የጉራጊኛ ዘፋኙ ፍታ ወልዴ በንግድ ሱቅ ምክንያት በተፈጠረ አለመግባባት የእናቱ ወንድም በሆነው አጎቱ ባለፈው ሰኞ በጥይት ተደብድቦ ተገደለ፡፡ ተጠርጣሪው በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውሎ ምርመራ እየተደረገበት ሲሆን የሟች አስከሬን ወደ ትውልድ ሃገሩ ተወስዶ የቀብር ስነ ስርአቱ ተፈፅሟል፡፡
ሟች እና ገዳይ ከስጋ ዝምድናቸው ባሻገር ከአመታት በፊት በፈጠሩት የልብ ወዳጅነት ነበር መርካቶ በሚገኘው አትክልት ተራ አካባቢ የንግድ ሱቅ የተከራዩት፡፡ ገዳይ የቤቱን ግማሽ አከራይቶ የተቀረውን የአሣ ንግድ ሲያካሂድበት፣ ሟች በበኩሉ ከሙዚቃ ስራው ጎን ለጎን የተለያዩ ተባራሪ ስራዎችን እየሰራ ኑሮውን ይገፋ እንደነበር ምንጮቻችን ይገልፃሉ፡፡
ከጊዜ በኋላ ነው ሟች የሱቁ ባለድርሻነት ጥያቄውን ያነሳው፡፡ ጉዳዩ እስከ ፍርድ ቤት ደርሶም የንግድ ቤቱን ሟች እንዲያስተዳድረው ወደሚል ውሳኔ ይቃረባል፡፡ ይሄኔ ገዳይ “ሁሉም ይቅርና በጋር እንስራ” የሚል ሃሳብ ማቅረቡን የሚናገሩት ምንጮች፤  ሟች ግን በዚህ አልተስማማም ይላሉ “እስከዛሬ በጋራ ፍቃድ እናውጣ ስልህ አሻፈረኝ ብለህ ለኔ ሊወሰን ሲል ነው እንዲህ የምትለው” በማለት ሃሳቡን ሳይቀበለው ቀረ፡፡ ሁለቱን ለማስማማት ጣልቃ የገቡ ሽማግሌዎችም የሱቁ ጉዳይ የመጨረሻ እልባት እስኪያገኝ ገዳይ በኢኮኖሚ እንዳይጎዳ ሟች በወር 4ሺህ ብር እንዲከፍለው አስማሟቸው ይላሉ - ምንጮች፡፡
ከስምምነቱ በኋላ ሟች እና ገዳይ ሰላማዊ ግንኙነት መቀጠላቸውን ያስታወሱት ምንጮች፤ በመሃል ገዳይ “4ሺህ ብሩ አይበቃኝም” የሚል ጥያቄ ማንሳቱን ይናገራሉ፡፡ ባለፈው ሰኞ ገዳይ ሟችን ልጋብዝህ በማለት መርካቶ ሰባተኛ አካባቢ በሚገኝ መጠጥ ቤት ውስጥ ከተገናኙ በኋላ በሽጉጥ ሶስት ጊዜ ተኩሶ እንደገደለው ምንጮቻችን ገልፀዋል፡፡ ነዋሪነቱ መርካቶ 7ኛ አካባቢ የነበረው ሟች፤ ባለትዳር እና የልጆች አባት ሲሆን አስከሬኑ ረቡዕ እለት ቤተሰቦቹ ወደሚገኙበት ሰባት ቤት ጉራጌ መሸኘቱንና የቀብር ስነ-ስርአቱም እዚያው መፈፀሙን ለማወቅ ተችሏል፡፡ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የወንጀል ምርመራ፤ ገዳይን በቁጥጥር ስር አውሎ ምርመራውን እያጣራ መሆኑን ለአዲስ አድማስ ገልጿል፡፡  
ሟች ፍታ ወልዴ ቀደም ሲል ከተለያዩ አርቲስቶች ጋር የጉራጊኛ ዘፈን አልበም ያወጣ ሲሆን በቅርቡም የራሱን አልበም እንዳወጣ ታውቋል፡፡

Published in ዜና

በዶክተር ብርሃኑ ደመላሽ የተፃፈውና በእውነተኛ ታሪክ ላይ የተመሰረተው የአባቴ ምክሮች ሀሳቦቼ መፅሀፍ ሰሞኑን ለንባብ በቅቷል።
95 ገፆች ያሉት መጽሐፍ፤ የደራሲው የመጀመሪያ ስራ ሲሆን በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ እንደሚያጠነጥንም ተገልጧል፡፡ መፅሐፉ መታሰቢያነቱ ለደራሲው ወላጅ አባት እና በፖለቲካ ምክንያት ለተሰዉ ዜጎች ሆኗል፡፡
መፅሐፉ በ30 ብር ለሽያጭ ቀርቧል፡፡

ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በአገራችን በተለያዩ ሆቴሎችና የመዝናኛ ስፍራዎች መከበር የጀመረው የፍቅረኛሞች ቀን (Valentine’s Day)፤ በዛሬው ዕለት በከተማዋ የተለያዩ ሥፍራዎች ይከበራል፡፡
በዓሉ ከሚከበርባቸው ሥፍራዎች መካከል ኢስተምቡል ሬስቶራንት፣ ዲ ኤች ገዳ ታወር፣ ሐርመኒ ሆቴልና ቬልቪው ሆቴሎች የሚገኙበት ሲሆን በዓሉ በአበባና የተለያዩ ስጦታዎች፣ በሙዚቃ ድግስ፣ በጣፋጭ ምግቦች ዝግጅትና በትዊስት እንደሚደምቅ አዘጋጆች አስታውቀዋል።
የኔታ ኢንተርቴይመንትና ዱም ሚዲያና ፕሮሞሽን በትብብር ባዘጋጁት “የፍቅረኛሞች ቀን” በተለያዩ የኪነጥበብ ዘርፎች የላቀ አስተዋጽዖ ያበረከቱ ባለሙያዎች እንደሚሸለሙ ታውቋል፡፡   

Monday, 17 February 2014 09:10

ስለት

…ሰናይት ይሏታል፡፡ እኔ ሰኒ እላታለሁ፡፡ ከተዋወቅን ያለፈው ሰኔ ሚካኤል 3ኛ አመታችንን ደፈንን፡፡ ዝም ብሎ መተዋወቅ እንዳይመስላችሁ፡፡ ከመላመዳችን የተነሳ ፊቷን አይቼ ምን እንደምታስብ መገመት ሳይሆን ማወቅ ጀምሬያለሁ፡፡
እወዳታለሁ፡፡
እሷም “እወድሃለሁ” ትለኛለች፡፡
3ኛ አመታችንን ባከበርን ማግስት እድል እጇን ዘረጋችላት፡፡ ስትዘረጋላት “ልጨብጣት ወይ?” ብላ አማከረችኝ፡፡ “ምን ይጠየቃል ጨብጫት እንጂ” አልኳት፡፡ “እንዴት እንዲህ ትለኛለህ? ያንተ እጅ እያለ ባትወደኝ ነው እንጂ…” ብላ አኮረፈችኝ፡፡
ቶሎ ታኮርፋለች፡፡ ጥቃቅን ነገሮች ሁሉ ያስኮርፏታል፡፡ ብስክስክ ናት፡፡ እኔም አመሏን ለምጀዋለሁ፡፡ እሷም አልፎ አልፎ ቱግ የምለውን ነገር ታውቅልኛለች፡፡ መቻቻል ማለት ይሄ አይደል…ቢሆንም ይሄ አመሏ አንዳንዴ ትዕግስቴን ይፈታተነኛል፡፡
ከሰኒ ጋር የት ተገናኘን?
ቡና ቤት! (ለማንም ግን አይነገርም፤ ምስጢር ነው፤ በተለይ በተለይ ቤተሰብ እንዳይሰማ!)
ስንላመድ ከቡና ቤት አውጥቼ መጀመሪያ ወደ ልቧ፣ ኋላም ወደ ቤቴ አስገባኋት፡፡ ስትረጋጋ ቤተሰቤን ልጠይቅ አለችኝ ፈቀድኩላት፡፡ ያኔ እግረ መንገዷን ከእድል ጋር ተገናኘች፡፡
ታድያስ የእድሏ በር የተከፈተው በኔ ምክንያት አይደለምን? በሩን ባልከፍተው ቁልፉን ያቀበልሁ እኔ አይደለሁምን?
ውጭ ሀገር መሰደድ እንደ ሎተሪ በሚታይባት ሀገር ውስጥ ከዚህ የበለጠ ምን ጥሩ እድል አለ ጃል? አለ እንዴ? የለም እኮ!!
መሄድ የለብሽም ብላት በጄ እንደማትል ልቦናዬ እያወቀው፣ አፌን ለምን አበላሻለሁ ብዬ “ይቅናሽ” ብላት በአትወደኝም ተተረጐመብኝና በለመድኩት ኩርፊያ ገረፈችኝ፡፡
ውጭ ሀገር ለመሄድ 1…2 …ማለት ተጀመረ፡፡ ግን “ፕሮሰሱ” እንደታሰበው እንደጥንቸል ሊሮጥ አልቻለም፡፡
አንድ ቀን ይሄን “ውጭ” የሚለውን ልቧን ወደ ውስጥ ለመሳብ በማሰብ፣ ሻይ ቡና ልበልሽ ብዬ አንድ እኔ ነኝ ያለ ካፍቴሪያ ውስጥ ቋጠርኳት፡፡ አንድ ሁለት እያልን ጨዋታችንን አደራነው፡፡ ልክ እንደጥንቱ…ከወትሮው ልማዳችን በሹካ መጐራረሱን ብቻ ትተን…ልክ እንደ ጥንቱ በደንብ አወጋን፡፡  
ምንጭ፡- (ባለ “ሚኒስከርቷ” የሥነግጥምና የአጫጭር ታሪኮች ስብስብ)

Published in ማራኪ አንቀፅ

ሚሉቲን ሴርዶጄቪች (ከኡጋንዳ፤ ካምፓላ)
ከሩብ ምዕተ ዓመት ውድቀት በኋላ የኢትዮጵያ እግር ኳስ፣ ባለፉት ጥቂት አመታት ማንሰራራቱና በአፍሪካ የእግር ኳስ መድረክ ላይ ቤተኛ እየሆነ መምጣቱ አንድ እርምጃ ነው፡፡ ለዚህ አስተዋጽኦ ያደረጉ ተጫዋቾች፣ አሰልጣኞች፣ ክለቦች፣ ስፖንሰሮች፣ ደጋፊዎች እና የፌዴሬሽን አመራሮች እንደየድርሻቸው ምስጋና ይገባቸዋል፡፡ ነገር ግን በዚሁ አህጉራዊ መድረክ ጠንካራ ተፎካካሪ የመሆን ምኞታችን ገና አልተሳካም፡፡ ፈተናውም ከእስካሁኖቹ ሁሉ የከበደ ነው፡፡ ለዚህም ነው የብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ ምርጫ፤ የብዙዎች መነጋገሪያ መሆኑ የማይገርመው፡፡
ለዚህ ትልቅ ሃላፊነት የሚመጥንና የሚስማማ አሰልጣኝ ለመምረጥ በተጀመረው እንቅስቃሴ፤ የአገር ውስጥ እና የውጭ ባለሙያዎች በእጩነት ስማቸው እየተጠቀሰ ውይይት መሟሟቁም ተገቢ ነው፡፡ የተጀመረው ውይይትም፤ በቅንነት፣ በብስለት እና በእውቀት እየዳበረ መሄድ አለበት፡፡ ለዚህም ይረዳ ዘንድ ቀደም ሲል በኢትዮጵያና በሌሎች የምስራቅ አፍሪካ አገራትና በደቡብ አፍሪካ የታወቁ ክለቦችን ያሰለጠኑ፤ እንዲሁም አስቀድሞ የሩዋንዳ አሁን ደግሞ የዩጋንዳ ብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ የሆኑትን የ44 ዓመቱ ሰርቢያዊ ሚሉቲን “ሚቾ” ሴርዶጄቪች በአሰልጣኞች ምርጫ ዙሪያ አወያይተናቸዋል፡፡

እንደምታውቀው እኔ ፕሮፌሽናል አሰልጣኝ ነኝ። የትኛውም ፕሮፌሽናል አሰልጣኝ ደግሞ ስለደሞዙ በይፋ ለመናገር ፈቃደኛ አይሆንም፡፡ ስለዚህም ከመናገር እቆጠባለሁ፡፡ ምክንያቱም መቼም ቢሆን የኔ ሩጫ ገንዘብ ለማግኘት አይደለም፡፡ ይልቁንም የሁልጊዜ ፍላጎቴ፣ ራዕይ  ላለው ፕሮጀክት መስራት ነው፡፡ እውነት ለመናገር፤ በአሰልጣኝነት በሰራሁባቸው አገራት ሁሉ ከማገኘው ንዋይ ይልቅ የምሰጠው አገልግሎት እና በትጋት ሰርቼ የማልፈው ይበልጣል፡፡ ለዚህም ይመስለኛል፤ በአሁኑ ጊዜ ከውጭ አሰልጣኞች መካከል በምስራቅ አፍሪካ የእግር ኳስ መድረክ ለረጅም ጊዜ በመቆየት ቀዳሚውን ስፍራ ለመያዝ የበቃሁት፡፡ በምስራቅ አፍሪካ አገራት በ14 ዓመታት የስራ ጊዜ ከፍተኛ ልምድ አካብቻለሁ፡፡ ሁሉም የሚያውቀው ደግሞ ለ5 ዓመታት በኢትዮጵያ እግር ኳስ እንደታማኝ ወታደር አገልግያለሁ፡፡ እናም በአሰልጣኝነቴ ከገንዘብ ይልቅ በስራዬ ከፍ ያለ ስኬት እና የማይረሳ ታሪክ ትቼ ማለፉን በይበልጥ እፈልገዋለሁ፡፡
አሁን በስራ ላይ ለሚገኘው የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ታላቅ አክብሮት አለኝ፡፡ በኢትዮጵያ ብቻ አይደለም፤ በስራዬ በኖርኩባቸው አገራት ውስጥ ከፌዴሬሽኖች እና ከእግር ኳስ ተቋማት ጋር ያለኝ ግንኙነት በመከባበር ላይ የተመሰረተ ነው፡፡ ስለዚህም በፌደሬሽን ስራዎች ላይ ጣልቃ ገብቼ ይህን አሰልጣኝ በዚህ ምክንያት ቅጠሩ በማለት ምክር በመስጠት ክብር ለመጋፋት አልፈልግም፡፡ ዋናው ነገር ኢትዮጵያ በአስደናቂ የባህል ትውፊቶቿ፤ ታሪኳ እና የአኗኗር ዘይቤ ልዩ አገር ናት፡፡ ይህን ክብር በመጠበቅ እና በማክበር፤ ከአገሬውና ከህዝቡ ጋር ተዋህዶ ሊሰራ የሚችል ሰው ያስፈልጋታል። ብሄራዊ ቡድኑ ከፊታችን ለሚጠብቁት ውድድሮች ረዥም የዝግጅት ጊዜ የለውም፡፡ ለ2015 የአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ ውድድር የሚደረገው  ከ8 ወራት በኋላ ነው፡፡ ይህ የማጣርያ ውድድር በመስከረም አካባቢ ተጀምሮ በ3 ወራት ውስጥ 6 ጨዋታዎች የሚደረጉበት ነው፡፡ ብሄራዊ ቡድኑ ይህን ከባድ ማጣርያ በከፍተኛ ዝግጅት በብቃት መወጣት እንዲችል በፍጥነት ውጤታማ አሰልጣኝ ያስፈልገዋል፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ ከሚሰሩ የእግር ኳስ አሰልጣኞች ጋር በታላቅ የስራ ፍቅር ተከባብሮ እና በጓደኝነት ተቀራርቦ የመስራት ልምድ አለኝ፡፡ ይህ ደግሞ አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻውንም ይጨምራል፡፡ የብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ ሆነው ለፈፀሟቸው ስኬታማ ተግባራት አድናቆት አለኝ፡፡ ሌሎችንም አደንቃለሁ ለጊዜው ግን፣ የአሰልጣኝ ምርጫ በሚካሄድበት ወቅት ከኢትዮጵያዊ አሰልጣኞች እገሌን ብዬ አድናቆቴን ብገልጽ ተገቢ አይሆንም፡፡ ግን እርግጠኛ ነኝ፤ በሙያችን የተዋወቅን አሰልጣኞች ሁሉ፤ ያለኝን ከበሬታ እና አድናቆት ያውቃሉ፡፡ የኢትዮጵያ እግር ኳስ አሰልጣኞች በአስቸጋሪ ሁኔታዎች ውስጥ በከፍተኛ ትጋት የሚሰሩ እና የሚያገለግሉ ናቸው፡፡ የኢትዮጵያ እግር ኳስ እንዲያንሰራራ ሁሉም በላቀ ደረጃ አስተዋፅኦ እንደነበራቸው አስባለሁ፡፡ በአሰልጣኝነት ሙያዬ ከኢትዮጵያውያን ጋር በመስራቴ ብዙ ትምህርት እና ልምድ ተጋርቻለሁ፤ አጋርቻለሁ፡፡ ለዚህ ደግሞ ለሁሉም ያለኝን የከበረ ምስጋና እገልፃለሁ፡፡ ባለሙያዎችን በስም እየጠራሁ ያልዘረዘርኩት አሁን ጊዜው ስላልሆነ ነው፡፡   በቴክኒክ ጉዳዮች ላይ ግን የማስበውን ነገር ሁሉ በዝርዝር ለመናገር ወደኋላ አልልም፡፡
የውጭ አገር  አሰልጣኞችን በተመለከተ አሁን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ላለበት አጣዳፊ ሁኔታ የሚሆን ባለሙያ በተፈለገው መስፈርት እና ብቃት በቀላሉ ማግኘት የሚከብድ ይመስለኛል፡፡ እኔም ለዚህ ሃላፊነት የሚመጥንና የሚስማማ የውጭ አሰልጣኝ ማን ነው ብባል፤ አንድም ሰው በአዕምሮዬ ሊመጣ አይችልም። ጥሩ አሰልጣኝ ለማግኘት በቂ ጊዜ ወስዶ መስራት ያስፈልጋል። ለአዲሱ አሰልጣኝ ቅጥር የሚሰሩትን ሁሉ በስራቸው እግዚአብሔር ይርዳቸው ነው የምለው። አሰልጣኝ ምርጫ ቀላል ነገር አይደለም፡፡ አሁን እግር ኳሱ ባለበት የተነቃቃ መንፈስ ለተሻለ ለውጥና ለላቀ እድገት በብቃት ተስማምቶ የሚያገለግል ባለሙያ ያስፈልጋል፡፡ ኢትዮጵያውያን እግር ኳስ አፍቃሪዎች ካላቸው ትልቅ ስሜት ጋር የሚስተካከል ትልቅ ስኬት ለማስመዝገብ የሚሰራ አሰልጣኝ እንጂ የሚያጎድል ሰው መመረጥ የለበትም፡፡ ማንም ሰው ደጋፊዎችን የማስከፋት እና ተስፋ የማስቆረጥ መብት የለውም፡፡ ከዚህ ጥቅል አስተያየት ባሻገር፣ የአሰልጣኝ ምርጫን በተመለከተ ከላይ በጠቀስኳቸው ምክንያቶች የተነሳ ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን እገሌ  ብዬ ለመጠቆም አሁን አልችልም፡፡
ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝንት ከሚፈለጉ እጩዎች አንዱ ሆኜ ስሜ በመነሳቱ ብቻ ለእኔ ትልቅ ክብር ነው፡፡ ለአሰልጣኝነቴ ዋጋ የሰጠ እውቅና በመሆኑ ከልብ ያስደስተኛል፡፡ አንድ ባለሙያ፣ ከምንም ነገር በላይ ለሙያው እውቅና ሲሰጠው ነው እርካታ የሚሰማው፡፡ ቢሳካ፤ ህልሜ እውን እንደሆነ እቆጥረዋለሁ፡፡ ምክንያቱም ሁሉም  አሰልጣኞች ትልልቅ ብሄራዊ ቡድኖችን በሃላፊነት ለመምራት ይፈልጋሉ፡፡ ሃቁን ልንገርህ፡፡ ኢትዮጵያዊያን ለእግር ኳስ ያላቸውን ፍቅር እና ስሜት እንዲሁም ልዩ ብሄራዊ ክብራቸውን ለሚያውቅ ሰው፤ ይህን ትልቅ ሃላፊነት ሲያገኝ፣ የዘወትር  ህልሙ እውን ሆነ ማለት ነው፡፡ የእግር ኳስ አሰልጣኞች ትልቁ ሃይል፤ በሃላፊነታቸው ለህዝብ ደስታን መፍጠር ነው፡፡ ለ90 ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን  ደስታ መፍጠር የሚቻልበት ሃላፊነትን ማግኘት እጅግ ያጓጓል፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝነት ታላቅ ክብር  ነው፡፡
የኢትዮጵያ እግር ኳስ፣ አሁን መስቀለኛ መንገድ ላይ ያለ ይመስለኛል፡፡ ምክንያቱም ባለፉት ጥቂት ዓመታት የተፈጠሩ መነቃቃቶች እና ውጤቶች ወደኋላ እንዲያፈገፍጉ ማንም አይፈልግም፡፡ ለዚህም ነው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የአጭር እና የረጅም ጊዜ ውጤታማ እቅዶችን የያዘ ብቁ አሰልጣኝ የሚያስፈልገው። የአጭርጊዜ እቅዱ በ2015 በሞሮኮ የሚስተናገደው 30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ነው፡፡ የረጅም ጊዜ እቅዱ ደግሞ በ2018 ራሽያ የምታስተናግደው 21ኛው የዓለም ዋንጫ ነው፡፡ አዲሱ የብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ እነዚህን አቅዶች ማሳካት የሚችል ፤ የተነቃቃውን ለውጥ በማስቀጠል ለላቀ እድገት የሚተጋ ሊሆን ይገባል፡፡ በምንኖርባት ፕላኔት ውስጥ፤ ለዚህ ሃላፊነት የሚስማማ፤ ይህን ከባድ ሃላፊነት በብቃት መወጣት እና መስራት የሚችል አንድ ባለሙያ አውቃለሁ፡፡ ግን እገሌ ብዬ ስሙንና ማንነቱን ለመንገር መብት የለኝም፡፡ ምክንያቱም ይህ ሰው፤ በሌላ አገር የኮንትራት ስራ ላይ ስለሚገኝ ነው፡፡
እንደሁልጊዜው ልባዊ መልካም ምኞቴን መግለጽ እፈልጋለሁ፡፡ ለአንተም ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብም፡፡ በርቱ፤ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ትክክለኛ ቦታው ከምርጦች ተርታ ነው፡፡ እዚያ ቦታ እንዲደርስ ሁላችሁም በህብረትና በትጋት ስሩ፡፡ ከስምንት አመት በፊት ከጋዜጣችሁ ባደረግነው ቃለምልልስ፣ የብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ ብትሆን በማለት መልካም ምኞትህን ገለጽህልኝ እንደነበር አስታውሳለሁ፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ የመሆን ልባዊ ምኞት እንዳለ ሆኖ፤ እኔ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ ሆንኩ አልሆንኩ  ምንግዜም የዋልያዎቹ ቁርጠኛ ደጋፊ ሆኜ እቀጥላለሁ፡፡


በ2014 የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ እና ኮንፌደሬሽን ካፕ  ደደቢት እና  መከላከያ በቅድመ ማጣርያ  የመልስ ጨዋታዎቻቸው የምስራቅ አፍሪካ ክለቦችን ጥሎ ለማለፍ ትንቅንቅ ያደርጋሉ፡፡ ከሳምንት በፊት ደደቢት በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ የዛንዚባሩን ኬኤምኬኤም በሜዳው 3ለ0 ሲያሸንፍ ጎሎቹን ዳዊት ፍቃዱ፤ ሺመክት ታደሰ እና ማይክል ጆርጅ ከመረብ አሳርፈዋል፡፡ በአፍሪካ ኮንፌደሬሽን ካፕ  መከላከያ ከሊዮፓርድስ ከሜዳ ውጭ በተገናኘበት ጨዋታ 2ለ0 ተሸንፏል፡፡
በኬንያው ብሄራዊ ስታድዬም ናያዮ በተደረገው የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ ለሊዮፓርድስ ሁለቱን ጎሎች ያስቆጠሩት አምበሉ ማርቲን ኢምባላምቦሊ እና ጃኮብ ኬሊ ናቸው፡፡ ደደቢት ከኬኤምኬኤም ጋር ከሜዳው ውጭ በሚያደርገው የመልስ ጨዋታ ከ2ለ0 በታች መሸነፍ፤ አቻ መውጣትና በማናቸውም ውጤት ማሸነፍ ጥሎ ለማለፍ ይበቃዋል፡፡
መከላከያ ደግሞ የኬንያውን ኤኤፍሲ ሊዮፓርድስ በሜዳው አስተናግዶ 3ለ0 ከዚያም በላይ በማሸንፍ የማለፍ  እድሉን ይወስናል፡፡  በቅድመ ማጣርያው ከኢትዮጵያው ደደቢት እና ከዛንዚባሩ ኬኤምኬኤም ጥሎ ማለፍ የሚችለው ክለብ በአንደኛ ዙር የማጣርያ ምእራፍ የሚገናኘው ከቱኒዚያው ክለብ ሲኤስ ኤስፋክሲዬን ጋር ነው፡፡
በሌላ በኩል ከኢትዮጵያው መከላከያ እና ከኬንያው ኤኤፍሲ ሊዮፓርድስ ጥሎ የሚያልፈው በአንደኛ ዙር የማጣርያ ምእራፍ የሚገናኘው  ከደቡብ አፍሪካው ሱፕር ስፖርት ዩናይትድ ወይም ከቦትስዋናው ጋብሮኒ ዩናይትስድ አሸናፊ ጋር ይሆናል፡፡ ሱፕር ስፖርት ዩናይትድ በቅድመ ማጣርያው የመጀመርያ ጨዋታ ጋብሮኒ ዩናይትድስን 2ለ0 አሸንፎታል፡፡

ዛሬ በእንግሊዝ በርሚንግሃም በሚካሄደው የ2 ማይል የቤት ውስጥ ውድድር የ23 ዓመቷ አትሌት ገንዘቤ ዲባባ የውድድር ዘመኑን ሶስተኛ የዓለም ሪከርዷን ልታስመዘግብ እንደምትችል ግምት አገኘች፡፡ ገንዘቤ ባለፈው ሁለት ሳምንት በ3ሺ ሜትር እና በ1500 ሜትር የቤት ውስጥ ውድድሮች ሁለት አስደናቂ የዓለም ሪከርዶችን አስመዝግባለች ዛሬ በበርሚንግሃም “ሳልስበሪ ኢንዶር ግራንድፕሪ” የ2 ማይል ሩጫ  ከ5 ዓመት በፊት በመሰረት ደፋር የተመዘገበውን ክብረወሰን ገንዘቤ ዲባባ ለመስበር እንደምትችል ተዘግቧል፡፡ ከተሳካላት በውድድር ዘመኑ 3 የዓለም ሪከርዶችን ያስመዘገበች ምርጥ አትሌት እንደምትሆን መረጃዎች አውስተዋል፡፡ ገንዘቤ በ2014 የውድድር ዘመን ከገባ ወዲህ በማሳየት ላይ የምትገኘው አስደናቂ ብቃት ከወር በኋላ በፖላንዷ ከተማ ስፖት በሚደረገው የዓለም አትሌቲክስ የቤት ውስጥ ሻምፒዮና ላይ በ3ሺ እና በ1500 ለድርብ የወርቅ ሜዳልያ ድሎች ግንባር ቀደም እጩም አድርጓታል፡፡
ገንዘቤ ከሳምንት በፊት በስዊድን ስቶክሆልም በ3ሺ ሜትር የቤት ውስጥ ሩጫ  ያሸነፈችው ርቀቱን በ8 ደቂቃ ከ16.60 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ በማጠናቀቅ አዲስ የዓለም ክብረወሰን አስመዝግባ ነበር፡፡ ይህ ሪከርድ አስቀድሞ በመሰረት ደፋር ተመዝግቦ የነበረውን የሰዓት ክብረወሰን በ7 ሰኮንዶች ያሻሻለ ሲሆን ከ1993 እኤአ ወዲህ በ3ሺ ሜትር የቤት ውስጥ ሩጫ ሊመዘገብ ፈጣን ሰዓት ተብሎ ከፍተኛ አድናቆት አግኝቷል፡፡ አትሌት ገንዘቤ ዲባባ ከዚሁ የ3ሺ ማይል አዲስ የዓለም ክብረወሰኗ 5 ቀናት በፊት ደግሞ በጀርመን ካርሉስርህ በተደረገ የ1500ሜትር የቤት ውስጥ ሩጫ በሪከርድ ሰዓት አሸንፋ ነበር፡፡ በ1500 ሜትር የቤት ውስጥ ሩጫው አትሌት ገንዘቤ ያሸነፈችው ርቀቱን በ3 ደቂቃ ከ55፡17 ሰኮንዶች በማገባደድ ሲሆን አስቀድሞ በሩሲያዊ አትሌት ተይዞ የነበረውን ክብረወሰን በ3 ሰኮንዶች አሻሽላዋለች፡፡

የማህጸን በር ካንሰር፣
በማህጸን አካባቢ የሚፈጠር የቅማል ዘር በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት ከሚተላለፉ  መካከል ናቸው፡፡
ዶ/ር ሰሎሞን ኩምቢ (ተባባሪ ፕሮፌሰር) በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የጽንስና ማህጸን ሕክምና ትምህርት አስተማሪ እና እስፔሻሊስት ናቸው፡፡ ዶ/ር ሶሎሞን በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት የሚተላለፉ በሽታዎችን ምንነት እና መፍትሔያቸውን ለዚህ እትም ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡
ጥ/    የግብረስጋ ግንኙነት ሲባል ምን ማለት ነው?
መ/    የግብረስጋ ግንኙነት ማለት በተለምዶ የወንድ ብልት በሴቷ ብልት ውስጥ ሲገባ ማለት ነው፡፡ ነገር ግን እንደሰዎቹ ስምምነት የሚፈጸሙ ሌሎችም የግብረስጋ ግንኙነቶች አሉ?
ጥ/    በሰዎች ስምምነት የሚፈጸሙ ሲባል ምን አይነቶች ናቸው?
መ/    የግብረስጋ ግንኙነት እንደ ሰዎቹ ስምምነት ይፈጸማል ሲባል በእንግሊዝኛው (Oral & Anal) ማለትም አንዳንድ ጊዜ በአፍ እና በፊንጢጣም በኩል ይፈጸማል፡፡
ጥ/    በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት የሚተላለፉ በሽታዎች ሲባል ምን አይነት ናቸው?
መ/    የሚከሰቱትን ችግሮች በግብረስጋ ምክንያት የሚከሰቱ አካላዊ ጠንቆች ቢባሉ የሚሻል ይመስለኛል፡፡ ችግሮቹ የተለያዩ ሲሆኑ በብዛት የሚታወቁት ግን የአባላዘር በሽታዎች ተብለው የሚጠቀሱት ናቸው፡፡ ከዚህ በተለየ ግን ለምሳሌ...
የማህጸን በር ካንሰር፣
የማህጸን በር ካንሰርን የሚያመጡት ቫይረሶች በመሆናቸው ከወንድ ወደሴት በሚተላለፉበት ወቅት ለበሽታው መከሰት እንደ አንድ ምክንያት ይቆጠራል፡፡ አንዲት ሴት የማህጸን በር ካንሰር እንዳይከሰትባት ለመከላከል ሲባል የሚሰጠው ክትባት የግብረስጋ ግንኙነት መፈጸም ከመጀመሩዋ በፊት ቢሆን የሚመረጥ መሆኑን የህክምናው ዘርፍ ባለሙያዎች ያስረዳለሉ፡፡  
በአስገድዶ መደፈር ወይንም በሰምምነት በሚደረግ ግንኙነት ምክንያት የሴቷ ብልት የውስጥ ክፍል መቀደድ፣
በማስገደድም ይሁን በስምምነት በሚፈጸም ግንኙነት ሳቢያ የሚከሰት የሽንት መቋጠር ችግር፣
በግብረስጋ ግንኙነት ጊዜ ከሚፈጠር አግባብ ያልሆነ የኃይል መጠቀም ወይንም የሰውነት አለመመጣጠን ሳቢያ የሚፈጸም ከሆነ በሴቷ ብልት አካባቢ የሚገኙትን አካላት ጭምር የሚያጠቃ ይሆናል፡፡
ማህጸን አካባቢ የሚፈጠር የቅማል ዘር፡-
በማህጸን አካባቢ የሚፈጠር የቅማል አይነት ከወንድ ወደ ሴት ወይንም ከሴት ወደ ወንድ ሲተላለፍ በሚፈጠረው የመራባት ሁኔታ ቅጫም ሊኖረው ሲችል ከዚያም ወደብብት እና ወደ አይን ፀጉር ጭምር ሊተላለፍ ይችላል፡፡ ስሜቱም በብልት ወይንም በብልት ጸጉር ላይ የማሳከክእና የማቃጠል ሊሆን ስለሚችል ሴትየዋ ወይንም ሰውየው እንደዚህ ያሉ ስሜቶች ከታዩባቸው ቶሎ መፍትሔ መውሰድ ይጠበቅባቸዋል፡፡   
የተለያዩ የቆዳ በሽታዎች በግብረ ስጋ ግንኙነት ምክንያት ሊተላለፉ ይችላሉ፡፡
ጥ/    ሁሉንም በሽታዎች በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት የሚተላለፉ ማለት ይቻላል?
መ/    የሚተላለፉት …Sexually transmissible infectious… ተብለው የሚለዩት ናቸው፡፡ እነርሱም በአማርኛው ጨብጥ፣ ቂጥኝ፣ ውርዴ፣ አባኮዳ፣ ባምቡሌ፣ የሴቶችን ፈሳሽ የሚያመጣ ፕሮቶዝዋ፣ ካንዲዳ የሚባል የፈንገስ አይነት እና ሌሎችም በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት የሚተላለፉ ተብለው የሚፈረጁ ሕመሞች አሉ፡፡ ነገር ግን በብዛት በማህጸን አካባቢ የማህጸኑ፣ የቱቦው እና የእጢው መቆሸሽ (Pelvic inflammatory disease) በሚባል የሚጠራውን ሕመም የሚያመጡት ጎኖሪያ (ጨብጥ)፣ ክላይሚድያ፣ ማይኮ ፕላዝማ እና ዩሪያፕላዝማ የሚባሉ የህዋስ አይነቶች ናቸው፡፡ ስለዚህ ከግብረስጋ ግንኙት ጋር የሚያያዝ ችግር ነው ብሎ መውሰድ ይቻላል፡፡
ጥ/    በተላላፊ በሽታዎቹ ምክንያት የሚከሰተው ሕመም ምን ይመስላል?
መ/    ከተላላፊ በሽታዎቹ ጋር ያሉት ጠንቆች ከማህጸን በላይ እርግዝና፣ ማህጸን ወይንም ብልት አካባቢ የሚኖር ሕመም፣ መካንነት ወይንም ልጅ አለመውለድ፣ በውስጥ አካል (ጉበት)፣ የሆድ እቃ አካባቢ መሰራጨት፣ የአእምሮ፣ የቆዳ፣ የልብ ኢንፌክሽን የማምጣት ...ወዘተ የመሳሰሉትን ሕመሞች ሊያስከትል ይችላል፡፡ ከተጠቀሱት ሕመሞች በተጨማሪም በአለም አቀፍ ደረጃ በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት በመተላለፍ በሽታ ከሚባሉት ውስጥ ኤችአይቪ ቫይረስም አንዱ ነው፡፡
ጥ/    ከግብረስጋ ግንኙነት ጋር ተያይዘው የሚመጡ የሰውነት ጠንቆች ሲባል ምን ማለት ነው?
መ/    ከግብረስጋ ግንኙነት ጋር ተያይዘው የሚመጡ የሰውነት ጠንቆች ሲባል ከላይ እንደገለጽኩት ግንኙነት የሚደረግበት የሴቷ ብልት መቀደድ፣ ፊስቱላ የመሳሰሉት ነገሮች ባህሪያቸው መተላለፍ ሳይሆን በግንኙነት ምክንያት የሚከሰቱ ጠንቆች ሊባሉ የሚችሉ ናቸው፡፡ የማህጸን በር ካሰርንም በቀጥታ ተላላፊ በሚል ከባድ ድምዳሜ መስጠት ባይቻልም ቀደም ሲል ካንሰሩ የነበረባት ሴትጋር በወሲብ የተገናኘ ሰው ወደሌላ ሴት ሲሄድ ቫይረሱን ሊያስተላልፍ ይችላል የሚሉ አስተያየቶች አሉ፡፡
ጥ/    ተላላፊ የተባሉት በሽታዎች በዚህ ዘመንም አሉ? ወይንስ?
መ/    በእርግጥ በግሌ በቅርብ ያጠናሁት ጥናት የለም፡፡ ነገር ግን የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት የሚተላለፉ በሽታዎችን ወይንም የአባላዘር በሽታዎችን በጤና ጣቢያ ደረጃ በቀላል እንዴት ማከም እንደሚቻል ለማሳየት መመሪያ ሲያወጣ የተሰራ ጥናት እንደሚያሳየው ጎኖሪያ፣ ክላሚድያ፣ ትሪኮሞኒያሲስ፣ ካንዲድያሲስ የተባሉት ሕመሞች አሁንም ያሉ ሲሆን እንዲያውም በመሪነት ደረጃ የሚጠቀሱ ናቸው፡፡  ባጠቃላይ ግን ሕመሞቹ በሙሉ አሁንም አሉ ማለት ይቻላል፡፡
ጥ/    በተላላፊ በሽታዎች ምክንያት የሚፈጠሩ የማሳከክ ስሜቶችን ጨው በመሳሰለው ነገር በመጠቀም መታጠብ ምን ይህል ይረዳል?
መ/    አንዳንድ ሴቶች ውሀ በማፍላት በጨው የመታጠብ ወይንም የመዘፍዘፍ እርምጃን ይወስዳሉ፡፡ ይህ በሰዎች ዘንድ ጥሩ ስሜትን ሊፈጥር ይችላል፡፡ ጨው ተፈጥሮአዊ ነገር ስለሆነ ምናልባት የማቃጠል ስሜት ይኖረው እንደሆነ እንጂ ጉዳቱ ብዙም አይታየኝም፡፡ ነገር ግን አንዳንድ ኬሚካሎችን እንደመታጠቢያ መውሰድ በቁስል ወይንም በተቆጣ ሰውነት ላይ ሌላ ችግር ሊያስከትል ስለሚችል አይመከርም፡፡ ጨው ግን ብዙም ጥቅሙ ባይታወቅም ጉዳት ግን የለውም፡፡
ጥ/    ሰዎች እንደመፍትሔ ሊወስዱት የሚገባ እርምጃ ምንድነው?
መ/    መፍትሔውን ስናስብ በቅድሚያ ትኩረት መደረግ ያለበት ጥንቃቄ የተሞላበት የግብረስጋ ግንኙነት ማድረግ ነው፡፡ ይህም ማለት መከላከል የሚቻልበትን ዘዴ መጠቀም ሲሆን ለዚህም አንዱ የሴቶችና የወንዶችን ኮንዶም መጠቀም ማለት ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በተለይም ወጣቶች ከትዳር በፊት የግብረስጋ ግንኙነት ማድረግ እንደማይገባቸው ይመከራል፡፡ ይህ ሀይማኖታዊ ብቻ ሳይሆን በሳይንሱም መንገድ የሚመከር ነው፡፡ ለወጣቶቹ እንደአማራጭ የሚመከረው ፍቅራቸውን በመላፋት ወይንም በመሳሳም ደረጃ ገድበው እንዲይዙት ነው፡፡ ከዚህ በተረፈ የሰውነትን እምቅ የሆነ ስሜት ለማውጣት Masturbation መጠቀም አንዱ ሳይንሳዊ ምክር ነው፡፡ ሁኔታዎች ከዚህ በላይ የሚገፉ ከሆነ ግን ሁለቱም ፍቅረኛሞች ምርመራ አድርገው የጤንነት ሁኔታቸውን በማረጋገጥ ግንኙነት ማድረግ ይችላሉ፡፡ ይህ ምክር የሚሰጠው ለኤችአይቪ ብቻ ሳይሆን ለአባላዘር በሽታዎችም ነጻ መሆን አለመሆን ማረጋገጫነት የሚመከሩ ናቸው፡፡ ከምር መራው በሁዋላም ከዚያ ከሚያውቁት ሰው ጋር ብቻ ግንኙነት ማድረግ ይገባቸዋል፡፡ የአባላዘር በሽታ በወንዶች ላይ ቶሎ ሲገለጽ በሴቶች ላይ ግን በተፈጥሮ ምክንያት ቶሎ ላይታወቅ ይችላል፡፡ ስለሆነም ሕመሙም በጊዜው ስለማይደረስበት በሴቶች ላይ ይበረታል፡፡ ነገር ግን የአባላዘር በሽታዎች ሊታከሙ ወይንም ሕመማቸውን ለመቀነስ የሚ ችሉ ናቸው፡፡ ስለዚህም ባጠቃላይ የሚሰጠው ምክር...
ችግሩ ከመከሰቱ በፊት አስፈላጊውን ጥንቃቄ ማድረግ
ችግሩ ከተከሰተ በግልጽ ከፍቅረኛ ወይንም ከትዳር ጉዋደኛ ጋር መመካከር
ችግሩ ከተከሰተ በአስቸኳይ ወደጤና ተቋም በመሄድ ማማከር ይገባል፡፡
    ሰዎች አስቀድመው አስፈላጊውን እርምጃ ከወሰዱ ቫይረሶቹ፣ ባክቴሪያዎቹ፣ ፈንገሶቹ እና የፕሮቶዞዋው እና ቅማሉን ጨምሮ የሚታከሙና ሊድኑ የሚችሉ ናቸው፡፡





Published in ላንተና ላንቺ
Saturday, 15 February 2014 13:27

ሳንሱረኞቹ

         ምስኪን ጁዋን! አንድ ቀን በራሱ ጠባቂ እግር ስር አንበረከኩት፡፡ እያጣደፈ ወደ ላይኛው እርካብ ያወጣው የዕድሉ መሰላል ቁልቁል ተሽቀንጥሮ የሚፈጠፈጥበት የውድቀት ዕጣ ፈንታው ወጥመድ እንደነበር ከቶም አልጠረጠረም፡፡ ይህን መሰሉ ውድቀት፤ ነገሮችን ችላ ባልንበት ቅፅበት የሚከሰት ነው፡፡ ችላ የማለት አመል በተጠናወተው ሰው ላይ ደግሞ ይብሳል፡፡ በተለይ፤ ያልተጠበቀ ገጠመኝ የሚፈጥረው በደስታ የማነሁለል አባዜ፤ አንድን ያልተጨበጠ ጉዳይ ፍፁም የሆነ ያህል እንድናምን የማድረግ ሀይል አለው፡፡
ለዚህም ነበር ጁዋን፤ ማሪያና ፓሪስ ውስጥ እንዳለችና እሱንም እንዳልረሳችው ሹክ ብሎት፤ አድራሻውን የሰጠውን ሰው አምኖ፤ ለማገናዘብ ፋታ ሳይወስድ እንኳ፤ በሀሴት ሰክሮ ደብዳቤውን መፃፍ የጀመረው፡፡
የዚያ ደብዳቤ ስጋት ግን፤ ቀን ስራውን ባግባቡ እንዳያከናውን፤ ሌትም እንቅልፉን እንዲያጣ አደረገው፡፡ ስለምን ጉዳይ ነበር ወረቀት ሙሉ የቸከቸከው? ለማሪያና ገጥግጦ ፅፎ በላከው ደብዳቤ ላይ ምን ነበር የዘበዘበው?
ጁዋን፤ በደብዳቤው ላይ የፃፈው ጉዳይ ሁሉ፣ አንድም ለትችት የሚያጋልጥ ወይም ጉዳት የሚያመጣ ይዘት እንደሌለው ያውቃል፡፡ ግን “በሌላውስ አይን ሲታይ?” ነው ጥያቄው፡፡ ሰዎቹ እንደሁ፤ የማንኛውንም ሰው ደብዳቤ ገንግነው፣ አሽትተው፤ የእያንዳንዷን መስመር ዐረፍተ ነገሮች፣ ሀረጋት፣ ያልተለመደ አይነት የቃላት አገባብ፣ የስርዓተ ነጥብ አጠቃቀም ሁሉ ብጥርጥር ብትንትን አድርገው እንደሚያነብቡና ሌላው ቀርቶ በድንገት፣ የወረቀቶች ገጽ ላይ ጠብ ያለ ነገር ቢያጋጥማቸው፤ ለዚሁ በተዘጋጀው ማሽን እገዛ በጥንቃቄ አነፍንፈው፣ በተጠና የቅብብሎሽ አሰራር፣ ከአንዱ መርማሪ ወደ ሌላው እያስተላለፉ በትጋት እንደሚመረምሩ ይታወቃል፡፡ ከየትም፤ ወዴትም የተላኩ ፖስታዎች ሁሉ፤ በጥንቃቄ የሚበረበሩበትን የግዙፉን ሳንሱር ጣቢያ ቅጥልጥል የምርመራ ሰንሰለት ማጣሪያ አልፈው፤ ከየትየለሌ ደብዳቤዎች መካከል ጥቂቶቹ ብቻ ናቸው ተቀባዮቻቸው ዘንድ ለመድረስ ጉዞአቸውን የሚቀጥሉት፡፡ ይሄ ሂደትም ባብዛኛው በወራት የሚቆጠሩ ጊዜያትን ሊወስድ ይችላል፤ ካስፈለገም ለአመታት፡፡ ይህም ማለት፤ የደብዳቤው ችግር አልባነት እስኪረጋገጥ ድረስ ባሉት የምርመራ ጊዜያት የላኪም ሆነ የተቀባይ የነፃነትና የህልውና ጉዳይ በስጋት መክረሙ ነው ማለት ነው፤ እስኪጣራ! ለዚህም ነው ጁዋን በጭንቅ የተያዘው፡፡ እሱ በላከው ደብዳቤ ጦስ ማሪያናን አጉል እንዳያረጋት ክፉኛ ሰግቶ ነበር፡፡ ከምንም በላይ ማሪያና፤ እንደምትመኘው፤መኖር ትፈልግበት በነበረው አሁን ባለችበት ስፍራ በአስተማማኝ ደህንነት ውስጥ መቆየት አለባት፡፡ ሆኖም ግን፤ የሳንሱረኞቹ ምስጢራዊ እዝ፤ በየትኛውም የአለም ክፍል ተንፈራጥጦ የተንሰራፋ ነው፡፡ አባላቱም፤ በቁጥጥር ስር ሊያውሉት የሚፈልጉትን ማንኛውንም ሰው የገባበት ገብተው፣ ጆሮውን ይዘው በማምጣት ሊቀፈድዱት ይችላሉ፡፡ ታዲያ በአንዲት ፓሪስ ውስጥ በምትገኝ መኖሪያ መንደር ውስጥ በተሸሸገችው ማሪያና አንገት፣ ሸምቀቆ ከማስገባትስ ማን ሊያስቆማቸው ይቻለዋል? የሰዎቹ ዋንኛ የመኖር ተልዕኳቸውስ ይኸው አይደል? በመንግስት ባለስልጣናቱ አይን ሞገስ የሚያገኙበትን፣ የሹማምንቱ አምሮት ይረካ ዘንድ የሚወነጨፉለትን፣ የሌላውን ጎጆ ሰላም የማራቆት ዒላማቸውን አሳክተው ወደ ሞቀ እልፍኛቸው ከተፍ! ከተፎዎች፡፡
እናም፤ እጅን አጣጥፎ መቀመጥ አይበጅም፡፡ የሆነ ነገር መደረግ አለበት! የሰዎቹን እኩይ ተግባር ለማደነቃቀፍ የሚቻለውን ሁሉ ማድረግ! ማንም ሳያውቅ አፈርና ጠጠር ውስጡ ሞጅሮ መመርመሪያ ማሽኑን ማስተጓጎል፡፡ አዎ!ጭራሽ እንዳይላወስ ሆኖ እንዲቆም መሽከርከሪያ ጥርሶቹን ማርገፍ! ብቻ፤ የሚመጣውን አደጋ ለማስቆም ማንኛውንም አቅም የሚፈቅደውን እርምጃ ሁሉ መውሰድ!
ጁዋን፤ ይህን ረቂቅ ሴራውን በውስጡ እያውጠነጠነ ነበር፤ ከሌሎች ለሳንሱረኝነት ክፍት የስራ ቦታ ከሚያመለክቱ ሰዎች ጋር ተሰልፎ የተመዘገበው፡፡ ለሞያው ብቁ የሚያደርግ ክህሎትም ሆነ ስራውን የመፈለግ ዝንባሌ ኖሮት አይደለም፤ ራሱ ጽፎ የላከውን ደብዳቤ መልሶ እጁ ለማስገባት ብቻ እንጂ፡፡ ምንም እንኳ እቅዱ፤ ለመተግበር ቀርቶ ለማሰብም የሚከብድ ያልተለመደ አይነት ውጥን ቢሆንም፡፡ ወዲያውኑ ተቀጠረ፡፡ ሰዎቹ በየቀኑ አዳዲስ የሳንሱር ሰራተኞችን ይቀጥራሉ፡፡ በአዲስ ገቢዎቹ ተቀጣሪዎች ላይም ያን ያህል ጥብቅ ቁጥጥር ሲያደርጉባቸው አይታዩም፡፡ ከሰራተኞቹ መካከል ድብቅ ፍላጎቱን የሚጎነጉን ቢገኝ ግን የሳንሱር ክፍሉ ምህረት የለውም፡፡ እናም እንዲህ ቸል ማለታቸው፤ ‹አንድ ምስኪን አዲስ ቅጥር ሳንሱረኛ፤ የሚፈልገውን ደብዳቤ ለማግኘት ቢሞክር ምን ያክል እንደሚቸገርና የፈለገውን ቢያገኝም ን‘ኳ፤ አይኑ ስር ተዝረክርከው በተከመሩት እልፍ አዕላፍ ደብዳቤዎች እድል ላይ መወሰን የሚችል ሆኖ ሳለ፤ በአንድ ወይም በሁለት ደብዳቤዎች ላይ ትኩረት ቢያደርግ ምን ሊያመጣ ይቻለዋል?› ብለው ስለሚያስቡ ይሆናል፤ አለ ጁዋን ለራሱ፡፡ ቀድሞውኑም ቢሆን እኒህን መሰል ግምቶቹን ተማምኖ ነበር፤ በሳንሱር ጣቢያው የፖስታ ቅድመ ምርመራ ቅርንጫፍ ክፍል ውስጥ ሰርጎ ለመግባት የተነሳው-በስውር ሊያከናውነው የነደፈውን ሴራ ለብቻው እያብሰለሰለ፡፡
የግዙፉ ሳንሱር ጣቢያ የውጪ ገፅታ ማራኪነት፣ በሆዱ ውስጥ ሌት ተቀን የሚከናወነውን ከፍተኛ የስራ ውጥረት የሚጠቁም ምንም ፍንጭ አይሰጥም። ጁዋን፤ ውሎ ሲያድር በጀመረው የሳንሱረኝነት ሞያ ይበልጥ እየተመሰጠ . . . ሄደ፡፡ በየእለቱ በሚያከናውነው ተግባር ምቾት እየተሰማው መጣ፡፡
አቅሙ በፈቀደው መጠን እየተፍጨረጨረ፣ ለማሪያና የላከውን ደብዳቤ እጁ ለማስገባት የሚያደርገውን ጥረት ያላንዳች መሳቀቅ በሰላማዊ ሁኔታ ገፋበት፡፡ በተቀጠረ በወሩ የፍንዳታ አደጋ የሚያስከትሉ ነገሮችን ይዘዋል ተብለው የሚታሰቡ እሽጎች በረቀቀ መንገድ ወደሚመረመሩበት ‹ኬ ክፍል› ባጋጣሚ ተመድቦ ሲሄድ እንኳ፤ ምንም ታህል ፍርሀትና መጨነቅ ሳይነበብበት ተረጋግቶ ነበር የታዘዘውን ሁሉ ያቀለጣጠፈው፡፡
በርግጥ፤ እሱ ‹ኬ ክፍል› በተመደበ ገና በሦስተኛው ቀን ላይ፣ በምርመራ ላይ ከነበረ የታሸገ ፖስታ በተከሰተ ፍንዳታ፤አንድ እሱን መሰል አዲስ ቅጥር ሳንሱረኛ ተቃጥሎ፣ ቀኝ እጁ እርር ብሎ ተንጨርጭሮ ከጥቅም ውጪ ሆኗል፡፡ ምንም እንኳ የ ‹ኬ ክፍል› የሳንሱር ምርመራ ኃላፊው፤ አደጋው የተፈጠረው በሰራተኛው ገደብ የለሽ ንዝህላልነት መሆኑን ማረጋገጫ ቢሰጡም፡፡ አደጋውን ተከትሎ ጁዋንና ሌሎቹ ሰራተኞች ለዚህ መሰሉ ጉዳት የመጋለጥ ስጋት  ወደሌለበት ክፍል እንዲዛወሩ ተፈቀደላቸው፡፡ የእለቱ ስራ ሰአት ከመጠናቀቁ በፊት ታዲያ፤ከሰራተኞቹ መሀል አንዱ፤በእንዲህ ያለ ክፉ አደጋ ባንዣበበበት የስራ ቦታ ለሚያከናውኑት ተግባር ተጨማሪ የደመወዝ ክፍያ ሊደረግላቸው እንደሚገባ አሰሪዎቻቸውን የሚያፋጥጥ ሀሳብ ጠንስሶ፣ ሰራተኞቹን በህቡእ ለአመፅ አስተባበረ። ጁዋን ግን በአመፁ እንቅስቃሴ አልተባበረም። ይልቅስ ጉዳዩን ደጋግሞ ካሰበበት በኋላ፣ ወደ ላይ አለቆቹ ሄዶ፣ የአመፁን ቆስቋሽ ሰው ማንነት በምስጢር ሪፖርት አደረገ፡፡ ለዚህም መሰሉን አሳልፎ የመስጠት የአጋላጭነት ‹ምስጉን› ተግባሩ ውዳሴና እድገት ተቸረው፡፡ የአለቃውን ቢሮ በር ከፍቶ እየወጣ ሳለም፤… ‹መቸም፤ገና ለገና እርሜን፤ ዛሬ ብቻ፤ ይኼን የማጋለጥ ነገር ስለፈፀምኩ፤ የአቃጣሪነት ባህሪ አይጠናወተኝም› ብሎ ራሱን በከንቱ አጽናና፡፡ ከዚህ ምስጋናን ካተረፈለት ድርጊቱ በኋላም የደብዳቤዎች መርዛምነት ወደሚመረመርበት ‹ጄ ክፍል› ሲዛወር፣ ከናወነው መልካም ተግባሩ የዕድገት መሰላል በመወጣጣት ላይ መሆኑ ጠልቆ ተሰማው፡፡
ጠንክሮ በመስራትም በፍጥነት ወደ ሌላኛው ረቀቅ ያለ የምርመራ ተግባር ወደሚከናወንበት፣ የእያንዳንዱን ደብዳቤ ይዘት አጣርቶ ማንበብ ወደሚችልበት ‹ኢ ክፍል› ተዛወረ፡፡ በዚህ ክፍል ውስጥም ራሱ ጽፎ የላከውን ደብዳቤ እንደሚያገኘው እርግጠኛ ሆነ፡፡ ‹ይኼ ጊዜ ደርሶ እዚህ ለመገኘት ስል ነበር እስከዛሬ ፍዳ የበላሁባቸውን ክፍሎች ሁሉ ማለፍ የነበረብኝ› አለ፡፡
ያም ሆኖ ግን፤ ፋታ በማይሰጠው ሳንሱረኝነቱ ተጠምዶ፤ ዋናውን ሊያሳካው ያለመውን እቅዱን እስኪዘነጋ ደረሰ፡፡ ቀን በቀን እየታፈሱ የሚቀርቡለትን ደብዳቤዎች፤ ከጧት እስከ ማታ ወንበሩ ላይ ተሰፍቶ፤ አይኖቹን በያንዳንዱ መስመሮች ላይ አጨንቁሮ እያነበበ፤አንቀፆቻቸውን በቀይ እስኪርቢቶ ሲያሰምር መዋልና ወደ ሳንሱር ቅርጫቱ ማጎር የእለት ተዕለት ኑሮው ሆነ፡፡ በእነዚያ አሰቃቂ ቀናት ውስጥም፤ቅርጫቱን ካጨቀባቸው የደብዳቤ ልውውጦች፤የሰዎችን ምስጢራዊ የቋንቋ አጠቃቀም የመረዳትና የመታዘብ እድል አግኝቷል። እንደ ‹‹አየሩ ከብዷል›› ወይም ‹‹የትራፊኩ መጨናነቅ አያፈናፍንም››  አይነት ቀላል የሚመስሉ በደብዳቤ ጽሁፎች ውስጥ የተመሰጉ ወሽመጥ ሀረጋት ፤መንግስትን ለመገልበጥ የሚሰነዘሩ ‹‹ሽብር ቀስቃሽ!›› መልዕክቶች ስለመሆናቸው በሳንሱረኝነት ለሰላ ንቁ አእምሮው ፍንትው ብሎ ይገለጥለት ነበር።
በቃ! በልጓም አልባ ጉጉቱ የጦዘ ታታሪነት ውሎ አዳሩ፣ በአናት ባናቱ ሹመት ይደራርብለት ጀመር። እንግዲህ ይኼ ሁሉ ሲሆን እሱን ምን ይሰማው እንደነበር ለማወቅ አለመቻላችን ይቆጫል። እናም በዚህ ከነፋስ የፈጠነ በረራው፤ የተወሰኑ ደብዳቤዎችን ብቻ ተረክቦ ወደሚመረምርበት ‹ቢ ክፍል› ደረሰ። ሌሎቹን የምርመራ ሂደቶች አልፈው ከእጁ የደረሱትን አንድ እፍኝ ያህል ጥቂት ደብዳቤዎች እጅግ በጥንቃቄ፤ ከሙሉ የመልዕክታቸው ይዘት ትርጉም ጀምሮ በየአንቀፆቻቸውና ዐረፍተ ነገራቱ፣ ሀረጋቱ፣ ቃላቱና ፊደላቱ መካከል እየተመላለሰ ደግሞ ደጋግሞ ማንበቡን ቀጠለ። አጉሊ መነፅሩንም ባግባቡ መጠቀም ነበረበት። በአይን የማይታዩ የማይክሮ ፕሪንት ረቂቅ ምልክቶችን አጣርቶ ለማሳለፍ የሚያስችል ኤሌክትሮኒክ ማይክሮስኮፕም በጠረጴዛው ላይ ቀርቦለታል፡፡ ጠረናቸውንም ጭምር  በጥንቃቄ ሲያነፈንፍ ውሎ ራስ ምታት እየጠለዘው ነበር ቤቱ የሚደርሰው። እጁን በሙቅ ውኃና ሳሙና ሙልጭ አድርጎ ከታጠበ በኋላ፣ አልጋው ላይ ጋደም ብሎ ፍራፍሬዎችን እየገመጠ፣ ቀኑን ሙሉ ባከናወነው የላቀ ተግባሩ እርካታን ተመልቶ በዚያው ያሸልባል። እናቱ ብቻ ነች በእሱ ነገር በጭንቀት ተወጥራ የምትብሰለሰለው፡፡
እሷም ብትሆን ግን ከገባበት ማጥ ጎትታ የማውጣት አቅም የላትም፡፡ እውነቷን ይሁን  ባይታወቅም፤ ሁልጊዜ ከስራ ሲገባ፤ ‹‹ሎላ ደውላ ነበር፤ ከጓደኞቿ ጋ መናፈሻው ስፍራ ናት፤ ይመጣል ብለው እየጠበቁህ ነው…›› ትለዋለች። ወይም ደግሞ ቀይ ወይን ጠጅ ገዝታ ከራት ማዕዱ ጋ ጠረጴዛ ላይ ታቀርብለታለች፡፡
ጁዋን ግን ንክች አያደርጋትም፡፡ አንዲትም የግዴለሽነት ድርጊት ብትሆን ከጥንቃቄ ጉድለት ለሚመጣ ውድቀት ትዳርጋለቻ! ከዚያም በላይ ደግሞ አንድ ሳንሱረኛ ማንንም ቢሆን ማመን አይጠበቅበትም፡፡ እናቱስ ብትሆን፡፡ የቀረበለትን ግብዣ ዝም ብሎ መቀበል የለበትም። የተቀነባበረ ሴራ ቢሆንስ፡፡ ህ! ዙሪያ ገባውን ተጠራጣሪ፤ጥላውንም የማያምን መሆን ይገባዋል፡፡ የተሰማራበት የሞያ መስክ ራስን የመካድ ያህል መስዋዕትነት የሚጠይቅ፤ ግን ደግሞ በእድገት የሚመነጥቅ መሆኑን አሳምሮ ያውቀዋል፡፡
ተመርምረው በወደቁ ደብዳቤዎች ጢም ብሎ የሞላው የጁዋን ቢሮ የሳንሱር ቅርጫት፤በመላ የሳንሱር መስሪያ ቤቱ ካሉት ቅርጫቶች ሁሉ የተጨበጨበለት ሆኖ ነበር፡፡ ራሱን በራሱ ‹‹አንተ ታላቅ ሰው እንኳን ደስ አለህ!›› ለማለት የቃጣው ግን፤ በመጨረሻ እሱ ራሱ ጽፎ የላከው ደብዳቤ እጁ ሲገባ ነው፡፡ እናም ልክ ሌሎቹን ደብዳቤዎች ሲመረምር እንደሰነበተው፤ በእሱው በራሱው ጽሑፍ ላይም፤ ያለ ምንም አድልዎና ርህራሄ፤ ያንኑ ጥንቃቄ የተመላበትን አይነት ምርመራ አለማድረግ አልቻለም፡፡ ቀጣሪዎቹም እንዲሁ፤ በማግስቱ፤ ልክ እንደ ሌሎቹ እልፍ አእላፍ ደብዳቤዎች ሁሉ፤ በእሱ ደብዳቤ ላይም፤ ያለ ምንም አድልዎና ርህራሄ፤ ያንኑ በቁጥጥር ስር የማዋል ተግባራቸውን አለማድረግ አልቻሉም፡፡ እነሆ በተሰማራበት የሳንሱረኝነት ሞያው ፍቅር የወደቀ ምርኮኛም ሆነ፡፡ ቅርጫት ሙሉ…
(‘’The Censors’’ combines the real and the fantastic, a Latin American style called ‘’magical realism.’’)

Published in ልብ-ወለድ

         ከጥቂት ወራት በፊት ነው፡፡ እኔና የስራ ባልደረባዬ ምሳ በልተን በካዛንቺስ ኢንተርኮንትኔንታል ሆቴል በኩል ወደ ቢሮአችን እየሄድን ነበር - በእግራችን፡፡ ሆቴሉ ፊት ለፊት አንዲት አነስተኛ የሸቀጥ ኪዮስክ (ሚኒ ሱፐር ማርኬት) ነገር ተከፍታ አየንና ጐራ አልን፡፡ አንዲት ወጣት ቁጭ ብላለች - ብቻዋን። ቤቷን ከቃኘን በኋላ ባዶ እጃችንን ላለመውጣት የታሸገ ቆሎ አነሳን - ለመግዛት፡፡ ወጣቷ “ሳንዱችና እርጐም አለ” አለችን - ፈገግ ብላ፡፡ ከባልደረባዬ ጋር ተያየንና “እርጐውን እንሞክረው” ተባባልን፡፡ እርጐው መጣልን፡፡
ሁለታችንም ወደድነው፡፡ በተለይ እኔ በእርጐው ተደነቅሁ፡፡ ምክንያቱም ከብዙ ሱፐር ማርኬቶች እርጐ ስገዛ በጣም ነው የሚኮመጥጠኝ። ይሄኛው ግን ጣፋጭ ነው፡፡ በእርጐ ሰበብ ወደ ሚኒ ሱፐር ማርኬቷ መመላለስ ጀመርን፡፡ የቢፍና ቺዝ ሳንዱቹንም ለመድነው፡፡ እንደ እርጐው ንፁህና ጣፋጭ ነው፡፡ ሆድን ያዝ ያደርጋል፡፡ ኪስ አይጐዳም፡፡ አሁን በአብዛኞቹ የስራ ቀናት ምሳ የምንበላው በዚህች ቤት ነው፡፡ ለብዙዎቹ ባልደረቦቻችን ጠቁመናቸውም ተጠቃሚ ሆነዋል። መጀመሪያ ስንጐበኛት ኦና የነበረችው ያቺ ሚኒ ሱፐርማርኬት ዛሬ በእጅጉ ተለውጣለች፡፡ ቤቷ “ፀጋ ወተት” ትባላለች፡፡
ፀጋ ወተት ከጎኑ ካለው ቀበሌ በተከራያት በጣም ጠባብ ክፍል ውስጥ የወተት ተዋጽኦና የተለያዩ ዓይነት ሳንዱቾች  ያቀርባል፡፡ የፀጋ ወተት መስራችና ኃላፊ፣ ወ/ሮ ሰብለወንጌል ዘውዱ፣ ከጧት እስከ ማታ እንግዶቿን ያለዕረፍት ስታስተናግድ ስለምትውል አንዳንድ ጊዜ ለሚያናግሯት ሁሉ መመለስ እንደሚያቅታት ትናገራለች፡፡ ለመሆኑ ሰብለ ምን ብታቀርብ ነው ገበያው እንዲህ የደራላት?
ወ/ሮ ሰብለ፣ በአንድ ማይክሮዌቭና ለብቻዋ የቺዝ፣ የጥጃ፣ የዶሮ፣ የሞርቶዴላ (አሳማ) ሥጋና የቱና ሳንዱዊቾች በማዮኔዝ እያሰናዳች ከእርጎ ጋር ማቅረብ ከጀመረች  ስምንት ወር ሞልቷታል። ብዙ ሰዎች የተለያዩ አማራጮች በማግኘታቸው ደስተኛ እንደሆኑ የምትናገረው ወ/ሮ ሰብለ፤ አንዳንድ ደንበኞች እርጎና ሳንድዊች፣ ሌሎች ደግሞ እንደፍላጎታቸው ሳንድዊች ወይም እርጎ ብቻ እንደሚያዙ ገልጻለች፡፡
ይኼኔ፣ “ለካስ ሰው፣ አማራጭ ካገኘ በደስታ ይቀበላል!” በማለት፣ በሚጥሚጣና በማር የምታቀርበውን እርጎ ብዙም ባልተለመደ ሁኔታ እንደየሰው ፍላጐት በስትሮበሪና በቸኮሌት  ማቅረብ ጀመረች፡፡ የደንበኞቿ ቁጥርም አየጨመረ መጣ፡፡ ገበያው ደራ፣ ገቢዋ አደገ፡፡
ሰብለ ሥራ ስትጀምር፣ ሳንድዊች ሰሪዋ፣ እርጎ አቀባይዋ፣ ሌሎች ሸቀጦች ሻጭዋ፣ ገንዘብ ተቀባይዋ፣ ዕቃ ሰብሳቢዋ እሷው ብቻ ነበረች። ዛሬ ሁለት ማይክሮዌቮች ተጨምረው፣ ዘጠኝ ሰራተኞች ተቀጥረው በሁለት ፈረቃ 24 ሰዓት እየሰሩ ነው። አሁን የእሷ ሥራ በአብዛኛው ገንዘብ መቀበል፣ የጎደሉ ነገሮችን እያዩ ማሟላት፣ … በአጠቃላይ ድርጅቱን በበላይነት መምራት ነው፡፡
የካዛንቺሷ በቅርቡ ሥራ ትጀምር እንጂ፤ ፀጋ ወተት ከተቋቋመ አምስት ዓመት ሲሆነው ድርጅቱን በበላይነት የሚመሩት የወ/ሮ ሰብለወንጌል አክስት ወ/ሮ ሂሩት ዮሐንስ ናቸው። የወተት ላሞች ስላላቸው ለምን እንደቺዝ ያሉ የወተት ተዋፅኦዎችን እያዘጋጀን አናቀርብም በሚል ወተት፣ እርጎ፣ አይብ፣ … ማቅረብ ጀመሩ። የካዛንቺሱ ዓይነት የወተት ተዋጽኦ መሸጫ በ22 አካባቢ ከፍተው ነበረ። ገበያ ስላልነበረው ዘጉት። በካዛንቺሱ መኖሪያ ቤታቸው አካባቢ ወተት፣ እርጎ፣ አይብ፣ … ሲሸጡ ከቆዩ በኋላ ወተት ማቀናበሪያ (ፓስቸራይዝድ ማድረጊያ) መሳሪያ ገዝተው ይኸኛውን ኪዮስክ እንደከፈቱ ሰብለ ገልፃለች፡፡
ለመሆኑ የደንበኞች አስተያየት ምንድን ነው? ስል ጠየቅዟት - ሰብለን፡፡
ሆድ የማይጎረብጥ፣ በቀላሉ የሚፈጭ ለጤና የተስማማ ምግብ ስለሆነ ደንበኞች በጣም ወደውታል፤ በጣም ነው የሚያደንቁት፡፡ ሦስት አራት ጊዜ የሚመጣ ሰው አለ፡፡ እዚህ ቤት በቀን ቁርስ፣ ምሳ፣ መክሰስና እራት የሚበላ ሰው አለ። አሁን ገበያ በደንብ ስላለው፣  በሁለት ፈረቃ 24 ሰዓት ነው የምንሰራው፡፡ የሌሊት ተረኞች ሲገቡ፣ ቀን የዋሉት ይወጣሉ፡፡ ጧት ደግሞ የቀኖቹ ሲገቡ፣ ያደሩት ይወጣሉ፡፡ እንደዚህ ነው የምንሰራው፡፡
በስንት ብር ካፒታል ጀመርሽ?
በ50 ሺ ብር ነው
አሁን ገቢው እንዴት ነው?
በጣም ጥሩ ነው፡፡ ዋጋው ርካሽ ስለሆነ ብዙ ትርፍ የለውም እንጂ ከወጪ ቀሪ በቀን እስከ 7 ሺ ብር ይገኛል፡፡
ዋጋችሁ እንዴት ነው?
በጣም ርካሽ ነው፡፡ ይኼው ዓመት ሊሞላን ነው፤ ዋጋ እንኳን አልጨመርንም፡፡ ሰው ጥራት ያለው ነገር በርካሽ ዋጋ ስለሚፈልግ በጀመርንበት ነው እየሸጥን ያለው፡፡ እርጎ በሚጥሚጣ 8 ብር፣ በማር 10 ብር፣ በስትሮበሪና በቸኮላት 15 ብር ነው፡፡ ይኼ በፊትም የነበረ ዋጋ ነው፡፡
ለመሆኑ ምን ዓይነት ሰዎች ናቸው እዚህ የሚጠቀሙት?
ልጆቻቸውን ይዘው የሚመጡ ቤተሰቦች አሉ፡፡ ወጣት ወንዶችና ሴቶች፣ ጎልማሶች፣  ወንደላጤዎች፣ የቢሮ ሴቶችም ወጣ ብለው መጥተው ምሳቸውን በልተው ይመለሳሉ፡፡ አረጋውያን ወንዶችና ሴቶችም እርጐአቸውን ጠጥተው ይሄዳሉ፡፡ “እስካሁን የት ነበርሽ?” የሚሉኝ ብዙ ናቸው፡፡
ቤቷ ጠባብ ተጠቃሚው ብዙ ነው፡፡ እንዴት ነው የሚስተናገዱት?
ቤቷ ጠባብ ከመሆኗ የተነሳ ከሰራተኛ ጋር በጣት ከሚቆጠር ጥቂት ሰው በስተቀር ማስተናገድ አትችልም፡፡ ውጭ በረንዳ ላይ እንዳይቀመጡ ደግሞ ተከልክሏል፡፡ ስለዚህ ጊዜያዊ መፍትሔ ብዬ ቁጥር አዘጋጅቻለሁ፡፡ አንድ ሰው እርጎ ሲይዝ ወዲያው ይሰጠዋል፡፡ ሳንድዊች ሲያዝ ደግሞ ቅደም ተከተሉ ተሳስቶ ቅሬታ እንዳይፈጠርና ሁሉም እንደአመጣጡ እንዲስተናገድ፣ የተራውን ቁጥር ጽፌ ቲኬት እሰጠዋለሁ፡፡ ተራው እስኪደርስ ውጭ ሲጠብቅ ይቆይና ቁጥሩ ሲጠራ ተቀብሎ፣ በቁሙ በልቶ የተጠቀመበትን ፕላስቲክ ቆሻሻ መጣያ ውስጥ ወርውሮ ይሄዳል፡፡ መኪና ውስጥ ሆነው አዘው የሚበሉና አስጠቅልለው ወደ ቤት የሚወስዱም (ቴክ አዌይ) አሉ፡፡ ሌሊት ጭምር አራት አምስት ጊዜ የሚመጡ አሉ፡፡ ይህ የሚያመለክተው  በጣም እንደወደዱት ነው፡፡ ዝግጅታችንን ስለወደዱልን በጣም እናመሰግናለን። ወደፊትም የሰውን ፍላጎት እያየን ጥራት ያለው ነገር ማቅረባችንን እንቀጥላለን፡፡
ከወተት ተዋጽኦ ውጭ በመደርደሪያዎቹ ላይ ብዙ የሱፐርማርኬት ሸቀጦች ይታያሉ፡፡ እነዚህ ሁሉ የእናንተ ምርቶች ናቸው?
አይደሉም፡፡ እኔ እዚህ ውስጥ የምሰራው ብቻዬን አይደለም፡፡ አብረውኝ የሚሰሩ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ አንድ ቀን አንዲት ልጅ ሙልሙል ዳቦ ይዛ መጣችና “እኔ እንደዚህ ዓይነት ነገር እሰራለሁ፡፡ ይህን ለናሙና ቅመሺውና ጥሩ ከሆነ እዚህ ላስቀምጥና ይሞከር” አለች፡፡ አንድ ሰው ሳንድዊች ያዝና ወረፋ ሲጠብቅ፤ ይርበዋል ወይም የሚቸኩል፣… ሊሆን ይችላል፤ ይኼኔ ያንን ሙልሙል በእርጐ በልቶ ሊሄድ ይችላል፤ ብዬ አሰብኩና ተቀበልኳት፡፡ እውነትም በጣም እየተወደደ ነው፡፡ ያቺም ልጅ ተጠቀመች፣ እኔም ተጠቀምኩ፡፡ አብሮ ሊሄድ የሚችል ነገር እዚህ ማቅረብ ለሰውም ጠቀሜታ አለው፡፡
ሙልሙል ብቻ አይደለም እኔ ጋ እየተሸጠ ያለው፤ ብዙ ነገር አለ፡፡ ማር፣ ማዮኔዝ፣ ስትሮበሪ፣ ቸኮላት፣ ..የሚያቀርቡልኝ ልጆች አሉ፡፡ ሽሮ በርበሬ፣ ኩኪሶች፣ ቋንጣ፣ ቆሎ፣ቺፕስ፣ የለውዝ ቅቤ ... የሚያቀርቡ ሰዎች አሉ፡፡ እኔ ጋ ያለውን አይተው፣ ከእኔ ንግድ ጋር የሚሄድ ነገር ሲያመጡ፣ እውነትም ይሸጣል፡፡ ሁለታችንም እንጠቀማለን። እንግዲህ እኔ የምሰራው ለብቻዬ ሳይሆን ለሌሎችም የሥራ ዕድል ፈጠርኩ ማለት ነው፡፡
ከአንቺ ምርት ውጭ ያሉት ነገሮች ምንድናቸው?    
ዓሣ፣ የፈረንጅና የአበሻ ዶሮ፣ እንቁላል፣ .. የእኔ ምርቶች ደግሞ ቅቤ፣ የፀጉርና የገበታ፣ አይብ አለ፡፡ አንድ ሰው በዓመት በዓል ጊዜ ወደ እኔ ሱቅ ቢመጣ የተለያዩ ነገሮች ፍለጋ በየቦታው ሳይንከራተት ከአንድ ቦታ ያገኛል፡፡ ይህም ድካምና ወጪ ይቀንስለታል፡፡ እኛ ቤት ያለው ነገር ርካሽና አቅምን ያገናዘበ ነው፡፡ ለምሳሌ የእኛ የፀጉር ቅቤ፣ ንፁህና ጥራቱ የተጠበቀ ስለሆነ ለምግብ ሊሆን ይችላል፡፡ አቅም የሌለው ሰው አንድ ኪሎ በ150 ብር መግዛት ካልቻለ፣ የፀጉሩን 200 ግራም ቅቤ በ30 ብር ገዝቶ አንጥሮ መጠቀም ይችላል፡፡
የእናንተ ዕቃዎች ዋጋቸው ምን ያህል ነው?
የምግብ ቅቤ አንድ ኪሎ 150 ብር ነው፡፡ አይብ ግማሽ ኪሎ ከ 20 ብር ጀምሮ አለ፡፡ የአበሻ ሙሉ ዶሮ 80 ብር፣ የተገነጠለ 90 ብር፣ የፈረንጅ እንደኪሎው 115 ብር፣ ዕንቁላል ደግሞ 2.50 ብር ይሸጣል፡፡
ይህን ሥራ ከጀመርሽ በኋላ ያጋጠመሽ ችግር አለ?
ሥራው በጣም ጥሩ ነው፡፡ ሰውም ለምዶታል ወዶታል፡፡ ነገር ግን ከፍተኛ የመስሪያ ቦታ ጥበት አለብኝ፡፡ ቦታው በቅርቡ ለልማት ይፈርሳል ስለተባለ ቀበሌው ሌላ ሰፋ ያለ ቤት እንዲሰጠኝ አልጠየቅሁም። ሌላው ችግር መብራት ነው። ደንበኞቼን ቶሎ ቶሎ ለማስተናገድ ሁለት ተጨማሪ ማይክሮዌቭ ብገዛም፣ መብራት በየጊዜው ስለሚጠፋና ስለሚቆራረጥ በስራዬ ላይ እንቅፋት ሆኖብኛል፡፡ ለመብራት ኃይል ሳመለክት “ይስተካከላል” ከማለት በስተቀር ሲያስተካክሉ አላየሁም፡፡
የወደፊት እቅድሽ ምንድነው?
ይህን ሥራ ሰው በጣም ስለወደደልኝ ከዚህ ይበልጥ ማስፋፋት ነው እቅዴ፡፡ እኔ ወጣት ነኝ። መንግሥት፣ ደንበኞቼን ወረፋ ሳይጠብቁና ሳይጨናነቁ የማስተናግድበት ሰፋ ያለ ቦታ ቢሰጠኝ ከዚህ በላይ በመስራት ደንበኞቼን የማስደሰት እቅድ አለኝ፡፡  
በሚኒ ሱፐር ማርኬት ቁርስ ሲመገቡ ያገኘኋቸው ወ/ሮ አልጋነሽ የ69 ዓመት የዕድሜ ባለፀጋ ናቸው፡፡ ስለምግቡና ስለቤቱ አስተያታቸውን ጠየቅኋቸው፡-  
ምግቡ በጣም ጥሩ ነው፡፡ ልጅቱን በጣም ነው የማደንቃት፤ ጎበዝ ናት፡፡ ሠራተኞቹም ጎበዞች ናቸው፣ እንግዳ በደንብ ያስተናግዳሉ፡፡ እሷ በተለይ በፈገግታ ነው የምታስተናግደው፤ ምንም እንከን የማይገኝባት ሴት ናት፡፡ በርቺ ነው የምለው፡፡  
ወ/ሮ ሰብለ ፀጉር መስራት በጣም ያስደስታታል። በ1993 ዓ.ም 12ኛ ክፍል እንደጨረሰች የፀጉር ሥራ ሙያ ካልተማርኩ ብላ ማሰልጠኛ ት/ቤት ገብታ ከ10 ወር በኋላ ተመረቀች፡፡ ጥሩ ችሎታ ስለነበራት ት/ቤቱ አስቀርቷት እዚያው ማሰልጠን ጀመረች። ከዚያም ለ10 ወራት ካስተማረች በኋላ ሁል ጊዜ አንድ አይነት ማስተማር ሰለቻትና ተወችው፡፡
ከማሰልጠኛው እንደለቀቀች የኬንያውያን ፀጉር ቤት ተቀጥራ መስራት ጀመረች፡፡ የፀጉር ሥራ ብዙ ጊዜ መቆም ስለሚጠይቅ እግሯን ያማት ጀመር፡፡ ኬንያውያኑም ወደ አገራቸው ሲሄዱ ማቋረጥ አለ፡፡ ስለዚህ የፀጉር ስራውን ተወችው፡፡ ንግድም ሞክራ ነበር፡፡ የልብስ ሱቅ ከፍታ ስላልሆነላት ተወችው። በመጨረሻ ከቤተሰብ ጋር እየሰራሁ ላግዛቸው በማለት 22 አካባቢ በነበረው ፀጋ ወተት ሰራች። ያ ሲዘጋ የካዛንችሱን ፀጋ ወተት ከፍታ መስራት ጀመረች፡፡

Page 4 of 13