፍ ጥያቄ ነው! አገራችን እንደምታውቂው የገንዘብ እጥረት አለባት፡፡ ይህንን ነገር ለመሸፈን ከተሞች አንዳንድ ሁነቶችን ማዘጋጀት አለባቸው፡፡ የገንዘብ ሁኔታ እንዲጎለብት የተለያዩ ፕሮጀክቶችን በመፍጠርና ስምምነቶችን በማድረግ፣ ከእነዚያ የአውሮፓ ከተሞች ተሞክሮዎችን ይወስዳሉ፤ በገንዘብም ይደጎማሉ፡፡ የጎንደር የቬንሰን ታሪክም ይሄ ነው፡፡
ይህን ፕሮጀክት የጀመሩት እርስዎ ነዎት ይባላል?   
ትክክል ነው! ፕሮጀክቱን የጀመርኩት እኔ ነኝ፡፡ ፕሮጀክቱን ቢያንስ ለስድስትና ለሰባት ወር ብቻዬን ነው የሰራሁት፤ ማንም ሰው አያውቅም ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ ነው በግልፅ ወደ ከንቲባ ጽ/ቤትና ወደ ከተማ አስተዳደሩ ያሸጋገርነው፡፡ እነዚህ ሰዎች ጎንደር የቬንስን እህት ከተማ እንደመሆኗ፣ የእነሱም ከተማ ስለሆነች ይህን ራስ ግንብ ማደስ እንደሚፈልጉና የሙዚየም፣ የሀንድክራፍትና የቱሪዝም ልማነት እንዲሆን ገንዘቡን አቀረቡ፡፡ የግንቡ ፕሮጀክት አራት ምዕራፍ ነው ያለው፡፡
አንዱ ሙዚየም ልማት ነው፡፡ ሁለተኛው የሀንድክራፍት ልማት ሲሆን ሶስተኛው ቱሪዝም ልማት ነው፡፡ አራተኛው ደግሞ ግንቡን መጠገን ነው፡፡ አሁን የተሰራው የፕሮጀክቱ አራተኛ መዕራፍ ነው፡፡ የግንቡ ጥገና አልቆ ዛሬ ሊመረቅ እስፍራው ተገኝተናል፡፡
ይህ ግንብ ሲጠገን፣ የዩኔስኮ ንብረት የዓለም ህዝብ ንብረት በመሆኑ፣ ሶስት ነገሮች መጠበቅ አለባቸው፡፡
አንደኛው ኦተንትሲቲ (የዱሮ ይዞታውን የጠበቀ መሆን አለበት)፣ ይህ ማለት ለእድሳቱ የምንጠቀመው እንጨት፣ ድንጋይና ሌሎች ቁሳቁሶችም ጭምር የዱሮ መሆን አለባቸው ማለት ነው፡፡ ሁለተኛው ድሮ ከነበረው ከባቢ ጋር ቅንጅት (integrity) ያለው መሆን አለበት።
ከኢትዮጵያ ኪነ-ህንፃ ሁኔታ ጋር የተስማማና የተቀናጀ መሆን አለበት፡፡ በሶስተኛ ደረጃ “ሲንክሮናይዜሽን” የሚባል ነገር አለ፡፡ ይሄ ማለት አዲስ እንጨት ለእድሳቱ ካስገባሽ አዲስ ለመሆኑ ምልክት ማስቀመጥ አለብሽ፡፡ እነዚህ ሶስት መሰረታዊ ጥንቃቄዎች ተሟልተው ሲታደሱ ቅርሱ የቀደመ ምንነቱን አያጣም፡፡ ይህ ራስ ግንብም በዚህ መሰረት ነው የታደሰው፡፡
እርስዎ ሃገርዎን እንደሚያስጎበኙት ውጭ አገራትን የመጎብኘት ዕድል ገጥመዎታል? እስቲ ስለሌሎች አገራት አስጎብኚዎች ይንገሩኝ…
ለጉብኝት የሄድኩባቸው የውጭ አገሮች ብዙ ላይሆኑ ይችላሉ፤ ነገር ግን በሌላም ስራ የሄድኩባቸው ብዙ ቦታዎች አሉ፡፡ ከአፍሪካ ብንጀምር ሱዳን፣ ኬንያ፣ ዚምባብዌ… ወደ አውሮፓ ስንመጣ ትምህርቴን አልጨረስኩም እንጂ የመጀመሪያ ስኮላርሺፕ ያገኘሁት ቡልጋሪያ ነበር። ምስራቅ አውሮፓን ብትወስጂ ሀንጋሪ፣ ራሺያ እና ሌሎችንም አውቃለሁ፡፡ ከምዕራብ አውሮፓ ፈረንሳይን አይቻለሁ፡፡ ሁለት ጊዜ የመሄድ እድል ገጥሞኛል፡፡ ህንድ ሄጃለሁ፡፡
እንግሊዝም እንዲሁ። የማስጎብኘት ሁኔታው እንደየአገሩ ይለያያል፡፡ በሄድኩባቸው ቦታዎች ሁሉ ጉብኝት አድርጌያለሁ፤ ለቬንሰንም ጉዳይ ፈረንሳይ ሄጃለሁ፣ በአስጎብኚም ጎብኝቻለሁ፡፡ አስጎብኚ ለመሆን የታሪክ ሰው መሆን ያስፈልጋል ብለው ያምናሉ?
የታሪክ ሰው መሆን ያን ያህል ላያስፈልግ ይችላል፡፡ ቢሆንም ግን ጥሩ ነው፡፡ ዋናው ልብ ልንል የሚገባው አስጎብኚ ሁሉም ነገር ማለት ነው፡፡ ቀደም ሲል እንዳልኩት አስጎብኚ ምንም ነገር “አላውቅም” ማለት የለበትም፡፡
ፖለቲከኛ፣ የባዮሎጂ ሰው፣ የጂኦሎጂ ሰው፣ አርኪዎሎጂስት፣ የታሪክ ሰው፣ …ሁሉንም መሆን አለበት፡፡
ዘርፈ-ብዙ እውቀት ያስፈልገዋል፡፡

Published in ባህል

ሲዝን - 2
“ዋናው ነገር ጤና --- እድሜ መስተዋት ነው እናያለን ገና”
ለትራንስፖርት ችግሩ 12ሺ በራሪ ወረቀት ታትሟል
23 ዓመት የዘገየው የአውሮፕላን ስጦታ ለህወሓት ተበረከተ

እንግዲህ ከዛሬ ጀምሮ “ፖለቲካ በፈገግታ ሲዝን - 2” ይቀርባል ማለት ነው፡፡ እኔ የምለው ግን ፅሁፍን በሲዝን ከፋፍሎ በማቅረብ ፈር-ቀዳጅ ነኝ አይደል? የታሪክ ሽሚያ ተጀምሯል ብዬ እኮ ነው፡፡ (ባለቤትነቴ ይመዝገብልኝ!)በእርግጥ እኔም ብሆን ከየትም አላመጣሁትም።  “ሰው ለሰው” እና  የእነ ሰይፉ ቶክ ሾው ሲያደርጉ አይቼ ነው! (እኔ ግን ፅሁፍ በድጋሚ አላቀርብም!) በዚህ አጋጣሚ በሲዝን-2 ምንም ዓይነት የቅርፅ ለውጥ እንዳላደረግሁ ስገልፅላችሁ ኩራት ይሰማኛል፡፡ ወደ ወጋችን ከመግባታችን በፊት ግን እንኳን ለህወሓት 39ኛ ዓመት የምስረታ በዓል በሰላም አደረሳችሁ!! ለማለት እወዳለሁ (አይመለከተንም የምትሉ ዝለሉት!)  
ስለህወሓት በዓል ሳነሳ አንድ ነገር ትዝ አለኝ፡፡ ከጥቂት ሳምንት በፊት በቀድሞ የህወሃት አባላት  የተመሰረተው “አረና” የተባለ ተቃዋሚ ፓርቲ፤በትግራይ የስብሰባ ቅስቀሳ ሲያደርግ አባላቱ እንደታሰሩበት ገልፆ ነበር። ከዚያ ደግሞ “የህወሓት 39ኛ የልደት በዓል ስብሰባዬን አስተጓጎለብኝ” የሚል ስሞታ በዚሁ ጋዜጣ ላይ አነበብኩ፡፡ መጀመርያ ላይ እንዴት ሊሆን ይችላል ብዬ ከራሴ ጋር ተሟግቼ ነበር። በኋላ ግን “ጠርጥር አይጠፋም ከገንፎ መሃል ስንጥር” አልኩ - ለራሴ፡፡ እንኳንም ጠረጠርኩ! ለምን መሰላችሁ? ከህወሓትም ቢሆን አንዳንድ “አድርባይ ካድሬዎች” አይጠፉማ! እነሱማ የተቃዋሚዎችን እንቅስቃሴ በማደናቀፍ የህወሓትን ህልውና የሚያስጠብቁ መስሏቸው ነበር፡፡ ያልገባቸው ምን መሰላችሁ? ህወሓት የታገለው ለነፃነት እንጂ ለአፈናና ለጭቆና አለመሆኑን ነው!
እናላችሁ ---የአረናን ስብሰባ ያስተጓጎሉት ህወሓት 17 ዓመት ሙሉ ለምን እንደታገለ በቅጡ ያልገባቸው “ፍሬሽ ካድሬዎች” እንደሆኑ ጠርጥሬአለሁ፡፡ ወይም የድል አጥቢያ አርበኞች! እንጂማ ቱባዎቹ  ታጋዮች ያንን ሁሉ መስዋዕትነት የከፈሉት ለአፈናና ለጭቆና ሳይሆን ለነፃነትና ለዲሞክራሲያዊ ሥርዓት መስፈን እንደሆነ ጠንቅቀው ያውቁታል፡፡ (አንዳንዶች ሥልጣን ሲጨብጡ ቢዘነጉትም!) ከሁሉም የገረመኝ ደግሞ ስብሰባው የተስተጓጎለው በህወሃት 39ኛ ዓመት የልደት በዓል ሰበብ መሆኑ ነው፡፡ (በዓል እኮ ኢመርጀንሲ አይደለም!)
እኔ የምላችሁ----የኢህአዴግ ድርጅቶች የምስረታ በዓላቸውን ሲያከብሩና ጠቅላላ ጉባኤያቸውን ሲያካሂዱ ለምንድነው እርግማን የሚያወርዱት? (የፓርቲ ባህል ይሆን?) ባለፈው ሰኞ ጠቅላላ ጉባኤውን ያካሄደው ኦህዴድ ያወጣውን የብስጭት መግለጫ ሰምቼ ግርም አለኝ፡፡ ደሞ እኮ ያ ሁሉ እርግማን የወረደው ማን ላይ እንደሆነ ብናውቅ አርፈን እንቀመጥ ነበር፡፡ ክፋቱ ግን የእርግማኑ ባለቤት አልተገለፀልንም፡፡ አገር ውስጥ ይኑር ውጭ? የምናውቀው ነገር የለም፡፡  እንዴ ---- ካልጠፋ ጊዜ ለምንድነው በጉባኤና በበዓል ወቅት ጠላት እየፈጠሩ እርግማን የሚያወርዱት? ቢያንስ በዓሉን በፌሽታ አክብሮ በነጋታው መደንፋት ይቻላል እኮ! (የፀረ-እርግማን አዋጅ እንዲረቀቅ ፒቲሽን እያሰባሰብኩ ነው!)
በበዓል ወቅት ደስ የሚለው ምን እንደሆነ ታውቃላችሁ? እንደ ሱዳኑ ፕሬዚዳንት የአውሮፕላን ስጦታ ማበርከት! (“ያለው ማማሩ” አሉ!) አልበሽር የህወሓትን በዓል እኮ ሞቅ አደረጉት! (የልብ ወዳጅ ይሏል ይሄ ነው!) ትንሽ ቅር ያለኝ ምን መሰላችሁ? ስጦታው ትንሽ በመዘግየቱ! ይታያችሁ---በዚህች አውሮፕላን ነበር  ታጋይ መለስና ጓዶቻቸው በ1983 ዓ.ም ከካርቱም ወደ አዲስ አበባ የተጓዙት፡፡ (ታሪካዊ አውሮፕላን ናት እኮ!) እኔማ ፓይለቱንም ይሰጡናል ብዬ እየጠበቅሁ ነው (ታሪካዊ ፓይለት ነዋ!)
እስቲ ከበዓል ወጎች ወደ ልማታዊ ወጎች ደግሞ እንግባ፡፡ እንዳለመታደል ሆኖ ግን  መብራት፣ ውሃ እና ስልክ እንዲሁም ትራንስፖርት በሌሉበት ነው ስለልማት የምናወጋው፡፡ ግን ይሁን ---ምንም ቢሆን የእድገት ምስቅልቅል የፈጠረው ችግር ነው፡፡  እንደ ማንኛችንም የመዲናዋ ነዋሪ በትራንስፖርት ችግሩ  ግራ የተጋባው ኢቴቪ፤ ሰሞኑን ምን እንዳደረገ ታውቃላችሁ? የትራንስፖርት ችግሩን በተመለከተ ምላሽ የሚሰጠው ቢያጣ ተራ አስከባሪዎችን መፍትሄው ምንድነው ሲል ጠየቀ (“የቸገረው እርጉዝ ያገባል” አሉ!) ናላችሁ--- አንድ ተራ አስከባሪ ለኢቴቪ ጥያቄ እንዲህ ሲል መለሰ “የትራንስፖርት እጥረት የሚፈጠረው ሠራተኛው ከየመሥሪያ ቤቱ በአንድ ጊዜ ግር ብሎ ስለሚወጣ ነው” አለና መፍትሄውን ሲያስቀምጥም “ሠራተኛው ተራ በተራ ቢወጣ እኮ መጨናነቅ ሳይፈጠር ሁሉም ዘና ብሎ ወደ ቤቱ ይገባል” ብሎ አረፈው - ተራ አስከባሪው፡፡ አስቂኝ መፍትሄ ቢሆንም ከአዲስ አበባ ትራንስፖርት ቢሮ ሃላፊዎች መቶ በመቶ  ይሻላል፡፡
 የአዲስ አበባ ትራንስፖርት ቢሮ የኮሙኒኬሽን ሃላፊ ያለችውን ስሙልኝ “ቢሮው እንደቢሮው የምንሰራው ሥራ አለ፤ ባለድርሻ አካላቱም እንደ ባለድርሻ አካላት---” በቃ! ይሄን ብቻ ነው ማለት የቻለችው፡፡ (ምንም አላለችም እኮ!) አንድ ሌላ የቢሮው ሃላፊ ለትራንስፖርት ችግሩ መፍትሄው ምንድነው ሲባሉ ምን እንዳሉ ታውቃላችሁ? ተሳፋሪዎች ችግር ሲገጥማቸው ለቢሮአቸው ይጠቁሙ ዘንድ 12 ሺ በራሪ ወረቀቶችን አሳትመው ማሰራጨታቸውን ተናገሩ (በራሪ ወረቀት ታክሲ አይሆንም እኮ!) ከሁሉም ግን የታክሲ ባለንብረቶች ማህበር መሪ የሰጡት መፍትሄ ይሻላል “ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት ከተፈለገ ዘርፉ ባለሃብቶችን አማላይ መሆን አለበት፤በአሁኑ ሰዓት  ወደ ዘርፉ የሚገባ ባለሃብት የለም” ብለዋል፡፡ (“እውነቱን ተናግሮ የመሸበት ማደር---” አሉ!)
 ጠ/ሚኒስትሩ ባለፈው ሰሞን የሰጡትን ጋዜጣዊ መግለጫ እንዴት አገኛችሁት? እኔ በበኩሌ ታዝቤአቸዋለሁ - ጠ/ሚኒስትሩን። እንዴ---ከእኛ ከነዋሪዎቹ እሮሮ ይልቅ ለእነ መብራት ሃይል ጥብቅና የቆሙ መሰሉ እኮ፡፡ (ፓርቲያቸው አዟቸው ይሆን እንዴ?) እውነቴን እኮ ነው … በውሃ እጦት … በመብራት መጥፋት …በኔትዎርክ መቆራረጥ የምንሰቃየው እኛ እያለን እሳቸው ቃላቸውን ጠብቀው ለማያውቁት ተቋማት ተሟገቱላቸው፡፡ (ሰው አግኝተዋል?) እኔማ እንደዚያን እለት ንግግራቸው፣ ፓርቲያቸው የውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን የኮሙኒኬሽን ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ያደረጋቸው  መስሎኝ ነበር፡፡ እናላችሁ…የምንጠጣው ውሃ እያሳጣን ለሚያስጨንቀን ተቋም ሲከራከሩ “ውሃና ፍሳሽ በየጊዜው ውሃ ሲቋረጥ ህብረተሰቡን ይቅርታ ይጠይቃል” አሉ፡፡ (የኛ አገሩን አልመሰለኝም!)
ለነገሩ ይቅርታ ተባልንም አልተባልንም አይሞቀንም አይበርደንም (ለምደነዋላ!( ለጊዜው ግን ለአዲስ አበባ ነዋሪ አንገብጋቢው ጉዳይ ይቅርታ አይደለም፡፡ ውሃ ነው! መብራት ነው! ኔትዎርክ ነው! ጠ/ሚኒስትሩ ሽንጣቸውን ገትረው የተከራከሩላቸው እነመብራት ኃይል፤ነዋሪውን  ይቅርታ ካልጠየቅን ብለው ድርቅ የሚሉ ከሆነ ግን እንዲህ ያደርጉ፡፡ የይቅርታ የሥራ ሂደት ባለቤት ይሹሙ፡፡ (ራሱን የቻለ ሥራ እኮ ነው!) እስከዚያው አላስችል ካላቸው ደግሞ በየቀኑ ይቅርታ መጠየቁን ስለማይችሉት አንዴ የስድስት ወሩን ወይም የዓመቱን ይቅርታ ያሽሩን (መብራት፤ውሃና  ኔትዎርክ መጥፋቱ እንደሆነ አይቀር!)
በነገራችሁ ላይ የአዲስ አበባ መስተዳድር ቴሌቪዥን ሰሞኑን በእነ ቴሌና መብራት ኃይል ላይ የሰራው ፕሮግራም አንጀቴን አርሶኛል፡፡ (ቀላል አሸሞሩባቸው!)  ያውም እኮ በሙዚቃ እያጀቡ ነው፡፡  የደንበኞች ቅሬታን ያሰሙና የአብዱ ኪያርን “እስከ መቼ---” የሚል ዘፈን ይለቃሉ - በማጀቢያነት፡፡ ከዚያ ደግሞ የቴሌኮሙ  ኃላፊ በ6ወር ውስጥ የኔትዎርክ ችግር እንደሚፈታ ሲናገሩ ያሰሙንና  “ዋናው ነገር ጤና… ዕድሜ መስተዋት ነው እናያለን ገና” የሚል ዘፈን ያስኮመኩሙናል፡፡ (ለካስ አሽሙር ከፅሁፍ ይልቅ በቲቪ ይመቻል!) እኔማ ---የሌሎችም ባለስልጣናት ንግግርና መግለጫ እንዲህ በዘፈኖች ታጅቦ ቢቀርብልን  ብዬ ተመኘሁ፡፡ (ከእነለዛው ነው ታዲያ ማለቴ ከእነአሽሙሩ!)
  በመጨረሻ የ100 ብር የሞባይል ካርድ የሚያሸልም ጥያቄ ላቅርብና ልሰናበት፡፡
ጥያቄ - ከሚከተሉት ውስጥ ለቴሌ ኔትዎርክ መቆራረጥ ምክንያት የሆነው የትኛው ነው?
ሀ. ሳቦታጅ (አሻጥር)
ለ. ሰማይ ጠቀስ ፎቆች (ባይኖሩንም)
ሐ. የኦፕቲክ ፋይበር ስርቆት
መ. የመብራት መጥፋት
ሠ. ኪራይ ሰብሳቢነት
ረ. ሁሉም መልስ ናቸው
አሸናፊዎች የ100 ብር ካርዳቸውን የሚያገኙት በቴክስት ሜሴጅ ነው - እንደ ቴሌ ፍቃድ ማለት ነው፡፡
(ኔትዎርክ ከተገኘ ይሸለማሉ!)





      ተምሮ ላገሩ የማይጠቅም ወይም ዕውቀቱ የጋን መብራት የሆነ ምሑር ለጦቢያ አይበጃትም! የሕዝቡን ሰቆቃ የሚያዳምጥ፣በወገን ላብና ደም ሆዱን አሳብጦ፣ ንብረት አካብቶ የሚናጥጥ ባለስልጣን ለጦቢያ አይበጃትም! የሕዝብን አንደበት ለጉሞ ዲሞክራሲያዊና ሰብዓዊ መብትን ገፍፎ፣ ያገርን ስም አጥፍቶ፣ ውበቷን ጥላሸት ቀብቶ፣ ትውልድ ሲመክን የዳር ተመልካች ሆኖ ሐይ! የማይል፣ ያገር ሉዓላዊነትና የወገን ቁስል ሰቆቃ የማይሰማው፣ በወተት ፋንታ መርዝ እየተጋቱ ለሚገኙ አዳጊና አገር ተኪ ሕፃናት የማይቆም ሥርዓት ለጦቢያ አይበጃትም!!
እንዳለመታደል ሆኖ  ጦቢያችን በብዙ ጠላቶች የተወረረች አገር ሆናለች፡፡ ረሐብና ድህነት ቀንደኛ ጠላቶቿ ናቸው፡፡ ኋላ ቀር ፖለቲካዊ ባህልና ሥርዓትም እንደዚሁ፡፡ የአልሸባብ አሸባሪ ቡድንም ክፉ ዓይኑን የጣለባት ሌላው ጠላቷ ነው፡፡ በታሪካዊ ጠላትነት የምትታወቀው ግብፅም የዋዛ የምትታይ ጠላት አይደለችም፡፡ ከምንም በላይ ደግሞ ለዚህ ጽሑፍ መነሻ የሆነኝ ቀንደኛ ጠላት የባህል ወረራ ሲሆን ያለ ጥይት ኮሽታ ወደርየለሽ ትውልድ አጥፊና ተተኪ የሚያሳጣ የጠላቶች ሁሉ ጠላት ነው፡፡
ባህል (Culture) ለሰው ልጅ ከሚቀርቡ እንስሳት (the primates) ሰውን ልዩ በማድረግ አካባቢውን በፍጥነት በመቆጣጠር ለዛሬው ሰውነቱ ያበቃው ትልቁ መሣሪያ ነው፡፡ በአሜሪካዊው ‘አንትሮፖሎጂስት’ ኤድዋርድ ታይለር አገላለጽ መሠረት፣ ባህል በሁለት ተከፍሎ ሊታይ ይችላል፡፡
በቁስ የሚገለጹ (material culture) ወይም (artifacts) ለምሳሌ፣ ያገራችንን ባህል የሚያሳዩ ቁሳቁሶች ሆነው ለጦር ሜዳ የሚያገለግሉ ጦር፣ ጋሻ፣ የሙዚቃና ሙዚቃ ነክ ባህል መሣሪያዎች-- ማሲንቆ፣ ክራር፣ በገና፣ እምቢልታ፣ ወዘተ ናቸው፡፡
በቁስ የማይገለጹ (non-material culture) ኃይማኖቶች፣ እምነቶች፣ ሞራል፣ ህግ፣ ልማዶች፣ የሠርግ ዘፈን፣ ፉከራው፣ ቀረርቶው ወዘተ … ናቸው፡፡ አንድ ሕፃን ከተወለደ ቀን ጀምሮ የቋንቋ ልሳነ ዕድገቱን በማዳበር እየተኮላተፈ በሚያየው፣ በሚሰማውና በሚዳስሰው ነገር ሁሉ ሐሳቡን ለመግለፅ ወይም ለመናገር ይሞክራል፡፡ ያየውን ለመተግበር ይጥራል፡፡ በጥቅሉ የመማርን ሂደት ይጀምራል፡፡ የሕፃኑ የመጀመሪያ ት/ቤት ቤተሰብ ሲሆን፣ በአካባቢ አብረው የሚያድጉ ልጆች (peers)፣ ት/ቤትና ሚዲያ ሌሎች የሚማርባቸው ወኪሎች (socializing agents) ናቸው፡፡
አንድ ሕፃን የማኅበረሰቡን ወይም ኅብረተሰቡን ሕግና ደንብ ጠብቆ እንዲያድግና ከአካባቢው ጋር ራሱን አጣጣሞ በዲሲፕሊን ታንፆና መልካም ሰብዕና ተላብሶ እንዲያድግ የቤተሰቡ ሚናና ኃላፊነት ከባድ ነው፡፡ ማኅበረሰቡ የማይቀበለውን ሥራ የፈፀመ ወይም ደንብ የጣሰ ልጅ ሲያጋጥም “አሳዳጊ የበደለው” የሚል ክፉ ስም ይለጠፍበታል፡፡ ይህ እንዳይሆን የወላጆች ሚና ታላቅ ነው፡፡
ከጎረቤት አብሮ አደግ (peers) እና ከት/ቤት የክፍል ጓደኞች፣ ከመምህራን፣ ከት/ቤቱ ማኅበረሰብ የሚቀስመው በጎም ይሁን መጥፎ ትምህርት በልጁ ሕይወት ላይ የሚያሳድረው አሉታዊ ወይም አወንታዊ ተፅዕኖ የዋዛ አይደለም፡፡
ሚዲያ አራተኛው “ሶሻላይዚንግ ኤጀንት” ሲሆን መጻሕፍት፣ ጋዜጦች፣ ቴሌቪዥን፣ ሬዲዮ፣ ፊልሞች፣ ኢንተርኔት ወዘተ … በዚሁ ሥር የሚካተቱ ሆነው በተለይም ሠለጠኑ በተባሉ ከተሞች ላይ ላሉ ሕፃናት እና ወጣቶች ቅርብ በመሆናቸው ተጠቃሚው ወይም ተጎጂው የከተማው ወጣት ይሆናል፡፡ በተለይ ኢንተርኔትና ፊልሞች በባህላችን ላይ የተጣሉ ጋሬጣዎች ናቸው፡፡
የአውሮፓ፣ የአሜሪካና ሌሎች የሠለጠኑ አህጉራት፣ ሕፃናቶቻቸው ከረቀቀው የዓለም ቴክኖሎጂ ጋር በለጋ እድሜያቸው እንዲተዋወቁላቸው የማይፈነቅሉት ድንጋይ የለም፡፡ የአውሮፕላን አሻንጉሊት ፈታተው እስከመገጣጠም ድረስ እንዲካኑ ይደረጋል፡፡ ለፈጠራ ይዘጋጃሉ። ጎጂና ጠቃሚ ነገሮችን ከወዲሁ እንዲያውቁ ተደርጎ በጥንቃቄ ያድጋሉ፡፡ መንግስታቸው ከወላጆች ባልተናነሰ ለሕፃናት እንክብካቤ ያደርጋል። “እኔ ከሞትኩ …” የሚለውን የሐገሬን ብሒል አይከተልም። ይልቅስ አገር ተተኪ እንዳታጣ ይታትራል፡፡ ይተጋል፡፡
ወደ አገራችን ነባራዊ ሁኔታ ስንመለስ ግን የአዳጊ ልጆችና የወጣቶች ጉዳይ አሳዛኝ ሁኔታ ውስጥ ነው ያለው፡፡ ከአውሮፓና ከአሜሪካ ወሲብ ቀስቃሽ ፊልሞች (Pornography) ወደ አገር በገፍ ሲገቡና በየቪዲዮ ቤቱ ታጭቀው፣ ድምፅ በሌለው መሣሪያ አዳጊዎችን ሲያጠፉ ሐይ የሚል በመጥፋቱ  በአገሪቱ አዲስ ትውልድ ላይ የሞት ጥላ እያንዣበበ ይገኛል፡፡
ከአፄ ኃይለስላሴ ዘመነ መንግስት ጀምሮ የሕዝቡን አኗኗር፣ ወግ፣ ባህል፣ እሴትና ዲሲፕሊን በወፍ በረር መቃኘት አሁን ለቆምንበት ዘመን ማሳያ ስለሚሆን እነሆ!
በዚያ የዘውድ ሥርዓት ወግና ባህል የሚከበርበት፣ የማኅበረሰቡን እሴቶችና የአኗኗር ዲሲፕሊኖች ያልጠበቀ ሰው የሚወገዝበት ዘመን ነበር፡፡ ዳንስ ቤቶች ቢኖሩም ውሱንና ምራቃቸውን ዋጥ ያደረጉ፣ ኃላፊነት የሚሰማቸው ሰዎች፣ ባህሉን ሳይጥሉ የሚዝናኑ ወጣቶች ያለ ሰዓት እላፊ ገደብ የሚዝናኑበት ክለቦች ነበሩ፡፡ ሲጋራ ማጨስ የአራዳነት ምልክት በመሆኑ እነ “ቫይስሮይ” እነ “ኬንት” በየዳንስ ቤቱ እንደጉድ ይጨሱ ነበር፡፡ ነገር ግን አንዲት ሴት እርቃኗን እንድትደንስ መረን አትለቀቅም ነበር፡፡ ይህን ተግባር ፈፅማ የት ልትገባ? የት ልትኖር? በማን አገር?
በአደባባይ በጣም አጭር ቀሚስ በዘመኑ አጠራር “ሱፐር ሚኒ” ለብሳ በከተማ ስትዘዋወር የታየች ሴት፣ በፖሊስ ታድና የገንዘብና የእስር ቅጣቷን ቀምሳ ትወጣ ነበር፡፡ ሚዲያዎችም ይህንን ተቀባይነት የሌለው ተግባር ይዋጋሉ፡፡ ኅብረተሰቡም “ውጉዝ ወከመ አርዮስ” በማለት ይረግማል፡፡ መንግስትና ህግ አስከባሪው አካልም የራሱን ሚና ይጫወታል፡፡
ወደ ደርግ ዘመነ መንግስት ስንመጣ ለየት ያለ ነገር እናስተውለናል፡፡ መጤና ጎጂ ባህልን ለመዋጋት ሥር-ነቀል እርምጃ ወሰደ፡፡ የምሽት ክበቦችንና ጭፈራ ቤቶችን ጥርቅም አድርጎ ዘጋ፡፡ በቀን የመጠጣትን ልማድ ለማስወገድ በቀን ሲጠጣ የተገኘ፣ ጠጅ የተሞላበት ብርሌ በአናቱ ይዞ በጠራራ ፀሐይ “እኔን ያየህ ተቀጣ…” እያለ በአደባባይ እንዲዞር ተደረገ፡፡ ወጣት የሆነ ሁሉ ከ12 ሰዓት በፊት ቡና ቤት አልኮሆል ሲጎነጭ ቢገኝ፣ የቡና ቤቱ ባለቤት አበሳውን ያይ ነበር፡፡ ጠጪውም እንደዚያው፡፡
ገደብ የለሽ ወሲብን ለመግታት የጋብቻ ውል የሌላቸው ጥንዶች ለቀን ወይም ለአዳር አልጋ እንዳይከራዩ አገደ፡፡ ሴተኛ አዳሪነትን ላለማበረታታት በተለያዩ ፋብሪካዎች እንዲቀጠሩና ሴተኛ አዳሪዎችን መልሶ ለማቋቋም ብዙ ሙከራዎች ተደረጉ፡፡ ጉለሌ ጋርመንትና ሳሙና ፋብሪካዎች በምሳሌነት ይጠቀሳሉ፡፡ ወጣት ብቻ ሳይሆን ማንም ሰው በሥራ ሰዓትና በግልፅ ሁኔታ በረንዳ ላይ ተኮልኩሎ ጫት መቃም ተወገዘ፡፡ ወጣ ያለ መጤ አለባበስና ስታይል የሚያሳይ ወጣት “ጆሊ ጃኪዝም” የሚል ስም ተሰጥቶት፣ በልዩ ዓይን ስለሚታይ ከማኅበረሰቡ ቅጣት (Social sanction) ለመዳን ራሱን ከአገሩ ባህል ጋር ወዲያው ያመሳስላል፡፡ የወንድ ወይዛዝርትነትና የአሜሪካን “ሂፒዎች” አለባበስ፣ አጋጌጥ በአገራችን አይታለምም ነበር፡፡
ውድ አንባቢያን! በደርግ ዘመን የተፈፀመው ሁሉ ትክክል ነው ወይም ስህተት ነው የሚል አቋም ይዤ እንዳልተነሳሁ እንድትገነዘቡልኝ አደራ እያልኩ፣ ለንፅፅር የቀረበ በመሆኑ ዳኝነቱን ለእናንተ ትቼዋለሁ፡፡
ኢሕአዴግ በግንቦት ወር 1983 ዓ.ም አገሪቱን በቁጥጥር ስር አዋለ፡፡ ደብዛቸው ጠፍቶ የነበሩት የምሽት ክበቦች ቀስ በቀስ መከፈት ጀመሩ፡፡ ጫት ቤቶች ቁጥራቸው በእጥፍ ጨመረ፡፡ የቃሚው ወጣት ቁጥርም እንደዚሁ፡፡ ድሮ ባገር ቤት በአዋቂ (ጠንቋይ) ቤቶች ከቅል ተሠርቶ የትልቅ ብርሌ ቅርፅ ያለው፣ የትምባሆ ቅጠል ተጨቅጭቆ (ተወቅጦ) በቀሰም ትምባሆ የሚማግበትና የሚንበቀበቅ “ጋያ” ነበር፡፡ ያ በዘመናዊ መልክ ከአረብ አገራት “ሺሻ” በሚል ስያሜ ‘በኮባልት’ ዓይነት ብረት ተሠርቶ ወደ አገራችን በገፍ ገባ፡፡ በሺሻ ስም ኮኬይን፣ ማሪዋና፣ ሄሮይን፣ የመሳሰሉት ጠንካራ የሀሺሽ ዓይነቶች (Hard drugs) በኮንትሮባንድ መልክ ገብተው መቸብቸብ ጀመሩ፡፡ እድሜ ለጃማይካዊያን! “ካናቪስም” ረከስ ባለ ዋጋ በተጠቃሚው እጅ ገባ። ወጣቱ በእነዚህ ሐይቆች እየሰጠመ የተለያየ የወንጀል ድርጊት ተዋናይ ሆነ፡፡
ከባለስልጣናት ጀምሮ እስከ ባለፀጋዎች ድረስ ዳንኪራ የሚመታባቸው፣ ሴቶች እርቃናቸውን  ሆነው የሚደንሱባቸው፣ ሐሺሽ የሚጨሱባቸው ጭፈራ ቤቶች በዋና ከተማይቱ አብበው የወጣቱን ልብ በመሰብሰብ ወቃጣ አደረጉት፡፡ ለአገር የማያስብ ስልብ ሆነ፡፡
በችግርና በተለያየ ምክንያት ሥራዬ ብለው በሴተኛ አዳሪነት ከተሠማሩት እህቶቻችን በተጨማሪ፣ ኑሮን ለማሸነፍና በአለባበስም አንሶ ላለመታየት አንዳንድ ሴት የመንግስትና የግል ድርጅት ሠራተኞች እንዲሁም የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች በደላሎች አማካኝነት ሥጋቸውን በገንዘብ መለወጥ ጀመሩ፡፡
ስለ ኢንተርኔት አጠቃቀም፣ ምን ዓይነት ፊልም መርጠው ማየት እንደሚገባቸው የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርት ያልተሰጣቸው አዳጊዎችና ወጣቶች … በወሲብ ፊልምና በ “ፌስ ቡክ” ላይ ተጥደው በመዋል የደባል ሱስ ቁራኛ፣ የልጅ ጡረተኛ ሆኑ፡፡ ወጣቱ ስለ ዕድገትና ብልፅግና እንዳያስብ የተሰጠው ማደንዘዢያ (anesthesia) እንዳስተኛው ቀረ፡፡  
ኤፍኤም ሬዲዮ ጣቢያዎች፣ አደንዛዥ ዕፅን ጨምሮ በሌሎች ማህበራዊ ጠንቆች ዙርያ ወጣቱንና ማኅበረሰቡን በማስተማር ፈንታ፣ ለአውሮፓ እግር ኳስ የላቀ ትኩረት ሰጡ፡፡ እገሌ የተባለው ተጫዋች ሚስቱ ባረገዘችበት ወቅት የተለየ ፒጃማ ወይም ፓንት እጅግ ውድ በሆነ ፓውንድ ገዛላት፣ የሕፃኑ ልደት ሲከበር በአልማዝ የተሠራ ስጦታ ተገዛለት፣ እንቶኔ የተባለው ተጫዋች በዚህን ያህል ፓውንድ /ዶላር/ ለዚህ ክለብ ተሸጠ፡፡ ሌላው ታዋቂ ተጫዋች ከሠርጉ በኋላ ለጫጉላ ሽርሽር ውድ በሆኑ የዓለም መዝናኛዎችና ሆቴሎች ተዝናና ወዘተ፡፡ የፈጀው ዘግናኝ ገንዘብ ይጠቀሳል፡፡ ወገኖቼ፤ ድህነትና የኑሮ ውድነት ለሚጨፍርበት መከረኛ ሕዝብ ይሄ ምኑ ነው? እኔ ሁሌም እንቆቅልሽ የሚሆንብኝ ከተትረፈረፈው የሚዲያ የአየር ሰዓት ጥቂቱ እንኳን  ለምን ትውልድ ለሚያድን ትምህርት እንደማይውል ነው፡፡
የሥነ-ልቦና እና የሶስዮሎጂ ባለሙያዎችን በማሳተፍ ስለ ሕፃናት አስተዳደግ፣ ስለ ዲሲፕሊን፣ ስለ ባህል፣ ስለ ወጣት አጥፊነት፣ ስለ ትምህርት ክትትልና ስለ ውጤታማ የአጠናን ዘዴ፣ ስለ መጤ (ዲቃላ) ጎጅ ባህል፣ ስለ ሥነ-ተዋልዶ ጤና ትምህርት (ዕድሜያቸውን ባገናዘበ መልኩ)፣ ስለ ቅድመ ጋብቻ ወሲብ፣ ስለ አባላዘር በሽታዎችና ኤች አይቪ ኤድስ ወዘተ … ወጣቱ እንዲማር ቢደረግ አንዱ የትውልድ ማዳን ሥልት አይሆንም ነበር? የታሪክ ምሁራንን በመጋበዝ ውድ ስለሆነው ታሪካችን፣ ስለ ቅድመ አያቶች ጀግንነት፣ ስለ አገር ፍቅር፣ ስለ ቅርሶቻችን እንዲማሩ ቢደረግ ጠቀሜታው የጎላ አይሆንም?
የሌሎች ዓለማትን ተሞክሮ በመውሰድ የዘመኑን ድንቃድንቅ የሣይንስ ግኝቶችና የቴክኖሎጂ ውጤቶች ሕፃናት እንዲያውቁ ቢደረግ---ከልጅነታቸው ጀምሮ የፈጠራ ችሎታቸውን ቢያዳብሩ ብዙ ሳይንቲስቶች አናወጣም ነበር? መልሱን ለአንባቢያን ትቼዋለሁ፡፡
እጅግ አሳሳቢ እየሆነ የመጣው የግብረ ሰዶማዊያን ጉዳይ ሌላው ትኩረት የሚሻ ማህበራዊ ቀውስ ነው፡፡ በተለይም በ1ኛ ደረጃ ት/ቤቶች በሚማሩ ሕፃናት ወንድ ልጆች ላይ የሚፈፀመው የግብረሰዶማዊያን ሠይጣናዊ ድርጊት ለጆሮ የሚቀፍ ነው፡፡ ዘግናኝ ወንጀል እየተሠራባቸው ጉዳቱ በደረሰባቸው ልጆችና ወላጆች ገመና ተዳፍኖ እንዳልፈነዳ “ቮልኬኖ” ከተማይቱን እያንቀጠቀጠ ይገኛል፡፡
አገሪቱ ተስፋ የጣለችባቸው የነገው ዶክተሮች፣ መሀንዲሶች፣ ተመራማሪዎች፣ ሣንቲስቶች ወዘተ … ባልተጠበቀ ሁኔታ የሳጥናኤል ኮሌጅ ተመዝጋቢና ተመራቂ ሆነው ማየት በተለይም ለወላጆች ዘግናኝ ነው፡፡ ሰቆቃ ነው፡፡ የወለደ ፍርዱን ይስጥ። ኢትዮጵያዊ  ነኝ የሚል ዜጋ ሁሉ ተጠቂ የሆኑ ሕፃናትን እንደራሱ ልጆች አድርጎ በዓይነ ሕሊናው ይመልከት፡፡
የአዳጊ ሕፃናትን ጉዳይ ችላ ብሎ ወይም ስለነገው አገር ተረካቢ ወጣት እጣ ፈንታ ምንም ሳይጨነቁ ስለ ፖለቲካ፣ስለ አገር ዕድገትና ብልፅግና፣ ስለ ዲሞክራሲ፣ ስለ ግብርና መር ኢኮኖሚ፣ ስለ 1ለ5 አደረጃጀት፣ስለ ዩኒቨርስቲዎች ቁጥር መጨመር፣ ስለ ካይዘን፣ ስለ መድብለ ፓርቲ ሥርዓት፣ ስለ  ፎረም፣ ስለ ካቢኔ፣ ስለ ፓርላማ፣ ስለ አነስተኛና ጥቃቅን ወዘተ … መለፈፍ በአገር ሞት ላይ እንደመዝፈን የሚቆጠር ነው፡፡ የህፃናትን ህይወት ሳንታደግ የቱንም ያህል ለልማት ብንታትር ትርፉ ከንቱ ድካም ነው፡፡ ልማት ልማት ብለን የለማችውን አገር የሚረከበን እንዳናጣ እሰጋለሁ። እናም መንግስትን ጨምሮ የሚመለከታቸው ክፍሎችና ሕብረተሰቡ ለአዳጊዎቻችን ልዩ ትኩረት ይስጥ፡፡


Published in ህብረተሰብ

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
እኔ የምለው…እንግዲህ ጾም መግባቱም አይደል! ጿሚዎች… ‘እውነተኛ ጾም ያድርግላችሁማ!’
ስሙኝማ…አንድ የኃይማኖት አባት ስለ ጋብቻ እያስተማሩ ነበር፡ እናላችሁ…የተለመዱትን ነገሮች ከተናገሩ በኋላ ምን አሉ መሰላችሁ… የዘንድሮ ጋብቻ መቶ በመቶ አይደለም፣ አርባ/ስድሳ ነው፡ ስለዚህ ተቻቻሉ፡፡” አሪፍ አይደል!
ስሙኝማ…እንደምንሰማውና አንዳንድ ጊዜም እንደምናየው ዘመናዊው ትዳር ውስጥ የሚታዩ ነገሮች ለማስረዳትም አስቸጋሪ ናቸው፡፡
ለምሳሌ ሴቷ አሥር፣ ወንዱ ዘጠና የሆኑበትን ትዳር አስቡት፡፡ አረቄውን ሲገለብጥ ያመሽና ሆዱን ገልብጦ ቤት ይገባል፡፡ ከዛ ድሮ የሚያውቃቸውንና ካመሸበት ቤት የሰማቸውን ስደቦች ያወርድባታል፡፡ ራት ይቀርብለታል፡
“ሴቱ በየቤቱ ስንት ይሠራል፣ ይሄን የጎርደሜ ወንዝ የመሰለ ልቅላቂሽን ወጥ ብለሽ ታቀርቢያለሽ!” እሷ እኮ ልቡ ሌላ ዘንድ “ልቡ ውጪ ውጪ እንዳይል…” ብላ ዘጠኝ ሰዓት የጣደችውን ወጥ ያወጣችው ከምሽቱ ሦስት ሰዓት ነው! ደግሞም ጆርዳና ኩሽናም ይሁን ሌላ ላይ ያየችውን የማጣፈጫ ዘዴዎች ሁሉ ተጠቅማለች፡፡
“እሺ አሁን ይሄ ወጥ ምን ጎደለው ነው የምትለው!”
“ዝም በይ! አፍ አለኝ ብለሽ ታወሪያለሽ!” በስድብ ካለፈላትም ጥሩ ነው፡፡ እናማ… ‘ክላይማክሱ’ ላይ ምን ይላል መሰላችሁ…“እኔ እኮ አንቺን ያገባሁ ጊዜ ዓይኔን ምን ጋርዶኝ እንደነበር…!”
ደግሞላችሁ አረቄው ያልታሰበበትን የሰውነት ክፍል ‘ይተነኩስና’ እንትንዬ ነገር ሲፈልግ እንኳን…አለ አይደል…“አሁን መለፍለፉን አቁሚ! አውልቂና አልጋው ላይ ውጪ!…” ምናምን የሚል ትዕዛዝ ነው። “ዛሬ ቀኑን ሙሉ ሆዴን ሲቆርጠኝ ነው የዋለው…” “ቡአ ወረደኝ መሰለኝ ሲያቀለሸልሸኝ ይኸው ሦስት  ቀኔ…” ምናምን ብሎ ምክንያት አይሠራም፡፡
እናላችሁ… በሴት አሥር ወንድ ዘጠና ያለው ግንኙነት ደግሞ ምን አለፋችሁ… ‘ትዌልቭ ይርስ ኤ ስሌቭ’ ፊልም ላይ ያለውን ‘የባሪያና አሳዳሪ’ ነገር ሊሆን ምንም አይቀረው፡፡
ደግሞላችሁ…ወንድ አሥር ሆኖ ሴት ዘጠና ስትሆን ሌላ የተከታታይ ፊልም ጽሁፍ በሉት፡፡ በሆነ ነገር ይተነኳኮሱና “ተው እባክህ…አሁን አዲስ አበሻ ቀሚስ መግዛት ቁም ነገር ሆኖ ነው! የሰዉ ባል ስንት ነገር ያደርጋል…”
“አምስት ሺህ ብር ከየት ላምጣ…ደሞዝተኛ ነኝ እኮ! በቀደም አይደለም እንዴ ለቀሚስና ለቦዲ ብለሽ ሦስት ሺህ ብር የወሰድሽው!”
ከት ብላ ትስቅበታለች፡፡ (ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…በማሾፍ ከት ብላ መሳቅ የምትወድ ሚስት ላለችው አባወራ እዘኑለት፡፡ ያን ጊዜ ነው…“ነገሩ ነው እንጂ ጩቤው ሰው አይጎዳም…” የሚያሰኘው!)
“ሦስት ሺህ ብር ገንዘብ ሆና ስትከነክንህ ኖራለቻ! የሰው ባል መኪና ይገዛል…” ትላለች። (እኔ የምለው…የሰውን ባል ማጣቃሻ የሚያደርጉ ሚስቶች…የሚያወሩት ‘መላ ምት’ ነው ወይስ የ‘ተግባር’ ተሞክሮ! ቂ…ቂ…ቂ… መታወቅ አለበታ!)
እናላችሁ…‘ክላይማክሱ’ ላይ ምን ትላለች መሰላችሁ…“ድሮም ስንጋባ እማዬ ‘ይሄ ሰውዬ ቀፎኛል’ ስትል የነበረው ለካስ እውነቷን ነው…”
እናላችሁ……ወንድ አሥር ሴት ዘጠና የሆኑበት ግንኙነትም ስንትና ስንት ተከታታይ የሬድዮ ድራማ ይወጣው ነበር!
እኔ የምለው በቃ የሰው እንትናዬና የሰው እንትና ‘እነሆ በረከት’ መባባል.. አለ አይደል… “እና ምን ይጠበስ!” የሚያስብል ሆነና አረፈው! ነው ወይስ ነገሩ ሀያ/ሰማንያ ለሆነ ትዳር በወር ይሄን ያህል ጊዜ የራስ ካልሆነ ሰው ጋር ‘እነሆ በረከት’ ምናምን የሚፈቅድ ያልተጻፈ ህግ አለ!
እናማ ዘንድሮ… ስኳርም ሆነ ጨው የሆነ ነገር ሲመዘን እንኳን አንድ ኪሎ ግራም ማለት ዘጠና ግራም ሊሆን ይችላል፡፡ ዕድለኛ ከሆናችሁ ዘጠና አምስት ግራም፡፡
ስሙኝማ… ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…የዘንድሮ የጓደኝነት ግንኙነት በአብዛኛው ሀያ ሰማንያና አሥር ዘጠና ነው፡፡ ምንም አይነት ከልብ የሆነ መተሳሰብ የሌለበት አንዱ በአንደኛው ተጠቃሚ የሚሆንበት፡፡ ልክ ያ ‘ተጠቃሚነት’ ሲያበቃ ‘ጓደኝነቱም’ ያልቅለታል፡፡
እናማ…የእውነት ካወራን አይቀር… ምን አርባ/ስድሳ ያልሆነ ነገር አለ! የት ቦታ ነው ልባችሁን የሚሞላ ‘መቶ በመቶ’ አገልግሎት የምታገኙት!  ስንት ቦታ ነው ጥራቱ የተሟላ መቶ በመቶ’ ምርት የምታገኙት!  የት ቦታ ነው “እንከን የማይወጣለት ግሩም ባህሪይ ያለው…” የሚባል ‘መቶ በመቶ የሆነ ሰው የምታገኙት!  
ሁሉም ነገር በ‘ኮንዶሚኒየም ተሞክሮ’ እየተመራ ይመስላል፡፡
ለነገሩ በደረጃው ያሉ የቦሶቻችን ነገር አይታችሁ እንደሆነ ምናልባት አርባ/ስድሳ የተቀራረበበት ጊዜ ከነበረ እንጃ…ግን ወደ ዘንድሮ ሁሉም ነገር ወደ አሥር ዘጠና እየተጠጋ ይመስላል፡፡ የሚሰማን ጠፋሳ! እናማ… ምን መሰላችሁ በርካታ ቦታዎች ላይ ጥራት ያለው አገልግሎት የማግኘታችን ዕድል ከአሥር/ዘጠናም እያነሰ ነው፡፡
እናላችሁ… መቶ በመቶ የሚባል ነገር ቀርቷል፡፡
ስሙኝማ… እንግዲህ ጨዋታም አይደል…”የስ ሜን” (“yes men”) አልበዙባችሁም! አለ አይደል… የራሳችንን አእምሮ ሳናሠራ ሌላው የተናገረውን የምናስተጋባ፣ ያደረገውን “ይበል፣ ይበል” የምንል ማለት ነው፡፡
እናላችሁ…ዓላማ አለን ከሚሉን በላይ ሰውና አገርን መቀመቅ የሚከቱ ዓላማቸው ‘የሆድ ጉዳይ’ ብቻ የሆኑ… አለ አይደል… ‘ሀያ/ሰማንያ’፣ ‘አሥር/ዘጠና’ የሚል ሳይሆን በ‘ዜሮ/መቶ’ ራሳቸውን ተገዢ ያደረጉ “የስ ሜን” (yes men) ናቸው፡፡
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…በድሮ ጊዜ ቢሆን ንጉሦችና ነገሥታት ዙሪያቸውን በ”yes men” ይከበባሉ፡፡
እናላችሁ…“የስ ሜን” (yes men) የጌቶቻቸውን የሌላቸውን ገድል እየተረኩላቸው፣ ማን እንደሰጣቸው የማይታወቀውን ኒሻን እየደረደሩላቸው… ምን አለፋችሁ የመላዕክትን ክንፍ ሊቀጥሉላቸው ምንም አይቀራቸው፡፡ ዘንድሮም እንደነዚህ አይነት “የስ ሜን” (yes men) የሆንን እየበዛን ነው፡፡ ዜሮ/መቶ በሆነ ግንኙነት የሚሉንን ለመሸከም፣ የሚነግሩንን “እሰይ፣ እሰይ…” ብለን አጨብጭበን ለመቀበል፣ “ዝለል!” ሲሉን “ስንት ሜትር?” የምንል…የዜሮ/መቶ ሰዎች በዝተናል፡፡    
እኔ የምለው… እግረ መንገዴን የሆነ ነገር ትዝ አለኝማ… ስድብ እዚህም ደረጃ ደረሰና አረፈው! የምር…አይ የ‘ጦቢያ’ ነገር የሚያሰኝ ነው፡፡ የድሮዎቹ የኢትዮጵያን ህዝብ ቁጥር ሲጠየቁ “አምስት መቶ አንሞላም…” ምናምን አሉ የተባሉት እንኳን የሆነ መስመር ላይ ቆመዋል፡፡ ጥያቄ አለን…በአእምሮ ‘ብስለት’ና በምላስ ‘ስለት’ መካከል ያለው ልዩነትና አንድነት ይጠናልንማ! ታዲያ ልክ ልካችንን ሲነግሩን እንደ ደነዘዝን የ‘ሜሊኒየሙ የልማት ግብ’ ምናምን የሚሉት ጊዜ ሊደርስ አይደል! እኔ የምለው…ብዙዎቻችን ነቅተንም እንቅልፍ ላይ የሆንን አይመስላችሁም፡፡
የምር… ብዙ ነገራችን ላይ የሆነ ድንዛዜ አይታያችሁም! ነገርየው’ኮ “አልበዛም ወይ ድንዛዜ…” አይነት ነገር እየሆነ ነው፡፡
(ጥቆማ አለን… “ጊዜ ሲከዳ መሬቱ ያድጣል” የሚሏትን አለማወቅ ስንቱን አንስቶ ዘጭ እያደረገው ነው! “ጊዜ ይከዳል…” አራት ነጥብ፡፡)
የምር ግን አንዳንዴ “ምንድነው እንዲህ መላ ያሳጣን?” ትላላችሁ፡፡ ለምንድነው ‘ዕብድ’ የሚያክል ጉርሻ በሁለት ጉንጮቹ የሚያላምጠው ሰው፣ በሌላኛው ሰው ግማሽ ጉንጭ እንኳን የማትሞላ ቅምሻ የሚናደደው? እናማ…የአሥር/ዘጠና አስተሳሰብ ‘ሁሉን’ ነገር ለእኛ፣ ‘ትንሽ’ ወይም ‘ምንም’ ነገር ለሌላኛው ሰው አይነት ህይወት ውስጥ ከቶናል፡፡
የምር እኮ…የምንጨነቀው ጎተራችንን ስለሞላው የራሳችን እህል ሳይሆን በአንዲት አቁማዳ ስለተሸከፈችው የሌላኛው ሰው ሹሮ እህል ነው። አሁን አንድ አቁማዳ ሹሮ የትኛውን ረብጣ ብር ታመጣና ነው!
እና የ‘አርባ/ስድሳ’፣ የ‘አሥር/ዘጠና’ አስተሳሰብ እያራራቀን ነው፡፡
ደህና ሰንብቱልኝማ!

Published in ባህል
Page 2 of 13